uz
Feedback
መጽሐፍ ቤት Bookstores

መጽሐፍ ቤት Bookstores

Kanalga Telegram’da o‘tish
3 933
Obunachilar
-424 soatlar
-107 kunlar
-2830 kunlar
Postlar arxiv
በአፍላነቴ በተፈጥሮ አስገዳጅነት ጭምር ብርቱ የሆነ የተቃራኒ ጾታ ፍላጎት የተፈጠረብኝ ቢሆንም 'ሰይጣን አለባት' በሚል ተልካሻ ምክንያት የሚንቁኝና የሚያገሉኝ በዙ፡፡ በተገፋሁ ቁጥር ፍላጎቴ በእጥፍ አደገ፡፡ 'አንድ ወንድ አፈቅርሻለሁ ካለኝ ሳላቅማማ እኔም አፈቅርሃለሁ እለዋለሁ' ብዬ የነበረ ቢሆንም የፍቅር ጥያቄ የሚያቀርብልኝ ጠፋ፡፡ያኔ ለራሴ የፍቅር ደብዳቤ ፃፍኩ፡፡ ‹‹ጫሊ ጉድ ሰማሽ?›› አልኳት የክፍላችንን ፍልቅልቅ ተማሪ ‹‹የምን ጉድ?›› ‹‹ደብዳቤ ተፃፈልኝ›› ‹‹ከማን?›› ‹‹አላውቅም›› ‹‹እንዴት አታውቂም?›› ‹‹ስም የለውም፡፡ ግን ከዚህ በፊትም ጽፎልኝ ያውቃል›› ደብዳቤውን ከደብተሬ ውስጥ አውጥቼ ሰጠኋት፡፡ ወሬው ተናፈሰ፡፡ የሆነ ሰው ማንነቱን ሳይገልፅልኝ ደብዳቤ እንደሚጽፍልኝ ተወራ፡፡ የክፍሌ ሴቶች በየቀኑ 'የሚጽፍልሽን ወንድ አወቅሽው?' በሚል ጥያቄ ያዋክቡኝ ጀመር። የሆነ ወንድ እንደሚያፈቅረኝ ተረጋገጠ፡፡ ተፈቃሪነቴ በተማሪ ቤቱ በተወራ ወቅት አንድ ብጣሽ ወረቀት ደብተሬ ስር ተቀምጠ፤ ልቤ ዘለለች፡፡ 'እኔም እንደ እኩዮቼ አፍቃሪ አገኘሁ' ብዬ በደስታ ተሞላሁ፡፡ ተፈላጊ የመሆን ስሜት ሀሴትን ፈጠረብኝ፡፡ በደስታ ውስጥ ሆኜ አንድ አንቀጽ ጽሑፍ ብቻ ያለውን ደብዳቤ ማንበብ ጀመርኩ. . . ‹‹ላንቺ የፍቅር ጥያቄ የሚፅፍልሽ ማን እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ የሚያፈቅርሽ ሰይጣን ነው፡፡ አንቺ ሴት ሰይጣን ነሽ፡፡ ወንዱ ሰይጣን ደግሞ ያፈቅርሻል፡፡ እሺ ካልሽው መውደቅሽ ይቆማል›› ይላል ደብዳቤው። ሰውነቴ እየተንቀጠቀጠ አለቀስኩ.... #ክራራዊ_ህይወት ደራሲ ተስፋኣብ ተሾመ አሳታሚና አከፋፋይ ጃፈር መጽሐፍት

ምንገድ ላይ (በእውቀቱ ስዩም) በቀደም ከሆነ ቦታ ተነስቼ ወደ አልሆነ ቦታ ስራመድ ኡራኤል ፊትለፊት ካለው አስፋልት ላይ ስደርስ የሚገርም ነገር ተከሰተ፤ አንድ የጎዳና ተዳዳሪ ቡሌ በፌስታል, ሸክፎ አስፋልት እያቁዋረጠ ሳለ አንድ ሞተረኛ ከላይ ሲንደርደር መጥቶ ደንብቆ ጣለው ፤ የሸገር ሞተረኞች ለምን እንደሚካልቡ አይገባኝም፤ አለምን ከጥፋት የሚታደግ መልክት ለማድረስ የሚነዱ እንጂ የጠወለገ በለጨ የጫኑ አይመስሉም፤ ሞተረኛው ከሞተሩ ተስፈንጥሮ አስፋልቱ ዳር ተዘረረ ፤ ሞተሩ ግን በራሱ ፈቃድ እየበረረ ሂዶ ባቅራቢያው ከሚገኝ ጋራጅ ውስጥ ገብቶ ተሰወረ፤ የጎዳናው ሰውየ ተሽቀንጥሮ መንገዱ ጠርዝ ላይ ተገኘ፤ ወድያው ባካባቢው የነበረው ህዝብ ሞተረኛውን እና የጎዳናውን ሰውየ ተካፍለው ከበብ ከበብ አድርገው ቆሙ፤ ብብዙዎች ፊት ላይ ሀዘን በግልፅ ይነበባል ፤ ቢያንስ ከሁለት አንዱ አለመሞታቸው ብዙዎችን ያስደበረ ይመስለኛል ፤ እኔ ሁሌም ከተጎጂው ጎን መሰለፍ ስለሚያስደስተኝ ፣ ከጎዳና ተዳዳሪው አጠገብ ቆምኩ፤ ተጎጂው ቀና ብሎ አየኝ፤ መላከ ሞትን ያባረረ ኡራኤል መስየ ታይቸው ይሆንን ብየ ራሴን ሸነገልሁ፤ የጎዳናው ሰውየ የፈራሁትን ያህል አልተጎዳም፤ ደጋግሞ የመገጨት ልምድ ያካበተ ይመስላል፤ የቀኝ እግሩ መሀል አገዳ ላይ ብቻ የመድማትና የመጫጫር ምልክት አየሁ፤ -አይዞህ ወንድም ጥላ! በዚች እግርህን ታይበት ‘ አልሁና ከቦርሳየ ውስጥ ሁለት መቶ ብር በማውጣት ዘረጋሁለት፤ በልግስናየ ልቡ ተነክቶ ተጠምጥሞብኝ ያለቅሳል የሚል ግምት ነበረኝ፤ ‘እናትህ ትጎዳ ! (በትክክል ያለኝ እንኩዋ ከ-ትጎዳ-ይከፋል )፤ በሁለት መቶ ብር ምንላቀቅ መስሎሀል?’ አለና እጅጌየን ጥቅጥቅ አርጎ ያዘኝ; ክፉኛ አንደዞረበት ተገለጠልኝ፤ ‘አይዞህ ዠለሳዊ ! በዚህ ደግሞ ጭንቅላትህን ታይበት’ አልሁና ቸክ ፈርሜለት ጉዞየን ቀጠልሁ፤

