yero's reflections/ የየሮ ንጽረቶች
Відкрити в Telegram
ይህ ቻናል በተለየዩ ጉዳዮች ላይ የራሴን ምልከታ የማሰፍርበት ነው። በጽሑፎቹ መንፈሳዊ፣ ሃገራዊና ማህበራዊ ነክ ጉዳዮች ይዳሰሳሉ። መልካም የሆነ ተጽዕኖ መፍጠር ከቻለ ብዕሬ ለምን ይለጎም?
Показати більше305
Підписники
Немає даних24 години
-17 днів
-130 день
Архів дописів
"አመስጋኝ ነኝ" ን የጻፍኩበት ሰሞን....
ጥሩ ቤተሰባዊነት የናኘበት ወዳጅነት ነበረን፤ ለጊዜው ስሟን ከማልጠቅሳት "ጓደኛዬ" ጋር። ጓደኝነቱ ሌላ ይዘት አልነበረውም፤ በቃ ጥሩ ወዳጆነት ብቻ። ከዛ ባለፈ በተፈጠረልኝና ባገኘሁት አጋጣሚ በሕይወቷ ላይ በጎ አሻራ እንደነበረኝ አውቃለሁ።
ታዲያ በአንድ አጋጣሚ ከዚህች ወዳጄ ጋር በቅርበት የምናሳልፍበትን ሁኔታ መፈጠሩን ተከትሎ የተለየ ነገር ማስተዋል ጀመርኩ። በሕይወቴ እንኳን ቅርብ ከምለው ሰው ይቅርና ለእኔ ጥሩ እይታ የላቸውም ብዬ ከማስባቸው ሰዎች ገጥሞኝ የማላውቀው አይነት ባህሪ ተመለከትኩ። አክብሮት አጥነት በተላበሰ አኳሃን ያሳየችኝ ድርጊቶች አስቀየሙኝ።
ተቀየምኩ፤ የቅርብ ከምንለው ሰው ያልጠበቅነው ነገር ስንመለከት ሊሰማን የሚችለው አይነት ስሜት ተሰማኝ። ክፉም ሆነ ደግ አልተናገርኩም። ውስጤ ያስከፋኝን ነገር ይዤ ወደ ራሴ መለስ ማለትን ሞከርኩ። ቀጥሎ ልቤ ካዘነባት ልጅ ይልቅ በዙሪያዬ የከበቡኝን ወዳጆቼንና ደግነታቸውን መቁጠር መረጥኩ። ቆጥሬ የማልጨርሳቸው መልካምነታቸው ከአእምሮዬ በላይ የሆኑ ወዳጆቼ ተዘልለው ታዩኝ።
የአንዳንዶቹ ደግነት ድንቅ ነበር፤ ተርኬ የማልዘላቃቸው፤ አውርቼላቸው የማይወጣልኝ ወዳጅነት። ያልተገደበ ፍቅር፣ ያልተቆጠበ መልካምነት፣ ያልደበዘዘ ትኩረት፣ በእኔ መለዋወጥ ያልተለወጠ እምነት ያሳዩኝ ደጋግ ነፍሶች።
እናም በመገረም ብዕሬን አንስቼ መጻፍ ጀመርኩ "አመስጋኝ ነኝ...." ብዬ።
በሂደት ውስጤ የነበረው ቅሬታ ተጠራርጎ ሲሄድ ተሰማኝ። እንደውም ለዚች ወዳጄ ከበፊቱ የተሻለ ፍቅርና ርህራሄ በውስጤ አደረ። ችግሩ እኔ ሳልሆን እርሷ መሆኑን ለማስተዋል አቅም አግኝቻለሁና።
ወዳጆቼ በሚገጥሙን ጉራማይሌ መልክ ባላቸው ሁነቶች ውስጥ በምንመለከተውንና በምንሰጠው ግብረ መልስ ላይ ጠንቃቆችና ብልህ መሆን ጠቃሚ ነው። የሚጠሉን ሰዎች ሲገጥሙን የሚወዱንን እንቁጠር። ሕይወት ጨለምለም ያለ ገጽታዋ ሲበረታ ጭልጭል በሚለው ብረሃን ላይ አይናችንን እናድርግ። ስላልሆነና ስለጎደሉ ነገሮች ከማጉረምረም ስላገኘናቸውና ስለተሳኩልን ነገሮች እናመስግን። በተቻለ መጠን በአሉታዊ የሕይወት ንጽረት ላለመወሰድ እንጠንቀቅ። አዎ የምናየውን እንምረጥ!
መልካም ዕለተ ሰንበት!
በተጓዝኩባቸው የሕይወት ጎዳናዎች የታዘብኩት ነገር ቢኖር አብዛኛው ነገር ተለዋዋጭ መሆኑ ነው። ሰው፣ ሁኔታው፣ዙርያ ገባው በሞላ በለውጥ እሽክርክሪት ውስጥ የተጣለ ይመስል ይለዋወጣል። ሌላው ቀርቶ እኔ ራሱ ምን ያህል እንደተለወጥኩ ሳስብ መገረም ይቀድመኛል። የቀንና የሌሊት ያህል የጎላ ለውጥ.......
በዚህ ሁሉ ጉዞዬ ካለለውጥ ስለቀለጠ ነገር ሳስብ ሁለት ነገር አስተውላለሁ። የመጀመሪያው እግዚአብሔር ነው፤ ትናንት እንደሆነው ዛሬም ያው መሆኑ! ሁለተኛው በእግዚአብሔር "ያውነት" ላይ ያለኝ እውቀት ነው። ከመቅጽፈት ሁሉ በሚለዋወጥበት ዓለም በሁኔታ ከመዋዠቅ ይልቅ እየጸና የሄደ መረዳት፤ አዎ የእግዚአብሔር አለመለወጥ!
https://t.me/Yeroreflect
ዓድዋ ታሪክ ብቻ አይደለም!
