uk
Feedback
በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪

በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪

Відкрити в Telegram

♥አላማው ☞መንፈሳዊ ወንድምነት እህትነት ማጠናከር ☞መንፈሳዊ ምግብን ተመግበን ንስሀ ገብተን በቅዱስ ቁርባኑ የበቃን መሆን ☞ተሞክሮዎችን በማካፈል መልካም ፍሬዎችን ማግኘት 👉ወደ ግሩፕ ለመቀላቀል @egzabehertalakenew

Показати більше
1 719
Підписники
Немає даних24 години
-17 днів
-1430 днів
Архів дописів
ምንነትና ኃይል ከነፍሳችን እንዳይገለጥ ከጽድቅ መንፈስ በጣም የራቀ አኗኗር ለዓመታት አስለምዶን ቆይቶአል፡፡     በመሆኑም አብዛኞቻችን የፍቅር እውነተኛ ትርጉም ተደብቆብናል፡፡ ፍቅር የሕይወታችን ብቻ ሳይሆን የሰብአዊነታችን አካል መሆኑን ስለዘነጋን፤ ፍቅርን አስፈላጊና በተመረጠ ቦታ ላይ የምንገልጸው ስጦታ አድርገነዋል፡፡ ከሌላ ሰው በተሰጠን ጊዜ የምንመልሰው ምላሽ አድርገነዋል፡፡ በቤተሰብ፣ በጾታና በትውውቅ ግንኙነቶች መካከል የተወሰነ የመግባባት አጥር አድርገነዋል፡፡ ሲመቸን፣ ደስተኛ ስንሆን፣ ጉድለት ሲጠፋልን፣ ችግር ሲርቅልን የምንገለጽው ስሜት አድርገነዋል፡፡ ፍቅር ግን እጅግ በጣም ትንሽ ከምትባለው የሰኮንዶች መልካም ነገር ጀምሮ ሁሉንም የተቀደሰ መልካም አሳብ፣ መልካም ቃልና መልካም አኗኗር የሚጠቀልል የመለኮት ውበት ነው፡፡    ለዚህ ደግሞ መታመኛ ምስክራችን የተፈጠርንበት የልዩ ሦስትነት መልክ ነው፡፡ መልካችን የሆነው ወላዲ አባት እግዚአብሔር አብ መለኮታዊ አሳብ(ልብ) ነው፡፡ ተወላዲ ልጁ እግዚአብሔር ወልድ መለኮታዊ ቃል ነው፡፡ ከአብ የሠረፀው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሕይወት(እስትንፋስ) ነው፡፡ (የዮሐንስ ወንጌል 1፥1)     ነፍስ የነዚህን ሦስት አካላት መልክ በሕልውናዋ በመያዝ፤ ልባዊ(የምታስብ)፣ ነባቢ(የምትናገር) እና ሕያው(የምትኖር) ሆናለች፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ፍቅር ነው ካልን፤ እንግዲያ በልዩ አካላዊ ሦስትነቱም እንዲሁ አሳቡም ፍቅር፣ ቃሉም ፍቅር፣ ሕልውናውም ፍቅር ነው ማለት ነው፡፡ (አብ ፍቅር ነው፣ ወልድ ፍቅር ነው፣ መንፈስ ቅዱስ ፍቅር ነው)    ስለዚህ የእኛ ሰው የመሆናችን ቁልፍ እዚህ ውሰጥ አለ፡፡ የሰብአዊነት መልካችን እግዚአብሔር ሲሆን፤ እንደ መልካችን በመገለጥ ፍቅርን ስናስብ፣ ፍቅርን ስንናገር እና ፍቅርን ስንኖር ሰውነትን አግኝተነዋል፡፡     አንድ አሳብ፣ አንድ ቃልና አንድ ድርጊት በፍቅር ወለል ላይ ቆሞ እርምጃ ሲጀምር፤ መልኩ የሰውነትን ቅርጽና የሰውነትን መንፈስ ይይዛል፡፡ የእግዚአብሔርንም ኃይል ይሸከማል፡፡ (አንዱ ቃል በፍቅርና በጥላቻ ባሕሪይ ሲነገር የተለያየ ተጽዕኖ የሚፈጥረው በዚህ ምክንያት እንደሆነ ልብ ይሏል!) ከዚህ ባሻገር ግን፤ የሰው እጅና እግር፣ የሰው ጭንቅላት፣ የሰው ቆዳና በአጠቃላይ የሰውን ውጪያዊ መልክ መያዝ ብቻውን "ሰው" አያሰኝም፡፡ በዚህ ልኬት ላይ የሰውነት ሚዛን ቢሰፈር ኖሮ፤ ራሳቸው የሰው ልጆች ከሠሯቸው ተንቀሳቃሽ ሮቦቶች(artificial intelligence) ጀምሮ ብዙ ቁሳዊ ነገሮች ሰው የመሆንን ስያሜ ይጋሩት ነበር፡፡ ወደ ሥጋና ደሙ መጓዛችንን እንቀጥላለን... #ጸባኦት_ይከተላችሁ @bemaledanek