ቻይናዊው ሻወር እየወሰደ እያለ፣ ድንገት ቤቱ በእሳት ይያያዛል... ራቁቱን በመስኮት ዘሎ ይወጣል። ትንሽ እንደተረጋጋ ሚስቱ የሚቃጠለው ቤት ውስጥ መቅረቷን ያስታውሳል፤ ነገር ግን "እንግዲህ ቀኗ ካልደረሰ መውጣቷ አይቀርም" ብሎ ችላ ይላታል። ወዲያው ግን አንድ በጣም አስደንጋጭ ነገር ትዝ ይለውና፣ በአስደናቂ ጀግንነት ድጋሚ ዘሎ ወደሚቃጠለው ቤት ይገባል። ሚስቱንም አንከብክቦ ይዟት ይወጣል። ​በኋላ ላይ ጋዜጠኞች ተሰብስበው፦ "እንዴት በዚህ ድፍረት ወደሚቃጠለው ቤት ገብተህ ሚስትህን ልታተርፋት ቻልክ? ስታገኛትስ በምን ሁኔታ ላይ ነበረች?" ብለው ጠየቁት። ​ስሜቱን በራሱ ቋንቋ እንስማው... ​我不能把手机和妻子单独留在家里。我一直担心她会拿起我的手机偷看信息。当我急匆匆地冲进家门时,果然不出所料,她正一边被浓烟包围着剧烈咳嗽,一边在翻看我的手机。最终,我把她和手机一起救了出来。 ​አቻ ትርጉም ከትንሽ ቅመም ጋር ​"ስልኬንና ሚስቴን ብቻቸውን እቤት ውስጥ መተው ፈጽሞ አልችልም! 'የተላላኩትን መልዕክት እያነበበች ይሆን?' የሚለው ስጋት እረፍት ነሳኝ። ​ዘልዬ እቤት ውስጥ ስገባ ልክ እንደፈራሁት፤ በጭስ ተከባ የቀሚሷ ጫፍ በእሳት እየተቀጣጠለና እያሳለች ስልኬን ስትፈትሽ አገኘኋት! በጨዋነት ስልኬን ተቀብየ ልወጣ  ስሞክር  'ዢዋን ማናት? ለምንስ የልብ ኢሞጂ ላክህላት?' እያለች በዚያ ጭስ ውስጥ መጨቃጨቅ ጀመረች። ሌላ አማራጭ ስላልነበረኝ፣ ከነስልኩ አንጠልጥዬ ይዣት ወጣሁ።" ​ክፉ ጊዜ ላይ ነን እ? 😁 Alex Abraham

"የአስራ ሰባት አመት ወንድም እንዳለኝ ነግሬሽ አውቃለሁ?" "አላስታውስም" "የአስራ ሰባት አመት ወንድም አለኝ" "ምን ሆነ?" "ዘመቷል" "መዝመት ማለት?.... ወደ ጦርነቱ?" ጮኸች። በቡናቤቱ የነበሩ ሌሎች ሰዎች በሙዚቃውና በግል ወሬያቸው ተይዘው ባይሆን ድንጋጤ ያዘለ ድምጿ ያስደነግጣቸው ነበር። ወንድሜ እንደዘመተ የሰማኹ ቀን 'ወደ ጦርነቱ ነው የዘመተው?' ብዬ እንደተደናበርኩ እሷም ተደናበረች "አዎ። ወደ ጦርነቱ ነው የዘመተው" "ቤተሰብ እንዴት ፈቀደ?" "በቤተሰብ ፈቃድ አይደለም" "ታፍሶ ነው?" "አልታፈሰም። ስለ ጦርነቱ እንደ አቅሙ መረጃ ይሰበስብ ነበር። ነሸጠውና ተመዘገበ። ነገር ግን ወደ ስልጠና ከገባ በኋላ ስልክ አግኝቶ ደውሎልኝ እንደፈራ ነገረኝ" "እኔን" ደረቷን መታች "እኔን" ደረት መነረቱን ደገመች "እሱ ከሄደ በኋላ እናቴ ደህና አይደለችም። 'አዳዲሶቹ ጥይት ማብረጃ ይሆናሉ' ሲባል ሰምታለች። ወንድሜ ፈንጂ አምካኝ አልያም ጥይት ማብረጃ ሆኖ በአሰቃቂ ሁኔታ እንደሞተ እርግጠኛ ናት" "የኔ እናት" ደረት መድቃቱን ሰለሰች "አይኗን ማየቱ ያስጨንቃል፥ ምግብ በመከራ ነው የምትበላው፥ለሊት ትቃዣለች" "እኔ ልሰቃይላት" "መሄድ የነበረብኝ እኔ ነበርኩ። እኔ የሱን እጥፍ እድሜ ኖሬያለሁ፥ ሰላሳ አምስት አመቴ ነው። ከሱ በተሻለ ህይወትን አጣጥሜያለሁ። እርሱ ግን ልጅ ነው" "አንተስ ምን በወጣህ?" "ከሱ በተሻለ ኖሬያለሁኝ" "ገና በ ሰላሳ አምስት?" "ከ አስራ ሰባት አይሻልም? እሱ እኮ ምንም አልኖረም" እንባዋ የመናገር ፍላጎትቴን አናረው። ለቅሶዋ በእናቴ ፊት የምሸሽገውን የታፈነ ስሜቴን እንድዘረግፍ ምክኒያት ሆነኝ። "በጦርነት የሞተ ወንድም እንዳለኝ ነግሬሻለሁ?" "አልነገርከኝም" "ታላቅ ወንድሜ በባድመ ጦርነት ወቅት 'ጠላት የአገራችንን ድንበር ሊደፍር አይገባም' ብሎ ከሻቢያ ጋር ለመፋለም ሄዶ መስዋዕት ሆነ። መሞቱን መርዶ ተነገረን እንጂ አስክሬኑን የመቅበር እድል አላገኘንም" "እኔን" ሌላ ደረት መድቃት "ታናሽ ወንድሜ ደግሞ በ ዘጠና ሰባት ነው የሞተው" "እንዴ....?" "ተባራሪ ጥይት ነው የበላለው። ከምርጫ ጋር በተያያዘ ጉዳይ አገር ስትታመስ ከመንግሥት ሰራዊት ለተቃዋሚዎች የተተኮሰች ጥይት ወንድሜን በላችው" "ምን ጉድ ነው?" እንባ የተቀላቀለበት ደረት መድቃት ያጀበው ንግግር "ምን የሚሉት መኣት ነው? እንዴት ያለ መራራ እድል ነው?" ስታለቅስ አብሬያት አለቀስኩ። "እናቴ ግማሽ አእምሮዋን አጥተዋለች" "ለእኔ ያድርገው" እንባና ደረት መድቃት አልተለያትም "ተስፋ ቆርጫለሁ። አዲስ ህይወት የማልሞክረው፥ እንደ ህፃን ከእናቴ ቤት መውጣትን የምፈራው 'ለማን ትቼያት እሄዳለሁ?' በሚል ስጋት ነው። አራት ወንዶችን ወልዳ ሁለቱ የጥይት ሲሳይ የሆኑባት እናቴ ስለምታሳዝነኝ ከአጠገቧ መራቅ ያስጨንቀኛል" ከ #ነገን_ፍለጋ መፅሐፍ የተወሰደ ደራሲ ተስፋአብ ተሾመ