ዓድዋ ለነጻነትና ለክብር ሲባል በሃይል ከላቀና በጉልበት ከበረታ ሠራዊት ጋር ለመፋለም የመድፈርና የሚከፈለውን ዋጋ ሁሉ ከፍሎ ድልን የመቀዳጀት ህያው አሻራ ነው።
ዓድዋ ድል ብቻ አይደለም፤ ዓድዋ ሃቃችንም ነው። የእኛ ብቻ ሳይሆን በገዛ ሃገራቸውና በወንዛቸው የቀኝ ግዛት ቀንበር ስር ወደቀው ለነበሩ ሁሉ ሃቅ ነው።
እንኳን 129ኛው የዓድዋ ድል በዓል አደረሳችሁ!
"Unexpressed emotion will never die. They are buried alive and they will come forth later in uglier ways."
Sigmund Ferud
ከአስር ወር ገደማ በኋላ ዳግም ተመልሼለሁ። በትዕግስትና በታማኝነት መጠበቃችሁን አለማመሰግን ንፉግነት አይሆንም? ወደሚቀጥለው.... አብረን እንዝለቅ!
https://t.me/Yeroreflect
" እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን፥"
(ወደ ዕብራውያን 10:19-20)
በሰዎች ሕይወት ላይ የታሰበበት አሉታዊ ተጽዕኖ ከማሳረፍም ሰዎችን ደስ ለማሰኘት የሰዎች አሉታዊ ተጽዕኖ ተቀባይ ከመሆን ተጠበቁ።
ለማግባት ስታስቡ....
"ለማግባት ዝግጁ ነኝ?" ከሚለው ጥያቄ በፊት በትክክል መመለስ ያለባቸው ጥያቄዎች እንዳለ ይሰማኛል።
"ፍቅር ለመስጠትና ለመቀበል ዝግጁ ነኝ?
ላካፍለው የምችለው በቂ ፍቅር አለኝ? የሚሰጠኝን ፍቅር ለማጣጣም አቅሙን አለኝ? እንዴት እንደምወድ እንዴትስ መውደድ እንደሚገባኝና እንዴት መውደድ እንሚኖርብኝ በስረዓቱ ለይቼ አውቃለሁ?
እንዴት ልወደድ እንደሚገባኝ፣ እንዴት ልወደድ እንደሚኖርብኝስ በስረዓቱ እረዳለሁ?
ከዚህ ሁሉ አስቀድሜ ለራሴ ፍቅር እንዳለኝ፤ ለራሴ ትክክለኛ ዋጋ እንደምሰጥ አረጋግጬለሁ?
በአጠቃላይ ምን መስጠት ይኖርብኛል?
ምንስ መስጠት እችላለሁ?
ምን መቀበል እፈልጋለሁ?
ምንስ መቀበል ይኖርብኛል?
ከልብ የሆነ ይቅርታ ለመጠየቅና ይቅርታ ለማድረግ ልቤን አበረታለሁ?
እነኚህና መሰል ጥያቄዎችን በትክክል ሳንመልስ፤ መልሳችንም ግልጽና አዎንታዊ ሳይሆን ጋብቻን ማሰብ ተገቢ አይመስለኝም።
ማግባት ቀላል ነገር ነው፤ ከአዳም ጀምሮ አባቶቻችን ሲያገቡ....ሲያገቡ....ሲያገቡ ነው የኖሩት። መጋባት የኖረ ነው ወደፊትም የሚኖር ነው። በዚህ ምድር ላይ ከማግባት ይልቅ አለማግባት የሚከብድ ይመስለኛል። እንኳን ጋብቻ ተፈልጎ "ትዳር አትስጠኝ" ተብሎ ተጸልዮም ያለማግባት እድሉ በጣም ጠባብ ነው። ካላገቡ ሰዎች ይልቅ ያገቡ ሰዎች ቁጥር እጅግ ይልቅብን የለ። ስሜት፣ የማህበረሰብ አኗኗር፣ በዙሪያቹ ያሉ ሰዎች ግፊት....ወዘተ ሳታውቁት እያካለባችሁ ጋብቻ በር ላይ ያደርሳችኋል። ለማግባት ማግባት መፈለግ የግድ አይመስለኝም፤ ብዙዎች የግድ ታገባላችሁ፤ አዎ የግድ እናገባለን። ግን ለምንድን ነው የምናገባው? ማግባት ስላለብን? ሰዎች ስላገቡ? ማግባት የተፈጥሮ ስረዓት ስለሆነ? ብቸኝነት ምቾት ስለነሳን? ልጆች መውለድ ስለሚኖርብን? አግቡ እየተባልን ስለምንጨቀጨቅ?
ወይንስ በቂና የተትረፈረ ፍቅር ስላለን? መውደድ፣ መንከባከብ (care)፣ ማገልገል፣ መጠበቅ (protect)፣ ማገዝ (Support)ና ለእኔ ላልነው መኖር ስለምንፈልግ? የምንሰጠው ነገር ስላለንና መስጠት ስለምንችል? እነዚህን ነገሮች ለአጋራችን ለመስጠት የተዘጋጀነውን ያህል እኛም መቀበል ስለምንፈልግና መቀበል ዝግጁ ስለሆንን?
ስለጋብቻ ከማሰብ በፊት ከላይ ያነሳናቸውን ጥያቄዎች መመለስ እጅግ ጠቃሚ ይሆናል። እናም ራሳችሁን ጠይቁ!
"You're rare, So people are gonna fall in love with the idea of having you, but most of them aren't used to rare, they're foreign to it, so they'll lack the capacity to treat you as such. And that's where they lose you."
"No amount of admiration for another human being can justify sacrificing one's judgment."
Nathaniel Barnden
ፍቅረኛዬ ስንገናኝ ስልክህን flight mood ላይ የምታደርገው የምትደብቀኝ ነገር ስላለ ነው ብላ ስትቀውጠው ከርማ ተጣላችኝ። እንዲሁ ከመሬት ተነስታ፤ በዚሁ ተልካሻ ምክንያት። አሁን ይሄ ምክንያት ይሆናል?
ሁሌም ሳገኛት ስልኬን flight mood ላይ አደርገዋለሁ። በዚህ ጉዳይ በርከት ላሉ ጊዜያት አውርተንበት እናውቃለን።
የመጀመሪያ ቀን...
እርሷ:- ውዴ ለምንድንነው ስንገናኝ ሁሌ ስልክህን flight mood ላይ የምታደርገው?
እኔ:- የእኔ ቆንጆ ለአንቺ የምሰጠውን ጊዜ ማንም እንዲሻማ ስለማልፈልግ ነው።
አርሷ:- አመሰግናለሁ የእኔ አሳቢ...ብላ ነበር።
ግን ለምን እንደሆነ እንጃ ይህ ጉዳይ ውሎ እያደረ እየከነከናት በተደጋጋሚ መጠየቋን ተያያዘችው....(ያው ስሟን በክፉ ላለማንሳት መጠየቋን አልኩ እንጂ መነዝነዟን ቢባል ነው የሚሻለው)። ቆይታ በመጨረሻው ቀን "ሁለተኛ እኔን ስታገኘኝ ስልክህን ከ flight mood ላይ አንስተህ እኔ ጋር ነው የምታስቀምጠው።" አለች ቆጣ ብላ።
"እንዴ የውጫሌ ስምምነት?" አልኩ።
ግን እንደምንም ብዬ ራሴን አረጋግቼ መተማመን በመካከላችን ሊሰፍን እንደሚገባ ለማስረዳት ብሞክርም "ወይ ፍንክች! ሙቼ ካልተገኘሁ" አለች
"ይህን ያህል መተማመን ካልቻልንማ እንዳልሽ።" ብያት በሠላም ተለያየን። ያው በሰላም አልኩት እንጂ እርሷ ብዙ ነገር ብላኛለች፤ ካለ ስሜ ስም ሰጣኛለች። "አይታመነም" ትላለች አሉ። ብቻ ምን አለፋችሁ ዋናው መለያየታችን ነው።
ወዳጆቼ መተማመን ከሌለና መጠራጠር በግንኙነት መካከል ከሰፈነ አስቸጋሪ ነው፤ የእርሷ ግን ከሌሎቹ የተለየ ነው። አሁን ሶስቱ ፍቅረኞቼ አንድም ቀን እንደ እርሷ ተጠራጥረውኝ ሆነ ስለ ስልኬ ጠይቀውኝ አያውቁም፤ እጅግ አድርገው ያምኑኛል። ወንድሞቼ ከተጠራጣሪ ሴት ይሰውራችሁ¡
ምክሩ ግን ለሴት እህቶቼ ነው!
ካመሸሁበት ወደ ቤት ስገባ አባቴና እናቴ ቁጭ ብለው ቴሌቪዥን ያያሉ። ኢቲቪ መዝናኛ ላይ "ይህም አለ" የሚል ፕሮግራም ይተላለፋል። በመሃል ከዜና አቅራቢዋ
"በኢጣሊያን ከእናታቸው ቤት አልወጣም ያሉ ጎልማሳ ልጆች በፍርድ ቤት ውሳኔ ተባረሩ" የሚል ዜና ሰማሁ። በመጀመሪያ ዜናው አስገርሞኝም አስቆኝም ነበር። ልክ አባቴና እናቴ ዜናውን ስምተው እርስ በእርሳቸው ሲተያዩ ነው ሳቄ በኖ የጠፋው። እይታቸው ውስጥ "ለካስ እንዲህም ማድረግ ይቻላል።" የሚል አይነት ግርምት ነበረው።
"ምን አይነት ዜና ነው?" አልኩ መልሼ። ይሄ አመጽ መቀስቀስ ነው። በፍቅር ተዋዶና ተጋምዶ የኖረን ቤተሰብ መለያየትና መከፋፈል እየተሰበከ ነው። ኧረ መጨካከን፤ ሚዲያዎቻችን ግን ወዴት ወዴት እየሄዱ ነው?
ለማንኛውም ይሄ ነገር ከቁጥጥር ሳይወጣ ለማስተባበል ጣልቃ ገባሁና "ድሮም ኢጣሊያናዊያን እጅግ አስቸጋሪ ናቸው። የእኛንም ሃገር ከአንድ ሁለቴ ለመውረር መጠው ስትን ጉድ ሰርተው....." አባቴ አላስጨረሰኝም "እሽሽሽሽ....ዜና እናዳምጥበት" አለኝ
እዚህ ቤት ውስጥ ተወልጄ አድጌ "እሽሽሽ...." ስባል ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነው።
መብራት ሃይል ምናለበት መብራቱን ድርግም አድርጎ ውለታ ቢውልልኝ? ጋዜጠኛዋስ ቶሎ ብትጨርስ ምን ነበረበት? ጭራሽ ፈገግ ብላ ዝርዝሩን ማንበብ ቀጠለች። ከዚህች ጋዜጠኛ ጋርማ የሆነ የኋላ ታሪክ ይኖረን ይሆን እንዴ? የእኔ ነገር አይታወቅ ብዬ....አስተውዬ ብመለከታትም አላውቃትም። አያያዟ ከእኔ ጋር የግል ጸብ ያላት ነው የሚመስለው።
ጭራሽ ዜናው ስታጠቃልል "ፍርድ ቤቱም ጎልማሳ ልጆቼ ከቤት ይባረሩልኝ በሚል ከወላጅ እናታቸው የቀረበለትን አቤቱታ ተቀብሎ ጎልማሶቹ ከቤት እንዲባረሩ መወሰኑ ተገልጿል፡፡" በሚል ቋጨችው። እርፍ!
አባቴና እናቴ በድጋሚ ፈገግታ በተሞላበት ሁኔታ ተያዩ፤ አሁንኛው ላይ አባቴም አንገቱን ወደታችና ወደላይ እየነቀነቀ ነበር። "አሁን ገባኝ" ይመስላል።
"ኧረ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ባለስልጣን....
