uk
Feedback
"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

Відкрити в Telegram

@Dan12bot ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

Показати більше
1 134
Підписники
Немає даних24 години
-27 днів
-2330 днів
Архів дописів
#ሆሳዕና (የዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት) ሆሣዕና ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ተብሎ የሚጠራ ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መገቢያ ዋዜማ ነው። ሆሣዕና አስቀድሞ ካለው ረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። ይህን ስም በዚሁ ሰንበትና በዋዜማዎቹ ዕለታት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ‘ሆሣዕና በአርያም’’ ‘ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት’’ ‘ዕለተ ሆሣዕናሁ አርዓየ… ‘ ወዘተ. በማለት ሆሣዕና የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድና ሌሎችም አባቶች በየቦታው እየጠቀሱና እየተዘመረለት በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ እየተረከ ስለሚዘምር ይህ ሰንበት በጌትነትና በክብር በውዳሴና ቅዳሴ ሆሣዕና በአርአያም እየተባለ በሽማግሌዎችና በሕፃናት አንደበት በድንጋዮችም ልሳን ሳይቀር እየተመሰገነ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በከብር ሲገባ ለሰጣቸው ለተቀደሰ ሰላሙና ፍቅሩ መታሰቢያ ሆኖ የተሰጠ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሌላ ቀን እንደ ተራ ሰው ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ይገባ ነበር፡፡ በዚህ ቀን ግን የአይሁድ ንጉሥ ሆኖ በክብር ገባ፡፡ ከቢታንያ ተነሥቶ ደብረ ዘይት ሲደርስ ከሐዋርያቱ ሁለቱን በቤተፋጌ ሰው ተቀምጦባት የማያውቅ ውርንጭላ እንዲያመጡለት ላካቸው፡፡ “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሒዱ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርሷ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁም አምጡልኝ፡፡ ማንም አንዳች ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ" አላቸው፡፡ ማቴ.21፡1-17 ወደ ቤተፋጌም ሄደው አህያዪቱን አገኙአት፡፡ ሲፈቱአትም ሳለ ባለቤቶቹ መጡባቸውና አስቆሟቸው፡፡ እነርሱም ኢየሱስ እንደፈለጋት ነገሩአቸው፡፡ ባለቤቶቹ ይህንን ሲያውቁ ተዋቸው፡፡ ሐዋርያትም የአህያዪቱን ውርንጭላ ፈትተው ወደ ኢየሱስ ወሰዱ፡፡ አጠገቡም ሲደርሱ ልብሳቸውን በአህያዪቱ ውርንጭላ ላይ አንጥፈው ኢየሱስን አስቀመጡት፡፡ #ለምን_ዘንባባ_ያዙ_ቢባል፡- ዘንባባ እሾሃም ነው ፤አንተም የኃይል የድል ምልክት አለህ ሲሉ፤በሌላም በኩል ዘንባባ እሳት ለብልቦ ይተወዋል እንጂ አይበላውም አንተም ባህርይህ አይመረመርም ሲሉ፤አንድም ዘንባባ ረጅም /ልዑል/ ነው አንተም ባሕርይህ ልዑል ነው ሲሉ ዘንባባ ይዘው ተቀብለውታል፡፡ #የተምር_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡- ተምር ፍሬው አንድ ነው አንተም ባህርይህ አንድ ነው ሲሉ፡፡አንድም፤ተምር ልዑል/ረጅም/ ነው አነተም ልዑለ ባህርይ ነህ ሲሉ፡፡ አንድም፤የተምር ፍሬው በእሾህ የተከበበ ነው በቀላሉ መለቀም አይቻልም ፤ የአንተም ምስጢር አነተ ካልገለጠከው አይመረመርም ሲሉ ነው፡፡ #የወይራ_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡- ወይራ ጽኑዕ/ ጠንካራ/ ነው አንተም ጽኑዓ ባህርይ ነህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ለመስዋዕት ይሆናል፤ አንተም መስዋዕት ትሆናለህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ዘይቱ ለመብራት ይሆናል አንተም የዓለም ብርሃን ነህ ሲሉ ይህንን ይዘው አያመሰገኑ ተቀበሉት፡፡ #ልብሳቸውንም_ማንጠፋቸው፡- እንኳን አንተ የተቀመጥክባት አህያ እንኳን መሬት መርገጥ አይገባትም ሲሉ ልብሳቸውን አነጠፉለት፡፡ እነዚያ ያላመኑ አይሁድ ለተቀመጠባት አህያ ይህንን ያህል ክብር ከሰጡ፤ በድንግልና ጸንሳ ለወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምን ያህል ክብር ልናድረግለት ይገባን ይሆን?፡፡ #የዕለተ_ሰንበት_መዝሙር (ከጾመ ድጓ) ወእንዘ ሰሙን በዓለ ፋሲካ ቀርቡ አርዳኢሁ ለአምላከ ጽድቅ ኀበ ደብረ ዘይት ሙራደ ዓቀብ ሀገረ እግዚአብሔር ወተቀበልዎ ሕዝብ ብዙኃን አዕሩግ ወሕፃናት ነሢኦሙ አዕፁቀ በቀልት እንዘ ይብሉ ሆሣዕና በአርያም ተፅዒኖ ዲበ ዕዋል ቦአ ሀገረ ኢየሩሳሌም በትፍሥሕት ወበሐሴት ይሁቦሙ ኃይለ ወሥልጣነ፡፡….. ትርጉም: “በፋሲካ በዓል ሰሞን የእውነት አምላክ ደቀ መዛሙርት ወደ ደብረ ዘይት ቀረቡ፤ በሀገረ እግዚአብሔር (ኢየሩሳሌም) አቀበቱ ላይ ብዙ አረጋውያንና ሕፃናት የዘንባባ ቅጠል ይዘው ሆሣዕና በአርያም እያሉ ተቀበሉት፣ በአህያ ውርንጫ ላይ ተጭኖ በፍጹም ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ። ለእነዚህ ኃይልና ሥልጣንን ይሰጣቸዋል። #መልዕክታት ዕብ.8÷1-ፍጻ. ከተናገርነውም ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፡፡ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር የተተከለች ናት፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ) 1ኛ ጴጥ.1÷13 ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡  (ተጨማሪ ያንብቡ) #ግብረ_ሐዋርያት የሐዋ.8÷26-ፍጻ. የእግዚአብሔር መልአክም ፊልጶስን ተናገረው፤ እንዲህም አለው÷ “በቀትር ጊዜ ተነሣና በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ በሚያወርደው በምድረ በዳው መንገድ ሂድ፡፡” ተነሥቶም ሄደ፡፡” እሆም÷   (ተጨማሪ ያንብቡ) #ምስባክ "ንፍሑ ቀርነ በዕለት ሠርቅ፡፡ በእምርት ዕለት በዓልነ፡፡ እስመ ሥርዓቱ ለእስራኤል ውእቱ" መዝ.80÷3 ትርጉም፦ በመባቻ ቀን በታወቀችው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤ ለእስራኤል ሥርዐቱ ነውና÷ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ ነውና፡፡ ወይም "እምአፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስተዳሎከ ስብሓተ፡፡ በእንተ ጸላዒ፡፡ ከመ ትንሥቶ ለጸላዒ ወለገፋዒ፡፡" መዝ.80÷2 ትርጉም፦ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ፡፡ ስለ ጠላት÷ ጠላትንና ግፈኛን ታጠፋው ዘንድ፡፡ #ወንጌል ዮሐ.12÷1-11 ፋሲካ ከሚውልበት ከስድስተኛው ቀን አስቀድሞ ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው አልዓዛር ወደ ነበረበት ወደ ቢታንያ መጣ፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ) ቅዳሴ ፡- ቅዳሴ ዘጎርጎርዮስ፡፡

#የሕያዋን_ሁሉ_እናት አባታችን አዳም በኃጢአት ከወደቀ በኋላ ንስሐ በገባ ጊዜ አምላካችን ጌታ እግዚአብሔር የድህነት ቃል ኪዳን ገባለት ቃል ኪዳኑም ‹‹ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ›› የሚል ነ
#የሕያዋን_ሁሉ_እናት አባታችን አዳም በኃጢአት ከወደቀ በኋላ ንስሐ በገባ ጊዜ አምላካችን ጌታ እግዚአብሔር የድህነት ቃል ኪዳን ገባለት ቃል ኪዳኑም ‹‹ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ›› የሚል ነበር ። ስለሆነም አዳም ዐምስት ሺ ዐምስት መቶ ዘመን ሙሉ የሕይወት ምክንያት የሆነችውን የልጅ ልጁ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከአብራኩ ከተከፈሉ ቅዱሳን ልጆቹ የምትወለድበትን ቀን ተስፋ እያደረገ ኖረ ። የእመቤታችንን የድንግል ማርያምን የመወለዷን ዜና ተስፋ በማድረግ ‹‹ ሴት ›› ይላት የነበረውን ሚስቱን ሔዋንን በእመቤታችን ምሳሌነት ‹‹ ሔዋን ›› የሕያዋን ሁሉ እናት ብሎ ሠየማት ። ( ዘፍ 3 ፥ 20 ) ዳግማዊ አዳም ክርስቶስም የአዳምን ተስፋ በመስቀል ላይ በፈጸመ ጊዜ እውነተኛዋን ሔዋን ( ዳግሚት ሔዋንን ) ድንግል ማርያምን በዮሐንስ ወንጌላዊ በኩል ለሕያዋን ምዕመናን ሁሉ እናት አድርጎ ሰጠ ፡፡ ይህን የከበረ ምሥጢር የማይረዳ ‹‹ ሰው እንዴት ያሳዝናል ? ›› እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ግን የቀዳማዊ አባታችንን የአዳምን እንዲሁም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሀለው ብሎ ያከበረንን ዳግማዊ አዳም የተባለውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቃል ተቀብለን ‹‹ የሕያዋን ሁሉ እናት ›› ድንግል ማርያምን ልደቷን በፍጹም ደስታ እናከብራለን ከተወደደ ልጇ ምሕረትን ትለምንልን ዘንድም ወደ እርሷ እናንጋጥጣለን ፡፡

