cookie

Ми використовуємо файли cookie для покращення вашого досвіду перегляду. Натиснувши «Прийняти все», ви погоджуєтеся на використання файлів cookie.

avatar

የቅድስት በርባራ እና ቅድስት ማሪና የታዳጊዎች እና የወጣቶች በጎ አድራጎት ማኅበር

ማኅበሩን በሚመለከት ያለዎትን ማንኛውም ዓይነት አስተያየትም ሆነ ጥያቄ ቀጣዩን ማስፈንጠሪያ ይጠቀሙ 👉 @StBARBARAStMARINAComment_bot

Більше
Рекламні дописи
208
Підписники
Немає даних24 години
Немає даних7 днів
Немає даних30 днів

Триває завантаження даних...

Приріст підписників

Триває завантаження даних...

በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስ በጀመረው ፍጹም ሰላማዊ ና ሕጋዊ መንገድ ከመንግሥት ጋር የደረስንበትን ውጤት በየጊዜው የምናሳውቃችሁ ስለሆነ እንደዚህ ቀደሙ ፍፁም በሆነ መንፈሳዊ ጨዋነት የቅዱስ ሲኖዶስን መልእክት እንድትጠባበቁ፤ አሁንም ቢሆን ያለመዘናጋት ቤተ ክርስቲያናችሁን በጥብቅ ሁኔታ እንድትጠብቁ እና ቤተ ክርስቲያናችሁ ላይ የሚያጋጥሙትን ችግሮች ሁሉ በተዋረድ ላለው መዋቅራችሁ እንድታሳውቁ አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡ ያዕቆብ መልእክት ፩፤፪-፫ “ወንድሞቼ ሆይ የእምነታችሁ መፈተን ትእግስትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፤ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደሙሉ ደስታ ቁጠሩት” ወስብሐት ለእግዚአብሔር እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ የካቲት ፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
Показати все...
በስመ አብ፤ ወወልድ፤ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!! ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ወቅታዊ ጉዳይ ከመንግሥት ጋር እየተደረገ ስለሆነው ውይይት እና የካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በሀገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ደረጃ ሊደረግ ስለታሰበው ሰላማዊ ሰልፍ አስመክቶ የተሰጠ መግለጫ ሮሜ ፭፤፫-፬ “ መከራ ትእግስትን እንዳያደርግ፤ ትእግስትም ፈተናን፤ ፈተናም ተስፋን እንዳያደርግ እያወቅን በመከራችን ደግሞ እንመካለን” የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን! በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በቅርቡ ከቤተ ክርስቲያናችን ሃይማኖታዊ፤ ቀኖናዊ እና አስተዳደራዊ ሥርዓት ፍጹም ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ በመደራጀት የቤተ ክርስቲያንን መብትና ጥቅም የጎዳ ተግባር መፈጸሙ ይታወሳል፡፡ የተከበረውን የአበው ሐዋርያዊ ሢመተ ኤጲስ ቆጶስነት ሥርዓት በመፈጸማቸው ምክንያት በተፈጠረው የቤተ ክርስቲያንን ሉዓላዊ ክብርና ልዕልና የማቃለል፣ ሀገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ውለታ የዘነጋ፣ ሕልውናዋን እና አንድነቷን ለመናድ የተደረገ ከፍተኛ ጥቃት በመፈጸሙና መንግሥትም የቤተ ክርስቲያናችንን ሕግና ሥርዓት፣ እንዲሁም ተቋማዊ ሕልውና እንዳያስከብር እና እንዳያከብር በተደጋጋሚ ሲጠይቅ ቆይቷል፡፡ ከዚህም ውስጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በየካቲት ፪ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ባወጣው መግለጫ መንግሥት በዚሁ አካሄድ ሕግ እየጣሰ እና የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር እና ልእልና እያዋረደ የሚቀጥል ከሆነ ቤተ ክርስቲያን መንግሥት የጣሰውን ሕግ መሠረት በማድረግ መብቷን ለማስከበር እስከ አሁን ድረስ ፍጹም ሰላማዊ የሆነውን እንቅስቃሴዋን አድማሱን በማስፋት በየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለማድረግ ያቀደችውንና ያሳወቀችውን ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ ያለማንም ከልካይነት በራሷ አደባባይ የምታከናውን መሆኑን ስታሳውቅ ቆይታለች፡፡ በዚሁ መሠረት መንግሥት ቅዱስ ሲኖዶስ በመግለጫው የሰጠውን ቀነ ገደብ ከግምት ውስጥ በማስገባትና ጥሪውን በመቀበል በየካቲት ፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለአስቸኳይ ውይይት ዝግጁ መሆኑን በተመረጡ የሀገር ሽማግልዎች አማካኝነት መልእክቱ ሲደርሰን ካለው ወቅታዊ የሰላም እና ጸጥታ ሁኔታ አንጻር ጥሪውን በመቀበላችን በብፁዕ ወቅዱስፓትርያርክ የተመራ አሥራ ሁለት ብፁዓን ሉቃነ ጳጳሳት ፣ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የሀገር ሽማግልዎች በተገኙበት ሰፊ ውይይት ተካሂዷል፡፡ በውይይቱም የተነሱት ነጥቦች በዋንኛነት ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ፤ ቀኖናዊ እና አስተዳደራዊ ሕግን መሠረት ባደረገ መልኩ ጠብቃ የምትሠራ እና ከዚህ ውጭ ምንም አይነት ድርድር የልለው መሆኑን ገልጻለች፡፡ በዚህም መነሻ መንግሥት የቤተ ክርስቲያንን አቋም በመቀበል ወደፊትም የቤተ ክርስቲያንን አንድነት እና ሉዓላዊነትን በጠበቀ መንገድ እንደሚሠራ አረጋግጧል፡፡ በዚህ የፈተና ጊዜ ውስጥ የቅዱስ ሲኖዶስን መመሪያ በመቀበል ራስን የቤተ ክርስቲያን ሕልውና መስዋእት አድርጎ በማቅረብ፤ በክርስቶስ ደም የከበረችውን ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቅ እና የማስጠበቅ ከጸጉር መላጨት እስከ ገመድ መታጠቅ በእንባና በዋይታ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ሀዘናችሁን የገለጻችሁበት መንገድ የቤተ ክርስቲያን ሕልውና ማስጠበቅ መሠረት ሆኗል፡፡ በዚህም ሂደት ሕይወታቸውን በሰማእትነት፤ አካላችሁን ለአካል ጉዳት፤ ኑሯችሁን ለፈተና ፤ ለስደት፤ ለእንግልት እንዲሁም ለእስራት አሳልፋችሁ የሰጣችሁ ልጆቻችን ቅዱስ ሲኖዶስ ሁልጊዜም ውለታችሁን ሲያስታውስ የሚኖር ሲሆን የጉዳት ሰለባ ለሆኑቱም መንግሥት የድርጊቱን ፈጻሚዎች ለይቶ በሕግ አግባብ ተጠያቂ እንደሚያደርግ እና አሁን ላይ እስር፤ ወከባ፤ እንግልት እየተፈጸመባቸው ያለት ብፁዓን ሉቃነ ጳጳሳት፤ የሀገረ ስብከት ሠራተኞች፤ አገልጋይ ካህናት እና በተለያዩ አደረጃጀቶች የሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱን ልጆች ችግሩ በአስቸኳይ እንዲቆምና የታሠሩትም እንዲፈቱ፤ አገልግልታቸውን በሰላምና በነጻነት መስጠት እንዲችሉ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ በትናትናው እለት ከመንግሥት ጋር ባደረግነው ውይይት መንግሥት የቤተ ክርስቲያኒቱን አቋም ሙሉ በሙሉ የተቀበለ ቢሆንም ይህንን ለማስፈጸም የሚያስችል የአፈጻጸም የድርጊት ጊዜ የሚያስፈልግ በመሆኑ እሁድ የካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም እንዲካሔድ የተወሰነው ሀገር ዓቀፍ እና ዓለም አቀፍ የአደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ ለተወሰነ ጊዜ እንዲራዘም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ በዚሁ እለትም ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁለም በየአጥቢያችሁ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ዓውደ ምሕረት ላይ ባለመቅረት የተለመደውን የእለተ ሰንበት የሥርዓተ ቅዳሴ፤ የጸሎት፣ የምሕላ እና የትምህርተ ወንጌል ከወትሮው በተለየ የመንፈሳዊ ሥርዓት በማከናወን እንድታሳልፉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ የተከበራችሁ ውድ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤ ቅዱስ ሲኖዶስ በየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የጠራውን ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ ለተወሰኑ ቀናት እንዲተላለፍ ያደረገው የአቋም ለውጥ አድርጎ ሳይሆን አስቀድማ ቤተ ክርስቲያናችን በሮቿን ለሰላም ክፍት በማድረግ ባስተላለፈችው ጥሪ እና በአስቀመጠችው ቀነ ገደብ መሠረት በመንግሥት በኩል ወዲያውኑ ችግሩን ለመፍታት ፍላጎት በማሳየቱ ምክንያት ብቻ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ነገር ግን መንግሥት የገባውን ቃል እና የወሰነውን ውሳኔ የማይፈጽም ከሆነ መንፈሳዊ ተጋድሏችን የሚቀጥል ይሆናል፡፡ ይህ ሂደት በባህሪው ረዥም ተጋድል እና ጽናት የሚጠይቅ በመሆኑ እስከ አሁንም በፍጹም አንድነት እና መደማመጥ የቅዱስ ሲኖዶሱን ድምጽ እየሰማችሁ በአንድነት እና በሕብረት እንደቆማችሁት ሁሉ ወደፊትም የቅዱስ ሲኖዶስን ድምጽ በትጋት እንድትጠብቁ እያሳሰብን በሕግ የተያዙት ጉዳዮችም የሕግ ሂደታቸውን ተከትለው የሚቀጥሉ መሆኑን እና እኛም በልዩ ሁኔታ የምናውቃቸው መሆኑን እንገልጻለን፡፡ መንግሥትም የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብሎ የውይይት መድረክ በማዘጋጀት የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ በማክበር በውሳኔው መሠረት የሚፈጸም መሆኑን ስላረጋገጠልን ቤተ ክርስቲያን ታመሰግናለች፡፡ በተጨማሪም በዚህ የፈተና ወቅት በየደረጃው የምትገኙ በሀገር ውስጥ እና በመላው ዓለም የምትገኙ የቤተ ክርስቲያናችን የሥራ ኃላፊዎች፤ ሉቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ መነኮሳት፤ አገልጋይ ካህናት፤ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፤ ልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ማህበራት እና መላው ምእመናንና ምዕመናት እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያኗ ጎን የቆማችሁ እና አጋርነታችሁን የገለጻችሁ የሃይማኖት ተቋማት፤ የሕግ ባለሙያዎች፤ ግለሰቦች፤ የማህበረሰብ አንቂዎች፤ የጥበብ ሰዎች፤ የሰብዓዊ መብት ተቋማት እና በዚህ ሂደት ውስጥ ድጋፍ ስትሰጡ የነበራችሁ የተለያዩ አካላት ቤተ ክርስቲያን እያመሠገነች ወደፊትም ልዩ ዕውቅና የምትሰጥ መሆኑን እናሳውቃለን፡፡
Показати все...