ኧረ የሳንሱር ያለ...." አጉተመተምኩ።
ያን እለት ማታ ጸጥታ በዋጠው ቤት እራት ተበልቶ በሠላም ታደረ....አይ አይ እኔ እንኳን በሠላም አላደርኩም፤ ሌሊቱን እንዲሁ ሲያቃዠኝ ነበር ያደረው። ጠዋት ላይ ሀገር ሰላም ብዬ ተሰነስቼ ወደ ሳሎን ስገባ አባቴ ነጭ ወረቀት ይዞ ማመልከቻ ነገር እየጻፈ ደረስኩ።
ቀልባችሁ ግፍፍ ይበል!
"ባለህበት ቁም" የተባለ ሰው ይመስል በቆምኩበት ደርቄ ቀረሁ፣ ብርድ ብርድ አለኝ፣ እግሬን ብርክ ብርክ አለኝ።
አባቴ በጠቋሚ ጣቱ መነጸሩን ዝቅ አድርጎ ሲመለከተኝ "እስካሁን እዚሁ ቤት ውስጥ ነህ? ድፍረትህ!" ያለኝ መስሎ ተሰማኝ።
በተከበርኩበት ከተማማ ተከስሼ ከዚህ ቤት በፖሊስ ተጎትቼ ወጥቼ ለእነዛ "እስከመቼ የቤተሰብ ጥገኛ ሁነህ ትኖራለህ?" እያሉ ለሚነዘንዙኝ ሰዎች የወሬ ርዕስ አላበረክትም፤ ማን ደስ ይበለውና? እንደተከበርኩ ሹልኩ ብዬ.....ጓዜን ጠቅልዬ... እየወጣሁ ነው....ጓዜን አልኩ ያው ያለኝን ለማለት ነው።
ለማንኛውም የሚከራይ ቤት ካለ ንገሩኝ።
ቆንጅዬ፣ ወጣትና ያላገባች የቤት አከራይ ብታገኙልኝ ደግሞ ወሮታውን ከፋይ ነኝ።
@Yero_Insights
ከድሬደዋ ወደ አዲስ አበባ በሚበረው አይሮፕላን ገብቼ ወንበሬ እንዳያዝኩ ከኋላዬ ጠይም ቆንጅዬ ልጅ ተከትላ አጠገቤ ተቀመጠች። የልጅቷን ውበት ስመለከት ከድሬ አዲስ የአንድ ሰዓት ገደማ በረራ ብቻ በመሆኑ አዘንኩ። ምናለበት አስር ሰዓት ቢሆን? ምናለ እያረፍን በስሶት በአራት ቀን ብንጓዝ? የምን መጣደፍ ነው? አልኩ በውስጤ።
አይሮፕላኑ አኮብኩቦ ሲነሳ ከልጅት ጋር ወሬ ጀመርኩ። ደግሞ ለወሬ ማን ብሎኝ ።በጫወታችን መሃል ለስራ እየተጓዘች መሆኑ ስረዳ
"አዲስ አበባ ነው ስራ ቦታሽ?" ጠየኳት
"አይ አይደለም፤ አዲስ ለራሴ ጉዳይ ለቀናት ነው የምቆየው፤ ለስራ የምጓዘው ወደ ቤኒሻንጉል አሶሳ ነው፤ እሁድ ወደ አሶሳ እበራለሁ።"
አብረን ዘላቅና አልኩ በልቤ፤ ለእርሷ ግን አልነገርኳትም።
"አሶሳ ከዚህ በፊት ሂደሽ ታውቂታለሽ ወይስ የመጀመሪያሽ ነው?"
"ኧረ የመጀመሪያዬ ነው፤ የማውቀው ሰው እንኳን የለም።"
እያወራን እየተጫወትን ወደ መዳረሻችን እየደረስን መሆኑን አብራሪው ሲናገር፤ ስልኳን መቀበል እንዳለብኝ አስታወስኩ፤ አብራሪው ወደ መዳረሻችን መድረሳችንን ሳይሆን ልትለያዩ ስለሆነ ስልኳን ተቀበል ያለኝ ያህል ነበር የተሰማኝ። እናም ስልኳ ቁጥሯን ጠየኳት፤ በአክብሮት።
"ኧረ ባክህ? ምን አይነቱ ደፋር ነህ ባክህ።".....አላለችም፤ ግን ፊቷ ላይ ያነበብኩት ከዚህ የተለየ አልነበረም። እንደ ማቅማማት ብላ ስልክ ቁጥሯን መናገር ጀመረች
0912..... እየነገረችኝ ያለችው ቁጥር የውሸት መሆኑ ውስጤ ሹክ አለኝ። ውስጤን ደግሞ አምነዋለሁ፤ አይዋሸኝም። ቁጥሩን ነግራኝ እንደ ጨረሰች
"ስምሽን ማን ልበለው?" አልኳት
"የፈለከውን በለ" አለች ሹፈት በተሞላበት አኳሃን።
ልጅቷ ዘጋችኝ፤ መልሼ ከድሬደዋ አዲስ አበባ በረራ በማጠሩ አመሰገንኩ፤ ከእንደዚህ አይነቷ ጋር በርከት ያለ ሰዓት መቀመጥ እጅ እጅ ይላላ። "ስታስጠላ" አልኩ ድምጼን ሳላሰማ
"ማስጠላት እንኳን አታስጠላም አለኝ" ውስጤ
"ካናደደች እንደ አስጠሊታ ትቆጠራለች አልኩት ለውስጤ። ውስጤ ዝም አለ ይፈራለኛል።
እና ወሬዬን ለመቋጨት ያህል ብቻ ፈገግ ብዬ "መልካም፤ ስልክሽ እንደሚሰራ ተስፋ አደርጋለሁ" አልኳት
አሁን ያንን የውሸትና የሹፈት ፈገግታ እያሳየችኝ "እንቢ ካለህም ደጋግመህ ሞክረው አንድ ቀን መስራቱ አይቀርም።" አለችኝ
ክፉ አልተናገርኩም። ልክ አይሮፕላናችን ቁልቁል ተወርውሮ ወደ መንደርደሪያው አርፎ ለመቆም ሲሰናዳ የመልሶ ማጥቃት እርምጃ ውስጥ መግባት እንዳለብኝ ተሰማኝ።