#ደብረ_ዘይት (የዐቢይ ጾም አምሥተኛ ሳምንት) የዐቢይ ጾም የአምስተኛው ሳምንት ደብረ ዘይት ይባላል፡፡ ጌታ በደብረ ዘይት የዳግም ምጽአቱን ነገር ማስተማሩ ይነገርበታል፡፡ ደብረዘይት የስሙ ትርጓሜ የዘይት ተራራ ማለት ነው ስያሜ የተሰጠው በቦታው ብዙ ወይራ ተክል ይበቅልበት ስለ ነበር ነው፡፡ እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ደቀመዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድን ነው?›› አሉት (ማቴ. 24፥3፣  ዘካ. 14፥5 ፤ ሐዋ. 1፥11 ፤ 1ኛ ተሰ. 4፥16 ፤ ራዕ. 22፥7) #አመጣጡስ_እንዴት_ነው? ጌታ ይህንን ዓለም ለማሳለፍ ለሁሉም እንደ ሥራው ለመክፈል በግርማ መለኮቱ በክበብ ትስብዕቱ ይመጣል፡፡ ጊዜው ዘመነ ዮሐንስ ወርሃ መጋቢት ዕለት እሑድ መንፈቀ ሌሊት እንደሆነ ሊቃውንት ተናግረዋል፡፡ ምነው የሚያውቀው የለም ይባል የለምን? ቢሉ እውነት ነው የሚያውቀው የለም ብዙ የዮሐንስ ዘመን፤ ብዙ የመጋቢት ወር፤ ብዙ የእሑድ ዕለት አለና ለይቶ የሚያውቅ የለም፡፡ ሞት ለማን አይቀርምና ሁሉም ይሞታል፡፡ ዘፍ. 3፥19 በዕለተ ምጽአት ቅዱስ ገብርኤል ስምንቱን ነፋሳተ መዓት ከየመዛግብታቸው ያወጣቸዋል፡፡ ዛፏን ነቅለው ደንጊያውን ፈንቅለው ምድርን እንደ ብራና ይዳምጧታል፡፡ ቅዱስ ሚካኤል መለኸት ይነፋል፡፡ 1ኛ መቃ. 9፥8 ቅዱስ እግዚአብሔር ዘያነቅሖሙ ለሙታን ሲል በዱር በገደል በባሕር በየብስ በመቃብር ውስጥ ያሉት በአውሬ ሆድ ውስጥ ያሉ ሁሉ ይሰበሰባሉ፡፡ በሁለተኛው ነጋሪት ሲመታ አጥንትና ሥጋ አንድ ሆነው ፍጹም በድን ይሆናሉ፡፡ ሦስተኛው ነጋሪቱን መቶ (ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ህያው ዘኢይመውት) ንቃሕ መዋቲ ዘትነውም ባለ ጊዜ መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ደጉ ደጉነቱን ክፉውም ክፋቱን ይዞ ይነሳል፡፡     ወንዱ የ30 ዓመት ሴቲቱ የ15 ዓመት ሆነው ጻድቃን ብርሃን ለብሰው ብርሃን ተጎናጽፈው ከፀሐይ 7 እጅ አብርተው ማቴ.13፥43 ኃጥአን ጨለማ ለብሰው ፍጹም ዲያቢሎስን መስለው ይነሳሉ፡፡ ጻድቃን ስለሠሩት መልካም ሥራ ኑ የአባቴ ቡሩካን ብሎ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳቸዋል፡፡ ኃጥአንን ስለ ክፉ ሥራቸው (ከኔ ሂዱ) ገሃነም ይሰዳቸዋል፡፡ ጻድቃን ደስ ይላቸዋል ኃጥአን ግን ያዝናሉ፤ ዋይ ዋይ ይላሉ፤ ደረት ይደቃሉ እንባቸው ያፈሳሉ፡፡ የማይጠቅም ለቅሶ የማይጠቅም ሐዘን ሰቅለው የገደሉትም አይሁድ ክብሩን አይተው ላይጠቀሙ ይጸጸታሉ፡፡     #ምልክቱስ_ምንድን_ነው? ብለው ጌታን ሲጠይቁ ‹‹ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፡- ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፡፡ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ አትደንግጡ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው፡፡ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥት በመንግሥት ላይ ይነሳል፤ ረሃብም ቸነፈርም መናወጥም በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል ይገድሉአችሁማል፤ ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ›› አላቸው፡፡ በዳግም ምጽአቱ ጊዜ ከቅዱሳኑና ከሰማዕታቱ ጋር ለመቆም ያብቃን፡፡ #የዕለተ_ሰንበት_መዝሙር_ከጾመ_ድጓ እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ወይቤሎሙ ለአርዳኢሁ ዑቁኬ ኢያስሕቱክሙ ወንበሩ ድልዋኒክሙ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን ወአመ ምጽአቱሰ.... (ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ ተዘጋጅታችሁም ኑሩ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል፡፡....) #የዕለቱ_ምንባባት 1ኛ ተሰሎንቄ 4÷13-ፍጻ፡- ወንድሞቻችን ሆይ÷ ስለ ሞቱ ሰዎች÷ ተስፋ እንደሌላቸው ሰዎች እንዳታዝኑ ልታውቁ እንወዳለን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ እንደ ተነሣ ካመንን እንዲሁ እግዚአብሔር ሙታንን በኢየሱስ ያስነሣቸዋል ከእርሱም ጋር ያመጣቸዋል፡፡..... 2ኛ ጴጥ.3÷7-14፡- አሁንም ሰማይና ምድር በዚያ ቃል ለእሳት ተዘጋጅተዋል፤ ኃጥኣን ሰዎች እስከሚጠፉበት እስከ ፍርድ ቀንም ተጠብቀዋል፡፡ነገር ግን ወንድሞቻችን ሆይ÷ ይህን አትርሱ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ አንዲት ቀን እንደ አንድ ሺህ ዓመት÷ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን ነውና፡፡..... ሐዋ. 24÷1-21፡- በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ ጋር ወረደ፤ ጳውሎስንም በአገረ ገዢው ዘንድ ከሰሱት፡፡..... (ተጨማሪ ያንብቡ) #የዕለቱ_ምስባክ መዝ. 49÷2 እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጽእ ወአምላክነሂ ኢያረምም እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፡፡ ትርጉም፦ እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፡፡ አምላካችንም ዝም እይልም፤ እሳት በፊቱ ይነድዳል በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ፡፡ #የዕለቱ_ወንጌል ማቴ. 24÷1-25፡- ጌታችን ኢየሱስም ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሄደ፤ ደቀ መዛሙርቱም ወደ እርሱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንጻ አሠራር አሳዩት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው÷ “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፤ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም፡፡.....” (ተጨማሪ ያንብቡ) #የዕለቱ_ቅዳሴ፦ ቅዳሴ አትናቴዎስ ምንጭ፡- (የማቴዎስ ወንጌል 24፥1 ትርጓሜ፣ መዝገበ ታሪክ ቁጥር 2፣ ግጻዌ)

ፍቅር ምን እንዳደረገው ተመልከቱ፤ በአርያም ካለው ከእሳት አዳራሹ ስቦ በቤተልሔም ዋሻ በከብቶች በግርግም አስተኛው። ብርሃንን እንደ ልብስ የሚጎናጸፈው እርሱን በበለሳን ቅጠል እንዲጠቀለል አደረገው።
ፍቅር ምን እንዳደረገው ተመልከቱ፤ በአርያም ካለው ከእሳት አዳራሹ ስቦ በቤተልሔም ዋሻ በከብቶች በግርግም አስተኛው። ብርሃንን እንደ ልብስ የሚጎናጸፈው እርሱን በበለሳን ቅጠል እንዲጠቀለል አደረገው። ዘመን የማይቆጠርለትን አምላክ ጽንስ፣ ሕፃን፣ ልጅ፣ ጎልማሳ አደረገው። ፍቅር... በአባቱ የሚወደደውን አንድያ ልጅ በአይሁድ ዘንድ የተጠላ አደረገው። በመላእክት የሚመሰገነውን ጌታ በፈሪሳውያን መሪር አንደበት እንዲሰደብ አደረገው። ፈታሒውን ዳኛ እጆቹን ታስሮ የሰውን ፍርድ ፍለጋ እንዲንከራተት አደረገው። ፍቅር በኩሩቤል ጀርባ ለሚቀመጠው አምላክ የመስቀል ዙፋን አበጀለት። የመቃብር አልጋም አዘጋጀለት። ፍቅር የእግዚአብሔርን ልጅ ሐፍረትን ንቆ በፊቱ ስላለው የምእመናን ደስታ እርቃኑን እንዲሰቀል አደረገው! መድኃኒት በምትሆን ሕማሙ ከኃጢአት በሽታ ሁላችንንም ይፈውሰን! መጋቢት 27 ጥንተ ስቅለት በዲያቆን አቤል ካሳሁን

ከኃጢያታችን የበለጠ እግዚአብሔርን እጅግ የሚያሳዝነው ይቅር አይለንም ብለን ማሰባችን ነው። በደል የሌለበት አምላክ ከእኛ ከትቢያዎቹ ጋር ራሱን አቻ አድርጎ "ኑና እንዋቀስ፤ ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፤ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዛቶ ትጠራለች" ብሎ የምሕርት ጥሪ እያቀረበ ይቅር አይለኝም ሰንል ሲሰማን ያዝናል። (ኢሳ,፩፥፲፰) አንተ በክፉ ሥራህ ራስህን ብትጠላውም እንኳን እግዚአብሔር ግን አይጠላህም፤ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳለው «እግዚአብሔር ለአንተ ያለው ፍቅር አንተ ለራስህ ካለህ ፍቅር ይበልጣል» እንደ ይሁዳ ብትክደው ፣ ወዳጅህን ብትሸጥ፣ ንጹሕ ደም በግፍ ብታፈስስ፣ ሙዳየ ምጽዋቱን ብትዘርፍ፣ እንደ ይሁዳ በአምላክነቱም ጨርሶ ባታምን እንኳን ፈጣሪ የሚጠብቀው የምትሞትበትን ሳይሆን የምትጸጸትበትንና የምትመለስበትን ቀን ብቻ ነው።በወንጌሉ «እርሱም ገና ሩቅ ሳለ አባቱ አየውና አዘነለት» እንደሚል እግዚአብሔር ከእርሱ እጅግ በጣም ርቀህ እያለህ እንኳን እያየ ያዝንልሃል እንጅ አያዝንብህም። (ሉቃ. ፲፭፥፳) (ከዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ሕማማት መጽሐፍ የተወሰደ)

