ar
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

إظهار المزيد
2 639
المشتركون
-224 ساعات
+37 أيام
+5630 أيام
أرشيف المشاركات
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_29 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ዕለት ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ #ሐዋርያ_አርስጦስ አረፈ፣ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #አባ_አካክዮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያው_አርስጦስ ሚያዝያ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ዕለት ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ ሐዋርያ አርስጦስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከሐዋርያት ጋራ በጽርሐ ጽዮን የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከተቀበለ በኋላ በሀገሩ ሁሉ ቋንቋ ተናገረ። ሐዋርያትንም እያገለገለ ከእሳቸው ጋራ ሲሰብክ ብዙ ጊዜ መከራ ተቀበለ። ከዚያም በኋላ ሐዋርያት መርጠው ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ሾሙት። በዚችም አገልግሎት ጥቂት ቆይቶ ብናጥስ በሚባል አገር ላይ ሁለተኛ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በውስጥዋ አስተምሮ አንድነትንና ሦስትነትን በማሳወቅ የሰዎቿን ልቡና ብሩህ አደረገ። የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሶ አብያተ ክርስቲያንን ሠራ በክብር ባለቤት በጌታችንም ስም አጸናቸው። ታላላቅ አስደናቂ ተአምራትን በማድረግ መራራ የሆኑ ውኃዎችን ለውጦ ጣፋጮች አደረጋቸው የደረቁ እንጨቶችንም እንዲያለመልሙና እንዲአፈሩ አደረጋቸው። በደዌ የተጨነቁ ብዙ በሽተኞችንም አዳነ ወደ በጎ እርጅና ደርሶ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ። እነሆ ሐዋርያው ጳውሎስ በመልእክቱ አስታውሶታል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_አካክዮስ በዚህችም ቀን ንጹሕ ደግ ቅን የሆነ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አባ አካክዮስ አረፈ። ይህንንም ቅዱስ ከሀድያን ብዙ ቀኖች አሠቃዩት እግዚአብሔርም በእጆቹ ብዙ ተአምራትን አደረገ ከዚህም በኋላ በፍቅር አንድነት አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_28 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ስምንት በዚች ቀን በኮራሳት ተራራ በገድል ተጠምዶ የሚኖር #ቅዱስ_ሜልዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ መቅሱር ከሚባል አገር #ቅዱስ_ብስጣውሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሜልዮስ_ዘደብረ_ኮራሳን ሚያዝያ ሃያ ስምንት በዚች ቀን በኮራሳት ተራራ በገድል ተጠምዶ የሚኖር ቅዱስ ሜልዮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም አባት ኮራሳት በሚባል አገር በተራራ ባሉ ዋሻዎች ከሁለት አርድእቱ ጋራ ይኖር ነበር። የኮራሳት ንጉሥ ሁለቱ ልጆቹ ወደዚያ ወጡ ከእርሳቸውም ጋራ አገልጋዮች አሉ አራዊትን አጥምደው በፍላፃዎች ይገሉ ዘንድ መረባቸውን ተክለው አርባ ምዕራፍ ያህል ሔዱ። መረቡን በጠቀለሉት ጊዜ ይህን ቅዱስ አባት ማቅ ለብሶ ጠጉሩም የረዘመ ሁኖ አገኙት። የንጉሥ ልጆችም በአዩት ጊዜ ፈሩ አንተ ሰው ነህን ወይም መንፈስ ብለው ጠየቁት እርሱም በዚህ ተራራ ውስጥ የምኖር ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሰው ነኝ ብሎ መለሰላቸው። እነርሱም ከእሳትና ከፀሐይ በቀር አምላክ የለም እንዳንገድልህ ሠዋላቸው አሉት። እርሱም እሳትና ፀሐይ የተፈጠሩ ናቸው እናንተም ተሳስታችኋል ፍጥረቶችን በፈጠረ በዕውነተኛ አምላክ ታምኑ ዘንድ እኔ እለምናችኋለሁ ብሎ መለሰላቸው። በዚያን ጊዜ ይህን አባት ሁለቱን አርድእትም ይዘው ጽኑ ሥቃይ አሠቃዩአቸው በዚህ ወር በዐሥራ ሦስት የሁለቱን አርድእት ራሳቸውን ቆረጡአቸው የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ። አረጋዊ ቅዱስ ሜልዮስን ግን ዐሥራ አምስት ቀን ያህል ሲአሠቃዩት ኖሩ ከዚህ በኋላ በመካከላቸው አቆሙት አንዱ በፊት አንዱ በኋላ ሁነው በፍላፃ ይነድፉት ጀመር። እርሱም በእናንተ ላይ ክፉ ያልሠራውን ለመግደል ሁለታችሁ ስለተስማማችሁ እንዲሁ እንደሥራችሁ በፍላፃችሁ ነገ ትሞታላችሁ አላቸው። ሰምተውም አልፈሩም ነፍሱን እስከሚአሳልፍና ምስክርም ሆኖ የሰማዕትነት አክሊልን እስከሚቀበል ነደፉት እንጂ። በማግሥቱም እንደልማዳቸው ለአደን ወጡ የዱር አህያም አገኙ ተከትለውም ቀስታቸውን አስፈነጠሩ እግዚአብሔርም ፍላፃቸውን ወደልባቸው መለስ ቅዱስ ሜልዮስም እንደተናገረባቸው ሞቱ። በዚህ ቅዱስም እጅ ጌታችን ተአምራትን ገለጠ በአንዲት ዕለትም አልፎ ሲሔድ በመንገድ ላይ የሞተ ሰው አገኘ የአገር ሰዎች ግን አንዱን መነኰስ አንተ ነህ የገደልከው ብለው ያዙት። ቅዱስ ሜልዮስም ጸለየ የሞተውንም በውኑ የገደለህ ይህ መነኵሴ ነውን አለው ያን ጊዜ የሞተው ተነሥቶ እርሱስ አልገደለኝም ነገር ግን ብዙ ገንዘቤን ከአንድ ቄስ ዘንድ አደራ አስጠበቅሁ ስለዚህ ገደለኝ ከዚህም ጣለኝ አለ ደግሞ እንዲህ ብሎ ለመነው ዕገሌ ወደሚባል ወደዚያ ቄስ ሒደህ ገንዘቤን ከርሱ ተቀብለህ ለልጆቼ ስጥ ቅዱስ ሜልዮስም እስከ ትንሣኤ ቀን በሰላም አርፈህ ተኛ እኔ ገንዘብ አከፋፋይ ዳኛ አይደለሁም አለው ያንጊዜም ተኛ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ብስጣውሮስ በዚህችም ቀን መቅሱር ከሚባል አገር ቅዱስ ብስጣውሮስ በሰማዕትነት አረፈ። የዚህም ቅዱስ አባቱ ጻድቅ ሰው ነው እናቱን ግን ሰይጣን አስቷት ወደ እስልምና ገባች እርሱም ፈሪሀ እግዚአብሔርን እየተማረ እስከሚጐለምስ አደገ አካለ መጠንም አድርሶ ሚስት አገባ ከርሷም ልጆችን ወለደ። ብዙ ዘመናትም በአለፉ ጊዜ አንገተ ደንዳና በቀለኛ ሰው በእርሱ ላይ ተነሥቶበት ወደ እስላሞች መኳንንት ሒዶ ሰው ወደ እኛ ሕግ ቢገባ ልጆቹም ሃይማኖቱን ይከተላሉ ይህ ብስጣውሮስ ግን ከሕጋችን የተለየ ነው ብሎ ነገር ሠራበት። የእስላሞች ዳኞችም በሰሙ ጊዜ መልዕክተኞች ልከው ወደርሳቸው ወደ ሸንጎ አቀረቡት ስለ ሃይማኖቱም ጠየቁት ክርስቲያን እንደሆነ ያለ ፍርሀት ክርስቲያን ነኝ ብሎ ታመነ። ዳኛው ግን ይሸነግለው ዘንድ በፍቅር ይናገረው ጀመረ ከከበረችና ከቀናች ሃይማኖቱ ይመልሰው ዘንድ ብዙ ስጦታዎችን እንደሚሰጠው ቃል ገባለት ቅዱሱ ግን ከቶ አልተመለሰም ወደ ስጦታውም ከቶ ልቡ አላዘነበለም። ከዚህ በኋላ ወደ ግዞት ቤት ወስደው በእግረሙቅ እንዲአሥሩት በአንገቱም የተበሳ ታላቅ ግንድ አሥረው በግንባሩ ደፍተው በኲስ ላይ እንዲጥሉት መኰንኑ አዘዘ። እንዲሁም አደረጉበት እስከ ሦስት ቀን በእሥር ቤትም ሳለ ፀዐዳ ርግብ መጥቶ ጋረደው ስለዚህም የእሥር ቤቱ ጠባቂ ምስክር ሆነ። ከዚህም በኋላ ዳኞች ወደ ሸንጎ አስቀርበው ከእንግዲህ አንታገሥህም ወደ ሃይማኖታችን ከምትገባና ወይም በእሳት ከምናቃጥልህ ምረጥ አሉት። እርሱም እኔ ከእናንተ ጋራ ለዘላለሙ ዕድል ፈንታ የለኝምና የወደዳችሁትን አድርጉ ብሎ መለሰላቸው። በዚያን ጊዜም እጅግ ተቆጡ ያለ ርኀራኄ ይደበድቡት ዘንድ አዘዙ ያገር ሰዎችም በጫማቸው መቱት አንዲት ሴትም መጥታ በጫማዋ መታችው ወዲያውኑ እጆቿ ደረቁ። ከዚህም በኋላ ባለ ሰይፍ ከመኰንኑ ታዝዞ ወጣ ሰይፉንም መዝዞ ሳያቋርጥ መላልሶ አንገቱን መታው። ምቱም ወደ ጐን ሒዶ ጆሮውን ቆረጠው አመታቱ ክፉ ስለ ሆነ ከሥሮቿ ብዙ ደም ፈሰሰ። ከዚህም ደግሞ ተዉት ወደ እምነታቸው ሊአስገቡት እምቢ በአላቸውም ጊዜ ሁለተኛ ሰይፉን መዝዞ ሰያፊው የከበረች አንገቱን ቆረጠው በመንግሥተ ሰማያትም የምስክርነት አክሊልን ተቀበለ። ሥጋውንም ከእሳት ጨመሩ ግን አልተቃጠለም። ዘመዶቹም መጥተው በድኑን ወደአገሩ ወሰዱ። በቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ ጐን ቀበሩት። የክብር ባለቤት ጌታችንም ብዙ ድንቆች ተአምራትን ከሥጋው ገለጠ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም ቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዚያ 27 #ቅዱስ_ፊቅጦር_ሰማዕት ሚያዝያ ሃያ ሰባት በዚች ቀን የከበረ ቅዱስ ፊቅጦር በሰማዕትነት አረፈ። ለዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ኀርማኖስ ነው እርሱም ለዲዮቅልጥያኖስ የአማካሪዎቹና የሰራዊቱ አለቃ ነው ስለ አምልኮ ጣዖት ሥራ ምክሩና ንግግሩ ሁሉ ከእርሱ ጋራ ነበር የእናቱም ስም ማርታ ይባላል በክርስትናዋ የጸናች ብፅዕት ናት። ቅዱስ ፊቅጦርም በአደገ ጊዜ አባቱ ወደ ንጉሥ አቀረበው ንጉሡም በመንግሥቱ ውስጥ ሦስተኛ ማዕርግ አድርጎ ሾመው በዚያን ጊዜ ዕድሜው ሃያ ዓመት ነበረ። እርሱም የዚህን ዓለም ክብር ናቀ ሥጋ አይበላም ወይን አይጠጣም ዘወትርም ይጾማል ጸሎትንም ባለማቋረጥ በቀንና በሌሊት ይጸልያል። በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም የታሠሩትን ይጐበኛቸዋል ለድኆችና ለምስኪኖችም ይመጸውታል። የቅዱሳን ቆዝሞስና ድምያኖስ እናት ቅድስት ቴዎዳዳን በገደሉዋት ጊዜ ንጉሡን ስለ መፍራት ሊቀብራት ማንም አልደፈረም። ይህ ቅዱስ ፊቅጦርም መጥቶ ሥጋዋን ወሰደ ከንጉሥ ስለሚመጣው ቅጣት ሳይፈራ ቀበራት። ጣዖት ስለ ማምለኩ አባቱን ዘወትር የሚገሥጸውና ብዙ ጊዜም የሚመክረው ሆነ አባቱም ወደ ንጉሥ ከሰሰው እንጂ አልሰማውም። ተከሶም ወደ ንጉሥ በአቀረቡት ጊዜ አማልክት ያልሆኑ ርኲሳን ጣዖታትን ለሚያመልክ ሰነፍ ዝንጉ ልብ የለሽ ለሆነ ንጉሥ አላገለግልም። ከዛሬ ጀምሮ ለሕያው ንጉሥ ክርስቶስ እገዛለሁ የሰጠኸኝንም ገንዘብህን ንሣ ብሎ ከፊቱ ትጥቁን ፈትቶ ጣለላት። አባቱ ኀርማኖስም ወደ እስክንድርያ እንዲልከውና በኄርሜኔዎስ መኰንን ዘንድ በዚያ ፊቅጦር እንዲቀጣ ንጉሡን መከረው። በዚያን ጊዜም ከአደባባይ አወጡት እናቱም በብዙ ልቅሶ ልትሸኘው መጣች። እርሱም ሲመግባቸው ስለ ነበሩ የታሠሩ ምእመናን ስለ ድኆችና ምስኪኖች ስለ ሙት ልጆችና ስለ ባልቴቶች የሚሹትን በመስጠት እንድትጐበኛቸው አዘዛት ከዚያም አፉን