"በነገራችን ላይ እኔም ወደ አሶሳ እየሄድኩ ነው፤ አሁን በትራንዚት ወደ አሶሳ ነኝ" ብዬ "bording Pass"ን አሳየኋት። ወደ አሶሳ እንደምጓዝ ስታውቅ ደንገጥ አለች።
"የአሶሳ ልጅ ነኝ፤ እኛ አሶሳዎች ደግሞ እንግዳ አቀባበል ላይ አንታማም። እሁድ አይደል እመጣለሁ ያልሽኝ? እሁድ እደውልልሻለሁ።" ብዬ አይሮፕላኑ እንደቆመ ሻንጣዬን ከሻንጣ መስቀመጫው ለማውረድ ተነሳሁ።
ጓዜን ሸክፌ ወደ ቀጣዩ በረራ ለመድረስ እየተጣደፍኩ ከኋላ "የእኔ ወንድም....የእኔ ወንድም" የሚል ድምጽ ሰማሁና ዘወር አልኩ፤ ልጅቷ እየተከተለችኝ ነው። ወደ እኔ ቀርባ ፈራ ተባ እያለች
"የቅድሙ ስልክ ላይሰራልህ ስለሚችል ሌላ ስልክ ልስጥህ?" አለች እየተሸማቀቀች።
እኔም እርሷ ቅድም ያሰየችኝን አይነት ፈገግታ በተራዬ ፈገግ ብዬ "አታስቢ፤ ችግር የለውም እስኪሰራ ደጋግሜ እደውላለሁ፤..... ያው አንድ ቀን መስራቱ አይቀር።" ብያት በቆመችበት ትቼት ጉዞዬን ቀጠልኩ። አሁን ከዚህ በላይ ሌላ ደስታ ምን አለ ጎበዝ?
@Yero_Insights
ስትሰክር ደስ ይለኝ ነበር....
ስካርታም ነች፤ ምንም እንኳን የሰከረች ቀን ሰፈሩን በሞላ እንቅልፍ ብትነሳም እኔ ግን ብቻዬን እደሰታለሁ። ሰክራ በመጣች ቁጥር በደስታ እጠብቃታለሁ። ምክንያቱም በውድቅት ሌሊት ሰፈሩ ሁሉ በግድ ተቀስቅሶ ለእኔ የሚቀርበውን የፍቅር ውዳሴ እንዲያደምጥ የሚገደደው ሰክራ ከመጣች ብቻ ነው።
ተከራይቼ ከምኖርበት ቤት ግድግዳ ብቻ የሚለየን ጎረቤቴ ነች። ስሟን አላውቀውም፤ በእርግጥ እርሷም ካልሰከረች እንዲች ብላ አታናግረኝም፤ቀና ብላም አታየኝም። ግቢ ውስጥ ካሉ ተከራዮች ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ቢኖራትም ከእኔ ጋር ግን እንደማይተዋወቅ ሰው እንኖራለን፤ እስካልሰከረች ድረስ። ከሰከረች ግን....
አሁን ባለፈው መስከረም አንድ ጎረቤቱን ሁሉ ቡና ስትጠራ እኔን አልጠራችኝም። "ሰካርታም ቤት ቡና ተጠራሁ አልተጠራሁ ምን ይቀርብኛል?" አልኩ ለራሴ፤ ባለመጠራቴ ግን ቅር ብሎኝ ነበር። ከቤታችን ፊትለፊት ከተሰደሩ ቤቶች ተከራይ የሆነው አንዱ ወጣት ከቤቷ ቡና ጠጥቶ ከወጣ በኋላ ያለመደበትን እኔ ቤት ጎራ ብሎ "በበዓል ቀን ቡና የሚጠራህ ጠፋ እንዴ አልጋ ላይ መገላበጥ?" አለኝ፤ ሽሙጥ መሆኑ ነው። ታዲያ ያን እለት ጎረቤቴ አመሻሽ ላይ ለባብሳ ስትወጣ ሳያት ሰክራ እንደምትመጣ በማወቄ ፈገግ አልኩ፤ "እኩለ ሌሊት ላይ ማን ወዳጅ እንዳለውና እንደሌለው ይታያል የለ" አልኩ በልቤ ያንን አብሽቅ ጎረቤቴን እያስታወስኩ።
ያልኩት አልቀረም እኩለ ሌሊት ላይ የውጪው በር "ጓ" አለ። ጎረቤቴ መጣች ማለት አይደል። ያንን የፍቅር ገለጻ መዓት፣ ያንን ከጎቤቶቼና አከራዮቼ ጋር ያዙኝ ልቀቁኝ ለመስማት ተዘጋጀሁ።
"አንተ ሰውዬዬዬዬዬዬ..." ጀመረች
"ቀን ቡና ስላልጠራውህ ተናደሃላ ሃሃሃ... ውይ ውይ እኔ ልናደድ፣ እኔን እኔን የእኔ ውድ። ና በቃ ላፍላልህ እስከ ሶስተኛ ድረስ ነው ማፈላልህ።...."
"ኧረ በቃ ዝም በይ ሰው ትረብሺያለሽ" አለቻት ያቺ ለዛ ቢስ ጎረቤቷ። አሁን ከስንት አንድ ቀን ለደቂቃዎች የግቢው ሰው እንቅልፉን ቢያጣ ምን ይቀርበታል? ጎረቤቷ አበሳጨጭኝ። የሰካራሞች መብት ይከበር ማለት ሁሉ ቃጣኝ። ደግነቱ ሰካራሟ ጎረቤቴ ስትሰክር ማንን አትሰማም።
"አቦ አንቺ ዝም በይይይይይይ፤ ቀን አንቺ አይደለሽ ቡና ልጥራው ስልሽ 'ተዪው የሆነ ኩራተኛ ነው።' ያልሽኝ። አንቺን ብሎ መካሪ፤ ምቀኛ......"
