የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
Відкрити в Telegram
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
Показати більше2 635
Підписники
Немає даних24 години
+157 днів
+5530 день
Архів дописів
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ጋር ወደ ግብጽ ሀገር ተሰዳ ስትመለስ ቁስቋም በምትባል ሀገር ገብታ ያረፈችበት በዓል ኅዳር 6 ነው፡፡
ጌታችን ከ3 ዓመት ከ6 ወር የግብጽ ስደት በኋላ ወደ እስራኤል እንደሚመለስ ሆሴዕ በትንቢት መነጽርነት ተመልክቶ “ልጄንም ከግብጽ ጠራሁት ” ብሎ ተናግሯል
ሆሴ 11÷1
«ተመየጢ ተመየጢ ሱላማጢስ ...ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ ተመለሽ » መኃ 7፥1
እመቤታችን ሆይ ሐገራችን ኢትዮጵያን ቅድስት ቤተክርስቲያንን እና ሕዝቧን ይባርክ ዘንድ ለምኝልን። አሜን።
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን
https://youtube.com/@finotebirhan12
#ቅድስት_ሰሎሜ፦ አምላክን የወለደች የቅድስት ድንግል የእመቤታችን የአክስቷ ልጅ መታሰቢያዋ ነው። እርሷም የማጣት ልጅ የሌዊ ልጅ የሚልኪ ልጅ የካህን አሮን ልጅ ናት። ለማጣት ሦስት ሴቶች ልጆች አሉት የታላቂቱ ስም ማርያም ነው የሁለተኛዪቱ ስም ሶፍያ የሦስተኛዪቱም ሐና ነው ይቺም ማርያም ሰሎሜን ወለደቻት ሶፍያም ኤልሳቤጥን ወለደቻት ሐናም አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ወለደቻት።
እመቤታችንም ድንግል ስትሆን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በወለደችው ጊዜ ይቺ ቅድስት ሰሎሜ የእመቤታችንን አወላለድ እንደ ሴቶች ሁሉ አወላለድ መስሏት ተጠራጠረች ከዚህም በኋላ የድንግል እመቤታችን ገላዋን ዳሠሠቻት ያን ጊዜ እጇ ተቃጠለ ሕፃኑን በዳሠሠችው ጊዜ ደግሞ ዳነች።
በዚህም በኅቱም ድንግልና አምላክን እንደወለደች አወቀች። ከተረገመ ኄሮድስ ፊት እመቤታችን በሸሸች ጊዜ ከዮሴፍ ጋራ በመሆን አብራ በመሰደድ የእመቤታችንን ድካሟን ተካፍላ አገለገለቻት ከስደት እስከ ተመለሱ ድረስ ሕፃኑን ታዝለዋለች የምታጥብበትም ጊዜ አለ።
መድኃኒታችን ሰው በሆነበት ወራት ሁሉ አልተለየችም በመከራውም ቀን ከእመቤታችን ጋራ ከከበሩ ሁሉ ሴቶች በትምህርቱ ወራት ከተከተሉት ጋራ እያለቀሰች ነበረች።
በተነሣባት ዕለት ወደ መቃብር ገሥግሣ ከሐዋርያት ቀድማ ያየች ናት። በኃምሳኛውም ቀን መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ ከባልንጆሮቿ የከበሩ ሴቶች ጋራ ሰማያዊ ሀብትን ተቀብላ በክብር ባለቤት መድኃኒታችን ስም ሰበከች ብዙዎችንም አሳመነች። ከአይሁድም ብዙ ስድብና ሽሙጥ አገኛት ከዚያም አረፈች።
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን
https://youtube.com/@finotebirhan12
ኅዳር_6
እመቤታችን_ከተወደደ_ልጇ ጋር ደብረ ቁስቋም ገብተው ካገኛቸው ድካም ያረፉበት፣ የአረጋዊ ቅዱስ_ዮሴፍ፣ የቅድስት_ሰሎሜ
ደብረ_ቁስቋም
ኅዳር ስድስት በዚህች ዕለት ክብርት እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር ከስደት በሚመለሱበት ጊዜ ደብረ ቁስቋም ገብተው ካገኛቸው ድካም ዐረፉ፡፡
አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ከስደት በተመለሰች ጊዜ እንዲህ ሆነ፡- የብርሃን እናቱ ክብርት እመቤታችን ልጇን ይዛ ከእነ ዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብፅ ስትሰደድ ግብፅ ደርሰው በዚያ ቢቀመጡም ነገርን ግብፅ አልተመቸቻውም፡፡ ሕዝቡም በሰላም አልተቀበላቸውም፡፡ እንዲያውም በምድረ ግብፅ ብዙ ተሠቃይተዋል፡፡ ከግብፅም ተነሥተው ወደ ኢትዮጵያ በመጡ ጊዜ ግን ኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉ በሰላምና በፍቅር ተቀበላቸው፡፡ ከመንገዱና ከርሃብ ጥሙ ጽናት የተነሣ እጅግ ደክማለችና የኢትዮጵያ ሰዎች እመቤታችንን አይተው እጅግ አዘኑላት፡፡ ‹‹ይህችስ የነገሥታት ዘር ትመሥላለች ነገር ግን አንዳች ችግር አጋጥሟት ተሰዳ ወደ ሀገራችን መጥታለች..›› ብለው እንክብካቤን አደረጉላት፡፡ እግራቸውን አጥበው በክብር ማረፊያዎች ላይ አሳረፏቸው፡፡ መልካም መስተንግዶም አደረጉላቸው፡፡ እመቤታችንም ከድካሟ ካረፈች በኋላ ሀገሪቱን በእጅጉ ወደደቻትና የተወደደ ልጇን ‹‹ይህን ሀገርና ሕዝቧን በመላ ወድጃቸዋልሁና በዚህ እስከ መጨረሻው እንኑር›› አለችው፡፡ ጌታችንም ክብርት እናቱን ‹‹ይህች ቅድስት ሀገር ናት፣ በኋለኛው ዘመን የቅዱሳን መነኮሳት ቦታ ትሆናለች፡፡ በውስጧም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እመሰገንባታለሁ፤ የአንቺም ስም ሳይጠራ አይውልባትም›› አላት፡፡
ከዚህም በኋላ ጌታችን ደመና ጠቅሶ በእርሷ ላይ ተቀመጡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤልም መጣና እየመራቸው መላ ኢትዮጵያን ጎበኟት፡፡ እመቤታችንም ሀገሪቱንና ሕዝቦቿን ወዳቸዋለች ደስም ተሰኝታባቸዋለችና ጌታችን ለክብርት እናቱ ‹‹ይህችን ቅድስት ሀገር አሥራት አድርጌ ሰጠሁሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም እጅግ ተደስታ ‹‹ልጄ አምላኬ›› ብላ አመሰገነችው፡፡ ከዚህም በኋላ ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ እየተዘዋወሩ መላዋ ኢትዮጵያን በኪደተ እግራቸው ባረኳት፡፡ ጌታችንም ‹‹በዚህ ቦታ እንዲህ ዓይነት ቤተ ክርስቲያን ይታነጻል፤ እከሌ የሚባል እንዲህ ዓይነት ቅዱስ ይነሣል…›› እያለ ብዙ ምሥጢራትን ለክብርት እናቱ ነገራት፡፡ ከዚህም በኋላ የስደቱ ዘመን ሲያልፍ ሄሮድስም በመጨረሻ ክፉ አሟሟትን ሲሞት መልአኩ ወደ ገሊላ አውራጃ እንዲመለሱ ነገራቸው፡፡ እመቤታችንም ‹‹ከዚህች ሀገርስ ባንሄድ እመርጣለሁ›› ስትለው የተወደደ ልጇ ግን ‹‹እናቴ ሆይ ጽድቅንና ፈቃድን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናል›› ብሎ አጽናናትና ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሄዱ፡፡