መረጃ! በሕገ ወጡ ሹመት ላይ የተሳተፉ የቀድሞ ሊቃነ ጳጳሳትና ግለሰቦች ከዛሬ የካቲት 3 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት እንዳይገቡ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አግዷል። የሕግ ኮሚቴው ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው አቤቱታ መሠረት ክስ እስከሚመሠረት ድረስ ከጉዳዩ አንገብጋቢነት አንጻር ጉዳት ይደርሳል ብሎ ፍርድ ቤቱ በማመኑ ከላይ የተጠቀሰውን እግድ አስተላልፏል። ከላይ የተጠቀሱት ግለሰቦች እግዱን ቢተላለፉ በወንጀል እንደሚጠየቁ የሕግ ኮሚቴው ገልጿል። እግድ ተሰጠ ማለትም ክስ ቆመ ማለት እንዳልሆነ ያስታወሰው ኮሚቴው የምንጠይቃቸው የወንጀልና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ይቀጥላሉ ብሏል። የፌደራል ፖሊስ ፣ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ የኦሮሚያ ፖሊስና ሰላም ሚኒስቴር እግዱን እንዲያስፈጽሙ ኃላፊነት የተጣለባቸው ተቋማት ናቸው።
Показати все...
ጾሙ ከተጀመረም በኋላ ሕዝቡ ወደ አምላኩ እንዳይጮህ እና እንዳይጸልይ ለማወክ የሕዝብ አስተዳዳሪ ሆነው የተሾሙ የመንግሥት ሹማምንት ሊያገለግሉት ኃላፊነት የተቀበሉበትን የሀገሪቱን ሕግ ጥሰው ምእመናን ልጆቻችን ጥቁር ለብሰው ወደ መሥሪያ ቤት እንዳይገቡና በመንግሥት ቢሮዎችም አገልግሎት እንዳያገኙ በተለይም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት እና አንዳንድ በፌዴራል እና በከተማ መስተዳድር ቢሮዎች ጥቁር የለበሱ እና በሀዘን ላይ ያሉ ልጆቻችንን በማሠር ሲያንገላቱ በዓይናቸው ያዩ ምስክሮች አረጋግጠውልናል፡፡ በዚህም ሹማምንት ስልጣናቸውን ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት እየተጠቀሙበት መሆኑን እና ለቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ከፍተኛ ንቀት እና ጥላቻ ያላቸው መሆኑን ተረድተናል፡፡ ይህ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየደረሰ ያለው መከራና በደል በዚህ ዘመን በጉልህ የሚጠቀስ የቤተ ክርስቲያን የስደትና የመከራ ጊዜ ነው፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያን የስደትና የመከራ ጊዜ በቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ መዝገብ እና በመጽሐፈ ስንክሳር ተመዝግቦ ይቀመጣል፡፡ ለትውልድም ይተላለፋል፡፡ ይህ የፈተና ዘመን ያልፋል፤ ነገር ግን በዚህ ታሪክ ውስጥ ከእውነት ጎን የቆማችሁ ስማችሁ በታሪክ እና በወርቅ ቀለም ሲፃፍ በቤተክርስቲያን ላይ መከራ ያበዛችሁ ክፉ ታሪካችሁን ዛሬ በእጃችሁ ጽፋችሁ አልፋችኋል፡፡ በዚህ አጋጣሚ ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት እና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውጭ ሌሎች የክልል ርዕሳን መስተዳድሮችና ከተሞች በተለይም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፤ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት፤ የሲዳማ ክልላዊ መንግስት፣ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት፤ የሱማሌ ክልላዊ መንግሥት፤ የቤንሻንጉል ክልላዊ መንግሥት፣ የሐረሪ ክልላዊ መንግሥት፣ የአፋርና ጋምቤላ ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት፤ በጎፋ ዞን የሳውላ ከተማ እና ሌሎች ስማቸውን ያልጠቀስናቸው መንግሥታዊ ተቋማት የቤተ ክርስቲያናችንን ጥሪ በመከተል በአግባቡ ሕግና ሥርዓትን ለማስከበር የወሰዳችሁ ፍትሐዊ እና ሕጋዊ መፍትሔዎችን እናደንቃለን፣ በቤተ ክርስቲያንም ስም እናመሰግናለን፡፡ እንዲሁም ሀዘናችሁ ሀዘናችን ነው ብላችሁ ከጎናችን የተሰለፋችሁ አኃት አብያተ ክርስቲያናት፤ የሃይማኖት ተቋማት፣ ድርጅቶች እና ጉባኤያት፤ የእስልምና እምነት ተከታዮች፤ በእምነት የማትመስሉን ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ስላደረጋችሁልንና ስለምታደርጉልን እርዳታና ትብብር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን፡፡ ጸሎተ ምሕላውን ስናውጅ መንግሥት ሕግ አክብሮ እንዲያስከብር፣ የቤተክርስቲያኒቱን ክብር እና ልዕልና እንዲያከብር፣ በሃይማኖታችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን እንዲያቆምና ወደ ውስጡ ማየት እንዲችል ነበር:: ይህ ድርጊት እስከ አሁን ድረስ ግን መንግሥት ለዘመናት ሕጋዊ ተቋም እና የሀገር ባለውለታ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያንን ከመስማት እና ችግሯን ከመቅረፍ ይልቅ የማዋከቡን ሥራ አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡ በዚህም መንግሥት ችግሮችን ኃላፊነት ተሰምቶት እንዲፈታ ያደርገዋል የሚል እምነት ቢኖረንም አገዛዙ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ ልቡ መደንደኑን መመልከታችን በእጅጉ ልባችንን ሰብሮታል፡፡ በተለይም ቤተ ክርስቲያናችን ያወጀችው የ፫ ቀናት ጸሎትና ምህላ በአግባቡ እንኳን ሳይጠናቀቅ ከመንግሥት ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ወቅታዊ የፀጥታ ጉዳይን አስመልክቶ በየካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የተሰጠው የሰልፍ ክልከላ መግለጫ መንግሥት አሁንም ችግሩን ለመፍታት ሳይሆን ቤተክርስቲያኒቱን ለአንዴና ለመጨረሻ ለማውደምና ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማጥፋት የታወጀ አዋጅ መሆኑን በጽኑ እንድናምን አድርጎናል፡፡ በመግለጫውም፡- ፩ኛ. በእምነቱ አባቶች በተመሳሳይ መልኩ ሰልፍ ተጠርቷል በማለት መጥቀሱ የቤተክርስቲያን የመጨረሻው አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ አውግዞ የለያቸውን አካላት የእምነቱ ተከታይ ማድረግ ብቻ ሳይሆን መብት ያላቸው ሕጋዊ አካላትና የቤተ ክርስቲያን አባቶች አድርጎ መጥራቱ አሁንም ላይ ማብራርያ ለመስጠት መሞከሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር የሚነካ እና የሚያጠለሽ እንዲሁም ሕግና ሥርዓትን ከማስከበር ይልቅ ለሕገ ወጦች ጠበቃ ሆኖ የሚከራከረው መንግሥት መሆኑን ጭምር ለመረዳት ችለናል፡፡ በመሆኑም ቤተክርስቲያን በመንግሥት የደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል ተሰጠ የተባለው መግለጫ የቤተ ክርስቲያናችንን ሕጋዊ መብት የገፈፈ እና ሕገ ወጥ መግለጫ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያን አትቀበለውም፡፡ ፪ኛ. ጉዳዩን የውጪ እና የውስጥ ጠላቶች የፈጠሩት ነው በማለት የተለመደውን ፖለቲካዊ ቅርፅ ለማስያዝ መሞከርም ቤተክርስቲንያንም ሆነ ሕዝብን መናቅ በመሆኑ የምንቀበለው አይሆንም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በተለይ ላለፉት ፬ ዓመታት በሀሰተኛ ትርክት ልጆቿ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል መከራን ሲቀበሉ ችግሮችን በሆደ ሰፊነት ችላ ያለፈችው የሀገር መሠረት እንዳይናጋ፣ ቅጥሯ እንዳይደፈር በማሰብና በሀገር አንድነት ላይ ባላት የማይናወጽ ጽኑ አቋም ምክንያት መሆኑን መንገር ለቀባሪው ማርዳት ነው፡፡ ጉዳዩ ግልፅ የሆነ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ሆኖ እያለና መፍትሄውም በመንግሥት እጅ የሚገኝ ብቻ መሆኑ እየታወቀ የፖለቲካ ቅርፅ ለማስያዝ መሞከር ችግሩን ያባብሰው እንደሆን እንጂ አይፈታውም፡፡ በሰሞኑም ቤተ ክርስቲያናችን በመዋቅር የምትመራ እና ልጆቿም ድምጽዋን አውቀው በአግባቡ የሚሰሟት መሆኑ እየታወቀ ሆነ ተብሎ ቃላት አጠቃቀሙ እንኳን ኦርቶዶክሳዊ ያልሆነ የሀሰት እና ጸብ አጫሪ የሆኑ መልእክቶችን በአደባባይ የተለጠፉ መሆናቸውን ሲታይ ምን ያህል