Adhanom Mitiku / አድኃኖም ምትኩ
Kanalga Telegram’da o‘tish
Ko'proq ko'rsatish
3 876
Obunachilar
+424 soatlar
+827 kunlar
+8530 kunlar
Postlar arxiv
ዛሬ ማታ 12:30 ጀምሮ እምንወዳቸው ሰዎች ተሰባስበዋል ስለመፅሃፎቻቾን እንጨዋወታለን ። ቆንጆ ምሽት ይኖረናል ሰዓታችሁን አመቻችታቹ ከስር ባለው ሊንክ በኩል ጎራ በሉልን 🙏❤
“ምነው አምና በሞትኩ፥ እንዲያ እንዳማረብኝ!?”
ዝምታ ይረብሸኛል።
ለዚያም ነው፥ መንገድ ስሔድ መጽሐፍ ይዤ የምዞረው፣ ሁሌም ጆሮዬ ውስጥ ‘ኤርፎን’ የምወትፈው፣ ልተኛ ስል፥ ያለችውን ፀጥታ እንኳን ላለማስተናገድ፥ የኾነ ነገር ከፍቼ ነው የምተኛው ...
በዝምታ ውስጥ ከመኾን፥ ዝም ብሎ ከሚቀደደው ቱሪናፋው ከቤ ጋር ብውል እመርጣለሁ። ዝምታ ሽሽት የማልደውልበት፣ የማላነበው፣ የማልሰማው ዜና የለም።
ዝምታ እፈራለሁ!
መንገድ ስሔድ… ስቀመጥ!
የማነበው መጽሐፍ ካልያዝኩ፣ ስራመድ የምሰማበት ኤርፎን ካልወተፍኩ…. ፖሊሶች አቻኩለው ከቤት አስወጥተውኝ ነው የሚሆነው!
ዝምታ እፈራለሁ!
አስታውሳለሁ፤ 12ኛ ክፍል ነበርኩ። ሙዚቃ ከፍቼ እያጠናሁ፥ የአጎቴን የለቅሶ ሳግ ሰምቼ ደንግጬ “ምነው አመመህ?” አልኩት፤ እሱ ሙዚቃ እየተጫወተበት ያለውን ‘ቴፕ’ ዐየት አድርጎ፥ ወደ ጣርያው አፍጥጦ፣ እምባው ቁልቁል ወረደ!
አሞት መስሎኝ ነበር… ከዚህ በፊት ሲያመው ያቃስታል፤ ሲብስበትም ማስታገሻ ይውጣል እንጂ አያለቅስም ነበር።
አጎቴ ጥቁር ነው፤ ፊቱ ክስክስ ያለ… ሲያወራ ግን እንደሚታየው ኮስተር ያለ ማንነት እንደሌለው የሚያስታውቅበት፥ ቁጥብ፣ ደስ የሚል ሰው ነው።
ልጅ እያለሁ የገዛልኝን ቼኮሌት እና ብስኩት፥ ታሞ አልጋ ሲይዝ ሲጋራ እያመጣሁ ክሼዋለሁ ።
ቤቢ፥ “ያቺን ነገር አትገዛልኝም?” ይላል፤ እገዛለታለሁ። ሲጋራውን በእጁ እያገላበጠ ካያት በኃላ፥ አፉ ላይ እንዳለ እለኩሰለታለሁ።
ዐብሮን ማንም በሌለበት ጊዜ ሁሉ፥ “አትብላ” የተባለውን፣ “አትንካ” የተባለውን ሁሉ እሰጠው ነበር።
እያጠናሁ ስለነበረ፣ ሲያለቅስ አይቼው ስለማላውቅ፣ ደንግጬ ስለነበረ፣… ዘፋኟን ባውቃትም ግጥሙን አላጤንኩትም ነበር፤ ዘፈኑ እንደረበሸው ሲገባኝ፥ ወተት እንደገነፈለበት ሰው፥ ስበር ሔጄ የቴፑን ሶኬት ነቀልኩለት ።
የማባብልበት መንገድ ስለጠፋኝ፥ “ምግብ ላምጣልህ?”፤ “ውሃ ላምጣ” አልኩት። ጣርያ ጣርያ ዕያየ ዝም ሲለኝ ከፊቱ ዞር አልኩለት።
በዚያው ሰሞን፣ ሲብስበት ሐኪም-ቤት ደግመው አስገቡት፤ አልቆየም፤ ሞተ!
የኾነ ቀን ...
