ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Відкрити в Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Показати більше636
Підписники
Немає даних24 години
-47 днів
-1230 день
Архів дописів
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሐምሌ ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን #ለሰማዕቱ_ለቅዱስ_መርቆሬዎስ ቁጥር የሌላቸው ተአምራትንና ድንቆችን ባሳየበት በምስር አገር #ለቤተ_ክርስቲያን_ቅዳሴ_ቤቱና_ለልደቱ ዓመታዊ በዐል፣ #ለነቢዩ_ቅዱስ_ኄኖክ_ከሞት_ለተሰወረበት (ለዕርገቱ) በዐል፣ ከኒቆምድያ አገር ለሆነች ለሐዋርያዊት ለቅዱስ ጳውሎስ ረድእ #ለቅድስት_ቴክላ_ለዕረፍት_በዐል፣ ባና ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_እንዲኒና_ሰማዕትነት_ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዐል፣ #ለአባ_ይስሐቅ_ሰማትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል፣ በድሜራ አቅራቢያ ድምድል ከሚባል አገር ለሆነች #ለቅድስት_ኢላርያ ሰማዕትነት ለተቀበላችበት ለዕረፍት በዓል፣ ከእስክንድርያና ከባሕያራ አውራጃ ቀራቁስ ከሚባል መንደር ለሆኑ ለከበሩ #ቅዱሳት_ቴክላና_ሙጊ ሰማዕትነት ለቀበሉበት ለዕረፍት በዓል፣ ባንዋን ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_አበከረዙን_ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና ለሶርያው ሰው ለሰማዕቱ #ለቅዱስ_ዱማድዮስ_ለዕረፍት በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በፍቅር አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከስድስት_መቶ_ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው፣ አትሪብ ከሚባል አገር #ከሃያ_አምስት_ሽህ_ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው ረድኤትና እግዚአብሔር አምላክ በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚችም ዕለት የያሬድ ልጅ #ቅዱስ_ኄኖክን የመላልኤል ልጅ የቃይናን ልጅ የኄኖስ ልጅ የሴት ልጅ የአዳም ልጅ ኄኖክን መላእክት ይዘው አሳረጉት ይኸውም በመባርቅትና በነፋሳት ላይ ተጭኖ በመብረር ወደ ሰማይ ወስደው ከረቂቃን መላእክት ጋር አኖሩት የእግዚአብሔርም ትእዛዝ ጸሐፊ ተባለ።
❤ እንዲህም አለ "ከማደሪያው ከሚወጣው ከቅዱሱና ከገናናው በጸናች ኃይሉ ከሠራዊቱ ጋር በሲና ተራራ ከሚገለበጠው ጋር በመነጋገር ተመላለስኩ። ሁሉም ይፈሩ ነበር በውኃ ዳርም ሳለሁ የልመናቸውን መታሰቢያ ጻፍኩ እስከ አንጎላቸሁና ሕልም እንደሚያይ እስከምሆን ይችም በአርሞን ግራና ቀኝ ያለች አገር ናት"። በደብር ቅዱስ ለነበሩ ለኃጢአት ለሚተጉ ለሴት ልጆች ይዘልፋቸው ዘንድ ቃል እንደጠራውና እንዳሳየው ተናገረ።
❤ እንዲህ አለ "በበረድ ደንጊያ ወደ ተሠራ ታላቅ ቤት ቀረብኩ በበረድ ደንጊያ የተሠራ የዚያ ቤት ግድግዳ እንደ ሳንቃ ልዝብ ነው ከዚህ ቤት የሚበልጥም ሌላ ቤት አየሁ ደጃፉም የተከፈተ ነው በእሳት ቅጽርም የተሠራ በክብር ከሁሉ የሚበልጥ ነው። በውስጡም ከፍ ያለ የእግዚአብሔርን ዙፋን አየሁ መልኩም እንደ ውርጭ ነው አጎበሩም እንደሚያበራ ፀሐይ ነው ከዙፋኑም በታች የኪሩቤል ድምፅ ይሰማል። ዳግመኛም ወደ ሰባት ተራራዎች ደረስኩ ሦስቱ በምሥራቅ በኵል ሦስቱ በአዜብ በኵል ናቸው የመካከለኛው ግን ሰማይ ጠቀስ ነው የመላእክትም ጌታ በላዩ አለ"። ሌሎች አራት ገጾች ኪሩቤልን አየ ስለ ክርስቶስም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ "የዘመናት አለቃ ወደ ሆነው የሰው ልጅ ተጠራ ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ የነበረ ሆነ" ሁለተኛም "ለጻድቃን የጽድቅ በትር ለአሕዛብም ብርሃን ተስፋ ለሌላቸወሰ አለኝታ ይሆናል" አለ።
❤ በሰማይ ገጽ ስለሚመላለሱ ብርሃናት እንዲህ አለ "አንዱም አንዱ በየወገናቸው በሠለጠኑበትና በተሠየሙበት ጸንተው ይኖራሉ" ስለ ነፋሳትም መውጫዎች እንዲህ ብሎ ተናገረ "ሦስቱ በሰማይ ገጽ ሦስቱ በምድር ገጽ ሦስቱ በግራ ናቸው"። ስለ አዳምም እንዲህ አለ "እነሆ በሬ ከምድር ወጣ ፀዓዳም ሆነ" ስለ ሔዋንም "ሴት እምቦሳ ከርሱ ወጣች" አለ።
❤ ስለ ምኵራብም "ያንን አሮጌ ቤት እስከሚአሳንሰው ድረስ አየሁ አለ ምሰሶዎቹንም ከውስጡ አወጣ"። ስለ ቤተ ክርስቲያንም "ጌታ አዲስ የበጎች ቤት አምጥቶ እስቲሠራ ድረስ አየሁ ከቀድሞውም ቤት የበለጠ ነው በጎችም ሁሉ በውስጧ ይሠማራሉ" አለ። ስለ ምእመናንም "የእሊህም በጎች ፀጒራቸው ንጹሕ ነጭ ነው የተበተኑትም ከአራዊት ጋራ ይሠማራሉ ሁሉም በአንድነት ተሰብስበው ገራሞች ሁነዋልና"። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ኄኖክ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 27 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_መርቆሬዎስ፦ በዚች ቀን ቁጥር የሌላቸው ተአምራትንና ድንቆችን ባሳየባት በምስር አገር የቅዱስ መርቆሬዎስ ቅዳሴ ቤተ ክርስቲያኑ ሆነ። ልደቱም በዚሁ ዕለት ነው፡፡ ታሪኩን፦ ከኅዳር 25 ይመልከቱ።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያዊት_ቅድስት_ቴክላ፦ ይህችም ቅድስት አገሯ ኒቆምድያ ነው። በቅዱስ ሐዋርያ በጳውሎስ ዘመን ሐዋርያዊት ሆነች። ቅዱስ ጳውሎስም ከአንጾኪያ ከተማ በወጣ ጊዜ ወደ ኒቆምድያ ከተማ ሔደ በዚያም ስሙ ሰፋሮስ የሚባል ምእመን ሰው ነበረ ቅዱስ ጳውሎስን ወስዶ በቤቱ አኖረው ብዙ አሕዛብም የሐዋርያው የጳውሎስን ትምህርት ይሰሙ ዘንድ በእርሱ ዘንድ ይሰበሰቡ ነበር። ይህች ቅድስት ቴክላም በቤቷ መስኮት ተመለከተች የሐዋርያውንም ትምህርት ሰማች እንዲሁም ትምህርቱን እያዳመጠች ሳትበላና ሳትጠጣ ሦስት ቀኖች ቆየች ትምህርቱም በልቧ አደረ አባትና እናቷ ቤተሰቦቿ ሁሉ አዘኑ። ከምክርዋም እንድትመለስ ሐዋርያው ጳውሎስንም እንዳትከተል ለመኑዋት ነገር ግን አልሰማቻቸውም።
❤ ሁለተኛም አባቷ ወደ ንጉሡ ሒዶ ሐዋርያው ጳውሎስን ከሰሰው ንጉሡም ወደ እርሱ አስቀርቦ ስለ ሥራው ጠየቀው። ነገር ግን የሚቀጣበት ምክንያትን በላዩ አላገኘም ነበር። ሐዋርያው ጳውሎስንም እንዲአሥሩት አዘዘ።
❤ ይህች ቅድስት ቴክላም ልብሶቿንና ጌጦቿን ከላይዋ አስወገደች። ወደ ቅዱስ ጳውሎስም ሒዳ ከእግሩ በታች ሰገደች በእርሱም ዘንድ እየተማረች ተቀመጠች። ወላጆቿም በፈለጓት ጊዜ አላገኟትም በሐዋርያው ቅዱሰሰ ጳውሎስ ዘንድ እርሷ እንዳለች ሰዎች ነገሩዋቸው በመኰንኑም ዘንድ ከሰሱዋት እርሱም በእሳት እንዲአቃጥሉዋት አዘዘ። እናቷም "ስለርሷ ሴቶች ሁሉ እንዲገሠጹና እንዲፈሩ አቃጥሏት" እያለች ጮኸች ብዙዎች የከበሩ ሴቶች በሐዋርያው ጳውሎስ ትምህርት አምነው ነበርና እርሷ ግን በሚአቃጥሏት ጊዜ ልቧን አጽንታ ቅዱስ ጳውሎስን ተመለከተችው።
❤ ዳግመኛም ሲጸልይ ቅዱስ ጳውሎስን አወጡት በላይዋም በመስቀል ምልክት አማተበ። ራሷንም ወደ እሳቱ ምድጃ ወረወረች። ሴቶችም ያለቅሱላት ነበር። ያን ጊዜም እግዚአብሔር ብዙ ዝናብን በረድና መብረቅን ላከ የእሳቱም ምድጃ እንደ ቀዝቃዛ ጠል ሆነ ቴክላም ሩጣ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ተሠውሮ ወደ አለበት ቦታ ደረሰች ራሷንም ላጭቶ ትከተለው ዘንድ ለመነችው እንዲሁም አደረገላት።
❤ ወደ አንጾኪያ ከተማም በሔደች ጊዜ ከመኳንንቶች አንዱ ሊአገባት ፈለገ መልኳ እጅግ ውብ ነበረና እርሷም ዘለፈችው ረገመችውም እርሱም በዚያች አገር ገዥ በሆነ በሌላ መኰንን ዘንድ ከሰሳት እርሱም ለአንበሶች እንዲጥሏት አዘዘ። በአንበሶች መካከልም ሁለት መዓልት ሁለት ሌሊት ኖረች እነዚያም አንበሶች እግርዋን ይልሱ ነበር እንጂ ምንም አልከፉባትም።