እየተንገዳገደች ወደ በሬ ተጠግታ በሬን እየመታች "ጎረቤቴ ቀን ቡና ልጠራህ ብዬ ፈርቼህ ነው። እውነት እውነት፤ ይህቺንም እንጥራው ብላት የበለጠ ይንቀባረርብሻል አለችኝ...አንተ ግን ምን አባህ ሁነህ ነው የምትንቀባረረው፤ የሆንክ ጉረኛ...ጉራ ብቻ.....ጉራ ብቻ........"ከበሬ እየራቀች መጣች...
ግና ተመልሳ ወደ በሬ መጣችና በሬን መልሳ እየደበደበች
"ግን ግን ግን ቀብራራነትህን እኮ ነው የምወደው። የምር ሃሃሃሃ ...የሆነ እንዲህ ብለህ የምትኮሳተረው ነገር ስወደው ሃሃሃሃ..። ባለፈው እንደዛ ተኮሳትረህ አጠገባችን ስታልፍ ቤኪ ምን አለች መሰለህ....." ሳትጨርስ የትልቁ ቤት በር ተከፈተ። አከራዮቼ እንደለመደባቸው አባብለው ሊያስገቧት መሆኑ ነው።
አከራዮች በጣም ይወዷታል። እንደዛ ሰክራ ሰፈር እያመሰች ፊታቸውን ራሱ አያጠቁሩባትም። እንደውም ሰክራ መጣ በእኔ ምክንያት ግቢውን ስለምትበጠብጥ እኔን ልቀቅ ለማለት ይከጅላሉ።
"ጋሼ ጋሼ እንኳን መጡ እንደውም ስፈልጎት ነው የመጡት፤ ይህንን ዝጋታል ልጅ ዛሬ ወጦ ከእኔ ምን እንደሚፈልግ ይንገረኝ፤ ና ውጣ አንተ....አንተን እኮ ነው። ይኸው ጋሼ መጠዋል"
"ሲነጋ እርሱን ቁጭ አድርገን አንድ በአንድ እንዲናገር እናደርገዋለም። አሁን ግን ከብርድ ላይ ወደ ውስጥ ግቡ።" አሉ ጋሼ
"እንብዮ ጋሼ ወጦ ካላናገረኝ አልገባም፤ ምን እንደሚያመጣ አያለው። ቱ አልገባም።"
በስንት መከራና ልመና ወደ ቤቷ ለመግባት ከተስማማች በኋላ "አንተ ተስማለህ አይደል፤ አውቀህ እንደተኛ ሰው አታስመስል እሺ፤ አስመሳይ፤ እየሰማህ ነው አውቃለሁ። እኔ ልጅት የምፈራ መስሎህ ነው? ማንንም አልፈራም እሺ፤ ብትኮሳተር ብትንቀባረር I don't care....." በሯ ላይ ደረሰች "ግን ጋሼ እወደዋለሁ እኮ......አንዴ ብቻ ይውጣና ልየው፤ አንዴ ብቻ"
"አሁን ተኝቷል ጠዋት ራሱ መጦ ያይሻል፤ አሁን ገብተሽ ተኚ" አሏት
"ሰክረሽ እየመጣሽ ማን ይወድሻል ብለውኝ ነበራ ባቡፈው... ግን'ኮ አሁን አልስከርኩም ትንሽ ብቻ የጠጣሁት። አንተ....ሰከራም አትወድም እንዴ? እእእእእ......? ዝጋታም......" ገብታ በሯን ዘጋች ተከትሎ የጎረቤቷ ቤኪ ቤት ተዘጋ በመጨረሻም የአከራዮች ቤት። የግቢው ነዋሪ በሙሉ ለተወሰኑት ደቂቃዎች ከእንቅልፉ ተቀስቅሶ ለእኔ የሚቀርበውን የፍቅር ውዳሴ አደመጠ። እፎይ...ደስ ሲል....ሰካራም አይጥፋ ብዬ ተኛሁ።
ይህንን ከመሰሉ ምሽቶች በኋላ በነጋታው ጠዋት ምንም እንዳልሰማ ምንም እንዳልተፈጠረ ኮስተር ብዬ እወጣለሁ። አርሷም ቀጣይ እስክትሰክር ድረስ እንዲች ብላ ቃል አተነፍስም። ሕይወት ይቀጥል ነበር....ነበር ነው።
ዛሬም ምሽት ላይ ለባብሳ ስተወጣ ሰክራ እንደምትመጣ አስቤ በጉጉት ጠብቄያት ነበር። አልቀረችም፤ እኩለ ሌሊት ላይ የውጪው በር "ጓ" አለ።እኔም ቀጣዩን ሁነት ለመከታተል ጆሮዬን አሰገኩ።
"ዳኒዬ.... ዳኒ አለም...ዳኒን ነው የምወደው...ዳኒ የእኔ ምርጥ..... የእኔ ቆንጆ..... እርሱን የማገባው......."
ቀልቤ ግፍፍ አለ። "ማን ነው ደግሞ ዳኒ?" አላውቀም። ውስጤ መከፋትና መረበሽ ጀመረ።
"ዳኒዬ ዳኒሻ የእኔ ተናፋቂ......" ቤቷ ተከፈተ፣ ገባች ።ከዚያም ተዘጋ። ጸጥታ ሰፈነ።
ለመጀመሪያ ጊዜ የጎረቤቴ ስካር ሲረብሸኝ ታወቀኝ። በሰካራም ምክንያት እንቅልፍ እንደተነሳሁ ተሰማኝ። ተበሳጨሁ "የማንም ጋጠወት በሌሊት እየመጣ ሰፈሩን ሲበጠብጥ ሃይ የሚል መጥፋቱ ገና ዛሬ ከነከነኝ። እነ ጋሼ ይህቺን ቦዘኔ ስረዓት ሊያስይዙልን ይገባል.....አሁንስ በዛ" አልኩ ለራሴ
"ቆይ ግን ዳኒ ማን ነው?" ይላል ውስጤ።
በእርግጥም ያናደደኝ ስካሯ ሳይሆን ዳኒ መሆኑ ውስጤ ቢገባውም ማመን አልፈለኩም። ልክ እንደ ብዙሃኑ ሁሉ ምንም ነገር ለመውደድም ሆነ ለመጥላት ከነገሩ ምንነት ይልቅ ለራስ ከሚሰጠው ፋይዳና ከራስ ማዕከላዊነት አንጻር የማየት አባዜ ሳይጠናወተኝ አንቀረም።
@Yero_Insights
በሰዎች መካከል እንደ እባብ ልባም በእንደ እርግብ የዋህ.....
መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ በኩል እንደ ናታን ዳዊትን እንደ ነፍሱ አድርጎ የሚወድና የሚሟገትለት ቅን፤ እንደ ሩት ምራቷን ኑሃሚንን "ሕዝብሽ ሕዝቤ አምላክሽ አምላኬ" ብላ እንግዳ ወደሆነ ምድር አብራ ለመሆን የምትከተል አይነት ወዳጆችን የምንመለከትበት ሲሆን በሌላ በኩል እንደ ቃየን ከመሠዊያ መልስ ወንድሙን የሚገድል፤ እንደ የዮሴፍ ወንድሞች የገዛ ወንድማቸውን ነፍስ ለማጥፋት ጉድጓድ የሚጥሉና አሳልፈው የሚሸጡ ሰዎችን ክህደት እንመለከትበታለን።
ከሰዎች ጋር በሚኖረን መስተጋብር እነዚህን ሁለቱንም ጎራዎች መኖራቸውን ካላወቅን ቀሊል ያይደለ ዋጋ እንከፍላለን። መልካም የሚሆኑላችሁ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ የሚከፉባችሁ መጥፎ ሰዎችም መኖራቸውን መዘምጋት አይገባም። ሁሉም ሰው መጥፎ፤ ሁሉም ደግሞ ደግ ሊሆንላችሁ አይችልም።
እግዚአብሔር ሲወዳችሁ አንዱ የሚባርካችሁ በሰዎች ነው። በሕይወታችሁ ውስጥ አብረዋችሁ የሚቆሙ፣ የሚዪግዙችሁ፣ የሚረዷችሁና ለእናንተ ብለው ዋጋ የሚከፍሉ ሰዎችን ይሰጣችኋል። ዙሪያችንን ስንመለከት ከእኛ ከተቀበሉት ይልቅ ለእኛ የሰጡት ሚዛን የሚደፋ፤ ያልተገደበ ፍቅር ያሳዩን፣ በፈለግናቸው ጊዜ የተገኙልን ወዳጆች አሉን። በአንዳንዶች ውስጥ ምክንያት አልባ ፍቅር እንመለከታለን፤ ካለምንም ምክንያት ይወዱናል፤ እየተበደሉ ይቅር ይሉናል።
በእርግጥ አንዳንዴ ይህ አይነት መልካም ወዳጅነት ጨለምተኛ በሆነ ንጽረታችን በከዱንና በጎዱን ሰዎች ተሸፍኖ የወዳጆቻችንን ብርቱ ወዳጅነት መልክ ያጠፋብናል። ምክንያቱም እኛ ሰዎች አንዳንዴ ከአዎንታዊው አሉታዊውን ማየት ይቀለናልና ነው። አስተውለን ከተመለከትን ግን እነኚህ ወዳጆቻችን በዙሪያችን መኖራቸው አይቀሬ ነው። ቆም ብሎ ዙሪያገባውን መቃኘትና መልካም ወዳጆቻችንን መለየት፣ ስለ እነርሱም አመስጋኝ መሆንና ለእነርሱ የሚገባውን ስፍራ መስጠት በእጅጉ ይጠቅማል። በመልካም ወዳጆች ተከበን ራስን እንደ ባይተዋር መቁጠር መልሶ ውስጥን ስለሚጎዳ።
በሌላ በኩል ግን ከክፉ ባለእንጀሮች ራስን መጠበቅ መረሳት የለበትም። እንደ ቃየል በስኬታችሁ ፊታቸው የሚጠቁር፤ እንደ የዮሴፍ ወንድሞች በወንድማቸው ሕልም ጥላቻቸው የሚበረታ ስታዩ ርቀትን መጠበቅ ግዴታ ይሆናል። በእርግጥ አንዳንዶች በማስመሰል የተካኑ ናቸው፤ በዚህ አስመሳይነታቸው አሉን ከምትሏቸው ወዳጆቻችሁ ዝርዝር ውስጥ ግንባር ቀደም ልታደርጓቸው ትችላላችሁ። በደስታችሁ ማይደሰቱ ወይም ደስታችሁኝ የሚያደበዝዙበት አስተያየት ጣል ማድረግ የሚያዘወትሩ፤ ስታዝኑ ከፊታቸው ፈገግታ የሚነበብ አሊያም ከንፈር መምጠጣቸው የውሸት ሲመስል፣ ከጀርባችሁ ሲያወሩ ስታገኟቸው፣ የቀናውን ምክራችሁ ማጣጣል ሲቀናቸው ስታዩ ይህንን ወዳጅነት ቆም ብላችሁ ማጤንን መምረጥ አለባችሁ።
አዎ ሁልጊዜ ዙሪያ ገባችሁን በአስተውሎት ተመልከቱ። ከሕይወታችሁ መራቅ ያለባቸውን ከሕይወታችሁ ለማራቅ አትፍሩ። በዘመን የማይተኩ ብርቅዬ ስጦታዎቻችሁና በረከቶቻችሁ የሆኑ ወዳጆቻችሁን ደግሞ የሚገባው አክብሮትና ጊዜ ስጡ። አዎ ደግሜ እላለሁ፤ ከሰዎች ጋር ባላችሁ ግንኙነች እንደ እባብ ልባም እንደ እርግብ የዋህ መሆንን ምረጡ!
"People are not your most important asset. The right people are."