   "እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደ ሆነ አየ፤ እግዚብሔርም ብርሃንንና ጨለማን ለየ" የሚለው ቃልም እንደሚነግረን፤ በጨለማው ዓለም ላይ ብርሃን በተገለጠ ጊዜ አብረው በቅድስና የተገለጡት መላእክት መልካም(ታማኝ፣ ታዣዥ፣ ንጹሕና ጽኑ) እንደሆኑ እግዚአብሔር አየ፡፡ ስለዚህም ለእነርሱ የመንፈሱን ኃይልና ግርማ አካፍሎ አገልጋዩ ሲያደርጋቸው፤ በጨለማው ጊዜ የካዱት መላእክት ከዚህ ሹመት የተለዩ ሆኑ፡፡ ይህንንም መለየት መጽሐፍ "ከዚያም ወዲያ በሰማይ ስፍራ አልተገኘላቸውም" በማለት ይገልጸዋል፡፡ (የዮሐንስ ራእይ 12፥8)     መላእክትን እንዲመራ አክብሮ የፈጠረው ሳጥናኤል በክፉነት ፍላጎቱን ገልጾ ርኩስ በመሆን ከሰማይ ቅድስና ሲለይ፤ ከድቶ ባፈነገጠው ነገድ ፋንታ፤ ፍጥረታትን የሚያስተዳድር፣ እንደ ተቀደሱት መላእክት በብርሃን ጸጋ የሚመላለስ፣ በክብርም ከፍ ያለ ፍጡር መቶኛው ሙሉ ነገድ ይሆን ዘንድ "እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረ፤ በእግዚአብሔር(በፍቅር) መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው።" (ኦሪት ዘፍጥረት 1፥27)     "ከሰማይ(ከብርሃን) ስፍራ ያልተገኘለት" ጨለማው ዲያቢሎስ፤ እርሱ በተዋረደበት ቦታ ላይ እኛ ባለ ክብር ሆነን መፈጠራችን በእጅጉ ያስቀናዋል፡፡ ይባስ ብሎ በእግዚአብሔር ምሳሌ ተፈጥረን በብርሃን ጸጋ በመክበር አስተዳዳሪ መሆናችን ደግሞ ተመኝቶ ያጣውን ገዢነት በኛ ተፈጥሮ ላይ ስላየው መገመት በማንችለው የጥላቻ ጥግ አምርሮ እንዲጠላን አደረገው፡፡ (የተፈጠርንበት ቀን 6፥ ዲያቢሎስ ጥላቻን ያለማቋረጥ ወደኛ እንዲገልጽ የአሳቺነት መታወቂያን ያተመበት ቀን ነው)     በፍጥረት ወገኖቹ ከሆኑት መላእክት ጋር በመጀመሪያ ተዋግቶ የተሸነፈው ዲያቢሎስ፤ ከመላእክትም በላቀ ክብርና ግርማ የተፈጠረውን የሰው ልጅ በቀጥታ ተፋልሞ ሊጥለው እንደማይችል ከቀደመ ሽንፈቱ ተሞክሮ ወስዶአል፡፡ በአዳምና በሔዋን ላይ መልቶ የነበረውም የብርሃን ጸጋ ጨለማነቱን በመቃወም ማንነቱን እንደሚገልጥበት ያውቃል፡፡ ስለዚህ እውነተኛ መልኩን(ጥላቻውን) በሥጋ ደብቆ በእንስሳ አካል ተሰውሮ ወደ ሔዋን ሄደ፡፡ (ይሄ በሥጋ የመደበቅ ጉዳይ፥ ዘግይቶ ክፉው መንፈስ በኛ የሥጋ ባሕሪይ ላይ የርሱን መለያ እንዲያስቀመጥ ፈለግ የተወ ምሪት ሆኖአል፡፡ ጥላቻንም በባሕሪያችን የማፍለቅ ግፊት የመጣው ከዚህ በኋላ ነው፡፡ የመጀመሪያው ጥላቻን በሰው አካል የመግለጥ የመናፍስት ሴራ በቃየን ባሕሪይ ላይ ተጀመረ)     እዚህ ጋር ያለው እቅድ ተነድፎለት የታለመው የእባቡ ምኞት፤ አዳምና ሔዋን በራሳቸው ፈቃድ ወስነው ከራሳቸው ላይ ያለውን የብርሃን ጸጋ እንዲገፍፉት ነው፡፡ የተሰጣቸውን መልክ እንዳይኖሩት ሌላ በር መክፈት ነው፡፡ እንዲህ የሚሆነው ደግሞ ከእግዚአብሔር አምላካቸው ፈቃድ ሲለዩ እንደሆኑ ገልጽ ስለሆነ፤ ከሴቲቱ ጠጋ ብሎ "በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት።" (ኦሪት ዘፍጥረት 3፥1)    ዲያቢሎስ ወደ ሔዋን እንደደረሰ ተቀዳሚ ሥራው ያደረገው የእግዚአብሔር የሆነውን አሳብ ከውስጧ መለወጥ ነው፡፡ "በውኑ አትብሉ ብሎአልን?" ሲል በአንጻራዊ ጎን ያለውን፥ ትእዛዝ ተላልፎ የመብላትን አሳብ፥ እንደታውጠነጥን ዕድል አመቻቸላት፡፡ ሔዋንም የእግዚአብሔር መልክ ያላት የፍጥረታት ንግሥት ከመሆን ባለፈ፥ እግዚአብሔርነት አገኛለሁ በሚል ዲያቢሎሳዊ ቅዠት አትንኩ የተባለውን የዛፍ ፍሬ ከባልዋ ጋር ወስዳ በላች፡፡     በዚህ ጊዜ ከእነርሱ መልክ ውጪ ያለውን፥ የነፍስ ባሕሪይ የማታውቀውን፥ በልዑል አምላክ እቅድ ውስጥ ያልተቀመጠውን፥ "ክፋትን" የማገናዘቢያ ዓይኖቻቸው ሲከፈቱ፤ ከሰውነታቸው ላይ የብርሃናቸው ጸዳል ተገፍፎ "ዕራቁታቸውን እንደሆኑ አወቁ" (ኦሪት ዘፍጥረት 3፥6)፡፡ (ባዕድ አምልኮት የሚባለው ገለጻ ይህንን ያመለክተናል፡፡ ነፍስ ባሕሪይዋ ከተሠራበት ውጪ ያለውን መልክ አታውቀውምና የጣዖታት አምላክነት ለርሷ ባዕድ ይሆናሉ)     ብርሃናዊነታቸው ከሥጋዊ አካላቸው ላይ የተነሣው አዳምና ሔዋን፤ የተፈጥሮአቸው ጸዳል ተሰብስቦ በለስ የቀጠፉበት የእጅ ጣታቸው ላይ የወቀሳ ማስታወሻ ሊሆን ጥፍር ሆኖ በቀለ፡፡ ነፍስም በሥጋ ላይ የነበራት ቁጥጥር ተነሥቶ ከአፈርማው ተክለ ቁመና በታች ተሸሸገች፡፡ የዚህ ጊዜ አዳምና ሔዋን ተስምቶአቸው የማይታወቅ አዲስ ሥጋዊ ስሜትን አስተናገዱ፡፡ ፈሩም፡፡ ስለዚህም ወደ ጫካው ዘልቀው ገቡና ከብርሃን እግዚአብሔር ፊት ተሸሸጉ፡፡ (ኦሪት ዘፍጥረት 3፥8)     እነሆም አዳም በባሕሪይው ከእንግዲህ ብርሃንን በመፍራትና ባለመፍራት መካከል የሚዋልል አዲስ ጠባይ ያለው ሰው ሆነ ማለት ነው፡፡ መልኩን በመግለጥና ባለመግለጥ ፈንታ የሚዋትት ሕይወትን ጀመረ ማለት ነው፡፡ የሰው ልጅ ነፍሱ በሥጋው ላይ እንድትሰለጥን መንገዱን በእምነት ጎዳና አድርጎ ከከፈተላት፤ እስትንፋሲቱም ከእግዚአብሔር የተካፈለቺውን መለኮት በሥጋ ላይ በመግለጽ መንፈሳዊ ጠባያቶቿን ታስነብባለች፡፡ ሰው ፍቅርን ፍጹም አጽንቶ ሲመላለስበት፤ ከሞት ቅጣት ጋር ተያይዞ የመጣበትን የቀደመውን ፍርሃት አውጥቶ ይጥላል፡፡ (1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፥18)    ቅዱሳን ሰማእታት ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ተገደው፤ እሳት ውስጥ የሚገቡት፣ በመጋዝ የሚሰነጠቁት፣ ወደ ገደል የሚወረወሩት፣ በፈላ ውኃ የሚቀቀሉት፣ በሰይፍ የሚታረዱት፣ በጦር የሚወጉት ለዚህ ነው፡፡ በጽድቅ አኗኗር ዘመናቸውን ሲያሳልፉት፤ የነፍስ ተፈጥሮአቸው እንደ ቀደመው የአዳም ገጽታ በሥጋ ላይ ብርሃን ሆኖ ስለሚሰለጥን፤ ከነፍስ ወደ ውጨኛው አካል የሚፈልቀው ፍቅር በዓለም ላይ ዲያቢሎስ የሚነዛውን ፍርሃት ሁሉ ገርስሶ ይጥልላቸዋል፡፡     ሰዎች እንግዲህ ፍቅርን በመኖርና ባለመኖር መካከል ዕለቶቻችን እየዋዠቁ የሚገኙት፤ ነፍስ ከአካሏ እግዚአብሔር ጋር በመሆን ባሕሪያቶቿን እንዳታንጸባርቅ ርኩሳን መናፍስት በብዙ መስመሮች አልፈው ወደ ኑሮአችን እየመጡ የጥላቻን ገጽታ እንድናውቀው በሥጋ ምሽግነት ስለሚዋጉን ነው፡፡     ሔዋን ስለ ዛፉ ፍሬ እያሰበች ያላትን መለኮታዊ መልክ እንዳታስተውል መንፈሱ የመጤ እውቀት ጥላ ሆኖ ከፊት ወደኋላ እንደሸፈናት፤ ሁላችን የአዳም ዘሮች ትክክለኛውን የፍቅር ትርጉም በዓለማዊ ፍልስፍናዎችና ትንተናዎች አዛብተን መልካችንን እንድናጣ፤ በየዘመኑ በሚነሡ ርዕዮቶች፣ አመለካከቶች፣ ፍልስፍናዎች፣ ንድፈ ሐሳቦች፣ የኑሮ ዘይቤዎችና ሳይንሳዊ አስተንትኖቶች ጀርባ ዲያቢሎስ የራሱን ጽልመታዊ አካሄድ እያስገባ፤ ተፈጥሮአችንን እያበላሸው ይገኛል፡፡    "ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና" ካልን፤ እግዚአብሔር ደግሞ ፍጹም መልካምና ቅዱስ ነው፡፡ (1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፥8) ስለዚህ ፍቅርን የምናውቀው ቅዱስ በሆነው መልካም ነገር ሁሉ ውስጥ ነው ማለት ይሆናል፡፡     ከጥንት የሰዎች መነሻ ታሪክ አንስቶ እስከ ዛሬው ዘመናችን ድረስ ክፉ መናፍስት የተቀደሰውን መልካም ነገር ባላንጣ ሆነው የሚዋጉት ፍቅርን እንዳንኖረው ነው፡፡ እግዚአብሔርን የማያውቅ ጊዜ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ትውልድ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ሕይወት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ አሳብ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ እውቀት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ጥበብ፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ንብረት፣ እግዚአብሔርን የማያውቅ ሥልጣን በምድራችን ላይ እንዲንሰራፋ ሰፊውን ድርሾ ወስዶ ሚናውን በሚገባ የተጫወተው የዲያብሎስ ሠራዊት፤ የአዳም ልጆች መልካቸውን ማስታወስ አቅቶአቸው፤ የዘመኑን ሥጋዊ መልክ መስለው እንዲኖሩ የፍቅርን

