የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
Відкрити в Telegram
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
Показати більше2 639
Підписники
-224 години
+87 днів
+5630 день
Архів дописів
🔴#ስንክሳር ጥር 12
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ዐሥራ ሁለት በዚችህም ቀን የክብር ባለቤት ጌታ #በቃና_ዘገሊላ ለሰራ ተአምር መታሰቢያ ነው፣ የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤል_ቅዱስ_ያዕቆብ_እሥራኤልን የረዳበት ነው፣ ኃይለኛ የሆነ #ቴዎድሮስ_በናድሌዎስ በሰማእትነት ሞተ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቃና_ዘገሊላ
ቃና ዘገሊላ በቀጥታ ትርጉም የገሊላዋ ቃና ማለት ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን አስተምህሮ በጥምቀት በዓል ማግስት(ጥር 12) ቀን የቃና ዘገሊላ በዓል ይከበራል፡፡ ይህ በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር ተያይዞ በድምቀት የሚከበር መጽሐፍ ቅዱሳዊ ዳራ ያለው በዓል ነው፡፡ በዓሉ ቃና ዘገሊላ የሚል ስያሜ ያገኘው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የገሊላ ሀገር ክፍል በምትሆን ቃና በተባለችው ቦታ በፈፀመው ተአምር መነሻነት ነው፡፡
የቃና ዘገሊላ ጥንተ ነገሩ ወይም ታሪኩ የተፈፀመው የካቲት 23 ቀን ነው፡፡ ነገር ግን አባቶቻችን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ጋር ለማክበር ብለው የየካቲቱን በዓል ወደ ጥር 12 አምጥተውታል፡፡ ይህም ውኃ ወደ ወይን የተለወጠበትን በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር ለማስተሣሠር ለማስኬድ ነው፡፡ በመሆኑም የቃና ዘገሊላ በዓል ጥር 12 ቀን ይከበራል፡፡
በቃና ዘገሊላ ምን ተፈፀመ?
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የገሊላ ክፍል በምትሆን በቃና በተደረገ ሠርግ ላይ ከእናቱ ከድንግል ማርያም ጋር ተገኝቶ ነበር፡፡ ‹‹ወሀለወት ህየ እሙ ለእግዚእ ኢየሱስ›› ‹‹የጌታ የኢየሱስ እናትም በዚያ ነበረች›› እንዳለ ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ (ዮሐ 2÷1) እመቤታችን ለሠርገኞቹ ዘመድ ነበረችና ከልጇ ከወዳጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ በሰርጉ ላይ ታድማ ነበር፡፡ እናትን ጠርቶ ልጅን መተው ሥርዓት ስላልሆነ፤ በተጨማሪ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ከጌታ ጋር በሰርጉ ታድመዋል፡፡ ይህም መምህርን ጠርቶ ደቀ መዛሙርቱን መተው ሥርዓት ስላልሆነ (ተገቢ ስላልሆነ) ነው፡፡ የሠርጉ ሥነ-ሥርዓት በሠመረ ባማረ ሁኔታ እየተከናወነ ሳለ ድንገት የወይን ጠጅ አለቀ፡፡ አስተናባሪዎቹ በጭንቀት ባሕር ሰጥመው ምን እንደሚያደርጉ ግራ በገባቸው በጠበባቸው ጊዜ የችግር ጊዜ ደራሽ የኃዘን ጊዜ አፅናኝ የሆነችው የአምላክ እናት ድንግል ማርያም ቅዱስ ገብርኤል እንደተናገረ በፀጋ የተሞላች ናትና (ሉቃ 1÷28) ማንም ሳይነግራት የልቦናቸውን ጭንቀት አይታ፣ ጎዶሎአቸውን ተመልክታ ወደ ልጇ ወደ ወዳጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘወር ብላ ‹‹ወይንኬ አልቦሙ›› ‹‹ወይን ጠጅ እኮ አልቆባቸዋል›› አለችው፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?›› ‹‹ጊዜዬ ገና አልደረሰም›› አላት፡፡ እመቤታችንም ለአገልጋዮቹ ‹‹የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ›› አለቻቸው፡፡ ጌታም በቦታው የነበሩ ስድስት ጋኖች ውኃ ሞልተው እንዲያመጡ አዘዛቸው፡፡ ውኃውንም ወደ ወይን ለውጦ ለሊቀ ምርፋቅ (ለአሳዳሪው) እንዲሠጡት አዘዘ፡፡ አሳዳሪውም ወደ ወይን የተለወጠውን ውኃ በቀመሰ ጊዜ አደነቀ፡፡ ከወዴት እንደመጣ ስላላወቀ ሙሽራውን ‹‹ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን የወይን ጠጅ ያቀርባል ከሰከሩም በኋላ መናኛውን ያቀርባል አንተ ግን መልካሙን እስከ አሁን አቆይተሃል›› አለው፡፡ ወይኑም በሰው እጅ ያይደለ በሠማያዊው አባት የተዘጋጀ ስለነበር ጣፋጭ እና ልብን የሚያስደስት ነበር፡፡
‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?››
ይህንን የጌታችንን ንግግር ብዙዎች በዘመናችን ሲሣሣቱበት ይታያል ፡፡ ክብር ይግባውና አምላካችን ይህንን የተናገረው እናቱን ሊያቃልል ሽቶ አይደለም፡፡ ስለሆነም ከመጽሐፍ ቅዱስ አንፃር ይህን አረፍተ ነገር መመልከቱ በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ በተናጠል ስንመለከት ‹‹አንቺ ሴት›› ሴት የሚል ቃል የፆታ መጠሪያ ነውና በፆታዋ አክብሮ ሲጠራት ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሔዋን ከአዳም በተፈጠረች ጊዜ አዳም እንዲህ ሲል ተናግሮ ነበር ‹‹ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት ሥጋም ከሥጋዬ ናት እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል›› (ዘፍ 2÷23) በመሆኑም ጌታ አንቺ ሴት ማለቱ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ መንሣቱን ለማጠየቅ ነው፡፡ ‹‹ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?›› የሚለውን ዐረፍተ ነገር የንቀት ስለመሰለን ብቻ ‘ የዳቦ መልክ የያዘ ድንጋይ፤ ዳቦ ነው እንደማይባል’ የንቀት ንግግር ነው ልንል አይገባም፡፡ ጌታም እንዲህ ሲል ውኃውን ወይን አድርግላቸው ብትይኝ አላደርግም እልሽ ዘንድ ከአንቺ ጋር ምን ፀብ አለኝ ማለቱ ነው፡፡ ይህ ንግግር በመጽሐፍ ቅዱስ በብዙ ቦታ ተጽፎ እንደሚገኘው በዕብራውያን ዘንድ የተለመደ የአነጋገር ዘይቤ ነው፡፡ለአብነት ይሆን ዘንድ ጥቂት ጥቅሶችን ከመጽሐፍ ቅዱስ እንመልከት፡-
የሰራፕታዋ ሴት በ 1ነገ 17÷18 ላይ እንደምናገኘው ልጇ በሞተባት ጊዜ ኤልያስን በሐዘን በለቅሶ እንዲህ ብላ ነበር ‹‹የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ከአንተ ጋር ምን አለኝ?›› ትወልጃለሽ ብለህ የወለድኩት ልጅ ምን በድዬህ ምንስ አስከፍቼህ ሞተብኝ? ስትል ነው እንጂ አባባሏ የንቀት ወይም የማቃለል አይደለም፡፡
በጌርጌሴኖን አንድ አጋንንት ያደረበት ሰው ወደ ጌታችን ቀርቦ ‹‹የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ከአንተ ጋር ምን አለኝ?›› አለው፡፡ እውነት ይህ ቃል የንቀት ይመስላልን? የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ብሎ አምላክነቱን እየመሰከረ ሊያቃልለው ይችላልን? ደግሞስ ላለመጥፋት ፍፁም የሚፈልግ ሰው ሊያድነው ሥልጣን ያለውን ሊንቅ ይችላልን? አይችልም፡፡ ይህ ቃል የሚያመለክተው ምን አጠፋሁ ስለምን ልታጠፋኝ ወደድክ በማለት መፍራት መራዱን ነው፡፡ (ሉቃ 8÷28-29) ስለሆነም ‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?›› የሚለው የንቀት አለመሆኑን ከሁለቱ ጥቅሶች መረዳት እንችላለን፡፡ እመቤታችን እና ጌታ በንግግር አልተቃረኑም ንግግራቸው የፍቅር ነበር፡፡ ንግግራቸው የመግባባት ስለነበር ነው ‹‹አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ?›› ካላት በኋላ ዘወር ብላ አገልጋዮቹን የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ ያለችው፡፡
‹‹ጊዜዬ አልደረሰም›› ጌታ ይህን ቃል የተናገረው ስለ ብዙ ምክንያቶች ነው፡፡ ጊዜዬ አልደረሰም ማለቱ፡-
እግዚአብሔር ነገሮችን የሚያከናውንበት የራሱ ጊዜ አለው፡፡ በመሆኑም ይህን ተአምር የምፈፅምበት ጊዜዬ አልደረሰም ሲል ነው፡፡
አንድም ጋኖቹ ውስጥ የቀረ ወይን ስለነበረ ባለው ላይ አበርክቶ እንጂ ውኃውን ወደ ወይን አልለወጠውም እንዳይሉ ወይኑ ከጋኑ ተንጠፍጥፎ እስኪያልቅ ድረስ ጊዜዬ አልደረሰም አለ፡፡
አንድም ይሁዳ ከሠርግ ቤት ወጣ ብሎ ነበርና ወደ ሠርግ ቤቱ እሰኪመለስ ጊዜዬ አልደረሰም አለ፡፡ ይሁዳ በቃና የገለጠውን ምስጢር ለእኔ ስላላሣየኝ ተከፍቼበት ከተአምራቱ ቢያጎድለኝ በሞቱ ገባሁበት፤ ሸጥኩት እንዳይል ምክንያት ለማሳጣት እንዲህ አድርጓል፡፡
አንድም እውነተኛ የሕይወት ወይን የሆነውን ደሜን የምሠጥበት ጊዜ ገና ነው ሲል፡፡
