uk
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Відкрити в Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Показати більше
2 640
Підписники
+124 години
+47 днів
+6130 день
Архів дописів
ሕፃኑም በማሕፀኗ እያለ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሰላምታ በሰጠቻት ጊዜ እንዲህ ብላ ጮኸች "ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ የማኅፀንሽም ፍሬ ቡሩክ ነው። የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጪ ዘንድ እኔ ምንድን ነኝ እነሆ እንዴት ነሽ ስትይኝ የሰላምታሽን ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ልጁ በማሕፀኔ ውስጥ በደስታ ዘለለ። ከዚህም በኋላ ጌታችንን አየችው በአምላክነቱም አመነች የሚያምኑበትም በመዳናቸው ደስ አላት ዕድሜዋንም በፈጸመች ጊዜ በበረሀ ውስጥ ሳለች አረፈች። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት፣ #መዝገበ_ቅዱሳን እና #ከገድላት_አንደበት)

🔴 ስንክሳር #የካቲት_16 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ ስድስት በዚችም ዕለት የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም አማላክን ለወለደች #ለእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም በዓልን ያደርጋሉ፣ የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች #ቅድስት_ኤልሳቤጥ አረፈች፣ ጻድቁ ንጉሥ #አፄ_ገብረ_ማርያም የእረፍት ቀናቸው ነው ፣ የጻድቅና #ቅዱስ_ንጉሥ_ነዓኩቶ_ለአብ መታሰቢያው ነው፣ #አቡነ_መልከ_ጼዴቅ ዘሚዳ ልደታቸው ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ኪዳነ_ምሕረት (#የሰባቱ_ኪዳናት_ማሕተም) የካቲት ዐሥራ ስድስት በዚችም ዕለት የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም አማላክን ለወለደች ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓልን ያደርጋሉ። በዚች ዕለት መታሰቢያዋን ለሚያደርግ ስሟን ለሚጠራ ለድኆችና ለችግረኞች እስከ ቀዝቃዛ ውኃ ለሚሰጥ የክብር ባለቤት ከሆነ ከተወደደ ልጅዋ ከጌታችንና ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳንን ተቀብላለችና። ይህችም የከበረች እመቤታችን ልጅዋ ንጹሕ ሥጋዋን ተዋሕዶ ከብቻዋ ኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ፈጽሞ ስለእኛ መዳን ወዶ ያደረገውን መከራ ተቀብሎ ሙቶ ተነሥቶ ከዐረገና በአባቱ ዕሪና ከተቀመጠ በኋላ እርሷን እናቱን ማርያምን በደቀ መዝሙሩ ዮሐንስ ዘንድ ትቷት ነበር እነሆ ልጅሽ እርሱንም እነሆዋት እናትህ ብሎ አደራ እንዳስጠበቀው። ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ማርያም ትጸልይ ዘንድ ያለ ማቋረጥ ወደ ልጅዋ መቃብር ሁል ጊዜ ስትሔድ ኖረች ይኸውም ጎልጎታ ነው። አይሁድም በአዩዋት ጊዜ ቍጣንና ቅናትን ተመልተው በድንጊያ ሊወግሩዋት ወደዱ እግዚአብሔርም ከዓይናቸው ሠወራት ከዚህም በኋላ ዳግመኛ መጥታ በዚያ እንዳትጸልይ ተማክረው ከመቃብሩ ዘንድ ጠባቂዎችን አኖሩ እርሷ ግን በየዕለቱ መሔድን አላቋረጠችም ጠባቆችም አያይዋትም የልጅዋ የጌትነቱ መጋረጃ ሠውርዋታልና መላእክትም መጥተው ያገለግሏታል ጌታችንም ዘወትር ይጐበኛታል የምትሻውንም ይፈጽምላት ነበር። ከዚህም በኋላ መላእክት ወደ ሰማይ አሳረጓትና የጻድቃንን ማደሪያዎች አሳዩዋት አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብም ወዳሉበት አደረሱዋት ከአዳም ጀምሮ እስከዚያ ዕለት በአካለ ነፍስ ያሉ አባቶች ሁሉ አንቺን ከሥጋችን ሥጋን ከዐፅማችን ዐፅምን ለፈጠረልን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የአምላክ ልጅ ከአንቺ ሰው በመሆኑ በአንቺ ድህነት አግኝተናል ከጥፋትም የሕይወት ወደብ ሆነሽልናልና እያሉ ሰገዱላት። ከዚያም ወደ ተወደደ ልጅዋ የእሳት መጋረጃ ወደተተከለበት ወደ ጌትነቱ ዙፉን አደረሷት ጌታችንም እጇን ይዞ ወደ ውስጠኛው መጋረጃ አስገብቶ ከጌትነቱ ዙፋን ላይ አውጥቶ ከእርሱ ጋር አስቀመጣት ያዘጋጀላትንም ዐይን ያላየው ጆሮ ያልሰማው በሰው ልቡና ያልታሰበ ተድላ ደስታን ሁሉ ነገራት። ከጌትነቱ ዙፋንም በታች የእስራኤል ንጉሥ አባቷ ዳዊትን የነቢያትና የመላእክት ማኀበር እንደ ግድግዳ ከበውት በመሰንቆ ሲያመሰግን አየችው እንዲህም ይላል ልጄ ስሚ በጆሮሽም አድምጪ ወገንሽን የአባትሽንም ወገን ርሺ ንጉሥ ደም ግባትሽን ወዷልና እርሱም ጌታሽ ነውና። ዳግመኛም የሥቃይን ቦታ ያሳዩዋት ዘንድ መላእክት ከዚያ ውሰዷት ለሰይጣንና ለሠራዊቱ በእርሱ ጐዳና ለሚጓዙ ሁሉ ወደተዘጋጀ ወደጨለማው ዳርቻ አደረሷት እመቤታችን ማርያምም ወዮልኝ ወደዚያ እንዳይመጡ ለሰው ልጆች ማን በነገራቸው አለች መልአኩም አመቤቴ ቡርክት ማርያም ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኖራልና ለአንቺም ከአንቺ በኋላም በቃል ኪዳንሽ ለሚታመኑ አትፍሪ አላት ከዚህም በኋላ ወደ ቦታዋ መለሷት። ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ድንግል ማርያም ስለ ኋጥአን እጅግ እያዘነች ኖረች እንደ ዛሬይቱም የካቲት ዐሥራ ስድስ ቀን በጎልጎታ ቦታ ቁማ ወደ ልጇ እንዲህ ብላ ለመነች ልጄ ሆይ በእግዚአብሔር አባትህ በክርስቶስ ስምህ ከአንተ ጋርም ህልው በሆነ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ አማፅንሃለሁ ዓለም ሁሉ ሊሸከምህ የማይችል ሲሆን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በተሸከመችህ ማሕፀኔ አማፅንሃለሁ ልጄ ሆይ ያለ ሕማም ያለ ድካም ከእኔ በመውጣትህ በመወለድህ በአሳደጉህ ጡቶቼ በሳሙህ ከንፈሮቼ በአቀፋህ እጆቼ ከአንተ ጋር በተመላለሱ እግሮቼ አማፅንሃለሁ ። በውስጡ በተኛህበት በረት በተጠቀለልክበት ጨርቅ አማፅንሃለሁ የምወድህ ልጄ ሆይ በልቡናዬ ያለውን ሁሉ ትፈጽም ዘንድ የልመናዬን ቃል ሰምተህ ወደእኔ ትመጣ ዘንድ ወዳንተ ፈጽሜ እማልድሃለሁ። የብርሃን እናቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንዲህ ብላ በጸለየች ጊዜ እነሆ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ከእርሱም ጋር አእላፍት መላእክት አሉ በዙሪያውም ሁነው ያመሰግኑታል እርሱም እናቴ ማርያም ሆይ ምን ላድርግልሽ አላት እመቤታችንም ለተወዳጅ ልጅዋ እንዲህ ብላ መለሰችለት ልጄ ወዳጄ ሆይጌታዬና ፈጣሪዬ አለኝታዬና መጠጊያዬ በእናቴ ማሕፀንም ሳለሁ ባንተ ጸናሁ አንተም ጠበቅኸኝ ሁልጊዜም ስም አጠራሬ አንተ ነህ። አሁንም ጸሎቴንና ልመናዬን ስማኝ ቃሌንም አድምጥ እኔ እናትህ እኔም አገልጋይህ የምለምንህ ይህ ነው መታሰቢያዬን ለሚያደርጉ በስሜ አቢያተ ክርስቲያን ለሚሠሩ ወይም የተራቆተውን ለሚያለብሱ የተራበውን ለሚያጠግቡ የተጠማውንም ለሚያጠጡ የታመመውን ለሚጐበኙ ያዘነውን ለሚያረጋጉ የተከዘውንም ደስ ለሚያሰኙ ወይም ምስጋናዬን ለሚጽፉ ልጆቹንም በስሜ ለሚሰይም በበዓሌም ቀን በማኅሌት ለሚያመሰግን አቤቱ ዐይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰውም ልቡና ያልታሰበውን በጎ ዋጋ ስጣቸው በአማላጅነቴም የሚታመነውን ሁሉ ከሲኦል ነጻ አድርገው ከአንተ ጋር የደረሰብኝን ረኃቡንና ጥማቱን መከራውን ሁሉ አስብ አለችው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዳልሽው ይሁንልሽ የሰጠሁሽም ቃል ኪዳን እንዳይታበል በራሴ ማልኩልሽ አላት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን ድንግል ማርያም በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። https://t.me/finotebirhan12

🔴 ነገ የካቲት 16, 2014 ዓ.ም ከ11:30 ጀምሮ የማይቀርበት የሰንበት ት/ቤታችን የዓውደ ምህረት ጉባኤ #መምህር : ሊቀ ሊቃውንት ማዕበል ፈጠነ #ዘማሪ : ዲን ብሩክ ይብራኽ #ቦታ : ጽርሐ
🔴 ነገ የካቲት 16, 2014 ዓ.ም ከ11:30 ጀምሮ የማይቀርበት የሰንበት ት/ቤታችን የዓውደ ምህረት ጉባኤ #መምህር : ሊቀ ሊቃውንት ማዕበል ፈጠነ #ዘማሪ : ዲን ብሩክ ይብራኽ #ቦታ : ጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል ቤ/ክ

🔴 ስንክሳር #የካቲት_15 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ነቢይ #ቅዱስ_ዘካርያስ አረፈ፣ ሰብስጥያ በምትባል አገር የሰማዕታት #ቅዱሳን_አርባ_ሐራ_ሰማይ ቤተ ክርስቲያናቸው ተከበረች፣ በገድል ተጠምዶ የኖረ #ቅዱስ_አባ_በፍኑትዮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዘካርያስ_ነቢይ የካቲት ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ታላቅ ዕውነተኛ ነቢይ ዘካርያስ አረፈ። እርሱም ከሌዊ ነገድ ነው የአባቱም ስም በራክዩ ነው በገለዓድም ወለደው በባቢሎንም ምርኮ ጊዜ ተማረከ ከዚያ ሳለም በላዩ የወረደለትን መለኮታዊ ትንቢትን ተናገረ መንፈስ ቅዱስም በእርሱ አንደበት ጠቃሚዎች የሆኑ ብዙ ቃሎችን ተናገረ። ለኢዮሴዴቅም እንዲህ ብሎ ትንቢትን ተናገረ በኢየሩሳሌም እግዚአብሔርን ካህን ሆኖ የሚያገለግል ልጅን ትወልዳለህ ከሚጠትም በኋላ እንደቃሉ ሆነ። ለሰላትያልም ትንቢት ተናገረለት ባረከውም ወንድ ልጅ ትወልዳለህ ስሙንም ዘሩባቤል ትለዋለህ እርሱም በኢየሩሳሌም መቅደስን ይሠራል አለው ዳግመኛም ለፋርስ ንጉሥ ተናገረ የድል ምልክትንም ገለጠለት። ጌታችን በውርንጫዪቱና በታላቂቱ አህያ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ስለ መምጣቱ ተናገረ። ይሁዳም መድኃኒታችንን ክርስቶስን አሳልፎ በመስጠቱ ስለ ተቀበለው ሠላሳ ብር ትንቢት ተናገረ። መድኃኒታችንም በሚሰቀልበት ዐርብ ሌሊት ስለ ሐዋርያት መበተን ተናገረ። በቀትር ጊዜም ስለ ፀሐይ መጨለም ተናገረ። ስለ እስራኤል ልጆች ኀዘንም እንዲህ አለ ያን ጊዜ የወጉትን ያዩት ዘንድ አላቸው ወደ ኀዘንም ይመለሳሉ እንደ ሚወዱትም ያለቅሱለታል ሰው ለበኵር ልጁ እንደሚያዝን ጽኑ ኀዘንን ያዝናሉ። የትንቢቱም ወራት በተፈጸመ ጊዜ በሰላም አረፈ በነቢያት መቃብርም ተቀበረ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_አርብዐ_ሐራ_ሰማይ በዚህችም ዕለት ሰብስጥያ በምትባል አገር የሰማዕታት አርባ ሐራ ሰማይ ቤተ ክርስቲያናቸው ተከበረች። በስማቸው የተሠራች ቤተ ክርስቲያናቸውን ታላቁ አባት ቅዱስ ባስልዮስ በዚህች ዕለት አከበራት። ስለ እነርሱም ድርሳናትን ደረሰ። በዚህችም ዕለት በዓላቸውን አከበረላቸው። እነዚህም ቅዱሳን በአልፊያኖስ ዘመን ተጋደሉ እርሱም ከንጉሠ ነገሥት ቈስጠንጢኖስ ከመኳንንቶቹ አንዱ ነው። ከአይሁድ አገሮችም በአንዱ ላይ አነገሠው ክርስቲያኖችንም እንዲጠብቃቸውና እንዲያከብራቸው አዝዞት ነበር። እርሱ ግን ወደዚያ አገር በደረሰ ጊዜ ጣዖትን አመለከ ሰዎችንም ሁሉ ጣዖት እንዲአመልኩ አስገደዳቸው ብዙዎች ምእመናንም ተነሥተው እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገሙ። በዚያችም ሌሊት እሊህ አርባ ጭፍሮች ወደ መኰንኑ ደርሰው በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ምስክር ይሆኑ ዘንድ እርስ በርሳቸው ተስማሙ። በእንቅልፋቸውም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ለሰውነታቸው ብርታትን ሰጣቸው በጥዋትም ተነሥተው የጭፍራ አለቃ በሆነ በአግሪጎላዎስ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ። በላያቸውም ተቆጥቶ አስፈራራቸው እነርሱ ግን አልፈሩም በደንጊያም እንዲወግሩአቸው አዘዘ። በአቅራቢያቸውም የውሽባ ቤት በአጠገቧ ያለ የውኃ ጒድጓድ ነበረች ከውርጭ ጽናትም የተነሣ ትረጋለች በውስጥዋም ይጥሏቸው ዘንድ መኰንኑ አዘዘ። በውስጥዋም በጣሉአቸው ጊዜ ከውርጭ ጽናት የተነሣ ሕዋሳታቸው ተቆራረጠ ከእርሳቸውም አንዱ ፈራ ከዐዘቅቱም አውጡኝ ብሎ ወጣ ወደ ወሽባው ቤትም ገባ ፈጥኖም ሞተ ዋጋውንም አጠፋ የፈለገውንም አላገኘም። አርባ አክሊላትም ከሰማይ ሲወርዱ በሠላሳ ዘጠኙ ሰማዕታት ላይም ሲቀመጡ አንዱ አክሊልም በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ ሲቀር ከወታደሮች ይህን ያየ ከዚያ ተነሥቶ በጌታ አምኖ ልብሶቹንም አውልቆ ቅዱሳን ወደአሉበት ወደ ዐዘቅቱ ወረደ በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ የቀረውንም አክሊል ወሰደ። እሊህም ጐልማሶች ሰማዕታት በዚያች ዐዘቅት በነበሩበት ጊዜ እናቶቻቸው ያጽናኗቸውና ያስታግሡአቸው ነበር። እነርሱም ብዙ ጊዜ ቆዩ እንጂ ቶሎ አልሞቱም። ከሀድያንም ጭኖቻቸውን ሊሰብሩ ፈለጉ ፈጥነው እንዲሞቱ እግዚአብሔርም ወዲያውኑ ነፍሳቸውን ወሰደ ጭኖቻቸውን መስበር አልተቻላቸውም። ከዚህ በኋላም በእሳት ሥጋቸውን እንዲአቃጥሉ በተሽከረካሪም ጭነው ወስደው ወደ ባሕር እንዲጥሏቸው መኰንኑ ወታደሮችን አዘዘ። ሲጭኑአቸውም ያልሞተ ሕፃን አገኙና ተውት እናቱም ከሠረገላው ውስጥ ልትጥለው ተሸክማው ሮጠች ወታደሮችም ስለአልሞተ ከለከሉአት ወዲያውኑ በጫንቃዋ ላይ ሙቶ ከቅዱሳን ጋር እንዲሆን ወደ ተሽከርካሪው ጣለችው። ወደ ስብስጥያ ከተማ ጭነው ወስደው በእሳት አቃጠሉአቸው ወደ ባሕርም ጣሉአቸው። ከዚህም በኃላ በሦስተኛ ቀን ለስብስጥያ አገር ኤጲስቆጶስ ተገለጡለተ። እንዲህም አሉት ወደዕገሌ ወንዝ ሐድ ሥጋችንንም ታገኛለህና አሸክመህ አምጣው ኤጴስቆጶሱም ከካህናት ጋራ በሌሊት ተነሥቶ ወደ ወንዙ ሔዱ የቅዱሳንንም ሥጋቸውን በአንድ ቦታ ተሰብስቦ እንደ ከዋክብት እያበራ አገኙት ከእርሳቸውም አንድ እንኳን አልጐደለም በክብር ተሸክመው ወስደው በመልካም ቦታ በክብር አኖሩአቸው። ዜናቸውም በአራት ማእዘን ተሰማ መታሰቢያቸውንም አደረጉ በዓለም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን ታነፀላቸው ከሥጋቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ስንክሳር #የካቲት_14 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ አራት በዚህች ቀን የአንጾኪያ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #አባ_ሳዊሮስ አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #አባ_ቄርሎስ አረፈ፣ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #አባ_ያዕቆብ አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ቄርሎስ የካቲት ዐሥራ አራት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት ቄርሎስ አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ አምስተኛ ነው። ይህም አባት ፍዩም ከምትባል ሀገር ነው በእርሷም ቅስና ተሹሞ ኖረ ከዚህም በኋላ ከዚያ ለቆ ከምስር ከተማ ውጭ ወደ ሆነች የኢትዮጵያውያን የጕድጓድ ውኃ ወዳለበት ወደ ቅዱስ ፊቅጦር ገዳም ደረሰ በውስጡም ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ ብዙ ዘመናት ኖረ። የዕውቀቱና የቅድስናው ዜና በተሰማ ጊዜ ያለ ውዴታው ይዘው በእስክንድርያ ሀገር ሊቀ ጵጵስና ሾሙት መንጋውንም በበጎ አጠባበቅ ጠበቀ በቊርባንና በጸሎት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሊሠሩት የሚገባቸውን ለካህናት ሥርዓትን ሠራ። በሹመቱም ሰባት ዓመት ከዘጠኝ ወር ከሃያ ሰባት ቀን ኑሮ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ያዕቆብ በዚህችም ዕለት የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት አባ ያዕቆብ አረፈ። እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ኃምሳኛ ነው። ይህም አባት እልመቱዝ የተባለ የግብጽ ንጉሥ በነገሠ በዐሥራ ሰባት ዓመት ተሾመ እርሱም ለመኰንኑ ለወልደ ኀሮን ረሽድ ወንድም የሆነ ነው በዚህም አባት ዘመን የአስቄጥስ ገዳማት ታድሰው መነኵሳቱ ወደሳቸው ተመለሱ። አፎን በሚባል አገር ስሙ መቃርስ የሚባል ሰው ነበረ ወደዚህ አባት ወደ ያዕቆብ መጥቶ ወደቤቱ በመሔድ ቤቱን ይባርክለት ዘንድ ለመነው እርሱም አብሮት ሔደ። ታሞ የነበረ ልጁም ሞተ ወደ አባ ያዕቆብም አቅርቦ እንዲህ ብሎ ለመነው ከርሱ በቀር ልጅ የለኝምና አባቴ ሆይ ራራልኝ እርሱም እነሆ ሞተ ስለርሱ ወደ እግዚአብሔር ትማልድ ዘንደ እለምንሃለሁ አለው። አባ ያዕቆብም እንደ እምነትህ ይሁንልህ አትፍራ አለው ሕፃኑንም ከአባቱ ተቀበሎ ታቀፈውና በላዩ ጸለየ በመስቀል ምልክትም አማተበበት ስለርሱም ወደ እግዚአብሔር ለመነ ጌታችንም ልመናውን ተቀበለው የሕፃኑ ነፍስ ተመልሳ ዐይኖቹን ገለጠ ከሞትም ድኖ ተነሣ አባቱንም ልጅህን ውሰድ የሞተ አይደለም ያንቀላፋ ሁኖ ነው እንጂ አለው። የሕፃኑም አባት ይህን ድንቅ ሥራ በአየ ጊዜ እጅግ ፈራ የገንዘቡንም እኩሌታ ለምጽዋት ብሎ ሰጠው እርሱም ወደ ኢየሩሳሌም ልኮ ሃይማኖታቸው ለቀና ምእመናን ሁሉ ወደርሷ በመጡ ጊዜ መጠጊያ ትሆን ዘንድ ቤተ ክርስቲያንን ሠራበት። የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ዲዮናስዮስም ወደ ምስር በመጣ ጊዜ ከአባ ያዕቆብ ጋር ተገናኝቶ ከእርሱ ዘንድ ጥቂት ቀኖች ተቀምጦ ወደ ሀገሩ ተመለሰ። ይህም አባት ያዕቆብ በሹመቱ ዐሥር ዓመት ከስምንት ወር ከሦስት ቀን ኑሮ በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ስንክሳር #የካቲት_13 የካቲት ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን የከበረ #ቅዱስ_ሰርግዮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ የእስክንድርያ አገር #ሊቀ_ጳጳሳት_ጢሞቴዎስ አረፈ፣ ለሶርያ መስፍን ልጁ የሆነ ለተመሰገነ ለሁለተኛው #ቅዱስ_አውሳብዮስ የምስክርነቱና የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ ታላቁ ሰማዕት #ቅዱስ_ፊቅጦር የተወለደበት ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሰማዕት_ቅዱስ_ፊቅጦር በዚህች ቀን ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፊቅጦር የተወለደበት ነው፡፡ የዚህ ቅዱስ እናቱ ማርታ አባቱ ደግሞ ኅርማኖስ ይባሉ ነበር፡፡ አባቱ የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ ባለሟል በነበረ ሲሆን