መፃጒዕ የዓቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት ስያሜው መፃጒዕ ነው ትርጉሙም ድዊ( በሽተኛ) ማለት ነው። ይህ ሰንበት የህሙማን ፈውስ መታሰቢያ ዕለት ነው ማለት ይቻላል። እንግዲህ በዕለቱ በሚነበበው ወንጌላይ እንደምንመለከተው ( ዩሐ 5:25)  በቤተ ሳይዳ ለሠላሳ ስምንት ዓመት በአልጋው ላይ ያለ  በህመም የሚሰቃይ  ሰው ታሪክን እናገኛለን። ይህ ሰው በተስፋ በመቁረጥና ሰው የለኝም  በሚል እምነት ማጣት ለሠላሳ ስምንት  ዓመታት በደዌ ይሰቃይ ነበር። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደ እርሱ በመጠጋት  "ልትድን ትወዳለህን? " ብሎ ነፃ ፈቃዱን ጠየቀው እግዚአብሔር አምላክ ለሁሉም ነገር ነጻ ፍቃድን አይከለክልምና። መፃጒዕ " አዎን ጌታዬ ሆይ ነገር ግን ውኃው በተናውጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም " አለ።  የተጠየቀው መዳን ሆኖ ሳለ መፃጒዕ ግን የዓመታት ብሶቱ እና ያለመዳን ምክንያቱ ሰዉ ማጣቱ መሆኑን ማስራዳት ጀመረ።  አንተ ሰው  ሰው የለኝም  ብለህ የምትነግረውን አምላክ ብታቀውስ ኖሮ ይህን ባላልክ ነበር። አንተ በሽተኛ ሆይ ያዳነህንስ ብታዉቅ በሰው ብዛት መዳን እንደማይቻል ትረዳ ነበር። የመፃጉ አለማመን ግን ኢየሱስን የሚሰራውን ሥራ ከመሥራት አላገደውም። "ተነሥና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ" አለው። ክርስቶስ ሲል ሠላሳ ስምንት ዓመት በአልጋ የነበረ ደካማ የተሸከመውን አልጋ ይሸከማል። ከክርስቶስ ሲወጣ ደግሞ ማንም የማይጥለው ብርቱ በጠጠር ይሞታል። አይሁድም ዛሬ ሰንበት ነው አልጋህን ልትሸከም አይገባህም አሉት። ሠላሳ ስምንት  ዓመት በህመም ሲሰቃይ ያረዱት ወደ መጠመቂያው ያላወረዱት እና ያላዘኑለት ዛሬ ድኖ አልጋውን በመሸከሙ ተጉረመረሙብት። ይሁሉ ዓመት በአልጋ የነበረው በሽተኛ አልጋውን መሸከሙ ነው የሚያስገርመው ወይስ በሰንበት መዳኑ? መፃጒዕም " ያዳነኝ እርሱ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ" አላቸው። የዳነ ሰው የሚሸከመው ነገር አለው። በእግዚአብሔር የዳነ የእግዚአብሔርን ሸክም ይሸከማልና። እነርሱም አልጋህን ተሸከም ያለህ ማነው?  ብለው ጠየቁት የተፈወሰው መፃጒዕ ግን ያዳነው ማን እንደሆነ አላወቀም። ድኖ አዳኝን አለማወቅ እንዴት ያለ አለመታደል ነው? ኢየሱስም ያዳነውን ሰው " እነሆ ድነሃል ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳት በድል ተጠንቀቅ" አለው። ያም ሰው ሄዶ ያዳነው ጌታችን ኢየሱስ እንደሆነ ለአይሁድ ነገራቸው።  አይሁድም ጌታችን ኢየሱስን ያሳድዱትና ሊገድሉትም ይሹ ነበርና።  ልበ መፃጒነት  ከአካላዊ መፃጒነት ይከፋልና ለመፃጉዕ ካለፈው ይልቅ  የፊቱ ከፋበት። ያንን ተስፋ ያልነበረውን መፃጒዕ ከደዌ ስጋው ፈውሶ ህይወትን የሰጠው እኛንም ካለብን ደዌ ስጋወነፍስ እግዚአብሔር ይፈውሰን። ✍️እውነተኛው ሠላም ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የጽሙና ጊዜ አለህ?  ✍🏽 ዲያቆን አቤል ካሣሁን እንደ ጻፈው በጸሎት ጊዜ ሐሳቡ እየተበተነበት የተቸገር አንድ ደቀ መዝሙር ወደ አረጋዊ አባት ሄዶ ስለሆነው ነገር ይነግራቸዋል። እኛም አረጋዊ ልጁን በምሳሌ ሊያስተምሩት ስለ ፈለጉ ከፊቱ ውኃ አመጡ። ከዚያም በውኃው ላይ ጠጠር በመወርወር ልክ የሚርገበገብ ሞገድ ሲፈጠር ያን ደቀ መዝሙር ፊቱን በውኃው ውስጥ እንዲያይ ጠየቁት። ተማሪውም በውኃው ውስጥ ጥላ የሚመስል ነገር እንጂ መልኩን ማየት እንዳልቻለ ነገራቸው። ቀጥለውም አረጋዊው ውኃው እስኪረጋጋ ጠብቀው “አሁንም መልሰህ ተመልከት?” አሉት። አየ፤ “አሁን ልክ እንደ መስታወት ውኃው ፊቴን እያሳየኝ ነው” አላቸው። አረጋዊውም “ልጄ ሆይ፣ አንተም እንዲሁ ሂድና ራስህን አረጋጋ። ያን ጊዜ በጸሎትህ ውስጥ መጽናናትን ታገኛለህ” አሉት። (Paradise of the holy fathers)  የቆርቆሮና የብረት ጩኸት ጋጋታ ባለበት ውብና ለስላሳ የሆነውን የዋሽንት ድምጽ መስማት የሚቻለው ማን ነው? ሁከትና ረብሻ በሚነግስበት፣ የማይቋረጥ ግፊያና አለመረጋጋት ባለበት የሰዎች ግርግር ውስጥ ሆነህ እንዴት የመንፈስ ቅዱስን ድምጽ ልትሰማ ትችላለህ? የእግዚአብሔርን ድምጽ በአውሎ ነፋስ ፋጨት፣ በምድር መናወጥ፣ በሚያስገመግም የእሳት ድምጽ ውስጥ አታገኘውም። እርሱ የሚናገረው ከእነዚህ ሁሉ በኋላ በሚሆነው “ትንሽ የዝምታ” ጊዜ ነው።(1ኛ ነገ 19፥12)  ልክ የመድኃታችንን የልብሱን ጫፍ በስውር ነክታ ከቁስሏ እንደ ተፈወሰችው ሴት፣ አንተም የነፍስህን ቁስል ለማድረቅ በመቅደሱ የሞላውን የጌታን የልብሱን ዘርፍ በምሥጢር የምትዳስስበት የብቻ ጊዜ ያስፈልግሃል?   ከእሾህ ወይን ከኩርንችትም በለስ እንደማትለቅም፣ ራስህን ከዚህ ዓለም ሁከት የምትለይበት ጊዜ ሳይኖርህ እውነተኛ የነፍስ መጽናናትን ልታገኝ አትችልም። ለዚህም ነው ጌታችን በወንጌል “ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ፤ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ” በማለት ያስተማረን። ላዘነችው ነፍስህ መጽናናትን፣ ለልቡናህ ዕረፍትን ትፈልጋለህ? ስለ ኃጢአትህ የምታፈሰው የንስሐን እንባስ ትሻለህ?  እንግዲያውስ ከሰው ርቀህ በርረህ ወደ ፈጣሪ የምትሄድበት የጽሙና ጊዜ ይኑርህ።  የእስራኤል ልጆች የመላእክትን እንጀራ የተመገቡት ቆነጃጅቱ በሚዘፍኑበት እና ለጣዖት የሚቀርብ ዳንኪራ በነገሠበት ግብጽ አይደለም። ሰማያዊውን መና ያገኙት ግብጽን ጥለው ከወጡ በኋላ በበረሃ ሳሉ ነው። አብርሃም ታላቅ ሕዝብ የሚሆንበትን ጽኑዕ ቃልኪዳን የተቀበለው ያደገበትን አገር እና የአባቱን ቤት ጥሎ በመውጣቱ ነው። አንተስ እንደ እስራኤል ልጆች መላእክት እንዲመግቡህ፣ እንደ አባታችን አብርሃምስ ታላቅ ሕዝብ መሆን ትፈልጋለህ? እንግዲያውስ ዛሬውኑ ከግብጽ የምትሸሽበትን ዕቅድ ያዝ። የአባትህን ቤት ትተህ ለጥቂት ጊዜ ፈቀቅ የምትልበትንም ገዳም አስስ።  ጌታን ያጠመቀውና ለብዙዎች በብርሃኑ ደስ የሚያሰኝ “የሚነድ መብራት” የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ ሁሉ በፊት ብቻውን ከአምላኩ ጋር በበረሃ ነበር። የሐዲስ ኪዳኑ ባለ ራእይ ቅዱስ ዮሐንስ እነዚያን ሁሉ ሰማያዊ ምሥጢራት የተመለከተው ብቻውን በፍጥሞ ደሴት ሆኖ ነው። ስሙን በአሕዛብ፣ በነገሥታቱና በእስራኤል ልጆች ሁሉ ፊት ይሸከም ዘንድ የተመረጠው ቅዱስ ጳውሎስ፣ ከሁሉ አስቀድሞ ግን የመረጠው አምላኩ መንፈሳዊውን ኃይል ያስታጥቀው ዘንድ የገዛ ድክመቶቹን ተሸክሞ ብቻውን ወደ አረብ በረሃ ገስግሶ ነበር።  ያንተስ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በመንፈስ የምትጎለምስበት በረሃህ ፣ እንደ ወንጌላዊው ዮሐንስ ጣዕመ መንግስተ ሰማያትን የምትዘከርበት ፍጥሞ ደሴትህ፣ እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ በነፍስ ታድሰህ የምትወጣበት አረባዊ ገዳምህ  የት ነው? መቼ መቼስ ወደዚያ ትወርዳለህ?

#ምኩራብ (የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት) ምኩራብ ማለት ለአምልኮትና ለትምህርት ለህብረተሰቡ አገልግሎት የሚሰጥ የአይሁድ ቤተ ጸሎት ነው። ጌታ በመዋዕለ ስብከቱ በእስራኤል ሀገር ብዙ ምኩራቦች ስለነበሩ እየገባ ወንጌልን አስተምሮባቸዋል። በዚህም “ቦአ ኢየሱስ ምኩራበ አይሁድ ወመሀረ ቃለ ሃይማኖት” እንዲል ቅዱስ ያሬድ ኢየሱስ ወደ አይሁድ ምኩራብ ገብቶ የሃይማኖት ቃልን አስተማረ። ከሚለው የቅዱስ ያሬድ ዜማ ሥያሜውን አግኝቷል። በምኩራብ ጸሎትና ትምህርት ይፈጸምበታል። መሥዋዕት ግን አይከናወንም። መሥዋዕት ግን በታላቁ ቤተ መቅደስ በኢየሩሳሌም ብቻ ይፈጸም ነበር። በዚህ ሳምንት የሚነገረው ታሪክ ጌታ ቤተ መቅደሱን የገበያ ማዕከል አድርገው ሸቀጥ ዘርግተው በጉን ላሙን ርግቡን እየሸጡ አገኛቸው። በዚህ ተቆጥቶ በጉን ላሙን ርግቡን ከምኩራብ አስወጥቶ ሸቀጣቸውንና መደርደሪያቸውን እንዲሁም ወርቅና ብራቸውን በነፋስ በተነባቸው ይላል። በዚህ ሁኔታ ከቤተ መቅደስ አስወጥቶ "ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች እናንተ ግን የሽፍቶችና የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችኋት" በማለት ወቅሷቸዋል። “አሰስሉ ወአውፅኡ ዘንተ እምዝየ ወኢትረስዩ ቤተ አቡየ ቤተ ምሥያጥ” እንዲል ዮሐ. 2፥16፤ ማቴ. 21፥13። ይህን ተአምር በማሳየት ቤተ ጸሎት የተቀደሰ ከገበያ የተለየ መሆኑን አስተምሮበታል። በሰንበተ ምኩራብ ጌታ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ለዋጮችን ማስወጣቱ ወርቅና ብሩን በነፋስ መበተኑ ላሞችን በጎችን በጅራፍ መግረፉ ቤተ መቅደሱን ማንጻቱ ወዘተ ይነገራል። (የዚህም በዓል ታሪክ ዝርዝር ሁኔታው ማቴዎስ 21፥12-13 ላይ ተጠቅሷል፡፡) #የቅዳሴ_ምንባባት፦ ቆላስ. 2፥16-23 «እንግዲህ በመብል ወይ በመጠጥ ወይም ስለ በዓል ወይም ስለ ወር መባቻ ወይም ስለሰንበት ማንም አይፍረድባችሁ እነዚህ ሊመጡ ያሉት ነገሮች ጥላ ናቸውና፣ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው፡፡ .......፡፡» ያዕ. 2፥14-26 «ወንድሞቼ ሆይ፣ እምነት አለኝ የሚል፣ ሥራ ግን የሌለው ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል እምነቱስ ሊያድነው ይችላልን ......፡፡» ሐዋ. 1ዐ፥1-9 «በቂሣርያም ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራ የመቶ አለቃ የሆነው ቆርኔሌዎስ የሚሉት አንድ ሰው ነበር፡፡ እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር እግዚአብሔርን የሚያመልክና የሚፈራ ለሕዝብም እጅግ ምጽዋት የሚያደርግ ወደ እግዚአብሔርም ሁልጊዜ የሚጸልይ ነበረ፡፡ ....፡፡" #ምስባክ- መዝ 68፥9 እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ ትዕይርቶሙ ለእለ ይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ ወቀጻዕክዋ በጾም ለነፍስየ፡፡ (የቤትህ ቅንዓት በልታኛለችና የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቆአልና ነፍሴን በጾም አስመረርኋት፡፡) #ወንጌል፡- ዮሐ 2፥12-25 «ከዚህ በኋላ ከእናቱና ከወንድሞቹ ከደቀ መዛሙርቱም ጋር ወደ ቅፍርናሆም ወረደ፣ በዚያም ጥቂት ቀን ኖሩ፡፡ የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፡፡ ወደ መቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤ የገመድም ጅራፍ አበጅቶ ሁሉን በጎችንም በሬዎችንም ከመቅደስ አወጣቸው፣ .....፡፡» (ከመድብለ ታሪክ እና ግጻዌ የተወሰደ)

+ ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል + ንጉሥ ሕዝቅያስ በጠና ታምሞ ተኝቶአል::  ነቢዩ ኢሳይያስ ሊጠይቀው መጣ:: ሆኖም እንደ ልማዱ እግዚአብሔር ይማርህ አላለውም:: ለጆሮ የሚከብድ  ቃል ጥሎበት ወጣ:: "ትሞታለህና ቤትህን አስተካክል!" ነቢዩ ይህንን ብሎት ከወጣ በኁላ ሕዝቅያስ ወደ ግድግዳው ዞሮ ስቅስቅ ብሎ አለቀሰ:: አምላኩ በንግግር ብዛት የሚሰማ አምላክ አይደለምና ፊቱን ወደ መቅደሱ አቅጣጫ አዙሮ አለቀሰ::  ከጥቂት ደቂቃ በኁዋላ ነቢዩ ኢሳይያስ ሌላ መልእክት ይዞ ተመለሰ:: እግዚአብሔር እንዲህ ይላል :- ጸሎትህን ሰምቻለሁ ዕንባህን አይቻለሁ በዕድሜህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት እጨምራለሁ" (ኢሳ 38:5) ሕዝቅያስ ቤትህን አስተካክል ከተባለ በኁዋላ ፊቱን አዙሮ ከማልቀስ በቀር ምንም አላደረገም:: ሕዝቅያስ ሆይ ከአልጋህ ሳትወርድ ያስተካከልከው ቤት ምን ዓይነት ቤት ነው? ለባሪያዎችህ መመሪያ ሳትሠጥ የምታስተካክለው ቤትስ እንዴት ያለ ነው? በደቂቃዎች ውስጥ ትሞታለህ ከተባልክ በኁዋላ ዐሥራ አምስት ዓመት ያስጨመረልህ ምን ዓይነት ማስተካከያ አድርገህ ነው? ለእኛም ንገረንና ዕድሜ እናስጨምር:: ሕዝቅያስ ከአልጋው ሳይነሣ ያስተካከለው ቤቱ ልቡ ነበር:: ልብህን ካስተካከልህ ቤትህ ይስተካከላል:: እግዚአብሔር እንደሆን ትሞታለህ ቢልህም መሞትህን አይፈልግም:: እርሱ ከኃጢአትህ እንጂ ካንተ ጋር ጸብ የለውም:: "በውኑ ኃጢአተኛ ይሞት ዘንድ እፈቅዳለሁን? ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ከመንገዱስ ይመለስና በሕይወት ይኖር ዘንድ አይደለምን?" ይላል መሐሪው (ሕዝ 18:23) እርሱ ትሞታለህ የሚልህ መኖርህን ፈልጎ ነው:: አንዴ ብያለሁ ብሎ አይጨክንብህም:: በንስሓ ተመለስ እንጂ ምሬሃለሁ ለማለት ይቸኩላል:: አሁን ትሞታለህ ብዬው አሁን ትድናለህ ብለው ይንቀኛል ሳይል ተመልሶ ይምርሃል:: ኃጢአትህንም ወደ ጥልቁ ይጥለዋል:: በጎ እንድትሠራም ዕድሜ ይጨምርልሃል:: አንተ ብቻ ተመለስና አሁኑኑ ንስሓ ግባ:: ከበደል አልጋ ጋር ያጣበቀህን ፈተናም ድል መንሻው ጊዜ አሁን ነው:: ሕዝቅያስ በደቂቃ ዕንባ ምሕረት አግኝቶ ዕድሜ ካስጨመረ በዐቢይ ጾም ሙሉ የሚያለቅስ ምን ያህል ዕድሜ ያገኝ ይሆን? ወዳጄ አንተም ተነሣና በዚህ ወር ቤትህን አስተካክል:: እንደ ሕዝቅያስ ፈጣሪህ ይጠብቅሃል:: የተቀየምከውን ይቅር በል  የበደልከውን ካስ የሚበቀልህን የማይተኛ ጠላትህን ዲያቢሎስ ተበቀለው:: የዐቢይ ጾም የወንጌል ምንባብ ስለ ዲያቢሎስ ፈተና ሦስቱ ወንጌላት የተናገሩትን ስናስተውል ሦስት ዓይነት ጥቅሶች እናገኛለን:: አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ። (ሉቃ 4:2) በምድረ በዳም ከሰይጣን እየተፈተነ አርባ ቀን ሰነበተ (ማር 1:13) የሚሉት ቃላት ጌታችን ዐርባውንም ቀን መፈተኑን ያሳያሉ:: አርባ ቀንና አርባ ሌሊትም ከጦመ በኋላ ተራበ። ፈታኝም ቀርቦ እንዲህ አለው (ማቴ 4:2) የሚለው ደግሞ ከጾሙ በኁዋላ የቀረቡለትን ሦስት ፈተናዎች የሚያሳይ ነው:: ሦስተኛው ጥቅስ ደግሞ ከተፈተነ በኁዋላ ያለው ሲሆን ዲያቢሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። (ሉቃ 4:13) ይላል:: ዲያቢሎስ ፈተናውን ቢጨርስም የሚተወው ለጊዜው እንጂ መፈተኑን አያቆምም::  የዲያቢሎስ ፈተና ስልቱ ይቀያየራል እንጂ ይቀጥላል:: ዐቢይ ጾም ዲያቢሎስ ድል የተደረገበት የጦር ዐውድማ ነው:: በዚህ ወራት ድል ያላደረግነውን ፈተና በሌላ ጊዜ አናደርገውም:: ሰነፍ ገበሬ በሰኔ ይሞታል እንደሚባለው በዐቢይ ጾም የተኛ ክርስቲያን መቼም አይነቃም:: ከነስሙ ሁዳዴ (ሰፊ እርሻዬ) የምንለው ይህ ጾም ለነፍሳችን ብዙ ዘር የምንዘራበት አጋንንት መድረሻ የሚያጡበት ጾም ነው:: በዐቢይ ጾም ያልተገራ አንደበት መቼም አይገራም:: በዐቢይ ጾም ያልተፈወሰ ቂም መቼም አይፈወስም:: ጌታችን በወንጌል አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥል ጋኔን ያለበትን ልጅ ሲፈውስ "ይህ ዓይነቱ ጋኔን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም" ብሎ ነበር:: ሀገራችንን አንዴ ወደ እሳት አንዴ ወደ ውኃ የሚጥላት የጥላቻ ጋኔንም ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም:: ወዳጄ ከቁስልህ የምትፈወስበት ወር እንደደረሰ ዕወቅ:: አንተስ ብትሆን ልትላቀቀው እየፈለግህ ያቃተህ ክፉ ልማድ የለብህም:: እንደ ቅዱስ ጳውሎስ "የምፈልገውን መልካም ነገር አላደርግም የማልፈልገውን ክፉ ነገር ግን አደርጋለሁ:: ምንኛ ጎስቋላ ለዚህ ለሞት ከተሠጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?" ብለህ ምርር እንድትል ያደረገህ ኃጢአት የለም? እንግዲያውስ እወቀው:: ይህ ዓይነቱ ወገን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም:: ይህ ጾም ቁስል የሚሽርበት ጾም ነው:: ይህ ጾም ሸክም ማራገፊያ ጾም ነው:: እንደ ሕዝቅያስ በዚህ ወር ቤትህን በንስሓ አስተካክል:: ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ የካቲት 15 2012 ዓ ም ዝዋይ ኢትዮጵያ

የእግዚአብሔርን ፈቃድ ልትረዳ የምትችለው ሁልጊዜ አንተ በምትፈልገው መንገድ ብቻ እንዲሠራ ባለመጠበቅ ነው። አንዳንዴ በአንተ እና በአምላክህ ሐሳብ መካከል የሰማይና የምድር ያህል ልዩነት ሊኖር ይችላል። ራሱ ባለቤቱም "ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፥ እንዲሁ መንገዴ ከመንገዳችሁ አሳቤም ከአሳባችሁ ከፍ ያለ ነው” ብሎናል።(ኢሳ 55፥9) "ፈቃድህ ይሁን" ብለህ ከጸለይህ በኋላ "የምትፈልገውን ብቻ በመጠባበቅ ፈጣሪህን የፈቃድህ አገልጋይ አታድርገው። በጸሎትህ አምላክ የሚወደውን ወይም ፈቃዱን ማወቅ ከፈለግህ "አንተ የምትወደውን እንደ ብቸኛ መልስ አትጠባበቅ። ዲያቆን አቤል ካሳሁን

#መጋቢት_10 #ቅዱስ_ዕፀ_መስቀል መጋቢት አስር በዚች እለት የክብር ባለቤት ጌታችን አምላካችንና መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል የተገለጠበትና የተገኘበት ነው። የዚህም የከበረ ዕፀ መስቀል መገለጡና መገኘቱ ሁለት ጊዜ ሆኗል። መጀመሪያ የፃድቁ ንጉስ የቆስጠንጢኖስ እናት በሆነች በንግስት እሌኒ እጅ ነው። «እርሷ ለእግዚአብሔር ተስላ ነበርና ልጇ ቆስጠንጢኖስ ወደ ክርስቲያን ሀይማኖት ቢገባ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዳ መስቀሉን እስከ አገኘችው ድረስ ልትፈልግው በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳት መካናትንና አብያተ ክርስቲያናትን ልታንፃቸው ነው። ከዚህ በኋላ ልጇ አምኖ የክርስትና ጥምቀትን በተጠበቀ ጊዜ እሌኒ ቅድስት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደች ከእረሷ ጋርም ብዙ ሰራዊት ነበር ደርሳም ስለ ከበረ መስቀል መረመረች የሚያስረዳት አላገኘችም የአይሁድ ወገን የሆነ አንድ ሽማግሌ ሰው አስራ በርሀብና በጥማት አስጨነቀችው። በተጨነቀም ጊዜ ለንግስት እሌኒ የጉልጎታን ኮረብታ አስጠርጊ ብሎ ነገራት እርሷም ይጠርጉ ዘንድ አይሁድን አዘዘቻቸው። ቤቱን የሚጠርግ ሰው ሁሉ ጥራጊውን በውስጡ የከበረ መስቀል በአለበት በጌታችን መቃብር ላይ እንዲጥል አይሁድ አስቀድመው አዝዘው ነበርና ንግስት እሌኒ እስከ ደረሰችበት ጊዜ ከሁለት መቶ አመት በላይ ጥራጊያቸውን ሲጥሉበት ኖሩ ኮረብታም ሆነ። አይሁድም በጠረጉ ጊዜ ሶስት መስቀሎች ተገለጡ የክብር ባለቤት ክርስቶስ የተሰቀለበት የትኛው እንደሆነ አላወቁም። የሞተ ሰውም አግኝተው አመጡ። አንዱንም መስቀል አምጥተው በሞተው ሰው ላይ አኖሩት አልተነሳም ደግሞ ሌላውን መስቀል አምጥተው በሙቱ ላይ አኖሩ አሁንም አልተነሳም ከዚህም በኃላ ሶስተኛውን መስቀል አምጥተው በሙቱ ላይ አደረጉት ያንጊዜ የሞተው ሰው ተነሳ እሌኒም የክርስቶስ መስቀል እንደሆነ አውቃ ሰገደችለት የክርስቲያንም ወገኖች ሁሉ ሰገዱለት። ለልጅዋ የላከችው ይህ መስቀል ነው የሚል በሌላ መፅሀፍ ይገኛል የቀረው ግን ግንዱ በውስጡ ተተክሎበት የነበረው ከእርሱም እኩሌታውን ከቅንዋቱ ጋራ ወደ ልጅዋ የላከችው ነው። ከዚህም በኃላ ስራአታቸውና የህንፃቸው ነገር በመስከረም ወር በአስራ ሰባት ተፅፎ የሚገኝ አብያተ ክርስቲያናትንና የከበሩ ቦታዎችን አነፀች። ሁለተኛው በሮሙ ንጉስ በህርቃል ዘመን የሆነው ሲሆን የፋርስ ሰዎች በግብፅ አገር ሳሉ ወደ አገራቸው ሊመለሱ ወደዱ። ከሹማምንቶቻቸው አንዱ የጦር መኰንን ተነጥሎ ወደ ኢየሩሳሌም አልፎ ደረሰ ወደ ከበረ መስቀል ቤተ ክርስቲያንም ገባ። መስቀሉም በላዮ በተተከለበት ግንድ ፊት ታላቅ ብርሀን ሲበራ አይቶ ሊያነሳው እጁን ዘረጋ። እሳትም ወጥታ እጁን አቃጠለችው። ከክርስቲያን በቀር ማንም ሊነካው እንደማይችል የመስቀልን የክብሩን ነገር ሰዎች ነገሩት። ሁለት ዲያቆናትንም ይዞ የከበረ መስቀልን እንዲሸከሙ አዘዛቸው ከኢየሩሳሌም ብዙ ሰዎችን ማርኮ ወደ አገሩ ተመለሰ። የፋርስ ሰዎች ኢየሩሳሌምን እንዳጠፏት ብዙዎች ሰዎችንም እነድ ማረኩና የከበረ የክርስቶስንም መስቀሉን እንደ ወስዱ የሮም ንጉስ ህርቃል በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ። ስለርሱም እንዲፆሙ ምእመናንን አዝዞ ወደፋርስ ዘምቶ ወጋቸው ብዙዎችንም ገደላቸው የከበረ እፀ መስቀልንም እየፈለገ በሀገራቸው ሁሉ ዞረ ግን አላገኘውም። ያ ዲያቆናቱና መስቀሉን የወሰደ መኰንን ከቦታዎች በቤቱ አነፃር ባለ በአንድ ቦታ ላይ ወስዷቸው ጥልቅ ጉድጓድ እንዲቆፍሩ አዝዞ በዚያ የከበረ መስቀልን አስቀበረ እነዚያንም ዲያቆናት ገደላቸው። ነገር ግን ያ መኰንን የማረካት የካህናት ወገን የሆነች በእርሱ ቤት የምትኖር አንዲት ብላቴና ነበረች። እርሷም የከበረ መስቀልን ሲያስቀብርና ሁለቱን ዲያቆናት ሲገድላቸው በቤቱ ውስጥ ሁና በመስኮት ትመለከት ነበር ወደ ንጉስ ሀርቃልም ሂዳ መኰንኑ ያደረገውን ሁሉ ነገረችው። ይህንንም ንጉስ ሰምቶ እጅግ ደስ አለው ያቺ ብላቴናም መራችው ከእርሱም ጋራ ብዙ ሰራዊት ሆኖ ኤጲስቆጶሳትና ካህናትም ነበሩ። ወደ ቦታውም እስከምታደርሳቸው ያቺን ልጅ ተከተሏት ቅፍረውም የከበረ እፀ መስቀልን አገኙት ከአዘቅቱም አወጡት ንጉሱና ሰራዊቱም ሰገዱለት። በልብሰ መንግስቱም አጐናፀፈው ታላቀወ ክብርንም አከበረው እጅግም ደስ አለው ከሰራዊቱ ጋር። የዚህም መስቀል ሁለተኛ የተገለጠበትና የተገኘበት በዚች ቀን በመጋቢት አስር ነው፡፡ ከዚህ በኃላ ንጉሱ የከበረ እፀ መስቀልን ተሸክሞ ወደ ቁስጥንጥንያ ከተማ ወሰደው፡፡ የመድኃኒታችን የመስቀሉ በረከት ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)