የድንግል ማርያም አማላጅነት በገሊላ ቃና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሠርግ ቤት ሣለ የወይኑን ማለቅ የማይመለከት ሆኖ አይደለም፡፡ ነገር ግን የእናቱን የድንግል ማርያምን አማላጅነት ሊገልጥ ስለወይኑ ማለቅ እስክትነግረው ድረስ አንዳች ነገር አላደረገም፡፡ ኋላ ግን የጭንቀት አማላጅ ድንግል ማርያም ስለ ወይኑ አሰበች ልጇ ወዳጇን ለመነች፡፡ እርሱም የእናቱን ልመና ተቀብሎ ተአምራቱን ፈፀመ፡፡ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሣይነግሯት በልብ ያለውን የምታውቅ የምትመረምር እናት ናትና የሠርጉ አስተናባሪዎች ይሄ ጎደለ
በአንዲት አለትም ስሙ ቡላ የሚባል ገዳማዊ ወደርሱ መጥቶ እርስ በርሳቸው ሰላምታ ተሰጣጡ አባ ብላም እንዲህ አለው ወንድሜ ወቅሪስ ሆይ በቻህን አትሁን ጥቂት ወንድሞችን ካንተ ጋር አኑር እንጂ ያረጋጉህ ዘንድ ከሰይጣንም ጦርነት እንድትድን እንዲሁም አደረገ።
ከዕለታትም በአንዱ ሀይማኖትን በለወጡ በአርዮስ በንስጥሮስና በማኒ አምሳል ሆነው ሶስት ሰይጣናት ወደርሱ መጥተው በሀይማኖታቸው ተከራከሩት እርሱም በቅዱሳት መፃህፍት ቃላትና ሀይማኖታቸው በቀናች አባቶች ትምህርት ረታቸውና አሳፈራቸው።
ብዙዎችም የሆኑ ድንቆች ተአምራቶችን የሚሰራ ሆነ በአንዲትም እለት ወደ ቤተ ክርስቲያን በሄደ ጊዜ ተዘግታ አገኛት መነኮሳቱም መክፈቻ ፈልገው አላገኙም በላይዋም በአማተበ ጊዜ በሩ ተከፈተለት።
አባትህ ሞተ ብለው በነገሩት ጊዜ ዋሽታችኃል አባቴስ የማይሞት ሰማያዊ ነው አለ ተብሎ ስለርሱ የሚነገርለት ወቅሪስ ይህ ነው ዜንውም በገድሉ መፅሀፍና የአባቶች ዜና በተፃፈበት መፅሀፍ አለ።ከዚህም በኋላ ፈፅሞ በአረጀ ጊዜ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ሄደ።
አምላከ ቅዱሳን በጥምቀቱ ይቀድሰን:: ከበረከተ ጥምቀቱም ያድለን::https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ጥር_11
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር አስራ አንድ በዚች ቀን የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ተጠመቀ፣ የከበረ #እንጣልዮስ በሰማእትነት ሞተ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ #አባ_ዮሀንስ አረፈ፣ የከበረ ተጋዳይ ለሆነ አባት #አባ_ወቅሪስ የእረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#በዓለ_ጥምቀት (#በዓለ_ኤዺፋንያ)
ጥር አስራ አንድ በዚች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአጥማቂው ዮሀንስ ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ ውኃ ተጠመቀ።
ይችም እለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች ትርጓሜውም "መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው። "ልዩ የሆነች የሶስትነቱን ምስጢር ገልጦባታልና አብ ከሰማይ ሆኖ የምወደው በርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት እያለ ሲመሰክር ወልድም በዮርዳኖስ ወንዝ ቁሞ ሳለ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በወልድ ራስ ላይ ሲቀመጥ ይህ አጥማቂው ዮሀንስ እንደመሰከረ።
እንዲህ ሲል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠምቆ ከውኃ በወጣ ጊዜ ወዲያውኑ ሰማይ ተከፈተ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወረዶ በጌታችን ራስ ላይ ተቀመጠ ከሰማይም እንዲህ የሚል ቃል መጣ ይህ የምወደው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ነው እርሱንም ስሙት።
በዚች እለት ጌታችን ራሱን ገልጦአልና ከዚህ በፊት ሰላሳ አመት ያህል ራሱን አልገለጠም ነበር ግን በዚች እለት ለእስራኤል ልጆች ራሱን ገለጠ እነሆ የእግዚአብሔር በግ የአለምን ኃጢአት የሚያስወግድ ብሎ መጥምቁ ዮሀንስ እንደገለጠው የከበረ ወንጌል ምስክር ሆነ።
እኔ አላውቀውም ነበር ነገር ግን እስራኤል ያውቁት ዘንድ በውኃ ላጠምቅ ስለዚህ መጣሁ አለ። በዚህም በዓል የእግዚአበሄር ልጅ የክርስቶስ የጌትነቱ ክብር ተገልጧል እርሱም የአለሙን ሁሉ ሀጢአት ለማስወገድ የሚሰዋ የእግዚአብሔር አማናዊ በግ ነው።
ስለዚህም ይህ በዓል በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ዘንድ የከበረና ከፍ ከፍ ያለ ሆነ በርሱም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ በአከበረው ውኃ ይነፁበታል የተቀበሉትንም ንፅህና ጠብቀው ቢኖሩ በውስጡ የኃጢአታቸውን ስርየት ያገኛሉ።
ስለዚህም ከክፉ ነገር ሁሉ ተጠብቀን የፈጣሪያችንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የቸርነቱን ብዛት ልናመሰግን ይገባናል እርሱ ስለ እኛ ሰው ሆኖ ከኃጢአታችን አድኖናልና።
ለእርሱም ከቸር አባቱ ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ክብር ምስጋና ስግደትም ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_እንጣልዮስ_ሰማዕት
በዚችም ቀን ከፋርስ አገር ሰዎች ወገን የሆነ የከበረ እንጣልዮስ በሰማእትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ አስቀድሞ በሮም አገር የሰራዊት አለቃ መኰንን ሆኖ አስራ አምስት አመት ኖረ።
የክብር ባለቤት ክርስቶስን ንጉስ ዲዮቅልጣኖስ በካደው ጊዜ ይህ ቅዱስ ሰማያዊ መንግስትን መረጠ የዚህ የኃላፊውንም አለም ክብር ንቆ ተወ መጥቶም በከሀዲው ንጉስ ፊት በመቆም እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ ንጉሱም ስለ ድፍረቱ ደነገጠ።
ከፋርስ ሰዎችም ከታላላቆቹ ወገን እንደሆነ በአወቀ ጊዜ በሽንገላ በጎ ነገርን ተናገረው ምናልባት ከጌታ ክርስቶስ ሀይማኖት ልቡን መመለስ ቢችል ብሎ ለሰራዊት አለቃ ለኅርማኖስ ሰጠው። ኅርማኖስም ጌታ ክርስቶስን ከማምለክ ሀሳቡን ሊአስለውጠው ባልተቻለው ጊዜ ወደ ንጉሱ መለሰው እርሱም በየራሱ በሆነ ስቃይ አሰቃየው።
ጌታችንም መልአኩን ልኮ ከመከራው ሁሉ ያፀናውና ያረጋጋው ነበር በብዙ በተለያዩ ስቃዮችም እየተሰቃየ ለረጅም ጊዜ ኖረ ብዙ ጊዜም ሰቅለውታልና ከዚያም አርደው ቆዳውን ገፈፉት ምላሱንም ቆረጡት ለነጣቂዎች አውሬዎችም ጣሉት በጨለማ ቤትም ዘጉት ሶስት ጊዜም ነፍሱን አሳለፈ እግዚአብሔርም አስነሳው።
ዲዮቅልጥያኖስም ማሰቃየቱን በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡት የሰማእትነት አክሊልንም በመንግስተ ሰማያት ተቀበለ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ዮሐንስ_ሊቀ_ዻዻሳት
በዚችም ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባ ዮሀንስ አረፈ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ አራተኛ ነው። ይህም አባት ሊቀ ጵጵስና ከመሾሙ አስቀድሞ ወደ ህንድ አገር በባሕር ላይ በመርከብ እየሄደ ሁልጊዜ የሚነግድ ነጋዴ ሆኖ ነበር ከዚያ ፊት ግን በምስር ሀገር በሰማዕቱ በቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን በፀሀፊነት የሚያገለግል ዲያቆን ነው ፀሀፊነቱንም ትቶ የሚነግድ ሆነ።
በዘጠኝ መቶ አራት አመተ ሰማእታት የካቲት አራት በእሁድ እለት ኤጲስቆጶሳቱ መርጠው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት በመልካም አጠባበቅም መንጋውን የሚጠብቅ ሆነ።ሊቀ ጳጳሳት ሆኖ ከመሾሙ በፊት ሀያ ሽህ ያህል የወርቀወ ዲናር ነበረው ከመሞቱ በፊት ለድኆችና ለችግረኞች ለአብያተ ክርስቲያን ለገዳማትም ሁሉን ገንዘቡን ሰጥቶ ጨረሰ።
በሹመቱም ወራት ከህዝብ ምንም ምን እጅ መንሻ አልተቀበለም በሹመቱም ሀያ ስምንት አመት ኖረ በዘጠኝ መቶ ሰላሳ ሁለት አመተ ሰማእታት በዚች ቀን በጥምቀት በአል አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ወቅሪስ_ገዳማዊ
በዚችም እለት የከበረ ተጋዳይ ለሆነ አባት አባ ወቅሪስ የእረፍቱ መታሰቢያ ነው። ይህም ቅዱስ አባት በባስልዮስ ዘንድ አደገ እርሱም ቅስና ሾመው ይህም ቅዱስ በደም ግባቱ በላህዩ ደስ የሚል ፊቱም የሚያምር ነበር።
በቀድሞው ግብሩ ወጣት ሆኖ ሳለ የሹሙን ሚስት ተመኛትና እጅግም ወደዳት እርሷም ወደደችው ወደ ሌላ ቦታ ሄደው ፍላጎታቸውን ይፈፅሙ ዘንድ ተማከሩ ለዚህም ነገር ሲዘጋጁ በህልሙ ራእይን አየ። እርሱ ታስሮ በፍርድ አደባባይ ቆሞ ነበር ሌሎችም ብዙዎች እስረኞች ከእርሱ ጋር አሉ ስለ በደላቸውም እያንዳንዳቸውን ይመረምሯቸው ነበር እርሱም በልቡ የታሰርኩት በምን ይሆን ባሏን ልነጥቀው ስለፈለግሁ ስለዚያች ሴት ነውን እርሱ ከስሶኝ ወደዚህ ታላቅ ግዳጅ ላይ አደረሰኝን አለ።