አባቴ፥ ስለወንድሙ ቸርነት፣ ዘናጭነት፣ ስፖርተኛነት፣ ሰው ወዳድነት፣ አለኝታነት፣ ስለጓደኞቹ ብዛት፣… ሲተርክልኝ ያስለቀሰቺው ዘፋኝ፥ የዝና ነጋሽ ትዝ አለቺኝ።
ያስለቀሰውን የዘፈን ካሴት ከፈትኩት፤ ሆዱን ያባባው “ገዳሙ” ዘፈን ጋ ደረስኩ።
እስክስታ ሚያስመታ ‘ሪትም’ ያለው ዘፈን ነው
“.........አሆዬ እኔ ላንተ ብዬ፣ መጣሁኝ ጠቅልዬ
አዬዬ፥ እኔ ላንቺ ብዬ፥ መጣሁኝ ጠቅልዬ
“እሀሀ ገዳሙ፥ አሀሀ ገዳሙ
እሀሀ ገዳሙ፥ አሀሀ ገዳሙ
“አላስኬድ፣ አላስኬድ አለኝ፥ ይሄ ጫማ
እኔም ልበቢስ ነኝ፥ ቢመክሩኝ አልሰማ
“እሾህ ብቻ ኾኖ፥ እግሬን ብዳብሰው
እንዴት መራመጃ፥ መሔጃ ያጣል ሰው?
“ኧረግ እናናዬ፣ አረግ እናናዬ
ኧረግ እናናዬ፣ አረግ እናናዬ
“አሄ አሄ አሄ አሄ
አሄ ኡሁ
“ይወዘውዘኛል፥ ይወዝውዝ አባቱ
እህል አሸክሞኝ አርጎኝ ጎረቤቱ
አሞኝ፣ አሞኝ ውሎ፥ አሞኝ ሊያድር ነወይ?
እህል ሰርቶ መብላት፥ ጤና ላይሆን ነወይ?
“ምነው አምና በሞትኩ፥ እንዲያ እንዳማረብኝ
መለየት በሽታ፥ እንዲ ሳይጠናብኝ
“ያመኝ የነበረው፥ አያመኝም ተውኩት
ያስታማሚ ነገር ሲቸግር አየሁት
“እህህህ ገዳሙ
ጠይሙ፣ ጠይሙ..........”
ይላል
ከዛ ቀን በኋላ፥ ተረጋግቼ ሥራዬ ብዬ ሰምቼው ዐላውቅም፤ ነገር ግን ሁሉም ስንኞች ልቤ ውስጥ በአግባቡ ከመሰነድ አላዳነኝም
ድንገት ከተከፈተ፥ የሚረብሸኝ ዘፈን ኾነ ....
“ድል ስቀዳጅ፣ ደስ ብሎኝ ስጠጣ፣ እንዳማረብኝ ግደለኝ አስታማሚ ሳታሳየኝ!” ማለት ጀመርኩ። “ያደረ የዋለ በሽታ አትሰጠኝ” እለው ጀመር
“ይህ ዘፈን ምን ያህል ይረብሽሃል?” ስባል “ከዝምታ በላይ!” ማለት ጀመርኩ።
የግጥሙ ኀይል ነው፥ ወይስ የአጎቴ ኹኔታ ሕይወትን እንድፈራት ያደረገኝ?
ሕይወትን ምን ያህል ባካብዳት ነው፥ እያሸነፍኩ እንኳን “ምነው አምና በሞትኩ፥ እንዲያ እንዳማረብኝ…” የምትል ስንኝ የምታሳድደኝ?
ፈሪ ሰው እንዲህ ነው፤
ከ ጠ’መንጃ በላይ ፥ ቃል ያሳድደዋል!
© Adhanom Mitiku
የፊታችን ቅዳሜ ከ 12:30 ጀምሮ ከምወደው ከ Tewodros Tsegaye ጋር ቆንጆ ቆይታ እናደርጋለን ። ፕሮግራሙን በቀጥታ መከታተያ ሊንክ አስቀምጣለሁ ❤🙏
ኑልን❤
እመንገድ ላይ አየኋት ። ወፍራለች ፣ ጡቷ እንድድሮው አይደለም ። ቦርጫም ሆናለች፣ ትልቅዬ የጭቃ መከላከያ ጫማ ተጫምታለች
ልጅ አቅፋለች ። ብዙ አመት አብረን ተንዘላዝለን ተጨቃጭቀን ..
ተዋደን ...
ተዳርተን...
ተማምተን፣ ተሳስበን ሙሉ ቀን ተጠፋፍተን ምነው የት ጠፋህ የት ጠፋሽ ተባብለናል ። ተለያየን ብለን ታርቀናል ፣ተበዳድለን ይቅርታ ተባብለናል
ትክዝ አልኩ ፦
ልጅነቷ ውስጥ ልጅነቴ ነበር። ጠረኗ ውስጥ ትዝታዬ ተወሽቋል ። እንድተለያየን ሁለት ወር ሳንቆይ ከኔ ጋ እያለች ከሚጀነጅናት ጋ መሰለኝ
አብራው መኖር ጀመረች አራት ወር እንደቆዩ ተለያዩ ሲጣሉ አርግዛ ነበር መሰለኝ ብዙ ሳትቆይ ወለደች ልጁም የሱ ነው ተባለ ።
ምን አለ ልጁ የኔ ቢሆን ...!
አባትህ እንዲ መጥቶ፣ ሰርቶ ፣ሄዶ ፣በድሎኝ፣ ጠቅሞኝ፣ ገለመሌ እንዲ ሆነን ተጣብሰን ተዋደን ብዙ ግዜ ቆይተን ገለመሌ ትላለች
እኔም የልጄ እናት እንዲ አድርጋ እንዲ ሄደን፣ ወጥተን ወርደን እንዲ አቶድም እሷ እንዲ ናት እያልኩ ለልጄ እነግረው ነበር ።
ምን አለ እኔጋ እያለች ሙሉ እንድሆንላት ተመስጣ ባትደምር ባትቀንስ ፣ ምናለ እኔስ ባልፈለሳሰፍ ዝም ብዬ ገፋፍቼ አታልዬ አስርግዣት ቢሆን ።
ህፃን ልጅ አቅፋ ጎስቁል ብላ ልጅነቷን በልጇ ተሸሽጋ እየሸኘችው ነው ።
ውዱን ጊዜያችንን አብረን ነበርን ። ምን አለ ያቀፈችው ልጅ ከኔ ቢሆን፣ ምን አለ ያረገብኩት ጡቷ በኔ ልጅ ምክንያት ቢወድቅ ።
ልጇ እሷን አይመስልም። ምን አለበት ሌላው ይቅር ልጆ እሷን ቢመስል ።
ውድድ ...ሳምምም... እቅፍፍ ...ባደርገው ።
አብሮነታችን ምንም ቋሚ የሚናገር ነገር ሳይገነባ አለፈ ።
እሷ ግን ታድላ መኖርያ ምክንያት አገኘች ።
በድርበቡ ሰላም ብያት ልጆን እጁን ስሜው አይን አይኖን እያየሁ ከላይ ከላይ ካወራን ቀጥሎ
"ለኔም ውለጂልኝ" አልኳት ሳቀች ሳቋ ውስጥ ልጅነቷ ወጣ ፣
በማርያም.... እ....?🙏
ስለት አሳዘንኳት መሰለኝ ፊቷ ቅር አለው፣ "በዚህ ልጅ የበላውት ፍዳ ብታቅልኝ ኖሮ.... "አለች
መንገዷ አባጣ ጎርባጣ እንደነበረው ብዙ ነገሯ ይናገራል
ግዴለም ሁን ያለው ነው የሚሆንው ።እኔም ስንት መከራ ሳይገለኝ ምሮኛል ፣ሰንት ሞት አምልጫለሁ
መጥፎ ነገር ብቻ የሚያልፈኝ በእውነቱ እኔ ማነኝ?!
ባይልልን ነው !