ተመልሰውም ሊሄዱ ሲነሡ የኢትዮጵያ ሰዎች ልዩ ልዩ አምሐ እጅ መንሻ ሰጧቸው፡፡ ልዩ ልዩ ልብሶች፣ ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ፣ ሽቱ እና ሥንቀቸውን በግመሎች ላይ ጭነው እመቤታችንንና የተወደደ ልጇንም በበቅሎ ላይ አስቀምጠው በክብር ሸኟቸው፡፡ እመቤታችንም ልጇን ታቅፋ በበቅሎ ተቀምጣ በበረሃው በመጓዝ ወደ መጣችበት አገር ሄደች፡፡ ኢትዮጵያንም የሰጧትን ብዙ እጅ መንሻዎች በግመሎች ጭና ይዛ ወደ አገሯ በተመለሰች ጊዜ ከአንድ ባሕር ዳር ደረሰች፡፡ ከዚያም የጀልባውን ባለቤት ‹‹እግዚአብሔርን ስለመውደድ አሻግረኝ›› ብላ ለመነችው፡፡ ባለጀልባውም ‹‹እነሆ ዕቃ የተጫኑ አምስት ግመሎችና ከአንቺ ጋር ከዚህም ሕፃን ጭምር አምስት ሰዎች እመለከታለሁ፣ አንቺ የተቀመጥሽባት በቅሎም አለች፡፡ ጀልባዋም ታናሽ ናት፣ የመቀመጫ ክፍሏም በውስጧ የተሳፈሩት ሰዎችም ተጨናንቀው ነው ያሉት፡፡ ስለዚህ እንዴት ላሻግርሽ እችላለሁ? ነገር ግን እመቤቴ ሆይ! ይቅርታ አድርጊልኝ ይህን በክፋት አላደረግሁትምና›› አላት፡፡
ክብርት እመቤታችንም የጀልባው ባለቤት ሊያሻግራት እንዳልቻለ በተረዳች ጊዜ ‹‹ልጄ ሆይ የእግዚአብሔር ልጅ እንደመሆንህ ይህን ትልቅ ወንዝ ለመሻገር የአምላክነትህን ሥራ ትሠራ ዘንድ እለምንሃለሁ›› ስትል ማለደችው፡፡ ያንጊዜም ጌታችን ክብርት እናቱን ‹‹የወለደሽኝ እናቴ ሆይ! አትዘኝ›› ብሎ አረጋጋት፡፡ ዳግመኛም ‹‹በእኔ ፈቃድ በአባቴ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ካንቺ ሰው ሆኛለሁና ሰው መሆኔንም ከአባቴ በቀር መስተፍሥሒ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስም በቀር ያወቀ የለም፡፡ ዳግመኛም በሕያዋንና በሙታን ለመፍረድ ለሁሉም እንደየሥራው እከፍለው ዘንድ እመጣለሁ፡፡ ያችንም ሰዓት የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ የአዳም ልጆችም ቢሆኑም ከእኔና ከአባቴ ከመንፈስ ቅዱስም በቀር የሚያውቃት የለም፡፡ ያንጊዜ ‹ዐመፅን የሚናገር አንደበት ሁሉ ይዘጋል› ብሎ አባትሽ ዳዊት እንደተናገረ እከራከራለሁ የሚል አንደበት እንደድዳ ምላሽ ያጣል›› አላት፡፡
ክብርት እመቤታችን ማርያምም ይህንን ሁሉ ምሥጢር የተወደደ ልጇ የነገራትን ታስተውለው በልቧም ትጠብቀው ነበር፡፡ ጌታችንም አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለክብርት እናቱ ይህንን ከነገራት በኋላ ቀኝ እጁን ዘርግቶ ከወንዙ ማዶ ጢር በሚባል ተራራ ያሉትን ድንጋዮች ጠቀሳቸው፡፡ ያንጊዜም እነዚህ ድንጋዮች እየተገለባበጡ መጥተው እንደ ጀልባ ሆነው በወራጁ ወንዝ ላይ ተንሳፈፉ፡፡ ከዚያም እመቤታችንን ከሕፃኑ ጋር ከነቤተሰቧና ከነጓዟ አሻገሯት፡፡
እነዚህንም ድንጋዮች ያዩ ሰዎች ሁሉ እጅግ አድንቀው ‹‹ብቻውን ድንቅ ተአምራት ያደረገ፣ እስራኤልን የፈጠረ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን የጌትነቱም ስም የተመሰገነ ነው›› እያሉ አመሰገኑ፡፡ እነዚህም የተባረኩ ሰዎች ወንዙን ከተሻገሩ በኋላ በዚህች አገር ለስምንት ቀን ተቀመጡ፡፡ ከዚህም በኋላ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ስለደረገላት መልካም ሥራ ሁሉ እግዚአብሔርን ፈጽማ እያመሰገነች ወደ አባቷ ወደ ዳዊት አገር ተመለሰች፡፡
ዳግመኛም በኋለኛው ዘመን ጌታችን በዚህ በደብረ ቍስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቶቹን ሰበሰባቸውና ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንን አክብሮ የቍርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለወገኖቹ ሰጣቸው፡፡ ለዚህም ነገር የእስክንድርያ አገር ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱሳን አባቶቻችን ቄርሎስና ቴዎፍሎስ ምስክሮቹ ሆኑ፡፡
#አረጋዊ_ቅዱስ_ዮሴፍ እና #ቅድስት_ሰሎሜ
ዳግመኛም በዚህች ቀን የአረጋዊ ቅዱስ ዮሴፍ እና የቅድስት ሰሎሜም መታሰቢያቸው ነው።
#አረጋዊ_ቅዱስ_ዮሴፍ፦ መልካም ሽምግልና የነበረው የእመቤታችን ድንግል ማርያም እጮኛዋ ድካሟን ለመሳተፍ ክብር ይግባውና ለጌታችንም አሳዳጊው ለመሆን የተገባው መታሰቢያው ነው።
እርሱም እመቤታችንን በእርሱ ዘንድ ካስጠበቋት ጀምሮ በሁሉ ነገር ያገለግላት ነበር። በመከራዋም ሁሉ አልተለያትም። በወለደችም ጊዜ በቤተ ልሔም ከርሷ ጋራ ነበረ። ወደ ግብጽም በተሰደደች ጊዜ ከእርሷ ጋራ ብዙ መከራ ደረሰበት። ከዚህም ዓለም የሚለይበት ጊዜው በደረሰ ጊዜ ወንዶችና ሴቶች ልጆቹን ተሰናበታቸው እጆቹንም ዘርግቶ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። የዘለዓለምን ሕይወት ወረሰ።
በአረፈበትም ጊዜ ጌታችን ወደርሱ መጥቶ እጆቹን በላዩ ጫነ ለሥጋውም መፍረስና መበስበስ እንዳያገኘው ኃይልን ሰጠው በአባቱ በያዕቆብም መቃበር አኖሩት።
የህዳር ሚካኤል ዮኒፎርም የሚሰጥበት ቀን
በ 07.03.2016 ህፃናት
በ 08.03.2016 ማዕከላዊያን
በ 09.03.2016 ወጣት
ከ 10.03.2016 ከህፃናት እስከ ባለትዳር ይሰጣል።
ባለ ትዳር ከ 07.03.2016 አስከ 10.03.2016 የምንሰጥ መሆኑን እንገልፃለን።
ማሳሰቢያ :- ከዚህ ቀን ውጪ የሚመጣ አባል ንብረት ክፍሉ የማይሰጥ መሆኑን እንገልፃለን።
ጥቅምት_27
መድኃኔዓለም (በዓለ ስቅለት)
ጥቅምት ሃያ ሰባት በዚህች ዕለት የአምላካችን የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው።
መድኃኒታችን ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቸርነቱ ስለኹላችን ድኅነት ሲል ራሱን ወድዶ ፈቅዶ ለሞት አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ፍቅሩን አሳይቶናል። በቅዱስ ወንጌልም እርሱም መድኃኒታችን " ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም" ብሎ ነግሮናል። እውነት ነው፣ ራስን ነፍስን ስለጠላት ነፍስ አሳልፎ ከመስጠት በላይ ምን ድንቅ ነገርና ምን ድንቅ ፍቅር አለ?