❤ ከዚህም በኋላ በሁለት በሬዎች መካከል አሥረው በከተማው ውስጥ ሁሉ አስጐተቷት። ነገር ግን ምንም ምን ክፉ ነገር በላይዋ አልደረሰም ከዚያም በኋላ ለቀቁዋት። ወደ ቅዱስ ጳውሎስም ሔደች እርሱም አረጋጋት አጽናናትም። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንድትሰብክ አዘዛት።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሐምሌ ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቋ_ሰማዕት ሰይጣንን በራሱ ጠጉር ይዛ ለደበደበችው በእግሮቿም ለረገጠችው #ለቅድስት_መሪና ለዕረፍት በዓል፣ ከቀጰዶቅያ አገር ለሆነ በመስቀል ላይ ጌታችንን ከሞተ በኋላ የቀኝ ጎኑን ለወጋው #ለቅዱስ_ለንጊኖስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከአብጥልማዎስ ከመታሰቢያው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ሰማዕቷ_ቅድስት_መሪና፦ የዚችም ቅድስት የአባቷ ስም ዳኬዎስ ነበር እርሱም በአንጾኪያ ሀገር ለጣዖታት ካህናት አለቃ ነበር ያን ጊዜ ንጉሡም ከሀዲው ዳኬዎስ ነበር። አምስት ዓመትም በሆናት ጊዜ እናቷ ሞተች አባቷም ከከተማ ውጭ ለምትኖር ሞግዚት ሰጣት እርሷም ክርስቲያናዊት ነበረች የክርስቶስ የሆነ የሃይማኖት ትምህርትን ሁሉ አስተማረቻት። ዐሥራ አምስት ዓመትም በሆናት ጊዜ አባቷ ሞተ።
❤ ከዚህም በኋላ ሰዎች የሰማዕታትን ተጋድሏቸውንና መከራቸውን ሲናገሩ ሰምታ የጌታ ክርስቶስ ፍቅር በልቧ አደረ በሰማዕትነት መሞትንም ፈልጋ ሔደች።
በዚያን ጊዜም ከሀዲ መኰንን ወደዚያች አገር ደረሰ እርሷንም አይቶ ወደርሱ አስመጣትና "ከወዴት ነሽ" አላት "ክብር ይግባውና ከጌታ ኢየሱስ ሰዎች ወገን ነኝ ስሜም መሪና ነው" አለችው። ደም ግባቷንና ላሕይዋንም አይቶ መታገሥ ተሳነው እሺ ትለው ዘንድ በብዙ ነገር አባበላት። እርሷ ግን ረገመችው የረከሱ አማልክቶቹንም ረገመች።
❤ ያን ጊዜም በብረት ዘንጎች ይደበድቧት ዘንድ ደሟ እንደ ውኃ እስኪፈስ ሕዋሳቷን ይቆራርጡ ዘንድ አዘዘ። ያን ጊዜም ወደ ጌታ እግዚአብሔር ጸለየች የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም መጥቶ አዳናት። ሁለተኛም ወደ ወህኒ ቤት ያስገቧት ዘንድ አዘዘ ጌታችንም ወደ ሰማይ አውጥቶ የቅዱሳን ሰማዕታትንና የጻድቃንን ማደሪያዎች አሳይቶ ወደ ቦታዋ መለሳት። በማግሥቱም ሥጋዋን በመጋዝ እንዲሠነጥቁ ጐኖቿንም እንዲሰነጣጥቁና በእሥር ቤት እንዲጥሏት አዘዘ ያን ጊዜም የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ አዳናት።
❤ በወህኒ ቤቱ ውስጥም ቁማ ስትጸልይ እጅግ የሚያስፈራ ታላቅ ዘንዶ ወደ ርሷ መጣ በአየችውም ጊዜ ደነገጠች ሰውነቷ ሁሉ ተንቀጠቀጠ መናገርም ተሳናት። ያን ጊዜም እጆቿ በመስቀል ምልክት አምሳል እንደተዘረጉ በልቧም ስትጸልይ ወደርሷ ቀርቦ ዋጣት። ያን ጊዜም ሆዱ ተሠንጥቆ ያለ ጉዳት ወጣች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው።
❤ ሁለተኛም በጥቁር ሰው አምሳል ሰይጣንን አየችው እጆቹም በጉልበቶቹ ላይ ተጨብጠው ነበር። ፊቷንም በመስቀል ምልክት አማትባ በራሱ ጠጉር ይዛ ደበደበችው። በእግሮቿም ረገጠችው ያን ጊዜም ክብር ይግባውና የጌታ ክርስቶስ ዕፀ መስቀል ተገለጠላት በላዩም ነጭ ርግብ ተቀምጣ እንዲህ ብላ አነጋገረቻት "መሪና ሆይ የመንፈስ ቅዱስን የጸጋ አረቦን ተቀብለሻልና ደስ ይበልሽ"።
❤ በማግሥቱም መኰንኑ ልብሷን አራቁተው ዘቅዝቀው ሰቅለው እንዲአቃጥሏት ደግሞም ውኃ ከአፈሉበት ጋን ውስጥ እንዲጨምሩዋት አዘዘ። በውስጡም ሁና ስትጸልይ ከሰማይ ርግብ መጣ በአፉም ውስጥ የወርቅ አክሊል ነበር ማሠሪያዋንም ፈትቶ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሦስት ጊዜ አጠመቃት እግዚአብሔርንም እያመሰገነች ከውኃው ውስጥ ወጣች።
❤ መኰንኑም እንደ ዳነች በአየ ጊዜ ራሷን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ወደ ሰማዕትነቱ ቦታም በደረሰች ጊዜ ነፍሷን በፍቅር ይቀበል ዘንድ ወደ ጌታችን ጸለየች። ክብር ይግባውና ጌታችንም ተገለጠላት ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያዋንም ለሚያደርግ ገድሏንም ለሚጽፍ ወይም ለሚያነበውና ለሚሰማው ኃጢአቱን እንዲአስተሠርይለት ለርሷም ርሱን እንዲሰጣት ቃል ኪዳን ሰጣት።
❤ ከዚህም በኋላ ራሷን በሰይፍ ቆረጡ ከእርሷም ብዙ ተአምር ተገለጠ ዕውራን አይተዋልና፣ ሐንካሶች በትክክል ሔደዋልና፣ ደንቆሮዎችም ሰምተዋልና፣ ዲዳዎችም ተናግረዋልና ቁጥር የሌላቸው ብዙ ሰዎችም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቷ በቅድስት መሪና ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ወታደሩ_ሰማዕት_ቅዱስ_ለንጊኖስ፦ ይህም ቅዱስ ከጲላጦስ ጭፍሮች ውስጥ ነበር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ደኅንነት መከራ እንዲቀበል የፈቀደበት ሰዓት በደረሰ ጊዜ በእርሱ ላይ የፈለጉትን ያደርጉ ዘንድ ለዐመፀኞች ፈቅዶላቸው ነበር። ይህም ለንጊኖስ ጌታን ይሰቅሉት ዘንድ ጲላጦስ ከአዘዛቸው ወታደሮች ውስጥ ነበር።
❤ በመስቀል ላይ ከሞተ በኋላ ጌታችንን የቀኝ ጐኑን ወጋው ከጐኑም ደምና ውኃ ፈሰሰ። ይህንንም አይቶ እጅግ አደነቀ ከዚህም በፊት ፀሐይ እንጨለመ፣ ጨረቃ ደም እንደሆነ፣ ዐለቱም እንደተሠነጠቀ፣ ሙታንም እንደተነሡ አይቶ ነበር።
❤ ጌታችንም በተነሣ ጊዜ ስለ ትንሣኤው የሆነውን ሰምቶ ይህን ምሥጢር ይገልጽለት ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። ሐዋርያው ጴጥሮስንም ላከለት እርሱም ነቢያት ስለ ጌታችን፣ ስለ መከራው፣ ስለ መሰቀሉ፣ ስለ መሞቱ፣ ስለ መነሣቱ፣ ስለ ዕርገቱም ትንቢት እንደተናገሩ ነገረው። እርሱም ከቅድስት ድንግል በሥጋ ተወልዶ ዓለምን ለማዳን የመጣ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ እንደሆነ አስረዳው።
❤ ያን ጊዜም በቅዱስ ጴጥሮስ ቃል አመነ የምድራዊ ንጉሥ አገልግሎትንም ትቶ ወደ ቀጰዶቅያ ሔደ በውስጧም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንደ ሐዋርያት ሰበከ። አይሁድም በጠላትነት ተነሡበት በመሳፍንትም ዘንድ ከሰሱት በላዩም የሐሰት ምስክር አስነሡበት ስለዚህም ሐምሌ 23 ቀን ራሱን በሰይፍ አስቆረጡት የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ ቅዱስ ለንጊኖስ በጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 23 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለለንጊኖስ ዘኂሩተ አምላክ ቀጸበቶ። ለጴጥሮስ ረድእ ከመ ይትወከፍ ትምህርቶ። ከመ ኢያሐስብ ቦቱ ዘኲናለ እዱ ርግዘቶ። በኃጢውኢሁ ለዘኢፈቀደ ሞቶ። ምሕረቶ እሴብሕ ወዓዲ ትዕግሥቶ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ_23።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ኢይቀሥፍ ወትረ ወኢይትመዓዕ ዘልፈ። አኮ በከመ ኃጢአትነ ዘገብረ ለነ። ወኢፈደየነ በከመ አበሳነ"። መዝ 102፥9-10 ። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 9፥5-ፍ.ም፣ ያዕ 2፥14-20 እና የሐዋ ሥራ 16፥13-16። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 19፥31-38። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ የዮሐንስ አፈወርቅ ወይም እግዚእነ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ ቅዱስ በጥላንም ጥበብ ያደርግ ነበር። ያለ ዋጋም ሰዎችን ያድናቸው ነበር። ነገር ግን ክብር ይግባውና በክርስቶስ እንዲያምኑ ይሻ ነበር። ስለዚህም ጥበበኞች ሰዎች በእርሱ ላይ ተነሡ ወደ ንጉሥም ሒደው ከቄሱ ጋራና ከአዳነውም ዕውር ጋራ በጌታችንም ከአመኑ ከብዙዎች ጋራ ከሰሱት። ወደ ንጉሡም በቀረቡ ጊዜ ንጉሡ ተቆጥቶ "ለአማልክት ሠዉ" አላቸው ባልታዘዙለትም ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጠ። የሰማዕታት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።
❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ በጥላንንም የጸና ሥቃይን አሠቃየው። ከእርሱም ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ በእጁም ብዙ ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን አመኑ። በሰማዕነትም ዐረፉ። ንጉሡም አይቶ በበጥላን ላይ ተቆጣ። ለአንበሳም አስጣለው አንበሳውም እግሩን ላሰው እንጂ ክፉ አላደረገበትም። ሁለተኛም ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚህም ምስክርነቱን ሐምሌ 19 ቀን ፈጽሞ በመንግሥተ ሰማያት አክሊልን ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ በቅዱስ በጥላንና ከእርሱ ጋራ በሰማዕትነት በዐረፉ ሰማዕታት በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_ሰማዕታት_ስማቸው_ሱርስ_ኅርማን #ያኑፋ_ስንጣንያ_የሚባሉ_የእስና_አገር_ሰዎች የሆኑ፦ የሰማዕትነታቸው ምክንያትም እንዲህ ነው መኰንኑ አርያኖስ ወደ እስና ከተማ ሦስት ጊዜ ደረሰ። በመጀመሪያ የተባረከች መስተጋድልት የሆነች ዳላዢን ገደላት። ስማቸውን አስቀድመን የጠራናቸው አራቱን ልጆቿንም ገደላቸው። የሰማዕነታቸውም ፍጻሜ ግንቦት ሰባት ቀን ሆነ። ሁለተኛም ስማቸው አውሳፍዮስ ታማን ኅርማን ባኮስ የሚባል አራቱን መኳንንት ገደላቸው። የሰማዕታቸውም ፍጻሜ ሰኔ ሰባት ቀን ሆነ። ሦስተኛም ጊዜ በቤቷ ውስጥ በዐልጋዋ ላይ ተኝታ የነበረችውን አሮጊት የአርያኖስ ወታደሮች ስለ እነዚህ ቅዱሳን ከጠየቷት በኋላ ገደሏት።
❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከክርስቲያን ወገን ያገኙትን ሁሉ እንዲገድሉ የተክል ማጠጫ በተባለች በከተማዋ ምዕራብም መግደልን እንዳያቋርጡ አዘዘ ወደ ከበረ አባት ወደ ባሕታዊ ይስሐቅም እስኪደርሱ ድረስ በመንገድ ብዙ ሕዝብን አገኙ። ያን ጊዜም ጠባቂያቸው እንዲህ እያለ ያጽናናቸውና ያረጋጋቸው ነበር "ወደ ሰማያዊት መንግሥት እንድትገቡ ጸንታችሁ ታገሡ"። እንዲህም ሲወስዷቸው መኰንኑ ደረሰ በአዩትም ጊዜ ሁሉም በአንድ ቃል "እኛ ክርስቲያን ነን" እያሉ በግልጽ ጮኹ መኰንኑም ሁሉንም እንደበግ ያርዷቸው ዘንድ አዘዘ። ጭፍሮች ግን በላያቸው በሰይፎች አጋና ተጫወቱ። በዚችም በሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን የእስናን ከተማ ሰዎች ከታናሾቻቸው እስከ ታላቆቻቸው ሴቶችንና ወንዶችን ጨረሷቸው። የመላእክት ሠራዊትም ነፍሶቻቸውን ይቀበሉ የብርሃን አክሊሎችንም ያቀዳጁአቸው ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከዚያ ወደ እስዋን ከተማ ሔደ ሁለተኛም ወደ እስና ከተማ ተመለሶ ሦስት ገበሬዎችን የእርሻ ዕቃቸውን ተሸክመው አገኘ። በመኰንኑም በአዩት ጊዜ "እኛ ክርስቲያን ነን" ብለው በግልጥ ጮኹ መኰንኑም ሰምቶ ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ በእርሻ መሣሪያቸውም ገደሏቸው የእነዚህም ስማቸው ሱሩፋስ፣ አንጣኪዮስ፣ ስሐድራ ይባላል የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ መስከረም ዐሥራ አንድ ቀን ነው።
❤ ይህንንም ቅዱስ አባት ኤጲስቆጶስ ይስሐቅን መኰንኑ አሥሮ ለጣዖት እንዲሠዋ አስገደደው። እምቢ ባለውም ጊዜ ወደ እሳት እንዲወረውሩት አዘዘ የሰማዕትነቱም ፍጻሜ ታኅሣሥ ዐሥራ አራት ቀን ነው ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ገንዘው ቀበሩት። የስደቱ ወራትም ከአለፈ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው በስሙ አከበሩዋት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአገረ እስና ሰማዕትነት ሁሉ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 19 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለከ_ሰማዕት_በጥላን። ዘሀገረ ትእማዳን። በእንተ ኢየሱስ ዘሞትከ በሰይፈ ኀፂን። ምስለ ዕውር ዘፈወስኮ ወምስለ መምህርከ ካህን። እንዘ ክዋኔከ ከመ ኤር ወስን"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ19።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወአፅዐንከ ሰብአ ዲበ አርእስቲነ። አኅለፍከነ ማእከለ እሳት ወማይ። ወአውጻእከነ ውስተ ዕረፍት"። መዝ65፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ18፥1-12።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ይትኀፈሩ ኵሎሙ እለ ይሰግዱ ለግልፎ። ወእለ ይትሜክሑ በአማልክቲሆሙ። ወይሰግዱ ሎቱ ኵሎሙ መላእቲሁ"። መዝ 96፥7-8። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥33-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 4፥12-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 23፥10-15። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 11፥25-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ነው። መልካም የቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሐምሌ ፲፱ (19) ቀን።
❤ እንኳን #ለመጋቢ_ሐዲስ_ለሊቀ_መላእክት_ለቅዱስ_ገብርኤል_ሕፃኑን_ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ ወደ ፈላ ውሃ ውስጥ በጣሏቸው ጊዜ ከእግዚአብሔር ተልኮ የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ አድርጎ ላደነበት ዓመታዊ መታሰቢያ በዐል፣ ትዕማዳን ከምትባል ከተማ ብልህ ለሆነ ለሰማዕቱ #ለቅዱስ_በጥላን_ሰማዕትነት_ለተቀበለበት_ለዕረፍቱ በዐልና #ለቅዱሳን_ሰማዕታት_ስማቸው_ሱርስ፣ #ኅርማን_ያኑፋ_ስንጣንያ የሚባሉ የእስና አገር ሰዎች ለሆኑ ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለዕረፍቻው በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከአባ_አቃራቦን_ከመቃርስና_ከስካ አገር ሰው ከሆነ #ከሙሴ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሕፃኑ_ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ኢየሉጣን_ቅዱስ_ገብርኤል_እንዳዳናቸው፦ ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደሌላ አገር እናቱ ይዛው ሸሸች በዚያም የሸሸችውን መኰንን አገኘችው። ሰዎችም ነገር ሠሩባት ወደርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት እርሷም "መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ" አለችው።