1• ፍቅር      1.1• ፍቅር ምንድነው? ክፍል - ፩     ✞ የሰው መልኩ ፍቅር ነው "እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፤ ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ።" (ኦሪት ዘፍጥረት 2፥7)     አምላክ ፍጥረታትን ሁሉ በስድስት ቀን ተከታታይነት ፈጥሮ ሥራውን ካበቃ በኋላ፤ በመጨረሻው ላይ ከፈጠራቸው ፍጡራን ሁሉ ለየት ያለ አንድ ፍጡርን በረቂቃን እጆቹ ሠራ፡፡ የመሬትንም ጭቃ አንስቶ ከመለኮቱ ኃይል የወጣ እስትንፋስን አሳረፈበት፡፡ በዚህ ጊዜ ሸክላው መንቀሳቀስ ጀመረና ሕይወት ያለው ልዩ አካል ሆነ፡፡  (እግዚአብሔር ከሁሉ የተሰወረ ሕላዌ ያለው መንፈስ ነውና፤ ጭቃ አንስቶ ሠራን ሲባል፥ ይሄ ክንውን መንፈሳዊ አንድምታ እንዳለው መረዳት ይገባናል፡፡ በሥጋ ምናብ እንደምንስለው አፈር የማድቦልቦል አይነት ሥራ ሠራ ማለት አይደለም፡፡ )    በተገለጸው የአፈጣጠራችን ሂደትም መሠረት የሰው ልጆች ከፍጥረታት ሁሉ በሦስት ነገሮች እንለያለን፡፡ አንደኛ ከሁሉ በስተመጨረሻ የተገኘን የአምላክ አሳብ መጥቅለያና ማረፊያ በመሆናችን እንለያለን፡፡ ሁለተኛ እግዚአብሔር ፍጥረታትን ያስገኛቸው በቃሉና በአርምሞ ሲሆን፤ እኛን ሁላችን ግን የእጁ ሥራ ነን፡፡ (ኢሳይያስ 64፥8) ሦስተኛ ምድራዊ አካል አፈር እና ሰማያዊ አካል የመለኮት እስትንፋስ ተዋሕደው ባሕሪያችንን ገንብተዋል፡፡ እነዚህ ሦስቱ ልዩነቶችም የሰው ልጅ ከሁሉ ፍጥረታት ይልቅ በእጅጉ የከበረ ፍጡር ስለመሆኑ ያሳያሉ፡፡     በሦስተኛነት የተጠቀሰው የልዩነታችን እውነት ግን የከበረን ፍጡራን ብቻ ሳንሆን የእግዚአብሔር መልክ የተሳለብን የንጉሥ ልጅ ንጉሦች እንደሆንን ያስረግጣል፡፡ "እግዚአብሔርም አለ። ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤" (ኦሪት ዘፍጥረት 1፥26)     እግዚአብሔር በራሱ መልክ አምሳል አድርጎ ሰዎችን የፈጠረው በእስትንፋሱ በኩል ነው፡፡ ሁሉንም ፍጡራን ሲያስገኝ ከክሂሎቱ እውቀት ወይንም ከሌላ ተፈጥሮ በመውሰድ በሥልጣኑ ጥበብ ሲፈጥር፤ አዳምን ግን ያስገኘው ከራሱ ውስጥ ካለ መለኮት አካፍሎ፥ እስትንፋሱን ነፍስ አድርጎ በመለገስ ነበረ፡፡     የሰው ልጅ አርአያ አምላክ ነው ሲባል፤ በተክለ ቁመናው፣ በአካላዊ ገጽታውና በተፈጥሮ ቅርጹ አይደለም፡፡ ይልቅስ በነፍሱ ነው፡፡ ነፍስ ከእግዚአብሔር አካል እስትንፋስ በመውጣት ሳትጎድል፥ በኛ ሥጋ ውስጥ በማደሯ፤ የርሱን ረቂቅ ባሕሪያት ማንነቷ አድርጋ በመያዝ ፈጣሪን የሚመስል ሕልውና ይዛ ትገኛለች፡፡     ነፍስ የእግዚአብሔር ክፍል እንደመሆኗ መጠን፤ እርሱ የሆነውን ነች፡፡ አምላክ መለኮታዊ ባሕሪይ እንዳለው እርሷም ከዚህ ባሕሪይ ተካፋይ ነች፡፡ አምላክ ረቂቅ ኃይል እንደሆነ እርሷም መንፈሳዊ አካል ነች፡፡ አምላክ በልዩ ሦስትነትና አንድነት ማንነቱ ሲገለጥ፤ እርሷም ሦስት ባሕሪያትን በአንድ አካል ላይ ሳትቀላቅልና ሳትነጣጥል ይዛለች፡፡ አምላክ የማይለወጥ አንድ ፈጣሪ እንደሆነው፤ ነፍስም መሞት፣ መጥፋትና መቀየር የማያገኛት ጽኑዕ ነች፡፡ አምላክ የሁሉ አስተዳዳሪ ንጉሥ እንደሆነ፤ የንጉሥ አካል ንጉሥ የሆነቺው ነፍስም በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትን ሁሉ አዳም እንዲገዛ ምክንያት ነበረች፡፡ "...የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።" (ኦሪት ዘፍጥረት 1፥26)     አሁን ይህንን ግንዛቤ እንደ መሠረታዊ ብያኔ ወስደን፤ ወደተነሣንበት ርዕስ ስንመጣ "ፍቅር ማለት ምን ማለት ነው?" የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የሚያስችል ቃል፤ መጽሐፍ ቅዱስ በ1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፥8 ላይ "እግዚአብሔር ፍቅር ነው" በማለት ያስቀምጣል፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር ከሆነ ዘንዳ፥ ነፍስም ደግሞ ፍቅር ናት፡፡ በሌላ አገላለጽ፤ ፍቅር ማለት የነፍስ ጠባይ ነው፡፡ ፍቅር ማለት የሰው መለኮታዊ መልክ ነው፡፡     ፍቅር የተሰኘውን የእግዚአብሔርነት አካል፤ የምንማረው፣ የምንሰለጥነውና እንደ መረጃ የምንቀበለው ግኝት ወይንም እውቀት አይደለም፡፡ (ከሰው ልጆች መካከል የገዛ መልኩን ከሌላ ሁለተኛ አካል የሚቀበል ማነው?)     ፍቅር ስንወለድ አብሮን የሚወለድ ማንነት ነው፡፡ ፍቅር ስናድግ አብሮን የሚያድግ አካላችን ነው፡፡ ፍቅር ባለ የሕይወት ዘመናችን ሁሉ ላይ የማይጠፋ፣ የማይቆረጥ፣ የማይለይና የማይጣል ውሳጣዊ ክፍለ ባሕሪይ ነው፡፡     አንዳንዴ ሰዎች "እኔ ፍቅር የለኝም" ብለው በደፈናው ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ አላወቁትም እንጂ እያሉ ያሉት "እኔ መልክ የሌለኝ ሕይወት አልባ ፍጡር ነኝ" ነው፡፡ ያለ ነፍስ የተፈጠረ አንድም የሰው ዘር እንደሌለ ሁሉ፤ ያለ ፍቅርም የተገኘ ነፍስ ሊኖር አይችልም፡፡     ፍቅርን ከሕልውናው መዝገብ አውጥቶ የጣለ ብቸኛው ፍጡር ዲያቢሎስ ነው፡፡ (አሁን ያለንበት ዓለም የፍቅርና የጥላቻ ፍትጊያ መነሻ ሰበዙ የሚመዘዘው ከዚህ ፍጡር የዓመፃ ታሪክ ላይ ነውና እስቲ ነገሩን በዝርዝር እንየው)     ከሁሉ አስቀድሞ በራሱ ዓለም ይኖር የነበረው ቅዱስ እግዚአብሔር፤ በአርምሞ ኃይል "ሰማይንና ምድርን በመጀመሪያ ከፈጠረ" በኋላ፤ በቃል በመናገር ደግሞ እግዚአብሔር በፈጠረው ዓለም ላይ "ብርሃን ይሁን አለ፡፡" ኦሪት ዘፍጥረት 1፥3)     የእግዚአብሔር ቃል ብርሃንን ወደ ዓለም ከማስገባቱ በፊት፤ ሰማይና ምድር በተፈጠሩበት የመጀመሪያው ቀን አብረው ስለተፈጠሩት መቶ የመላእክት ነገድ በመጽሐፍ ቅዱስና በሌሎች በርካታ መንፈሳዊ መጽሐፍት ላይ ተመዝግቦ እናገኛለን፡፡ ከእሳትና ከነፋስ በልዩ ጥበብ የተፈጠሩት መላእክት፤ ሁሉ ጨለማ በነበረበት የዓለም ገጽታ ውስጥ ፈጣሪያቸውን ለማግኘት በተሰጣቸው የእውቀት ፈቃድ መመራመር ያዙ፡፡ መላእክቱን ሁሉ መርቶ ወደ አምላካቸው እንዲያደርስ አለቃ ሆኖ የተመረጠው ሳጥናኤል ነበረ፡፡     ይህ መልአክም የእግዚአብሔር ሕልውናና ኃይል በብርሃን ባልተገለጠበት ሁኔታ ከእርሱ ማዕረግ ከፍ ያለ ሕይወት ያለው ፍጥረት አለመኖሩን ከተረዳ በኋላ በልቡ የመታበይን አሳብ አፈለቀ፡፡ (ዲያቢሎስ ክፉ ማንነቱን ከባሕሪዩ ወይንም ከልቦናው ነው ያነቃት፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ በጭራሽ የማይታውቅ ጠባይን ከእውቀቱ ውስጥ በራሱ ፈቃድ አፍልቆታል፡፡ (ትንቢተ ኢሳይያስ 14፥8-20 ፤ የዮሐንስ ወንጌል 8፥44) በእርግጥም በባሕሪይው ፍጹም ቅድስና ያለው እግዚአብሔር፤ ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረታት ሲፈጥር አንድም ቅዱስ ያልሆነ ፍጥረት አላስገኘም፡፡ ኦሪት ዘልደትም በመነሻው ላይ ከፍጥረታት መገኘት በኋላ "መልካም እንደሆነ አየ" በማለት ስድስት ጊዜ በተደጋጋሚ ያስቀመጠው የእግዚአብሔር እይታ፤ በስድስት ቀን ውስጥ የተፈጠሩት ሁሉም ፍጡራን በፈጣሪያቸው ቅድመ አሳብ መልካም እንደሆኑ ያስረዳል፡፡)     ከዚህ ጊዜ በኋላ የእግዚአብሔር ቃል በዓለም "ብርሃን ይሁን" የሚለውን አምላካዊ ሥልጣን ገለጠ፡፡ በተፈጠሩበት የቅድስና አሳብ ጸንተው የቆዩት መላእክት ይህንን ኃይለ ጸዳል ለብሰው ብርሃናውያን ሲሆኑ፤ ክሕደትን ያስገኘው ሳጥናኤልና ያመኑበት መላእክት ደግሞ ጽልመትን ማንነት ጨለማን መገለጫ አድርገው ቀሩ፡፡ (ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፥12)