ለጉመው ወሰዱት። በእስክንድርያ አገር ወደ መኰንኑ ኄርሜኔዎስ ዘንድ በደረሰ ጊዜ ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ ሰማያት አውጥቶ ስለ ክብራቸው ለመናገር የሚያስጨንቁ የብርሃን ማደሪያዎችን አሳይቶ ወደ መኖሪያው መለሰው። መኰንኑም በእሳት በአፈሉት በዝፍት በዲን ደግሞ አሠቃየው ከዚያም በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከበታቹ እሳትን አነደዱ። ደግመው ከውሽባ ማንደጃ ውስጥ ጨመሩት በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም አሠቃዩት የክብር ባለቤት ጌታችንም ያጸናውና ከሥቃዩ ያስታግሠው መልአኩንም ልኮ ከቁስሉ ይፈውሰው ነበር። ከዚህም በኋላ ወደ እንዴናው ከተማ ላከው በዚያም ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት ምላሱን ቆረጡ። በእሳት ያጋሉዋቸውን ችንካሮች በጐኖቹ ውስጥ ጨመሩ እግዚአብሔር ግን አጽንቶ አስታግሦ ያለ ጉዳት በደኀና ያነሣዋል። ከዚህም በኋላ በዚያ በረኃብ እንዲሞት ከዱር ባለ ግምብ ውስጥ አሠሩት። እርሱ ግን መጥረብ የሚያውቅ ስለሆነ ላይዳዎችን በመጥረብና በመሸጥ በየጥቂቱ እየተመገበ የቀረውን ለድኆች እየሰጠ ኖረ። አንድ መኰንንም መጥቶ በዚያ ግምብ አቅራቢያ አደረ ስለ ቅዱስ ፊቅጦርም እርሱ የንጉሥ የሠራዊት አለቃ የሆነ የኀርማኖስ ልጅ እንደሆነ ነገሩት። መኰንኑም ወደርሱ አቅርቦ ብዙ ሸነገለው ባልሰማውም ጊዜ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ ጅማቶቹን መዘዙ አፉን መቱት ቊልቊል ሰቅለው በእጆቹ ላይ ከባድ ደንጊያ አንጠለጠሉ። ከዚያም ከሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት ሙጫ አደሮ ማርና ዘይትን አፍልተው በላዮ ደፉበት በማበራያም አበራዩት አፉንም በአሞትና በእሬት አመረሩት ዐይኖቹንም አወለቁት ደግመውም ዘቅዝቀው ሰቀሉት። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ተገልጾለት አጸናው አረጋጋው። ሥሮቹንና ሕዋሳቶቹን በቦታቸው መለሰለትና አዳነው። አንዲት ዓሥራ አምስት ዓመት የሆናት ብላቴና ነበረች ቅዱስ ፊቅጦርን ሲአሠቃዩት በቤቷ መስኮት ታየው ነበር። መላእክትንም በእጆቻቸው አክሊሎችን ይዘው እነርሱም በቅዱስ ፊቅጦር ራስ ላይ ሲያኖሩአቸው አይታ እንዴት እንዳየች ለአሕዛብ ነገረቻቸው እጅግም አደነቁ። ከእርሳቸውም ብዙዎች በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት አረፉ፡፡፡ ያቺም ብላቴና በጌታችን አመነች መኰንኑም ራሷን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። የሕይወት አክሊልንም ተቀበለች ሁለተኛም የአመኑትን ሁሉ ራሳቸውን እንዲቆርጡአቸው አዘዘ የሕይወትንም አክሊል ተቀበሉ። ከዚህም በኋላ የከበረች የቅዱስ ፊቅጦርን ራስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ተጋድሎውንም ፈጽሞ የሕይወትና የድል አክሊልን ተቀበለ። ምእመናን ሰዎችም ሥጋውን ወስደው በከበሩ ልብሶች በድርብ በፍታ ገነዙት። እናቱ ማርታም ከአንጾኪያ እስክትመጣ በንጹህ ቦታ አኖሩት በመጣችም ጊዜ ከዚያ ወሰደችው። ውብ ቤተ ክርስቲያንም ሠርታ ሥጋውን በውስጥዋ አኖረች ከእርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_26 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ስድስት በዚህች ቀን የሱሲ ልጅ #ቅዱስ_ሱስንዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣የጠራቢ ልጅ #ቅዱስ_ዮሐንስ በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሱስንዮስ ሚያዝያ ሃያ ስድስት በዚህች ቀን የሱሲ ልጅ ሱስንዮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም የከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ወዳጅ ነበረ። የእግዚአብሔር መልአክም ተገለጠለትና ሰማዕት እንደሚሆን ነገረው ይህም ነገር በልቡ አደረ። ከዚህም በኋላ አምልኮ ጣዖትን እንዲአስፋፉና እንዲአድሱ ከሹመት ደብዳቤ ጋራ ንጉሡ ወደ ኒቆምድያ ላከው። ቅዱሱም አይቶ እጅግ አዘነ ከዚያም ወደርሱ አንድ ቄስ አምጥቶ የክርስትናን ትምህርት ተምሮ ተጠመቀ። ከዚህ በኋላም ወደ አንጾኪያ ተመለሰ ፍጥረቱ ልዩ የሆነ ልጅን ወልዳ እኀቱን አገኛት። ከዚህ በፊት ሴት ልጅ ወልዳ ገድላ ደሟን ጠጥታለች ሰይጣን አድሮባታልና በወፍና በከይሲ አምሳልም ይገለጣል በአገር ውስጥም ልጅ በሚወለድ ጊዜ ወደርሱ ወርዳ በሥራይም ገድላ ደሙን ትጠጣለች። ቅዱስ ሱስንዮስም ይህን በአየ ጊዜ ጦሩን አንሥቶ ከልጅዋ ጋራ እኀቱን ገደላት ልጅዋ የሰይጣን ልጅ ነውና ሁለተኛም ሥራየኞች ስለሆኑ ባሏንና የባሏን አባቱን ገደላቸው እነርሱ በሥራያቸው ሰውን እያሳመሙ ይገድላሉና። ከዚህም በኋለ ወደኒቆምድያ ተመልሶ ወደዚያ ወደ አጠመቀው ቄስ ደርሶ ያደረገውን ሁሉ ነገረው። ወደ አገሩ አንጾኪያም በተመለሰ ጊዜ ከእርሱ የሆነውን አባቱ ሱሲ አወቀ መገደሉንም ወዶ ከንጉሥ ዘንድ ነገር ሠራበት። ያን ጊዜም ቅዱስ ሱስንዮስ ወደ ጣዖታት ቤት ሒዶ ወደ ሲኦል ይወርዱ ዘንድ በጌታችን ኢየሱስ ስም አዘዛቸው ያን ጊዜም ምድር አፍዋን ከፍታ ዋጠቻቸው ጣዖታቱንም እንዳጠፋቸው ወሬው ተሰማ። አባቱም ዳግመኛ በንጉሥ ዘንድ ከሰሰው ታላቅ ሥቃይም ያሠቃዩት ዘንድ ንጉሥ አዘዘ በብረት ዘንጎችም ደበደቡት በመንኰራኲርም አበራዩት በመዶሻም ቀጥቅጠው ሁለተኛ ደግመው እህል በሚአበራዩበት መሣሪያ አበራዩት። ከዚያም በከተማው ውስጥ ጐተቱት። የክብር ባለቤት ጌታችንም ያጸናውና በሥቃዩም ውሰጥ ያስታግሠዋል ከቁስሉ የሚፈውሰውን መልአኩንም ልኮ ያለ ምንም ጉዳት አነሣው። ብዙ ሰዎችም አይተው በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በርሱ ምክንያት ሰማዕታት ሆኑ። ንጉሥም ከማሠቃየቱ በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። በሥቃዩም ወራት በሰማዕትነት የሞቱት ቍጥራቸው አንድ ሺህ አንድ መቶ ዘጠኝ ሆነ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዮሐንስ_ሰማዕት በዚህችም ቀን የጠራቢ ልጅ ቅዱስ ዮሐንስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ከነነዌ አገር ነው አባቱ ጣዖትን የሚጠርብና የሚያመልክ ነው። እናቱ ግን ክርስቲያናዊት ናት ልጅ በአጣችም ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ለመነች ጌታም ልመናዋን ተቀብሎ ይህን የተባረከ ልጅ ሰጣት ስሙንም በሥውር ዮሐንስ ብላ ጠራችው። ስምንት ዓመትም በሆነው ጊዜ የጠረበውን ጣዖት እየሸጠለት ኣባቱን ያገለግል ነበር። በአንዲት ዕለትም ጣዖቱን ሊሸጥ ሲሔድ የእግዚአብሔር መልአክ ተገናኘውና ጣዖት የሰይጣን ማደሪያ እንደሆነ ነገረው ጣዖቱንም ከእጁ እንዲጥለው አዘዘው በክብር ባለቤት በክርስቶስ ማመንን አስተማረው። ወደ አባቱም በተመለሰ ጊዜ ሰማይና ምድርን በውስጣቸውም ያለውን ሁሉ ከፈጠረ ከክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም እኔ ለሰው እጅ ሥራ አልሰግድም አለው። አባቱም ሰምቶ በእሥር ቤት አሠረው እናቱም መጥታ በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ደሙን ያፈስ ዘንድ አጸናችው። ከዚህም በኋላ በነገራቸው ሊሸነግሉት የአገር ሰዎች መጥተው የአባትህን አምላኮች ለምን ተውክ አሉት። እርሱም እኔ የሰው እጅ ለሠራቸው ጣዖቶች አልሰግድም አነርሱ የርኲሳን አጋንንት ማደሪያዎች ናቸውና አላቸው አባቱም ይህን በሰማ ጊዜ ምሳር አንሥቶ አንገቱን ቆረጠው በድኑም አልወደቀም በደሙ እስከተጠመቀ ድረስ በእግሮቹ ቆመ እንጂ። እናቱም በደሙ ተጠምቃ አቤቱ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የአቤልን መሥዋዕት በምድረበዳ የተቀበልክ ይህንን መሥዋዕት ከእኔ ተቀበል አለች። በዚያን ጊዜ በአባቱ ሰይጣን አደረበትና አበደ። ሚስቱም ወደ ልጅዋ መቃብር ወስዳው ስለርሱ ጸለየች ቅዱስ ዮሐንስም በሌሊት ወደርሱ መጥቶ አባቱን በጦር ወጋው ሰይጣኑም ከእርሱ ወጣ። ከዚህ በኋላም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነና በስሙ ተጠመቀ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_25 #ቅድስት_ሣራ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ አምስት በዚች ቀን ቅድስት ሣራ ከሁለቱ ልጆቿ ጋራ በሰማዕትነት አረፈች፡፡ ይቺም ቅድስት ከአንጾኪያ አገር ናት እርስዋም ከዲዮቅልጥያኖስ መኳንንት ለአንዱ ስሙ ስቅራጥስ ለሚባል ሚስቱ ናት እርሱም በፊት ክርስቲያን ነበረ በኋላ ንጉሡን በመፍራት ካደ እርስዋ ግን በክርስትናዋ ጸንታ ኖረች። ባልዋ ስቅራጥስም እኔ የክርስቲያንን ሃይማኖት እወዳለሁ የንጉሡን ሥቃይ ከመፍራት በቀር ክርስቶስን በልቤ አልካድኩትም ይላት ነበር። እንደዚህም ስትኖር ሁለት ልጆችንም ወለደች በአንጾኪያም አገር የክርስትና ጥምቀትን ልታስጠምቃቸው አልተቻላትም። አብያተ ክርስቲያናት ተዘግተዋልና ጠፍተዋልምና ሰውን ወዳድ ክርስቶስን ብዙ ስለመውደዷ ልጆቿን ታስጠምቃቸው ዘንድ ታላቅ ተጋድሎ አደረገች ወደ እስክንድርያ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጴጥሮስ ልትሔድ ወዳ አሽከሮቿን አስከትላ ሁለቱን ልጆቿን ይዛ በመርከብ ተሳፈረች። የክብር ባለቤት ጌታችንም የሃይማኖቷን ልዕልና ለመጪው ትውልድ ሊገልጥ ወዶ ያቺ መርከብ ለመሥጠም እስከምትደርስ በባሕር መካከል ጥቅል ነፋስን አስነሣ። ይቺ ቅድስትም ልጆቿ ሳይጠመቁ እንዳይሞቱ ፈራች ተነሥታም ጸለየች ከዚያም ምላጭ አንሥታ ጡቷን የቀኙን በጣች ከደሟም ወስዳ ፊታቸውን በመስቀል ምልክት ቀባች በደረታቸውና በጀርባቸውም ላይ እንዲሁ አደረገች በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በባሕሩ ውስጥ አጠመቀቻቸው ያን ጊዜም ታላቅ ጸጥታ ሆነ። ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰች ጊዜ ከሀገር ልጆች ጋራ ያጠምቃቸው ዘንድ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጴጥሮስ ልጆቿን አቀረበች በዚያን ጊዜም ከሀገር ልጆች አጠመቀ። ወደልጆቿም ደርሶ ሊአጠምቃቸው ወሰዳቸው ያን ጊዜ ውኃው ረጋ እነርሱን ትቶ ከአገር ልጆች አጠመቀ ውኃውም ተፈትቶ ወረደ ደግሞ ሊአጠምቃቸው ወደ ልጆቿ ተመለሰ አሁንም እንደቀድሞው ውኃው ረጋ እንዲሁም ሦስት ጊዜ አደረገ ውኃውም ይረጋል አደነቀ። እናታቸውንም አቅርቦ ጠየቃት እርሷም ፈርታ ተንቀጠቀጠች ከእርሷም የሆነውን በባሕር መካከል ዐውሎ ነፋስ እንደተነሣባት ጡቷን በጥታ ደሟን እንደ ቀባቻቸውና በባሕር ውስጥ እንዳጠመቀቻቸው ነገረችው ስለ አደረገችውም ድፍረት በፊቱ ሰግዳ ይቅር ይላት ዘንድ ለመነችው። አባ ጴጥሮስም ሴትዮ አትፍሪ ሃይማኖትሽ ፍጹም ነው አንቺ በባሕር ውስጥ በአጠመቅሻቸው ጊዜ በመለኮታዊት እጁ ያጠመቃቸው ባለቤቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና አይዞሽ አላት።ማጥመቁንም በፈጸመ ጊዜ ሥጋውን ደሙን አቀበላቸው ይቺም ቅድስት ወደ አንጾኪያ ቤቷ ተመለሰች። ባሏም በአያት ጊዜ ይህን በማድረጓ ተቆጥቶ ወደ ንጉሡ ሒዶ ከሰሳት ያደረገችውንም ነገረው። ንጉሡም ወደርሱ ያቀርቧት ዘንድ አዘዘ ስትቀርብም ወደ እስክንድርያ ለምን ሔድሽ ከክርስቲያን ወገኖች ጋራ ልታመነዝሪ ነውን አላት። እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችለት ክርስቲያኖች አያመነዝሩም እንደናንተ የረከሰ ጣዖትን አያመልኩም ከእንግዲህ ደግሞ ከእኔ ቃልን አትሰማም የወደድከውን አድርግ ሁለተኛም በእስክንድርያ ካንቺ የሆነውን ንገሪኝ ብሎ ጠየቃት ምንም ምን አልመለሰችለትም ። ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም እጆቿን የኋሊት አሥረው ሁለቱንም ልጆቿን በሆድዋ ላይ አድርገው ሦስቱንም በእሳት ያቃጥሉአቸው ዘንድ አዘዘ። ፊቷንም ወደ ምሥራቅ መልሳ ወደ ክብር ባለቤት ጌታችን ጸለየች ከዚያም ከልጆቿ ጋራ አቃጠሉዋት የድልና የሕይወት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቷ ለዘላለም ይማረን አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_24 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ አራት በዚህች ቀን የቅዱስ ኤስድሮስ ባልንጀራ #ቅዱስ_ፃና በሰማዕትነት አረፈ፣ ጳጳሳት ስልሳ አምስተኛ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ስንትዩ አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ፃና ሚያዝያ ሃያ አራት በዚህች ቀን በመጋቢት ዐሥራ ስምንት ቀን የተጻፈ የቅዱስ ኤስድሮስ ባልንጀራ ቅዱስ ፃና በሰማዕትነት አረፈ፡፡ ይህም እንዲህ ነው ባልንጀራው ከኤስድሮስ ጋራ ከአሠቃዩት በኋላ ባልጀራው ኤስድሮስ በሰማዕትነት ሞተ። ቅዱስ ፃናም በእሥር ቤት ቀረ ከአገረ ፈርማ መኰንንም ታሠረ በእርሱም ፈንታ ሌላ መኰንን ተሾመ። ያንን መኰንንም የክብር ባለቤት የሆነ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም የሚጠራ ክርስቲያንን ሁሉ እንዳያስቀር ከሀዲው ንጉሥ አዘዘው። ስለ ቅዱስ ፃናም እርሱ ከጭፍሮች ውስጥ እንደሆነ ጽኑዕ ሥቃይም እንዳሠቃዩትና ከአላማውም እንዳልተመለሰ በነገሩ ጊዜ የከበረች ራሱን ይቆርጡት ዘንድ አዘዘና ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። የቅዱስ ፃና እናቱም ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት በሆነ ጊዜ አስቀድማ እንዳየች አሁንም ብርሃናውያን መላእክትን የቅዱስ ፃናን ነፍስ ሲያሳርጓት አይታ ለሰው ነገረች። ምዕመናንም ሥጋውን ወስደው ገንዘው ሰምኑድ በሚባል አገር ከባልንጀራው ከኤስድሮስ ሥጋ ጋር አኖሩት። በውስጥዋም እስከ ዛሬ በዓል ይደረግላቸዋል። ወደ እርሳቸው በእምነት ለሚመጣም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ይታያል። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ስንትዩ_ሊቀ_ጳጳሳት በዚህችም ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ስልሳ አምስተኛ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ስንትዩ አረፈ፡፡ ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ መንፈሳዊ ነው። በአስቄጥስም ገዳም በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን በበጎ ሥራ በገድል ተጠምዶ አድጎ በዚያው ገዳም አበምኔት ሁኖ ተሾመ። ከዚህም በኋላም ሕዝቡና ኤጲስቆጶሳቱ መርጠውት በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት። ነገር ግን በዘመኑ ሁሉ ከእስላሞች ነገሥታት ታላቅ ችግርና ኀዘን ደረሰበት። ይኸውም በእርሱ ዘንድ ምንም ምን ያልኖረውን ሊሰጣቸው የሌለውን ብዙ ገንዘብ ይሰጣቸው ዘንድ ፈልገው ይዘውታልና። እግዚአብሔር በእጆቹ ብዙ ድንቆች ተአምራቶችን አደረገ ብዙዎችን ጭንቅ ከሆነ ደዌያቸው አድኖቸዋልና ከሰዎችም ላይ ሰይጣናትና አስወጥቷልና በአገረ መርዩጥ ላይ በጸሎቱ ዝናምን አዝንሞአልና። እርሱም ዝናምን ከማጣት የተነሣ ወንዞቻቸው ጉድጓዶቻቸው ሁሉ ደርቀው ከረኃብና ከውኃ ጥም የተነሣ ለሞት ተቃርበው በታላቅ ረኃብ ሦስት ዓመት ኑረዋልና። በሰማዕት ቅዱስ ሚናስ ቤተ ክርስቲያን በዓልን ሊያከብር ወደርሳቸው በደረሰ ጊዜ የዚያች አገር ሰዎች ወደ ርሱ ተሰብስበው ውኃ በማጣት እንደ ተቸገሩ ነገሩት እርሱሙ ፈጽሞ አጽናናቸው። የቅዳሴውንም ሥርዓት ከፈጸመ በኋላ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ወዲያውኑ ታላቅ ነጐድጓዶችና ኩሬዎች ሁሉ ሞሉ የተክል ቦታዎች ሁሉ ረኩ። ረኃብ በሆነባቸው በእነዚህ ሦስት ዓመት እንደመላ ኖረ። አራተኛውም በአስቄጥስ አረቦች በተሰበሰቡ ጊዜ በዚያ የሚኖሩትን መነኰሳት ይገድሉአቸው ዘንድ ከበቡአቸው ይህም አባት መስቀሉን ይዞ ወደእርሳቸው ወጣ መስቀሉንም በአዩ ጊዜ ወደኋላቸው ተመልሰው ሸሹ በማንም ላይ ከቶ ጉዳት አላደረሱም። ደግሞ በትምርቱ ከአገሩና ከመንጋው ውስጥ ክህደትንና ኑፋቄን አስወገደ በዚያን ጊዜ ስለእኛ መከራ የተቀበለው ትብስእት ብቻውን ነው አምላክ አይደለም የሚሉ ነበሩና። ይህም አባት ስንትዩ በከበረ በታላቁ ጾም ወራት መልክትን ጽፎ ለአገሩ ሁሉ ላከ በውስጥዋም እንዲህ የሚል እያስተማረ "ስለእኛ መከራ የተቀበለ እግዚአብሔር ቃል በሥጋ ነው ከተዋሕዶ በፊት ሁለት የነበሩ በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ ስለሆነ አንዲት ሰዓት ወይም የዐይን ጥቅሻ ያህል ከቶ አልተለያዩም በመከራ ጊዜ ወይም በሞት ከመለኮቱ ያልተለየ እርሱ አካላዊ ቃል በሥጋው ስለ እኛ መከራን ተቀበለ"። ይቺም መልእክት በአገሩ ሁሉ በአነበቡአት ጊዜ የክርስቲያን ወገኖች ታላቅ ደስታ ደስ አላቸው እሊያ የሳቱትም ተመልሰው ንስሓ ገቡ። ሁለኛም ደግሞ ምላሳቸውን መቆረጥ የሚገባቸው የተሳሳቱ የመለኮት ባሕርይ ሞተች የሚሉ ሰዎች ተገለጡ እሊህም የብልንያ አገር ሰዎችና ኤጲስቆጶሳቸውም ነው። ይህም አባት ይህን የእብደትና የስንፍና ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አዝኖ መልእክትን በውስጡ እንዲህ ጻፈ "እግዚአብሔር ባሕርዩ አትመረመርም የማትዳሠሥ የማትታመም ናት እግዚአብሔር ቃል ከእኛ ነሥቶ ያለ መለያየትና ያለ መቀላቀል ከመለኮቱ አዋሐደው ከሰውነቱ ባህርይ በቀር ሕማምን አታስገባም" ሁለተኛም በውስጥዋ እንዲህ አለ "እኛ መከራ ከሚቀበል ከሥጋው እግዚአብሔር ቃልን አንለየውም በመከራውም በሥራው ሁሉ አንድ እንደሆነ እናምናለን እንጂ ሁለተኛም መለኮቱ በባሕርዩ የማይታመም የማይሞት እንደሆነ ከመለኮት ሳይለይ ስለእኛ መከራ ተቀብሎ ሞተ እንጂ"። የመልእክቱም ደብዳቤዎች ወደእነዚህ ሰዎች ደርሰው በአነበቡአቸው ጊዜ ከስሕተታቸው ተመልሰው በእውተኛዪቱ በቀናች ሃይኖት አመኑ። ኤጲስቆጶሳቸውም ጋራ ወደዚህ አባት ወደ ሊቀ ጳጳሳት ስንትዩ ፊት ቀርበው የቀናውን እምነት ተቀብለው አመኑ ታላቅ ስሕተታቸውንና በደላቸውንም ይተውላቸው ዘንድ ለመኑት እርሱም ስሕተታቸውን እያመኑ በኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ በካህናቱ በሕዝቡም ፊት እንዲሰግዱ አዘዛቸው እንዳዘዛቸው አደረጉ በደላቸውንም ተወላቸው። ይህም አባት አብያተ ክርስቲያናትን ስለማነፅ የስደተኞችንም ቦታዎች ስለማዘጋጀት ብዙ የሚአስብ ነው ከዚህ የሚተርፈውንም ለድኆችና ለምስኪኖች ይሰጣል። መልካም ጉዞንም በመጓዝ እግዚአብሔርን አገለገለው ሚያዝያ24 በሰላምም ዐረፈ። የሹመቱም ዘመን ዐሥራ አምስት ዓመት ሆነ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱሳኑ በረከት ረድኤት በሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን፡፡ https://t.me/finotebirhan12

ያን ጊዜም የክቡር ጊዮርጊስን ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ድል አድራጊ ጊዮርጊስም እጅግ ደስ አለው እሳት ከሰማይ አውርዶ ሰባውን ነገሥት ያቃጥላቸው ዘንድ መከራውም ከክርስቲያን ወገን ጸጥ ይል ዘንድ ጌታችንን ለመነው፡፡ ወዲያው እሳት ወርዶ ከሠራዊታቸው ጋር ሰባውን ነገሥታት አቃጠላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጾ ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ በምድር መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስሳለሁ በመከራም ውስጥ ሁኖ በባሕርም ሆነ በየብስ ወይም በደዌ በስምህ የሚለምነኝን እኔ ፈጥኜ ከመከራው አድነዋለሁ ይህንንም ጌታችን ተናግሮ በክብር ወደ ሰማይ ወጣ፡፡ ከዚህ በኋላ ራሱን ዘንበል አድርጎ በሰይፍ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያት አክሊላትን ተቀበለ፡፡ ከአገልጋዮቹም የቀሩት ሥጋውን ወስደው በልብስ ጠቀለሉት ወደ ሀገሩ ልዳም ወሰዱት፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው በውስጥዋ አኖሩት ከእርሱም ቍጥር የሌላቸው ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሮቆ በዚህችም ቀን ተአምራትን እስከ አሳየ ድረስ የተጋደለ ቅዱስ ሮቆ አረፈ። በአንዲት ዕለትም ለጸሎት ቁሞ ሳለ የንዳድ ትንኝ ነደፈው ቀስሉን እያሳየ በብዙ ልቅሶ ወደ ጌታችን ለመነ። ያን ጊዜም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደመና ላይ ተገለጠለት። በአንጻሩም ቁሞ ወዳጄ ሮቆ አትፍራ ላድንህ ወደ አንተ መጥቻለሁና ። ደግሞም የሮቆ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከንዳድ በሽታ አድነኝ ብሎ በስምህ ለሚለምነኝ የንዳድ በሽታ በላዩ ላላመጣበት ከአንተ ጋራ ቃል ኪዳንን ላጸና መጣሁ አለው። ይህንንም ብሎ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ቅዱስ ሮቆም በብዙ ገድል ተጠምዶ ኑሮ በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱሳኑ በረከት ረድኤት ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_23 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ሦስት በዚህች ቀን ታላቅና ክቡር የሆነ #የሰማዕቱ_የቅዱስ_ጊዮርጊስ የምስክርነት ፍጻሜ ሆነ፣ ተአምራትን እስከ አሳየ ድረስ የተጋደለ #ቅዱስ_ሮቆ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ጊዮርጊስ_ሊቀ_ሰማዕት ሚያዝያ ሃያ ሦስት በዚህች ቀን ፀሐይና የአጥቢያ ኮከብ የተባለ ታላቅና ክቡር የሆነ የሰማዕቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ የምስክርነት ፍጻሜ ሆነ። የዚህም ቅዱስ አባቱ መስፍን ነው ስሙም አንስጣስዮስ ይባላል ከቀጰዶቅያ አገር ነው የእናቱም ስም ቴዎብስታ ይባላል ከፍልስጥዔም አገር ናት ታናሽ ሆኖ ሳለ አባቱ አረፈ። ሃያ ዓመትም በሆነው ጊዜ የአባቱን ሹመት ሊቀበል ወደ ንጉሥ ዱድያኖስ ዘንድ ሔደ፡፡ ንጉሡም ጣዖት አቁሞ ጣዖትን እንዲአመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው። ይህንንም አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ በእርሱ ዘንድ ያለውን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ለምስኪኖች ሰጠ ባሮቹንም ነፃ አወጣቸው። ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። ንጉሡም አባበለው ብዙ ቃልኪዳንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም። ለመስማት እንኳ የሚያስጨንቅ ሥቃይን አሠቃየው ጌታችን ግን ያጸናዋል ቍስሉንም ያድነዋል ሦስት ጊዜም እንደ ሚሞት እርሱም እንደሚአሰነሣው በአራተኛውም የምስክርነት አክሊልን እንደሚቀበል ነገረው። ቃል ኪዳንም ሰጠው ስሙ በዓለሙ ሁሉ የተገለጠ ይሆን ዘንድ በተጋድሎና መከራ በመቀበልም ጽኑዕ በሆነ ሥቃይም ሰባት ዓመት እንደሚኖር መላእክትም እንደሚአገለግሉት ነገረው። ንጉሡም ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለመታዘዙና ባለመመለሱ እጅግ አዘነ ስለዚህም አትናስዮስ የሚባል ታላቅ ሥራየኛ አመጣ እርሱም መርዝን ቀምሞ በጽዋ መልቶ አስማት ደግሞ እንዲጠጣ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰጠው። ወዲያውኑ የሚሞት መስሎት ነበር። ቅዱሱም ያንን ጽዋ ጠጣው ምንም ጉዳት አልደረሰበትም። ያ መሠርይም በክብር ባለቤት በጌታ ኢየሱስ አምኖ በሰማዕትነት ሞተ። ከእርሱም ጋራ ሌሎች ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሙተው የሕይወት አክሊል ተቀበሉ ቍጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ሰባት መቶ ነፍስ ነው። ቅዱስ ጊዮርጊስም በዱድያኖስና በሰባ ነገሥታት ፊት በቆመ ጊዜ በዚያም የተቀመጡባቸው የዕንጨት ወንበሮች ነበሩ። ቅዱሱንም እሊህን የተቀመጥንባቸውን ወንበሮች እንዲበቅሉ እንዲአብቡና እንዲአፈሩ ታደርጋቸው ዘንድ ከአንተ እንሻለን አሉት። በዚያን ጊዜ ጸለየ እንዳሉትም አደረጋቸው ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ቍጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ በጌታችን አመኑ። ከዚህም በኋላ ቅዱሱን ወስደው በጐድጓዳ ብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት። አቃጥለው አሳርረውም ሥጋውንና አጥንቱን ፈጭተው አመድ አድርገው ከረጅም ተራራ ላይ በተኑት። ጌታችንም ነፍሱን ወደ ሥጋው መልሷት ደግሞ አስነሣው። ወደ ነገሥታቱም ተመልሶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ስም ሰበከ ቁጥር የሌላቸው አሕዛብ አይተው አደነቁ በጌታችንም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ። ነገሥታቱም ደግመው ሙታኖችን ብታሥነሣ አምላክህ እውነተኛ አምላክ እንደሆነ እናውቃለን በእርሱም እናምናለን አሉት። ቅዱሱም ጸለየ ከጉድጓድም ውስጥ ወንዶችና ሴቶች ጎልማሶችንም አስነሣላቸው እነዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ስም አስተማሩ የገሀነምንም ወሬ ተናገሩ ጥምቀትንም ተቀብለው ተመልሰው አረፉ። ከሀድያን ነገሥታት ግን ሙታንን ያስነሣህ አይደለም የረቀቁ ሰይጣናትን አሳየህ እንጂ ብለው ተከራከሩ። ከዚያም ከጭንቀታቸው ብዛት የተነሣ ከአንዲት ድኃ ሴት ዘንድ አስጠበቁት እርሷም እንጀራ ልትለምንለት ወጣች የእግዚአብሔርም መልአክ በላዩ ከበጎ ነገር ሁሉ የተመላ ማዕድን አቀረበላት። የዚያች መበለትም የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍን አበቀለ ታላቅ ዛፍም ሆነ። ያቺም መበለት በተመለሰች ጊዜ የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍ አብቅሎ ታላቅ ዛፍ እንደሆነ ስለ ማዕዱም ይህን ታላቅ ምልክት አይታ የክርስቲያኖች አምላክ ሰው ተመስሎ ወደእኔ መጣ አለች። ቅዱሱም እኔ አምላክ አይደለሁም የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ አላት። እርሷም እንዲህ ብላ ለመነችው የአምላክ አገልጋይ ከሆንክ ቸርነትህ እንድትደርሰኝ አለምንሃለሁ። ዕውር ደንቆሮ ዲዳ ጐባጣ የሆነ ልጅ አለኝና ታድንልኝ ዘንድ እለምንሃለሁ። ስለ ጌታችን እምነትም አስተማራትና በመስቀል ምልክት አማተበው ያንጊዜም አየ። ቅዱሱም በሌላ ጊዜ እንዲሰማ እንዲናገርና እንዲሔድ እንዲአገለግለኝም እኔ እሻለሁ አላት። በዚያን ጊዜ ንጉሡ በአገሩ ሜዳ ውስጥ ሲዘዋወር ያቺን ዛፍ አይቶ አደነቀ ስለ እርሷም ጠየቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ በእርሷ ዘንድ የተቀመጠባት የዚያች መበለት የቤቷ ምሰሶ እንደሆነ ነገሩት። ንጉሡም ተቆጣ ቅዱሱንም ከዚያ ወስዶ አሰገረፈው በመንኰራኩርም አበራዩት ሙቶም ከከተማ ውጭ ጣሉት ጌታም ከሞት አስነሣው ወደ ነገሥታቱም ተመለሰ ንጉሡም አይቶ ደነገጠ ስለ ሕይወቱም አደነቀ። ከዚህም በኋላ ይሸነግለው ዘንድ ጀመረ በመንግሥቱ ላይም ሁለተኛ ያደርገው ዘንድ ቃል ገባለት ቅዱስ ጊዮርጊስም እየዘበተበት ነገ በጥዋት ለአማልክቶችህ መሥዋዕትን አቀርባለሁ አንተም ሕዝቡ እንዲሰበሰቡ እዘዝ እኔ ስሠዋ እንዲአዩ አለው፡፡ ንጉሡም ዕውነት የሚሠዋ መስሎት ደስ አለው ወደ ቤተ መንግሥቱም እልፍኝ አስገብቶ አሳደረው፡፡ ለጸሎትም ተነሣ የዳዊትንም መዝሙር አነበበ የዱድያኖስ ሚስቱ እለስክንድርያ ንግሥት ሰምታ ቃሉ ደስ አሰኛት የሚያነበውንም ይተረጒምላት ዘንድ ለመነችው እርሱም እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ሰው እስከሆነበት ጊዜ የሆነውን ሁሉ ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀመረ ትምህርቱም በልቡዋ ተቀርጾ በክብር ባለቤት በጌታችን አመነች፡፡ በማግሥቱም ቅዱስ ጊዮርጊስ ለአማልክት ሲሠዋ ለማየት ሰው ሁሉ እንዲሰበሰብ ዐዋጅ ነጋሪ ዞረ የቤቷን ምሰሶ ያበቀለላት ያቺ መበለት ሰምታ ዕውነት መስሏት እጅግ እያዘነች ልጅዋን ተሸክማ እያለቀሰችም ወጣች፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስም በአያት ጊዜ ፈገግ አለ ልጅሽን በምድር ላይ አኑሪው አላት ከዚያም ልጅዋን ጠርቶ ወደ አጵሎን ሒድ ወደእኔም ይመጣ ዘንድ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ስም እዘዘው አለው፡፡ ያን ጊዜ ያ ልጅ ድኖ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዳዘዘው ወደ ጣዖቱ ቦታ ሒዶ አዘዘው፡፡ በጣዖቱ ያደረ ያ ርኵስ መንፈስም ከማደሪያው ወጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አለበት መጥቶ እኔ ሰውን ሁሉ የማስት እንጂ አምላክ አይደለሁም ብሎ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አመነ፡፡ ቅዱሱም ትውጠው ዘንድ ምድርን አዘዛትና ወዲያውኑ ዋጠችው ጣዖታቱንም ከአገልጋዮቻቸው ጋራ አጠፋቸው ንጉሡም ከወገኖቹ ጋር አፈረ፡፡ ብስጭትና ቁጣንም እንደተመላ ወደ ንግሥት ሚስቱ ዘንድ ገባ፡፡ እርሷም አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነውና ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አላልኩህምን አለችው፡፡ ይህንንም ከእርስዋ ሰምቶ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጣ ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ እምነት የከበረ ጊዮርጊስ እንደአስገባት አወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ከከተማ ውጭ እንዲጐትቷትና በመጋዝም እንዲሰነጥቋት አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች፡፡ በዚያም ጊዜ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥራ ነገሥታቱ ሁሉም ደነገጡ ኀፍረት ደግሞ እንዳይጨምርባቸው ከእርሱም እንዲአርፍ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ እንዲጽፍ ንጉሥ ዱድያኖስን መከሩት፡፡