© Adhanom Mitiku
ሁለቱም መፅሀፋችን ፥ በአማዞን
"አዎ! እሱ ጋ ያመኛል!" https://a.co/d/0e0zLEXY
በመኖር በኩል
https://a.co/d/0cxJAyE6
ልደት ❤
ዓመቱ ውብ ነበር። ደስታ ያልተለየው ጉዞ ነበር። "ድንቅ አድርጎልኛል የሠራዊት ጌታ" የሚለውን መዝሙር በየሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ....ስምንት ሰዓት እየዘመርኩ ጎረቤቶቼን ሳልረብሽ አልቀረውም።
እንኳን ጎረቤቶቼ አልሆናችሁ።🤗
መኖር ደስ ይላል፤ ነገ የተሻለ ይመጣል ብሎ መሥራት ደስ ይላል። ይቅር ማለት ደስ ይላል። በአሸናፊ ወዳጆች መከበብ፣ ድላችን በሚያስፈነጥዛቸው ወዳጆች መታጀብ ደስ ይላል።
የሚመርቁንና የሚጸልዩልን ወላጆች ማየት። የማንወደው ላይ አለማተኮር። ደስታን ችላ አለማለት፣ ድልን ማጣጣም፣ ችግር ላይ ክችች አለማለት ደስ ይላል።
በልደት ቀን እንኳን ተወለድኩ ማለትም ደስ ይላል።
መልካም ልደት Adhanom Mitiku
ባልተያያዘ ዜና፤
ሁለቱም መጻሀፋችን በአማዞን ገበያ ላይ ከዛሬ ጀምሮ ማግኘት ይቻላል ። ለጥቂት ጊዜ ገበያ ላይ ያልነበረው መጽሐፋችን "አዎ እሱ ጋ ያመኛል" ለ9ኛ ጊዜ፣ "በመኖር በኩል" ደግሞ ለ5ኛ ጊዜ ዛሬ ለገበያ ቀርቧል።
ችርስ ለደስታችን❤
ሰራተኛ እያፈላለኩ በደላላ አንዲት ልጅ አገኘው
አንገቷን እንደደፋች "ጋሽዬ እኔ የስራ ሆነ የሙያ ችግር የለብኝም ብቻ
ስራ እንዳልቆይ ተደግሞብኛል ፤ ሰርቼ እንዳልለወጥ አሰርተውብኛል" ምናምን ብላ ዘበዘበች
"ብሎ ነገር የለም እኔ ተረት ተረት አልወድም ድግምት ምናምን የለም " ብዬ ካለችው አምስት መቶ ብር ጨምሬ ቀጠርኳት
21 ቀን እንደሰራች
አንዴ
ጠረጴዛዬ ላይ አንገቴን ደፍቼ እየፃፍኩ አንድ ሶስቴ ስጠራኝ አልሰማ ብያታለሁ መሰለኝ
"ምን አባህ ይዘጋሃል ብላ"
ይዛው በነበረው ፔርሙዝ አናቴን አለቺኝ
ተጮኸ። I think እኔ ነኝ የጮህኩት
ጎረቤት ተሰበሰበ
መቼ ፣ ማን እንደመታኝ በደንብ ያወቅኩት ከሁለት ቀን በኋላ ነው
መንፈስ ፣ ድግምት ፣ ተተብትቦብኛል የሚለኝ ሰው ሲገጥመኝ የጀመረውን አረፍተነገር ሳይጨረሰው ነው የማመልጠው
የሻሼን ፍንክት የቀመሰ ሰው በዚህ ነገር አይፈላሰፍም😓😓
እማማ አፀደ የሚባሉ ጎረቤት አሉን የእናቴ ጓደኛ ናቸው። እማማ አፀደ አመም አድርጓቸው ህመማቸው በባሰ ቁጥር እናቴን ጠሏት።
ይሰድቧታል ሌባ ናት ይላሉ።
መሰሪ ናት ይላሉ።
ልትገለኝ ትፈልጋለች ይላሉ።
መርዝ አበላቺኝ ይላሉ ። አትምጣብኝ ብለው ስሞታ ይናገራሉ ሌሊት እቤቴ ልትገባ ነበር ይላሉ ።
ሰው እንዳትመስላችሁ ይላሉ ። እናቴ ቤታቸው መሄድ አቆመች ።
ከቤት መውጣት እያቆሙ ግቢያቸው መዋል ጀመሩ ....
እናቴ እሷ መሆኗን አትንገሩ ብላ ፤ ምግብ ትልክላቸዋለች ። በእህታቸውን ልጅ ፤ ምን ጎደለ ጤናቸው እንዴት ነው እያለች ትሰልላቸዋለች...
ንዴት ሊገድለኝ ይደርሳል ። እቆጣታለሁ << ስምሽን እያጠፉሽ እየሰደቡሽ እየጠሉሽ አትተያቸውም ወይ?>> እላታለሁ!!
<<ጭንቅላታቸው እጢ ወጥቶባቸዋል እሱ ነው ትንሽ ቀየር ያደረጋቸው እንጂ ፤ እሳቸው እንኳን ሳልበድል ብበድላቸው እንኳን በክፉ አያነሱኝም>> ትለኛለች።
ምግብ ትልክላቸዋለች ። በእህታቸው ልጅ በኩል የሚያስፈልጋቸውን መድኃኒት መግዣ ከኛ ወስዳ ... ተበድራም ቢሆን ትገዛላቸዋለች ። እሳቸው ያቺ ምናምንቴ ፣ ድግምታም ያቺ ነጠላ እያሉ ጮክ ብለው እናቴን ሲሰድቧት ይውላሉ ።
ጠላኋቸው !!