በዚህም ነገር እየተሸበረ ሳለ በቀድሞ ወዳጁ አምሳል አንድ ሰው መጣና የታሰርከው በምንድን ነው? አለው ስለ ሀጢያቱ ስለ አፈረ ሊሰውረው ወደደ ግድ ባለውም ጊዜ እንዲህ ነገረው ወዳጄ ሆይ እገሌ ስለሚስቱ የከሰሰኝ ይመስለኛል ስለዚህም ፈርቼ እሸበራለሁ በወዳጁ አምሳል ወደርሱ የመጣው መልአክም ወዳጄ ሆይ ይህን ስራ እንዳትሰራ ወደርሱም እንዳትመለስ በቅዱስ ወንጌል ማልልኝ እኔም ዋስ እሆንሀለሁ አለው በወንጌልም ማለለት በዚያንም ጊዜ ከእንቅልፉ ነቃ ያየው ራእይም እውነት እንደሆነ አወቀ።
ስለዚህም አገሩን ትቶ ወደ እስክንድርያ ሄደ በዚያም ስሟ ኄራኒ የሚባል እግዚአብሄርን የምትፈራ አንዲት ሴት አገኘ በተነጋገሩም ጊዜ የልቡን ሁሉ ነገራት እርሷም እነዚህን ያማሩ ልብሶችህን ተው ተርታ ልብስንም ለብሰህ እግዚአብሄርን አገልግለው አለችው።ከዚያም ወደ በርሀ ሄደ ከብዙ ተጋድሎ የተነሳ ሆዱ እንደ ድንጋይ እስከ ደረቀ ድረስ ቅጠላቅጠል እየበላ ኖረ ጌታችንም ወደርሱ መጥቶ ፈወሰው።
አጋንንትም ስለሚፈታተኑትና ስለሚያሰቃዩት እርሱ በፆምና በፀሎት በመጋደል በክረምት ዝናብ እየወረደበት ራቁቱን ቆሞ ያድራል በበጋም በቀን የፀሀይ ትኩሳት በሌሊትም ቁር ሰማያዊ ሀብት እስከተሰጠው ድረስ መላእክትም ወደርሱ መጥተው ሰማያዊ ኅብስትን ሰማያዊ መጠጥን ይመግቡት ነበር።
የተሰወሩ ራእዮችን ያውቅ ዘንድ ተገባው ሶስት ድርሰቶችንም ደረሰ አንዱ በበረሀ ስለሚኖሩ ሁለተኛው በአንድነት ስለሚኖር መነኮሳት ሶስትኛው ስለካህናት ነው።
🔴#ስንክሳር ጥር_10
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር አስር በዚህች እለት #የገሃድ_ጾም ነው፣ የከበረ አባት #አባ_ታውብንጦስ_ዘሲሐት ዕረፍቱ ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ጾመ_ገሃድ
ጥር አስር በዚህች ዕለት ምንም ምን መብልን ሰይቀምሱ ምእመናን ሁሉ እስከ ምሽት ይጾሙ ዘንድ ከእኛ አስቀድመው የነበሩ ታላላቅ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን መምህራን ሥርዓትን ሠሩ በምሽትም ቢሆን በታላቁ ጾም ከሚበላው በቀር ጥሉላትን እንዳይቀምሱ። በዚች ዕለት ምእመናን እስከ ምሽት እንደመጾሙን ያዘዙበት ምክንያቱ ይህ ነው የልደትና የጥምቀት በዓል በዓል በረቡዕ ወይም በዓርብ ቀን ቢሆን በበዓለ ኃምሳ የሚበላውን የጥሉላት መብል በጥዋት በመብላት ምእመናን ሁሉ በዓሉን እንዲአከብሩ የከበሩ አባቶቻችን ሐዋርያት አዝዘዋል እሊህ ሁለቱ የእግዚአብሔር ታላላቅ በዓላቶቹ ናቸውና።
እኛ በዚህ በኅላፊው ዓለም ተድላ ደስታ ደስ የሚለን ለሌሎች እንዳይመስላቸው እንደ አይሁድና እንደ አረማውያን በዓል በመብልና በመጠጥ ብቻ እንዳናደርግ ስለዚህ ከልደትና ከጥምቀት በዓል በዋዜማ ያሉትን ሁለቱን ዕለታት እንድንጾም አዘዙን የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕና በዓርብ ላይ በሚሆን ጊዜ በረቡዕና በዓርብ ፈንታ እንድንጾማቸው ይገባልና በዚህም ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል የጾም ሥራና የበዓል ማክበር ሥራ ነው። እንዲሁም በግብፃውያን አብያተ ክርስቲያን የተሠራ ነው።
በይረሙን በእሑድ ወይም በአይሁድ ሰንበት ቀን ቢሆን ይህም ጌታ የተገለጸበት ጥር ዐሥራ ቀን ነው በዋዜማው ዐርብ እስከ ምሽት ይጹሙ አስቀድመን እንደተናገርን ጥሉላት አይብሉ የልደትና የጥምቀት በዓልም ሰኞ ቀን ቢሆን በሰንበት ቀን ይጾም ዘንድ አይቻልም ነገር ግን ጥሉላትን ከመብላት ይጠበቁ።
በጥምቀትም ዕለት ከእኵለ ሌሊት በፊት ተነሥተው በውኃው ላይ ይጸልዩና ይጠመቁ ሕፃናትም በሚጠመቁ ጊዜ በውኃ እንዳይገድፉ ካህናቱም ከመንጋቱ በፊት ቀድሰው ቊርባኑን ያሳርጉ እጅግም ማልደው በጥዋት ከቤተ ክርስቲያን ይውጡ በከበረ ሥርዓታቸው ጌቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ።
የመለካውያን ወገኖች ግን የልደትና የጥምቀት ዋዜማ በቅዳሜ ቀን ወይም በእሑድ ቀን ቢሆን በሦስት ሰዓት ይቀድሳሉ ከወደዱም የተባረከ ኅብስት ተመግበው ውኃ ይጠጣሉ ከዚህም በኋላ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁነው በየሰዓቱ በመጸለይ ለበዓሉ የሚገባውን የነቢያትን ትንቢቶች ያነባሉ በዚያች ቀን በምሽት ይኸውም ጥር ዐሥር ነው በውኃው ላይ ይጸልያሉ ይህም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙት አልሆነም። እርሳቸው የኤጲፋንያን በዓል እንዲአክብሩ አዘዋል ይኸውም መድኃኒታችን የተገለጠበት ካኑን በሚባል በሮም ሁለተኛ ወር በሰባት ይህም ጥር ዐሥራ አንድ ቀን ነው።
መለካውያን ግን የከበሩ አባቶች የቤተ ክርስቲያን መምህራን ያዘዙትን ይተላለፋሉ በልደትና በጥምቀት በዓል ዓርብም ረቡዕም ቢሆን አስቀድመው በርሱ ፈንታ ሳይጾሙ በጥዋት ተነሥተው ይበላሉና። እኛንም ከበደላችን ያነጻን ዘንድ በዮርዳኖስም ወንዝ እንደ ተገለጸ የጌትነቱን ክብር በልቡናችን ይገልጥልን ዘንድ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው ጌትነት ክብር ስግደት ለእርሱ ይገባልና ከቸር አባቱ ጋር ይቅር ባይ ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ታውብንጦስ_ዘሲሐት
በዚህችም ዕለት አባ ታውብንጦስ አረፈ፡፡ ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ አባ ታኡና በሚባል በሮሜው ሊቀ ጳጳሳት ቤት አደገ እርሱም የምንኵስናን ልብስ አለበሰው። መንፈሳዊ ዕውቀትና ኃይል እንደተሰጠው አይቶ ከእስክንድርያ አገር ውጭ ስሙ ጤናዲራን በሚባል ቦታ ኤጲስቆጶስነት ሹሞ የገዳም አበ ምኔት አደረገው ከእርሱ ሥር ያሉ መነኰሳትም ሰባት መቶ ናቸው።
ከዚህም በኋላ ከእርሱ ጋር ላሉ መነኰሳት አለቃ የሆነ ኤጲስቆጶስ ታውብንጦስ ከከሀዲ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ስለሆነው ሁከት በሰማ ጊዜ ሸሽቶ ወደ ደብረ ሲሐት ገዳም ሒዶ እግዚአብሔርን ከምትፈራ ከአንዲት ድንግል ዘንድ ተቀመጠ። በእርሷ ቤትም ብዙ ዘመናት ኖረ በመጀመሪያ ወደርሷ በገባ ጊዜ ግን ንጉሡን ስለ መፍራት ጣዖትን ስታመልክ አገኛትና የክብር ባለቤት ጌታችን ክርስቶስን ወደ ማመን መለሳት።
ከዚያም ተርኑጥና መርኑስ ወደ ሚባሉ ገዳማት ሔደ የአብያተ ክርስቲያናትን ወሬ ይሰማ ዘንድ ፈልጎ በጾም በጸሎት ሌሊትም በመትጋት እያገለገለ በአንዲት ገዳም ውስጥ ሁለት ሦስት ቀን ተሠውሮ ያድር ነበር። የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ በላዩ እንዳደረ እግዚአብሔርም በእጆቹ ድንቆች ተአምራቶችን እንዳደረገ ከወንበዴዎችና ከዓመፀኞች ብዙዎችን መነኰሳትን አድርጎ ለክርስቶስ ወደ መገዛት እስከ መላሳቸው ድረስ መነኰሳቱ ሁሉ መሰከሩለት።
ከዚህም በኋላ ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ የሚሞትበትን ቀን ዐወቀ ልጆቹንም የክርስቶስ በሆነች በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ ትእዛዙንም እንዲጠብቁ አስተማራቸው ወዲያውኑ በሰላም ዐረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የተከበራችሁ የጥምቀት ዘማርያን በሙሉ
በቅድሚያ እንኳን ለበዓለ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ እያልን ለበዓለ ከተራ ታቦተ ሕጉ 8:00 ላይ በመንበረ ክብሩ የሚንቀሳቀስና የሚወጣ በመሆኑ ዘማርያን ቀድማችሁ እንድትገኙ ይሁን።
ከዚህ በተጨማሪም ለበዓለ ጥምቀት እና ቃና ዘገሊላ እለትም እንዲሁ ታቦተ ሕጉ ከጠዋቱ 3:30 የሚንቀሳቀስና የሚወጣ በመሆኑ ቀድማችሁ በአገልግሎት ስፍራ እንድትገኙ እናሳስባለን።
መልካም አገልግሎት ይሁንልን
እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ እያልን ሰ/ት/ቤታችን ለሚያስገነባው ሕንጻ ገቢ ማሰባሰቢያ ያዘጋጀውን ይህንን እጣ በመግዛትና በመደገፍ የበረከቱ ተሳታፊ ይሁኑ።
🔴#ስንክሳር ጥር_9
#አባ_አብርሃም_ገዳማዊ
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ዘጠኝ በዚህች ቀን የከበረ አባት አባ አብርሃም ዐረፈ፡፡ የዚህም ቅዱስ ሰው አባቱ ድኆችን የሚወዳቸውና የሚራራላቸው ነው። በዘመኑም በግብጽ አገር ታላቅ ረሀብ ሆነ እጅግ ባለጸጋ ነበርና ከደግነቱና ከታማኝነቱ ብዛት የተነሣ እርሱ በአለበት አገር ዙሪያ ያሉ አገሮች ሁሉም የምድራቸው ፍሬ በእርሱ ዘንድ አደራ ያስቀምጡ ነበር ረሀቡም በጸና ጊዜ በእርሱ ዘንድ በአደራ የተቀመጠውን እህል ሁሉንም ለድኆች ሰጠ እግዚአብሔርም ስለ ምድራቸው ፍሬ ሁሉንም ክፉ ቃልን እንዳይናገሩት አደረጋቸው። በእርሱ ዘንድ ያኖሩትን የምድራቸውን ፍሬ ሽተው ወደርሱ በሚልኩ ጊዜ ተነሥቶ ወደርሳቸው ይሔዳል እነርሱም በየራሳቸው ለያንዳንዱ የምድራቸው ፍሬ እንደደረሳቸው አድርገው ይጽፉለታል እንጂ ምንም ምን አይናገሩትም።