ከዚህ በኋላ ይህ አባት እለእስክንድሮስ ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ በመንበረ ሢመቱ ላይ ተቀመጠ አርዮስንም ከወገኖቹ ጋራ አውግዞ አሳደደው። የሀገር ታላላቆችም ከሕዝቡ መጡ ከውግዙቱ እንዲፈረታውም ለመኑት። በውግዘት ላይ ውግዘትን እንዲጨምር እንጂ እንዳይፈታ አባ ጴጥሮስ እንዳዘዘው ነገራቸው። ከዚህ በኋላ አርዮስ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሒዶ በግፍ አወገዘኝ ብሎ እለእስክንድሮስን ከሰሰው። ስለዚህም ንጉሡ ሦስት መቶ አሥራ ስምንት የከበሩ አባቶችን በኒቅያ ከተማ ሰበሰበ፡፡ ይህም አባት እለእስክንድሮስ ተመርጦ ለጉባኤው ሊቀ መንበር ሆነ አትናቴዎስም ጸሐፊ ነበር። አርዮስንም ተከራክረው ክህደቱን ግልጽ አደረጉ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከአባቱ ከአብ ጋራ ከሕይወቱ መንፈስ ቅዱስም ጋራ በመለኮቱ ትክክል እንደሆነ አስረዱት። ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። በአንድ ቃልም ጸሎተ ሃይማኖትን ከአባቶች ጋራ ሠሩልን ደግሞ በእርሳቸው ቤተ ክርስቲያን ለዘላለም የምትመራባቸው ሃያ ቀኖናን ሠርተው ወሰኑ። ከዚህ በኋላም ይህ አባት እለእስክንድሮስ ወደ መንበረ ሢመቱ ከድል ጋራ ተመለሰ። በበጎ አጠባበቅም መንጋውን ጠበቀ በወንጌላዊ ማርቆስ መንበርም አሥራ ሰባት ዓመት ኖሮ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ማርቆስ_ሐዲስ በዚህችም ቀን የሐዲስ ማርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፡፡ እርሱም በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች አርባ ዘጠነኛ ነው ። ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ነው እርሱም በሥራው ሁሉ ቅድስናውን ጠብቆ ኖረ የተማረም ዐዋቂ ሆነ ለወንጌላዊ ማርቆስም በስም ሁለተኛ ነው ። አባ ዮሐንስም ዲቁና ሾመው እጅግ መልካም ካህን ሆነ መጻሕፍትን በሚያነብ ጊዜ በአንደበቱ ቅልጥፍና በነገሩ ጣዕም የሚሰሙት ሁሉ ደስ የሚላቸው ሆኑ ። ከዚያም አባ ዮሐንስ ከእርሱ ጋራ አኖረው በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው ያለ እርሱም ምክር አባ ዮሐንስ ምንም ምን አይሠራም ። ከዚህ በኋላ በአባ መቃርስ ገዳም የምንኲስና ልብስ አለበሰው በዚያች የምንኵስና ልብስ በለበሰባትም ቀን ከቅዱሳን አረጋውያን አንድ ጻድቅ ሰው መጥቶ በእርሱ ላይ እንዲህ ብሎ በሕዝብ ፊት ይህ ስሙ ማርቆስ የሚባል ዲያቆን በአባቱ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ሊቀመጥ አለው ብሎ ትንቢት ተናገረለት ። የአባ ዮሐንስም የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ አባ ማርቆስን ሊቀ ጵጵስና እንዲሾሙት ኤጲስቆጶሳቱን አዘዛቸው በእርሱ መሾምም ደስ አላቸው ። ከአባ ዮሐንስ ዕረፍት በኋላም ያለ ፈቃዱ ሾሙት እርሱ ግን ከእርሳቸው ሸሽቶ ወደ አስቄጥስ ሔደ ሰዎችንም ልከው አሥረው ወደ መንበረ ሢመቱ አመጡት ። ከዚህ በኋላም ጸጥ ብሎ ስለ አብያተ ክርስቲያን የሚያስብ ሆኖ የፈረሰውን አነፀ ጠገነ፡፡ በዘመኑም የመናፍቃንን ጠባይ ከሕዝቡ ውስጥ አስወገደ ይኸውም በግብጽ አገር የተገለጡ ለብቻቸውም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የሚኖሩ ናቸው እርሱም አስተምሮ መክሮ መልሶ ከመንጋዎቹ ጋራ አንድ አደረጋቸው። እግዚአብሔርም በዚህ አባት እጅ ድውያንን በመፈወስ አጋንንትን በማስወጣት ብዙ ድንቆች ምልክቶችን ገለጠላቸው። ከእርሳቸውም አንዱን አስተውል አንተ ያለ ፍርሀት በድፍረት ሥጋውንና ደሙን የምትቀበል ባትሆን ይህ ባላገኘህም ነበር ከእንግዲህ ከክፉ ሥራና ከአንደበትህ ከሚወጣ ከከንቱ ነገርም ሰውነትህን ጠብቅ አለው። በዘመኑም በምዕራብ ያሉ እስላሞች ይሸጡአቸው ዘንድ ብዙ ክርስቲያኖችን ከሮም ግዛት ውስጥ ማርከው ወደ እስክንድርያ አመጡአቸው ይህም አባት እጅግ አዘነ ከየገዳማቱና ከምእመናን ብዙ ገንዘብ ለምኖ ከእስላሞች እጅ በሠላሳ ሽህ የወርቅ ዲናር ዋጃቸው የነፃነትም ደብዳቤ ጽፎ ነፃ አወጣቸው ። እንዲህም አላቸው ወደ አገሩ መመለስ የሚሻ እኔ ስንቅ ሰጥቼ አሰናብተዋለሁ ከእኔ ጋራ መኖር የሚሻም ካለ እኔ እጠብቀዋለሁ አላቸው። የተመለሱ አሉ ስንቅ ሰጥቶም ያሰናበታቸው አሉ ከእርሱ ዘንድ የቀሩትንም ጠበቃቸው አጋባቸውም። ከዚህ በኋላ ስለ መድኃኒታችን ቤተ ክርስቲያን አሰበ አደሳትም ሰይጣንም በሀገር ውስጥ ሁከት አስነሥቶ በእሳት አቃጠላት ይህም አባት መልሶ ዳግመኛ አደሳት። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ ጥቂት ታመመ በፋሲካ በዓል በእሑድ ቀንም ወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ተገለጠለት ለሚወዱት እግዚአብሔር ስለ አዘጋጀው ተድላ ደስታ ነገረውና ሥጋውንና ደሙን ከተቀበልክ በኋላ ታርፋለህ አለው። በነቃ ጊዜም እንዴት እንዳየ ከእርሱ ዘንድ ላሉ ኤጲስቆጶሳት ነገራቸው። ከዚያም የቅዳሴውን ሥርዓት ጀምሮ ቀድሶ ሥጋውን ደሙን ተቀበለ በዚያን ጊዜም አረፈ የሹመቱም ዘመን ሃያ ዓመት ሆነ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሚካኤል_ዘእስክንድርያ በዚህችም ቀን የከበረ አባት አባ ሚካኤል የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ ሦስተኛ ነው ። ይህም ቅዱስ ጻድቅ መንኲሶ በአስቄጥስ በቅዱስ ዮሐንስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ ተሾመ ከዚያም ያለ ፈቃዱ ወስደው በግድ ሊቀ ጵጵስና በእስክንድርያ አገር ላይ ኅዳር ሃያ አራት ቀን ሾሙት ። በሊቀ ጵጵስናውም ሥራ ተጠምዶ የሚጋደል ሆነ እንደ ሐዋርያትም አጠባበቅ መንጋውን ጠበቀ ። ታላቁ ጾምም በደረሰ ጊዜ ወደ አስቄጥስ በዚያ ሊጾም ወጣ ከመሾሙ በፊት በዚያ ገዳም ውስጥ በብሕትውና ሁኖ መጠመዱንና የቀድሞ መጋደሉን አሰበ ። ወደ ጌታችንም እንዲህ ብሎ ለመነ አቤቱ እኔ በብቸኛነት መኖርን እንደምሻ አንተ ታውቃለህ ለዚች ለተሾምኩባትም ሹመት ችሎታ የለኝምና የምትገባኝም አይደለችምና በይቅርታህም ብዛት ነፍሴን ወስደህ ከዚህ ድካም ታሳርፈኝ ዘንድ እለምንሃለሁ ጌታም ልመናውን ተቀበለ ከፋሲካ በዓል በኋላም በፍቅር አንድነት አረፈ፡፡ የሹመቱም ዘመን ሁለት ዓመት ከአምስት ወር ነው። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_22 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊው ጻድቅና ሐዋርያ #ቅዱስ_ተክለ_ሃይማኖት በዚህች ቀን ከኢትዮዽያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት ተባርከዋል፣ የከበረ #አባት_ይስሐቅ አረፈ፣ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ የሆነ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ አረፈ፣ #የሐዲስ_ማርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣ የከበረ አባት #አባ_ሚካኤል የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ሚያዝያ ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊው ጻድቅና ሐዋርያ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት በዚህች ቀን ከኢትዮዽያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት ተባርከዋል:: ጻድቁ ምድረ እሥራኤል የገቡት በየመንገዱ መንፈሳዊ ዘርን እየዘሩ: እያስተማሩና እያሳመኑ ነበር:: የወቅቱ ሊቀ ዻዻሳት አባ ሚካኤል ጋርም ተገናኝተው ቡራኬን ተሰጣጥተዋል:: ዋናው ጉዳይ ግን ከዚህ በሁዋላ ነው:: ጻድቁ እመቤታችንና ጌታችን ከጽንሰታቸው እስከ ዕርገታቸው የረገጧቸውን ቦታዎች ሲመለከቱ በፍጹም ተደሞ እንባቸው ይፈስ ነበር:: ምክንያቱም እግዚአብሔር ስላበቃቸው ተክለ ሃይማኖት የሚያዩት ቦታውን አልነበረም:: በገሃድ በቤተ መቅደስ ብስራቱን፣ በቤተ ልሔም ልደቱን፣ በቤተ ዮሴፍ ግዝረቱን፣ በፈለገ ዮርዳኖስ ጥምቀቱን፣ በቤተ አልዓዛር ተአምራቱን ይመለከቱ ነበር:: የጉብኝታቸው የመጨረሻ ክፍል ወደ ሆነው ቀራንዮ ደርሰው ጌታቸውን እንደ ተሰቀለ ሆኖ ቢመለከቱት ከዓይናቸው ይፈስ የነበረው ቁጡ እንባ መልኩን ቀየረና ዓይናቸው ጠፋ:: በዚያች ቅጽበት ስም አጠራሯ የከበረ እመቤታችን ድንግል ማርያም ፈጥና ደርሳ ተክልየን ወደ ሰማይ አሳረገቻቸው:: በዚያም የብርሃን ዐይን ተቀብለው፣ 6 ክንፍ አብቅለው፣ የወርቅ ካባ ላንቃ ለብሰው፣ ማዕጠንተ ወርቁን ይዘው፣ ከ24ቱ ካህናተ ሰማይም ተደምረው፣ ሥላሴን በአንድነቱና ሦስትነቱ ተመልክተው "ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ ይደሉ" ብለው መንበረ ጸባኦትን አጥነው ወደ መሬት ተመልሰዋል:: ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባት_ይስሐቅ ዳግመኛም በዚህች ቀን ከግብጽ ደቡብ ከእብክ አውራጃ ከሆሪን ከተማ የከበረ አባት ይስሐቅ አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሶስና ነው ታናሽም ሆኖ ሳለ እናቱ ሙታብቻውን ያለእናት አባቱ እያሳደገው ኖረ። ጥቂት በአደገም ጊዜ የአባቱን በጎች የሚጠብቅ ሆነ አባቱም ሌላ ሚስት አገባ በዚያ ወራትም ታላቅ ረኃብ ሆነ የአባቱም ሚስት ትጠላው ነበረ ከጥቂትም በቀር እንጀራ አትሰጠውም ያንኑም ሁልጊዜ ለእረኞች ሰጥቶ እርሱ ግን እሰከምሽት ይፈጸማል። ምሳውን ለእረኞች እንደሚሰጥና ሁልጊዜ እስከምሽት እንደሚጾም አባቱ ሰምቶ ዕውነት እንደሆነ ሊያይ ወደርሱ ሔደ ። ቅዱሱም ሕፃን የአባቱን መምጣት ዐውቆ በልብሱ ሦስት ጭቃ አድበልብሎ አሠረ እንደ ታሠረ በሚያየው ጊዜ ለአባቱ አምባሻ እንዲመሰለው ብሎ አባቱም በመጣ ጊዜ የልጁን ልብስ ፈትቶ አየ አምባሻም ሁነው አገኛቸው። የነገረውንም ሰው ምግቡን ለእረኞች ከሰጠ በዛሬዪቱ ቀን ይህ አምባሻ ከወዴት ተገኘለት ብሎ ጠየቀው እርሱም በእውነት ሰጥቷል አለ ሌሎችም ብዙዎች መጥተው በዚህ ነገር ምስክሮች ሆኑ አባቱም አደነቀ እግዚአብሔርንም አመሰገነ። ይህም በአደገ ጊዜ አባ ኤልያስ ወደሚባል ሰው ሔዶ መንኲሶ በዚያ እየተጋደለ ብዙ ዓመታት ኖረ። አባ ኤልያስም በአረፈ ጊዜ በርኑግ ወደሚባል ገዳም ሔደ ስሙ ዘካርያስ ከሚባል አረጋዊ ዘንድ በታላቅ ገድል ተጠምዶ ኖረ። አባቱም ያገኘው ዘንድ በሀገሮች ሁሉ ይዞር ነበረ በዚህ በበርኑግ ገዳምም በአገኘው ጊዜ ከእርሱ ጋራ እንዲመለስ አባቱ ለመነው አይሆንም አለ አባ ዘካርያስም ከአባቱ ጋራ ይሔድ ዘንድ እስከ ሚዐርፍም ከእርሱ ዘንድ እንዲኖር አዘዘው ይህ ቅዱስም ከአባቱ ጋራ ሔዶ እስከሚዐርፍ ድረስ ከእርሱ ዘንድ ኖረ። አባቱም በአረፈ ጊዜ አባቱ የተወውን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ ከከተማውም ጥቂት ራቅ ብሎ ለራሱ ታናሽ ማደሪያ ሠራ በሰላም እስከ ሚዐርፍባት ቀን ድረስ ያለ ማቋረጥ በበጎ ገድል በጾም በጸሎት በስግደት ኖረ በአረፈ ጊዜም በመልካም ቦታ አኖሩት ከዚያም ተሠወረ። ከብዙ ዘመናትም በኋላ እግዚአብሔር ሊገልጠው ወዶ በመቃብሩ ላይ መብራት ሲበራ እህል ለሚዐጭዱ ሰዎች ሦስት