ቸሩ አምላካችንን የአስቆሮቱ ይሁዳ ሊያስይዘው የሊቃነ ካህናቱን አገልጋዮች እየመራ አመጣቸው። እነርሱንም ማንን ትፈልጋላችሁ ሲላቸው የናዝሬቱ ኢየሱስን አሉት፣ እኔ ነኝ ቢላቸው የቸሩ አምላክን ድምጽ ሰምቶ አይደለም መቆም በሕይወት መጽናት የሚቻለው የለምና ወደ ኋላቸው ተስፈንጥረው ወደቁ። ደጋግሞም እንዲህ ኾነ። በኋላ ግን እኔ ነኝ ብሎ በፈቃዱ ይሁዳ ስሞ አሳልፎ ሰጣቸው።
ከያዙት በኋላ እያዳፉና እየጎተቱ በሰንሰለት አስረው ወደ ቀያፋና ሐና ግቢ ወሰዱት፣ እስከ ሦስት ሰዓትም አላሳረፉትም ሲያሰቃዩት አድረዋል፣ በራሱም ላይ ሰባ ሦስት ስቊረት ያለው ወደ ሦስት መቶ እሾኾችን የያዘ የእሾህ አክሊል ጎንጉነው ቢያደርጉበት የራስ ቅሉን ቀዶ ገብቶ እስከ ልቡ ዘልቋል። እንደምን ጭንቅ ነው? እንዲህም አድርገው ደግሞ እያፌዙ ርኲስ ምራቃቸውን ይተፉበትና በዘንግም ደጋግመው ይመቱት ነበር። እየተፈራረቁ ያለ ምንም ርኅራኄ ቸሩ አምላክ ሥጋው እየተቆረጠ እስኪወድቅ ድረስ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጽኑዕ ግርፋትን ገርፈውታል። የገረፉበትም ጅራፍ በላዩ ላይ ሥጋን እየጎመደ የሚጥል፣ ሕመሙ አንጀት ሰርሥሮ የሚገባ በስለት የተያያዘበት ነበር።
በኋላም አላሳረፉትም እንዲህ አድርገውትም በሊቶስጥራ አደባባይ ያንን ዕርጥብ መስቀል አሸክመው ወደ ቀራንዮ ወሰዱት። እርሱ ግን ይህን ኹሉ ግፍ ሲያደርሱበት አንድም አልተናገረም ነበር። በቀራንዮም በአምስት ጽኑዕ ቅንዋት (ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ) ቸንክረው ዕርቃኑን ሰቀሉት።
በዚህች ቀን ድንግል ማርያም ልቧ በሐዘን ተሰበረ መጽናናትንም አልፈለገች ነበር፤ ወዳጁ ቅዱስ ዮሐንስም ፍፁም ለቅሶን አለቀሰ እናቱንም እናት ትሆነው ዘንድ በእግረ መስቀሉ አደራን ተቀበለ። ቅዱሳት አንስት በፍጹም ሀዘንና በዋይታ ዋሉ። በስልጣኑም ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ። ሰባት ድንቅ የኾኑ ተአምራትንም አድርጎ አምላክ መኾኑን ገለጠ። ይህም ጽኑዕ የኾነ ለሰማይ ለምድር የከበደ ነገር ሲከሰት ፀሐይ አምላኬን ዕርቃኑ እንዴት አያለሁ ብላ ጨለመች። ጨረቃ ደም ኾነች፣ ከዋክብቱም ረገፉ፣ ንዑዳን ክቡራን ንጹሐን መላእክትም ትዕግስቱን እያደነቁ በጽኑዕ ሐዘንና መደነቅ ከቅዱስ ዕፀ መስቀሉ ፊት እንደሻሽ ተነጠፉ።
አስራ አንድ ሰዓት በሆነም ጊዜ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከታላቅ ክብርና ሐዘን ጋር ቅድስት ሥጋውን ከመስቀሉ አውርደው በክብር ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት። በሦስተኛውም ቀን እንደተናገረ ተነሳ።
በዛሬዋ ቀን ቤተ ክርስቲያን የመድኃኔለምን የስቅለት በዓል በደማቁ ታከብራለች፤ ይህም የለውጥ በዓል ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው ስጋውን የቆረሰው መጋቢት 27 ቀን ነው፤ ይህ በዓል ግን በዐቢይ ጾም ስለሚውል በዐቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለና በዓል ማክበር ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት 27 ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ሰርታልናለች፡፡
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን
https://youtube.com/@finotebirhan12
ቀሲስ ዶ/ር መዝገቡ ካሳ በደብራችን ያስተማሩት ትምህርት
11. በውጭው ክፍለ ዓለማት በሚገኙት አህጉረ ስብከት ሥር የተቋቋሙት አብያተ ክርስቲያናት የሚተዳደሩበት እራሱን የቻለ ሕግና ደንብ ባለመኖሩ በመዋቅራዊ አስተዳደራችን ላይ ከፍተኛ ክፍተት ሲፈጥር የቆየ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ ለውጭው ክፍለ ዓለማት አህጉረ ስብከት እና አብያተ ክርስቲያናት እራሱን የቻለ መተዳደሪያ ደንብ ተዘጋጅቶ የፀደቀ በመሆኑ በውጭው ክፍለ ዓለማት በሚገኙት ሁሉም አህጉረ ስብከትና አብያተ ክርስቲያናት በጸደቀው መተዳደሪያ ደንብ ብቻ ሥራቸውንና አገልግሎታቸውን እንዲያከናውኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
12. የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ኮሌጆች ወጥ የሆነ የጋራ መተዳደሪያ ደንብ እንዲኖራቸው በማሰብ ጉባኤው አስቀድሞ ተዘጋጅ እንዲቀርብ ባዘዘው መሠረት ተዘጋጅቶ የቀረበውን ረቂቅ መተዳደሪያ ደንብ መርምሮ በማጽደቅ በሁሉም በተቋቋሙትም ሆነ ወደፊት በሚቋቋሙት ኮሌጆች ሥራ ላይ እንዲውል ጉባኤው ወስኗል፡፡
13. ገዳማትና ገዳማዊ ሕይወት፣ የአብነት መምህራን እና ትምህርት ቤቶች እንዲሁም በአጠቃላይ ክብረ ክህነት እና ትምህርተ ኖሎት ተጠናክሮ እንዲቀጥል በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል እየተጠና አስፈላጊው ሁሉ ድጋፍና ክትትል እንዲደረግ ጉባኤው ወስኗል፡፡
14. የቤተ ክርስቲያናችን ሕጋዊ፣ ተቋማዊ፣ ሃይማኖታዊና ማህበራዊ መብቶች መከበርና የእምነት ነጻነታችንን እና የምእመናንን ደኅንነት በሕግ አግባብ ማስከበር ይቻል ዘንድ ልክ እንደ ዋናው መሥሪያ ቤት በሁሉም ክልሎች ውስጥ ባሉት አህጉረ ስብከት የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደ ሥራ እንዲገባ ጉባኤው ወስኗል፡፡
15. ወጣቱ ትውልድ በእምነቱ ጸንቶና በቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ በእውቀትና በሥነምግባር ይታነጽ ዘንድ በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ተዘጋጅቶ የቀረበው ሥርዓተ ትምህርት በሁሉም የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር እና አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ተግባራዊ እንዲሆን ጉባኤው ወስኗል፡፡
16. የ2016 ዓ.ም. ዓመታዊ በጀትን አስመልክቶ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል ተዘጋጅቶ የቀረበውን የበጀት ድልድል ጉባኤው መርምሮ በማጽደቅ ሥራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡
17. የቤተ ክርስቲያናችን የመልካም አስተዳደር ችግሮች የሚፈቱት እና የልማት ተቋማት የሚጠናከሩት ዘመኑን የዋጀ መዋቅራዊ አደረጃጀት በመፍጠር እና በእቅድ ተደግፎ በእውቀት ላይ የተመሠረተ የሀብትና የንብረት አስተዳደር ማስፈን ሲችል መሆኑን ጉባኤው በጽኑ ያምናል፡፡
በመሆኑም በባለፈው ጉባኤ የጸደቀው የ10 ዓመት የመሪ እቅድ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል እየተደረገለት የመሪ ዕቅዱ አፈጻጸም እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም
ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ጥቅምት 19 ቀን 2016 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን
https://youtube.com/@finotebirhan12
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜ እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የመክፈቻውን ሥርዓተ ጸሎት ከፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባውን ሲያካሂድ ሰንብቷል፡፡
በመሆኑም ምልዓተ ጉባኤው ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት፣ እየተከሰቱ ስላሉት ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎች እንዲሁም ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት በስፋት በመወያየት ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡
በዚሁ መሠረት፡-
1. የ2016 ዓ.ም. የመንበረ ፓትርያርክ ዓለም አቀፍ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ያሳለፈውን የጋራ የአቋም መግለጫ በመመርመርና አስፈላጊውን ማሻሻያዎች በማድረግ የበጀት ዓመቱ የቤተ ክርስቲያናችን የሥራ መመሪያ እንዲሆን ጉባኤው አጽድቆታል፡፡
2. ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መዋቅራዊ አደረጃጀቱን የበለጠ ተደራሽ በማድረግ ሐዋርያዊ ተልዕኮዋን መወጣት ትችል ዘንድ በአዲስ እንዲደራጁ ተጠንተው የቀረቡትን የአህጉረ ስብከት ይደራጅልን ጥያቄዎችን በመመርመር፡-
ሀ. የሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት፣
ለ. የሰሜን ጎጃም ዞን ሀገረ ስብከት
ሐ. የጎፋና ባስኬቶ ዞን ሀገረ ስብከት
መ. የምሥራቅ ጉራጌ ዞን ሀገረ ስብከት እራሳቸውን ችለው ሀገረ ስብከት ሆነው ተደራጅተው እንዲቀጥሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
3. ቤተ ክርስቲያናችን የመንፈሳዊ ኮሌጆቿን ቁጥር ከፍ በማድረግ የአገልጋይ መምህራንን ቁጥር ለማሳደግ ባላት እቅድ መሠረት ተጠንተው ከቀረቡት መካከል በ2016 ዓ.ም. የበጀት ዓመት በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ደብረ ብርሃን ከተማ ላይ፣ በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ደብረ ታቦር ከተማ ላይ ሁለት መንፈሳዊ ኮሌጆች እንዲቋቋሙ፣ በማዕከላዊ ጐንደር ሀገረ ስብከት ርእሰ ከተማ ውስጥ ለሚገኙት የምስክር ጉባኤ ቤቶች በኮሌጅ ደረጃ በጀት እንዲመደብላቸው እና በከንባታ ሐድያ ስልጤ ሀገረ ስብከት ሆሣዕና ከተማ ላይ አንድ የካህናት ማሠልጠኛ እንዲከፈት ጉባኤው ወስኗል፡፡
4. ቤተ ክርስቲያናችን ከውስጥና ከውጭ እየደረሱባት ያሉት ከፍተኛ የሆኑ ፈተናዎችን ተቋቁማ ሕልውናዋን አስከብራ መቀጠል ትችል ዘንድ ፡-
ሀ. ውስጣዊ ችግሮቻችን ቀኖና ቤተ ክርስቲያን በጠበቀ በውይይት እንዲፈቱ፣
ለ. ውጫዊ ችግሮችንና የመብት ጥሰቶችን በተመለከተ በችግሮቹ ዙሪያ ከሚመለከታቸው መንግስታዊ ተቋማት ጋር በመነጋገር ችግሮቹ እንዲፈቱ እና የቤተ ክርስቲያናችን መብትና ሕልውና ተጠብቆ እንዲቀጥል እንዲደረግ፣
ሐ. ለቤተ ክርስቲያናችን ሕልውና አደጋ የሆኑና ሊሆኑ የሚችሉ ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎችን አስመልክቶ በአግባቡ ተጠንተውናበማስረጃ ተተንትነው ከመፍትሔ ሐሳብ ጋር እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
5. ትላንት በሰሜኑ ኢትዮጵያ የሀገራችን ክፍል በተካሄደው ጦርነት በጠፋው የሰው ሕይወትና በወደመው ንብረት ከደረሰብን ሐዘን እኛ ኢትዮጵያውያን ገና ሳንጽናና ዛሬም በሀገራችን ኢትዮጵያ በበርካታ አካባቢዎች የተከሰቱት ጦርነቶች፣ ግጭቶችና አለመግባባቶች እያስከተሉት ያለው የንጹሐን የሰው ሕይወት መጥፍትና የንብረት ውድመት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤን በእጅጉ አሳዝኖታል፡፡ በመሆኑም ችግሩ በውይይትና በስምምነት እንዲፈታ የፌዴራልን የክልል መንግሥታት፣ እንዲሁም በግጭቱ ተሳትፎና ድርሻ ያላችሁ በሁሉም አካባቢ የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በሙሉ የበኩላችሁን ሚና በመወጣት እናት አገራችን ኢትዮጵያ ሰላሟና አንድነቷ ተጠብቆ ይቀጥል ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ከአደራ ጭምር በድጋሚ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
6. በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየተከሠተ ያለው ችግርና ፈተና የሚወገደው ሁሉም ኢትዮጵያዊያን በአንድነትና በሕብረት ለችግሮቹ መፈታት ድርሻ እንዳለን አውቀን እንደየእምነታችን አስተምህሮ በጸሎትና በምሕላ ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር በንስሓ መመለስ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶስ በጽኑ ያምናል፡፡ በመሆኑም ስለ ሀገራችን ሰላምና ስለ ቤተ ክርስቲያናችን አንድነት በመላው ዓለም በሚገኙት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አብያተ ክርስቲያናት በሙሉ ከህዳር 15 ቀን 2016 እስከ ታህሣሥ 27 ቀን 2016 ዓ.ም. ድረስ ጸሎትና ምሕላ እንዲፈጸምና መላው ሕዝበ ክርስቲያንም በአንድነትን በሕብረት ከላይ በተጠቀሱት ዕለታት በቤተ ክርስቲያን በመገኘት የበረከቱና የሥርዓተ ጸሎቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኖ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
7. የቤተ ክርስቲያናችንን ታሪክና ለሀገረ መንግስት ምሥረታና እድገት ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በማዕከል ደረጃ በማስረጃ አስደግፎ በመጻፍና በማደራጀት ትውልዱ እንዲረዳው በማድረግ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሕልውና አደጋ የሆነውን የሐሰት ትርክት መከላከል ይቻል ዘንድ የዝግጅት ሥራው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል በሊቃውንት ጉባኤ የበላይ ተቆጣጣሪነት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንንና የታሪክ ተመራማሪዎችን በማሳተፍ ተግባራዊ እንዲሆን ጉባኤው ወስኗል፡፡
8. ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ላይ ስለሚኖራት ተሳትፎና ሚና በተመለከተ ጉባኤው በስፋት የተወያየ ሲሆን ሀገራዊ ምክክሩ ሀገራዊ ችግራችንን እንደሚፈታና በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የሚነገሩትን የሐሰት ትርክቶች ሁሉ የሚታረሙበት እንደሚሆን ጉባኤው በጽኑ ያምናል፡፡ በመሆኑም በምክክር ሂደቱ ላይ ስለሚኖረን ተሳትፎና ሚና በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል እየተጠና አስፈላጊው ሁሉ እንዲፈጸም ሆኖ የምክክር ኮሚሽኑም ይህን የቤተ ክርስቲያናችን እቅድ በመርሐግብሩ በማካተት ቤተ ክርስቲያናችን የድርሻዋን እንድትወጣ እድሉን እንዲያመቻችልን ጉባኤው ጥሪውን ያቀርባል፡፡