አባታችን ሆይ እንዴት ትላለህ? እንደ ልጅ ካልኖርህ እንዴት "አባት" ትለዋለህ? ሌላውን ጠልተህ ራስ ወዳድ ከሆንክ እንዴት አባት "አችን" ብለህ በአንድነት ትጠራዋለህ? ምድራዊ ነገር ብቻ እያሰብህ እንዴት "በሰማያት የምትኖር" ትለዋለህ? ልብህ ከእርሱ ርቆ በአንደበትህ ብቻ እየጠራኸው "ስምህ ይቀደስ" እንዴት ትለዋለህ? ሥጋዊና መንፈሳዊውን እየቀላቀልህ "መንግሥትህ ትምጣ" ለምን ትለዋለህ? መከራን በጸጋ የማትቀበል ከሆነ "ፈቃድህ ይሁን" ለምን ትላለህ? ለራስህ ሆድ እንጂ ለተራቡት ግድ የማይሰጥህ ከሆነ ለምን "እንጀራችንን ሥጠን" ትላለህ? በወንድምህ ላይ ቂም ይዘህ "እኛም የበደሉልን ይቅር እንደምንል" እንዴት ትላለህ? የኃጢአትን አጋጣሚዎች ሳትሸሽ "ወደ ፈተና አታግባን" እንዴት ትላለህ? ክፉን ለመቃወም አንዳች ሳታደርግ "ከክፉ አድነን" እንዴት ትላለህ? ጸሎቱን ከልብህ ሳትሰማውስ እንዴት አሜን ትላለህ? ?! ዲ/ን ሄኖክ ሀይሌ

