ለዒድ አል-አድሃ በዓል የሀገር ቤት ጉዞ
—————
ክፍል 1
ለሙስሊሞች መደሰቻ ሁለት ታላላቅ በዓላትንና የጁምዓ እለትን ለደነገገው ለዓለማቱ ጌታ አላህ የላቀ ምስጋና ይገባው!!። እንደሚታወቀው ከነዚህ ውጪ ሌላ በሸሪዓ የተደነገገ ከቁርኣንና ከሀዲስ ማስረጃ ያለው ኢስላማዊ በዓል የሚባል ነገር የለም!!። እነዚህ በዓላትም መለኮታዊና ከአምልኮ የተያያዙ ናቸው።
በዚህ በተከበረው የዚል-ሒጃ ወር አቅማቸው የፈቀደላቸው ሰዎች፣ የጉዞውን ጣጣ የቻሉ ሰዎች የተከበረውንና መጎብኘቱ ግዴታ የሆነውን ብሎም መጎብኘቱ ከአምስቱ የእስልምና ማእዘናት የሆነውን የአላህን ቤት ለመጎብኘት የሚጓዙት በርካቶች ናቸው።
ይህን ያልቻሉ ደግሞ ቤተሰባቸው የተለያየ ክ/ሀገራትና ገጠር ያሉ ወገኖች ከቤተሰባቸው ለማሳለፍ ወደተለያዩ ክ/ሀገር ከተሞችና ገጠር ይጓዛሉ። ይህ ጉዞ አላህን ማመፅ ካልተቀላቀለበትና እስከ ፍፃሜው አላህን መታዘዝ ከሆነ ምንኛ ያማረ ጉዞ ነው!።
ይህ ጉዞ ለመልካም ነገርና ለቤተሰብ ዚያራ በመሆኑ የሚያስደስትና እጅግ የሚወደድ ቢሆንም፣ ተጓዦች አላህ (ይጠብቀንና) አላህን አያምፁበትም ፍፁም የሆነ ጉዞ ነው ማለት ግን አይደለም። በመሆኑም ተጓዦች ከእነዚህ አላህን በእጅጉ ከሚያስቆጡ ስህተቶች እንዲቆጠቡ ማስታወሱ ግድ ነው።
» እንዲያውም ገና ጉዞው ሲጀመር በተከበረው ዘጠነኛው ቀን፣ ያንን (የዚል-ሂጃ 9ኛ) ቀን መፆሙ ያለፈውንና የሚቀጥለውን ዓመት ወንጀል ያስምራል በተባለው የተከበረ ታላቅ ቀን፣ አላህ ሀራም ያደረገውን የከበደ ወንጀል አደንዛዥ እፅ የሆነውን ጫት እየበላ የሚጓዘው ህዝብ ከተጓዦች አብዘሃኛው ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም!። ጥቂት አላህ ያዘነላቸው ባሪያዎቹ ሲቀሩ አብዘሃኛው ተጓዥ ይህን አደገኛና አላህ ሀራም ያደረገውን አደንዛዥ እፅ እየበላ መጓዝ የተለመደ እየሆነ ነው።
በዚሁ አጋጣሚ ጫትን ለማይቅሙትና የዲን እውቀት ላላቸው ለጥቂቶች አንድ መልእክት አለኝ:- (ከሚቅሙ ሰዎች ጋር ተቀላቅላችሁ የምትሔዱ ካላችሁ በራሳችሁ ላይ አንድ ግዴታ ነገር ጥላችኋል፣ እሱም:- የተወገዘን ነገር ማውገዝ ነው!። አላህ ሀራም ያደረገውን ነገር ሲተገበር ዝም ካላችሁ እንደ ዲዳ ሸይጧን መሆናችሁን አትዘንጉ!፣ ማውገዝ ወይም መከልከልና ደዕዋ ማድረግ ካልቻላችሁ ጫት ከማይቅሙና ዘፈን ከማይከፍቱ ከቢጤዎቻችሁ ነው መሄድ ያለባችሁ።)
ታዲያ በጥቅሉ ጫትን በየተኛውም ጊዜ የምትቅሙ ሰዎች አላህን ልትፈሩ ይገባል!! ምንም ጥቅም የሌለውን አካልን የሚጎዳ፣ ገንዘብን የሚያባክን፣ አደንዛዥ የሆነን ነገር ሸሪዓችን እርም አድርጓል።
↪️ ጫት አካልን ጎጂ መሆኑን ታምኑበታላችሁ! እራስን የሚጎዳ ነገር መጠቀም ደግሞ አላህ ሀራም አድርጓል!!
↪️ ጫት ምንም አይነት ጥቅም እንደሌለውና ገንዘብን እንደሚያባክን ታውቃላችሁ!!
አባካኞች የሸይጧን ጓዶች መሆናቸውን ደግሞ አላህ በቁርኣኑ ተናግሯል።
↪️ ጫት አዕምሮን እንደሚቀይር ታምናላችሁ! አዕምሮን የሚቀይር ነገር ደግሞ ከአስካሪ መጠጥ ነው።
አስካሪ መጠጥ በእስልምና ሀራምነቱ ደግሞ እንኳን ለሙስሊሞች ለከሀዲውም ግልፅ ነው!!