9. የመረጃ ቋት መዋቅራዊ አደረጃጀትን በሁሉም ክልል አህጉረ ስብከት ደረጃ በማቋቋም እና እለት እለት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የሚከሰቱትን ችግሮችና የመብት ጥሰቶች በመረጃና ማስረጃ አስደግፎ ለዋናው ማዕከል የመረጃ ቋት በፍጥነት ተደራሽ በማድረግ በአንዱ ቦታ ችግር ሲደርስ በመላ ሀገሪቱ እና በውጭው ክፍለ ዓለማት ባሉት አህጉረ ስብከት በአንድነት ድምፅ መሆን ይቻል ዘንድ ተጠሪነታቸው ለዋናው ማዕከል የሆኑ የመረጃ ቋት ማዕከላት በሁሉም አህጉረ ስብከት ተቋቁመው ወደሥራ እንዲገቡ ጉባኤው ወስኗል፡፡
10. የቤተ ክርስቲያናችን ሀብትና ንብረት የሆኑት ቅዱሳት መጻሕፍትን፣ የሚዳሰሱና እና የማይዳሰሱ ቅርሶችንና በአጠቃላይ ንዋየ ቅድሳቶቻችን ግለሰቦች እና ተቋማት በሕገወጥ መንገድ አትመውና አሳትመው በማሠራጨትና ትክክለኛ ቅጅውን አዛብቶ በማተም ቤተ ክርስቲያናችን ለሐሰተኛ ትርክት እንድትዳረግ በማድረግ ከፍተኛ የሆነ በደል እየተፈጸመባት መሆኑን ጉባኤው በጽኑ ያምናል፡፡ በመሆኑም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ በኩል የተጀመረው የአዕምሯዊ ንብረት ምዝገባ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እና የቤተ ክርስቲያኒቱ መብትና ጥቅም እንዲከበር ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።የዩቲዩብ ቻናላችን https://youtube.com/@finotebirhan12
https://t.me/finotebirhan12
የአባቱ አገልጋዮችም ብዙ ወራት በሁሉ አገሮች ሲዞሩ ኑረው ወደ አውፊምያኖስ ጌታቸው ተመለሱ ። የእግዚአብሔር ሰው ቅዱስ ሙሴም ከሰንበት ቀኖች በቀር እህልን የማይቀምስ እስቲሆን ድረስ ተጋድሎውን በመጨመር በየሁለትና በየሦስት ቀኖች የሚጾም ሆነ ።
ከዚህም በኋላ እመቤታችን የከበረች ድንግል ማርያም ከዚያች ቤተ ክርስቲያን ካህናት ውስጥ ለአንድ ደግ ጻድቅ ቄስ ተገልጻ እንዲህ አለቸው በጥዋት ወደ ቤተ ክርስቲያን ውጭ ውጣ ከምሰሶ አጠገብ ብቻውን ቁሞ የሚጸልይ ሰው ታገኛለህ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ወደ ቤተ ክርስቲያን ግባ በለው በውጭ አትተወው ጾሙ ጸሎቱ በእግዚአብሔር ፊት መዓዛው ጣፋጭ እንደሆነ ዕጣን ተቀባይነትን አግኝቷልና ።
ሲነጋም ያ ቄስ ወደ ቅዱስ ሙሴ ሒዶ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ወደ ቤተ ክርስቲያን ግባ አለው ሙሴም አባቴ ሆይ በከበረ ቦታ ላይ መቆም የማይገባኝ ኃጢአተኛ ነኝና ተወኝ አለው ቄሱም ወደ ቤተ መቅደስ አስገባህ ዘንድ ከቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም ወዳንተ ተልኬአለሁ ብሎ መለሰለት ወደ ቤተ መቅደስም ያስገባው ዘንድ እንዳዘዘችው ነገረው ከዚህም በኋላ አስገባው ።
ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ ወደ ሀገረ ጠርሴስ ይሔድ ዘንድ አስቦ እርሷም የሐዋርያው ጳውሎስ አገር ናት እንዲህም አለ እስከ ዕለተ ሞቴ በውስጥዋ እኖራለሁ ሥጋው ምንም በሮሜ አገር የሚኖር ቢሆንም የትውልድ አገሩ ናትና በረከትን እቀበላለሁ ብሎ ነው ።
በሌሊትም ወጥቶ ወደ ባሕር ዳርቻ ሔደ ወደ ጠርሴስም ይሔድ ዘንድ በመርከብ ተጫነ በባሕር መካከልም ታላቅ ነፋስ ተነሣባቸው ባሕሩም ከነፋሱ ኃይል የተነሣ ታወከ ወደየትም እንደሚሔዱ አያውቁም ነበር ቀኑ ጨልሞባቸዋልና ስለ ነፍሳቸውም ድኅነት ወደ እግዚአብሔር ለመኑ በዚያንም ጊዜ ባሕሩ ጸጥ ብሎ ታላቅ ደስታ ሆነ ብርሃንም ታየ ወደ ሮሜ ሀገር ወደብም እንደ ደረሱ አወቁ ።
ቅዱስ ሙሴም ተነሥቶ በመርከብ ውስጥ ያሉትን በሰላምታ ተሰናብቷቸው ጉዞውን ጀመረ በልቡም እንዲህ አለ ይህ ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ እንግዲህ እስከ ዕለተ ሞቴ ራሴን ለማንም እንዳልገልጥ ሕያው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያውቀኝ የለምና በአባቴ ደጅ እኖራለሁ ይህንንም ብሎ ወደ አባቱ ቤት ተጓዘ ።
በመንገድም ላይ አባቱን ተገናኘው ብዙ ሰውም ተከትሎት ነበር የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ቀረብ ብሎ አባቱ የተቀመጠበትን ፈረስ ልጓሙን ያዘ እንዲህም አለው እግዚአብሔር የባረከህ ያከበረህ አንተ ደግ ሰው እግዚአብሔርም ኃጢአትህን ይቅር ይበልህ የልብህንም ልመና ይስጥህ እኔም መጻተኛ ድኃ ሰው እንደ ሆንኩ እወቅ ለመጻተኛነቴና ለችግረኛነቴ የምትራራ ሁነህ ከማዕድህ ፍርፋሪ ልትመግበኝ ከወደድህ መኖሪያዬን በቤትህ አንጻር በደጃፍህ አድርግልኝ ዋጋህንም የሚሰጥህ እግዚአብሔር ነውና ።
በዚያንም ጊዜ አውፊምያኖስ የልጁ የሙሴን ስደት አስታውሶ በተቃጠለ ልብ አለቀሰ መኖሪያውንም በቤቱ ደጅ እንዲሠሩለት አዘዘለት። ሁለተኛም ከአገልጋዮቹ አንዱን በሚያሻው ነገር ሁሉ እንዲአገለግለው አዘዘው ።
የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ያን የሚያገለግለውን ወንድሜ ሆይ ከሰንበት ቀኖች በቀር መብልና መጠጥ እንዳታመጣልኝ እለምንሃለሁ ይኸውም ከቁርባን በኋላ ግማሽ እንጀራና የጽዋ ውኃ ብቻ ነው አለው ። በጾምና በጸሎትም እየተጋደለ በዚያ በአባቱ ደጅ ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ ።
ሰውን የሚወድ ቸር ጌታችን ኢየሱስ ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው ወዶ ተገለጠለት እንዲህም አለው የመረጥሁህ አንተ ብፁዕ ነህ አንተ ፈቃዴን ፈጽመሃልና በዚህ ዓለም ከደስታ ኃዘንን ከብልጽግና ድኅነትን መርጠሃልና እኔም የማይጠፋ ብልጽግናን እሰጥሃለሁ ዳግመኛም ስምህን የሚጠራ መታሰቢያህንም ለሚያደርግ የተራበውን ለሚያጠግብ የተጠማውን ለሚያጠጣ የተራቈተውን ለሚያለብስ ገድልህንም ለሚጽፍ ወይም ለሚያጽፍ ስለ ስምህ በጎ ሥራ ሁሉ ለሚሠራ ቃል ኪዳንን ሰጠሁህ ። በሰማያዊት መንግሥትም በጎ ዋጋን እሰጠዋለሁ ተጠራጣሪ ካልሆነ በዚህ ዓለምም እጠብቀዋለሁ ከበጎ ነገር ሁሉ ምንም አላሳጣውም ።
አሁንም ከአራት ቀን በኋላ እወስድሃለሁ ምርጦቼ ነቢያት ሐዋርያት ጻድቃን ሰማዕታት ከአሉበትም አኖርሃለሁ ይህንንም ብሎ ከእርሱ ዘንድ ወደ ሰማይ በታላቅ ክብር ዐረገ ።
ቅዱስ ሙሴም ከእግዚአብሔር ዘንድ ይህን ጸጋ በተሰጠ ጊዜ እጅግ ደስ አለው ያን የሚያገለግለውንም ወንድሜ ሆይ እንግዲህ ስለ እኔ ከመድከም ታርፋለህና ወረቀትና ቀለም አምጣልኝ አለው። ያ አገልጋይም ከአነጋገሩ የተነሣ አድንቆ ወረቀቱንና ቀለሙን አመጣለት የከበረ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ገድሉን ሁሉ ጻፈ በአራተኛውም ቀን ያቺን የጻፋትን መጽሐፍ በእጁ ጨበጣት በእሑድ ቀንም በሰላም አረፈ ። መላእክት ነቢያት ሐዋርያት ጻድቃን ሰማዕታት ለሚያገለግሉት የዘላለም ተድላ ደስታ ለሚሰጥ ለነበረና ለሚኖር ፈጣሪያችን ምስጋና ይሁን እያሉ ነፍሱን ተቀበሏት ።