ቀን ያህል ታየ ሊያዩትም ወደቦታው ሲደርሱ ያ መብራት ከእርሳቸው ይሠወራል በሁሉ ዘንድ እስቲሰማም እንዲህ ሁኖ ኖረ። ከዚህም በኋላ በመቃብሩ ላይ እያበራ ያ መብራት ደግሞ ታያቸው ሥጋውም በዚያ እንዳለ ሁለተኛ በሕልም ነገራቸው ምእመናንም አክብረው በግመል ጭነው ወደ ሀገሩ መካከል ወደ ሆሪን ወሰዱት ነስሪን ከሚባል አገር መካከል ሲደርሱ ግመሉ በዚያ ተንበረከከ እንዲነሣም መቱት መነሣትንም እምቢ አለ መኖሪያው በዚያ ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ ዐወቁ። በዚያም በስሙ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ሥጋውን በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ_ሊቅ በዚህችም ቀን የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳትም ዐሥራ ዘጠነኛ የሆነ እለእስክንድሮስ አረፈ። ስለርሱም ሐዋርያዊ አባት አትናቴዎስ እንዲህ አለ አባቴ እለእስክንድሮስ ተቀምጦ ወንጌልን አያነብም ቁሞ ያነባል እንጂ ከርሱ ጋራም ብርሃን አለ። ሁለተኛም ስለርሱ ሲናገር ወደርሱ እመምኔቶች መጥተው በእኛ ዘንድ ሰባት ሰባት ቀን የሚጾሙ ደናግል አሉ ። በእጅዎቻቸውም ምንም ምን ሥራ አይሠሩም ብለው ነገሩት ። እርሱም እኅቶቼ ሆይ እኔ ሁለት ቀን እንኳ ከቶ አልጾምኩም ፀሐይ እስኪገባም ቆይቼ አልበላሁም በልክ እበላለሁ በልክም እጾናለሁ በልክ በመጠንም እሠራለሁ በልክ ይበሉ ዘንድ በልክም ይጾሙ ዘንድ በልክም ሥራ ይሠሩ ዘንድ ንጉሩአቸው በበጎ ሥራ ሁሉ ይሰለፉ አለ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ደጎች ምእመናን ናቸው እርሱም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ሁኖ ከታናሽነቱ ጀምሮ በውስጥዋ አደገ ። አባ መክሲሞስ አናጉንስጢስነት አባ ቴዎናስ ዲቁና ተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስም ቅስና ሹመውታልና እርሱም ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ድንግል ነው። አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ በግዞት ቤት ሳለ ይህ እለእስክንድሮስና አኪላስ ከውግዘቱ ይፈታው ዘንድ ስለ አርዮስ ወደርሱ ገብተው ለመኑት ስለርሱ አባ ጴጥሮስን ይማልዱለት ዘንድ ሁለቱን ለምኖአቸዋልና። አባት ጴጥሮስ ግን በውግዘት ላይ ውግዘትን ጨመረበት እንዲህም ብሎ ነገራቸው የክብር ባለቤት ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደደ ልብስ ለብሶ ተገለጸልኝ ልብሴን አርዮስ ቀደዳት አለኝ። ይህም የባሕርይ አንድነቴን ለያት ማለት ነው ውግዘቱንም እንድጨምርበት እርሱ አዘዘኝ። ደግሞ እንዲህ ገለጠላቸው አኪላስ ሊቀ ጵጵስና እንዲሾም ከርሱ በኋላም እለእስክንድሮስ እንደሚሾም አርዮስን እንዳይቀበሉት በምንም ሥራው እንዳይተባበሩት አዘዛቸው። አባ ጴጥሮስም ምስክርነቱን በፈጸመ ጊዜ አኪላስ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ፡፡ የአባት ጴጥሮስንም ትእዛዝ ተላልፎ አርዮስን ከውግዘቱ ፈታው። ቅስናም ሾመው ስለዚህም አኪላስ በመንበረ ሢመቱ ያለ ስድስት ወር አልኖረም በድንገት ሞተ።

ተገለጠለትና ‹‹ወደ ደብርህ ሂድ›› አለውና ደብረ አንጎት አደረሰው፡፡ በዚያም አባ በትረ ማርያምን አገኛቸው፡፡ እርሳቸውም ወደ ደብሩ እንዲመለስ ስለመከሩት ወደ ደብረ ሊባኖስ ተጉዞ ከአባ ጴጥሮስ ጋር በድጋሚ ተገናኘ፡፡ እርሳቸውም ‹‹ከእንግዲህስ ወዲህ ወዲያ አትበል፣ የሞቴም ጊዜ ደርሷልና አንተ በመንበሬ ተተክተህ ትሾማለህ፡፡ እንደእኔም ለብዙዎች አባት ትሆናለህ ነገር ግን መነኮሳት በከንቱ ወንጅለውህ ንጉሡ ያሥርሃል፣ ትሰደዳለህም›› ብለው ትንቢት ነገሩት፡፡ አባ ጴጥሮስም ባረፈ በ40ኛው ቀን መነኮሳቱ ተሰብስበው ዕጣ ቢጥሉ ለአባ ዕንባቆም ስለወጣ በእጨጌነት ሾሙት፡፡ ወዲያውም ሴቶችና ወንዶች መነኮሳትን በመልክ እንኳን እንዳይተያዩ በማድረግ እያስተማረ አገልግሎቱን ሲያከናውን ፈቃደ ሥጋቸውን ማሸነፍ የተሣናቸው መነኮሳት ‹‹ክብርህን ያሳንሳል፣ ስለአንተም አይጸልይም፣ እንዲያውም ‹ንጉሡ በአሳርና በመከራ ይሞታል› እያሉ ይናገራሉ›› ብለው በሐሰት ለንጉሡ በመንገር አጣሏቸው፡፡ ክፉዎችም በወጠኑት ሴራ ጻድቁ በንጉሡ ፊት ለፍርድ ቀረቡና ብዙዎቹ ‹‹ይገደሉ›› ብለው ፈረዱባቸው፡፡ ነገር ግን የዐፄ ልብነ ድንግል እንደራሴ ‹‹ከምንገድላቸው አስረን በግዞት ጉንጭ ወደሚባለው ቦታ እንውሰዳቸውና በዚያ ከሞቱ ይሙቱ›› ብሎ ሌላ ሀሳብ አቀረበ፡፡ ንጉሡም በዚህ ተስማምተው አቡነ ዕንባቆምን እጅና እግራቸውን አስረው እየደበደቡ አጋዟቸው፡፡ አቡነ ዕንባቆምም በግዞት ሆነው ሳለ ውኃ ሳይቀምሱ አንድ ዓመት ተቀመጡ፡፡ ከዚህም በኋላ እስከጎጃም ድረስ እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሰበኩ፡፡ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንም አነጹ፡፡ እስከ ምድረ ቢዘን ድረስም ወረዱ፡፡ በዚህም ጊዜ ግራኝ አህመድ ተነሥቶ ክርስቲያኖችን በግፍ መግደል አብያተ ክርስቲያናትን ማቃጠል ጀመረ፡፡ አቡነ ዕንባቆም ለግራኝ በዐረብኛ ቋንቋ ደብዳቤ ጻፉለት፡፡ ‹‹ክርስቲያኖችን አትግደሉ ተብሎ በቁርአን ተጽፎ እያለ አንተ ግን ለምን ትገድላለህ? አብያተ ክርስቲያናትንስ ለምን ታቃጥላለህ?›› ብለው ጻፉለት፡፡ ግራኝ አህመድም ደብዳቤአቸውን ካነበበ በኋላ ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ክርስቲያኖችን እንዳልገድል ቤተ ክርስቲያኖችንም እዳላቃጥል ከሚወጉኝ በቀር በክርስቲያን ላይ ክፉ እንዳልሠራ በአላህና ከሚስቶቹ በሦስቱ ጠለቅ ማልሁ›› ብሎ ተናገረ፡፡ ለአቡነ ዕንባቆምም ‹‹የክርስቲያን ሃይማኖት ከቁርአን የሚለይበትን መንገድ ትገልጽልኛለህና መጥተህ እየኝ›› ብሎ ልኮባቸው ነበር ነገር ግን አቡነ ዕንባቆም መንፈስ ቅዱስ ሳይፈቅድላቸው ቀርቶ ሳያገኙት ቀሩ፡፡ ዐፄ ልብነ ድንግል ሞቶ ልጁ ገላውዴዎስ ሲተካ አቡነ ዕንባቆምን ወደ እርሱ ይመጡ ዘንድ መልእክተኛ ላከባቸውና ሲመጡ ‹‹ስለ አህመድ ግራኝ ምን ባደረግ ይሻላል?›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም ‹‹የሥልጣንህ ሰይፍ ከአንገቱ ላይ ሆናለች፡፡ እኔም ወደ ጎጃም እሄዳለሁ፣ እከተልሃለሁ፣ በደንቢያ ላይም እንገናኛለን፡፡ ሐነፋውያን (የግራኝ ዘሮች) በእጅህ ይጠፋሉ፡፡ አንተም በመጨረሻ በእነርሱ እጅ በሰማዕትነት ታልፋለህ›› ብለው ይመጣ ዘንድ ያለውን ሁሉ በትንቢት ነገሩት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ዐፄ ገላውዴዎስ ግራኝን ካጠፋው በኋላ በሌላ ጊዜ የግራኝ ተከታይ ኢማም ኑር ገላውዴዎስን ገደለው፡፡ የንጉሡ እኅት ወለተ ጊዮርጊስም ወደ አቡነ ዕንባቆም መጥታ ያመነኩሳት ዘንድ ስለለመነችው ሥርዓተ ምንኩናን ፈጸመላት፡፡ ከገላውዴዎስ ቀጥሎ ዐፄ ሚናስ ሲነግስ አቡነ ዕንባቆምን መጥተው እንዲባርኩት ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም ከባረኩት በኋላ ወደ ደብረ ሊባኖስ እንዲመለሱ ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም እምቢ ቢሉትም ከብዙ ልመና በኋላ እሺ ብለውት ወደ ደብረ ሊባኖስ ሲሄዱ ልጆቻቸው በደስታ ተቀበሏቸው፡፡ እርሳቸውም እያስተማሩና መልካም አገልግሎታቸውን እየፈጸሙ አንድ ዓመት ከቆዩ በኋላ በ137 ዓመታቸው ሚያዝያ 21 ቀን 1553 ዓ.ም በሰላም ዐረፉ፡፡ በአባቶቻቸውም መቃር ተቀበሩ፡፡ ዐፄ ሠርፀ ድንግልም በ1580 ዓ.ም የአቡነ ዕንባቆምን ገድል አጻፈላቸው፡፡ ይህ ታሪካቸውም ከዚሁ ገድላቸው ላይ የተቀዳ መሆኑን የ1990 ዓ.ም የካቲት/መጋቢት እትም ሐመር ትገልጻለች፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_21 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ አንድ በዚህች ቀን የከበረ #አባት_ብሩታዎስ አረፈ፣ ዕለት የሐዋርያት አምሳል ሃይማኖትን የሚሰብክ #ዕጨጌ_ዕንባቆም መታሰቢያው ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቡሩታዎስ_ሐዋርያ ሚያዝያ ሃያ አንድ በዚህች ቀን የከበረ አባት ብሩታዎስ አረፈ፡፡ ይህም አባት የአቴና አገር የሆነ ከምሁራን ጥበበኞች አንዱ ነው እርሱም ደግሞ ደራስያን ከሆኑ ከአረጋውያን መምህራን ጋራ የተቆጠረ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስንም ተገኝቶት ስለ ቀናች ሃይማኖት ተከራከረው። የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት የቀናች እንደሆነች ተረድቶ አመነ በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እጅ ተጠምቆ የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዓት ተማረ። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጳውሎስ በአቴና አገር ቅስና ሾመው። በታላቂቱ አገር በአቴና የመምህራን አለቃ ከሆነ ዘመደ ላሕም አብሮባ ከተባለ ከከበረ ዲዮናስዮስ ጋራ ተገናኘ። እርሱም የክብር ባለቤት ስለሆነ ጌታ ኢየሱስ ሃይማኖት ብዙ ገለጠለት ከውስጡ ሥውር የሆነበትንም ተረጐመለት እጅግም ዐዋቂ ሆነ። ይህም አባት አምላክን የወለደች እመቤታችን የከበረች ድንግል ማርያም በዐረፈችበት ቀን ደርሶ በሐዋርያት መካከልም ቆመ በደረሰው ማኅሌትና ዝማሬ ጣዕም ባለው በመሰንቆ በዜማ ድምጽም አጽናናቸው። ከአይሁድና ከአሕዛብም ብዙዎቹን መልሶ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታ ክርስቶስ እምነት አስገባቸው። በተሰጠችውም ጸጋ ነግዶ ታላቅ ትርፍ አስገኘ። ሐዋርያትም ኤጲስቆጶስነት ሊሾሙት በፈለጉ ጊዜ ጌቶቼ ይቅርታ አድርጉልኝ እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት አልበቃሁምና የቅስናንም አገልግሎት ልፈጽም አልቻልኩምና ተውኝ ብሎ ማለዳቸው። በዕውቀቱና በሥራው ሰማያዊ ሀብትን ተቀብሎ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር ሔደ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዕንባቆም_ጻድቅ_ዘደብረ_ሊባኖስ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የሐዋርያት አምሳል ሃይማኖትን የሚሰብክ ዕጨጌ ዕንባቆም መታሰቢያው ነው፡፡ እርሱም በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባው ድረስ እግዚአብሔር ከእስልምና እምነት መርጦ ያመጣውና በደብረ ሊባኖስ ገዳም በዕጨጌነት ተሹሞ ቤተ ክርስቲያንን ያገለገለ ብዙ ሰማዕትነትንም የተቀበለ ታላቅ አባት ነው፡፡ አባ ዕንባቆም ዕጨጌ ዘደብረ ሊባኖስ፡- የሐዋርያት አምሳያቸው የሆኑ ሃይማኖትን የሚሰብኩ ዕጨጌ ዕንባቆም ሚያዝያ 21 ዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው መሆኑን ስንክሳሩ ይጠቅሳል፡፡ እርሳቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባቸው ድረስ እግዚአብሔር ከእስልምና እምነት መርጦ ያመጣቸው ታላቅ ሐዋርያ ናቸው፡፡ የመናዊው እጨጌ ዕንባቆም በዐረብ ምድር በየመን የተወለዱ ሲሆን አስቀድመው እስላም ነበሩ በኋላ ግን መጻሕፍትን መርምረው ዕውነትን ፈልገው በማግኘት በጌታችን በክርስቶስ አምነው ተጠምቀው ከመነኮሱ በኋላ በደብረ ሊባኖስ በአቡተ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ተሾመው እስከማገለግል የደረሱ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ አባ ዕንባቆም በ1416 ዓ.