#ቅድስት #የዐቢይ_ጾም_ሁለተኛ_ሳምንት የቅድስና ባለቤት የሆነው እርሱ እግዚአብሔር አምላክ ነው። እቀደስ አይል ቅዱስ፣ እባረክ አይል ቡሩክ ነው። በእርሱ የባሕርይ ቅድስና እኛን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ቡሩክ ሆኖ ባረከን፣ ቅዱስ ሆኖ ቀደሰን፣ሕያው ሆኖ ሕያዋን አደረገን። የጸጋ ቅድስናንም ከእርሱ አገኘን። ቅድስናው የተለየ፣ የከበረ፣ የሚመሰገን፣ የሚሰጥ/የሚያድል፣ የሚያነጻ፣ የሚባርክ እናም የሚያስተሰርይ ስለሆነ እንከን፣ ጉድለት የሌለበት ምሉዕ ነው። ለባለሟሎቹ ቢሰጠው የማይጎድል፣ ተከፍሎ የሌለበት ቅድስና ሆኖ እኛም የቅድስና በጸጋ ተካፋይ ሆነናል። የተሰጠንን ቅድስና ገንዘብ እንድናደርግ እና እንድንጠቀምበት ደግሞ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ በምጽዋትና በሌሎች በጎ ምግባራት መትጋት ይገባናል። ‹‹እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ›› እንዲል፡፡ (ዘፍ.፪፥፫፣ ዘሌ.፲፱፥፪) የት መሄድ እንዳለብንም በግልጽ ልበ አምላክ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹ወደ ቅዱስ መቅደስህ እሰግዳለሁ፤ ስለ ትምህርትህና ስለ እውነትህ ስምህን አመሰግናለሁ፤ በሁሉ ላይ ቅዱስ ስምህን ከፍ ከፍ አድርገሃልና›› ይላል። (መዝ.፻፴፯÷፪) የተቀደሰን መሥዋዕት በተቀደሰ ቦታ እንፈጽማለን። መቼ ቢሉ፣ በሰንበት፣ በበዓላት በማኅበረ ዐቢይ/ክርስቲያኖች በሚሰበሰቡበት፣ ስመ እግዚአብሔር በሚጠራበት፣ ታቦት  ባለበት፣ እግረ እግዚአብሔር በቆመበት ቅዱስ ስሙን ከፍ ከፍ በማድረግ ቅድስናን ገንዘብ እናደርጋለን። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ለዐቢይ ጾም ሁለተኛው እሑድ በአዘጋጀው ምስጋና አማካኝነት ዕለቱ ‹‹ቅድስት›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ትርጉሙም ‹‹የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች›› ማለት ነው።  (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ገጽ ፯፻፹፬) ቅድስት የሚለው ቃል ዕለቱ ‹‹ቅድስት›› ተብሎ የተሰየመበት ምክንያት ስለ ዕለተ ሰንበት እንዲሁም ስለ እግዚአብሔር አምላክ ፍጹም ቅድስና የሚያወሳ በመሆኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ፍጥረታቱ የእርሱን ስም በማመስገን ይኖሩ ዘንድ ለቅድስና ሕይወት ፈጥሯቸዋልና በሰንበት እሑድ ክርስቲያኖች የቅድስና ተግባራትን ከሌላው ቀን አብዝተው ይፈጽማሉ፡፡ ዕለት ከተግባር፣ ስም ከክብር የተባበረባት ክብርት ሰንበት ቅድስት ስለሆነች ቅዱስ ያሬድ “ቅድስት” ብሎ ጠራት። ይኸውም የምትቀድስ፣ ከብራ የምታከብረን፣ አክብረናት የምንከብርባት በመሆኗ ነው። ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በጾመ ድጓ “ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ፤ ሀቡ ስብሐተ ለስሙ፤ አክብሩ ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ፤ ዝግቡ ለክሙ መዝገበ ዘበሰማያት ኀበ ፃፄ ኢያማስኖ ወኢይረክቦ ሰራቂ፤ ድልዋኒክሙ ንበሩ ዘበላዕሉ ጸልዩ ኀበ ሀሎ ክርስቶስ” ትርጉም፦ “ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ስሙንም ጥሩ፤ ሥራውንም ለአሕዛብ ንገሯቸው፤ ለስሙም ምስጋናን አቅርቡ ሰንበትን አክብሩ፤ እውነትንም አድርጉ፤ ብል የማያበላሸው ሌባም የማያገኘው በሰማያት ያለ መዝገብን ለእናንተ ሰብስቡ፤ ተዘጋጅታችሁም ተቀመጡ፤ ክርስቶስ ወዳለበት ወደ ላይ አስቡ፡፡“  ስለዚህ ሰው ሰንበትን አክብሮ ጾሞ ጸልዮ፣ ቅድስናን ጠብቆ መኖር እንዲችል እግዚአብሔር የፍቅሩ መገለጫ የሆኑ ትእዛዛቱ ይነግሩናል። #ቅዱስ_ያሬድም_ወቅቱን “#ቅድስት” ብሎ ሲሰይም፦ ፩. #የአርባ_ቀን_ጾም_መጀመሪያ_በመሆኑ፦ ዕለቱ ከዐቢይ ጾም ቀናት ውስጥ አርባው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም መጀመሪያ ስለሆነች፣ ፪. #ቅድስት_ሰንበት_ላይ_በመዋሉ፣ እንግዲህ “የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ” ተብሏል፡፡ (ዘፀ.፳፥፰) የሰንበትን ቀን አስቀድሞ የቀደሰ የባረከ ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው፤ ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፎአልና፡፡” (ዘፍ.፪፥፫) “ከምእመናን ወገን አንድስ እንኳን በእሑድ ቀን ለገንዘብ መትጋት፣ ገንዘቤን አምጣ ብሎ መጣላት እና ዋስ መያዝ አይገባውም። ሁሉም ምእመናን ወደ ቤተ ክርስቲያን በንጽሕና በትሕትና ሆነው። ዳኛ ግብሬን፣ አበዳሪ ብድሬን፣ ኤጲስ ቆጶስ ዐሥራት በኵራት፣ ነጋ ድራስ ቀረጥ አምጡ ይሉናል ብለው ሳይፈሩ ይምጡ። ፫. #ወቅቱ_ወርኃ_ጾም_በመሆኑ፦ ምእመናን ይህንን ወቅት በጾም፣ በጸሎት፣ በእንባ፣ በስግደት፣ በአርምሞ፣ በመልካም ሥራ ቅድስናን የምናገኝበት፣ ጊዜው ሰው ወደ እግዚአብሔር አብዝቶ የሚተጋበት ወቅት በመሆኑ፣ ለእግዚአብሔር የሚገባ ነገር ለማድረግ የነገር ሁሉ መጀመሪያ፣ ለመልካም ነገር መነሻው በቅድስና በንጹሕ ልቡና መቅረብ ስለሆነ ቅድስት ብሏታል።  “እስመ ጾም እማ ለጸሎት ወእኅታ ለአርምሞ ወነቅዓ ለአንብዕ መቅድመ ኩሉ ግብር ሠናይት፤ ጾም ማለት የጸሎት እናት፣ የትሕትና እኅት፣ የእንባ ምንጭ፣የመልካም ሥራ ሁሉ መጀመሪያ ናት” እንዳለው ቅዱስ ያሬድ። ”ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ” የተባልን የተሰጠንን የጸጋ ቅድስና በእጃችን ላይ መኖሩን አመላካች ቃል ነው። (ኢዩ.፩፥፲፬) ፬. #የወንጌል_ትእዛዝ_በመሆኑ፡ ዕለቱን ተጠቅሞ ዓለምን አስተምሮበታል። “ዛቲ ዕለት እንተ ገብረ እግዚአብሔር ንትፈሣሕ ወንትሐሠይ ባቲ”  ትርጉም፡- “ይህች ዕለት እግዚአብሔር የሠራት ቀን  ናት፤ ሐሤትን እናድርግ፥ በእርስዋም ደስ ይበለን።” (መዝ.፻፲፯፥፳፬) ቅዱስ ዮሐንስም በራእዩ ሰንበት የጌታ ቀን ስለመሆኗ እንዲህ ይላል፤ “በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፡፡” (ራእ. ፩፥፲) ሊቃውንቱ በፍትሐ ነገሥት “ተጋብኡ ኵሎ ዕለት ኀበ ቤተ ክርስቲያን ወፈድፋደሰ በዕለተ ሰንበት ወበበዓላት ወበዕለተ ትንሣኤ ዘውእቱ ዕለተ እሑድ” ትርጉም፦ “ሁልጊዜ በቤተ ክርስቲያን ተሰብሰቡ፤ ይልቁንም በዕለተ እሑድ፣ በዕለተ ቀዳሚት፣ በጌታ በዓላት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተሰብሰቡ” በማለት አዘውናል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ ገጽ ፪፶፬) በትጋት ጾመን፣ ጸልየን ርስቱን እንድንወርስ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምልጃ፤ የቅዱሳን በረከት ይጠብቀን። የዕለቱ መዝሙር (ከጾመ ድጓ)፦ ግነዩ ለእግዚአብሔር #ምንባባት ➛ ፩ኛ ተሰ.፬÷፩-፲፫ ➛ ፩ኛ ጴጥ.፩÷፲፫-ፍጻ. ➛ ሐዋ. ፲÷፲፯-፴ #ምስባክ “እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ:: አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ፣ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ፤ (እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ፈጠረ፡፡ እምነትና በጎነት በፊቱ፣ ቅድስናና የክብር ገናናነት በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡” (መዝ.፺፭÷፭) #ወንጌል (ማቴ.፮÷፲፮-፳፭) #ቅዳሴ ዘኤጲፋንዮስ 

ጾም በአንተ ውስጥ የሆነ አንድ ነገር መለወጡን ተመልከት። ከጾም የምታገኝው ነገር የምግብ ለውጥ መሆኑን ብቻ አትመልከት። ለተሻለ ህይወት የሚደረግ ለውጥ መሆኑን ተመልከት። ይህም ማለት በአንተ ውስጥ ያለ ጉድለትንና በውስጥህ እንዳለ የሚሰማህን ከእግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር የሚሆን ድክመት ተመልከት ማለት ነው። ይህ ሳይሆን ከቀረ በሃምሳ አምስቱ የሁዳዴ ጾም ቀናት ውስጥ ራስህን አሸንፈህ ከቆየህ በኋላ ከእግዚአብሔር  ጋር የፍቅር ዝምድና እና የተረጋጋ ግንኙነት ሳትፈጥር ከጾሙ አስቀድሞ የነበረህን አቋም ሙሉ ለሙሉ ይዘህ ለመውጣት ከሆነ የነፍስህ ጥቅም ምን ሊሆን ነው? አንተ ምንም ዓይነት ለውጥ ሳታመጣና አስቀድመህ በነበርህበት ሁኔታ ውስጥ እያለህ እስከ አሁን ድረስ ስንት አጽዋማት እንዳለፉህ አስብ! በሁሉም አጽዋማት ውስጥ ፈቃድህ ደካማ ጎንህን ለማሸነፍ ስኬታማ እንድትሆን አድርጎህ ቢሆን ኖሮ ወይም ከእግዚአብሔር ጋር እንድትታረቅ አድርጎህ ቢሆን ኖሮ ወይም የእርሱን ፈቃድ ጣፋጭነት እንድትቀምስ አድርጎህ ቢሆን ኖሮ ከእግዚአብሔር። ጋር የሚኖርህ ዝምድና እስከ አሁን ድረስ እንደምን የሰፋና የጠለቀ ይሆን ነበር! ስለዚህ ንስሃ በመግባት ጾምህን ጀምር። ጾምህን በጸሎት በምጽዋት በስግደት በመንፈሳዊ ንባባት በቅዳሴ በኪዳን ጸሎቶች አጅበው። እነዚህን ሁሉ በማድረግህ ከእግዚአብሔር ጋር ትወዳጃለህ የሁዳዴ ጾም የያዛቸው በረከቶች ብዙ ናቸውና። እኒህን ካደረክ በመጨረሻ ላይ ውጤቱን ከአምላክህ ትቀበላለህ። አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ

የእግዚአብሔርን አባትነት በረሃብ እና በጥጋብ፣ በድህነት እና በባለጠግነት አትመዝነው። እርሱ ሲፈልግ በምግብ፣ ሲያሻው ደግሞ ያለ ምግብም ሊያኖርህ ይችላል። አባት ስለሆነ ግን ለአንተ ያዘጋጀው እና የፍቀ‍ሩ መታወቂያ ያደረገው መንግሥቱን ነው። ስለዚህ ከወራሽነት እንዳትወጣ ልጅነትህን ጠብቅ። መልካም የዐቢይ ጾም ይሁንልን!