የዚህም ቅዱስ እናት እግዚአብሔርን የምትፈራ ምእመን ናት ሰይጣንም ቀናባት በአንድ ክፉ ሰው ልቡና አድሮ በፋርስ ሰዎች ዘንድ ነገር ሠራባት እነርሱም ማርከው ወደ አገራቸው ወሰድዋት በአንዲት ሌሊትም ራዕይን አየች ያ ነገር የሠራባት ሰው በሲኦል ውስጥ በእሳት ሰንሰለት ታሥሮ "እግዚአብሔር ያደረገልሽን ተመለከትሽን ነገር የሠራብሽን ያንን ሰው ተበቅሎታልና" ይላታል እርሷ ግን "ጌታዬ ሆይ መከራና ሥቃይ በርሱ ላይ እንዲደርስ አልሻም" ትላለች ያ የሚያሳያትም "አንቺ ግን ወደ አገርሽ ተመልሰሽ በቤትሽ ትኖሪ ዘንድ አለሽ" ይላታል እንዲሁም ሆነ።
ባሏም በሞተ ጊዜ አብርሃም ድኃ አደግ ሆነ እርሷም እናቱ ሚስት ልታጋባው አሰበች እርሱ ግን ይህን አልወደደም እናቱም እጅግ ደስ ተሰኘችበት። ወደ ገዳም ሒዶ ሊመነኵስ በፈለገ ጊዜ እናቱ ልትሸኘው ወጣች እጆቿንም ወደ ሰማይ አንሥታ በመጸለይ ልጇን ወደ እግዚአብሔር አደራ አስጠበቀች። "አቤቱ ጌታዬ ይህን ቊርባንን አድርገህ ተቀበለኝ" አለች።
በዚያንም ጊዜ አባ አብርሃም ሔደ በአስቄጥስ በረሀ ውስጥ ተጒዞ በአባ ዮሐንስ አበ ምኔትነት ዘመን ወደ አባ መቃርስ ገዳም ደረሰ ወደርሱም ወደ አባ ዮሐንስ ገባ ተወዳጅ ልጅንም ሆነለት። በጎ ተጋድሎንም ጀመረ በአንዲት ሌሊትም ራዕይን አየ የበዓቱ ጣሪያ ተሰነጠቀ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጦ ወደርሱ ሲወርድ አየው ኪሩቤልም ያመሰግኑት ነበር እርሱም ፈርቶ ተንቀጠቀጠ ፈጥኖም ሰገደ ጌታችንም ባረከውና በታላቅ ክብር ወደ ሰማይ ዐረገ። ጌታችንም የወረደባት በቤቱ ጣሪያ የተሠነጠቀችው ምልክት ሁና እስከ ዛሬ በመታሰቢያነት አለች እርሷም ለመንፈሳዊ አባቱ ለአበ ምኔቱ አባ ዮሐንስ መኖሪያ ቅርብ ናት እርሷም በግቢግ ትባላለች። የእግዚአብሔርም መልአክ ሁል ጊዜ ይጐበኘዋል ብዙ ምሥጢራትንም ይገልጥለታል ያስገነዝበዋልም።
ከዚህም በኋላ አባ አብርሃም ወደ ደብረ ኀርዮን ሔደ በዚያም አባ ገዐርጊን አግኝቶት ወደ አስቄጥስ ገዳም ከእርሱ ጋር ወሰደውና እስከ ዕረፍታቸው ጊዜ በዚያች በዓት ኖሩ።
አበ ምኔቱ አባ ዮሐንስም በዐረፈ ጊዜ በአባ አብርሃም ላይ ሰይጣን ታላቅ ደዌ አምጥቶበት ዐሥራ ስምንት ዓመት በዚያ ደዌ ውስጥ ኖረ ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ የጌታችንን ሥጋና ደም ያቀብሉት ዘንድ ወንድሞችን ለመናቸው ከተቀበለም በኋላ መንፈሳዊ አባቱ አባ ዮሐንስ ወደርሱ መጥቶ "እነሆ ወደ ታላቅ ሠርግ እግዚአብሔር ጠርቶሃል" አለው። ከዚህም በኋላ ዕድሜው ሰማንያ ዓመት ሁኖት በሰላም ዐረፈ፡፡ በዓታቸውም እስከ ዛሬ የታወቀች ሁና ትኖራለች።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ከዚህም በኋላ መምህሩ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ እንድራኒቆስ ወሰደውና ልጁ ብንያሚን ያየውን ራእይ ነገረው እርሱም ቅስና ሾመውና ለቤተ ክርስቲያንም አስተዳዳሪ አደረገው አባ እንድራኒቆስም እስከ አረፈ ድረስ በበጎ አስተዳደር ቤተ ክርስቲያንን እየአስተዳደረ ኖረ ከዚህም በኋላ ይህ አባ ብንያሚን ሊቀ ጵጵስና ተሾመ በተሾመ ጊዜም ታላቅ መከራ ደረሰበት።
በእርሱ ላይም ታላቅ መከራ ከመድረሱ በፊት የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ከእርሱ የሚሆነውን ሁሉ አስረዳው እርሱም እንዲሸሽ ኤጲስቆጶሳቱም ከእርሱ ጋር እንዲሸሹ አዘዘው። በዚያንም ጊዜ ቀድሶ ለሕዝቡ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው በቀናች ሃይማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው እርሱ ከመልአኩ እንደተረዳ የሚሆነውን ሁሉ አስረዳቸው።
ከዚህም በኋላ ወደ ኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ ወደ ገዳማት አለቆችም መልእክቶችን ላከ እንዲሸሹም አዘዛቸው እርሱም ወደ አባ መቃርስ ገዳም ወደ አስቄጥስ በረሀ ከዚያም ወደ ላይኛው ግብጽ ሔደ።
አባ ብንያሚንም ከእስክንድርያ አገር ከወጣ በኋላ ከሮም ንጉሥ ከሕርቃል ዘንድ የተሾመ መኰንን መጣ እርሱም ሊቀ ጵጵስና የደረበ በአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ላይ የሠለጠነ ነው። ብዙዎች ምእመናንንም አሠቃያቸው ስሙ አባ ሚናስ የሚባል የአባ ብንያሚንንም ወንድም ይዞ አሠቃየው በጐኖቹም ውስጥ እሳት ጨምሮ አቃጠለው ከዚህም በኋላ በባሕር ውስጥ አሠጠመው።
በእነዚያም ወራቶች ንጉሥ ሕርቃል በሕልሙ እነሆ ግዙራን የሆኑ ብዙ ሕዝቦች በላይህ መጥተው በምድር ሁሉ ላይ ይነግሣሉ የሚለውን ራእይ አየ ለንጉሡም አይሁድ እንደሆኑ መስሎት ነበር ለወዳጆቹ ይህን ራእይ አስረዳቸው ራእዩ ግን ስለ እስላሞች መንግሥት የሆነች ናት። በዚያንም ጊዜ ያትሮብ ከሚባል ምድር መጥተው በሶርያ ምድር ነገሡ።
በዚያንም ወቅት የአጽ ልጅ ኡመር መጥቶ በግብጽ ላይ ነግሦ ሦስት ዓመት ኖረ ወደ እስክንድርያም ሒዶ አፈረሳት ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትንም አቃጠለ ከታችኛው ምድር ከባሕር ዳር ያለች የታወቀች የወንጌላዊ የቅዱስ ማርቆስን ቤተ ክርስቲያንንም እንዲሁም በእስክንድርያ አገር ዙሪያ ያሉ ብዙ ገዳማትን አቃጠለ በውስጣቸው ያለ ገንዘባቸውን ሁሉ ማረከ።
ከዚህም በኋላ የጭፍራ አለቃው የቅዱስ ማርቆስን የቤተ ክርስቲያኒቱን መርከቦች ወሰደ እጁንም ወደ ሣጥን አስገብቶ ሲዳስስ የቅዱስ ማርቆስን ሥጋ አገኘ ታላቅ እንደሆነም አውቆ በመርከብ ውስጥ በክብር አስቀመጠው።
ወልደ አጽ ኡመር ግን የአባ ብንያሚንን ሥራ ስለምን እንደሸሸም በአወቀ ጊዜ መልእክትን ጻፈለት እንዲህም አለው ና አትፍራ ወገኖችህን አብያተ ክርስቲያናትንም አስተዳድራቸው። አባ ብንያሚንም ሕርቃል በነገሠ በዐሥር ዓመት እስላሞች በነገሡ በሰባት ዓመት ከሸሸበት ቦታ መጣ ወልደ አጽ ኡመርም አባ ብንያሚንን በታላቅ ክብር አከበረው አብያተ ክርስቲያናቱንም ገንዘባቸውንም የካህናቱንም ምድራቸውን እንዲሰጡት አዘዘለት።
በአምስቱ ሀገሮች ላይ እነግሥ ዘንድ ወደ ምዕራብ አገር እሔዳለሁና ሒደህ ስለእኔ ጸልይልኝ በተመለስኩም ጊዜ የምትሻውን ሁሉ አደርግልሃለሁ አለው አባ ብንያሚንም እግዚአብሔር መንገድህን ያቀናልህ አለው በእርሱ ላይ የሚሆነውንም ሁሉ ነገረው።
በዚያን ጊዜም መርከቦቹን እንዲያቀርቡለትና እንዲሔድም ፈለገ በወደቡም ውስጥ መርከቦችን አዘጋጁለት ያቺንም የወንጌላዊ ማርቆስ ራስ በውስጧ ያለበትን መርከብ በገመድ አሥረው ጐተቷት ግን አልወጣችም መርከበኞችም ሁሉ ተሰበሰበው ቢስቧት ከቦታዋ አልተንቀሳቀሰችም።
የመርከቡም ሹም ፈራ በውስጧ የቅዱስ ማርቆስ ራስ ስለ አለባት ስለዚያች መርከብ ለኡመር ነገረው ኡመርም ለአባ ብንያሚን ይህን ነገረው ቅዱስ ማርቆስም ለአባ ብንያሚን በሕልም ተገለጠለትና ቦታ አዘጋጅልኝ አለው።
አባ ብንያሚንም በሰማ ጊዜ ተነሥቶ ወደ መኰንኑ ሔደ በመርከቡ ውስጥ ያለችው የከበረ የወንጌላዊው ማርቆስ ራስ እንደሆነች አስረዳው ከዚህም በኋላ አባ ብንያሚን የከበረ ማርቆስን ራስ ከመርከብ ውስጥ አውጥቶ ወሰዳት በዚያንም ጊዜ መርከቢቱ ከወደቡ ወጣች ገዥው መኰንን ኡመርም ይህን አይቶ እጅግ አደነቀ ብዙ ገንዘብም ሰጥቶ ለከበረ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራለት አዘዘው ያማረች ቤተ ክርስቲያንንም ሠራ የቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ራሱንም በውስጧ አኖረ።
ይህ አባት ብንያሚንም አረማውያንን ስለማስተማር እጅግ ታጋይ ሆነ ከእነርሳቸውም ብዙዎቹን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው አጸናቸውም። በዚህ አባት ዘመንም ከእርሱ አስቀድሞ እንደርሱ ያልሆነ እጅግ ታላቅ የሆነ ረሀብን እግዚአብሔር በሀገሩ ሁሉ አመጣ። ቊጥር የሌላቸው ብዙ ሰዎችም ሞቱ በሀገሩ ሜዳዎችና ገበያዎች ውስጥ የወደቁ ሆኑ።
ከዚህም በኋላ አባ ብንያሚን ለሁለት ዓመት ያህል እግሩን ታመመና በሰላም አረፈ የሹመቱም ዘመን ሠላሳ ዘጠኝ ዓመት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሚክያስ_ነቢይ
በዚችም ዕለት የነቢይ ሚክያስ መታሰቢያው ሆነ። የዚህም ነቢይ ከታናሽነቱ ጀምሮ አካሔዱ መልካም ሆነ ስለ ሥራው ማማርና ስለ ጽድቁ ሕዝቡ ሁሉ ያደንቁታል ያከብሩታል ሚክያስም ይሉታል ትርጓሜውም መልአክ ማለት ነው መልኩ እጅግ ያማረ ነውና የሚናገረውም ትንቢት እንደተናገረው ይሆናል የእግዚአብሔር መልአክም ተገልጾለት ያነጋገረው ነበር ሕዝቡ ግን ያንን መልአክ አያዩትም ድምፁን ግን ይሰማሉ ከእርሳቸውም ያደላቸው የሚያዩት አሉ በመሳፍንት መጽሐፍ እንደተጻፈ። በጐልማሳነቱም አርፎ በአባቶቹ ቦታ ተቀበረ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ጥር_8