ሕዝቡም ሁሉ በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተሰብስበው እያሉ ከመሠዊያው በላይ የጌታቸውን ሕጎቹንና ሥርዓቱን የሚያደርጉ ደጎች አገልጋዮች ባሮች የተመሰገኑ ናቸው እነርሱ ወደ ዘላለም ተድላ ደስታ ይገባሉና የሚል ቃልን ሲጮህ ሰሙ ።
ሊቀ ጳጳሳቱና ኤጲስቆጶሳቱ ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ሕዝብም ሁሉ በሰሙ ጊዜ በላያቸው ታላቅ ፍርሀት ወደቀባቸው ። የቅዳሴውም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ይህን ምሥጢር ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በመጸለይ ማለዱ በዚያንም ጊዜ የእግዚአብሔርን ሰው በአውፊምያኖስ ቤት ፈልጉት እነሆ እርሱ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጥቷልና የሚል ቃልን ሰሙ ።
ሊቀ ጳጳሳቱም ይህን ነገር ሰምቶ አውፊምያኖስን ጠራውና ይህ ታላቅ ጸጋ በቤትህ ውስጥ ሲኖር በሕይወቱ ሳለ እንድንጎበኘው በረከቱንም እንድንቀበል ለምን አልነገርከንም አለው አውፊምያኖስም እንዲህ ብሎ መለሰ ክቡር አባት ሆይ ቅድስናህ ይመስክር ይህን የሚመስል በቤቴ ውስጥ እንዳለ አላወቅሁም ።
በዚያንም ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱ ከሁሉ ካህናትና ሕዝብ ጋር ተነሥቶ ወደ አውፊምያኖስ ቤት ሔደ የከበረ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴንም በአረፈበት ቦታ አገኙት ክርታሱም በእጁ ውስጥ ነው ሊቀ ጳጳሳቱም ያቺን ክርታስ አንሥቶ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ የአውፊምያኖስ ልጅ እናቱም አግልያስ እስከሚለው ስሙ እስቲደርስ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አነበባት። እናትና አባቱም በሰሙ ጊዜ ደነገጡ መራር ልቅሶንም አለቀሱ ቤተሰቦቻቸውም ሁሉ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ አጽናንቶ ጸጥ አደረጋቸው።
በዚያንም ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱ የሐር ልብስ አስመጥቶ በክብር ገነዘው ወደ ቤተ ክርስቲያንም ወስደው ከሥጋው እስከሚባረኩ በቤተ መቅደስ አኖሩት። ካህናቱና ሕዝቡ ሁሉ ከዚህም በኋላ ብዙ በሽተኞች ዕውሮች ሐንካሶች ደንቆሮዎች ዲዳዎች መጥተው ከሥጋው በተሳለሙ ጊዜ ሁሉም ከደዌያቸው ዳኑ በዚያችም ቀን ታላቅ ደስታ ሆነ።
ሕዝቡም በበዙ ጊዜ የልጁን የሙሴን ሥጋ ከዐልጋው ላይ እንዳይጥሉት አውፊምያኖስ ፈራ ብዙ ገንዘብም አምጥተው ይበትኑ ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው። ሥጋውን ትተው ወደ ተበተነው ገንዘብ ይሔዳሉ ብሎ አስቦ ነበር ግን ከቶ አንድ እንኳ ወደ ገንዘብ የሔደ የለም ።
ከዚህም በኋላ ሥጋውን በታላቋ በሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን አኖሩ ከሥጋውም ብዙ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ ዕውሮች አይተዋልና ሐንካሶችም ቀንተው ይሔዳሉና ደንቆሮዎችም ይሰማሉና ለምጻሞችም ይነጻሉና አጋንንት ያደሩባቸውም ይወጡላቸዋልና ሁሉም ካለባቸው ደዌ ይድናሉና።
ሲገቡና ሲወጡም ሽታው እንዳያስጨንቀን ይህን ምስኪን አስወግዱልን ይላሉ ወጭትና ድስትም አጥበው በላዩ ይደፉበታል ውሾችም እንዲናከሱበትና እንዲበሉት የሥጋ ትርፍራፊ ይጥሉበታል ውሾች ግን ቁስሉን ይልሱለት ነበር እንደዚህም አብዝተው አሠቃዪት ።
ከዚህም በኋላ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ለአባቴና ለእናቴ ባሮች በደል እንዳይሆንባቸው ወዳንተ ውሰደኝ ። በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው ። ከዚህም በኋላ ገድሉን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጻፈ በእጁም ጨብጧት አረፈ ።
በእሑድ ቀንም ሕዝቡ ሁሉና ካህናቱ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳሉ የእግዚአብሔርን ሰው በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ቤት ፈልጉት የሚል ቃል ከሰማይ ሰሙ በዚያን ጊዜ ሔደው በአረፈበት ቦታ አገኙት። በእጁም ውስጥ የተጨበጠ ክርታስን አዩ ሊወስዷትም ሽተው መውሰድ ተሳናቸው ።
በአንድነትም በጸለዩ ጊዜ እጁ ተፈትታ ወስደው አነበቧት አባትና እናቱም ልጃቸው እንደሆነ አወቁ ታላቅ ጩኸትም ሆነ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ አክብረውም ቀበሩት መቃብሩም በሽተኞችን ሁሉ በመፈወስ ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራትን የሚያደርግ ሆነ ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ፊልጶስ_ሐዋርያ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የሆነ አንዱ ቅዱስ ሐዋርያ ፊልጶስ አረፈ። ጌታችንም በቂሣርያ አገር ውስጥ በአለፈ ጊዜ በውስጧ አስተማረ ትምህርቱንም ሰምቶ ክብር ይግባውና ጌታችንን አምኖ ተከተለው ከሰባ ሁለቱ አርድዕትም ጋር ተቆጠረ ።
ጌታችንም ይሰብኩ ዘንድ ሁለት ሁለት አድርጎ በላካቸው ጊዜ ከእርሳቸው አንዱ ይህ ደቀ መዝሙር ነው ። ከመድኃኒታችንም ዕርገት በኋላ ሐዋርያት ከሾሟቸው ከሰባቱ ዲያቆናት ውስጥ የተቆጠረ ነው ። እርሱም ወደ ሰማርያ ወርዶ አስተማረ ብዙዎችንም አሳምኖ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ። ከዚህም በኋላ የተጎዳውን ሥራየኛ ሲሞንንም አጥምቆት ነበር እርሱ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በገንዘብ ሊገዛ አስቧልና ።
ከዚህም በኋላ ወደ ጋዛ በሚወስደው መንገድ ይሔድ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ፊልጶስን አዘዘው በሔደም ጊዜ ለኢትዮጵያ ንግሥት ለህንደኬ በጅሮንዷ የሆነ ጃንደረባውን አገኘው እርሱም እንደ በግ ሊታረድ መጣ የሚለውን የነቢይ ኢሳይያስን መጽሐፍ ያነብ ነበር ።
ፊልጶስም ጃንደረባውን የምታነበውን ታስታውለዋለህን አለው ። ጃንደረባውም ያስተማረኝ ሳይኖር እንዴት አውቃለሁ አለ ። ፊልጶስም ስለ ጌታችን ስለ መከራው ለዓለሙ ሁሉ ድኅነት ስለሆነው ሞቱ እንደተነገረ ተረጐመለት ። ጃንደረባውም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አመነ ያን ጊዜም በፊልጶስ እጅ ከወንዝ ውኃ ውስጥ ተጠመቀ ከውኃውም በወጡ ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ፊልጶስን ነጥቆ ወሰደው ጃንደረባውም ሁለተኛ አላየውም ።
ፊልጶስም ወደ አዛጦን ከተማ ደረሰ እያስተማረም እስከ ቂሣርያ ሔደ በከተማዎች ሁሉ በመዞር ወንጌልን ሰበከ ከአይሁድና ከሳምራውያንም ብዙዎችን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን መልሶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ። ለሐዋርያ ፊልጶስም ከእርሱ ጋር ወንጌልን የሚሰብኩ አራት ሴቶች ልጆች ነበሩት ። አገልግሎቱንም ፈጽሞ በሰላም አረፈ ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሙሴ_ሙሽራው