ቅዱስ ፊቅጦርም በገዛ አባቱ እጅግ ተሠቃይቶ ምስክርነቱን የፈጸመው ታላቁ ሰማዕት ነው፡፡ ኅርማኖስ የተባለው ወላጅ አባቱ የክርስቲያኖችን ደም እንደ ውኃ ያፈስ የነበረው የዲዮቅልጥያኖስ ልዩ አማካሪና የሠራዊቱ አለቃ ነበር፡፡ እናቱ ሣራ ግን በክርስቶስ አምና የተጠመቀች ክርስቲያን ነበረች፡፡ እንዲያውም ልጇን ቅዱስ ፊቅጦርን ከመውለዷ በፊት የአምላክ እናት የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ወዳለበት ሄዳ "እመቤቴ ማርያም ለኢየሱስ ክርስቶስ ደስ የሚያሰኘውን ልጅ ስጪኝ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስን ደስ የማያሰኝ ልጅ ከሆነ ግን ማኅፀኔን ዝጊልኝ" ብላ በጸለየችው ጸሎት ነው ቅዱስ ፊቅጦርን ያገኘችው፡፡ ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር በዓለም ላይ ያሉ በክርስቶስ ያመኑ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ በግፍ ያስገድል በነበረበት ወቅት የተገኘ ታላቅ ሰማዕት ነው፡፡ ፊቅጦርን ገና 15 ዓመት እንደሆነው ንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስ "ከፍ ባለ ስልጣን አስቀምጥሃለሁ፣ እጅግ ብዙ ወርቅና ንብረትም እሰጥሃለሁ፣ በእስክንድርያም ላይ ገዥ አድርጌ እሾምሃለሁ ክርስቶስን ማመንህን ተውና ወደ ቤተ መንግሥቴ ግባ" ቢለውም ቅዱስ ፊቅጦር ግን ብዙ መከራንና ሥቃይን ተቀብሎ ሰማዕት መሆንን መረጠ፡፡ ቅዱስ ፊቅጦርም ዲዮቅልጥያኖስን "ክርስቶስን በምታፈቅረው ጊዜ አፈቀርኩህ ወደ አንተም መጣሁ፤ ክርስቶስን በጠላኸው ጊዜ ግን እኔም ጠላሁህ፣ ቤትህንም ጠላሁ" ብሎታል፡፡ ከብዙ ጊዜም በኋላ ዲዮቅልጥያኖስ ቅዱስ ፊቅጦርን በመንግሥቱ ውስጥ ሦስተኛ ማዕረግ አድርጎ ሾመው፡፡ እርሱ ግን ይጾማል ይጸልያል እንጂ በንጉሡ ቤት አይበላ አይጠጣም ነበር፡፡ ዕድሜውም 27 ነበር፡፡ አባቱንም ከጣዖት አምላኪነቱ እንዲመለስ ቢመክረው ሄዶ ለንጉሡ ከሰሰው፡፡ ፊቅጦርም "ለአንተ ለጣዖት አምላኩ አገልጋይ አልሆንም" በማለት በንጉሡ ፊት ትጥቁን ፈቶ ጣለ፡፡ የቅዱስ ፊቅጦር ወላጅ አባቱ ኅርማኖስ የከሃዲው ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስ የቅርብ እንደራሴና መስፍን ስለነበር ልጁ ፊቅጦርን የንጉሡን ሹመትና ልመና እንዲቀበል ብዙ ሲያግባባው ነበር፤ አባቱም ልጁ በሀሳቡ እንዳልተስማማለት ሲያውቅ ከዲዮቅልጥያኖስ ጋር ተማክሮ ልጁን ቅዱስ ፊቅጦርን ወደ እስክንድርያና ወደ ተለያዩ ሀገሮች በግዞት ተልኮ በዚያም ተሠቃይቶ እንዲሞት ፈደበት፡፡ ወደ ግብፅም ልከው በዚያ እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ነጥቆ ወስዶ በሰማያት የሰማዕታትን ክብር አሳይቶት ወደ ምድር መለሰው፡፡ ክፉዎቹም በብረት አልጋ አስተኝተው ከሥሩ እሳት አነደደዱበት፡፡ በሌላም ልዩ ልዩ በሆኑ ማሠቃያዎች እጅግ አሠቃዩት፡፡ መልአክም ተገልጦ ፈወሰው፡፡ ወደ እንዴናም አጋዙትና በዚያም ብዙ አሠቃዩት፡፡ ምላሱን ቆረጡት፤ በችንካርም ጎኖቹን በሱት፤ ቁልቁል ሰቅለውም ቸነከሩት፤ በእሳትም ውስጥም ጨመሩት፤ ዐይኖቹን አወጡት፤ እሬትና መራራ ሐሞትንም አጠጡት፡፡ ደግመውም ዘቅዝቀው ሰቀሉት፡፡ ጌታችንም ተገልጦ ካጽናናው በኋላ ፈወሰውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ፊቅጦር፣ ፋሲለደስ፣ ቴዎድሮስ በናድልዮስ፣ አውሳብዮስና መቃርዮስ እነዚህ ሰማዕታት በአንድነት በአንድ ዘመን አብረው ኖረው ተሰውተው ሰማዕት የሆኑ የሥጋም ዝምድና ያላቸው የነገሥታት ልጆች ናቸው። ዲዮቅልጥያኖስም የቅዱስ ፊቅጦርን ዐይኑን አስወለቀው፣ ነገር ግን የታዘዘ መልአክ መጥቶ የዓይኑን ብርሃን መልሶለታል፡፡ ሰማዕቱ በመዝለል ባሕር የሚሻገር እንደ አሞራ የሚመስል ፈረስ ነበረው፡፡ ከዚህም በኋላ ማሠቃየቱ ቢሰለቻቸው ሚያዝያ 27 ቀን አንገቱን ሰይፈው በሰማዕትነት እንዲያርፍ አድርገውታል፡፡ ሰማዕቱ ቅዱስ ፊቅጦር አንድ የሚነገር ትልቅ ታሪክ አለው፡፡ እርሱም በሰማዕትነት ካረፈ ከብዙ ዘመን በኋላ በራእይ ተገልጦ በ8ኛው ሺህ ዘመን በሀገራችን በኢትዮጵያና በግብፅ እንዲሁም በቁስጥንጥንያና በሮም ወደፊት የሚሆነውን ነገር ሁሉ በግልጽ የተናገረ መሆኑ ነው፡፡ ‹‹ስለ ሃይማኖት ቅዱስ ፊቅጦር ያየው ራእይ›› የሚል መጠሪያ ያለው ይህ ራእይ በሀገራችን ጎጃም ደብረ ጽሞና ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ከገድላት_አንደበት) https://t.me/finotebirhan12

🔴#መርሐግብራችሁን_ካሁኑ_አስተካክሉ Share #የካቲት 16 ከ11:30 ጀምሮ በአውደ ምሕረቱ ላይ #የዕለቱ መምህር : ሊቀ ሊቃውንት ማዕበል ፈጠነ #የዕለቱ ዘማሪ : ዘማሪ ዲ/ን ብሩክ ይብራኽ #አ