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ስምንት በዚች ዕለት በአስቄጥስ ገዳም #የአባ_መቃርስ ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት ነው፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_እንድራኒቆስ አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ብንያሚን አረፈ፣ #የነቢይ_ሚክያስ መታሰቢያው ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ታላቁ_ቅዱስ_መቃርስ
ጥር ስምንት በዚች ዕለት በአስቄጥስ ገዳም የአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን በከበረና በተመሰገነ በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ብንያሚን እጅ የከበረችበት ሆነ።
ከዚህም በኋላ መቆቅዝ ከሚባል ዐላዊ መለካዊ በአባ ብንያሚን ላይ መከራ ደረሰበት አባ ብንያሚንም ሸሽቶ ወደ ላይኛው ግብጽ ሔደ ዐሥር ዓመትም እስኪፈጸም በዚያ ኖረ ከዚህም በኋላ ያን ዓላዊ መቆቅዝን እግዚአብሔር አጠፋው ለአብያተ ክርስቲያን ሁሉ ጸጥታ ሰላም ሁኖ አባ ብንያሚንም ወደ መንበረ ሢመቱ ተመለሰ የአስቄጥስ ገዳም ሽማግሎችና መምህራን ወደርሱ መጡ ወደርሳቸውም ሒዶ አዲስ ቤተ ክርስቲያን እንዲ አከብርላቸው ለመኑት እርሷም የከበረ የአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ናት። በታላቅ ደስታም ተነሥቶ ከእሳቸው ጋር ሔደ የቤተ ክርስቲያኒቱንም መባረኪያ ጸሎት ጀመረ።
መሠዊያውንም በሜሮን ሊቀባ በጀመረ ጊዜ የክብር ባለቤት የጌታችን እጅ ከእርሱ ጋር ስትቀባ አየ ከታላቅ ፍርሀት የተነሣ በግምባሩ ፍግም ብሎ ወደቀ። ከኪሩቤልም አንዱ አነሣው እንዲህም አለው ተነሣ አትፍራ ልዩ የሆነውን ሥርዓት ለዚህ ቦታ ጻፍ ይህ የእግዚአብሔር ምሥጢር የሚፈጸምበት ነውና ማንም በትዕቢት ወይም መማለጃ በመስጠት እንዳይገባ በውስጡ በሚገባ ከሚሾም በቀር የሚደፍርና በውስጡ ከንቱ ነገርን የሚናገር አይኑር የእግዚአብሔር መመሰገኛ ቤቱ ነውና ይህም ሥርዓት በዚህ ቦታ እስከ ዘላለሙ የተሠራ ይሆናል።
እነሆ ዘመን ይመጣል የአባቶችንም ትእዛዝና ሥርዓት ያፈርሳሉ ይህም የከበረ ቦታ እንደ መሣለቂያ ቦታ ይሆናል። አባ ብንያሚንም ይህች የእግዚአብሔር ቤት የሰማይ ደጅ ናት አለ ይህንንም ከኪሩብ ጋር ሲናገር ከቤተ ክርስቲያኒቱ በስተምሥራቅ ተመለከተ አንድ መልኩ የሚያምር ጽሕሙ የረዘመ ፊቱም እንደ መልአክ ፊት የሚያበራ ሽማግሌ አየ። ለአባ ብንያሚንም ደስ አሰኘውና በልቡ እንዲህ አለ ከኤጲስቆጶሳት አንዱ ቢሞት በርሱ ፈንታ ይህን ሽማግሌ እሾመዋለሁ። ኪሩብም እንዲህ አለው ብንያሚን ሆይ ይህን አባት መቃርዮስን ኤጲስቆጵስን ታደርገዋለህን። እርሱ የሊቃነ ጳጳሳት አባታቸው ነውና ዛሬ ከልጆቹ ጋር ደስ ይለው ዘንድ መጥቷልና ከልጆቹም መንፈሳዊ ሹመት የሚሾም ወይም አለቃ የሚሆን አይታጣም ከገዳማቱም የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ አይታጣም።
አባ ብንያሚንም ልጆቹ ብፁዓን ናቸው አለ ኪሩብም እንዲህ አለ ብፁዓንስ የሚባሉ ትእዛዞቹን ጠብቀው ፍለጋውን ቢከተሉ እነርሱ ከእርሱ ጋር አሁን በአለበት ክብር ውስጥ ይሆናሉ ትእዛዞቹን ቢተላለፉ ግን ከእርሱ ጋር ዕድል ፈንታ አይኖራቸውም ።
አባ ብንያሚንም ኪሩብን እንዲህ አለው ጌታዬ ሆይ በዚህ ነገር በልጆቼ ላይ ተስፋ የሚያስቆርጥ ነገር አትናገር ነገር ግን በሰብል ውስጥ አንዲት ቅንጣት የተረፈች እንደሆነ እግዚአብሔር በውስጥዋ በረከቱን ያደርጋል። እንዲሁም የፍቅር ቅንጣት በውስጣቸው የተገኘ እንደሆነ እግዚአብሔር ከመንግሥቱ እንደማያርቃቸው እኔ አምናለሁ።
ከአረጋዊው አባ መቃርስ ርኃራኄ የተነሣ ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚን አደነቀ መልአኩ ኪሩብ እንዳዘዘውም ያንን ሥርዓት ጽፎ ለዘወትር መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖረው።
ዕድሜው በደረሰ ጊዜ ዕረፍቱ በዚች ቀን ይሆን ዘንድ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው እንዲሁም ሆነለት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_እንድራኒቆስ_ሊቀ_ዻዻሳት
በዚችም ዕለት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሠላሳ ሰባተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ እንድራኒቆስ አረፈ። ይህ አባት የሚራራ አዋቂ ሆነ እርሱ የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ተምሮአልና እርሱም ለእስክንድርያው ገዥ የአጎቱ ልጅ ነው ከእርሱ በፊት የነበሩ ሊቃነ ጳጳሳት በገዳማት እንደሚኖሩ ስለ ቤቱና ስለ ክብሩ ታላቅነት በዘመኑ ሁሉ በገዳም የሚኖር አልሆነም በእስክንድርያ ከተማ ባለው ቤቱ የሚኖር ሆነ እንጂ።
ይህ አባት ሕርቃል በነገሠ በዐሥር ዓመት ከእስክንድር ዘመነ መንግሥት በዘጠኝ መቶ ሠላሳ ሦስት ዓመት ተሾመ በዘመኑም ፀሐይን የሚያመልክ የፋርስ ነጉሥ ክስራን ተነሣ ብዙ የሆኑ ሠራዊቱንም ሰበሰበ የሶርያንና የፍልስጥኤምን አገሮች ከበባቸውና ዘረፋቸው። ከዚህም በኋላ ግብጽን ከበባት ወደ እስክንድርያም ከተማ ደረሰ በዙሪያዋም ሰባት መቶ ገዳማት አሉ በውስጣቸውም መነኰሳትን የተመሉ ነበሩ እነርሱም ገንዘብ ያላቸው በተድላ የሚኖሩ ናቸው ስለዚህም በነርሱ ላይ እግዚአብሔር ሥልጣንን ሰጥቶት ገዳማቱን አፈረሰ እነርሱንም ገደላቸው ከእርሱ ሸሽተው ከአመለጡ ከጥቂቶች በቀር የተረፈ የለም ገንዘባቸውንም ሁሉ ማረከ።
የእስክንድርያ ሰዎችም ንጉሥ ክስራ ያደረገውን በሰሙ ጊዜ የከተማውን በር ከፈቱለት እርሱም ይቺን አገር በእጅህ አሳልፌ ሰጥቻታለሁ አታፍርሳት በውስጧ ያሉትን ብርቱዎች ግደላቸው ዓመፀኞች ናቸውና እንደሚለው በሕልሙ አየ ።በዚያንም ጊዜ የሀገሩን ንጉሥ አሠረው የሀገሩንም ሰዎች እንዲህ ብሎ ተናገራቸው ሀገሪቱን ይጠብቋት ዘንድ በጦር ሠራዊት አደራጃቸዋለሁና ዕድሜያቸው ከዐሥራ ስምንት እስከ ሠላሳ ዓመት የሆኑትን ወጣቶች ብርታት ያላቸው የአርባና የሃምሳ ዓመት የሆኑትን እንድትሰበስቡልኝ እኔም ለየአንዳዱ ደመወዙን ሃያ ሃያ የወርቅ ዲናር እሰጠዋለሁ አላቸው።
እነርሱም እውነት መሰላቸወ ከእርሱም ዘንድ ስምንት ሺህ ሰዎች ወጥተው የሁሉንም ቁጥራቸውን ምዝገባ ጀመሩ እነርሱ ግን ወርቅ የሚቀበሉ ይመስላቸው ነበር ምዝገባቸውም በተፈጸመ ጊዜ ሁሉንም በሰይፍ ገደላቸው ።
ከዚህም በኋላ ወደ ላይኛው ግብጽ ወጥቶ ወደ ኒቅዮስ ደረሰ በዚያም ገዳማት በውስጣቸው ሰባት መቶ ሥራቸው ክፉ የሆነ መነኰሳት በዋሻዎችና በቦታዎች ሁሉ እንዳሉ ሰማ እነርሱን ሁሉንም በሰይፍ ገደላቸው።
የሮም ንጉሥ ህርቃልም የፋርስ ንጉሥ ክስራ ያደረገውን በሰማ ጊዜ ሠራዊቱን ሰብስቦ ወደርሱ ሔደ የክስራን ሠራዊት ሁሉንም ገደለ ሀገሩንም አጠፋ። የዚህ አባት እንድራኒቆስ ገድል ግን እጅግ ያማረ ነበረ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ ከዓመተ ሰማዕታት ሦስት መቶ አርባ ሰባት እስላሞች በግብጽ ከመንገሣቸው በፊት በመንበረ ሢመቱም ሰባት ዓመት ኖረ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ብንያሚን_ሊቀ_ጳጳሳት
በዚህችም ዕለት የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚን አረፈ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሠላሳ ስምንተኛ ነው። ይህም አባት ከእስክንድርያ ባርስጥ ከምትባል መንደር ከሀገሪቱ ከበርቴዎች ወገን ነው ከእስክንድርያ ምዕራብ ከምትገኝ ገዳም ውስጥ ስሙ ቴዎናስ ከሚባል ከአንድ ቅዱስ ሰው ዘንድ ከታናሽነቱ ጀምሮ መነኰሰና የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ተማረ ሁልጊዜ በበጎ ሥራ ያድግ ነበር።
በአንዲት ሌሊትም ብንያሚን ሆይ ደስ ይበልህ በሃይማኖት በትር የክርስቶስን በጎች ትጠብቃቸዋለህና የሚለውን ራእይ አይቶ ለመምህሩ ነገረው። መምህሩም ሰይጣናት በትዕቢት እንዳያስቱህ ተጠበቅ አለው እርሱም በትሩፋቱ ላይ ትሩፋትን ጨመረ።
🔴#ስንክሳር ጥር_7
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ሰባት በዚች ቀን #በዓለ_ሥሉስ_ቅዱስ ሕንጻ ሰናዖርን ያፈረሱበትና ቅዳሴ ቤታቸው ነው፣ የከበረ አባት የሮሜ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ሶል_ጴጥሮስ አረፈ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#በዓለ_ሥሉስ_ቅዱስ