እነዚህን ጥቂት ጫትን ሀራም የሚያደርጉ ነጥቦች አብዘሃኛው ጫት ቃሚ "ለእውነት ሲባል" ብሎ ያመነባቸውና የጤና ባለ ሞያዎች ያረጋገጡት እውነተኛ ጫት የሚያስከትላቸው አደጋዎች እንጂ ከራሴ የሆኑ ፈጠራዎች አይደሉም!።
ከላይ ለጠቀስኳቸው ነገሮች ማስረጃን ያልጠቀስኩት ከምንም በላይ ማስረጃው ግልፅና የሚታወቅ ከመሆኑ አንፃር ፅሁፉ እንዳይረዝም ብዬ ነው።
➡️ ከዚህ ጉዞ ሌላው ጥፋትና ከባድ ወንጀል ዘፈን፣ ነሺዳና መንዙማ እየተደመጠ መጓዙ ነው!!። ዘፈን አንዳንዶች ዘንድ ባህላዊ (በቋንቋቸው) ሲሆን ልክ እንደ ሙሃደራ (ሀዲስ) የሚቆጥሩት አሉ፣ ይህ ደግሞ በጥፋት ላይ ሌላ ጥፋት ነው።
በዘፈን ሀራምነት ሙስሊም ሆኖ የሚጠራጠር ያለ አይመስለኝም። አውቆ ማጣመም ፈልጎ ካልሆነ በስተቀር!፣ ምናልባትም ከአንዳንድ ጠሞ አጥማሚዎች ብዥታ የሚወድቅበት ሊኖር ስለሚችል እስቲ በጥቂቱ የሚከተሉትን ማስረጃዎችን እንመልከት፣ አላህ በተከበረው ቃሉ እንዲህ ብሏል:-
{
وَاسْتَفْزِزْ مَنِ اسْتَطَعْتَ مِنْهُم بِصَوْتِكَ} الإسراء ٦٤
“
ከእነርሱ የቻልከውንም ሰው በድምፅህ አታል።” አል-ኢስራእ 64
“
በድምፅህ አታል” የሚለውን በዘፈንና በአሎባልታ ጫወታ በዛዛታ ማለት ነው ተብሏል። ኢብን ከሢር የተሰኘው የቁርኣን ማብራሪያ ላይ ይህን አንቀፅ በሚያብራራው ቦታ ይመልከቱ።
አላህ የመልካም ባሪያዎችን ባህሪ ሲገልፅ በተቀደሰው ቃሉ እንዲህ ብሏል:-
{
وَالَّذِينَ لَا يَشْهَدُونَ الزُّورَ وَإِذَا مَرُّوا بِاللَّغْوِ مَرُّوا كِرَامًا} الفرقان ٧٢
“
እነዚያም በውሸት የማይመሰክሩ፣ በውድቅ ቃልም ተናጋሪ አጠገብ ባለፉ ጊዜ የከበሩ ሆነው የሚያልፉ ናቸው።” አል-ፉርቃን 72
“
ውድቅ ቃል” በማለት የተጠቀሰው ዘፈን ነው ተብሏል። ኢብን ከሢርን ይህን የቁርኣን አንቀፅ በሚያብራሩበት ቦታ ይመልከቱ።
አላህ በተቀደሰው ቃሉ ሙሽሪኮች ቁርኣን ከመስማት እንቢተኛ መሆናቸውንና ለቁርኣን ጀርባ መስጠታቸውን ሲያወግዝ እንዲህ ብሏል:-
{
أَفَمِنْ هٰذَا الْحَدِيثِ تَعْجَبُونَ{٥٩}وَتَضْحَكُونَ وَلَا تَبْكُون {٦٠}وَأَنتُمْ سٰمِدُونَ} النجم ٥٩–٦١
«
ከዚህ ንግግር ትደነቃላችሁን?፣ ትስቃላችሁምን?፣ አታለቅሱምን? እናንተ ዘንጊዎች ናችሁ።» አን-ነጅም 59-61
“
እናንተም ዘንጊዎች ናችሁ” የሚለውን ታላቁ ሷሃባ ዐብደላህ ኢብን ዐባስ እና ሱፍያን አስሰውሪ…የመሳሰሉ ሌሎችም “እናንተ ዘፋኞች ናችሁ” ማለት ነው የተፈለገበት በማለት ተናግረዋል። ኢብን ከሢር የቁርኣን ተፍሲርን ይመልከቱ።
ዐብደላህ ኢብኑ መስዑድ በጠንካራ ሰነድ “ዘፈን በልብ ውስጥ ንፋቅን እንደሚያበቅል” መናገራቸውም ተዘግቧል።
ስለ ዘፈን ሀራምነት ከቁርኣን አንቀፆች ባሻገር የተለያዩ እጅግ በርካታ ሶሂህ (ትክክለኛ) ሀዲሶች አሉ! ጊዜን ለመቆጠብና ፅሁፉ እንዳይረዝም ከሀዲስ ምንም አልጠቀስኩም።
ዘፈንና ነሺዳን በተመለከተ የቁርኣንና የሀዲስ ማስረጃዎችን በሰፊው ማንበብ የፈለገ የሚከተለውን ሊንክ ተጭኖ pdf ን አውርዶ ያንብብ።
ስለ ነሺዳና ዘፈን ⤵️ pdf
https://t.me/IbnShifa/933
✍🏻ኢብን ሽፋ (
t.me/ibnshifa)
የተለያዩ ት/ቶችን ለማግኘት የቴሌግራም ቻናላችን ⤵️ #join በማድረግ ይቀላቀሉ
https://telegram.me/IbnShifa
https://telegram.me/IbnShifa