አንድ ቀን ለምን ግን እንዲ ስምሽን እያጠፉ እየጠሉሽ እያልፈለጉሽ አልጠላሻቸውም? ብዬ እናቴን ጠየቅኋት።
<<ጓደኛዬ ናቸው! እዚህ ሰፈር ስመጣ እሳቸው ናቸው ያለመዱኝ ። እድር ያስገቡኝ ፥ የሌለኝን እቃ ያዋሱኝ ፥ የተቆረቆሩልኝ ፥ የአረሱኝ ፣የመከሩኝ...
እንዲህ አይባልም እያሉ መንገድ ያሳዩኝ እርሳቸው ናቸው ። ድንገት ታመው ነው የተቀየሩት ።ከሁሉም ጋር ነው መጣላት የጀመሩት እኔ ላይ ትንሽ ጠንከር አሉ እንጂ ...
በክፉ ግዜ እንኳን ወዳጅ ላይ ጠላት ላይ አይጨከንም!!
የጨዋ ሰው ልክ የሚታየው ሲጣሉት ነው ። በፍቅር ግዜ ሰው አይመዘንም ክፉ ግዜ ነው ሰው የሚያጠለው ....
አፀዱ እንዴት አይነት ጥሩ ሰው መሰሉህ ዛሬ ህመም ተጣብቷቸው እን'ጂ ። ስንት ቀን መሰለህ እጦት በሳቸው ሳብያ ከቤታችን የተባረረው ።
አፀደ ደግ 'ሩህሩህ ናቸው...
እናንተ ሳትወለዱ ማንም ሳይኖረኝ ነው ከኔ ጋር የነበሩት...
የአፀደ ውለታ አለብኝ !>>
© Adhanom Mitiku
ነጋልን ❤
ስለ በመኖር በኩል
ስለናንተ፣ መፅሃፍ ስታነቡ ስለመጣላቹ ፣ባይሆን ስላላችሁት፣ እንኳን ሆነ ስለምትሉት ደራሲው ፊት ለፊት ስለሚኖር ልክ ልኩን እንነግረዋለን ❤
ኑልን እስቲ ስለህይወት እንጨዋወት ❤
ዛሬ ከቀኑ 10:30 ጀምሮ ጃፓን መብራቱ ጋር ቱሪዝም ሚኒስቴር ህንፃ ግራውንድ ላይ ነው ቦታው
ፈገግታ ይሸውደኛል ። መንገዴ ላይ ያጠቃኝ ሁሉ ፈገግታውን ተጠቅሞ ነው የጣለኝ። የጎዳኝ ሁሉ ከጀርባዬ ሰንዝሮ ነው።
ፈገግታ ስስ ጎኔ ነው !!
ቤተሰቦቼ ቀጥተኛ ነበሩ አጥፍቼ የሚስቅልኝ አልነበረም፤ ወድቄ ፈገግ ብሎ አባብሎኝ የሚያውቅ ኖሮ አያውቅም።
ፈገግ እያለ የሚታገል ይጥለኛል ።
ፈገግታ ካየሁ ትግሉ የምር አይመስለኝም። አቅፎ ሰላም የሚለኝ ልቡ የሚወደኝ ይመስለኛል።
ልቡ ላይ በመጥፎ ያስቀመጠኝ ሰው ጥርሱ ፈገግ የሚልለት እና እጁ አጥብቆ የሚያቅፍለት አይመስለኝም ነበር።
እናት እና አባቴ ተደባብረው ፈገግ ብለው ሲጨዋወቱ አይቼ አላውቅም። ወንድም እና እህቴ አታለው ይዘው ቀጥተውኝ አያውቁም።
ቤተሰቦቼ ቀጥተኛ ነበሩ !
ፀባቸው ፊት ለፊት ነው። ቅሬታቸው ፊታቸው ላይ ይነበባል ።
ከተሰማቸው ስሜት ርቀው አያስመስሉም!
አይወደኝም የምለው ሰው ቀረብ ብሎ ለስለስ ብሎ ካዋራኝ ጋሻዬን ጦሬን እጥላለሁ። ስልት ያለው ጥላቻ አይገባኝም
አባቴ አጥፍቼ እንዳይመታኝ ከተማፀንኩት ይቅርታ አደረጎልኝ፥ አረሳስቶ መቶኝ አያውቅም ።
የተጣላሁት ሰው ፈግግ ብሎ ካወራኝ ይቅር ብሎኝ ነው የሚመስለኝ። ፈገግ እያሉ ክፋት የሚጎነጎኑ ሰዎች ሳይጥሉኝ ቀርተው አያውቁም።
በርግጥ የሰው ልጅ መሸነፍያ ሰፍራ አያጣም!!
©Adhanom Mitiku