ጥር ሰባት በዚች ቀን በዓለ ሥላሴ የሚከበረው ስለ ሁለት ምክንያቶች ነው:: ቀዳሚው ሕንጻ ሰናዖርን ማፍረሳቸው ሲሆን ሌላው ደግሞ ቅዳሴ ቤታቸው ነው::
#ሕንጻ_ሰናዖር
ሰናዖር ከሺዎች ዓመታት በፊት በአሁኗ ኢራቅ አካባቢ እንደ ነበረ የሚነገርለት ግዛት ሲሆን ስሙ ለሃገሪቱም: ለንጉሡም በተመሳሳይ ያገለግል ነበር:: ከናምሩድ ክፋት በሁዋላ ሰናዖርና ወገኖቹ ከሰይጣን ተወዳጁ::
ከጥፋት ውሃ (ከኖኅ ዕረፍት) በሁዋላ በሥፍራው በአንድነት ይኖሩ ነበርና እርስ በርሳቸው "ኑ ሳንበተን ስማችን የሚጠራበትን ሕንጻ እንሥራ:: በዚያውም አባቶቻችን በውሃ ያጠፋ እግዚአብሔርን እንውጋው" ተባባሉ::
ቀጥለውም ሰማይ ጠቀስ ፎቅን ገነቡ:: ከሕንጻው መርዘም የተነሳ በጸሐይ አብስለው በልተዋል ይባላል:: ቀጥለውም ጦር እያነሱ ፈጣሪን ሊወጉ ወርውረዋል::
መቼም የእነዚህን ሰዎች ክፋትና ቂልነት ስንሰማ ይገርመን ይሆናል:: ግንኮ ዛሬ ሰለጠንኩ በሚለው ዓለም እየተሠራ ያለው ከዚህ የከፋ ነው:: ቸርነቱ ቢጠብቀን እንጂ እንደ ክፋታችንስ ጠፊ ነበርን::
ርሕሩሐን ሥላሴ ግን የሰናዖር ሰዎች የሠሩትን አይተው ማጥፋት ሲችሉ አላደረጉትም:: የባሪያቸውን የኖኅን ቃል ኪዳን አስበዋልና:: ይልቁኑ "ንዑ ንረድ ወንክአው ነገሮሙ ለከለዳውያን-ቁዋንቁዋቸው እንደባልቀው" አሉ እንጂ::
ከለዳውያን ልሳናቸው ተደበላልቆ 71 ቁዋንቁዎች ተፈጠሩ:: እነርሱም ስምምነት አጥተው ተበተኑ:: ሥላሴም ያን ሕንጻ በነፋስ ትቢያ እንዲሆን በተኑት:: ስለዚህም እስከ ዛሬ ሥፍራው "ባቢሎን (ዝሩት)" ሲባል ይኖራል::
#ቅዳሴ_ቤት
ልክ የዛሬ 324 ዓመት አድያም ሰገድ ኢያሱ በኢትዮዽያ በነገሡ በ10ኛው ዓመት (በ1684 ዓ.ም) በጐንደር ከተማ ንግሥተ አድባራት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተሰርታ ተጠናቃለች::
ጥር 7 ቀንም ሊቁ ክፍለ ዮሐንስን ጨምሮ በርካታ ምዕመናን: ሠራዊት: መሣፍንትና ሊቃውንት ባሉበት ቅዳሴ ቤታቸው ተከብሯል:: በዕለቱም ታላቅ ሐሴት ተደርጉዋል:: ኢያሱ አድያም ሰገድ ኃያል: ደግ: ጥበበኛ: አስተዋይ: መናኝ ንጉሥ ነውና::
ቤተ ሥላሴን አስጊጿታልና ከዚህ ቀን ጀምሮ ጥር ሥላሴ በድምቀት የሚከበር ሆኗል:: ነገር ግን በተሠራች በ16 ዓመቷ ደጉ ኢያሱ ከተገደለ በሁዋላ ቤተ ክርስቲያኑ በአደጋ ፈርሷል:: ዛሬ የምናየው በ1708 ዓ.ም በልጁ በአፄ ዳዊት ሣልሳዊ የታነጸውን ነው::
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሶል_ዼጥሮስ
ዳግመኛም በዚህች ቀን የከበረ አባት የሮሜ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት ሶል ጴጥሮስ አረፈ። ይህንንም አባት ስለ ተጋድሎው ገናናነት ስለ አገልግሎቱም ስለ ትሩፋቱ ስለ አዋቂነቱና ስለ ደግነቱ ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ መልጥያኖስ ከአረፈ በኋላ መርጠው ሊቀ ጵጵስና በሮሜ ሀገር ላይ ሾሙት። በሐዋርያት አለቃ በጴጥሮስ ወንበር በተቀመጠ ጊዜ የዕሌኒ ልጅ የሆነ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስን የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው ከከሀድያን ጋር ስለሚያደርገው ጦርነት ምክንያት ገና አልተጠመቀም ነበርና የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሶ የእግዚአብሔርን አብያተ ክርስቲያናት ሠራቸው።
የዚህም አባት የሶል ጴጥሮስ ገድሉ እጅግ ብሩህ የሆነ ነው እርሱ ሁል ጊዜ ሕዝቡን ያስተምራቸዋልና ከልቡናቸውም ከሰይጣን የሆነ ጥርጥርንና ክፉ ሐሳብን ያርቃል። ከእነርሳቸው ሥውር የሆነውንም የመጻሕፍት ምሥጢር ተርጕሞ ያስገነዝባቸዋል። አይሁድንና ዮናናውያንን ሁል ጊዜ ይከራከራቸው ነበር ከእርሳቸውም ብዙዎችን መልሶ ወደ ቀናች ሃይማኖት አስገባቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ስሙም በምእመናን ዘንድ ፈጽሞ የሚያስፈራ ሆነ።
እግዚአብሔርን ስለ ማወቅና ስለ ወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ብዙ ድርሳናትን ደረሰ። በተሾመ በሰባተኛውም ዓመት ስለ አርዮስ በኒቅያ ከተማ ሃይማኖታቸው የቀና የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት የከበሩ አባቶች የአንድነት ስብሰባ ሆነ ይህም አባት ሶል ጴጥሮስ ከእርሳቸው አንዱ ነበር አርዮስንም ከተከታዮቹ ጋር ረገመው አውግዞም ለየው።
በሹመቱም ዐሥራ አንድ ዓመት ኖረ መልካም ተጋድሎውን ፈጽሞ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ለሰ/ት/ቤታችን የጥምቀት ዘማርያን በሙሉ የመጨረሻው የጥምቀት መዝሙር ጥናት ዛሬና ነገ ማለትም በ06/05/2015 እና 07/05/2015 ሲሆን መልክቶች የሚተላለፈውና ሰልፍ ምናየውም በዚሁ ቀን በመሆኑ በተቻለ አቅም ዘማርያን የሆናችሁ በመዝሙር ጥናቱ ላይ እንድትገኙ ይሁን ሠላመ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሰማዕት_ቅድስት_አርሴማ
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የታላቋ ሰማዕት የቅድስት አርሴማ ልደቷ ነው፡፡ የቅዱስት አርሴማ አባቷ ቴዎድሮስ ከሌዋውያንና ከኃያላን ነገሥታት ወገን ሲሆን እናቷ አትኖስያ ደግሞ ከጳጳሳት አለቆች ወገን ናት፡፡ ወላጆቿ በሃይማኖት በምግባር ያጌጡ በበጎ ትሩፋት የተመሰገኑ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ በጾም፣ በጾሎት፣ በምጽዋትና ዓሥራት በኩራትን በማውጣት በመንፈሳዊ ሥራ ሁሉ እየተጉ ቢኖሩም ነገር ግን እስክ እርጅናቸው ዘመን ድረስ ልጅ ስላልነበራቸው ያዝኑ ነበር፡፡ እናቷ ቅድስት አትኖስያ እንደ ነቢዩ ሳሙኤል እናት ሐና ጠዋት ማታ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ በእግዚአብሔር ፊት ታለቅስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር የልቧን ፈቃድ ይፈጽምላት ዘንድ ወደደና የቂሣርያውን ሊቀ ጳጳሳት ልድዮስን ስለ እርሷ ይጸልይላት ዘንድ አዘዘው፡፡
ሊቀ ጳጳሳቱም ስለ ቅድስት አትኖስያ ጸለየላት፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የሊቀ ጳጳሳቱንና የቅድስት አትኖስያን ጸሎት ሰምቶ መልኳ እጅግ ያማረችን ሴት ልጅ ቅድስት አርሴማን ሰጣት፡፡ እናቷም እየተንከባከበች አሳድጋት ዕድሜዋ ከፍ ሲል አምላክን በወለደች በእመቤታችን ስም ወደተሠራች ቤተ ክርስቲያን ታገለግል ዘንድ ሰጠቻት፡፡ ቅድስት አርሴማ ወጣት በሆነች ጊዜ ወላጆቿ ባል ያጋቧት ዘንድ ወደዱ ነገር እርሷ ይህንን ፈጽሞ አልወደደችምና ወላጆቿን "እኔ የሰማያዊው የክርስቶስ ሙሽራ ነኝ እንጂ ምድራዊ ሙሽራ አይደለሁም" አለቻቸው፡፡
ቅድስት አርሴማ ከእርሷ በፊትም ሆነ ከእርሷ በኋላ በመልክና በውበት የሚመስላት የለም፡፡ ይህን ዓለም እንደትቢያ በመቁጠርና ፍጹም በመናቅ ጌታችንን ከተከተሉት ቅዱሳት ደናግል አንስት ውስጥ በመልክና በውበት ቅድስት አርሴማን የሚመስል የለም፡፡ አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን በቀር የሚበልጣት ማንም የለም፡፡ እርሷም በምግባር በሃይማኖት ያጌጠች በመንፈሳዊ ተጋድሎ የበረታች በትሩፋት የበለጸገች ናት፡፡ ብሉይን ከሐዲስ አጠናቃ ተማረች፡፡ የአገሮችንም (የሮምያን፣ የጽርዕን፣ የሶርያን፣ የኪልቅያን) ቋንቋዎች ታውቅ ስለነበር ቅዱሳት መጻሕፍትንም ወደ ተለያዩ አገራት ቋንቋዎች ትተረጉማለች፡፡
ቅድስት አርሴማ 15 ዓመት በሆናት ጊዜ ከሃዲውን ዲዮቅልጥያኖስን ሰይጣን አስነሥቶት ነገሠ፡፡ ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን እርሱ መልኳ ውብ የሆነ ብላቴና ድንግል ሊአገባ ሽቶ በየሀገሩ ሁሉ ሒደው መርጠው ያመጡለት ዘንድ አሽከሮቹን አዘዘ። ይችንም የሚመስላት የሌለ ቅድስት አርሴማን በሮሜ አገር በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ አገኙዋት። ሥዕሏንም ሥለው ለንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ላኩለት ንጉሡም ሥዕሏን በአየ ጊዜ እጅግ ደስ አለውና ለሠርግ እንዲመጡ ወደ መኳንንቱ ላከ።
እሊያ ደናግልም ይህን ነገር በአወቁ ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ ድንግልናቸውንም ይጠብቅ ዘንድ አልቅሰው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ። ከዚህም በኋላ ተነሥተው በሥውር ሸሹ የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደ ሆነ ወደ አርማንያ ሀገርም ደርሰው በአንድ ቦታ ተቀመጡ ከእርሳቸውም ጋር የተሰደዱ ቁጥራቸው ሰባ አምስት የሆነ ወንዶች፣ ሴቶችም ሠላሳ ዘጠኝ የሆኑ ከእርሳቸው ጋራ አሉ። ምግባቸውን አያገኙም ነበርና በታላቅ ችግር ውስጥ ኖሩ ከእነርሱም መብራት የምትሠራ አንዲት ሴት ነበረች ከእርሷም የእጅ ሥራ ከሚገኘው በየጥቂቱ ይመገባሉ።
ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም የከበረች አርሴማን በፈለጋት ጊዜ አላገኛትም ግን በአርማንያ አገር እንዳለች ስለርሷ ሰማ። ደግሞ ለአርማንያ ንጉሥ ለድርጣድስ ስለርሷ ከዲዮቅልጥያኖስ ሸሽታ እንደ መጣች የአርሴማን ሥራ ነገሩት እርሱም አንዱን የአርማንያ መኰንን ለእኔ ጠብቃት ወደ እኔም ላካት ብሎ አዘዘው።
ደናግሉም ይህን በሰሙ ጊዜ ወደ ሌላ ቦታ ተሠወሩ ወደ ንጉሥም ወነጀሉአቸው ንጉሡም ቅዱስት አርሴማን በክብር አድርገው ያመጧት ዘንድ አዘዘ እርሷም ወደ እርሱ መምጣትን እምቢ በአለች ጊዜ እየጎተቱ ወስደው ወደርሱ አደረሷት።
የቅድስት አርሴማንም ላህይና ደም ግባቷን በአየ ጊዜ ድንግልናዋን ሊያረክስ ሽቶ እናቷ አጋታን አባብላ እሺ ታሰኝለት ዘንድ አዘዛት አጋታም ወደርሷ ሒዳ ልቧን አስጨከነች እንዲህም አለቻት። ዕወቂ ይህ ርኲስ አረሚ እንዳያረክስሽና ሰማያዊ ሙሽራሽን እንዳትተዪ እርሱም ክብር ይግባውና የእግዚአብሔር ልጅ ሕያው ክርስቶስ ነው።
ንጉሡም ይዞ ወደ እልፍኙ ሊአስገባት ከአደባባይ መካከል ተነሥቶ ድንግል አርሴማን ያዛት። በዚያንም ጊዜ በቅድስት አርሴማ ላይ የእግዚአብሔር ኃይል አደረባትና በምድር ላይ ጣለችው እርሱ ግን በጦርነት እጅግ የጸና አርበኛ ስለ ነበር በታናሽ ሴት ብላቴና ስለተሸነፈ ያን ጊዜ አፈረ። ራሷንም በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጧት ከዚህም በኋላ ደናግሉን ሁሉ ከእናታቸው አጋታ ጋር ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ።
አንዲት የታመመች ድንግል ነበረች በዐልጋዋ ላይም እንደተኛች ወደ ወታደሮች ጮኸች መጥተውም እንደ እኅቶቿ ራሷን ቆረጡ ሁሉም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ እነዚያንም ከሮሜ አገር አብረው የመጡ ወንዶችን ገደሏቸው ቁጥራቸውም ሰባ አምስት ናቸው ሥጋቸውም በተራራ ላይ የተጣለ ሁኖ ቀረ።
ሰማዕታትም ከተገደሉ በኋላ በንጉሡ ላይ ጋኔን ተጫነበት መልኩም ተለውጦ እንደ እርያ ሆነ። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ወደርሱ መጥቶ በላዩ ጸልዮ እስከ አዳነው ድረስ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። የቅዱሳን ሰማዕታትንም ሥጋቸውን ከተጣለበት ሰብስበው በአማረ ቦታ አኖሩአቸው ያማረች ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንም ተሠራችላቸው። ከእነርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። በዚህችም ቀን ልደቷ ተከብሮ ይዉላል፡፡
ለእርሱም ለጌታችን ከቸር አባቱ ጋራ ማሕየዊ ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋራ ክብር ምስጋና ስግደትም ይሁን፤ እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ኤልያስም ሕዝቡን የእግዚአብሔር ነቢይ እኔ ብቻዬን ቀርቻለሁ የጣዖቱ ነቢያት አራት መቶ ሃምሣ በዛፉም መስገጃ የተሾሙት እነሆ አራት መቶ ናቸው። ሁለት ወይፈኖችንም ይስጡን እነርሳቸውም አንዱን መርጠው አርደው በየብልቱ አወራርደው በዕንጨቶቹ ላይ ይከምሩት እሳትን ግን አያንድዱ። እኔም ሁለተኛውን ወይፈን አርዳለሁ እሳትንም አላነድም እነርሱም የጣዖቶቻቸውን ስም ይጥሩ እኔም የፈጣሪዬን የእግዚአብሔርን ስም እጠራለሁ ከእርሱም እሳትን ከሰማይ ያወረደ ፈጣሪ ነው አላቸው ሕዝቡም መልካም ቃል ተናገርክ ብለው መለሱለት።
እነርሱም የመረጡትን በሬ ለአማልክቶቻቸው አስቀድመው መሥዋትነትን አቀረቡ ግን የተቀበላቸው የለም ኤልያስም መሥዋዕቱን በአቀረበ ጊዜ ከእግዚአብሔር ታዝዛ እሳት ከሰማይ ወርዳ መሥዋዕቱን ዕንጨቱን በጒድጓድ ያለ ውኃውንም አቃጠላቸው መሬቱንም ላሰችው።
ኤልያስም ሕዝቡን እንዲህ አላቸው ጣዖቱን የሚያገለግሉ ነቢያተ ሐሰትን ያዝዋቸው ከእነርሱም የሚያመልጣችሁ አይኑር አላቸው ሕዝቡም ነቢያተ ሐሰትን ያዙ ኤልያስም ቂሶን ወደ ሚባል ወንዝ አውርዶ እየወጋ ጣላቸው። ከዚህም በኋላ ዝናብ ዘነበላቸው ደስ ብሏቸውም ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት።
አክአብም ለሚስቱ ኤልዛቤል ኤልያስ ያደረገውን ሁሉ አሳፋሪዎች ነቢያቶችንም በጦር ወግቶ እንደ ገደላቸው ነገራት ባልኖርባት አንተ ኤልያስ ኑረህባት አንተ ባትኖርባት እኔ ኤልዛቤል ኑሬባት ነገ ይህን ጊዜ ሰውነትህን ከነሳቸው እንዳዱ ሰውነት ባላደርጋት የያዘችውን ጥላ አማልክቶቼ እንዲህ ይጣሉኝ እንዲህም ይግደሉኝ ብላ ወደ ኤልያስ ላከች።
ስለዚህም ኤልያስ እጅግ አዝኖ እንዲህ አለ አቤቱ ነቢያቶችህን ገደሉ መሠዊያዎችህንም አፈረሱ እኔም ብቻዬን ቀርቻለሁ ነፍሴንም ሊገድሏት ይሿታል። እግዚአብሔርም ለጣዖት ያልሰገዱ ለኔ ሰባት ሽህ ሰዎችን አስቀርቻለሁና አትፍራ ያንተንም ነፍስ ማንም ሊወስዳት የሚችል የለም። ነገር ግን በሥጋህ ሕያው እንደሆንክ ወደ ሰማይ አወጣሃለሁ አለው።
አክአብም ከሞተ በኋላ የሞአብ ሰዎች አመፁ አካዝያስም ታሞ በሰማርያ ባለ እልፍኝ ተኛ ከዚች በሽታዬ እድን እሞትም እንደሆነ ወደ አቃሮን ጣዖት ወደ ዝንቡ ካህን ሔዳችሁ ጠይቁልኝ ብሎ መልክተኞችን ላከ እነርሱም ሊጠይቁለት ሔዱ።
ነቢዩ ኤልያስም መልክተኞቹን በዚህ ደዌ እንደምትሞት ዕወቅ ብላችሁ ለንጉሣችሁ ንገሩት አላቸው። ንጉሡም ኤልያስ እንደሆነ ዐውቆ ይጠሩት ዘንድ ከኃምሳ ወታደሮች ጋር የኃምሣ አለቃውን ላከ ሔደውም በተራራው ራስ ተቀምጦ አገኙት አለቃውም ነቢየ እግዚአብሔር ሆይ ንጉሥ ይጠራሃል ፈጥነህ ውረድ ና አለው ኤልያስም የእግዚአብሔር ነቢይ ከሆንኩ እሳት ከሰማይ ወርዳ አንተንና ወገኖችህን ታቃጥላችሁ አለው እሳትም ወርዳ እርሱንና ኃምሳውን ወታደሮች አቃጠለቻቸው።
ንጉሡም ዳግመኛ ከአለቃቸው ጋራ ኃምሳ ሰዎችን ወደርሱ ላከ አለቃቸውም የእግዚአብሔር ነቢይ ንጉሥ ይጠራሃልና ፈጥነህ ውረድ አለው ኤልያስም እኔ የእግዚአብሔር ነቢይ ከሆንኩ እሳት ከሰማይ ወርዳ ታቃጥልህ ከአንተ ጋር ያሉትን ኃምሳውንም አለው እሳትም ከሰማይ ወርዳ አቃጠለቻቸው።
ከዚህም በኋላ ንጉሡ ሦስተኛ የኃምሣ አለቃ ላከ እርሱ ግን ወደ ነቢዩ ኤልያስ በትሕትና መጥቶ ሰገደለት የእግዚአብሔር ነቢይ ሆይ ተገዛሁልህ ሰውነቴ በፊትህ ትክበር የእነዚህም የባሮችህ ሰውነት ትክበር አለው። ኤልያስም ተነሥቶ ወረደ ከእሳቸውም ጋር ወደ ንጉሡ ሔደ ንገሡንም እንዲህ ብሎ ተናገረው እግዚአብሔር እንዲህ አለ ቃልን ከጣዖት ትጠይቅ ዘንድ የእስራኤል ፈጣሪ የለምን ወደ አቃሮን ጣዖት ወደ ዝንቡ ካህን እንዴት ላክህ ነገሩ እንዲህ አይደለም በዚያ ሞትን ትሞታለህ እንጂ ከተኛህበት መኝታህ አትነሣም አለው ወዲያውኑ ሞተ።
ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ኤልያስን ወደ ሰማይ በሚያወጣበት ጊዜ ኤልሳዕና ኤልያስ ከገልገላ ተነሥተው ሔደው ወደ ዮርዳኖስ ደረሱ ኤልያስም መጠምጠሚያውን አውርዶ ጠቅሎ የዮርዳኖስን ውኃ መታበት ውኃውም ተከፍሎ ወዲያና ወዲህ ቆመ ሁለቱም ሁሉ በደረቅ ተሻገሩ ወጥተውም በምድር በዳ ቆሙ።
ኤልያስ ኤልሳዕን ካንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ሳልወጣ አደርግልህ ዘንድ የምትሻውን ለምነኝ አለው ኤልሳዕም ኤልያስን በአንተ ያደረ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ዕጥፍ ሁኖ የደርብኝ አለው።
ኤልያስም ኤልሳዕን ድንቅ ነገርን ለመንከኝ ነገር ግን ካንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ሳርግ ብታየኝ ይሁንልሀ ባታየኝ ግን አይሆንልህም አለው። በዚያንም ጊዜ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረስ መጣ ወደ መካከላቸውም ገብቶ አራራቃቸው ኤልያስም እንደዚህ በንውጽውጽታና በጥቅል ነፋስ ወደ ሰማይ ዐረገ። ኤልሳዕም አይቶ የእስራኤል ኃይላቸውና ጽናታቸው አባ አባ ብሎ ጮኸ ከዚህ በኋላ ዳግመኛ አላየውም ልብሶቹንም ለሁለት አድርጎ ከፈላቸው ኤልያስም ለኤልሳዕ መጠምጠሚያውን ጣለለት በኤልሳዕም ራስ ላይ ወረደ የኤልያስም ሀብተ መንፈስ ቅዱስ በኤልሳዕ ላይ ዕጥፍ ሁኖ አደረ ኤልያስም የሠራውን ተአምራት ኤልሳዕ ዕጥፍ አድርጎ ሠራ።
ይህም ኤልያስ በኋላ ዘመን ከኄኖክ ጋር ይመጣ ዘንድ አለው ሐሳዊ መሢሕንም ይቃወሙታል እርሱም ይገድላቸዋል በድናቸውም በአደባባይ ተጥሎ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት ይቆያል ከዚህም በኋላ ይነሣሉ የሙታን ትንሣኤም ይሆናል ይህም ኤልያስ ዕውነተኛ ነቢይ አስቀድሞ የነበረ በኋላም የሚገለጽ ነው በብሉይ ዘመንም ኑሮው በበረሀ ውስጥ ነበር።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ጥር_6