‹‹እማዬ ስራ ስይዝ ሀበሻ ቀሚስ እገዛልሻለሁ›› ‹‹ለማን?›› ‹‹ላንቺ ነዋ›› ‹‹ምን ላደርገው?›› ‹‹እንድትለብሺው›› ‹‹እኔው?›› ከንፈሯን እንደ አሽሙረኛ ሴት ታጣምመዋለች ‹‹አትፈልጊም?›› ‹‹ጽድቁ ቀርቶብኝ በወጉ በተኮነንኩ›› ‹‹ምን ማለት ነው?›› ‹‹ይልቅ ለራስሽ አስቢ። እኔ ረፍዶብኛል። ከዚህ በኃላ ማጌጥ አልፈልግም። አንቺ ሰው ከሆንሽ ለእኔ ከበቂ በላይ ነው›› ‹‹ሰው ከሆንኩ በኃላስ?›› ‹‹ከዛማ ምን እፈልጋለሁ?›› ‹‹እንደ ሌሎች እናቶች መሆን አትፈልጊም?›› ‹‹እኔ አሁን ከስሜያለሁ። ለማጌጥ ረፍዶብኛል፣ ለመዋብ ብሞክር አያምርብኝም›› ሁሉም ነገር ከእጇ ያመለጠ ይመስላታል፡፡ መጎሳቆልን እጣፋንታዋ አድርጋ ስለተቀበለች የተሻለ ነገር አትመኝም፡፡ መዋረድን ስለተለማመደች ከሰው እኩል መሆን ቅንጦት ይመስላታል፡፡ መድመቅ የተፈቀደላት አድርጋ ስለማትቆጥር መክሰሟን በፀጋ ተቀብላለች፡፡ ቀና የማለት መብት እንዳላት ስለማታውቅ በመጉበጧ ተቃውሞ የላትም፡፡ ማንን ትቃወማለች? ለማን አቤት ትላለች? ‹‹የኔ ልጅ ትምህርትሽን በርትተሽ ተማሪ፣ እንደ እኔ እንዳትሆኚ›› ‹‹እሺ›› ‹‹ባክኜ የቀረሁት ያልተማርኩ ደን^ቆሮ ስለሆንኩ ነው›› ‹‹እሺ›› 'እሺ' ከማለት በቀር ምን እላታለሁ? ደ^ንቆሮ መሆኗን ስትመሰክር 'ደን^ቆሮ አይደለሽም' ብላት ደስ ይለኛል፡፡ ነገር ግን የድን^ቁርና ልከኛ ትርጓሜና መለኪያ ሚዛኑ ምን እንደሆነ ስለማይገባኝ እሺ እላታለሁ፡፡ እሺ ብቻ ‹‹ህልሜ የምትመረቂበትን ቀን ማየት ነው፡፡ የምርቃትሽን ቀን አይቼ በማግስቱ ብሞት ግድ አይሰጠኝም›› እናቴ የምትጓጓለት የምርቃት ቀኔ ሲደርስ በመመረቂያ ስፍራው አልተገኘችም፡፡ አባቴና ጥቂት ጓደኞቼ ስጦታ ይዘውልኝ እንኳን ደስ አለሽ ሲሉኝ እናቴ በስፍራው አልነበረችም፡፡ ‹‹ለምን ቀረሽ?›› አልኳት ቤት ከመግባቴ ‹‹ፈርቼ›› ‹‹ምን ያስፈራሻል?›› ‹‹እንዲህ ያለ ቦታ በምን አቅሜ እገኛለሁ?›› ‹‹አቅም ያስፈልጋል ያለሽ ማነው?›› ‹‹በዛ ሁሉ ሰው መካከል እንደኔ አይነት ተራ ሰው ይገኛል?›› ‹‹ሁሉም'ኮ ተራ ሰው ነው›› ‹‹እንደዛስ አይሆንም›› ‹‹የተለዩ ሰዎች ቢኖሩ እንኳን ጥቂት ናቸው›› ‹‹የኔ ግን ይለያል›› ‹‹የምርቃቴ ቀን ያጓጓሽ አልነበረም?›› ‹‹ነበር›› ‹‹ታዲያ ለዓመታት ስትመኚው በነበረው ቀን በስፍራው መገኘት አልነበረብሽም? እኔ እንደሌሎች ሩቅ ቦታ አልተመደብኩም፡፡ እዚሁ አዲስ አበባ ነው የተማርኩኩት፡፡ በአንድ ታክሲ መምጣት እየቻልሽ መቅረትሽ ምን ይባላል?›› ‹‹አስፈራኝ፡፡ የልጅነት ቃልሽን ጠብቀሽ የገዛሽልኝን ሀበሻ ቀሚስ ለብሼ ስሞክረው አፈርኩኝ፡፡ ከኔ ሰውነት ጋር የሚሄድ አልመስልሽ ሲለኝ የለመድኩት ቡቱቶ ይሻለኛል አልኩ፡፡ እድሜዬን ሁሉ በጭስ ስጨናበስ ኖሬ የገዛሽልኝን ሽቶ መላመዱ ከበደኝ፡፡ ምርቃትሽ ቦታ ብገኝ የሰው ሁሉ አይን እኔ ላይ የሚያርፍ ስለመሰለኝ መቅረትን መረጥኩ፡፡ ከሰው እኩል በመሆንሽና ህልሜ ስለተሳካ ደስታ አስለቅሶኛል፡፡ ታዲያ እንባዬ የደስታ ብቻ አልነበረም፡፡ ሆድ ብሶኛል፡፡ በብቸኛ ልጄ የደስታ ቀን ባለመገኘቴ ሆድ ባሰኝ፡፡ እድሜዬን ሳስብ ከፋኝ፡፡ ደስታና ሀዘን አስለቀሰኝ› ተደብቄያት አለቀስኩ፡፡ #ክራራዊ_ህይወት ደራሲ ተስፋአብ ተሾመ አከፋፋይ ጃፈር መጽሐፍት

ፈገግታ ይሸውደኛል ። መንገዴ ላይ ያጠቃኝ ሁሉ ፈገግታውን ተጠቅሞ ነው የጣለኝ። የጎዳኝ ሁሉ ከጀርባዬ ሰንዝሮ ነው። ፈገግታ ስስ ጎኔ ነው !! ቤተሰቦቼ ቀጥተኛ ነበሩ አጥፍቼ የሚስቅልኝ አልነበረም፤ ወድቄ ፈገግ ብሎ አባብሎኝ የሚያውቅ ኖሮ አያውቅም። ፈገግ እያለ የሚታገል ይጥለኛል ። ፈገግታ ካየሁ ትግሉ የምር አይመስለኝም። አቅፎ ሰላም የሚለኝ ልቡ የሚወደኝ ይመስለኛል። ልቡ ላይ በመጥፎ ያስቀመጠኝ ሰው ጥርሱ ፈገግ የሚልለት እና እጁ አጥብቆ የሚያቅፍለት አይመስለኝም ነበር። እናት እና አባቴ ተደባብረው ፈገግ ብለው ሲጨዋወቱ አይቼ አላውቅም። ወንድም እና እህቴ አታለው ይዘው ቀጥተውኝ አያውቁም። ቤተሰቦቼ ቀጥተኛ ነበሩ ! ፀባቸው ፊት ለፊት ነው። ቅሬታቸው ፊታቸው ላይ ይነበባል ። ከተሰማቸው ስሜት ርቀው አያስመስሉም! አይወደኝም የምለው ሰው ቀረብ ብሎ ለስለስ ብሎ ካዋራኝ ጋሻዬን ጦሬን እጥላለሁ። ስልት ያለው ጥላቻ አይገባኝም አባቴ አጥፍቼ እንዳይመታኝ ከተማፀንኩት ይቅርታ አደረጎልኝ፥ አረሳስቶ መቶኝ አያውቅም ። የተጣላሁት ሰው ፈግግ ብሎ ካወራኝ ይቅር ብሎኝ ነው የሚመስለኝ። ፈገግ እያሉ ክፋት የሚጎነጎኑ ሰዎች ሳይጥሉኝ ቀርተው አያውቁም። በርግጥ የሰው ልጅ መሸነፍያ ሰፍራ አያጣም!! ©Adhanom Mitiku

የቆሰለ ነገር ፣የከሳ ፣የኮሰመነ እንሰሳ እሚያድን አውሬ ያስጠላኛል ምቹ ግዜ እየጠበቀ ድምፁን እና ሁኔታውን የሚቀያይር ሰው ግን ያስፈራኛል። ስዩም ፦ ጓደኛው ነኝ ጓደኛዬ ግን አይደለም። ብዙኅ አሳልፈናል ። ቢሰማብኝ የማፍረውን ነገር ወይ ቢሰማብኝ ጉድ የሚያደርግብኝን ነገር አልነግረውም ። እፈራዋለሁ። ቋሚ ወዳጅ ስለሌለው እና ዋሉልኝ ያለቸውን ሰዎች ሁሉ በየምክንያቱ ስለሚተዋቸው እፈራዋለሁ ። ከጓደኞቹ X ስር ስለማይጠፋ ስሜቱን ሁሉ የተሰማው ሰዓት ስለማያንፀባርቅ አብሬው ሆኜ አይጥ ለመያዝ ትክ ብላ እንደምታደባ ድመት ነው የማየው። እሱ እንደድመቷ ትኩረት ሲያደርግ ሁኔታው እንደድመቷ አይነት አይደለም አያስታውቅበትም ። ዘና እያለ እየሳቀ ሚስጥር እየነገረ ነው ሚስጥር የሚያስወጣው ። ስዩምን እፈራው ነበረ .....! ችግር ገጠመኝ ከሁሉም በላይ አብሮኝ ሆነ ያለውን ሁሉ ሰጠኝ አሰጣጡ ስሙልኝ እዩልኝ ያለው አልነበረም በችግሬ አብረውኝ ያልነበሩትን ስወቅሳቸው እያገዘ አላባባሰብኝም... "ተዋቸው አልሞላ ብሎቸው ነው" አለኝ ....ከነሱ ጋ ሆኜ ያጣጣልኩት ስዩም አብሮኝ ቆመ .... ተፀፀትኩ ...! ከብዙ ግዜያት በኋላ ስዩምን በየወሬው እንደዚ አትመስለኝም ነበር እያልኩ እሱ ላይ ያለኝን አቋም ተናዘዝኩ አልተናደደም ሳቀ ስልከው እና ሲላከኝ እንደኩያ አይደለም እንደታናሽ ነው ሲተማመንብኝ እንደታላቅ ነው ...! እሚያግዘን እና የሚኮራብን ወዳጅ የኛ ሲሆን የሚሰማውን ምቾት አሰማኝ ከጥቂት ግዜ በኃላ ... ስራ በዛብኝ ብዬ የሰጠሁንት ላግዝ ብሎ የወሰደውን ሙሉ ውክልና ተጠቅሞ መኪናዬን ሸጦ አውሮፓ መግባቱን ከሳምንት በሆላ ሰማሁኝ ... ስስቅ ላየኝ ሰው ተታልዬ አልመስልም ነበር ... ማመን ከመጠራጠር በላይ ዋጋ ያስከፍላል ማለት ነው ?? መፍራት ከመድፈር በላይ አቅም አለው ማለት ነው ?? ኮቴ በሰማን ቁጥር እየባነንን የት ድረስ እንሄዳለን ?? የሄድንበትን መንገድ እየጠየቅን መሄድ የሰውነት እጣ ፈንታ ነው ??.... በርግጥ የግዜ ጉዳይ እንጂ ከተካደ ሰው የከዳ ሰው ያሳዝናል!! © Adhanom Mitiku

እናንተ ከድካማቹ የበረታቹ ሆይ እንዴት ከባድ ግዜያችሁን አለፈላቹ ? እንዴት የተሰበረ ልባችሁን ጠገናችሁ? የአፈሰ እጃችሁ ባዶ ሆኖ ስታገኙት ..... ድንጋጤ እንዴት አደረጋቹ ? . . እናንተ ከድካማቹ የበረታቹ ሆይ ስትታመሙ ስታጡ ቤት ስትውሉ መረሳት እንዴት ሳይሰብራችሁ ቀረ ? .... ያልፍልኛል ብላችሁ የሄዳችሁበት መንገድ አባጣው ጎርባጣው አተርፍ ባይ አጉዳይ ሲደርጋቹ ምን አላችሁ?? . . እናንተ የበረታችሁ ድንገተኛ ሃዘን ጎጃቹ ሲገባ፣ ያተርፋል ያላችሁት ሲያከስር ፣ መከዳት ልባችሁን ሲያርደው ......እንዴት ጨለማው ነጋላችሁ? ተስፋችሁ የተሟጠጠ ማድጋችሁ የጎደለ ኪሳቹ የተራቆተ እለት ........ ጭንቀት እንዴት ድል ሆነላቹ . . እናንተ የበረታቹ ሆይ መውለድ እምቢ ሲላችሁ ፣ ልጃችሁ ሲታመም፣ ጤናችሁ ሲጓደል .....ተስፋ የለም ስትባሉ ልባቹ እንዴት ተስፋ አየ ??? . . መፅሃፍ ቅዱስ የበረቱ ሰዎችን የአንበሳን አፍ ከዘጉ ፣ከሰይፍ ስለት ካመለጡ፣ የእሳትን ሃይል ካጠፉ፣ የባእድ ጭፍሮችን ካባረሩ ፣በጦርነት ሃይለኛ ከሆኑ ሰዎች እኩል ከድካማቸው የበረቱትን ያወሳል ከድካም መበርታት ቀላል አይደለም ! ቅዱስ ዳዊት ልጁ አቤሰሎም ሲያሳድደው የሚያስጨንቁኝ እንዴት በዙ! ብዙዎች በእኔ ላይ ተነሡ። ብሏል ትግስተኛው እዮብ መከራ ሲሸከም ድካሙ ሲበረታበት ስለ ምን ከማህፀን አልሞትሁም ብሏል . . የሰው ልጅ ሃያል ነው ከድካሙ ይበረታል አይነጋም ያለው ይነጋል . . እናንተ የበረታችሁ ሆይ እናንተ ግን እንዴት እንዴት በረታቹ ??? © Adhanom Mitiku

ቻርለስ ቡኮውስኪ ቀጭን ሲጋራውን እየማገ ኢንተርቪው ለሚያደርጉት ሰዎች አንድ ጥያቄ ይጠይቃል፦ ‹‹ማንም ጠዋት ሳይቀስቅሰን ስንነሳ፤ ማታ ደግሞ ማንንም ሳንጠብቅ ስንተኛ፣ የፈለግነውን ማድረግ ስንችል። ምን ብለን እንፈርጀዋለን፤ ነፃነት ወይስ ብቸኝነት?›› መልሱን በዚህ መልኩ አስቀምጬዋለሁ..               ከረጅም ከባድ ቀን በኋላ ወደ ቤት እንገባለን። እዛ የሚጠብቀን ማንም የለም። ድመት እንኳን አላሳደግንም። ወደቤት እንደገባን ቁልፉን ጠረጴዛ ላይ እናስቀምጣለን። ይህ የእለት ተእለት ተግባራችን ነው። በህይወታችን ውስጥ የቀረው ብቸኛው ቁጥጥሮሽ ቁልፉን ጠረቤዛው ላይ ማስቀመጥ ነው። ጫማችንን እናወልቃለን።  “የት ነበራችሁ?” ብሎ የሚጠይቀን የለም፤ “ውሎህ እንዴት ነበር?” የሚለን አይኖርም። ወደ ኩሽና እንገባለን ፍሪጁን ከፍተን ግማሽ ጠርሙስ ውሃ እና መች እንዳስቀመጥነው የማናውቀውን እርጎ እናወጣለን። ቀጥሎ የረሳነውን የለውዝ ቅቤ በማንሳት በደረቀው ዳቦ ላይ እንለውሳለን። ከዛ ብዙም መጠበብ እና መጨናነቅ በሌለው መልኩ የፍሪጁን በር ወርውረን እንዘጋዋለን። እናም ሶፋችን ላይ ተቀምጠን ስልካችንን እንመለከታለን፤ ምንም አዲስ መልእክት አልተላከም። የለቀቅነውን ፎቶ ማንም ላይክ አላደረገውም። አለም እኛን ችላ ብላናለች። ስለዚህ ካየነው የቆየ “shutter island” የሚለውን ፊልም እንደገና እንገርባለን። ምክንያቱም ድግግሞሽ ከአዲስ ክስተት የተሻለ አስተማማኝ ነው የሚል አስተሳሰብ ስላለን። በዙርያችን የሚበጠብጥ ድምፅ የለም፤ ሙዚቃ የለም፣ ሳቅ የለም፤ ስለአስቤዛ የሚከራከረን የለም፤ ሁሉም በዝምታ ውስጥ ተውጧል። ማንም አያቋርጠንም ማንም ደግሞ ሙዳችንን አይቀይረውም። ከእኛ ጋር አልጋ የሚጋራን ስለሌለ አልጋው ላይ በነጻነት ተዘረጋግተን እንቀመጣለን። ቀዝቃዛ ድባብ ነገር ግን ምንም ማስመሰል የሌለበት እውነተኛ ስሜት። ብቻን መኖር ማለት የዚህ ሁሉ ባዶነት ፍፁም አለቃ ነን ማለት ነው። የቀዘቀዘውን ወጥ ሳናሞቅ አልጋችን ላይ መብላት እንችላለን። ያለምንም መረበሽ ቀኑን ሙሉ ተኝተን መዋል እንችላለን። ሳና ሳምንቱን ሙሉ መጥፋት እንችላለን። ማንም የእኛን ማብራሪያ አይጠብቅም፤ የትኛውም ሰው በቀስታ እየጠፋን እንደሆነ አይገነዝብም!። ሰዎች ብቻን መሆን ማለት ብቸኝነት ይመስላቸዋል። ነገር ግን ይህ የስነ ልቦና ኢኮኖሚካሊ ዘዴ ነው። ሌሎች ላይ ኢንቨስት ማድረግ አቁሙ ምክንያቱም በምላሹ የምታገኙት ደካማ ውጤት ነው። በስተመጨረሻ መብራታችንን አጥፍተን በቀዝቃዛ አልጋችን ላይ እንተኛለን። እናም ሚስጥራዊ ምቾት ይሰማናል። ማንም አይወደንም ማንም አይጠላንም፤ እና ማንም አይፈልገንም። ይህ ደግሞ በጣም ዘና የሚያደርግ ነፃነት ነው።       @Imagination_officially