አንድ አማኝ ቅዱስ ቁርባን ከተቀበለበት ጊዜ በኋላ ኃጢአት ቢያስተው ይቀሠፋል የሚባለው ሙሉ ለሙሉ ሐሰት ነው፡፡ እንዲህ ቢሆንማ፥ እኔን ጨምሮ ስንት ሰው እስካሁን ተቀሥፎ አልቆ ነበረ፡፡ "እንደ ቸርነትህ እንጂ እንደ በደላችን አይሁን" ከምንልበት የቅዳሴያችን የኅብረት ተማጽኖ በተቃራኒ የተሰለፈ፥ ዲያቢሎስ የሚያራግበው የወሬ ነፋስ ነው ይሄ፡፡ ሐዋሪያው ጴጥሮስ ሊቀ ካህኑ ኢየሱስ ራሱ ባርኮ ባቀበለው ሥጋና ደሙ ስለመቀደሱ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የመከራዋ ለሊት ስትደርስ፥ ማታቸው ስትመጣ፥ የጨለማ ሥልጣናቸውን አግኝተው ክርስቶስን ያሰሩ ጉልበተኞች "አንተም ከእርሱ ጋር ነህ" ቢሉት ከአንድም ሦስቴ "ኸረ አላውቀውም" ሲል ካደ፡፡ (የዮሐንስ ወንጌል 18፥25 ፤ የሉቃስ ወንጌል 22፥58) ሥጋውን በልቶ፥ ደሙን ጠጥቶ አላውቀውም? እንዴት ነው ነገሩ? ከተቆረበ በኋላ ስሕተት ሊኖር እንደሚችልና ጴጥሮስና ሐዋሪያቱ እነሆ በታሪካቸው አስተማሩ፡፡ አስቀድመው ሲከተሉት፣ ድንቅ ሥራውን ሲያዩ፣ ቃሉን ሲሰሙ የቆዩት ሥጋና ደሙን ከተቀበሉ በኋላ እንደማያውቁት ሆነው ጥለውት ሸሹ፡፡ ወደነበሩበት ሊመለሱ አፈገፈጉ፡፡ ሕብረተሰባችን መካከል ዛሬ እንደሚመላለሰው ወሬ ቢሆን፥ ሐዋሪያቱ መቀሠፍ ነበረባቸው፡፡ ነገር ግን ጴጥሮስ ሥጋና ደሙን ወስዶ ስለፈጸመው ጥፋት ንስሐ ገባ እንጂ አልተቀሠፈም፡፡ (የሉቃስ ወንጌል 22፥62) እንደውም ሦስት ጊዜ ደጋግሞ ከድቶ የነበረውን ስምዖን፥ በደልን ፈጽሞ የሚረሳው ጌታ ከትንሣኤው በኋላ ሲያገኘው "ትወደኛለህን?" አለው፡፡ ከዚህ በፊት በአስቸጋሪው ወቅት "አላውቀውም" ሲል የነበረው አገልጋይ፥ እዚህ ከንስሐ በኋላ ቋንቋው ተቀይሮ ሦስቴ "እንድወድህስ አንተ ታውቃለህ" ይለው ጀመረ፡፡ (የዮሐንስ ወንጌል 21፥15-17) ፍቅሩንም ሕይወቱንም አሳልፎ ሰጠው፡፡ ወንጌል የሚያውቀው እውነት እንግዲህ ይሄ ነው፡፡ ዛሬ አንዳንድ የንስሐ አባቶች፣ አገልጋይ ነን የሚሉ ሰዎችና ማኅበረሰብ ወጣቱን ከማስተማር ይልቅ ያርቁታል፡፡ "ወዮውልሽ" አይነት ማስፈራሪያዎች ከዛም ከዚህም ይወረወራሉ፡፡ ጫት ሲበላ ተው ትቀሠፋለህ የሚል እምብዛም የለም፡፡ መጠጥ ሲጠጣ ተው ትጠፋለህ የሚል ትንሽ ነው፡፡ ሥጋና ደሙን ልውሰድ ሲል ግን ብዙዎች ያንጎራጉራሉ፡፡ ለምን? ለምን ከሥጋና ደሙን ወጣቶችን እናርቃለን? ወጣቶች እወቁ! ቅዱስ ቁርባንን ለመውሰድ የተቀመጠ የዕድሜ ገደብ የለም፡፡ "ወጣት ከሆንክ ስለምታጠፋ አትቁረብ" የሚሉት፤ ስለ አምልኮት ሕይወትና የክፉ መናፍስት ጥልቅ ሥራ በተግባር ያልተገነዘቡ፥ በልምድ አካሄድ የሃይማኖትን ጎዳና የጀመሩ ሰዎች እንጂ ቤተክርስቲያን አይደለችም፡፡ ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ቀድሳ ሥጋና ደሙን አዘጋጅታ ጠቦቶቿን ከእረኛቸው ሥጋ የማካፈል አደራዋን ዘወትር ትወጣለች እንጂ ዕድሜውን ቆጥራ "አንተ አትቁረብ" የምትለው አንድም ወጣት የለም፡፡ ሲሆንማ፥ ይልቁኑ ሥጋና ደም ለማን በጣም ያስፈልጋል ካላችሁኝ ለወጣቱና ለጎልማሳው ነው ያስፈልጋል የምለው፡፡ ምክንያቱም ስሜታዊነት የሚወጣበት፣ ጉልበት የሚጠነክርበት፣ ብዙ ሥራ የሚሠራበት፣ ትዳር የሚመሠረትበትና እንደ አገርም አምራች ዜጋ የሚኮንበት የዕድሜ ክልል ስለሆነ፥ በዚህ የጉብዝና ጊዜ ነው እግዚአብሔር አብሮ መገኘት ያለበት፡፡ ስሜታዊነትን ወደ መንፈሳዊ ኃይል እንዲቀይረው፣ ጉልበታችን በመናፍስት እንዳይደክም አሊያ ለክፋት እንዳይውል፣ ሥራችን እንዲባረክ፣ ትዳራችን እንዲሰምር፣ የአገር ፍቅር ከታሪክ ቁጭት ጋር ያለው የተቀደሰ ዜጋ እንዲኖር ሥጋና ደሙ መቅረብ የነበረበት ለወጣቶች ነበረ፡፡ አልሆነም! ተገላበጠና ወጣቶች ከቅዱስ ቁርባን ሲርቁ ይኸው ነገራችንም ከብዙ እውነቶች ተገላብጦ ቁጭ አለ፡፡ #ጸባዖት_ይከተላችሁ @bemaledanek

እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ እንኪያስ ለምንድነው ምእመናን ከቅዱስ ቁርባን የተለዩት? ከክርስቶስ ማዕድ መካፈል ያቃተቸው ክርስቲያኖች ስለምን በርካታ ሆኑ? አዲስ ኪዳንን የምሕረት ዘመን ያሰኘው የመዳን ዋስትናችን የመስቀሉ መሥዋዕት ሆኖ እያለ ብዙዎች ከእርሱ ለምን ራቁ? የተዋሕዶ ሃይማኖት አንዱ ዓምድ (ዶግማ) የበጉ ሥጋና ደም ነው መባሉ በአማኞች ሕይወት ላይ ለምን በተጨባጭ አልተተረጎመም?.. ? የነዚህና መሰል ጥያቄዎች ቀጥተኛ መልስ በመነሻ አንቀጻችን ላይ የተጻፈው ይሆናል፡፡ እንደ እግዚአብሔር ለመሆን ያለማቋረጥ የሚጥረው ዲያቢሎስ፥ አትንኩት ብሎ በዐዋጅ እንዲከለከሉ ካደረጋቸው ገደቦች መካከል መቀደስ (ቀ ጠብቆ ይነበብ) በግንባር ቀደምነት ይጠቀሳል፡፡ ስናስታውስ፥ በመጀመሪያ በእኛ በእግዚአብሔር መካከል "አትብሉ"ን አሰበልቶ ከፈቃዱ ነጥሎን ነበር፡፡ አሁንም ይሄው አካሄዱ ይዘቱን ሳይለውጥ ቀጠለና "ብሉ" የተባለውን አትብሉ አስደርጎ ፈቃዱን እንዳንኖር እየተዋጋን ይገኛል፡፡ የተከለከልነውን አስፈቅዶ፥ የተፈቀደልንን ከልክሎናል፡፡ አንባቢ የምለውን ተመልከት፥ በነገሩ ላይ ጌታ ማስተዋልን ይስጥህ! ክፉው መንፈስ እንደ ፍላጎቱ በሰውነታችን ላይ ፈላጭ ቆራጭ እንዲሆን እኛነታችንን ከመንፈስ ቅዱስ መለያየት ያስፈልገዋል፡፡ በቃ ቅዱስ ቁርባን ላይ ከተለያየ አቅጣጫ የተከፈተው አጠቃላይ ዘመቻ ከዚህ የጠላት ፍላጎት ይመነጫል፡፡ ከእግዚአብሔር በራቅን ልክ እርሱ ወደኛ የሚጠጋበት ርቀት ያጥርለታልና፥ ከአምላክ ጋር የሚያስተባብረንን የኪዳኑን ጸጋ እንዳናገኘው ባገኘውና በሆነለት መንገድ ሁሉ እየተጠቀመ ያሸሸናል፡፡ እንዴት?                           3.3.1.  በኃጢአት በኩል ኃጢአት በሰውና በአምላክ መካከል ያለ የዓመፅ ግድግዳ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር እንዳንሆን የሚፈልገው መንፈስ፥ ኃጢአትን በማስተዋወቅ፣ በማስፈጸምና በመምራት ከመለኮት ንጽሕና ይለያየናል፡፡ ብቻ ሳይሆን፥ ኃጢአት ከሕይወታችን ሳይወጣ እንዲቆይ በማጽናት ቅድሰና እንዳያገኘን ነቅቶ ይጠብቃል፡፡ የመድኃኒታችን ሥጋና ደም ስለ ኃጢአት ሥርየት የተሠዋ ዘላለማዊ መሥዋዕት እንደሆነ በክፍል ፫ አይተናል፡፡ እነሆም ዲያቢሎስ በኃጢአት ረግረግ ተውጠን እንድንያዝ ሲወድ፥ ኃጢአትን ከሥር መሠረቱ ነቅሎ የሚጥለውን ቅዱስ ቁርባን በእጅጉ ይጠላዋል፤ ይፈራዋል፡፡ ይሄንን ፍራቻውንም ባላጋራ ሆኖ ላደረበት አስተሳሰባችን ለማጋባት የሚከተሉትን ሁለት ዋና ዋና ስልቶች አቀናጅቶ ይተገብራል፡፡ እንመልከታቸው፡፡                       1•  ከኃጢአት የመላቀቅ ፍራቻ "እኔ ኃጢአተኛ ነኝ፤ ለሥጋና ደሙ የበቃሁ አይደለሁም፤.. " የሚሉ ዓይነት ምላሾች፥ ቅዱስ ቁርባን ለምን እንደማይወስዱ ከተጠየቁ ብዙ ምእመናን ዘንድ ይነገራሉ፡፡ እነዚህ ንግግሮች በአብዛኛው ሰማያዊውን አምኃ ከማክበርና ከመፍራት የተነሱ እንደሆነ ይታሰባል፡፡ በእርግጥስ፥ ከኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ አካል የሚያካፍለን ክቡር ሥጋና ክቡር ደም እንደምን ያለ የክብር ጥግ፣ እንዴት ያለ የፍርሃት መጨረሻ ቢቸረው (ቸ ጠብቆ ይነበብ) ይመጥነው ይሁን? ነገር ግን መላእክት፣ ቅዱሳን እና ቀደም ሲል እምነታቸውን በየዋህነትና በፍቅር ሲኖሯት የነበሩት ሁሉ ለቅዱሱ መሥዋዕት የሰጡት የክብር ፍራቻ፥ ለዛሬዎቹ እኛ፥ ከኃጢአት ሳይርቁ የመኖር ፍራቻን የምናለባብስበት መጋረጃ ሆኖ ነው እያገለገለ ያለው፡፡ የአብዛኞቻችን "ለክርስቶስ ሥጋና ደም አልገባም" (ገ ጠብቆ ይነበብ) ከምትለዋ የትሕትና ንግግር ጀርባ፥ ኃጢአትን የለመደ ሽሽግ ማንነት አለ፡፡ በሥጋዊቷ ዓለም ስንኖር ክፋቶች ክፉነታቸው እንዳይገለጥልን፥ ቢገለጥልንም ከክፋቶች እንዳንመለስ ማድረግ የክፉ መናፍስት ቀንደኛ ሥራ ነው፡፡ ይኸውም ከእግዚአብሔር የሆነ ቅዱስ ዕውቀት በማሳጣትና ኃጢአትን ተላምደን እንድንኖር ሁለንተናችንን በማጠር የሚከውኑት ይሆናል፡፡ ስለ ኃጢአትና የኃጢአት ራስ ዲያቢሎስ ደገኛ ትምህርት ካለማግኘታችን ጋር ተያይዞ፥ ዓለም በዘመናት ሂደት ሰብስባ ባጠራቀመቺው የአስተሳሰብ ሥርዓት እንድንቀረጽ እየሆነ ከልጅነታችን እናድጋለን፡፡ ይሄ አስተዳደጋችን ደግሞ፤ ጠባይን፣ ፍላጎትን፣ ውሳኔንና ዓላማን ሁሉ በተጽዕኖ የሚነካ፥ ከሕይወታችን ጋር ተጋብቶ ያለ የማንነት መገለጫችን ይሆናል፡፡ ክፉው ለዚህ አስተዳደጋችን ነው እንግዲህ ኃጢአትን በተለያየ ዕውቀት በኩል ለአመለካከታችን በመመገብ፥ ዓመፃዎችን ከለጋነት የሚያለማምደን፡፡ [ወጣቶች፥] ኋላችሁን አስቡት እስኪ፡፡ እስከ አሁናችሁ ድረስ ያወቃችኋቸውና የለመዳችኋቸው ነገራት ምንድን ናቸው? ለጽድቅ ያላቸው ቅርበት ለኃጢአት ያላቸው ርቅትስ ምን ይመስላል?.. ምእመናን ከኃጢአት ጋር ተዛምደው የኖሩባቸው የዕድሜ ቆይታዎች ወደ ተቀደሰው መብል እንዳይመጡ የሚጠልፉ ዕንቅፋቶች ናቸው፡፡ ትናንትናችን ተሳስሮት የቆየው የልምድ ኑሮ ለውጥን አፍኖ የሚይዝ የክፉ መንፈስ ጥምጣም ነው፡፡ ለረጅም ጊዜያት ከውስጣችን ሲገነባ የቆየን ካብ ማፍረስ ራሱን የቻለ ጣር አለበት፡፡ ለምሳሌ ሐሜት ዕለት ተዕለታችን የሆነብን ሰዎች ከቅዱስ ቁርባን በኋላ ያሉት ቀኖቻችንን ምን እንደሚያወሩ ከወዲሁ ስለምናውቅ "የበቃሁ አይደለሁም" በሚል ቋንቋ ሸፍነን "ልምዴን የምተው አይደለሁም" የምትል የውስጠታችንን መልእክት እንተነፍሳለን፡፡ ዝሙት፣ ስካር፣ ዳንኪራ፣ ጉቦ፣ ውሸት፣ ስርቆት፣ ትዕቢት፣ ምቀኝነት፣.. ምሳሌ እንደጠቀስነው እንደ ሐሜቱ ናቸው፡፡ እነዚህና ሌሎችም "ለቁርባን አልገባም" እያልን እሽሩሩ የምንላቸው፣ የዲያብሎስ መንፈስ በምሽግነት የተደበቀባቸው፣ እንድላቀቃቸው በጽድቅ ቀናዒነት ያልጨከንባቸው፣ ከዘወትር ደቂቃዎቻችን መካከል ቦታ ያገኙ ኃጢአቶቻችን፥ የአዲስ ኪዳኑ ታላቅ መሥዋዕት ከሕይወታችን እንዲቋረጥ ለአጥፊው መንፈስ በብዙ አግዘዋል፡፡                      2•   ከኃጢአት ያለመላቀቅ  ፍራቻ ቅዱስ ቁርባንን የተመለከቱ እንደ ማኅበረሰብ ደንቦች ሲዛመቱ ከምንሰማቸው ወጎች መካከል "ቁርባን ዓለም በቃኝ ላለ ሰው ነው፣ ከተቆረበ በኋላ ኃጢአትን መሥራት ያልተላቀቀ ይቀሠፋል" የሚሉት ዝነኛ ሆነው ከጫፍ ጫፍ ተዳርሰዋል፡፡ ያሳዝናል! ወገኖቼ፥ ክርስቶስ የሚያፈቅር እንጂ የሚቀሥፍ፣ የሚያከብር እንጂ የሚያዋርድ፣ የሚያነሳ እንጂ የሚጥል፣ የሚያቅፍ እንጂ የሚገፋ በጭራሽ አይደለም፤ ሆኖም አያውቅም፤ ወደፊትም አይሆንም፡፡ እንኳን ሰዎችን "ሥጋና ደሜን ከወሰዳችሁ በኋላ ኃጢአት ሠራችሁ" ብሎ ሊያጠፋ ይቅርና፥ የጠፉ ሰዎችን ሲያይ የሚያለቅስ የዋህ አባታችን እንደሆነ የሰቀለቺውን ኢየሩሳሌም ባየ ጊዜ እንባውን አፍስሶ ገርነቱን ገልጧል፡፡ "በቅዱስ ቁርባን ምክንያት" መቅሠፍት ይመጣል የሚሉ መነሻቸው ያልታወቁ ድምፆች፥ ዲያቢሎስ የነዛቸው ተንኮሎች እንደሆኑ ሕዝበ ክርስቲያኑ ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡ አዎ፤ የጌታን ሥጋና ደም ሳይገባን (ገ ላልቶም ጠብቆም ይነበብ) መውሰድ አይፈቅድም (1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 11፥27)፡፡ ይሄ የሕግ ድንበር የተሰመረው ግን በመሢሑ በሥጋ መምጣት ያላመኑ፣ አምነውም በስሙ ያልተጠመቁ፣ የመስቀሉን ፍቅር ያልተቀበሉ፣ የቅዱስ ቁርባንን ሚሥጢር ያልተማሩ፣ መንፈሳዊ ኃይልን ለመፈታተን የሚቀበሉ፣ ለሌላ ድብቅ ተልዕኮና አጀንዳ የቀረቡ፣ ከመቁረብ በፊት ንስሐ ያልወሰዱ ሲኖሩ ለማረም ተፈልጎ እንጂ ክርስቲያኖችን ለማስፈራራት ታስቦ አይደለም፡፡ እንደውም ክርስቲያን ከክርስቶስ እንጀራና ጽዋ የማይካፈል ከሆነ ነው ዕዳ ያለበት፡፡