🔴#መርሐግብራችሁን_ካሁኑ_አስተካክሉ Share #የካቲት 16 ከ11:30 ጀምሮ በአውደ ምሕረቱ ላይ #የዕለቱ መምህር : ሊቀ ሊቃውንት ማዕበል ፈጠነ #የዕለቱ ዘማሪ : ዘማሪ ዲ/ን ብሩክ ይብራኽ #አዘጋጅ: ፍኖተ ብርሃን ሰንበት ት/ቤትና የደብሩ ስብከተ ወንጌል #አድራሻ: ከኢሚግሬሽን ከፍ ብሎ ጎላ ቅዱስ ሚካኤል ቤ/ክ

🔴 ስንክሳር #የካቲት_12 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ #ቅዱስ_ሚካኤል ወደ ረዓይታዊ ወደ ሶምሶን ተልኮ
🔴 ስንክሳር #የካቲት_12 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ #ቅዱስ_ሚካኤል ወደ ረዓይታዊ ወደ ሶምሶን ተልኮ ኃይልን ሰጥቶት ጠላቶቹን ድል እንዲያደርግ የተራዳበት መታሰቢያ ነው፣ ተጋዳይ የሆነ የከበረ አባት #አባ_ገላስዮስ አረፈ፣ ታላቁ አባት #አቡነ_ሠርጸ_ጴጥሮስ አረፉ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #የመላእክት_አለቃ_ቅዱስ_ሚካኤል የካቲት ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል ወደ ረዓይታዊ ወደ ሶምሶን ተልኮ ኃይልን ሰጥቶት ጠላቶቹን ድል እንዲያደርግ የተራዳበት መታሰቢያ ነው። በዚች ዕለት የከበረ ሚካኤልን እግዚአብሔር ወደ ረዓይታዊ ወደ ሶምሶን ላከው የፍልስዔም ሰዎች ሊገድሉት በጠላትነት በተነሡበት ጊዜ ድል እስከ አደረጋቸውና እስከ ገደላቸው ድረስ ረዳው ኃይልንም ሰጥቶ በአህያ መንጋጋ ከእርሳቸው አንድ ሺህ ሰዎችን ገደለ። ተጠምቶም ለሞት በተቃረበ ጊዜ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ተገለጠለትና አጸናው እግዚአብሔር ከአህያ መንጋጋ አጥንት ውኃን አፈለቀለትና ጠጥቶ ዳነ። ዳግመኛም ከሚስቱ ጋር ተስማምተው ዐይኖቹን አሳወሩ የራሱንም ጠጉር ላጩ አሠሩትም ከዚህም በኋላ ለጣዖቶቻቸው በዓልን በአዘጋጁ ጊዜ ሶምሶንን ወደ ጣዖቶቻቸው ቤት ወሰዱት በዚያም ሦስት ሽህ ያህል ሰዎች ተሰብስበው ነበር የከበረ ሚካኤልም ተገለጠለትና ኃይልን መላው የዚያንም ቤት ምሰሶዎች ነቀላቸው ቤቱም በላያቸው ወድቆ ከእርሱ ጋር ሁሉንም ገደላቸው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ከገድላት_አንደበት) https://t.me/finotebirhan12

#የካቲት_11 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥራ አንድ በዚች ቀን የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #ቅዱስ_በላትያኖስ በሰማዕትነት ሞተ፣ ተጋዳዩ ባለ አንበሳው #ቅዱስ_አውሎግ አረፈ፣ የአባ ስልዋኖስ ረድእ #ቅዱስ_አባ_በትራ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በላትያኖስ_ሰማዕት የካቲት ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት በላትያኖስ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ ብልህና አዋቂ የሆነ ታላቅ ተጋድሎን የሚጋደል ነው በሮሜ ሀገርም ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ በቅዱስ ጴጥሮስ ወንበር ላይ ዐሥራ ሁለት ዓመት በሰላም ኖረ። ሕዝቡን የቀናች ሃይማኖትን እያስተማራቸው ሳለ መኰንኑ ፊሊጶስ በንጉሥ ቀላውዴዎስ ላይ ተነሥቶ በገደለው ጊዜ በርሱ ፈንታ ነገሠ በምእመናንም ላይ ታላቅ መከራን አመጣ በዚህ በንጉሥ ዳኬዎስ እጅ ብዙዎች በሰማዕትነት ሞቱ። በዘመኑም ሰባት ሰዎች ከእርሱ ሸሹ ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዓመት ተኝተው ነቁ እርሱም በኤፌሶን ከተማ መስጊድ ሠርቶ በውስጡ ጣዖታትን አኖረ ሰዎችን ሁሉ ለጣዖታት እንዲሠዉ አስገደዳቸው ለጣዖታት ያልሠዉትንም ገደላቸው። ይህ የከበረ በላትያኖስም የጣዖታት አምልኮን እንደሚቃወም ሕዝቡም በክብር ባለቤት በክርስቶስ ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ እንደሚያስተምር ንጉሥ በሰማ ጊዜ ወደ ሮሜ አገር ልኮ ወደ ኤፌሶን ከተማ አስመጣውና ለጣዖታት እንዲሠዋ ለመነው። እርሱ ግን ቃሉን አልሰማም ተሣለቀበት አማልክቶቹንም ረገመ እንጂ። ንጉሡም ተቆጣ አንዲት ዓመት ያህልም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ በሰይፍ ራሱን ቆረጠው የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_አውሎግ_አንበሳዊ በዚህችም ዕለት ተጋዳዩ ባለ አንበሳው አውሎግ አረፈ፡፡ የዚህ ቅዱስ ወላጆች ከሀገረ ንጽቢን የሆኑ በበጎ ሥራ ፍጹማን በወርቅና በብርም የበለጸጉ ናቸው። ለልጃቸውም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ አስተማሩት ከጥቂት ቀኖች በኋላ ወላጆቹ ብዙ ገንዘብን ትተውለት ሞቱ። በአንዲትም ዕለት አውሎግ ያለህን ገንዘብህን ሁሉ ሽጠህ ለድኆች ሰጥተህ መከራ መስቀልህን ተሸክመህ ና ተከተለኝ የሚለውን የከበረ የወንጌልን ቃል አሰበና ወዲያውኑ ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች በትኖ ወደ አባ አውሎጊን ሔደ እርሱም በደስታ ተቀበለው። ስለ ርሱ እንዲህ የሚለውን ራእይ አይቶ ነበር እነሆ ወዳንተ ጐልማሳ ይመጣል ተቀበለውና ከሚያገለግሉ መነኰሳት ጋር ቀላቅለው እየፈተነውም ሦስት ዓመት ያህል ኖረ ፍጹም የሆነ ቅድስናውንም በአየ ጊዜ የምንኵስናን ልብስ የመላእክትንም አስኬማ አለበሰው። ከሰንበትም እስከ ሰንበት እየጾመ በብዙ ተጋድሎ ኖረ ምግቡም እንጀራና ጨው ነበረ በቀንና በሌሊትም ሰባት መቶ ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን ከስግደት ጋር ይጸልያል በዚህም ተጋድሎ አርባ ዓመት ኖረ። ከዚህም በኋላ ያሰናብተው ዘንድ መምህሩ አባ አውሎጊንን ማለደውና ወደ በረሀ ሔደ ከአንዲት ታናሽ ዋሻ ውስጥም ገብቶ እየተጋደለ ኃምሳ ዓመት ኖረ። ለፍላጎቱም የሚያገለግሉት ሁለት አንበሶችን እግዚአብሔር ሰጠው በአንዲትም ዕለት ታመመ አንበሶቹንም እጠጣ ዘንድ የሞቀ ውኃ እሻለሁ አላቸው። አንዱ አንበሳም ወደ ተራራ ሒዶ እረኛ አግኝቶ ወደ አባ አውሎግ አመጣው በአየውም ጊዜ ሰገደለትና አባቴ ሆይ ምን ትሻለህ አለው። እርሱም የሞቀ ውኃ ታጠጣኝ ዘንድ እሻለሁ አለው እንዳለውም አደረገለት ከዚህም በኋላ አንበሳው እረኛውን ወደቦታው መለሰው። ያም እረኛ ለእግሩ ተረከዝ ዓለሙ ሁሉ መጠኑ የማይሆን ጻድቅ ሰውን አገኘሁ ብሎ ለሰው ሁሉ ተናገረ በሰሙ ጊዜም ሰዎች ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ በሽተኞችንም ሁሉ አመጡለትና ፈወሳቸው። በዚያ ወራትም መምህሩ አባ አውሎጊን ጣዖትን የሚያመልኩ የፋርስ ሰዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት ለመመለስ ወደ ፋርስ ሀገር ሊሔድ ፈለገ ዳግመኛም ልጁ አውሎግን ከእርሱ ጋር ሊወስደው ወደርሱ መልእክተኛ ሊልክ ሽቶ ሳለ መንፈስ ቅዱስ አንበሳውን አስገነዘበውና አጽፉንና ወንጌሉን አንሥቶ ተሸከመ። አባ አውሎግንም ጕዞን አመለከተው ተነሥቶም አንበሳውን ተከትሎ ወደ መምህር አውሎጊን ደረሰ እርሱም በደስታ ተቀበለው። ሲጓዙም ከጤግሮስ ወንዝ ደረሱ ውኃውም ተከፍሎላቸው ተሻገሩ ወደ ሀገሩም ውስጥ በደረሱ ጊዜ አስተማሩአቸው ወደ ቀናች ሃይማኖትም መለሷቸውና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው። በአንዲትም ዕለት ደግሞ ቅዱሳን በተራቡ ጊዜ ምግባቸውን ይፈልጉላቸው ዘንድ አባ አውሎግ አንበሶችን አዘዘ ሒደውም እንጀራ በአህያ ላይ ጭኖ የሚጓዝ ሽማግሌ አገኙ ሕፃንም ከእንጀራው ጋር አለ ። አህያውንም ወደ ቅዱሳን አመጡት ከድንጋጤም የተነሣ ብላቴናው ሞተ ቅዱሳንም ጸልየው ሕፃኑ ድኖ ተነሣ ቅዱሳንም ተመገቡ አንበሶችም አህያውን ከእንጀራውና ከሕፃኑ ጋር ወደ ሽማግሌው መለሱት። ከዚህም በኋላ አባ አውሎግ ወደ በዓቱ ተመለሰና ጥቂት ታሞ አረፈ በታላቅ ክብርም ተቀበረ እነዚያ አንበሶችም መቃብሩን እየጠበቁ ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖሩ ከዚያም በኋላ ወደ ዱር ገቡ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_በትራ በዚህችም ቀን የአባ ስልዋኖስ ረድእ አባ በትራ አረፈ። ይህም ቅዱስ በደብረ ሲና ካለች በዓቱ በነበረ ጊዜ ትርኅምትን ይጠብቅ ነበር በራትም ጊዜ ለሥጋው የሚያሻውን ይመገባል። ፈርኑ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶስ በአደረጉት ጊዜ ትርኅምትን በማብዛት ሰውነቱን እጅግ አደከመ ደቀ መዛሙርቱም አባታችን ሆይ በገዳም በበኣትህ በነበርክ ጊዜ ትርኅምትን እንዲህ አላበዛህም ነበር አሉት ይህም አባት እንዲህ አላቸው "ያን ጊዜ በገዳም በችግር ውስጥ ነበርኩ ዛሬ ግን ከብዙዎች መካከል በአንድነት አለሁ የምሻውም ሁሉ ብዙ አለኝ ነገር ግን ሥጋዬን ቀጥቼ ብገዛው ይሻላል እንዲህም እየተጋደለ ኖረ ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ስንክሳር #የካቲት_10 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዐሥር በዚች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ የእልፍዮስ ልጅ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ፣ የንጉሥ ኑማርያኖስ ልጅ #የከበረ_ዮስጦስ በሰማዕትነት ሞተ፣ በገድል የተጠመደ #አባ_ኤስድሮስ አረፈ፣ የፋርስ ሀገር ኤጲስቆጶስ #አባ_ፌሎ በሰማዕትነት ሞተ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_እልፍዮስ የካቲት ዐሥር በዚች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ የእልፍዮስ ልጅ የከበረ ሐዋርያ ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ሐዋርያ በብዙ ሀገሮች ውስጥ ከሰበከ በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ ወደ ምኲራብም ገብቶ የክብር ባለቤት የጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት በግልጥ አስተማረ። ከእርሱ ለሚሰሙትም ሁሉ ብዙ ተአምራትን አደረገ። ንጹሕ በሆነ ልቡናም በእግዚአብሔር አመኑ። ራሳቸውንም አጸኑ። ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብም በልቡናው አሰበ፡፡ እንዲህም አለ። ሕዝቡ ከእርሱ ሰምተው እንዴት ያምናሉ አለ። እርሱም ሕዝቡ ወደተሰበሰቡበት ወደ ምኩራብ ገባ። ከአይሁድም የተቀመጡ የተሰበሰቡ ብዙ ሰዎችን አገኘ። በፍጹም ታላቅ ደስታ ያስምራቸው ዘንድም በመካከላቸውም ገባ። ለሁሉም በቃሉ ማስተማሩን አበዛ። ያለመፍራትም ሃይማኖቱን ገለጠ። አንድ ለሆነው ለእግዚአብሔር ልጅ ምስክር ሆነ። "የሕይወት ቃል ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ሁሉ አምላክ ነው። በእውነትም የእግዚአብሔር ልጅ ነው። እርሱ ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ ከአብ ጋር ነበርና። እርሱ በአብ አለ፤ አብም በእርሱ አለ። እርሱ የአብ ቃል ነው። እርሱ ሰውን በአርአያችንና በምሳሌያችን እንፍጠር አለ። እርሱ በሰማይ አለ። እርሱ ከአባቱ ጋር አለ። እርሱ በኪሩቤል ሰረገላ ይቀመጣል። ሱራፌልም ያመሰግኑታል። እርሱ በድንግል ማርያም ማሕፀን የተወሰነ በልዕልና በገናንነቱ ሥልጣን ነው። እርሱ ድንግል ማርያም የወለደችው ጌታችን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሰው የሆነ አምላክ ነው"። አንድ ሰው ስንኳን ሳይፈራ በተሰበሰቡት መካከል የሐዋርያው ምስክርነት ይህ ነበር። በእውነት አንድ ለሆነው ለእግዚአብሔር ልጅ ልደትም ምስክር ሆነ። እርሱ ነበርና። በሞቱም፣ በትንሣኤውም፣ ወደ አባቱ ወደ ሰማይ ስለማረጉም ምስክ ሆነ። ለተሰበሰቡትም በክርስቶስ ስለማመን አስተማራቸው። የተሰበሰቡትም የሐዋርያውን ትምህርት በሰሙ ጊዜ ከእርሱ ጋር ካለው ከአባታቸው ከሰይጣን የተነሳ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ላይ ፈጽመው ተቆጡ። ሁሉም ተሰብስበው ተቀመጡ። የተሰበሰቡት ሁሉ ደሙን ፈለጉ። ነገሩን የሰሙትም የተባረከ ሐዋርያን ያዙት። ከንጉሥ ከቀላውዴዎስም ወሰዱት። የሐሰት ምስክሮችንም በእርሱ ላይ አስነሡ። ለንጉሡም "ይህን ጥፋተኛ ሰው በሀገሩ በአውራጃው ይዘናል" አሉት፤ "እኔ የእግዚአብሔር የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ነኝ ይላቸዋል። ለንጉሡ እንዳይገዙም ይከለክላል" አሉት። ስለተባረከው ሐዋርያ ይህን ነገር በሰማ ጊዜም እስከሚሞት ድረስ በድንጋይ ይወግሩት ዘንድ አዘዘ። አይሁድንም እግዚአብሔር ረገማቸው። ንጉሡ አይሁድን እንዳዘዛቸውም በድንጋይ ወገሩት። ከዚህ በኋላ ቡሩክ የሚሆን የእልፍዮስ ልጅ የሐዋርያው የቅዱስ የያዕቆብ ምስክርነት የካቲት ዐሥር ቀን ሆነ። በኢየሩሳሬም ቤተ መቅደስ ተቀበረ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ገድለ_ሐዋርያት https://t.me/finotebirhan12

ሠላም እንደምን አላችሁ የሦስት ቀኑ ጉባኤ ዛሬ ማብቂያው እንደሆነ ይታወቃል 👉 ሰኞ የካቲት 7 ማህበረ ሠላም 👉 ማክሰኞ የካቲት 8 የራጉኤል ጎልማሣ ክፍሎች ጉባኤው ላይ መዝሙር ማቅረባቸው አይዘነጋም 👉 ዛሬ ረቡዕ የካቲት 9 ደግሞ የሰንበት ት/ቤታችን ተራ ስለሆነ በ10: 30 በመገኘት ዝማሬውን መርጠን አስታውሰን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እናቀርባለን ቢቻለን ሁላችንም ለማገልገል እንሞክር ሰአት እናክብር ሠላመ እግዚአብሔር ከሁላችንም ጋር ይሁን።

ሠላም እንደምን አደራችሁ የሦስት ቀኑ ጉባኤ ዛሬ ማብቂያው እንደሆነ ይታወቃል 👉 ሰኞ የካቲት 7 ማህበረ ሠላም 👉 ማክሰኞ የካቲት 8 የራጉኤል ጎልማሣ ክፍሎች ጉባኤው ላይ መዝሙር ማቅረባቸው አይዘነጋም 👉 ዛሬ ረቡዕ የካቲት 9 ደግሞ የሰንበት ት/ቤታችን ተራ ስለሆነ በ10: 30 በመገኘት ዝማሬውን መርጠን አስታውሰን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እናቀርባለን ቢቻለን ሁላችንም ለማገልገል እንሞክር ሰአት እናክብር ሠላመ እግዚአብሔር ከሁላችንም ጋር ይሁን።