❤ ሕፃኑም ቅዱስ ቂርቆስ ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና "አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ" አለው። ሕፃኑም መልሶ "አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና" አለው። እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ። መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በያይነቱ በሆነ ሥቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው እናቱም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሠቃያት እግዚአብሔርም ያለምንም ጉዳት ያነሣቸው ነበር። ብዙዎች አሕዛብም በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ። በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት። ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳናቸው።
❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑም በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ ያን ጊዜም ፍርሀትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች ከዚህም በኋላ ጸናች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው ልጅዋንም "ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ እኔም ልጅህ ነኝ" አለችው። "ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት" አለችው ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ ሐምሌ 19 ቀን በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና።
❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጎትቷቸው አዘዘ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል አዳናቸው መኰንኑም በታላቅ ሥቃይ ያሠቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወህኒ ቤት ዘጋባቸው። ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው አረጋጋውም። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በመላእኩ በቅዱስ ገብርኤል፣ በቅዱስ ቂርቆስና በእናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ ትዕማዳን ከምትባል ከተማ ብልህ የሆነ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_በጥላን፦ የዚህም ቅዱስ አባቱ አረማዊ ነበረ ስሙም አውጢኪዮስ ነበር እናቱ ግን አማኝ ነበረች ስሟም ኤልያና ነበር። በአደረገ ጊዜም አባቱ ጥበብን ሁሉ አስተማረው እጅግም አዋቂ ሆነ።
❤ በበጥላን ቤት አቅራቢያም አንድ ቄስ ይኖር ነበር። በጥላንም በፊቱ ሲያልፍ መልኩንና ዕውቀቱን ብልህነቱንና አስተዋይነቱንም ይመለከት ነበር ከሀዲ ስለ መሆኑም ስለርሱ ያዝን ነበር። ቄሱም በጥላን መንገድ መርቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ያስገባው ዘንድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው። ስለ በጥላንም ልመናውን በአዘወተረ ጊዜ በጥላን በእርሱ እጅ ያምን ዘንድ እንዳለው ጌታችን በራእይ ገለጠለት ቄሱም ደስ አለው ሁልጊዜም በፊቱ ሲያልፍ በጥላንን ያነጋግረውና ሰላምታ የሚሰጠው ነበር። ስለዚህም በመካከላቸው ፍቅር ጸና።
❤ ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ቤት ይገባና ስለ ሃይማኖት ይነጋገር ነበር። ቄሱም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ምን ያህል ክብር እንዳላት ለሚያምኑበትም ሁሉ ዕውቀትና ማስተዋል እንደሚሰጣቸው ድንቆችና ታላላቅ ተአምራቶች እንደሚደረግላቸው ታላቅ ፈውስም እንደሚያደርጉ ገለጠለት። በጥላንም ክብር ይግባውና በክርስቶስ የሚያምኑ ተአምራትን እንደሚያደርጉ ይህን በሰማ ጊዜም እጅግ ደስ ብሎት በዚያ ቄስ ትምህርት በጌታ አመነ ቄሱም ሁል ጊዜ የሃይማኖት ትምህርት ያስተምረው ጀመር።
❤ በአንዲትም ዕለት ቅዱስ በጥላን በከተማው አደባባዮች ሲያልፍ እባብ የነደፈውን አንድ ሰው ሲጨነቅ አየው እባቡም በርሱ ዘንድ ቆሞ ነበር በልቡም "የመምህሬን ቃል ልፈትን ክብር ይግባውና በክርስቶስ ከአመንክ በስሙ ታምራት ታደርጋለህ ብሎኛልና" አለ። እባቡ ወደ ነከሰውም ሰው ቀርቦ ኃይሉን ይገልጽለት ዘንድ እባቡንም ይገድለው ዘንድ ሰውዬውን ያድነው ዘንድ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ረጅም ጸሎትን ጸለየ ያን ጊዜም ሰውዬው ያለ ምንም ጉዳት ድኖ በጤና ተነሣ ከይሲውም ወደቀ ወዲያውም ሞተ። የበጥላንም ሃይማኖት ተጨመረለት።
❤ ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ ሁል ጊዜም ወደ ቄሱ እየመጣ ይማር ነበር። በአንዲት ቀንም ያድነው ዘንድ አንድ ዕውር መጣ። የቅዱስ በጥላም አባትም ባየው ጊዜ ዕውሩን ከውጭ መልሶ ሰደደው በጥላንም አባቱን "ማነው የፈለገኝ?" ብሎ ጠየቀው አባቱም "ልታድነው የማትችል አንድ ዕውር ነው" አለው። እርሱም አባቱን "የእግዚአብሔርን ክብር ታይ ዘንድ አለህ" አለው ይህንንም ብሎ ዕውሩን ጠራውና "ዐይኖችህ ቢገለጡ ያዳነህን ታመልከዋለህን?" አለው ዕውሩም "አዎን አምናለሁ" አለ ቅዱስ በጥላን በዕውሩ ላይ ረጅም ጸሎትን ጸለየ እጆቹንም በዕውሩ ዐይኖች ላይ አኑሮ "እንድታይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እመን" አለው ወዲያውኑም ዐይኖቹ ተገለጡ። አባቱም ይህን ድንቅ ሥራ በአየ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ከዕውሩ ጋር አመነ ቅዱስ በጥላንም ወደ ቄሱ ወሰደጃቸውና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ከዚህም በኋላ ባሮቻቸውን ነፃ አወጡ ገንዘባቸውንም ለድኆችና ለችግረኞች አከፋፈሉ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወኢነበርኩ ውስተ ዐውደ ከንቱ። ወኢቦእኩ ምስለ ዐማፅያን። ጸላዕኩ ማኅበረ እኩያን "። መዝ25፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 15፥1-13፣ ያዕ 1፥1-13 እና የሐዋ ሥራ 15፥13-20። የሚነበበው ወንጌል ማር 6፥ 1-ፍ14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሐምሌ ፲፰ (18) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው ለኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ለነበረው ለጌታችን ወንድም ለሚባለው #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ያዕቆብ_ለዕረፍት በዓል፣ ከቁልዝም ከተማ ለሆነ በከሀዲው በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ሰማዕትነት ለተቀበለ #ለቅዱስ_አትናቴዎስ_ለዕረፍት_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በፍቅር አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከእንዱራናና_ከጦቢያ፣ #ከኤስድሮስ_ማኅበር_ከዘጠኝ_ሽህ ጭፍሮችና #ከመኰንኑ_ከእንድራኒቆስና ከሠራዊቱ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ፦ ይህም የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ነው። እርሱም ከልጆቹ ሁሉ የሚያንስ ነበር። እርሱም ንጹሕ ድንግል ነበር ከጌታችን ጋራ አደገ ስለዚህም ክብር ይግባውና የጌታችን ወንድም ተባለ። ከጌታችን ዕርገትም በኋላ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም አገር ላይ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተምሮ ብዙዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው። እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ።