3•  ቅዱስ ቁርባን   ክፍል - ፯        3.3•  የመናፍስት ውጊያ በቅዱስ ቁርባን ላይ ውድቀትን በባሕሪዩ የተጣባት ክፉ መንፈስ "አምላክ እኔ ነኝ" ሲል ዋሽቷል፡፡ እንደ ፈጣሪ መሆን ተስፋ አልቆርጥ ያለ ምኞቱ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ወዳስገኛቸው እያመለከተ "የእኔ ናቸው" ማለትን ከጥንት ጀምሯታል፡፡ የሰውን ልጅ ጭምር! ሰውነት ቤተመቅደስነት እንደሆነ ተነጋግረናል፡፡ ዲያቢሎስ በዚህ ቤተመቅደስ ውስጥ ነው መመለክ የሚፈልገው፡፡ የሰውን ልጅ መግዛት፣ መቆጣጠር ይፈልጋል፡፡ ልክ እንደ አምላክ "ይሄን ይሄን አትንኩ" የሚላቸውን ትእዛዛት ያሰቀምጣል፡፡ እርሱ እንደፈቀደው እንዴት መኖር እንዲገባን ደንብና ሥርዓት የሚያሳዩ ሕግጋት ያረቃል፡፡ ከእግዚአብሔር በተቃራኒ የሚሠራ መንፈስ እንደሆነ ሲታወቅ፥ ሕግ አድርጎ የሚያስቀምጣቸው ትእዛዛቱ የእግዚአብሔርን እንደሚጻረሩ እንዲሁ ለመገመት አይከብድም፡፡ ጽድቅን የሚጠሩና በጽድቅ የሚያኖሩ ማንኛቸውንም ነገራት አትንኩ ይላል፡፡ ይሄ የክፋት ኃይል አዳምን ካሳተ በኋላ ዓለምን በመላ በራሱ መስመርና ዓላማ ለመምራት ያለመታከት ሲደክም ዘመናትን አሳልፏል፡፡ ተሳክቶለትም የምድር ማዕዘናት ጽድቅን በሚቃወሙ፣ በሥጋ ድክመት ላይ በሚመኩ ሥርዓቶች እንዲተዳደሩ አስገድዷል፡፡ ከዚህም የተነሳ በምድራችን የአስተሳሰብና የኑሮ ሚዛን ቅዱስ የሆኑት ከብደው፥ ርኩሳኑ በእጅጉ ቀልለውና በዝተው ይገኛሉ፡፡ ለዚህ በቂ ማሳያ አድርገን የምንናነሳው ርእሳችንን፥ የአዲስ ኪዳኑን አማናዊ ቃልኪዳን፥ የመድኃኒታችንን ሥጋና ደም ነው፡፡ [በተለይ] ባለንበት በዚህ ዘመን፥ ቅዱስ ቁርባን ሲባል የሚጠራው የኪዳኑ ስጦታ ከሰዎች ሕይወት በእጅጉ የራቀ ጉዳይ እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ከታዳጊነት እስከ መካከለኛው የዕድሜ እርከን ያሉ ብዙ አማንያን፥ ከሰማያዊው ማዕድ መካፈል ካቆሙ ሰነባብተዋል፡፡ ቅዱስ ቁርባን በእርጅና ጊዜ የሚወሰድ ልምዳዊ ድርጊት ወደ መሆን ከመጣ ቆየት ብሏል፡፡ ሕፃናት እስከ ዐሥራ መጀመሪያዎቹ ይቆርባሉ፤ ከዛ ሥጋና ደሙ የጠፋ እስኪመሰል ከቁርባን ጠፍተው ያድጋሉ፡፡   በመሆኑ ብዙው ሰው፥ "አንቱ በመቁረቢያ ዕድሜዎት እንዲህ ያደርጋሉ እንዴ?" እስከሚባልበት የጊዜ ማምሻ ድረስ ሕይወት እንደመራው፥ ኑሮ እየጣለው፥ እርሱም ሌላውን እየጣለ፥ የነፍስ እውነትን ረስቶ ይቆይና፤ የዕድሜ በረከት አግኝቶ ለሽበት ሲደርስ ቅዱስ ቁርባን ይቀበላል፡፡ ለዚህ ካልታደለም በዛው ጥቁር ጸጉር ሳለ፥ ጥቁር ኃጢአትና ጨለማ ዘመን ወርሶት፥ "ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ እኔ በእርሱ እኖራለሁ እርሱም በእኔ ይኖራል" ያለውን፥ የክርስቶስን ወዳጅነት በወጣትነቱ ሳያገኘው ወደ መቃብር ይሸኛል፡፡ ለመሆኑ ይሄ የሆነው ለምንድነው? ስለ ቅዱስ ቁርባን ስንማር የቆየነው ቃል ምንድን ነው? በውስጣችን ተቀርጾ ያለው መንፈሳዊ ትምህርት ምን አይነት ነው? እንዴት ነው ክርስትናን የተረዳነው? የመጽሐፍ ቅዱስን ቃላት እንዴት ነው የምንመለከታቸው? ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሞቶ ሞትን ድል ነሥቶ የዘላለም ሕይወት ሰጠን የሚለውን የድኅነት አገላለጽ እንዴት ነው የተገነዘብነው? ክርስቲያኖች ነን ስንል መቼም በክርስቶስ አምነን ነው፡፡ በክርስቶስ ስናምን፥ የተናገራቸውን የታመኑ ቃላት እናምናለን ማለት ይሆናል፡፡ እንግዲያው "እንካችሁ፥ ብሉ ይሄ ሥጋዬ ነው፤ ሁላችሁም ከእርሱ ጠጡ፤ ስለ ብዙዎች ኃጢአት የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይሄ ነው" ያለውን ቃል እንዴት ነው ያመንነው? "ሰው ዓለሙን ሁሉ አትርፎ ነፍሱን ግን ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል?" የሚለው ንግግር የቅዱስ ቁርባን ልክ ይዞ ቢነገር "ክርስቲያን ነገርን ሁሉ አድርጎ የክርስቶስን ሥጋና ደም ካልተቀበለ ምን ይበጀዋል?" ሊባል ይችላል፡፡ ይህም ማለት እንኳን ዓለማዊ፥ መንፈሳዊ ጉዳዮችን ሁሉ ምእመናን አድርገው፥ ከሥጋና ደሙ ጋር ባወቀ ካልተገናኙ ትልቁን ዋጋ አጥተውታል ማለት ነው፡፡ አስተምህሮቱ "የሚሥጢራት ሁሉ ፍጻሜ ቅዱስ ቁርባን ነው" እያለ የሚያውጀው ለዚህ ነው፡፡ ታዲያ ምንድነው የምናስበው? ምንድነው ከውስጣችን ቆይቶ ለዘመናት የገዛን አመለካከት? ስለ ዘላለም ሕይወት ያለን መንፈሳዊ እይታ ርቀቱ እስከየት ይጠልቃል? ስለ መቁረብ ስናስብ ምንድነው ወደ ጭንቅላታችን አስቀድሞ የሚመጣው?    