#ዘወረደ ‹‹ ዘወረደ » ማለት የወረደ ማለት ሲሆን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም በፈቃዱ ሰው ሆኖ ከሰማያት ወደ መሬት ፣ ከልዕልና ወደ ትሕትና ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን የሚያመለክት ነው ። ይህ ሳምንት አምላክ ሰው ፣ ሰው አምላክ ፣ ልዑሉ ትሑት ፣ ትሑቱ ልዑል ፤ ረቂቁ ውሱን ፤ ውሱኑ ረቂቅ የመሆኑ ምሥጢር የሚወሳበት ሳምንት ነው ። ይኸውም ‹‹ ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው ›› በማለት ከሰማይም የወረደው ወደ ሰማይም የወጣው ከሁለት አካል አንድ አካል ፣ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ ኾኖ በተዋሕዶ ከብሮ ሰው የኾነ አንዱ ክርስቶስ ብቻ መኾኑን ነግሮናል ። ( ዮሐ 3 ፥ 13 ) ይህ ኀይለ ቃል በዘወረደ ሰንበት በቅዳሴው ክፍለ ጊዜ የተነበበው ይህን ምሥጢር ለማጉላት ነው ፡፡ የሶርያው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬምም ‹‹ ሰው ሰውኛውን ተመላለስ አለ ፤ የሰውነት ሥራን ሠራ ፤ ይቅር ባይ ሰው ወዳጅ ነውና ። በልዩ አመጣጡ ሰው ሆኖ አዳነን ፡፡ ›› በማለት ቃሉን ጠብቆ ጊዜውን አክብሮ ከሰማይ መውረዱን መስክሯል ( ዮሐ 1 ፥ 14 ) መተርጉማን ‹‹ በልዩ አመጣጡ አዳነን ›› የሚለውን ቃል ሲተረጉሙ ‹‹ ቀድሞ ያድነን የነበረው በመልአክ ፣ በጸጋና በረድኤት እያደረ ነበር ፤ ዛሬ ግን ያዳነን ራሱ በሥጋ ተገልጦ ሰው ሆኖ ነውና ያአሁኑ አመጣጡ ልዩ ነው ›› ሲሉ ያመሠጥሩታል ። የመናፍቃን መዶሻ የኾነው ታላቁ ሊቅ ቄርሎስም ‹‹ ያዳነን ራሱ እግዚአብሔር ነው እንጂ አማላጅ ወይም መልአክ አይደለም ፤ በባዕድ ደም በዕሩቅ ብእሲ ሞት አላዳነንም ራሱ በደሙ አዳነን እንጂ :: ›› ሲል ተናግሯል ። ‹‹ ዐምስት ሺ ዐምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ እወለዳለሁ በሜዳህ ድኬ በመስቀሌና በሞቴ አድንሃለሁ ›› ብሎ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ከሰዓቱ አንድ ሰዓት ፣ ከዕለቱ አንድ ዕለት ፣ ከወሩ አንድ ወር ፣ ከዓመቱ አንድ ዓመት ሳያዛንፍ ሳያተርፍ ፣ ሳይቀንስ ሳይጨምር ሰው ሆኖ በጽኑዕ ቀጠሮው መጥቶ ማዳኑን ተናግሯል :: ዘመኑ ሲፈጸም መለኮት ምድራዊ ሰውነትን ገንዘብ ሊያደርግ ሥጋ ደግሞ ሰማያዊ እውቀትን ገንዘብ ሲያደርግ አካላዊ ቃል እግዚኣብሔር ወልድ ከሰማይ መውረዱን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲናገር ‹‹ የዘመነ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ ። ›› ( ገላ 4 ፥ ፬ ) ብሎ እንደተናገረ የጠፋውን አዳምን ፍለጋ ከአባቱ ዕሪና ሳይነጠል ከክብሩ ሳይጎድል ከሰማየ ሰማያት መውረዱን የምናዘክርበት ሳምንት ነው ። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ ቅድመ ዓለም የነበረ ዛሬም ያለ ፤ ወደ ፊትም ዓለምን አሳልፎ ለዘለዓለም የሚኖር ከላይ የወረደውን እርሱን አይሁድ ሰቀሉት በቃሉ የሚያድን የሁሉ ጌታ መሆኑን ምንም አላወቁምና ›› በማለት በዚህ ሳምንት ጌታችን እኛን ለማዳንና ፍቅሩን ሊገልጥልን ከሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ተወልዶ መከራ መቀበሉን ያዘክራል ፡፡ ዳግመኛም ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ጾመ ሕርቃል ይባላል ፡፡

"በጎ ነገር አግኝተህ እንደ ሆነ እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ነገር ከአንተ ጋር ጸንቶ ይኖራል፡፡ በጎ ያልሆነ ነገር ደርሶብህ እንደሆነም እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ያልሆነ ነገር ወደ በጎ ነገር ይቀየራል፡፡" ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