❤ በአንዲት ዕለትም በጎዳና ሲጓዝ አንድ ሽማግለሸ አገኘ። ቅዱስ ያዕቆብም "ሽማግሌ ሆይ በቤትህ ታሳድረኛለህን?" አለው። አረጋዊውም "እሺ እንዳልክ ይሁን" አለ በአንድነትም ሲጓዙ ጋኔን ያደረበት ሰው አገኘው በአየውም ጊዜ "የክርስቶስ ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ልታጠፋኝ መጣህን" ብሎ ጮኸ። ሐዋርያውም "በናዝሬቱ ኢየሱስ ስም ተዘጋ ከሰውዬውም ውጣ" አለው። ወዲያውም ያ ጋኔን ከሰውዬው ላይ ወጣ።
❤ ያ ሽማግሌም ይህን ድንቅ ተአምር አይቶ ደነገጠ ከሐዋርያው እግር በታችም ወድቆ እንዲህ አለው "ወደ ቤቴ ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን እድን ዘንድ ቤተ ሰቦቼም ሁሉ ይድኑ ዘንድ ምን ላድርግ" አለ ያን ጊዜም ሐዋርያው "አቤቱ ጌታዬ ሆይ መንገዴን አሳምረህልኛልና አመሰግንሃለሁ" ብሎ ጌታችንን አመሰገነው። ወደ ሽማግሌዎች ተመልሶ የድኅነትን ነገር ነገረው ከብር ይግባውና ስለጌታችን ሰው መሆን ስለ መከራው ስለ ሞቱና ስለ መነሣቱ አስተማረው።
❤ ከዚህም በኋላ ያ ሽማግሌ ሐዋርያውን ወደ ቤቱ አስገባው ቤተ ሰቦቹም ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ ቅዱስ ያዕቆብም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው።
❤ የከተማው ሰዎችም በሰሙ ጊዜ በሽተኞችን ሁሉ ወደርሱ አመጡ ሁሉንም አዳናቸው ለእነርሱም ሃይማኖትን አስተምሮ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው። ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመላቸው ያንን ሽማግሌም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመው ክብር ይግባውና የጌታችንንም ወንጌል ሰጣቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ያስተምር ዘንድ ወደ ሌሎች አገሮች ወጥቶ ሔደ። አንዲትም መካን ሴት ነበረች እግዚአብሔር ልጅን ይሰጣት ዘንድ ስርሷ እንዲጸልይላት ቅዱስ ያዕቆብን ለመነችው። እርሱም ጸለየላትና ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ያዕቆብ ብላ ጠራችው ልጅዋንም ተሸክማ ወደ ሐዋርያው መጥታ ሰላምታ አቀረበችለት ከልጅዋም ጋር ከእርሱ ተባረከች።
❤ ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ብዙዎች አይሁድ ወደርሱ ተሰበሰቡ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስም የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጠየቁት እነርሱ እርሱ ጌታች የዮሴፍ ልጅ እንደሆነ እርሱም ወንድሙ እንደሆነ እንዲነግራቸው አስበው ነበርና። ቅዱስ ያዕቆብም በሦስተኛ ደርብ ላይ ወጥቶ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ከአብ ጋራም ትክክል እንደሆነ ይገልጽላቸው ጀመረ።
❤ ይህንንም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቈጡ ከደርቡ ላይ አውርደው የጸና ግርፍትን ገረፉት ከእነርሱም ውሰጥ የልብስ ማጠብያ የእንጨት ገበታ የያዘ አንድ ሰው መጣ በዚያ እንጨትም ቅዱስ ያዕቆብን ራሱ ላይ መታው ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
❤ ስለርሱ ወይን እንዳልጠጣ ደም ከለው ወገን እንዳልበላ በራሱም ላይ ምላጭ እንዳልወጣ በውሽባ ቤት እንዳልታጠበ ሁለት ልብስን እንዳለበሰ ሁል ጊዜም እንደሚቆምና እንደሚሰግድ ተጽፏል። ከመቆም ብዙ የነሳ እግሮቹ አብጠው ነበር። ከዚህም በኋላ ዐረፈና በቤተ መቅደሱ ጎን ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_አትናቴዎስ፦ ይህም ቅዱስ ከነገሥታት ወገን ነበረ በሃይማኖቱም የጸና ነበረ። እኒህ ከሐዲያን ነገሥታት ዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ የጣዖታትን አምልኮ በዓወጁ ጊዜ ይህን አትናቴዎስን ለግብጽ አገር ገዥ አድርገው ሾሙት አብያተ ክርስቲያናትንም እንዲአፈርስ አዘዙት።እርሱ ግን ወደ ግብጽ በደረሰ ጊዜ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ሒዶ በረከትን ተቀበለ እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ነገረው በእርሱም ደስ አለው። ንጉሡም በሰማ ጊዜ ይዞ ይመረምረው ዘንድ ሌላ መኰንን ላከ።
❤ መኰንኑም በደረሰ ጊዜ ተገናኘውና "የአማልክትን ፍቅር ለምን ተውክ" አለው። አትናቴዎስም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኔ ከታናሽነቴ ጀምሬ ክብር ይግባውና የክርስቶስ ነኝ የቀናች ሃይማኖቴንም አልተውም"።
መኰንኑም "የንጉሥን ትዕዛዝ የሚለውጥ ሁሉ ቅጣት እንዲአገኘውና በጽኑ ሥቃይ እንዲሠቃይ አታውቅምን" አለው። ቅዱስ አትናቴዎስም እንዲህ አለው "አንተ ሰነፍ በአንተ ላይና በንጉሥህ ላይ ቸር ሕይወት ሰጭ እግዚአብሔርን በሚጠላ በአባትህ ሠይጣን ላይ የሚመጣው የዘላለም ሥቃይን እስከምታይ ጥቂት ታገሥ" አለው።
❤ መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ራሱንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ቅዱስ አትናቴዎስም ነፍሱን ከቅዱሳኑ ጋራ እንዲያሳርፍ ከቤተ ክርስቲያንም መከራን እንዲያርቅ የሮምንና የአኲስምን የክርስቲያን መንግሥት እንዲአጸና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ጸሎቱም በፈጸመ ጊዜ በክር ብሎ ሰገደ ጭፍሮችም ራሱን በሰይፍ ቆረጡ። ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ቀበሩት። ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋ ይሁን እኛንም በቅዱስ አትናቴዎስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 18 ስንክሳር
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለያዕቆብ_በኀበ_ማርያም_ዘተሐፅነ። ዕጓለ ማውታ እምእሙ እስመ ውእቱ ኮነ። ወዝንቱ ጻድቅ እኅወ እግዚእነ። ኢያብአ ውስተ አፉሁ ሥጋ ወወይነ ወኢገብረ ሎቱ ክልኤተ ክዳነ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ_18።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አፅናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4 ወይም መዝ 25፥4 ። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 13፥52-ፍ.ም ወይም ማር 6፥1-14።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሐምሌ ፲፭ (15) ቀን።
❤ እንኳን #ውዳሴ_ማርያውና ከ 14 ሺህ በላይ ድረሳናትንና ተግሣጻትን ለደረሰው ለታላቁ ሊቅ #ለአፈ_በረከት_ለቅዱስ_ኤፍሬም_ሶርያዊ_ለዕረፍት በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሶርያው_ሊቅ_አፈ_በረከት_ቅዱስ_ኤፍሬም፦ ይህም ቅዱስ ከዋክብት የሚያመልኩ ሰዎች አገር ነው አባቱ ክብር ይግባውና የክርስቶስን አምልኮት የሚጠላ የጣዖት ካህር ነበር። በዚያን ጊዜም የእግዚአብሔር ቸርነት ቀሰቀሳቸውና አነሳስታ የንጽቢን ጳጳስ ወደ ሆነው ወደ አባ ያዕቆብ ወሰደችው እርሱም የቤተ ክርስቲያን ትምህት አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው በእርሱ ዘንድ በጾምና በጸሎት ያለማቋረጥ እየተጋደለ ለብዙ ዘመናት ኖረ።