የጠንቋይ ልጅ! (አሌክስ አብርሃም) የሰርግ ፎቷችን ያለበት ቦርድ እየዞረ ተጋባዥ እንግዶች ሁሉ ይፈርሙና መልካም ምኞታቸውን ያሰፍሩ ነበር። ቆይቶ አንድ ጽሁፍ አየሁ፤ "መልካም ድህነት" ይላል። ብልግና አይደል? ጽሁፉን ጠንቅቄ አውቀዋለሁ፤ የእርሱ ነው። ለዓመታት ፍቅረኛዬ የነበረው የያሬድ እጅ ጽሁፍ! "ምነው ፀባዩ እንደ እጅ ጽሁፉ ቢያምር ኖሮ!" እላለሁ። አፈቅረው ነበር፤ እርሱም ያፈቅረኝ ነበር (ወይም ይመስለኛል)። "የሱቄ ጠባቂ ናት" የሚላት ሴት ጋር ተኛ። እዛ መገናኛ የልብስ ሱቅ አለው። ይቅርታ ላደርግለት ሰበብ ፈለግኩ። ጎበዝ ነው፤ በጥረቱ ኑሮን ያሸነፈ፣ እንዴት እዚህ ደረስክ ቢባል አንድ ሁለት ብሎ ደረጃውን የሚያስቆጥር። ደስ የሚል ሕይወት ያለው፣ ሀብታም የሆንኩ መስሎ እንዲሰማኝ ያደረገ። ሰበብ ፈለኩ ክህደቱን የሚመጥን.... ​"ታፈቅራታለህ?" "አላፈቅራትም!" "ጠጥተህ ሰክረህ ነበር?" "አረ! መጠጥ የሚባል አላሸተትኩም፣ እንኳን ልጠጣ!" "ሰልችቸሃለሁ?" " መቸም አትሰለችኝም፣ መቸም" "እና ለምን...?" "እኔጃ! በቃ አላውቅም!" አለ እንባ እየተናነቀው። ​የሰጠኝን ቀለበት ወርውሬለት ሄድኩ። ስድስት ወር ለመነኝ፣ አስለመነኝ፤ በጭራሽ አልኩ። ቆይቶ አንድ ልጅ ጋር ተዋወቅኩ። ጎረቤታችን የተከራየ የመንግሥት ሠራተኛ። ያሬድ ጋር በተለያየን ሰሞን፣ በቅንጡ መኪና የተመላለስኩበትን የሰፈሬን ኮብልስቶን መንገድ በእግሬ ስኳትን ያገኘሁት ሰው ነው። አብሮ በመኳተን ፀባዩና ትህትናው ማረከኝ። አቀርቅሮ የተማረ፣ ስልጡን ትሁት ነፍስ። ቅርርባችን ወደ ፍቅር አደገ። ሻይ ቡና ጀመርን። የኪራይ ቤቱ ጎራ ማለት ጀመርኩ። እሾህን በእሾህ ነው ብየ ከአመት አካባቢ በኋላ ቅልብጭ ባለች ሰርግ ተጋባን። አንዳንዱ እሾህ ሲያመረቅዝ ይኖራል። ያ ለካፊ እንደመጣ እንኳን ሳላየው፣ "መልካም ድህነት" ብሎ ቦርዱ ላይ ጻፈ። ሟርተኛ! ​ልክ ነበር፤ ገና ባገባሁ በሁለተኛ ዓመቴ ፀጉር የሚያቆም ድህነት ጋር ተፋጠጥኩ። የጠንቋይ ልጅ! ሀብቱንስ ያገኘው ጅብ ጋልቦ እንደሆነ ምናባቱ ይታወቃል? ይህን ሳስብ ነበር ደግሞ ነፍሴም በድህነት ቡጢ እየተጠናገረች መሆኑ የገባኝ። ድህነት ቃላትንም ቅላፄንም እሾህ ያደርጋል። ኑሮ ምቾት ሲነሳኝ በያሬድ ምቾት በቅናት ተቃጠልኩ። እርሱ በተልከሰከሰ እኔ ዋጋ መክፈል ነበረብኝ? ለምቾቴስ ብየ እንዳላየሁ ማለፍ ነበረብኝ? የአገራችን ሕይወት ለኩራትም ለይቅርታም አይመችም። ብር ብር ብቻ አልሆነም! "ጎልድ ዲገር" ባዮ ሁሉ ወርቁ ቢገኝ እስከምድር ወገብ ሊቆፍር ዶማውን ይዞ የሚዞር ነው። በዚህ ዘመን ማንም ቢያሟርት ደሃ ላይ ይደርሳል። ነብይ መሆን አይጠይቅም። ​በቀደም ታዲያ መንገድ ላይ ፀሐይ ሲከካኝ አገኘኝና መኪናውን አቁሞ "ግቢ" አለኝ። ኩራት እየተናነቀኝ፣ ግን ደግሞ መሃል አናቴን እንደጌሾ ያኮሸለለው ፀሐይ ገፍቶኝ ገብቼ ተቀመጥኩ። ምናልባትም የወሬ ጉጉት! መኪና ከትዳር ይመቻል። ደግሞ ቅዝቃዜው! ደግሞም ደስ የሚል ሽታው። የእራሴ ላብ ጠረን መኪናውን የሞላው እስኪመስለኝ የመቆሸሽ ስሜት ተሰማኝ። ​"ደህና ነሽ?" አለኝ። "አይመለከትህም፤ እንደውም ወራጅ!" እንደእብድ አደረገኝ። ​ወሬዬ ሁሉ የደሃ ሆኗል፤ "ወራጅ" የታክሲ ቋንቋ ነው። አላቆመም። እኔም እንደገና "ወራጅ"ን አልደገምኳትም። ነገር ነገር አለኝ፤ ይሄን ምቾት፣ ይሄን ሰላም፣ ይሄ ጎኔ የተቀመጠው ሰው የነጠቀኝ መስሎ ተሰማኝ። "እሱ ሰጠ፣ እሱ ነሳ፤ የሰው ነገር የሰው ነው" ብዬ ማለፍ አልቻልኩም። ነገር አማረኝ፤ አፌን መክፈት አማረኝ... ​"ፍቅሬን፣ እምነቴን ያለምንም ምክንያት ረጋግጠህ አንዲት ዱርዬ ጋር ተጋደምክ!" አልኩት። መንገዳችን ላይ አይኔን ተክየ። ለታክሲ የተሰለፈ ፀሐይ ያደረቀው ህዝብ፣ በዓል ሰሞን ነውና በጎች፣ በሬ መንገዱ ላይ ይርመሰመሳል። እንደዛ በግ፣ እንደዛ የኔ ቢጤ፣ እንደነዛ ተሰላፊወች ነኝ ከዚህ ሲመለከቱኝ። ተበሳጨሁ። ​እንደተረጋጋ "ልክ ነሽ፤ እንደ እንስሳ ራሴን መቆጣጠር ተስኖኝ የማይሆን ነገር ሠራሁ" አለና መሪውን በመዳፉ መታው። መሪው ምን ያርግ ዘዋሪው እንጅ መጠርቀም ያለበት። ​"እንደ እንስሳ አይደለም፣ እንደ ውሻ ነው የተልከሰከስከው!" አልኩት። "ውሻም እንስሳ ነው" አላለኝም። ​"አዎ፤ እንደ ውሻም፣ እንደ አህያም! ልክስክስና ደደብ ሆኜ አንድ ቀን የማይሆን ነገር ሰራሁ። አንድ የተረገመ ቀን! አንቺ ግን የልብ ይቅርታዬን ወርውረሽ፣ በትዳር ስም እኔ የሠራሁትን ለዘላለም ልትሰሪው ወሰንሽ" ​መኪናውን አቆመ፤ ሰፈሬ አድርሶኝ ነበር። እንዴት ሰፈሬን አወቀው? ምንም ሳልናገር ወርጄ ሄድኩ። "በትዳር ስም የማመነዝር ነው የሚመስለው?" አዘገምኩ፤ ወደምኖርበት ከከተማ የወጣ ኮንዶሚኒየም፣ አራተኛ ፎቅ ላይ ባለቤቴ ጋር ወደምኖርበት ድህነት። የጠንቋይ ልጅ! ቀና ብየ ህንፃውን ሳየው ጧት አስጥቻቸው የሄድኩት የባሌ ሁለት ሸሚዞች ህዝቡ ተሰዶ ባዶውን እንደቀረ አገር ባንዲራ በግዴለሽነት ይወዛወዛሉ። በትዳር ስም የማመነዝር መሠለኝ! ዞር ብየ ተመለከትኩ የአዲስ አበባ መብራት ፏ ብሏል። ስንት ያየሁባት ከተማየ እንደምራቅ የተፋችኝ መሠለኝ። የተሰደድኩ መሰለኝ...ሱዳን፣ ሊቢያ ቁሜ አዲስ አበባን በትዝታ የማያት!