#የካቲት_16 #ኪዳነ_ምሕረት (#የሰባቱ_ኪዳናት_ማሕተም) የካቲት ዐሥራ ስድስት በዚችም ዕለት የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም አማላክን ለወለደች ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓልን ያደርጋሉ። በዚች ዕለት መታሰቢያዋን ለሚያደርግ ስሟን ለሚጠራ ለድኆችና ለችግረኞች እስከ ቀዝቃዛ ውኃ ለሚሰጥ የክብር ባለቤት ከሆነ ከተወደደ ልጅዋ ከጌታችንና ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳንን ተቀብላለችና። ይህችም የከበረች እመቤታችን ልጅዋ ንጹሕ ሥጋዋን ተዋሕዶ ከብቻዋ ኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ፈጽሞ ስለእኛ መዳን ወዶ ያደረገውን መከራ ተቀብሎ ሙቶ ተነሥቶ ከዐረገና በአባቱ ዕሪና ከተቀመጠ በኋላ እርሷን እናቱን ማርያምን በደቀ መዝሙሩ ዮሐንስ ዘንድ ትቷት ነበር እነሆ ልጅሽ እርሱንም እነሆዋት እናትህ ብሎ አደራ እንዳስጠበቀው። ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ማርያም ትጸልይ ዘንድ ያለ ማቋረጥ ወደ ልጅዋ መቃብር ሁል ጊዜ ስትሔድ ኖረች ይኸውም ጎልጎታ ነው። አይሁድም በአዩዋት ጊዜ ቍጣንና ቅናትን ተመልተው በድንጊያ ሊወግሩዋት ወደዱ እግዚአብሔርም ከዓይናቸው ሠወራት ከዚህም በኋላ ዳግመኛ መጥታ በዚያ እንዳትጸልይ ተማክረው ከመቃብሩ ዘንድ ጠባቂዎችን አኖሩ እርሷ ግን በየዕለቱ መሔድን አላቋረጠችም ጠባቆችም አያይዋትም የልጅዋ የጌትነቱ መጋረጃ ሠውርዋታልና መላእክትም መጥተው ያገለግሏታል ጌታችንም ዘወትር ይጐበኛታል የምትሻውንም ይፈጽምላት ነበር። ከዚህም በኋላ መላእክት ወደ ሰማይ አሳረጓትና የጻድቃንን ማደሪያዎች አሳዩዋት አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብም ወዳሉበት አደረሱዋት ከአዳም ጀምሮ እስከዚያ ዕለት በአካለ ነፍስ ያሉ አባቶች ሁሉ አንቺን ከሥጋችን ሥጋን ከዐፅማችን ዐፅምን ለፈጠረልን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የአምላክ ልጅ ከአንቺ ሰው በመሆኑ በአንቺ ድህነት አግኝተናል ከጥፋትም የሕይወት ወደብ ሆነሽልናልና እያሉ ሰገዱላት። ከዚያም ወደ ተወደደ ልጅዋ የእሳት መጋረጃ ወደተተከለበት ወደ ጌትነቱ ዙፉን አደረሷት ጌታችንም እጇን ይዞ ወደ ውስጠኛው መጋረጃ አስገብቶ ከጌትነቱ ዙፋን ላይ አውጥቶ ከእርሱ ጋር አስቀመጣት ያዘጋጀላትንም ዐይን ያላየው ጆሮ ያልሰማው በሰው ልቡና ያልታሰበ ተድላ ደስታን ሁሉ ነገራት። ከጌትነቱ ዙፋንም በታች የእስራኤል ንጉሥ አባቷ ዳዊትን የነቢያትና የመላእክት ማኀበር እንደ ግድግዳ ከበውት በመሰንቆ ሲያመሰግን አየችው እንዲህም ይላል ልጄ ስሚ በጆሮሽም አድምጪ ወገንሽን የአባትሽንም ወገን ርሺ ንጉሥ ደም ግባትሽን ወዷልና እርሱም ጌታሽ ነውና። ዳግመኛም የሥቃይን ቦታ ያሳዩዋት ዘንድ መላእክት ከዚያ ውሰዷት ለሰይጣንና ለሠራዊቱ በእርሱ ጐዳና ለሚጓዙ ሁሉ ወደተዘጋጀ ወደጨለማው ዳርቻ አደረሷት እመቤታችን ማርያምም ወዮልኝ ወደዚያ እንዳይመጡ ለሰው ልጆች ማን በነገራቸው አለች መልአኩም አመቤቴ ቡርክት ማርያም ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኖራልና ለአንቺም ከአንቺ በኋላም በቃል ኪዳንሽ ለሚታመኑ አትፍሪ አላት ከዚህም በኋላ ወደ ቦታዋ መለሷት። ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ድንግል ማርያም ስለ ኋጥአን እጅግ እያዘነች ኖረች እንደ ዛሬይቱም የካቲት ዐሥራ ስድስ ቀን በጎልጎታ ቦታ ቁማ ወደ ልጇ እንዲህ ብላ ለመነች ልጄ ሆይ በእግዚአብሔር አባትህ በክርስቶስ ስምህ ከአንተ ጋርም ህልው በሆነ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ አማፅንሃለሁ ዓለም ሁሉ ሊሸከምህ የማይችል ሲሆን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በተሸከመችህ ማሕፀኔ አማፅንሃለሁ ልጄ ሆይ ያለ ሕማም ያለ ድካም ከእኔ በመውጣትህ በመወለድህ በአሳደጉህ ጡቶቼ በሳሙህ ከንፈሮቼ በአቀፋህ እጆቼ ከአንተ ጋር በተመላለሱ እግሮቼ አማፅንሃለሁ ። በውስጡ በተኛህበት በረት በተጠቀለልክበት ጨርቅ አማፅንሃለሁ የምወድህ ልጄ ሆይ በልቡናዬ ያለውን ሁሉ ትፈጽም ዘንድ የልመናዬን ቃል ሰምተህ ወደእኔ ትመጣ ዘንድ ወዳንተ ፈጽሜ እማልድሃለሁ። የብርሃን እናቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንዲህ ብላ በጸለየች ጊዜ እነሆ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ከእርሱም ጋር አእላፍት መላእክት አሉ በዙሪያውም ሁነው ያመሰግኑታል እርሱም እናቴ ማርያም ሆይ ምን ላድርግልሽ አላት እመቤታችንም ለተወዳጅ ልጅዋ እንዲህ ብላ መለሰችለት ልጄ ወዳጄ ሆይጌታዬና ፈጣሪዬ አለኝታዬና መጠጊያዬ በእናቴ ማሕፀንም ሳለሁ ባንተ ጸናሁ አንተም ጠበቅኸኝ ሁልጊዜም ስም አጠራሬ አንተ ነህ። አሁንም ጸሎቴንና ልመናዬን ስማኝ ቃሌንም አድምጥ እኔ እናትህ እኔም አገልጋይህ የምለምንህ ይህ ነው መታሰቢያዬን ለሚያደርጉ በስሜ አቢያተ ክርስቲያን ለሚሠሩ ወይም የተራቆተውን ለሚያለብሱ የተራበውን ለሚያጠግቡ የተጠማውንም ለሚያጠጡ የታመመውን ለሚጐበኙ ያዘነውን ለሚያረጋጉ የተከዘውንም ደስ ለሚያሰኙ ወይም ምስጋናዬን ለሚጽፉ ልጆቹንም በስሜ ለሚሰይም በበዓሌም ቀን በማኅሌት ለሚያመሰግን አቤቱ ዐይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰውም ልቡና ያልታሰበውን በጎ ዋጋ ስጣቸው በአማላጅነቴም የሚታመነውን ሁሉ ከሲኦል ነጻ አድርገው ከአንተ ጋር የደረሰብኝን ረኃቡንና ጥማቱን መከራውን ሁሉ አስብ አለችው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዳልሽው ይሁንልሽ የሰጠሁሽም ቃል ኪዳን እንዳይታበል በራሴ ማልኩልሽ አላት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን ድንግል ማርያም በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ እለእስክንድሮስ ቂርቆስንና እናቱን ወደ አደባባይ ያመጡአቸው ዘንድ አዘዘ ያን ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ ነበርና እንዲህም አለ ሕፃኑንና እናቱን ከቆዳቸው ጋር ራሳቸውን ላጩአቸውና በላያቸው የእሳት ፍሞችን ጨምሩ እርር ብለው እንዲቃጠሉ ዳግመኛም አራት ችንካሮችን ከትከሻዎቹ እስከ ተረከዙ ድረስ እንዲተክሉበት አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ መጥቶ ሥቃዮችን ከርሱ አራቀ። ዳግመኛም ከጥዋት እስከ ማታ ከሥቃይ መሣሪያዎች ውስጥ ጨምረው አዋሏቸው ግን ማሠቃየት ተሳናቸው። ከዚህም በኋላ ከማምጠቂያው ውስጥ ጨምረው መገዙአቸውና አመድ እስከሆኑ ከቅባትና ከጨው ጋር በብረት ምጣድ ውስጥ ቆሉአቸው ጌታችንም ከሞት አስነሥቶ አዳናቸው። ወደ መኰንኑም በገቡ ጊዜ  እንዲህ አላቸው በእውነት ከሙታን ተለይታችሁ የተነሣችሁ ከሆነ ይህ ጫማዬ ከእግሬ ወጥቶ እንደ ቀድሞው ሕያው እንዲሆን አድርጉ ሕፃን ቂርቆስም በጸለየ ጊዜ ያ ጫማ ታለቅ በሬ ሆነ ከአንገቱም ፍየል ወጣ። በዚያንም ሰዓት ለዐሥራ አንድ ሽህ አራት ሰዎች በሬውንና ፍየሉን አርደው ምሳ እንዲያደርጉላቸው መኰንኑ አዘዘ እንዲህም አለ ይህ በቅቷቸው ከጠገቡ ከዚህም ሌላ ምግብ ካልፈለጉ የተሠራው ሁሉ ዕውነተኛ ነዋሪ ነው። ከዚህም በኋላ አርደው ምሳ አደረጉላቸውና ከፍየሉ ሥጋ ስድስት እንቅብ ከበሬው ሥጋ አራት እንቅብ አተረፉ መኰንኑም የተረፈውን ሥጋ አይቶ ወደ ባሕር እንዲጥሉት አዘዘ። መኰንኑም ቢያፍር የሕፃኑን ምላስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ጌታችንም ምላሱን መለሰለት ዳግመኛም በታላቅ ጋን ውኃ እፍልተው ሕፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይጨምሩአቸው ዘንድ አዘዘ እናቱም አይታ ፈረች። ልጅዋም ወደ እግዚአብሔር በጸለየላት ጊዜ አምላካዊ ኃይልን አሳደረባትና ከልጅዋ ጋር ወደ ጋኑ ገባች። እንደ ውርጭም ቀዝቀዛ ሆነ ደግሞም በውስጡ መንኰራኲር ወዳለበት የብረት ምጣድ እንዲጨምሩአቸውና ሥጋቸው እሰከሚቦጫጨቅ እንዲስቡአቸው አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ በሕይወት አወጣቸው። መኰንኑም እነርሱን ማሸነፍ በተሳነው ጌዜ ቸብቸቧቸውን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚያን ጊዜ ለስም አጠራሩ ስግደት የሚገባው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ሕፃን ቂርቆስንም የምትሻውን ለምነኝ አለው። ሕፃኑም ሥጋዬ በምድር አይቀበር ስሜን ለሚጠራ መታሰቢያዬን ለሚያደርግ ቤተ ክርስቲያኔን ለሚሠራ የተጋድሎዬን መጽሐፍ ለሚጽፍና ለሚያጽፍ ወይም ለሚያነበው ለቤተ ክርስቲያኔ መባ ለሚያገባ በውስጧም ለሚጸልይ ለሁሉም ፍላጎታቸውን ስጣቸው ኃጢአታቸውንም ይቅር በል ስሜም በሚጠራበት በዚያች ቦታ የከብት ዕልቂት አይምጣ በሰውም ላይ እባር ቸነፈር በእህልም ላይ ድርቅ የውኃም ማነስ አይሁን። መድኃኒታችንም የለመንከኝን ሁሉ እሰጥሃለሁ አንተም በቀኜ ትኖራለህ ሥጋህንም ኤልያስ በዐረገበት ሠረገላ ውስጥ አኖራለሁ አለው ሕፃን ቂርቆስም በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት ጌታችንን አመሰገነው። ከዚህም በኋላ በሌሊቱ እኩሌታም ከእናቱ ጋር አንገቱን ተቆረጠ መድኃኒታችንም በማይጠፋ አክሊል ጋረደው ነፍሶቻቸውንም በታላቅ ክብር ከእርሱ ጋር አሳደገ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አብድዩ_ነቢይ በዚህች ቀን ዕውነተኛ ነብይ አብድዩ አረፈ። ይህም ነብይ የሐናንያ ልጅ ነው። በንጉሥ ኢዮሳፍጥም ዘመን ትንቢት ተናገረ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው። ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው አብዝቶ መከራቸውም ገሠጻቸውም። ይህም ንጉሥ አካዝያስ ይጠሩት ዘንድ ወደ ኤልያስ ከላካቸው ሦስተኛ መስፍን ነው። ከእርሱ አስቀድመው የመጡ እነዚያን ሁለት መስፍኖች በኤልያስ ቃል እሳት ከሰማይ ወርዳ ከእነርሳቸው ጋር ካሉ ወታደሮች ጋር በላቻቸው። ይህ ግን ወደ ኤልያስ በመጣ ጊዜ በፊቱ ተንበርክኮ ሰግዶ ተገዛለት እንዲህም  አለው የእግዚአብሔር ሰው ተገዛሁልህ የእሊህ የባሮችህ ሰውነትና የኔ ሰውነት በፊትህ ትክበር በእግዚአብሔር ነቢይ ላይ ፈጽሞ አልታበየምና ነቢዩ ኤልያስም ራራለት ወርዶም ከርሱ ጋር ወደ ንጉሡ ሔደ። ይህም አብድዩ ከምድራዊ ንጉሥ አገልግሎት የኤልያስ አገልገሎት እንደምትበልጥ የኤልያስም አገልገሎት ለሰማያዊ ንጉሥ አገልገሎት ታደርሳለችና ይህን በልቡ ዐወቀ ስለዚህ ምድራውያን ነገሥታትን ማገልገል ትቶ ነቢይ ኤልያስን ተከተሎ አገለገለው  በላዩም ከእግዚአብሔር ሀብተ ትንቢት አደረበትና ትንቢትን የሚናገር ሆነ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በዘጠኝ መቶ ዓመት በሰላም በፍቅር አንድነትም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘኑሲስ በዚህችም ቀን ዳግመኛ በሶርያ አገር  ያሉ የክርስቲያን ወገኖች የቅዱስ ጎርጎርዮስን የዕረፍቱን መታሰቢያ በዓል ያከብራሉ። ይህም አባት በነፍስ በሥጋ በበጎ ሥራ ሁሉ ከወላጆቹ ጋር ፍጹም ነው። እርሱ እግዚአብሔርን መፍራትንና ትምህርቶችን ተምሮ ዐውቋልና የቋንቋም ትምህርት እጅግ የሚያውቅ የዮናናውያንንም ቋንቋ የሚያነብና የሚተረጒም ለቀና ሃይማኖትም የሚቀና ሆነ በውስጡም በጎ ሥራ በጎ ጠባይ ተፈጸመለት ኑሲስ በምትባል አገርም ላይ ሳይወድ በግድ መርጠው ኤጲስቆጶስነት ሾሙት እርሷም ደሴት ናት የእግዚአብሔርንም መንጋዎች ጠበቀ በትምህርቱና በድርሰቶቹም ልቡናቸውን ብሩህ አደረገ የብሉያትንና የሐዲሳትንም መጻሕፍት ተረጐመ። ጳጳስ ሁኖ ስለነበረው ስለ ከሀዲው መቅዶንዮስ በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ዘመን በቊስጥንጥንያ ከተማ የመቶ ሃምሳ ኤጲስቆጶሳት የአንድነት ስብሰባ በሆነ ጊዜ ይህ ጎርጎርዮስ ከአባቶች ኤጲስቆጶሳት ጋር ሁኖ የሰባልዮስን ወገኖች መቅዶንዮስንና አቡሊናርዮስን ተከራከራቸው መልስ አሳጥቶም አሳፈራቸው። ስሕተታቸውንም ገለጠ። ይህም የካቲት አንድ ቀን ተጽፎአል የእነዚህንም ክህደት አስወገደ በቃሉ  ሰይፍነትም የንባባቸውን የስሕተት ሐረግ ቆራርጦ አጠፋ ከተሰበሰቡትም ጋር በሰላም ተመለሰ እነርሱ በድል አድራጊነት እነዚያም ከሀ**ድያን በኀፍረት ሆነው ተመለሱ ። ወደ መልካም እርጅና ደርሶ እግዚአብሔርንም ደስ አሰኝቶ አገልገሎ በሰላም አረፈ እነሆ በዚህ ወር ጥር ሃያ አንድ ቀን ከገድሉ ጥቂት ጽፈናል ይኸውም በግብጻውያን ዕረፍቱ ነው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)