❤ የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት አሕዛብን ተከራክሮ ይረታቸው ነበር። ኒቅያ በሚባል ከተማ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ በተደረገ ጊዜ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከአባ ያዕቆብ ጋር ወደ ቅዱሳን ጉባኤ ሔደ። ከሀዲው አርዮስንም አውግዘው ከለዩት በኋላ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም በዚያች ሌሊት ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ አየ ከዚህ ራዕይ የተነሳ አደነቀ ይገልጽለትም ዘንድ ወደ ጌታ ጸለየ "ይህ የቂሣርያ ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ባስልዮስ ነው" የሚል ቃል ከሰማይ ወደርሱ መጣ።
❤ ቅዱስ ኤፍሬምም ያየው ዘንድ ወዶ ወደ ቂሣርያ አገር ተጓዘ በደረሰም ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በማዕዘኑ በኩል ቆመ ቅዱስ ባስልዮስም ወንጌልን ሊያነብ በወጣ ጊዜ ዋጋው ብዙ የሆነ ከወርቅ የተሠራ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አየው። ሦስት ምልክቶችን እስኪያይ ድረስ ተጠራጠረ ምልክቶችም እኒህ ናቸው። ነጭ ርግብ መጥታ በራሱ ላይ አረፈች። ሁለተኛም በልብሱ ላይ የሚያርፉ ተዋሐስያን ይቃጠሉና ይረግፉ ነበር። ሦስተኛም ከአፉ የእሳት ነበልባል ወጥቶ በምዕመናን ላይ ያድር ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ባስልዮስ ቅዱስ ኤፍሬምን በስሙ ጠራውና እርስ በእርሳቸው ሰላምታ ተለዋወጡ። በአስተርጓሚ ይነጋገሩ ጀመር። የየራሳቸውን ቋንቋ ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልይ ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስ ለመነው። በጸለየም ጊዜ ተገልጾላቸው ያለ አስተርጓሚ ተነጋገሩ።
❤ ከዚህ በኋላም ቅዱስ ኤፍሬምን ዲቁና ሾመው ከጥቂት ወራት በኋላ ቅስና ሾመው ከእርሱም ብዙ ትሩፋቶች ተገለጡ በመንፈሳዊ ተጋድሎ ሁሉ ተጋደለ።
❤ አንዲት በወገን የከበረች ባለ ጸጋ ሴት ነበረች እርሷንም ለካህን ለማስመርመር ታፍር ነበር ከታናሽነቷ ጀምራ የሠራችው ኃጢያቷን ሁሉ ጽፍ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አመጣች። "አባቴ ሆይ በዚህ ክርታስ ውስጥ ያሉት ኃጢያቶቼ ይደመሰሱ ዘንድ ተናገር ብላ ለመነችው እርሱ እንዳልሽው ይሁንልሽ" አላት። እርሷ ክርታሱን በገለጠች ጊዜ ከአንዲት ኃጢያቷ በቀር ኃጢያቷ ሁሉ ተደምስሶ አገኘች ያችም ኃጢአት አስጨናቂና ታላቅ ኃጢአት ነበርች።
❤ በአገኘቻትም ጊዜ ያቺን የቀረች ኃጢአቷን ያጠፋላት ዘንድ አልቅሳ ለመነችው እርሱም "ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሒጂ እርሱ ይቺን የቀረች ኃጢአትሽ ያስተሠርይልሻል" አላት። ወዲያውም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሒዳ እርሷ የሆነውን ሁሉ ነገረችው። እርሱም እንዲህ አላት "ፈጥነሽ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ሒጂ ግን ሙቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱት ታገኚዋለሽ ሳትጠራጠሪም ይቺን ክርታስ በላዩ ጣይ ይደመስስልሻል።
❤ ያቺም ሴት ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ተመለሰች ሙቶ ተሾክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱትም አገኘችው። ያንንም ክርታስ በአስክሬኑ ላይ ጣለችው ወዲያውኑ ተደመሰሰላት።
❤ ይህም ቅዱስ ኤፍሬም ብዙ ተአምራቶችን አድርጓል በዘመኑ ዲዳን የሚባል አንድ ከሃዲ ተነሳ ይህም አባት ኤፍሬም ተከራክሮ ረታው።
❤ እጅግም ብዙ የሆኑ ዐሥራ አራት ሺህ ድርሳናትና ተግሣጻትን ደረሰ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክ የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያው ውዳሴዋ ነው። "አቤቱ የፀጋህን ማዕበል ግታልኝ" እስከሚል ደረስ ድርሳናት ደርሷል።
❤ መልካም የሆነ ገድሉንም በፈጸመ ጊዜ ወደ ወደደው ወደ እግዚአብሔር ሐምሌ 15 ቀን ሔደ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በብፁዕ ቅዱስ ኤፍሬም ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 15 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሐምሌ ፲፬ (14) ቀን።
❤ እንኳን ልክ እንደ #ቅዱስ_ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ሊሰቃይ ሲሔድ #ጌታችን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ ተገልጾ ለመለሰው #ለቅዱስ_አብሮኮሮንዮስ_ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና ለመነኰሳት አለቃ #ለታላቁ_አባት_አባ_መቃርስ_ለመታሰቢያ_በዓሉ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከሰማዕቱ_አሞንዮስ_ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_አብሮኮሮንዮስ፦ የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ከኢየሩሳሌም ነው የአባቱ ስም ክርስቶፎሮስ ነው ትርጓሜውም ክርስቶስን የለበሰ ማለት ነው ክርስቲያንም ነበረ የእናቱም ስም ቴዎዶስያ ነው እርሷ ግን ጣዖትን ታመልክ ነበረች።
❤ አባቱም በዐረፈ ጊዜ እናቱ ወሰደችው ከእርሱም ጋራ ብዙ ገንዘብ ይዛ ወደ አንጾኪያ ከተማ ሔደች ልጅዋንም በእስክንድርያ ከተማ ገዥ አድርጎ ይሾመው ዘንድ ለዲዮቅልጥያኖስ እጅ መንሻ ሰጠችው እርሱም ሾመው የሹመት ደብዳቤውንም ጽፎ ክርስቲያኖችን እንዲአሠቃዩ አዘዘው።
❤ ከአንጾኪያም ከተማ ወጥቶ ጥቂት እንደ ተጓዘ ወደእርሱ የሚያስፈራ ቃል ከሰማይ መጣ በስሙ ጠርቶ እንዲህ አለው "ከሀዲው ዲዮቅልጥየኖስ እንዳዘዘህ ብታደርግ አንተ በክፉ አሟሟት ትሞታለህ። እርሱም "ራስህን ትገልጥልኝ ዘንድ ጌታዬ ሆይ እለምህሃለሁ" አለው ወዲያውኑም የብርሃን መስቀል ታየው ዳግመኛም "በኢየሩሳሌም የተሰቀልኩ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ነኝ" የሚለውን ቃል ሰማ።
❤ ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ ተመልሶም ከአንጥረኛ ዘንድ የወርቅ መስቀል አሠራ ከዚያም በኋላ ወደ እስክንድርያ ከተማ ተጓዘ በጒዞውም ውስጥ ሊገድሉት ዐመፀኞች አረማውያን ተነሡበት እርሱም በእነርሱ ላይ በርትቶ ክብር ይግባውና በጌታ ክርስቶስ መስቀል ድል አደረጋቸው። እናቱም "በጦርነት ላይ ለረዱህና ላዳኑህ አማልክት መሥዋዕትን ሠዋ" አለችው እርሱም እንዲህ አላት "እኔስ አዳኝ በሆነ በመስቀሉ ኃይል ላዳነኝ ክብር ይግባውና ለእግዚአብሔር እሠዋለሁ"። ይህንንም በሰማች ጊዜ ልጅዋ አብሮኮሮንዮስ ክርስቲያን እንደሆነ ወደ ዐመፀኛው ዲዮቅልጥያኖስ ልካ ነገረችው። ዲዮቅልጥያኖስም ጭፍራ ልኮ ወደ ቂሣርያ ከተማ አስወሰደው የቂሣርያውንም ገዥ ስለ ርሱ እንዲመረምርና እንዲአሠቃየው አዘዘው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ በአቀረቡት ጊዜ በፊቱ ቁሞ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ለመሞት እስቲደርስም ጽኑዕ ግርፋትን ገረፈው ከዚህም በኋላ አሠረው። በዚያችም ሌሊት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ብርሃን ውስጥ ታየው ከእርሱም ጋራ ብርሃናውያን መላእክት ነበሩ ከማሠሪያውም ፈታውና በመለኮታዊ እጁ ዳሰሰው ከቍስሎቹም ሁሉ አዳነው።