በዚህችም ቀን ከሮሜ ሀገር የሆነ የከበረ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ አረፈ ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አውፊምያኖስ የእናቱ አግልያስ ነው እነርሱም እግዚአብዘሔርን የሚፈሩ እጅግም ባለጸጎች ናቸው ። አብዝተውም ይመጸውታሉ ሁልጊዜም ይጸልያሉ እስከ ዘጠኝ ሰዓትም ይጾማሉ ድኆችንና ችግረኞችንም ሳይይዙ አይበሉም ።
ነገር ግን ልጆች የሏቸውም ነበር የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ የተባረከ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ይለምኑት ነበር ጌታችንም ልመናቸውን ተቀብሎ ይህን መልኩ እጅግ ያማረ የከበረና የተባረከ ልጅን ሰጣቸው በወለዱትም ጊዜ በርሱ ደስ ብሏቸው ለድኆችና ለምስኪኖች ታላቅ ምሳ አደረጉ ስሙንም ሙሴ ብለው ሰየሙት ትርጓሜውም የእግዚአብሔር ሰው ማለት ነው ስለእርሱ እግዚአብሔር ልመናቸውን ሰምቷልና ።
ከዚህም በኋላ ሙሴን በመልካም አስተዳደግ አሳደጉት መንፈሳዊና ሥጋዊ ትምህርትን ጥበብን ሁሉ አስተማሩት ። አድጎም በጎለመሰ ጊዜ አባቱ አውፊምያኖስ ሚስቱ አግልያስን እነሆ ልጃችን ሙሴ አደገ ሚስትን ልናጋባውና በጋብቻውም ደስ ሊለን ለእኛ ይገባናል አላት ። የሙሴ እናት አግልያስም ሰምታ በዚህ ነገር ደስ አላት ከሮሜ አገር ታላላቆች ሰዎች ወገንም መልኳ እጅግ ያማረ አንዲት ብላቴና አጋቡት ። ታላቅ ሠርግንም በማዘጋጀት ሸልመው አስጊጠው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በጋብቻ ሥርዓት አክሊላትን አቀዳጇቸው ። ከዚህ በኋላ ሥጋውንና ደሙንም ተቀብለው ወደሚሠረጉበት ቤት ገቡ ።
ከዚህም በኋላ በማግሥቱ አውፊምያኖስ ሚዜውን ጠርቶ እንዲህ አለው ሙሽራው ወደ ሙሽሪቷ ገብቶ የጋብቻውን ሕግ እንዲፈጽም ንገረው ያ ሚዜውም በነገረው ጊዜ ወደ ሙሽራዪቷ ገባ ድንቅ የሆነ ውበቷንና ደም ግባቷን ተመለከተ በልቡም አስቦ እንዲህ አለ ይህ ሁሉ ውበትና ደም ግባት አላፊ ጠፊ አይደለምን ። ይህንንም ብሎ ወደ ሰማያዊት መንግሥቱ የሚደርስበትን መንገድ እንዲመራው እግዚአብሔርን ለመነው ።
ሙሽራዪቱንም እንዲህ አላት የተባረክሽ እኅቴ ሰላም ይሁንልሽ የእግዚአብሔርም ፍቅር አንድነት ከአንቺ ጋር ይኑር ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ እስከምንገናኝ ደኅና ሁኚ ። ይህንንም በሚላት ጊዜ ልብሶቹን አውልቆ ሰጥቷት ከእርሷ ዘንድ ወጣ የተሞሸረበትንም ልብስ ለውጦ ከባሕር ዳርቻ እስከሚደርስ መንገዱን ተጓዘ ።
ልብሶቹንም ሁሉ ሽጦ ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋትን ሰጠ እርሱም ጨርቅ በመልበስ እንደ ድኃ ሁኖ ቁራሽ እንጀራ እየለመነ በየጥቂቱ እየተመገበ እስከ ሀገረ ሮሀ ድረስ ሔደ ።
ከዚያም በደረሰ ጊዜ ወደቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገብቶ ለሮሀ ንጉሥ ለአቃርዮስ በስብከቱ ወራት የተላከለትን ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሥዕልና የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል አግኝቶ ከሥዕሎቹ ተሳልሞ በረከትን ተቀበለ ወደ ልዑል እግዚአብሔርም ፈጽሞ እያመሰገነ ጸለየ ። ወጥቶም ኑሮውን ከድኆችና ከምስኪኖች ጋር አደረገ ።
ከዚህም በኋላ መጸለይና መጾምን ጀመረ እስከ ምሽትም ይጾማል በቀንና በሌሊትም ጸሎቱን አያቋርጥም ምጽዋትንም ከድኆች ጋር ተቀብሎ እርሱ መልሶ ለሌሎች ይሰጣል ።
በዚያቺም ዕለት በነጋ ጊዜ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ ሲገቡ ሙሽራው ልጃቸው ሙሴ በጫጉላው ቤት እንደ ሌለ ሰሙ ደስታቸውም ወደ ኀዘን የሠርጉም ዘፈን ወደ ልቅሶ ወደ ዋይታ ተለወጠ ።
ከዚህም በኋላ አውፊምያኖስ ባሮቹን ጠርቶ ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው እንዲህም አላቸው ልጄን እስከምታገኙት ድረስ ሁለት ሁለት እየሆናችሁ ወደ ሀገሩ ሁሉ ሒዱ ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋትን ስጡአቸው ። እነርሱም በሀገሩ ሁሉ ተበታተኑ ። ከአባቱ አገልጋዮችም ሁለቱ አገኙት ግን አላወቁትም ምጽዋትንም ከድኆች ጋር ሰጡት ቅዱስ ሙሴም አውቋቸው እንዲህ ብሎ አመሰገነ ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ስለ አንተ ፍቅር ከአባቴ ባሮች እጅ ምጽዋትን እቀበል ዘንድ ለዚህ ታላቅ ክብር አድለህኛልና አመሰግንሃለሁ ።
ስንክሳር ጥቅምት_14
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ዐሥራ አራት በዚች ቀን ታላቁና የከበረው አባታችን #አቡነ_አረጋዊ ተሰወሩ፣ የቊስጥንጥንያ ንጉሥ የቴዎዶስዮስ ልጅ #ቅዱስ_ገብረ_ክርስቶስ አረፈ፣ ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የሆነ አንዱ #ቅዱስ_ሐዋርያ_ፊልጶስ አረፈ፣ ከሮሜ ሀገር የሆነ የከበረ የእግዚአብሔር ሰው #ሙሽራው_ቅዱስ_ሙሴ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ጻድቁ_አቡነ_አረጋዊ
ጥቅምት ዐሥራ አራት በዚህች ቀን ታላቁና የከበረው አባታችን አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል) የተሰወሩበት ነው።
እኚህ አባት ከ9 ቅዱሳን አባቶች አንዱ ሲሆኑ
አባታቸው ይስሐቅ የሮም ንጉስ ነበሩ፡፡ እናታቸው ንግስት እደና ይባሉ ነበር፡፡ የመጀመሪያ ስማቸው ዘሚካኤል ነው፡፡ ጥበብ መንፈሳ ሲማሩ አድገው ወደ እስክንድርያ ገዳም ገቡ፡፡ አበምኔቱ አባ ጳኩሚስ በፈቃደ እግዚአብሔር የመጡ መሆናቸውን አውቀው መዓረገ ምንኩስና ሰጥተዋቸዋል፡፡
የንጉሳዊ የቅንጦት ኑሮ ንቀው ትተው ገዳም ገብተው በምንኩስና ተወስነዋል፡፡ አባታችን በተጋድሏቸውም ከአባ እንጦንስ፣ ከአባ ጳውሊ እና ከአባ መቃርስ ቀጥሎ በአራተኛ ማዕረግ አበ መነኮሳት ሆነው ተመርጠዋል።
በገዳመ ዳውናስ 7 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደ ሮም ተመልሰው ሲያስተምሩ የሀገራችን ኢትዮጵያን ዜና ሰምተው ለመምጣት በ480 ዓ.ም ከአባ ፍሬምናጦስ በኋላ መንገድ ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በክንፉ ተሸክሞ አክሱም አድርሷቸዋል፡፡
ተመልሰውም ሄደው ስለ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ መስክረዋል፡፡ ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ጸንታ ትኖራለች ብለው ለሰባቱ ዘመዶቻቸው አበው መነኮሳት ነገሯቸው፡፡ ስምንቱም ጓዛቸውን ጠቅልለው በሮም ነግሶ የነበሩ ይስሐቅን (አባ ገሪማን) ጨምረው ንጉስ አልአሜዳ በነገሰ በአምስተኛ ዓመት ማለትም በ480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ዘጠኝ ሆነው መጥተዋል፡፡