#ጥር_15 አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥር ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን #ቅዱስ_ቂርቆስና_ቅድስት_ኢየሉጣ በሰማዕትነት አረፉ፣ #ነብዩ_ቅዱስ_አብድዩ አረፈ፣ በሶርያ ክርስቲያን ወገኖች #የቅዱስ_ጎርጎርዮስን የዕረፍቱን መታሰቢያ በዓል ያከብራሉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ ጥር ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን ቂርቆስ እናቱ ብፅዕት ኢየሉጣ ዳግመኛ ለከበረ  ሕፃን ቂርቆስ ማኅበር የሆኑ ዐሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ። በዚያንም ወራት የክብር ባለቤት የሆነ ክርስቶስን በሚያምኑ የክርስቲያን ወገኖች ላይ ታላቅ መከራና ስደት ሆነ። ስሟ ኢየሉጣ የሚባል አንዲት ሴት ነበረች እርሷም ከታናሽነቷ  ጀምራ ደግ ናት ስደትም እንደሆነ በሰማች ጊዜ መኰንኑን ከመፍራት የተነሣ ሕፃኗን ይዛ ከሮም ከተማ ተሰዳ የኪልቅያ አውራጃ  ከሆነ ከጠርሴስ ደርሳ ከዚያም  በሀገሮች ውስጥ እየተዘዋወረች ተቀመጠች። ወደዚያች አገርም ያ ከእርሱ የሸሸችው መኰንን እለእስክንድሮስ መጣ ጭፍሮቹም ክርስቲያኖችን ፈለጓቸው። ይቺንም ቅድስት ኢየሉጣን አግኝተው ያዝዋትና ወደ መኰንኑ አደረሷት የክርስቲያን ወገንም እንደሆነች ነገሩት። መኰንኑም ሴትዮ ተናገሪ ከወዴት ሕዝብ ወገን ነሽ ነገድሽ ምንድን ነው ሀገርሽስ ወዴት ነው አላት። የከበረች ኢየሉጣም እንዲህ ብላ መለሰችለት የአንጌቤን ሰው ለሆንኩ ለእኔ ወገኖቼ ለኢቆንዮን አገር አለቆች የሆኑ ኤሳውሮሳውያን ናቸው እኔም በአንተ ምክንያት ሸሽቼ ነበር እነሆ ዛሬ ግን በእጅህ ውስጥ ነኝ አለችው። መኰንኑም በእጄ ውስጥ እንደተገኘሽ ታውቂያለሽን አላት አሁንም የሚሻልሽን ምረጪ ስምሽንም ተናገሪ እኔንም እሺ በይኝና ለአማልክት ሠዊ የከበረች ኢየሉጣም ለረከሱ አማልክት እኔ አልሰዋም አለችው መኰንኑም ስምሽን ስጪ ተናገሪ አላት እርሷም የኔ ስም ክርስቲያን መባል ነው አለችው። መኰንኑም ይህስ ስንፍና ነው የሚጠቅምሽ አይደለም እንዳትሞቺ ስምሽን ስጪ ተናገሪ አላት። የከበረች ኢየሉጣም የኔ ስም ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞት የሚሽረው በሰዎች ዘንድ የምጠራበትን ከፈለግህ ስሜ ኢየሉጣ ነው ብላ መለሰችለት። መኰንኑም ጽኑ የሆኑ ሥቃዮችን በላይሽ ሳይመጣ ተነሥተሽ መሥዋዕትን ለአማልክት አቅርቢ አላት። የከበረች ኢየሉጣም ዕወነት ነገርን ለመሥራት የምትሻ ከሆነ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነ ሕፃን ልጅ ይፈልጉ ዘንድ ወደ ሀገሩ መንደር ላክ ወዳንተም ያምጡትና የምንገዛለትንና የምናመልከውን እርሱ ይንገረን አለችው። ያን ጊዜም የሦስት ዓመት ልጅ ይፈልጉ ዘንድ መኰንኑ ወታደሮችን ላከ የሀገር ሰዎችም ልጆቻቸውን ሠውረዋልና አላገኙም ከዚያም ከከተማው ቅጽር ውጭ በፀሐይ መውጫ ወዳለው በረሀ በኩል ወጡ የቅድስት ኢየሉጣንም ልጅ አገኙት ይህ ሕፃን የስንት ዓመት ልጅ ነው ብለው ስለርሱ ጠየቁ ሰዎችም ይህ ሕፃን የሦስት ዓመት ሲሆን የክርስቲያናዊት መበለት ልጅ ነው አሏቸው። ያንንም ሕፃን ይዘው ወደ መኰንኑ ወሰዱት መኰንኑም መልኩ የሚያምርና ደም ግባት ያለው እንደሆነ በአየው ጊዜ ደስ የምትል ደስተኛ ሕፃን ሰላምታ ይገባሃል አለው። ሕፃኑም እኔን ደስተኛ ማለትህ መልካም ተናገርክ ላንተ ግን ደስታ የለህም እግዚአብሔር ለዝንጉዎች ደስታ የላቸውም ብሏልና ብሎ  መለሰለት መኰንኑም ሕፃኑን ሳልጠይቅህ ይህን ያህል ትመልስልኛለህን አለው። ሕፃኑም ገና ከዚህ የሚበዛ ነገርን እመልስልሃለሁ አለው። መኰንኑም ሕፃኑን ስምህ ማን ነው አለው ከንጹሕ ዐዘቅትና ከማይለወጥ ከማይጠፋ ውኃ የተገኘ ሕፃን ስሜ ክርስቲያን መባል ነው ብሎ መለሰለት። መኰንኑም ዳግመኛ እንዳትሞት  ስምህን ንገረኝ አለው የከበረ ሕፃንም ስሜ ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞክሼ ስም የምትሻ ከሆነ እናቴ የሰየመችኝ ቂርቆስ ነው። መኰንኑም ሕፃን ቂርቆስን እሺ በለኝና ለአማልክት ሠዋ በሥጋህም ስታድግ እሾምሃለሁ በብዙ ወርቅና ብርም አከብርሃለሁ አለው። ሕፃኑም የሰይጣን መልእክተኛ ለዕውነትም ጠላቷ የሆንክ ከእኔ ራቅ አለው። መኰንኑም ሰምቶ ተቆጣ ደሙ እንደ ውኃ እስከሚፈስ ቆዳውን እንዲጨምቁትና እንዲገፉት አዘዘ። የከበረች ኢየሉጣም የልጅዋን ትዕግሥት ባየች ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገነችው። ከዚህም በኋላ መኰንኑ ጨውና ሰናፍጭ አምጡ አለ የሁለቱንም አፍንጮቻቸውን ከፍተው ያንን ጨውና ሰናፍጭ እንዲጨምሩባቸው አዘዘ ያን ጊዜ ሕፃኑ ትእዛዝህ ለጕረሮዬ ጣፋጭ ሆነ ከማርና ከስኳርም ለአፌ ጣመኝ ብሎ ጮኸ። ሁለተኛም መኰንኑ እንዲህ ብሎ አዘዘ የረዘሙና የተሳሉ በእሳትም እንደ ፍም የጋሉ ዐሥራ አራት  የብረት ችንካሮች  አምጡ ሰባቱን በእናቱ አካላት ውስጥ ጨምሩ በሕፃኑም ሁለት በጆሮዎቹ ሁለት በዐይኖቹ ሁለት በአፉና በአፍንጫው አንድ በልቡ ጨምሩ እንዲህ ሲጨመርበት ጆሮዎቹ እንዲአሩ ዐይኖቹም ይጠፉ ዘንድ አንደበቱም ይቃጠል ዘንድ ወደ ልቡም ጽኑ ሕማም ገብቶ እርሱ ከዚህ ዓለም በሞት እንዲለይ ለእናቱም እንዲሁ አድርጉ ችንካሮችም በቅዱሳኑ በሥጋቸው ሁሉ ተጨመሩ።      የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ትእዛዝ የብረቶቹ ግለት ጠፍቶ እንደ በረዶ ቀዘቀዘ ጤነኞችም ሆኑ መኰንኑም ወደ ወህኒ ወስዳችሁ በዚያ አሥራችሁ ዝጉባቸው አለ።                          ከዚህም በኋላ መኰንኑ የሥቃይ መሣሪያ ይሠራ ዘንድ አንዳዝዘው ብረትን የሚያቀልጥ ሰው አምጡልኝ አለ። በአመጡለትም ጊዜ ሰይጣኑ ወደ መኰንኑ ልብ ገብቶ አንደበቱን ዘጋውና መናገር ተሳነው ሕፃኑ ፈጥኖ አክሊልን ለመቀበል እንደሚተጋ ሰይጣን ስለ አወቀ ስለዚህ ዘጋው። ከዚህም በኋላ ሕፃኑ ሠራተኛውን ጠርቶ እኔንና እናቴን የሚያሠቃዩበትን የሥቃይ መሣሪያ መሥራት ትችላለህን ይህ መኰንን ግን ምንም የሚያውቀው ነገር የለም አለው ሠራተኛውም እንደምትሻው በል ንገረኝ እንደምታዝዘኝ እኔ መሥራት እችላለሁ አለው። ሕፃን ቂርቆስም ሊአዝዝ ጀመረ እንዲህም አለ ሁለት መላጫዎች ስፋታቸው አራት ክንድ የሆነ ለእኔና ለእናቴ ሥራ። ዳግመኛም የሚያስጨንቅ ራስን የሚመታና የሚሰብር አንገትንም የሚያሥር የሚዝቅም ሹካ ዐይንንም የሚያወልቅ አካልንም የሚበሳሳ አፍንጫንም የሚያጣምምና የሚሰብር ጆሮንም  የሚልጥ ሕዋሳትን የሚፈታና የሚለያይ እንደ ልጓም ሁኖ ምላስን የሚቆርጥ በሰውነትም ውስጥ ገብቶ የሚንቀሳቀስ ቆላፋ ጉጠትን ጐኖችንም የሚፍቅና የሚቆለምም አስጨናቂ የሆነ ጉልበቶችንና ጭኖችን የሚሰብር ጅማቶችንም የሚቆራርጥ ሥሮችንም የሚመዝ በዚችም አስጨናቂ መሣሪያ ጅማቶችን የሚታታ አድርግ። ዳግመኛም በላም አምሳል ሰፊ መቀመጫ ከናስ ሥራ ሦስት ቀዳዳዎችንም በዚያ መቀመጫ ውስጥ ቅደድ። በቁመቴም ልክ ሦስት ችንካሮችን ሥራ የችንካሮቹንም ራስ ከናስ አድርገህ በውስጡ ከሚጠሩት ዘንድ ፈጽሞ የማይለይ ልዩ ሦስት ብለህ ጻፍ። ዳግመኛም ጠምዝዞ ወደ ላይ የሚያወጣ ሁለት መሣሪያ ሁለት መጋዞችን ሁለት የብረት ምጣዶችን ሥራ አሁንም አንድ ታላቅ ጋን ሠርተህ በውስጡ አንገትን የሚጠመዝዝና የሚሠነጥቅ ተሽከርካሪ መሣሪያ አድርግ። በውስጥ የተሸሸገ የሆድ ዕቃን የሚመረምር እጅን ከብረት ሥራ እኔ የጻዕር  ስቃይን የምሠቃይበት ይህ ነው አለ። ብረት ሠሪውም ሰምቶ እጅግ አደነቀ የሚረዱትንም ከሀገር ውስጥ መቶ ሠራተኞችን ሰብስቦ መሥራት ጀመረ በአርባ ቀንም ጨረሰ።

የከበረ አርኬሌድስም ከመምጣቱ በፊት ለአበምኔቱ መንፈስ ቅዱስ አስረድቶት ነበር ወደርሱም በደረሰ ጊዜ አበ መኔቱ ደስ አለው የከበሩ መነኮሳትን ሁሉንም ሰበሰባቸውና በቅዱስ አርከሌድስ ላይ ፀለዩ። አበ ምኔቱም የምንኩስና ልብስን አስኬማንም አለበሰው መነኮሳቱ ሁሉም በእርሱ ደሰወ አላቸው የእግዚአብሄር ፀጋ በላዩ ተገለፃለችና። ከዚህም በኃላ የከበረ አርከሌድስ በጠባብ መንገድ ተጠመደ ፅኑ ገድልን ተጋድሏልና ሁልጊዜ በየሰባት ቀን የሚፆም ሆነ በቀንና በሌሊትም ይፀልያል እግዚአብሄርም ሀብተ ፈውስን ሰጥቶት በእምነት ወደርሱ የሚመጡትን ብዙዎች በሽተኞችን አዳነቸው። የሴቶችንም ፊት ከቶ እንዳያይ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገባ ከእናቱ ዘንድም አስራ ሁለት አመት ያህል ወሬው መሰማቱ በዘገየ ጊዜ በእርሱም የሆነውን አላወቀችም የሞተ መስሏታልና እጅግ አዘነች። ከዚህም በኃላ የእንግዶችና የመፃተኞች መቀቢያ የሚሆን ቤትን ሰራች መንገደኞችም እንዲአድሩበት አደረገች በአንዲትም እለት የብፁእ አርከሌድስን ዜና ሲናገሩ መንገደኞችን ሰማቻቸው እንርሱም ቅድስናውን ተጋድሎውን ምልክቶቹንም የመልኩንም ደም ግባት ሰምታ ልጅዋ እንደሆነ አወቀች ደሰግመኛም መንገደኞችን ጠየቀቻቸው ስራውን ሁሉ ነገሩዋት እርሱ ህያው እንደሆነ ተረዳች። በዚያንም ጊዜ ተነስታ ወደ ከበረ ሮማኖስ ገዳም ሄደች ወደ ልጅዋ ወደ አርከሌድስም እንዲህ ብላ ላከች እነሆ ፊትህን አይ ዘንድ ወድጄ እኔ እናትህ መጥቻለሁ። እርሱም ከቶ የሴቶችን ፊት እንዳለሰይ ከክበር ባለቤት ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገብቻለሁና ቃል ኪዳኔን ማፍረስ አይቻለኝም ብሎ መልሶ ወደርሷ ላከ ።ዳግመኛም ፊትህን ካላሳየኸኝ እኔ ወደ ዱር እሄዳለሁ አራዊትም ይበሉኛል ብላ ወደርሱ ላከች። የከበረ አርከሌድስም እርሷ እንደማትተወው እርሱም ለእግዚአብሄር የገባውን ቃል ኪዳን ማፍረስ እንደማይቻለው በአወቀ ጊዜ ነፍሱን እንዲወስዳት ወደ ጌታችን ለመነ ከዚህም በኃላ የበሩን ጠባቂ ወደ እኔ ትገባ ዘንድ እናቴን ተዋት አለው ።በገባችም ጊዜ ሙቶ አገኘችውና በታላቅ ድምፅ በመጮህ አለቀሰች ነፍሷንም ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ለመነች ልመናዋንም ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ። ከዚህም በኃላ ስጋዋን ከልጅዋ ስጋ ለይተው ለብቻዋ ሊቀበሩ ወደዱ ከከበረ አርከሌድስም በድን የእናቴን ስጋ ከስጋዬ አትለዩ በህይወቷ ሳለች ታየኝ ዘንድ ልቧን ደስ አላሰኘሁምና የሚል ቃል ወጣ።ይህንንም ቃል በሰሙ ጊዜ አጅግ አደነቁ እግዚአብሄርንም አመሰገኑት ሁለቱንም በአንድ መቃብር ውስጥ ቀበሩአቸው ጌታችንም ለበሽተኞች ታላቅ ፈውስን ከስጋው ገለጠ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_እምራይስ በዚህችም እለት የከበረች እምራይስ በሰማእትነት አረፈች። ይቺም ብፅእት በክርስቶስ ሀይማኖት ለፀኑ ለከበሩ አባቶች ልጅ ናት ፈሪሀ እግዚአብሄርንም እየተማረች አደገች።በአንዲትም እለት ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ስትወርድ ስለ ክርስቶስ የታሰሩ እስረኞችን አየች። እንርሱም ጳጳሳት ቀሳውስትና ዲያቆናት ናቸው ከእነርሱም ጋር ስሟን ይፅፍ ዘንድ መዘጋቢውን ለመነችው መዘገባትም ወደ ከሀዲውም መኮንን ወደ ቁልቁልያኖስ አቀረባት።እርሱም ለጣኦት ትሰግድ ዘንድ በብዙ ነገር ሸነገላት እምቢ ባለችውም ጊዜ ቸብቸቦዋን ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ከተባባሪዎቿም ጋር ምስክርነቷን ፈፀመች። አምላከ ቅዱሳን ለቅዱሳኑ ካደለው ፍቅራቸው ለእኛም አይንሳን:: በረከታቸውንም ያብዛልን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር_እና_ጥቅምት)