ብዙ ክርስቲያኖች ለቅዳሴ ይቆማሉ፡፡ የሚቆርቡት ግን ከሕፃናትና ከአዛውንት ውጪ ከእጅ ጣቶች የማይበልጡ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ይሄም ነገር የተለመደ ከመሆን አልፎ አሁን ያልተለመደው የወጣቶች ከሕይወት እንጀራ መቁረስ ሆኗል፡፡ ለምንድነው ነው እንደዚህ የሆነው? ለምንድነው ወጣቶች ከክርስቶስ ሥጋና ደም የማይቀበሉት? ለምንድነው መምህራን ስለዚህ ነገር አበክረው የማያሳስቡት? የሚያሳስቡትንስ፥ አማኙ ሕብረተሰብ የማይሰማቸው ለምንድነው? ሥርዓተ ቅዳሴ ያለ ቅዱስ ቁርባን መሥዋዕት ቅዳሴ ይባል ዘንድ አይችልም፡፡ ዝርዝር ትንታኔ ውስጥም ሳንገባ ከስያሜው ብንጀምር "ቅዳሴ" የሚለው ቃል የሚጠቁመው አንድን ነገር የመቀደስ ሂደት ነው፡፡ ያ በምስጋና፣ በአምልኮትና በኅብረት ጸሎት የሚቀደሰው ነገር ሕብሥተ ስንዴው እና ሕብሥተ ወይኑ ነው፡፡ የተቀደሰው ማዕድ ከዛ በእምነት የሚወስዱትን ሁሉ ይቀድሳቸዋል፡፡ ከቤተልሔም እስከ ቀራኒዮ የሚገሰግሰው ቅዳሴ፥ ዋነኛ አንድምታው ይሄ ነው፡፡ ቅዳሴ የአዲስ ኪዳን ቃልኪዳን የሚፈጽምበት ሰማያዊ ሥርዓት ነው መባሉ በክርስቶስ ሥጋና ደም ምክንያት ነው፡፡ ያለ ቅዱስ ቁርባን ቅዳሴ የለም፡፡ በዚህ መሠረት ቅዳሴ አስቀድሰን ከተቀደሰው ምግብና መጠጥ የማንሳተፍ ሰዎች፥ ምን ቀድሰንና በምን ተቀድሰን እንደተመለስን ያልታወቀበት ቆይታ አድርገን ነው የመጣነው ማለት ነው፡፡ ሱታፌ ቅዳሴ ኖሮ ከቅዱስ ቁርባን አለመቀበል አግባብ እንዳልሆነ የቤተክርስቲያን አያሌ ሥርዓተ መጽሐፍት በግልጽ ይደነግጋሉ፡፡ ሌላውን እንተወውና ራሱ ቅዳሴ ከቅዱስ ቁርባን [በፍትሐ ነገሥት ከተዘረዘሩ በቂ ምክንያቶች ውጪ] ሥጋና ደሙን አለመቀበል የአምላክን ትእዛዝ መተላለፍ ስለመሆኑ ገና በመግቢያው ክፍል ላይ ያስጠነቅቃል፦         "በቅዳሴ ጊዜ የሚገኙ ምእመናን፥ መጽሐፍተ ቅዱሳትን ባይሰሙ፣ ቅዳሴ እስኪፈጸም ድረስ ባይታገሡና ከቁርባንም ባይቀበሉ ከቤተክርስቲያን ይሰደዱ፤ ሕገ እግዚአብሔርን አፍርሰዋልና"                                                         መጽሐፈ ቅዳሴ የቅዳሴ ብቻ ሳይሆን የንስሐም አድራሻ ቅዱስ ቁርባን ነው፡፡ "በአዲሱ አቁማዳ አዲሱ ወይን ሊሞላ ይገባል" የሚለውን የጌታ ትእዛዝ ይዛ፥ ቤተክርስቲያን ማንኛውም ግለሰብ ሥጋና ደሙን ከመቀበሉ በፊት ንስሐ እንዲገባ ታዝዛለች፡፡ በመሆኑ ቅዳሴ ያስቀደሰ ሰው መቁረብ እንዲገባው ሁሉ፥ ንስሐውን የጨረሰ አማኝም ቅዱስ ቁርባንን መቀበል ምርጫው አይደለም፡፡ የውዴታ ግዴታው ነው፡፡ ጸድቶ የተቀመጠ ብርጭቆ ለታጠበለት አገልግሎት ካልዋለ፥ ቆሽሾ ከተቀመጠው ብርጭቆ ከመታጠቡ ባሻገር አልተለየም፡፡ ንስሐ የገባም አንድ ሰው፥ ከእግዚአብሔር መንግሥተ ማዕድ ተካፍሎ የዘላለም ሕይወትን የቃልኪዳን ማኅተም በሰውነቱ እስካልያዘ ድረስ የንስሐውን አገልግሎት ከግብ አላደረሰም፡፡ (የዮሐንስ ወንጌል 6፥51)

✝ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መዝሙሮችን በድምፅ / በኦድዮ ለማግኘት ከስር ( ክፈት ) ሚለውን ይጫኑ።

✝ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መዝሙሮችን በድምፅ / በኦድዮ ለማግኘት ከስር ( ክፈት ) ሚለውን ይጫኑ።

✝ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መዝሙሮችን በድምፅ / በኦድዮ ለማግኘት ከስር ( ክፈት ) ሚለውን ይጫኑ።

✝ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መዝሙሮችን በድምፅ / በኦድዮ ለማግኘት ከስር ( ክፈት ) ሚለውን ይጫኑ።

✝ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ መዝሙሮችን በድምፅ / በኦድዮ ለማግኘት ከስር ( ክፈት ) ሚለውን ይጫኑ።

በማለዳ ንቁ ቁጥር ! ፪ - Статистика та аналітика Telegram каналу @bemaledanek