Jim Collins
"All too many people have seen power and love as polar opposite..... [But] the two fulfill each other. Power without love is reckless, and love without power is sentiment."
Martin Luther King
"የአብርሃምና የሥራ ያድርግላችሁ"
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ከማልስማማበትና ከማልደሰትበት የጋብቻ መልካም ምኞት ውስጥ አንዱና ዋናው "ጋብቻችሁን የአብርሃምና የሥራ ያድርግላችሁ" የሚለውን ነበር። እንዴት ሰው የአብርሃምንና የሥራን አይነት ትዳር ለሰው ይመኛል ብዬ እጠይቅ ነበረ። አንዳንድ ጊዜ እንደ ምርቃት ሳይሆን ሙሹሮቹ ላይ እንደማሟረት ያህል ተሰምቶኝ ያውቃል።
በእርግጥ በአንድ በኩል እውነት ነበረኝ። የአብርሃምና የሳራ ቤት በብዙ ነገር እንደተፈተ አውቃለሁ። አንዳንዱ ፈተና ለመቀበል የሚከብድ አይነት ነበር። ለምሳሌ በምድር ረሃብ በሆነበትና በእንግድነት ለመቀመጥ አብርሃም ወደ ግብጽ ባቀናበት ጊዜ "መልከ መልካም ስለሆንሽ በአንቺ ምክንያት ይገድሉኛልና እህቱ ነኝ በይ፤ ስለአንቺ ህይወቴ ትድን ዘንድ" ብሎ ራሱን ለማትረፍ ሚስቱን የፈርዖን ሚስት ተደርጋ ልትወሰድ እስከምትችልበት ሁኔታ ላይ ትቷት ያውቃል።
ይህ ብቻ አልነበረም፤ የአብረሃምና ሥራ ቤት ልጅ በማጣትም ተፈትኗል። እግዚአብሔር ዘርን እባርካለሁ ብሎ ተስፋ ገብቶለት የአባቱን ሃገር ለቆ አምላኩ ወዳሳየው ሃገር ቢጓዝም ልጅ ሳያገኙ እርጅና ተጫጭኗቸዋል። ይስሃቅ እስከተወለደበት ድረስ ለረጅም ዘመናት ልጅ በማጣት ተፈትነዋል።
በዘህ ቤት ልጅ ማጣታቸው ግን ከፈተና በዘለለ ሌላ ፈተና አስከትሏል። አብረሃም በሚስቱ በሳራ ምክርና ግፊት ወደ አጋር (አገልጋያቸው) ገብቷል። አጋር ግን ከጸነሰች በኋላ ሥራን አቃለለቻት፤ ይሄ ደግሞ ለሥራ ንዴት ከአብርሃም ጋር የመጨቃጨቂያና የመካሰሻ ምክንያት ሁኗል። ይሄ ግጭትና ጭቅጭቅ ይስሃቅ ከተወለደ በኋላም ቀጥሎ እናየዋለን።
ታዲያ በዚህ ሁሉ ነገሮች የተፈተነን ትዳር በምን ሂሳብ "የአብርሃምና የሥራ ጋብቻ ያድርግላችሁ" በረከት ይሆናል? ሊዋጥልኝ አይችልም ነበር። በጊዜ ሂደት ግን አባቶች ታጋቢዎችን ለምን የአብርሃምና የሳራ ያድርግላችሁ እንደሚሉ ይገባኝ ጀመር። ምርቃቱ እንደ አብርሃምና ሥራ ፈተና የበዛበት ትዳር ይስጣችሁ ለማለት ሳይሆን የጋብቻን እውነታ ያገናዘበ ነበር።
ጋብቻ ሁሌ ፍቅርና መተሳሰብ፣ ሁሌ መሳሳቅና ዘወትር የተቃና የኑሮ መደላደል ያለበት ላይሆን ይችላል፤ በእርግጥም አይደለም። የጋብቻ ሕይወት ፈተና አልባ ይሆናል ብሎ መጠበቅ ሞኝነት ነው። ታዲያ ፈተና ለማያጣው የጋብቻ ሕይወት ጥሩ ምርቃት እንደ አብረሃምና እንደ ሥራ በብዙ ነገር ተፈትኖ፤ ጆሮን ጭው በሚያስብል ውድቀት ሁሉ መሃል ጸንቶ የሚቆም ጋብቻ ነው።
የእነ አብርሃም ቤት በእነዛ ሁሉ ነገሮች ውስጥ አልፎ አልተናደም። ቤቱ ሊፈርስባቸው የሚያስችሉ ብዙ ክፍተቶች ቢኖሩም ቤቱ እንዲፈርስ አልፈቀዱም። ሥራ የፈርኦን ቤት የንጉስ ሚስት ሁኗ መቅረትን አልመረጠችም፤ አብርሃም በእርጅናው ልጅ የሰጠችውን አጋርን አልመረጠም። በብዙ ፈተና ወድቀው ቢነሱ አልተነጣጠሉም አልተለያዩም። በዚህ ሁሉ ነገር ውስጥ ጸንተው መቆም ችለዋል። እንደ አብርሃም እንደ ሥራ ያድርግላችሁ ሲባል እንደ እነርሱ ተፈተኑ ማለት አይደለም፤ ይልቁንስ በብዙ ፈተናና መውደቅ መነሳት መሃከል በአብሮነት ጸንታችሁ የምትቆሙ ሁኑ ማለት ነው። ዬትኛውም ፈተና ዬትኛውም ውድቀት አይለያችሁ ማለት ነው። በእርግጥም ይህ ከምርቃት በላይ ምርቃት ከበረከት በላይ በረከት ነው።
@Yero_Insights
በሕይወታችን ትላልቅ ሞኝነቶችን አለፍ ሲልም ውድቀቶችን የምናስተናግደው ከእግዚአብሔር የተሻለ ለራሳችን እንደምናስብ በሚሰማን ወቅት ነው።
"If people take action that seems out of character, you will take note: what often appears out of character is actually more of their true character."
Robert green