፪ ታውቃለህ ? ሕይወት ለሴት ሌላ ናት… ጨካኝ ናት። ስነቃ ዙሪያዬ በእርጉዝ፣ ዙሪያዬ በሰርግ፣ ዙሪያዬ በ“ቆመሽ ቀረሽ” ምክር ታጅቦአል። አንተ እንደ መጀመሪያው አፍላ ፍቅር፣ አፍላ ጭቅጭቅ፣ አፍላ መውደድ ላይ ነህ። ኩርፌያዬ፣ ስጋቴ፣ ጭቅጭቄ ውስጥህ አልዘልቅም አለ። ቁም ነገር የሌለው ፍቅር፣ ያልበሰለ ፍቅር፣ ነገ የሌለው ፍቅር፤ 'አቤት እዚ ጋ ነኝ' የማይሉት ፍቅር ከወንድ በላይ ለሴት ምቾት አይሰጥም። የማይታገል ወንድ፣ ሃላፊነት የማይሸከም ወንድ፣ “እከለልበታለሁ” የማይሉትን ወንድ፣ “አለልኝ” የማይባል ወንድን ባል ማድረግ ያስፈራል። አስቴር አወቀ “ጠይም ዘለግ ያለ፣ የሰፋው ደረቱ ፍቅር ሃላፊ ነው ባረገኝ እህቱ…” እንዳለችው ነው። ፍቅር ሃላፊ እንደሆነ አስተዳደጌ ነግሮኛል ... አያያዛችን ... ፍቅሩ ሲያልፍ፣ የኑሮን ቀንበር ስንሸከም፣ ሲያንገዳግደን፣ ሃላፊነት ሲወጥረን፣ ልጆች ሲመጡ ....... ጫንቃችን “አልተዘጋጀም” አልኩኝ። እንዳላጠናክርህ የምለው አይገባህም፤ እንዳታጠናክረኝ አልጠነከርክም። ልቤ እየወደደህ አልረጋ አለ… “የት ነሽ?” ስባል “እዚ ጋ” ማለት ተሳነኝ፤ ልቤ ሸሸክ… ሄድኩኝ። የተለየውህ እንደ ዋዛ አልነበረም፤ ሌት ቀን አስቤ "ያልበሰለ ሰው ፍቅር አያሻግረም ብዬ እያዘንኩኝ ነው " © Adhanom Mitiku

፩ ታውቂለሽ ..... ? ተኩሰሽ ብትገይኝ ይታረድ ስለተባለ ስቃይ እንዳይበዛብኝ ነው የተኮሰችብኝ ነው የምለው.... አንቺ ለኔ እንደህልሜ ከልቤ ጠፍተሽ አታቂም ። ሌላ ቦታ ያለዉ ቸልታዬ አንቺ ጋ ሲደርስ አቅም አንሶት ይተጋል ተጎድቼ እምጨነቀው ጉዳቴን የምነገርሽ መንገድ ነው.... ድንገት ተለያየን እንደዋዛ ታውቂኝ የለ ስቃይን መሸከም ፣ የተሰማኝን አምእሮዬ ውስጥ ማስቀመጥ እችላለሁ .... እንዳልናፈቀ፣ እንዳልተጎዳ መሆን መንገዴ አስተምሮኝ የለ? ብንለያይም ልቤ አልተለየሽም ነበር . .... ልቤ ያላዜመሽ ያላወሳሽ ያልተረከሽ ቀን የለም ..... ሲሳካልኝ ፣ስወድቅ ፣ ሲደብረኝ ፣ የልቤን ሳወራ ከትውስታ ከትዝታዬ መሀል እየወጣሁ የማወሳሽ ሚስጥሬ ነሽ ታሪኬ ነሽ .....ትዝታዬም አንቺ ግን ሶስት ወር የምታቂውን ሰው ልታገቢ ነው??! ታድለሻል .....! እኔ የዘገየሁት እራሴን እየጠረብኩ፣ እየቀረፅኩ ፣ እያበጃጀሁት ነበር፣ ...... ያልመጣሁት መቀየሬን ላሳይሽ ፣ ማደጌን ላስዳስስሽ ነበር... ስደርስ ግን በሌላ መንገድ እየሄድሽ ነው.... የውነት ግን ደስተኛ ነሽ ?? ይሁን..... የኔን ግን እንዳልኩሽ ነው @Adhanom Mitiku