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ስድስት በዚህች ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ #በዓለ_ግዝረቱ ነው፣የአባታችን #የጻድቁ_ኖኅ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #ነቢዩ_ኤልያስ በሕይወት ሳለ በሥጋ በእሳት ሠረገላ ወደ ሰማይ ያረገበት፣ #ታላቁ_ቅዱስ_ባስልዮስ_ዘቂሣርያ አረፈ፣ የታላቋ ሰማዕት #ቅድስት_አርሴማ ልደቷ ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#በዓለ_ግዝረቱ_ለክርስቶስ
ጥር ስድስት በህዚች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ ግዝረት በመግባት የኦሪትን ሕግ ፈጸመ ልሳነ ዕፍረት ሐዋርያው ጳውሎስ ጌታ ክርስቶስ በሥጋው ግዝረትን ተቀበለ ለአባቶች የተሰጠውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ ብሎ እንደተናገረ።
ለብዙዎችም ጌታችን ወደ ቤተ ግዝረት እንዳልገባና እንዳልተገረዘ ይመስላቸው ነበር እነርሱ እንዳሰቡት ሁኖ ቢሆን ኑሮ አይሁድ ታላቅ ምክንያትን የሚያገኙ በሆኑ ነበር ጌታችን ግን የግዝረትን ሕግ ፈጸመ ለእኛ በግዝረት ፈንታ የክርስትና ጥምቀትን ሰጠን የፋሲካውንም ቂጣ በላ በእርሱም ፈንታ ሥጋውንና ደሙን ሰጠን።
የከበረ ወንጌል ስምንተኛው ቀን በተፈጸመ ጊዜም ሕፃኑን ሊገዝሩት ወሰዱት ሳትፀንሰው መልአኩ እንዳወጣለት ስሙን ኢየሱስ አሉት እንዳለ ንጽሕት ድንግል እመቤታችን ማርያም ጻድቅ አረጋዊ ዮሴፍን እንደ ሕጉ ልጄን እንዲገርዘውና ስሙንም እንድንሰይመው ብልህ የሆነ ገራዥ ሰው አምጣልኝ አለችው። ዮሴፍም ሔዶ የሚገርዝ ባለሙያ አመጣ ያ ባለሙያም ሕፃኑን ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በእናቱ በንጽሕት ድንግል ማርያም ክንድ ላይ አየው እንድገርዘው ሕፃኑን በጥንቃቄ ያዙት አላቸው።
ሕፃን ጌታ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው ባለሙያ ገራዥ ሆይ ደሜ ሳይፈስ ትገርዘኝ ዘንድ ትችላለህን በዚያች ዕለት ካልሆነ በቀር ደሜ አይፈስምና ጐኔን በጦር ሲወጉኝ ያን ጊዜ ውኃና ደም ይፈሳል ለአዳምና ለሚያምኑ ልጆቹ መድኃኒት ይሆናል።
የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረውን ያ ባለሙያ በሰማ ጊዜ አደነቀ ዕቃውንም ሰብስቦ ተነሥቶ ከሕፃኑ ጌታ እግር በታች ሰገደ ያንጊዜም ምላጮቹ በእጆቹ ላይ ቀልጠው እንደ ውኃ ሆኑ የከበረች ድንግል እመቤታችንን ማርያምን ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ የማሕፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው ይህ ልጅሽ ስለርሱ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የሕያው አምላክ ልጅ ነው አላት።
ሕፃኑም ለዚያ ባለሙያ ዳግመኛ መልሶ እንዲህ አለው እኔ ነኝ ትገዝረኛለህን ወይስ ተውክ ወይም ያባቶቼ አባቶች እንዳደረጉ እኔ ላድርግ ያም ባለሙያ የአባቶችህ አባቶች እነማን ናቸው አለው ሕፃን ጌታችንም አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብ የሕዝቡ ሁሉ አባቶች የሆኑ ናቸው ለእነርሱም ይህ ግዝረት አስቀድሞ ከአባቴ ዘንድ ተሰጣቸው ባለሙያውም እኔ ከአንተ ጋር እናገር ዘንድ አልችልም በአንተ ህልውና መንፈስ ቅዱስ አለና አለው።
በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ ጌታችን ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ አባት ሆይ ለአብርሃም ለይስሐቅ ለያዕቆብ አስቀድሞ ግዝረትን የሰጠሃቸው ያቺን ግዝረት ዛሬ ለእኔ ስጠኝ አለ። ያን ጊዜ ያለ ሰው እጅ በሕፃኑ ሥጋ ላይ ግዝረት ተገለጠች። ድንግልናዋ ሳይለወጥ ከድንግል ማሕፀን እንደ መውጣቱ የጌታችን ግዝረቱ የማይመረመር ሆነ እንዲሁ ወደ ሐዋርያት በተዘጋ አዳራሽ መግባቱና መውጣቱ እንደማይመረመር እንዲሁ እንደ ፈቀደ ከረቀቀ ጥበቡ ችሎታውን በመገረዝ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቆረጥ ገለጠ።
አዳምንና ልጆቹን ያድናቸው ዘንድ በፈቃዱ ከጐኑ በመስቀል ላይ የሚፈሰው ደምና ውኃ ካልሆነ በቀር ብዙም ሆነ ጥቂት ሊሆን አይችልም እርሱ በፈቃዱ ሕጉ እንዲፈጸም አስቀድሞ አዘዘ እንጂ።
ያም ባለሙያው ገራዥ ይህን ተአምር ባየ ጊዜ የሕፃኑንም ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አደነቀ የክብር ባለቤት ከሆነ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር በታች ሦስት ጊዜ ሰገደና በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ የእስራኤልም ንጉሥ ነህ አለው። ከዚህም በኋላ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተአምራቱ ያየውንና የሰማውን እየተናገረ ወደ ቦታው ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ኖኅ_ጻድቅ
በዚህችም ቀን ዳግመኛ የአባታችን የኖኅ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው እርሱም ከአባታችን አዳም ዐሥረኛ ትውልድ ነው። እርሱም ከታናሽነቱ ጀምሮ ኃጢአት እንደሚበዛ ክፋትም እንደሚመላ ደጋጎች እንደሚያንሱ ሥጋ የለበሰ ሁሉ በጥፋት ውኃ እንደሚደመሰስ አምላካዊ ምሥጢርን የሚያይ ሆነ ስለዚህም ፊቱ የተቋጠረ ሁኖ ፈጽሞ ያለቅስ ነበር።
አምስት መቶ ዓመትም ድንግልናውን ጠብቆ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ለአባታችን አዳም ሥጋ ሲያገለግል ኖረ ከዚህም በኋላ ሚስት እንዲያገባ ጌታ አዘዘው ሥጋ የለበሰ ሁሉ እንደሚደመሰስ ከርሱ ዘር በቀር የሚተርፍ እንደሌለ ነገረው። የአቡዚር ልጅ የሆነች ሐይከል የምትባል ሴት አገባ ወደርሷም ሦስት ጊዜ ገባ ሴምን ካምን ያፌትን ወለዳቸው።
ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን እንዲህ አለው ከዚህ ከደብር ቅዱስ ዕንጨቶችን ቊረጥ አራት ማእዘን አድርገህ ላንተ መርከብን ሥራ ውጭዋንና ውስጧንም የደሮ ማርና ሙጫ ለቅልቃት አለው። አቈልቋይዋን ሦስት መቶ ወርዷን ኃምሳ ቊመቷን ሠላሳ ክንድ አድርገህ ሥራት አለው።
ለዚያችም መርከብ መስኮት አውጣላት አንዲት ክንድ ስትቀር ለመጨረስም በደረሰች ጊዜ በዚያ የጐን ደጃፍ አውጣላት የአደራሽነትዋ እርከንን ሥራላት ሦስት ክፍል አድርገህ ሥራት። የመጀመሪያው ክፍል ለአራዊትና ለእንስሳ ይሁን ሁለተኛው ክፍል ለአዕዋፍና ለተንቀሳቃሽ ሁሉ ይሁን ሦስተኛውም ክፍል ለአንተና ለልጆችህ ከሚስቶቻቸው ጋር ይሁን።
ሁለተኛም እንዲህ አለው ከሚመገቧቸው መብሎች ሁሉ አስገባ ባንተ ዘንድ አኑር ላንተ ለአውሬዎችም ለእንስሶችም ሁሉ ምግብ ይሆንልሃል። ከዚህም በኋላ ኖኅ ርዝመቱ ሦስት ክንድ ጒኑ አንድ ክንድ ተኩል የሆነ የዕንጨት ደወል ሦስት ጊዜ የሚደውልበትን ሠራ በመጀመሪያ ለሥራ እንዲሰበሰቡ ሁለተኛው ለመብል ሲሆን ሦስተኛው ለዕረፍት ነው።
ከጥፋት ውኃ ስለመዳን መርከብን ሲሠራ የቃየል ልጆች ኖኅን አይተው ዘበቱበት እንዲህም አሉ ይህ ሽማግሌ አብዷል ውኃዎች ወደ ተራራዎች ራስ ይወጣሉ እንዴት ይለናል። ከዚህም በኋላ ኖኅ የአባታችን አዳምን ሥጋ ወሰደ ሤም ወርቁን ካም ከርቤውን ያፌት ዕጣኑን ወስደው ወደ መርከብ አስገቡ።
ኖኅም ወደ መርከብ ገባ ሚስቱ ልጆቹና የልጆቹ ሚስቶች ከጥፋት ውኃ ለመዳን ከርሱ ጋር ገቡ። ከንጹሐን እንስሳትና አዕዋፍ ተባዕትና እንስት ሰባት ሰባት ንጹሐን ካልሆኑ እንስሳትም ሁለት ሁለት ሴትና ወንድ አስገባ።
ከዚህም በዚያች ቀን ምንጮች ሁሉ ተነደሉ የሰማይም መስኮት ተከፈተ። በምድር ላይ አርባ ቀን አርባ ሌሊት ዝናም ሆነ ውኃውም ሞልቶ መርከቢቱን አንሳፈፋት ምድርንም ለቀቀች።
ውኃውም በምድር ላይ እጅግ በዛ ከሰማይ በታች ያሉትን ረጃጅም ተራራዎችን ሸፈነ። ውኃውም በላያቸው ዐሥራ አምስት ክንድ ያህል ከፍ ከፍ አለ ሥጋ የለበሰ ሁሉ ከአዕዋፍ ከእንስሳ ከምድር አራዊት ሁሉ በምድር የሚኖርና ሰውም ሁሉ ሞተ።
ውኃውም በምድር ላይ መቶ ሃምሳ ቀን አየለ እግዚአብሔርም ኖኅን አሰበው ከእርሱ ጋር በመርከብ ውስጥ ያሉትን እንስሶች ሁሉ ነፋስንም በምድር ላይ አመጣ ውኃውም ጐደለ። የቀላይ ምንጮች ተደፈኑ የሰማይም መስኮት ተዘጋ ከሰማይ የሚወርደውም ዝናም ቆመ ውኃውም እያለቀ ከምድር ይሸሽ ጀመር ከመቶ ኃምሳ ቀንም በኋላ ውኃው ጎደለ።
Вже доступно! Дослідження Telegram за 2025 — головні інсайти року 