ም አካባቢ የመን ውስጥ ነው የተወለዱ፡፡ አባታቸው እስላም ሲሆን እናታቸው ግን አይሁዳዊት ነበረች፡፡ አባታቸው በሕጋቸው መሠረት ሁለት ሚስት አግብቶ ከአንደኛዋ 7 ልጆችን ሲወልድ ከአንዷ ደግሞ 2 ልጆችን ወልዷል፡፡ ከሁለቱ አንዱ አባ ዕንባቆም ነበር፡፡ እርሱም ቁርአንን እና ልዩ ልዩ ቋንቋዎችን በሚገባ እየተማረ አደገ፡፡ ለእስልምና ሃይማኖቱ ቀናተኛ የነበረው ዕንባቆም የክርስትና ስም ሲነሳበት አይወድም ነበር፡፡ 114ቱንም የቁርአን ምዕራፎች (ሱራዎች) በቃሉ ይዞ ቀን ከሌሊት ይጸልይባቸው ነበር፡፡ አንድ ቀን በቁርአን ላይ ስለመሞትና መነሣት የተጻፈውን ሲያነብ ኅሊናው ታወከ፡፡ ወዲያውም ወደ ቁርአን ሊቅ ዘንድ ሄዶ ትርጉሙን ጠየቀ፡፡ ነገር ግን የተሰጠው ምላሽ ‹‹ለምን አነበብከው?›› የሚል ነበር፡፡ (በነገራችን ላይ ቁርአኑን ከዐረብኛ ቋንቋ ውጭ ወደ ሌሎች ቋንቋዎች መተርጎም እንደሌለበትና በእርሱ ላይ ስለተጻፉት ነገሮች ጥያቄ መጠየቅ ክልክል እንደሆነ ቁርአኑ ለራሱ ከለላ የሰጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡) ዕንባቆምም ለጥያቄው መልስ በማጣቱ ይልቁንም ስለጠየቀ በቁጣ ስለተገሠጸ በእስልምና ላይ የነበረው ፍጹም እምነት ወደ ጥርጣሬ ተቀየረ፡፡ በዚያም ዘመን የኢትዮጵያ ንጉሥና የአዳል ንጉሥ ጦርነት ገጥመው አዳሎች አሸነፉና ንጉሡ 51 የኢትዮጵያ ምርኮኞችን ለአባ ዕንባቆም አባት ላከለት፡፡ ምርኮኞቹም ዕንባቆም በሃይማኖት ምክንያት ከወገኖቹ ጋር አለመስማማቱን አይተው ወደ ኢትዮጵያ እንዲሄድ መከሩት፡፡ እርሱም አብሯቸው በመካ በኩል ዳህላክን አቋርጦ ከነጋዴዎች ጋር ወደ ኢትዮጵያ ወደብ ደረሰ፡፡ ዕንባቆምም መጀመሪያ ካገኘውና አብሮት ከመጣው ወሰንጌ ጋር በመርሐ ቤቴ ተቀመጠ፡፡ በዚያም ትምህርተ ሃይማኖትን መማር ጀመረ፡፡ በግእዝ ንባብ የጀመረውም ትምህርት ተአምረ ማርያም ላይ ሲደርስ የእመቤታችን ፍቅሯ ስላደረበት ወደ ክርስትናው ሃይማኖት ይበልጥ ተሳበ፡፡ የዕንባቆም የዘወትር ጸሎት ‹‹ወደ ዕውነተኛው ሃይማኖት ምራኝ›› የሚል ሆነ፡፡ አንድ ቀንም በክረምት ወደ ዠማ ወንዝ ወርዶ ሳለ በአንድ ጎልማሳ የተመሰለ ቅዱስ ተገለጠለትና የውኃውን ሙላት በተአምራት አሻግሮ ‹‹በዚህች መንገድ ሂድ›› ብሎ ካሳየው በኋላ ተሰወረው፡፡ ዕንባቆምም መንገዱን ይዞ ሲጓዝ ደገኛው አባ ጴጥሮስ ካለበት ገዳም ደረሰ፡፡ በገዳሙም ማረፊያ ሰጥተውት በዚያ ተቀመጠና ብዙ ቅዱሳት መጻሕፍትን ተማረ፡፡ ከዚህም በኋላ መጠመቅ እንደሚፈልግ ለአባ ጴጥሮስ ነገራቸውና አጥምቀው ስመ ጥቀቱን ዕንባቆም አሉት፡፡ ዳግመኛም በዚሁ ገዳም መነኮሰ፡፡ አባ ጴጥሮስም ከጳጳሱ ከአቡነ ማርቆስ በተገናኙ ጊዜ ስለ አባ ዕንባቆም ነገሯቸው፡፡ ጳጳሱም አባ ዕንባቆምን አስጠርተው በዐረብኛ ቋንቋ የተጻፈን ወንጌል እንዲያነብላቸው ሰጡት፡፡ እርሱም በድንብ አነበበላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ዲቁና ሰጡትና በቤታቸው አስቀመጡት፡፡ በዚህም ጊዜ ለጳጳሱ የሶርያን፣ የቅብጥን፣ የዕብራይስጥንና የአርመንን ቋንቋዎች ከነጽሕፈታቸው አስተማራቸው፡፡ ጳጳሱም ቆይተው ቅስና ሾሙት፡፡ አባ ዕንባቆም አንዱን የካቶሊክ እምነት ተከታይ ተከራክሮ ሲያሳምነው ጳጳሱ ተመልክተው በዚህ ደስ ተሰኝተው ከአንግብጦን ወረዳዎች ጢቆ በምትባል አገር ላይ ሾመው ላኩት፡፡ እርሱም በዚያ በእመቤታችን ስም የተዋበች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ስሟን ቤተልሔም አላት፡፡ ዜናውም በሁሉ ዘንድ መሰማት ጀመረ፡፡ የአባ ዕንባቆም የዘወትር ጸሎት መዝሙረ ዳዊት፣ መኅልየ ሰሎሞን፣ ወንጌለ ዮሐንስ፣ ውዳሴ ማርያምና አርጋኖን ነበሩ፡፡ የደብረ ሊባኖስ ገዳም መነኮሳት ራእይ ተገልጦላቸው አባ ዕንባቆምን ‹‹የደብረ ሊባኖስ አለቃ ትሆናለህ ነገር ግን መነኮሳቱ ከንጉሡ ጋር ያጣሉሃል›› ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ከዚህ ሹመትና የሰይጣን ፈተና ሸሽቶ ወደ ምድረ ግብጦን ሄዶ የሐብላሽ በምትባል ገዳም ተቀመጠ፡፡ ‹‹አቤቱ የገዳም አስተዳዳሪ ከመሆን ጠብቀኝ›› እያለ በመጸለይ በዚህች ገዳም 3 ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን የትሩፋቱ ዜና በእንደግብጦንና በዳሞት ተሰማ፡፡ ወደ ላሊበላም ተጉዞ ከዋልድባ መነኮሳት ጋር በመገናኘት ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ ቁርጥ አሳብ አድርጎ ሳለ መነኮሳቱ ‹‹ይህ አይሰምርልህምና ወደ ደብርህ ተመለስ›› ብለው መከሩት፡፡ እርሱ ግን ሳይመለስ ቅጻ ወደምትባል ሥፍራ ሄዶ በአንድ ገዳም ተቀምጦ የተለያዩ ተአምራትን እያደረገ ተቀምጦ ሳለ በደዌ ተያዘ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሳለ የታዘዘ መልአክ

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_20 #ቅዱስ_በብኑዳ_ሰማዕት አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ በዚህች ቀን ደንደራ ከሚባል አገር ደግሞ እልበደራ ከሚባል አገር ቅዱስ በብኑዳ በሰማዕትነት አረፈ። ይህ ቅዱስ ለብቻው የሚኖር ዕውነተኛ ተጋዳይ ነው የእግዚአብሔር መልአክም ተገልጦለት የመቀደሻ ልብስ ለብሰህ ወርደህ ለመኰንኑ ተገለጥለት አለው። በዚያን ጊዜ መኰንኑ አርያኖስ ከመርከብ ወርዶ ወደዚያች አገር ወደብ መድረሻው ጊዜ ነበር። ይህንንም ባሕታዊ ፈልጎት አላገኘውም ነበር ። እነሆ ቅዱስ በብኑዳም በፈቃዱ መጥቶ ወደ መኰንኑ ሔዶ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን በግልጥ እኔ ክርስቲያን ነኝ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ። መኰንኑም ፈልጎ ያጣው የታወቀ ባሕታዊ መሆኑን በአወቀ ጊዜ እንዲአሠቃዩት በእግር ብረትም አሥረው ከጨለማ ቤት እንዲጥሉት አዘዘ። በዚያን ጊዜም ብርሃን ወጣ የእግዚአብሔር መልአክም ከሕማሙ ፈወሰው አበረታው አጽናናውም። በዚያችም አገር ስሙ ቄርሎስ የሚባል ምእመን ሰው ነበረ ከእርሱ ጋራም ሚስቱና ዐሥራ ሁለት ጐልማሶች ልጆቹ አሉ። እነዚህን ሁሉንም የከበረ በብኑዳ አስተማራቸው አጽናንቷቸውም ራሶቻቸውን ቆርጠዋቸው በሰማዕትነት ሙተው አክሊልን ተቀበሉ። አርያኖስም ተቆጥቶ በቅዱሱ አንገት ከባድ ደንጊያ ሰቅለው ወደ ባሕር ይጥሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ በእግዚአብሔር ኃይልም ከድንጋዩ ጋራ ዋኘ። ደግሞ ከሰሌን ዛፍ ላይ ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ ያቺም ሰሌን ዐሥራ ሁለት ዘለላን አፍርታ ለመጪው ትውልድም መታሰቢያ ሆነች። ከዚህም በኋላ የከበረች ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_19 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ቅዱስ_ስምዖን_ሰማዕት_ዘአርማንያ ሚያዝያ ዐሥራ ዘጠኝ በዚች ቀን የአርማንያ ሰው የፋርስ ኤጲስቆጶስ የከበረ ስምዖን በሰማዕትነት አረፈ ከእርሱም ጋር መቶ ሃምሳ ሰማዕታት። ይህም ቅዱስ ትከሻ ነቃይ የተባለ የሐርመዝ ልጅ በሳቦር ግዛት ውስጥ ይኖራል። ይህም ሳቦር ሌላውን ንጉሥ ድል በሚያደርግ ጊዜ አሥሮ ትክሻውን ይመዝዘዋልና ትከሻ ነቃይ ተባለ። ይህም ከሀዲ ለጣዖት እንዲሰግዱ እያስገደደ ምእመናንን በጽኑዕ ሥቃይ አሠቃያቸው። ይህም የከበረ አባ ስምዖን ለንጉሥ ሳቦር መልእክት ጽፎ ላከለት። እንዲህ የሚል የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ ደሙ የዋጃቸው ከሰው ተገዢነት ድነዋል የክብር ባለቤት የክርስቶስ ተገዢ ናቸውና። ስለዚህ ተገዢ መሆን ከተሠራው ሕግ አብዝቶ መገበርም አይገባቸውም። የሕያው እግዚአብሔርን ሕግ ለለወጡ ከሀድያን አይገዙም። ስለ እርሳቸው ደሙን በአፈሰሰ በክብር ባለቤት በክርስቶስ ስም እንዲሞቱ እነርሱ ይመርጣሉ። ንጉሥ ሳቦርም ይህን መልእክት በአነበበ ጊዜ በዚህ አባት ላይ እጅግ ተቆጣ በሁለት ሰንሰለትም አሥሮ በእሥር ቤት ጣለው በዚያም ሃይማኖታቸውን ክደው ሰማይን ያመለኩ እነርሱም በሌላ የታሠሩ ብዙ እሥረኞችን አገኘ። ይህ ቅዱስም ገሠጻቸው አስተማራቸው እነርሱም ተጸጽተው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው መሰከሩ ራሶቻቸውንም ቆረጡአቸውና የሕይወት አክሊልን ተቀበሉ። ከዚህም በኋላ ይህን አባት ወደ ምስክርነት ሸንጎ አቀረቡት ከእርሱም ጋራ መቶ ሃምሳ ሰዎች አሉ እነርሱም አንገታቸውን እስከ ቆረጡአቸውና አክሊል እስከ ተቀበሉ ድረስ ያጽናናቸው ነበር። ከእርሳቸውም አንዱ ሰይፍን ከመፍራት የተነሣ ደንግጦ ሃይማኖቱን ሊክድ ወደደ በዚያ ከቆሙት አንዱ አትደንግጥ የሰይፍ በትር ዓይንህን ከሸፈንክ ምንም አይደለም ጽና። ከሰማዕታት ጋራ ተቆጥረህ ከክብር ባለቤት ክርስቶስ ጋራ ለዘላለም ነግሠህ ትኖራለህ ብሎ አጽናናው። እንዲሁም አደረገ የሕይወት አክሊልንም ተቀበለ። ስሙ ባሴቅ የተባለ ያንን ያጥናናውን ሰው ከሰሱት ንጉሡም አስቀርቦ ምላሱን አስቆረጠው። ቆዳውንም አስገፈፈውና ነፍሱን አሳለፈ የድል አክሊልንም ተቀበለ። ከዚህ በኋላም የከበረ ስምዖንን ወደ እርሱ አቅርቦ ለአማልክት ስገድ ያለዚያ በጽኑ ሥቃይ አሠቃይሃለሁ አለው። ቅዱሱም ትእዛዙን አልሰማም ሥቃዩንም አልፈራም ያን ጊዜም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዝዞ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_18 