፪ ታውቃለህ ? ሕይወት ለሴት ሌላ ናት… ጨካኝ ናት። ስነቃ ዙሪያዬ በእርጉዝ፣ ዙሪያዬ በሰርግ፣ ዙሪያዬ በ“ቆመሽ ቀረሽ” ምክር ታጅቦአል። አንተ እንደ መጀመሪያው አፍላ ፍቅር፣ አፍላ ጭቅጭቅ፣ አፍላ መውደድ ላይ ነህ። ኩርፌያዬ፣ ስጋቴ፣ ጭቅጭቄ ውስጥህ አልዘልቅም አለ። ቁም ነገር የሌለው ፍቅር፣ ያልበሰለ ፍቅር፣ ነገ የሌለው ፍቅር፤ 'አቤት እዚ ጋ ነኝ' የማይሉት ፍቅር ከወንድ በላይ ለሴት ምቾት አይሰጥም። የማይታገል ወንድ፣ ሃላፊነት የማይሸከም ወንድ፣ “እከለልበታለሁ” የማይሉትን ወንድ፣ “አለልኝ” የማይባል ወንድን ባል ማድረግ ያስፈራል። አስቴር አወቀ “ጠይም ዘለግ ያለ፣ የሰፋው ደረቱ ፍቅር ሃላፊ ነው ባረገኝ እህቱ…” እንዳለችው ነው። ፍቅር ሃላፊ እንደሆነ አስተዳደጌ ነግሮኛል ... አያያዛችን ... ፍቅሩ ሲያልፍ፣ የኑሮን ቀንበር ስንሸከም፣ ሲያንገዳግደን፣ ሃላፊነት ሲወጥረን፣ ልጆች ሲመጡ ....... ጫንቃችን “አልተዘጋጀም” አልኩኝ። እንዳላጠናክርህ የምለው አይገባህም፤ እንዳታጠናክረኝ አልጠነከርክም። ልቤ እየወደደህ አልረጋ አለ… “የት ነሽ?” ስባል “እዚ ጋ” ማለት ተሳነኝ፤ ልቤ ሸሸክ… ሄድኩኝ። የተለየውህ እንደ ዋዛ አልነበረም፤ ሌት ቀን አስቤ "ያልበሰለ ሰው ፍቅር አያሻግረም ብዬ እያዘንኩኝ ነው " © Adhanom Mitiku

photo content

፩ ታውቂለሽ ..... ? ተኩሰሽ ብትገይኝ ይታረድ ስለተባለ ስቃይ እንዳይበዛብኝ ነው የተኮሰችብኝ ነው የምለው.... አንቺ ለኔ እንደህልሜ ከልቤ ጠፍተሽ አታቂም ። ሌላ ቦታ ያለዉ ቸልታዬ አንቺ ጋ ሲደርስ አቅም አንሶት ይተጋል ተጎድቼ እምጨነቀው ጉዳቴን የምነገርሽ መንገድ ነው.... ድንገት ተለያየን እንደዋዛ ታውቂኝ የለ ስቃይን መሸከም ፣ የተሰማኝን አምእሮዬ ውስጥ ማስቀመጥ እችላለሁ .... እንዳልናፈቀ፣ እንዳልተጎዳ መሆን መንገዴ አስተምሮኝ የለ? ብንለያይም ልቤ አልተለየሽም ነበር . .... ልቤ ያላዜመሽ ያላወሳሽ ያልተረከሽ ቀን የለም ..... ሲሳካልኝ ፣ስወድቅ ፣ ሲደብረኝ ፣ የልቤን ሳወራ ከትውስታ ከትዝታዬ መሀል እየወጣሁ የማወሳሽ ሚስጥሬ ነሽ ታሪኬ ነሽ .....ትዝታዬም አንቺ ግን ሶስት ወር የምታቂውን ሰው ልታገቢ ነው??! ታድለሻል .....! እኔ የዘገየሁት እራሴን እየጠረብኩ፣ እየቀረፅኩ ፣ እያበጃጀሁት ነበር፣ ...... ያልመጣሁት መቀየሬን ላሳይሽ ፣ ማደጌን ላስዳስስሽ ነበር... ስደርስ ግን በሌላ መንገድ እየሄድሽ ነው.... የውነት ግን ደስተኛ ነሽ ?? ይሁን..... የኔን ግን እንዳልኩሽ ነው @Adhanom Mitiku

"ሴት ልጅ ፈፅሞ የማትረሳው ወንድ" (አሌክስ አብርሃም) ብዙ ወንዶች "ሴት የመጀመሪያዋን ወንድ በህይወት ዘመኗ ሁሉ አትረሳም የሚል ያረጀ ያፈጀ ነገር ሰምተው የመጀመሪያ ለመሆን ሲጋደሉ ይታያሉ!(ሲጋደሉ ይገባችኋል) ወንድ መቸስ ለጅል ድርጊቱ ሁሉ ሐውልት እንዲቆምለት የሚፈልግ ፍጡር ነው። እስኪ አሁን ላለመረሳት እንትን 😁 የሆነ ሆኖ ዛሬ የገረመኝንና ይሄን አመለካከት ውሃ የሚያስበላ ነገር አነበብኩ፤ ከአራት ሺ በላይ ሴቶች ከመላው አለም ጠይቂያለሁ ይላል ፀሐፊው ፤ እና ሴቶች ፈፅሞ የማይረሷቸው ወንዶች ብሎ አንደኛ ደረጃ ላይ ያስቀመጠው ምን ቢሆን ጥሩ ነው? (ምን አይነት ስክራፓጯሯሟሷ የሆነ ፆታ እንደሆነኮ) "አብሯቸው በዝናብ ውስጥ የሮጠ ወንድ ፈፅሞ አይረሱም " ይላል። ከምር ገርሞኛል። ካስቀመጠው ምክንያት አንዱ The "Us Against the World" Feeling ይለዋል። ስንፈስረው ሲዘንብ ሁሉም ሰው እየሮጠ ይጠለል የለ? በቃ እኔና አንች ሁነን ዓለም የሚፈራውን አድቬንቸር ተጋፈጥነው፣ አንች ጋር ከሆንኩ ምንም አልፈራም እንደማለት ነው ለሴቷ። ለወንዱ ደግሞ ሜካፔ ታጥቦ ፀጉሬ ተንጨባሮ ክብሬ ምናምኔ ከሚል ፍርሃት በላይ አብሬህ የትም እገባለሁ የሚል መልእክት ይፈጥርበታል። ዙሮ ዙሮ ወንዱ ዝናቡ ሲቆም ይረሰዋል ሴቷ ግን ለዘመናት በዘነበ ባጉረመረመ በጠረረ ሰዓት ሁሉ በዝናብ የቀጨመ ፀጉሯን እያከከች ታስታውሰዋለች ይላል። (እንግዲህ የሮጣችሁ መስክሩ) እኔኮ አንዲት የሰፈሬ ልጅ በተገናኘን ቁጥር ህፃናት ሁነን የሩፋኤል ዝናብ ውስጥ የቦረቅነውን ስታነሳ ማስታወሷ ይገርመኝ ነበር! እስከአሁን በዝናብ ውስጥ ሲሮጡ የተነሱትን ፎቶ የለጠፉ ፍቅረኞች አልገጠሙኝም። አላችሁ? ሞክሩት የባዝ ሩም ፎቶ ሰልችቶናል¡ የሆነ ሆኖ አሁን ሁለት ጠቃሚ ሀሳብ አለኝ ... 1. ከአሁን በኋላ ከእህቶች ጋር ራት የመብላት ዕድል ከገጠመኝ የአየር ትንብያ ቀድሜ አይቸ ነው ቀጠሮ የምይዘው፤ ዶፍ በሚወርድበት ቀን ሐምሌ 23 ወይም ነሐሴ 19 ምናምን ! ወይ በዝናብ ሩጦ ዘላለም መታወስ ነው አልያም "አባቴ በዚህ በዝናብማ አንሄድም እዚሁ እንደር?" የሚል አማራጭ ነው። እሽ አንች ቅደሚ ወደሩማችን እማየ፣ አንተ ቅደም አባየ ... የተባረከ ጥናት! 2. ሰርጎች በዝናብ ቀን አውላላ ሜዳ ላይ ቢደገሱ ፍች የሚቀንስ አይመስላችሁም? በዝናብ ውስጥ ከሮጡ ሲጋቡ አይረሳሱም፣ መንጨባረሩንም ከቀን አንድ ጀምሮ ይለምዱታል😁 ማሳሰቢያ ፦ ሴትን ልጅ ካለፍላጎቷ ዝናብ ውስጥ መጎተት የዝናብ ውስጥ ፆታዊ ጥቃት ነው!!