❤ በማግሥቱም መኰንኑ ስለ ቅዱሱ ዜና ሙቶ እንደሆነ ወይም አልሞተ እንደሆነ ጠየቀ ለእርሱ የሞተ መስሎት ነበረና። ቅዱሱም በመጣ ጊዜ ጤነኛ ሁኖ አየውና መኰንኑ አደነቀ በዚያ የነበሩ ሕዝቡም አይተው እጅግ አደነቁ እንዲህም እያሉ ጮኹ "እኛ በግልጥ ክርስቲያን ነን በቅዱስ አብሮኮሮንዮስ አምላክ እናምናለን"። ከእነርሱም ጋራ ሁለት መኳንንትና ዐሥራ ሁለት ሴቶች እናቱ ቴዎዶስያም ነበሩ መኰንኑም ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ። እነርሱም ቆረጡአቸው። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ሐምሌ ስድስት ቀን ተቀበሉ።
❤ ቅዱስ አብሮኮሮንዩስን ግን ምን እንደሚያደርግበት እስቲአስብ ድረስ ሦስት ቀን አሠረው ከዚህም በኋላ አውጥቶ እንዲህ አለው "ልብህ እንዲመለስ ነፍስህንም እንድታድን ለአማልክትም እንድትሠዋ እነሆ በአንተ ላይ ሦስት ቀናት ታገሥኩ"። ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት "መኰንን ሆይ የለም ልቤ ወደ ስሕተት አይመለስም ክብር ይግባውና ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ እንደሌለ አውቄ ተረድቼአለሁ ጣዖታቱም ሁሉ ከዕንጨትና ከደንጊያ በሰው እጅ የተሠሩ ፍጡራን ናቸው እንጂ አማልክት አይደሉም አይጐዱም አይጠቅሙም"።
❤ መኰንኑም ሰምቶ እጅግ ተቆጣ ጐኖቹንም በሰይፍ እንዲሰነጣጥቁ አዘዘ አርኬላዎስ የሚባል ባለ ሰይፍም የቅዱሱን ጐኖቹን ሊሠነጥቅ እጁን ዘረጋ ያን ጊዜም እጁ ደረቀች ወድቆም ሞተ። መኰንኑም ተቆጥቶ በምድር ጥለው ይገርፉት ዘንድ አዘዘ እንደ አዘዘም ገረፉት በሰይፍም ጐኖቹን ሠንጥቀው በቍስሉ ውስጥ መጻጻ ጨመሩ እስከ ወህኒ ቤትም ድረስ በእግሩ ጐተቱት በዚያም ሁለት ቀኖች ኖረ ከዚህም በኋላ አውጥቶ እሳትን በተመላች ጕድጓድ ውስጥ ጣለው ክብር ይግባውና ጌታችንም አዳነው ምንም ምን አልነካውም።
❤ ብዙ ከማሠቃየቱም የተነሣ መኰንኑ በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ ቅዱስ አብሮኮሮንዮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለአብሮኮሮንዮስ_በኢየሩሳሌም ዘተወልደ። እምለባሴ ክርስቶስ አቡሁ በአርዑተ ወንጌል ዘተጸምደ። በትእዛዘ ንጉሥ ሠዊዐ ሶበ ለጣዖት ፈቀደ። ቃል ዘይከልኦ እምሰማይ ወረደ ወበቊስላቲሁ አንበረ መለኮት እደ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ_14።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ በእንቲአሁ ይቀትሉነ ኵሎ፡አሚረ። ወኮነ ከመ አባግዕ ዘይጠብሑ። ንቃሕ እግዚኦ ለምንት ትነውም"። መዝ 43፥22-23። የሚነበቡት 1ኛ ተሰ 4፥1-13፣ 1ኛ ጴጥ 5፥6-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 14፥19-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 13፥1-10። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ እንኳን #ለዘመነ_ክረምት_ሦስተኛ_ሳምንት_ዕለት እሑድ (ሰንበት) እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፮ "ንጉሥ ውእቱ #ክርስቶስ_ንጉሥ_ውእቱ_ክርስቶስ መሐሪ ውእቱ ይሁብ ዘርአ ለዘራኢ፤ (ን)፣ ያሠርቅ እክለ ለሲሳይ ያነሥኦ እድ ለነዳይ፤ (ን) ዘየኀይድዎ ሥልጣነኖ ዘይኤዝዝ ትፍሥሕተ ለጻድቃኒሁ፤ (ን)፣ ወሠርዐ ሰንበት ለሰብእ ዕረፍት ገባሬ ሕይወት #ያርኁ_ክረምተ_በበዓመት ንጉሥ ውእቱ ክርስቶስ፣ ንጉሥ ውእቱ ክርስቶስ። ትርጉም፦ ከዓለም በፊት #ክርስቶስ_ንጉሥ_ነው፣ #ክርስቶስ_ይቅር_ባይ መሐሪ ነው፣ ለዘሪ ዘርን ይሰጣል፤ የተዘራውን ዘር ለምግብ እንዲኾን ፍሬያማ ያደርገዋል፣ ደሀውን ከድህነቱ ያነሣዋል ባለጠጋ ያደርገዋል። (አዝ) ሥልጣኑን የማይቀሙት፤ ለጻድቃን ደስታን የሚያዝ የሚሰጥ፤ እርሱ የሕይወት መገኛ በመሆኑ የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ ያርፉ ዘንድ ሰንበትን ለዕረፍት ሠራ፤ #ክረምትን_በየዓመቱ የሚያመጣ #ክርስቶስ_ንጉሥ_ነው_ክርስቶስ_ንጉሥ ነው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዚህ_ሳምንት_የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዘያበቊል ሣዕረ ለእንስሳ። ወሐምልማለ ለቅኔ እጓለ እመሕያው። ከመ ያውፅእ እክለ እምድር"። መዝ 103፥15-16። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 9፥1-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥15-ፍ.ም፣ የሐዋ ሥራ 27፥21-33። የሚበበውወንጌል ማቴ 24፥36-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ኤጲፋንዮስ። መልካም ዕለተ ሰንበትና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሐምሌ_፲፫ (13) ቀን።
❤ እንኳን #ለአገረ_ቅፍጥ_ኤጲስቆጶስ ከነቢያት ትንቢትም አንዳንዱን መጽሐፍ በሚነብ ጊዜ ትንቢቱ የሚነበብለት ነቢይም ወደርሱ መጥቶ ንባቡን እስቲፈጽም ይቆይ ለነበረ፤ እጆቹን አንሥቶ በሚጸልይ ጊዜ ጣቶቹ እንደ ፋና ይበሩ ለነበር ለታላቁ አባት #ለአባ_ብስንድዮስ_ለዕረፍቱ_መታሰቢያ በዓልና በግብፅ ደቡብ ከቡና አውራጃ ከጡሕ ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_አሞን_ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል መታሰቢያ በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የአገረ_ቅፍጥ_ኤጲስ_ቆጶስ_አባ_ብስንድዮስ፦ ይህም ቅዱስ ሰው መንኵሶ በታላቅ ገድል ተጠምዶ ቅዱሳት መጻሕፍትንም አጠና ከቅዱሳት መጻሕፍትም ውስጥ የዳዊትን መዝሙርና የነቢያትን መጻሕፍት አጥንቶ ነበር። ከነቢያት ትንቢትም አንዳንዱን መጽሐፍ ያነብ ነበረ። ትንቢቱ የሚነበብለት ነቢይም ወደርሱ መጥቶ ንባቡን እስቲፈጽም ይቆይ ነበር።
❤ ስለርሱ እንዲህ ተባለ እርሱ እጆቹን አንሥቶ በሚጸልይ ጊዜ ጣቶቹ እንደ ፋና ይበሩ ነበር እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ። እርሱም በዕድሜው ዘመን ሁሉ የሴት ፊት አላየም። ራሱን ወደ ምድር ያዘነብል ነበር እንጂ። በሆድዋ ውስጥ ታላቅ ደዌ የነበረባትም አንዲት ሴት ነበረች ከበዐቱ ደጅ ጠበቀችውና በድንገድ አገኘችው። እርሱም ሮጠ እርሷም ተከትላው ሮጠች ወደ እርሱ መድረስም በተሳናት ጊዜ እግሩ የረገጠቻትን አንዲት እፍኝ አፈር ዘግና በእምነት በላች ከደዌዋም ፈጥና ተፈወሰች።
❤ በአንዲት ዕለትም የሚያበሩ ሦስት ሰዎች አየ እነርሱም "አንተ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ትመግባት ዘንድ አለህ" እያሉ መክፈቻ ቅልፍን ሰጡት። ከዚህ በኋላ ቅፍጥ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ተሾመ የቊርባን ቅዳሴ በሚቀድስ ጊዜም ጌታችንን እጆቹ በመሠዊያው ላይ ሆነው ይመለከተው ነበር። መላእቶቹንም በዙሪያው ቁመው ያያቸው ነበር።
❤ በአንዲት ዕለትም አንድ ቄስ ሊቀድስ ገባ በቅዳሴ እኩሌታ ላይም በመሠዊያው ፊት እያለ ምራቁን ተፋ። ቅዳሴውም በተፈጸመ ጊዜ ይህ አባት ገሰጸው እንዲህ አለ "በሚያስፈራው ወሠዊያው ፊት በምትቆም ጊዜ ከእግዚአብሔር ጌትነት የተነሳ አትፈራምን የተፈኸውስ ምራቅ በመሠዊያው ዙሪያ በቆመ ኪሩብ ክንፈች ላይ እንደረሰ አታውቅምን"። ያን ጊዜም ያንን ቄስ መንቀጥቀጥ ያዘው ተሸክመውም ወደ ቤቱ ወሰዱትና ታሞ ሞተ።
❤ ይህም ቅዱስ አባት አንደበቱ ጣዕም ያለው ነበር በሚያነብ ጊዜ በሚያስተም ጊዜ በሚመክርም ጊዜ አይጠገብም ነበር። የዕረፍቱ ቀን በቀረበ ጊዜ አውቆ ሕዝቡን ጠራቸውና አስተማራቸው መከራቸውም በቀናች ሃይማኖትም ይጸኑ ዘንድ አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ።