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የቅዱስ ሱስንዮስ አገልጋይ #ቅዱስ_አውሳብዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የአባ ብሶይ ወንድም #አባ_ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አውሳብዮስ_ሰማዕት ሚያዝያ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የቅዱስ ሱስንዮስ አገልጋይ ቅዱስ አውሳብዮስ በሰማዕትነት አረፈ፡፡ የአባ ብሶይ ወንድም አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ዲዮቅልጥያኖስም ቅዱስ ሱስንዮስን በሚያሠቃየው ጊዜ ንጉሥ ሆይ አውሳብዮስ የሚባል አገልጋይ አለው፣ እርሱም በፍጹም ልቡ እንደ ጌታው ክርስቶስን ያመልከዋል፡፡ የአንተን አማልክ አያመልክም አሉት፡፡ አምጡት አለ፡፡ ወደ እርሱ በቀረበ ጊዜ ስለ ሃይማኖቱ ጠየቀው፡፡ እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ፡፡ ንጉሱም ብዙ አባበለው አማልክቶቹን ማምለክ በመተው ገሰጸው፡፡ ቅዱሱም የዕውነተኛ አምላክ የአግዚአብሔርን አምልኮ በመተው ንጉሡን መልሶ ገሰጸው፡፡ ስለዚህም ንጉሡ ቁጣን ጨመረ ሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ይህም ቅዱስ ከጌታ ከሱስንዮስ ቀድሞ የሰማዕትነትን አክሊል በመንግስተ ሰማያት ተቀበለ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ጴጥሮስ_ሰማዕት በዚችም ዕለት የአባ ብሶይ ወንድም አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ሲድራቅ የእናቱ ስም ማርያም ነው። ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ ከርሳ የምትባል የእናቱ እኅት ወስዳ ከልጅዋ ጋራ አሳደገችው። ሰባት ዓመትም በሆናችው ጊዜ ወደ መምህር ወሰደቻቸውና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሕጉንም ተማሩ በጾም በጸሎትም ሲጋደሉ ኖሩ። የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤልም ተገለጠላቸው ስለ ክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ምስክር እንደሚሆኑ ነገራቸው። ከጥቂት ወራትም በኋላ ሰይጣን ዲዮቅልጥያኖስን አስቶት ለጣዖት በሰገደ ጊዜ እሊህን ቅዱሳን ክርስቲያኖች እንደሆኑ ነገር ሠሩባቸው። የእንዴናው ገዥ አርያኖስም ወደርሱ አስቀርቦ ለጣዖት እንዲሰግዱ ግድ አላቸው እምቢ በአሉትም ጊዜ ደማቸው እስኪፈስ ከባላ ላይ ሰቅለው እንዲገርፉአቸው አዘዘ። ከጾምና ከስግደት የተነሣ ሥጋው ስለደከመ የሥቃዩ ሕማም ለጴጥሮስ ታወቀው ያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ከሕማሙ ፈወሰው። አርያኖስም አይቶ ጴጥሮስን ወደ ምሥራቅ ሀገር ወስደው በዚያ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዘዘ። አባ ብሶይም በእሥር ቤት እያለ መልአክ ነጥቆ ወደ ወንድሙ ወደ ጴጥሮስ አደረሰው፡፡ እርስ በርሳቸውም ተቃቅፈው ተሳሳሙ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም እንዲሰበስባቸው ወደ ጌታችን ጸለዩ እነሆ ወደ እርሳቸውም ከሰማይ ቃል መጣ። እንዲህ የሚል ተጋዳዮች ሆይ በሰማያት በብዙ ጉባኤ መካከል ትኖራላችሁና ሰላም ይሁንላችሁ ሥጋችሁም በምድር አይለያይም። ከዚህም በኋላ መልአክ አባ ብሶይን ወደ እሥር ቤት መለሰው። ጭፍሮችም ኃያል ድል አድራጊ አባ ጴጥሮስን ራሱን ቆረጡ ሥጋውንም በዕንጨት ላይ ሰቀሉ። አባ ብሶይም በጭልታ ይሰደው ዘንድ የእሥር ቤት ጠባቂውን ለመነው ሒዶም የአባ ጴጥሮስን ሥጋ ዋጀው በሽቱ አድርጎ ገንዞም በሥውር ቦታ ቀበረ። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_17 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_ዘብዴዎስ ሚያዝያ ዐሥራ ሰባት በዚህች ቀን የዘብዴዎስ ልጅ የወንጌላዊ ዮሐንስ ወንድም ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም በእስያ ውስጥ ከአስተማረ በኋላ ዕርቅ በተገኘባት በእውነተኛ አምላክ በጌታችን ወንጌል ሊያስተምራቸው ወደ ተበተኑ ወደ ዐሥራ ሁለቱ ነገድ ወጣ። እነርሱም አንድ አምላክን የሚአመልኩ አልነበሩም እየራሳቸው የመረጡትን የሚአስቷቸው ጣዖታትን ያመልኩ ነበረ እንጂ። ከቄሣር ሥልጣን በታች የተሾመ ኄሮድስም ሹመቱ በሚዳብር መንግሥቱ በሚያጽና ገንዘብ ብዙ ግብር እንዲገብሩ እጅ መንሻም እንዲአስገቡ አዘዘ። ያዕቆብ ግን ወደእርሳቸው በደረሰ ጊዜ በአገራቸው ቋንቋ ሰበከላቸው የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ ማወቅን እግዚአብሔር ሰጥቶት ነበርና የሚያውቀው የሰው ቋንቋ ብቻ አልነበረም የእንስሳና የአራዊት የሰማይ ወፎችንም ቋንቋ ነበረ እንጂ። በውስጣቸው በሰበከም ጊዜ የከፋ ሥራቸውን ትተው በሕያው እግዚአብሔር በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት በሆነ መንፈስ ቅዱስ ነፍሶቻቸው በእጁ ውስጥ በተያዙ በአንድ አምላክ እንዲያምኑ አዘዛቸው። እርሱም በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ የሚመጣ ነው። ዳግመኛም በማይጠፋና በማይበላሽ በሰማያት ድልብ ይሆናቸው ዘንድ ከገንዘባቸው ለችግረኞችና ለድኆች እንዲመጸውቱ አዘዛቸው። ትምህርቱንም በሰሙ ጊዜ ከክፋ ሥራቸው ተመልሰው በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብም ትምህርቱን ፈጥነው ስለተቀበሉት እጅግ ወደዳቸው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው በየአገራቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው። ዳግመኛም ከእንስሶቻቸው ከሚዘሩአቸው እህሎችና ወይን አትክልቶች ፍሬዎች ለካህናትና ለድኆች ምግብ ሊሆን ለቤተ ክርሰቲያን የመጀመርያውን መባ እንዲሰጡ አዘዛቸው። ሕዝቡም በአንድ ቃል ያዘዝከንን ሁሉ እኛ እናደርጋለን አሉት። ከዚህ በኋላ ከእንስሳት መጀመሪያ የተወለደውን ከእህሉም ቀዳምያቱንና ዓሥራትን ለቤተ ክርስቲያን አመጡ። ኄሮድስም ቅዱስ ያዕቆብ ለቤተ ክርስቲያን መባ ይሰጡ ዘንድ እንዲሚያዝ በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ጭፍራ ልኮ ወደርሱ አስመጣውና "ሕዝቡ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ምጽዋትና ለቤተ ክርስቲያን መባ እንዲሰጡ የምታዝ አንተ ነህን" አለው። "አዎን እኔ ነኝ" አለው ያን ጊዜ ኄሮድስ ተቆጥቶ ራሱ በሰይፍ አንገቱን መትቶ ቆረጠው። በኢየሩሳሌምም ሁከትና ሽብር ሆነ ደግሞ ከፋሲካ በዓል በኋላ ሊገድለው አስቦ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ወስዶ አሠረው የእግዚአብሔር መልአክም ኄሮድስን ቀሠፈው ተልቶ ተበላሽቶ ሞተ ልዑል አምላክን አላከበረውምና። የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ግን ምዕመናን ወሰዱት ገንዘው በቤተ መቅደስ ውስጥ ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የሐዋርያው የቅዱስ ያዕቆብ በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክስር ሚያዝያ_16 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ቅዱስ_አንቲቦስ ሚያዝያ ዐሥራ ስድስት በዚህች ቀን የበአርማ አገር ኤጲስቆጶስ ቅዱስ አንቲቦስ በሰማዕትነት አረፈ። እርሱም የመለኮትን ነገር ለሚናገር ለወንጌላዊው ዮሐንስ ረድኡ ነው። እርሱም ከአይሁድ ወገን በግዛቱ ውስጥ አንድ ሰው የሚታይ እስከ አልሆነ ድረስ አይሁድን ያጠፋቸውና ኢየሩሳሌምንም በአፈረሳት በአስባስያኖስ ልጅ በግማትያኖስ ዘመን ነበረ። ከእስራኤል መንግሥት ትውልድ ያላቸውንም ብዙዎችን ገደላቸው ለመንግሥቱና ለራሱ ስለ ፈራ ነው። የክብር ባለቤት ክርስቶስ አምላካቸውና ንጉሣቸው ድል አድራጊና እነርሱም ወገኖቹ እንደሆኑ ክርስቲያኖች ይናገራሉና ስለዚህ ከአማንያን ብዙዎችን ገደለ። ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሱ ሸሸ የዮሴፍ ልጅ በሮሜ ከተማ ታሥሮ ሳለ ወደ ኢየሩሳሌም ጭፍራ ልኮ የይሁዳን ተወላጆች ወደርሱ አስመጣቸው የክብር ባለቤት ስለሆነ ክርስቶስ መንግሥት በጠየቃቸው ጊዜ ክርስቶስ ሰማያዊ ንጉሥና በሰማያት የሚኖር እንደሆነ በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ ለሁሉም እንደየሥራው ሊከፍለው ዳግመኛ ይመጣ ዘንድ እንዳለው አስረዱት። ይህንንም ሰምቶ እጅግ ፈራ ክርስቲያኖችንም ማሠቃየቱን ተዋቸው። ቅዱስ አንቲቦስን ግን የክብር ባለቤት ክርስቶስን ሊአስክደው ሽቶ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው እርሱም በሥቃዩ ውስጥ በመታመን ጸና ፣ ከዚህም በኋላ ከናስ በተሠራ በላመ ፈጅ ጋን ውስጥ አድርገው ከበታቹ እሳትን አነደዱ እርሱም በውስጧ ሁኖ ስለከበረ ስሙ ምስክር ሊሆን ያደለው እግዚአብሔርን ፈጽሞ ያከብርና ያመሰግን ነበር። ከዚህም በኋላ ስሙን ለሚጠሩና መታሰቢያውን ለሚያደርጉ ከነፍስ ከሥጋ ደዌ ሁሉንም ይፈውሳቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ፈለገ። ከዚህም በኋላ ከነሐስ በተሠራው በላመ ፈጅ ውስጥ የምስክርነቱን ተጋድሎ ፈጽሞ ነፍሱን ሰጠ። በድኑንም ሲጥሉት ምእመናን አንሥተው በታላቅ ክብር ፈጽሞ እያመሰገኑ ወስደው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት። እርሱም አስቀድሞ በግዞት ቤት ሳለ ከወንጌላዊ ዮሐንስ ዘንድ የሚያጽናናውና የሚአረጋጋው ቸር ጠባቂ እረኛና ታማኝ አገልጋይ ካህን የሚለው መልእክት ወደርሱ መጣ። እንዲህም ብሎ ሁለተኛ ነገረው በሰማዕትነት እንደሚሞት አንተ ከከበሩ ሐዋርያትና ከሰማዕታት ጋራ ተቆጥረሃል። ደግሞ ከሥጋው ጣፋጭ የሽቱ ቅባት እንደሚፈስ ስለርሱ ተነገረ እርሱም መዓዛው እጅግ ጣፋጭ የሆነ በእምነት ለሚሻው ሁሉ እስከ ዛሬ ጠቃሚ የሆነ ነው በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ክርስቶስ ተንስአ ሙታን በዐቢይ ኃይል ወስልጣን አሰሮ ለሠይጣን አግአዞ ለአዳም ሠላም እምይእዜሰ ኮነ ፍሥሐ ወሰላም ።እንኳን አደረሠን አደረሳችሁ ።https://t.me/finotebirhan12