"ይቅርታ...! ብዙ አለመውደዴ እና አለመብሰሌ ነው እንደዛ እየፈለግሽኝ ሳልጠነቀቅልሽ፥ ስሜትሽን ሳላስታምመው ችላ ያልኩሽ" አልኳት። "ጥሩ ልጅ እንደሆንሽ ግዜ አሳይቶኛል፣ መልካም ልጅ እንደሆንሽ የሆንሽልኝ ነገሮች በግዜ ብዛት የበለጠ ተገልጦልኛል " አልኳት። ትንሽ በስሱ ፈገግ ብላ... " እንኳን ተውከኝ..! ብዙ ቀን አግኝቼ እንኳን ተውከኝ ማለት ፈልጌ ነበር ... መበሻሸቅ ይመስልብኛል ብዬ ነው የተውኩት።" "ስለተውከኝ ... ስለገፋኸኝ ...ከመጤፍ ስላልቆጠርከኝ ... ስንት ቀን እያሰብኩ ሃሴት ተሰምቶኝ ያውቃል። ያሁኑን ባሌን በየት በኩል አገኘው ነበር? አንተ ባትገፋኝ፤ ብዬ መሰለኝ። መገፋትን ማጣጣሜ ይሆናል ፍቅር በዚህ መጠን እንዲገባኝ ያደረገኝ ብዬም ይሆናል፤ የጠፋኝ ቦታ ስለተገኘልኝ ደስ ብሎኝ ይሆናል። ብቻ እንኳን ተውከኝ ! የቆምንበትን ስፍራ የምናጣጥመው በመጣንበት መሰላል ላይ ተንጠላጥለን አይደል? እጃችን ላይ ያለው ክብደት መጠን ቀድሞ የያዝነው ነገር ክብደት እንድንዝል እና እንድንበረታ የሚያደርግ ሃይል አለው አይደል? በዚህ መጠን መወደድ እንደሚገባኝ፤ ቆንጆ እንደሆንኩ፤ የራሴን ስሜት እና ፍላጎት ቦታ መስጠት እንዳለብኝ፤ ፍቅር ካጉል ስጋት እና ካጉል ቅናት ውጪ መቆም እንደሚችል፤ ህልሜ ላይ ማታኮር እንዳለብኝ፤ የአጋሬ ህልም እንዲሳካ አስተዎጽዖ ማበርከት እደምችል አንተ ባትተወኝ ኖሮ በምን አውቅ ነበር?? አንዳንድ ሰው የሚውልልን ገፍቶን ነው !! አለመፈለግን በደንብ ስላሳየኻኝ መፈለግ ውስጥ ያለን ውበት አየሁት !! ሳትኮራብኝ ስትቀር ሲኮራብኝ የሰጠኝ ምቾት ልቤ ላይ ሃሴት አፈሰሰልኝ ። ያኔ እንዴት መኖር ደስስ እንዳለኝ ለስሜቴ ሲጠነቀቅ ሴትነቴ ጎላልኝ ። ሳከብረው እና ማክበሬን እውቅና ሲሰጥልኝ የሚ'ሰሙትን ስሜቶች አየኾቸው ። አንዳንድ ጉዳቶች በየት በኩል አግኝተው እንደሚጠቅሙን አናውቅም። የሆነው ሁሉ ሆኖ ሳለ... ስለተውከኝ አመሰግናለሁ ስል ምክንያቴ ብዙ ነው ። © Adhanom Mitiku

ሳገባ የሚስቴ እናት ልጄን በምንም ምክንያት እንዳታስቀይማት እንዳታስከፋትም ጭምር አለችኝ። በእርግጥ ንግግሩ እንግዳ አልሆነብኝም። እንደማንኛውም እናት ለልጇ በደንብ የምትመክረኝ አማት ነበረች። ከትዳራችን ከሶስት አመት በኋላ እኔና ሚስቴ በሆነ ነገር እየተጨቃጨቅን እንደነበር አስታውሳለሁ ስህተት ሰርቻለሁ አውቃለሁ። ይቅርታ ሳልጠይቃት በንዴት ከቤት ወጥታ አደረች። ሚስቴም በሚቀጥለው ቀን ወደቤት ተመለሰች። ነገር ግን ግራ በሚያጋባ ሁኔታ ስታየኝ ተመለከትኳት። አንዳንዴ ኩሽና ጠረጴዛ ላይ ተቀምጣ ጣሪያው ላይ እያፈጠጠች አገኛታለሁ። እና ከሌላ ቀን በተለየ መልኩ ፀጉሯ ጠቁሮና ረዝሞ ከጉልበቷ በታች ሲወዛወዝ አየው። በጣም ያምር ነበር። እስከዛሬ ባላየውም ዛሬ ግን የፀጉሯን እርዝመትና ልስላሴ በደንብ አስተዋልኩት። ማታ በጣም ተነፋፍቀን ስለነበር ለመጀመርያ ግዜ ረጅም ሰዓት ወሲብ ፈጸምን። ጠዋት ስነሳ አልጋዬ ጋር የለችም። ወደሳሎን ሰሄድ ሶፋ ላይ ተቀምጣለች። በተቀመጠችበት ትቻት ወደ መታጠቢያ ቤት ስሄድ ኮቴ ሰማው። በድንገት ዞር ብዬ ስመለከት ከኋላዬ በከባድ ሁኔታ እያየችኝ አየዋት። ዛሬም መሽቶ ነጋ። ፀባችንን በእርቅ ሰላም ካሰፈንን ሁለት ቀን አለፈ። ታድያ በነጋታሁ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ከፍተኛ የውሃ ጥም ለቆብኝ ተነሳሁ። ሚስቴ እንደተለመደው አልጋ ላይ የለችም። ወደሳሎን ስሄድ ግርግዳውን በግንባሯ እየፈተገች አገኘዋት። በጣም ደነገጥኩ ልቤ ተወርውሮ የሚወጣ መሰለኝ። ከዚህ በላይ መሄድ አልቻልኩም። ባለችበት አልፌያት ሄድኩ። እሷ ግን እንዳፈጠጠችብኝ ነበር። በሚንቀጠቀጠው እጄ ስልኩን አንስቼ እናቷ ጋር ደወልኩ። ከሚስቴ ጋር ያጋጠመንን ፀብ እና ስለ ልጅዋ አጠራጣሪ ባህሪ ልነግራት ስል አቋረጠችኝና “አታስቀይማት አታስከፋት አላልኩህም ነበር” አለችኝ። እኔ፦“ስለ ፀባችን እንዴት አወቅሽ?” የሚስቴ እናት መለሰችልኝ፦ “ሚስትህ ሁለት ቀን ሙሉ ከኔ ጋር ነበረች። ለምን እርቅ ለመፈጸም አልመጣህም!” ☠ @Armemo_offical