አባ አረጋዊ እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀ መዝሙራቸውን ማትያስን አስከትለው እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩና ድውያንን እየፈወሱ ደብረ ዳሞ ደረሰዋል፡፡
ከእግረ ደብር ሆነው አሁን ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ በንግግሩ ሐሰት የሌለበት አምላካችን በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ በመዝሙር 90/91፥11-16 ላይ “በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። እንዳለው የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ስደሳ ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው አናት አድርሷቸዋል፡፡
ወዲያው ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል፡፡ ቦታውም ደብረ ሃሌ ሉያ ተብሏል፡፡ በዚያ ዕለት ግማሽ ህብስት በልተው ጠገቡ፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድራዊ ሕብስት አልተመገቡም፡፡ በሰንበተ ክርስታያን ከቅዳሴ በኋላ ሕብስተ ሰማያዊ እያመጡላቸው ይመገቡ ነበር እንጂ፡፡ ኋላም ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀ መዛሙርት ተሰብስበውላቸዋል፡፡
ዘጠና ዘጠኝ አመት ሲሞላቸው ጌታ በመንፈቀ ሌሊት ተገልጾ ምድራዊ መንግስትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ህልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግስቴን አወርሰሃለሁ ብሎ ቃልኪዳን ሰጣቸው፡፡ በስምህ የተማጸነውን እስከ አስራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ አንተም ከሞት ገጽ ትሰወራለህ ብሎ ተስፋቸውን ነገራቸው፡፡ እሳቸው መነኮሳቱን ሰብስበው ከእንግዲህ በሥጋ አታዩኝም ብለው ነግረዋቸው አበምኔት ሾመውላቸው በዚህች ዕለት በዚያው በደብረ ዳሞ ተራራ በስተምስራቅ አቅጣጫ ተሰውረዋል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ገብረ_ክርስቶስ
በዚህችም ቀን ዳግመኛ የቊስጥንጥንያ ንጉሥ የቴዎዶስዮስ ልጅ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። ይህም ቴዎዶስዮስ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው ሚስቱም በጎ የምትሠራ እግዚአብሔርንም የምትፈራ ናት ስሟም መርኬዛ ነው። እነርሱም ልጅ ስለሌላቸው ያዝኑ ነበር ወደ ኢየሩሳሌምም ሒደው ስእለትን ተሳሉ ቸር መሐሪ ወደሆነ እግዚአብሔርም ለመኑ እርሱም ልመናቸውን ተቀበሎ ይህን ያማረ ልጅ ሰጣቸው ስሙንም አብደልመሲህ ብለው ሰየሙት ትርጓሜውም ገብረ ክርስቶስ ማለት ነው ። የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ የሥጋዊንም ትምህርት አስተማሩት ።
አድጎ በጕለመሰም ጊዜ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ አጭተው እንደ ሥርዓቱ አጋቡት ከሌሊቱ እኩሌታም በሆነ ጊዜ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ተነሥቶ ወደሙሽራዪቱ ገባ እጅዋንም ይዞ ከእርስዋ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ። ከዚያም የሃይማኖት ጸሎት በአንድ አምላክ እናምናለን የሚለውን እስከ መጨረሻ ጸለየ የተሞሸረበትንም ልብስ ከላዩ አውልቆ የግምጃ ልብስን ለበሰ ወደ ሙሽሪቷም ሒዶ ራስዋን ሳማት እንዲህም እያለ ተሰናበታት እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኑር ከሰይጣን ሥራ ሁሉ ያድንሽ ። እርሷም አልቅሳ ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ ለማንስ ትተወኛለህ አለችው እርሱም በእግዚአብሔር ዘንድ እተውሻለሁ እኔም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ልከተለው እሔዳለሁ የአባቴ መንግሥት አላፊ ነውና አንቺም መሐላሽን አስቢ አላት ያን ጊዜ መሐላዋን አስባ ዝም አለች ።
ለሠርጉም የታደሙት ሁሉ እንደተኙ በሌሊት ወጥቶ ሔደ ወደ ባሕርም ዳርቻ ደርሶ በመርከብ የሚጓዙ መንገደኞችን አገኘ የዓመት መንገድ ወደሚሆን አርማንያም እስከሚደርስ ከእነርሱ ጋር ተጓዘ ።
ነግቶ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ በገቡ ጊዜ ሙሽራውን ልጃቸውን አላገኙትም ሙሽሪትንም ልጃችን ወዴት አለ ብለው ጠየቋት እርሷም እንዲህ አለቻቸው ። በሌሊት ወደ እኔ ገባ መሐላን አማለኝ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ራሴንም ስሞኝ ከእኔ ዘንድ ወጣ እኔም እያለቀስኩ ብቻዬን አደርኩ ነገርዋንም ሰምተው ወድቀው በመጮህ ታላቅ ልቅሶን አለቀሱ ።
በዚያችም ጊዜ በሀገሮች ውስጥ ሁሉ ልጁን ገብረ ክርስቶስን ይፈልጉት ዘንድ ንጉሡ አምስት መቶ አገልጋዮቹን ላከ ለድኆችና ለምስኪኖችም ምጽዋት አድርገው የሚሰጥዋቸውን ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው ።
ገብረ ክርስቶስ ግን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአርማንም አገር በተሠራች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ደጅ የሚኖር ሆነ ። አባቱ የላካቸውም ሁለቱ አገልጋዮች ከዚያ ደርሰው ስለርሱ መረመሩ ግን ወሬውን ማግኘት ተሳናቸው ለድኆችም ምጽዋትን ሰጡ እርሱም ከድኆችም ጋር ምጽዋትን ተቀበለ ።
በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ከኖረ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለአንድ ቄስ ተገለጸችለት ቦታውንም አመልክታ እንዲህ አለችው ። የእግዚአብሔር ሰው ገብረ ክርስቶስን ይዘህ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስገባው ከውጭ አትተወው ቄሱም እመቤታችን እዳዘዘችው አደረገ ።
ከዚህም በኋላ የተመሰገነ ገብረ ክርስቶስ በሌሊት ተነሣ ከእመቤታችንም ሥዕል ፊት ቁም ጸለየ እንዲህም አላት እመቤቴ ሆይ የተሠወረ ሥራዬን አንቺ ለምን ገለጥሽ አሁንም ወደሚሻለኝ ምሪኝ ይህንንም ብሎ የእመቤታችንን ሥዕሏን ተሳልሞ በሌሊት ወጥቶ ወደ ባሕሩ ወደብ ደረሰ ወደሌላ ሀገርም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ተሳፈረ። ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ከአባቱ አገር ደረሰ የአባቱና የእናቱም ባሮች እየናቁትና እየሰደቡት በአባቱ ደጅ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ ።
Вже доступно! Дослідження Telegram за 2025 — головні інсайти року 