❤ ከሥጋውም ብዙ ተአምር ተገለጠ ደቀ መዝመሩ ከመግነዙ ጥቂት ቁራጭ ወስዶ በእምነት በሽቶኞችን ሁሉ ይፈውስ ነበር። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በአባ ብስንድዮስ ጸሎቱ ይማረን በረከቱ ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_አሞን፦ ይህም ቅዱስ ከግብጽ ደቡብ ከቡና አውራጃ ጡሕ ከሚባል አገር ነው። ለዚህም ቅዱስ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ተገለጸለት ከእርሱ የሚሆነው ሁሉ ነገረው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ እንዴናው ከተማ ሒዶ አውግስጦስ የሚባል መኰንን ፊት ክብር ይግባው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኰንኑም በመንኰራኵር ውስጥ በእሳት ላይ በመጣል በእሳት በአጋሉት በብረት አልጋ ላይ በማጋደም ከላም ቆዳ በተሠራ ጅራፍ በውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥ በመጨመር ጽኑዕ ስቃይም አሰቃዩት። የራሱንም ቆዳ ገፈው በራሱ ላይ የእሳት ፍም አኖሩ እግዚአብሔርም ያጸናው ነበር ያለምንም ጉዳት ጤነኛ አድርጎ ያስነሳው ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ ክብር ይግባው እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በጎልማሳ አምሳል በብርሃን ሠረገላ ላይ ሁኖ ተገለጠለትና አጽናናው እንዲህም አለው "ወዳጄ አሞን እኔ ከአንተ ጋራ እኖራለው ስምህን የሚጠራውን፣ መታሰቢያህን የሚያደርገውን ሁሉ፣ ወይም ገድልህ የሚጽፈውን ሁሉ እኔ በመንግሥቴ ውስጥ አስበዋለሁ ኃጢያቱንም እደመስሳለሁ አገርህም እጠብቃለሁ" ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጥቶ ከእርሱ ዘንድ አረገ።
❤ ይህም ቅዱስ በሥጋው ሳለ ታላላቅ ታምራቶችንና ድንቆችን አደረገ ወዲያውንም በሠይፍ ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ። ቅዱስ ዮልዮስም በዚያ ነበር ሥጋውን ወስዶ በመልካም ልብስ ገነዘው ከሁለት አገልጋዮቹም ጋር ወደ አገሩ ላከው በላይኛው ግብጽም ታላላቅ የሆኑ ድንቆችንና ተአምራቶች እያሳየ እስከ ዛሬ አለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ሰማዕት በቅዱስ አሞን ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 13 ሰንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለብስንድዮስ_ዘይኔጽር_ነቢያት። እስከ ይፌጽም ኣንብቦ ጸሐፍ ትንቢተ። ወሰሚዓ ካዕበ ዘገብረ ትእምርተ። ብእሲት ጥዕየት እምደዌሃ ወሐይወት ሕይወተ። እምአሠረ እግሩ ቅድስት በሊዓ መሬተ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ_13።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሐምሌ ፲፪ (12) ቀን።
❤ እንኳን ለከበረ መልአክ ለመላእክት አለቃ #ለቅዱስ_ሚካኤል_የፋርስ_ንጉሥ ወደ ሆነ ወደ ሰናክሬም ሠራዊት እግዚአብሔር ለላከበት ቀን #ንጉሥ_ሕዝቅያስን ረድቶ በአንድ ሌሊት ከሰናክሬም ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ አርበኞች ለገደለበት ለወራዊ መታሰቢያ በዓልና ስርያቆስ ከሚባል አገር ለሆነ #ለአባ_ሖር ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #የአባ_ሖር_ማኅበር_ከመቶ_ሰባት_ወንዶችና_ከሃያ_ሴቶች_ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን፡፡
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ቀን የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ #የቅዱስ_ሚካኤል_የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚች ቀን የፋርስ ንጉሥ ወደ ሆነ ወደ ሰናክሬም ሠራዊት እግዚአብሔር ላከው ከሰናክሬም ሠራዊት ከሰናክሬም ሠራዊትም መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ አርበኞች ገደለ።
❤ ይህም እንዲህ ነው ሰናክሬም ኢየሩሳሌምን በከበባት ጊዜ ሕዝቅያስንና ፈጣሪው እግዚአብሔርን እየዘለፈ ወደ ሕዝቅያስ መልእክተኞችን ላከ እንዲህም አለ "እግዚአብሔር ያድናችኋል እያለ ሕዝቅያስ አያስታችሁ ከእጄ የሚያድናችሁ ማን ነው"።
❤ የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስ እጅግ አዘነ ወገኖቹንና አገሩ ኢየሩሳሌምንም ያድን ዘንድ ማቅ ለብሶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። እግዚአብሔርም ልመናውን ተቀበሎ ወደ ፋርስ ንጉሥ ወደ ሰናክሬም ሠራዊት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ላከለት። ድንቅ ሥራንም ሠርቶ ኢየሩሳሌምንና የይሁዳን ሰዎች ሁሉ አዳናቸው።
❤ ስለዚህም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል መታሰቢያ በዚች ቀን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት ይማረን ረድኤቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ሖር፦ ይህም አባት ስርያቆስ ከሚባል አገሩ ነው። አባቱም አንጠረኛ ነበር አንዲት እኅቱም ነበረችው። ጎልማሳም በሆነ ጊዜ ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደ አገረ ፈርማ ሔደ በመኰንኑም ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑ ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው ከሥቃዩም ድኖ ተነሣ። መኰንኑም በእጁ ላይ ጌታችን ያደረገውን ይህን ተአምር አይቶ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋራ አመነ። በሌላ መኰንን እጅም ከሚስቱና ከልጆቹ ጋራ በሰማዕትነት ሞተ።
❤ ቅዱስ አባ ሖርን ግን ወደ እንዴናው ላከው በዚያም በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ አሠቃዩት በመንኰራኵሮችም አበራዩት ዘቅዝቀውም ሰቅለው በእሳት በአጋሉት የብረት በትር ደበደቡት። መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘ የሰማዕትነትን አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሐምሌ 12 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለሖር_በኀበ_እግዚኡ_ዘተመዝገነ። አመ ጽዕለተ ተወክፈ ወበትረ ኀፂን ርሱነ። ወሶበ እምኔሁ ነጸረ ዕበየ ተአምር ዘኮነ። ምስለ ብእሲቱ ወደቂቁ ከዊኖ ፍልጣነ። በእደዊሁ መኰንን አምነ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሐምሌ_12።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦"ይትዐየን መልአከ እግዚአብሔር ዓውዶሙ። ለእለ ይፈርህዎ ወያድኅኖሙ። ጠዐሙ ወታምእሩ ከመ ኄር እግዚአብሔር"። መዝ 33፥7-8። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 24፥30-36።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ኢይድኅን ንጉሥ በብዝኀ ሠራዊቱ። ወያርብህኒ ኢድኅነ በብዝኃ ኃይሉ። ወፈረስኒ ሐሰት ኢያድኅን"። መዝ 32፥16-17። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 9፥17-30፣ ይሁ 1፥7-14 እና የሐዋ ሥራ 10፥3-9። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 18፥1-9። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ነው። መልካም የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤል የወራዊ በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