ጉዳዩን ላልተገባ ፖለቲካዊ ጥቅም እንደተፈለገ ለመረዳት ችለናል፡፡ ይህ ተለጠፈ የተባለውም ሕገ ወጥ ጽሑፍ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ያልሆነና ፈጽሞም ሊሆን የማይችል መሆኑን ጭምር ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ ፫ኛ. የትኛውም ሰልፍ በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል ማድረግ አይቻልም በማለት የተደረገው ክልከላን በተመለከተም ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ከዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ውስጥ መሠረታዊ መብት ሆኖ የተጠቀሰ እና በሕገ መንግሥቱም አንቀፅ ፴ ላይ በግልጽ የተደነገገ በመሆኑ መንግሥት ራሱ የሚመራበትን ሕገ መንግሥት ማክበርና ማስከበር ይኖርበታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ላይ ከላይ የተጠቀሰው ከፍተኛ መከራና በደል ምክንያት ከብዙ ሺህ ዓመታት በላይ ጸንታ የመጣችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በእኛ በልጆቿ ዘመን ስትፈርስ ዝም ብሎ መመልከት በጭራሽ የሚታሰብ አይሆንም፡፡ ይህን በደላችንን ለዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ለማሳወቅ እና መንግሥትም ከሚያደርገው ጣልቃ ገብነትና አፈና ወጥቶ ሕግ እንዲያከብር እና እንዲያስከብር የጠራነው የየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ሰላማዊ ሰልፍም መንግሥት ተገቢውን ጥበቃ በማድረግ እንድናከናውን መፍቀድ አሊያም የጠየቅናቸውን ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄዎቻችንን በአግባቡ እና አንድ በአንድ መመለስ አማራጭ የሌለው መፍትሔ መሆኑን ደግመን ደጋግመን ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥም የሚደርስብንን ሞት፣ መከራና ስደት እኛ አባቶች ከመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ጋር ደስ ብሎን የምንቀበለው እንጂ ቤተ ክርስቲያናችን እና ሀገራችን ስትፈርስ ቆመን የምንመለከት፣ ዝም የሚል አንደበትና የሚሸከም ኀሊና የማይኖረን መሆኑን በአጽንዖት እናሳስባለን፡፡
Показати все...
#የቅዱስ_ሲኖዶስ_ሙሉ_መግለጫ በስመ አብ፤ ወወልድ፤ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!! ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከጥር ፳፱ እስከ የካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለ ፫ ተከታታይ ቀናት በመላው ዓለም የታወጀው የነነዌ ፆም እና ምሕላ መጠናቀቅን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ:: ++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++ በትንቢተ ዮናስ በሰፊው እንደተጠቀሰው የነነዌ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ላይ ስለአመጹ እና ግብራቸውም በእግዚአብሔር ፊት አጸያፊ በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር ዮናስን “ተነስተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደ ፊቴ ወጥቷልና በእርስዋ ላይ ስበክ” በማለት አዘዘው፡፡ ትንቢተ ዮናስ ምዕ ፩ ቁጥር ፪ ዮናስም ድምፁን ከፍ አድርጎ ለነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል ሲሰብክ “የነነዌ ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡ ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፤ እርሱም ከዙፋኑ ተነስቶ መጎናጸፊያውን አወለቀ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ፡፡ አዋጅም አስነገረ፤ በነነዌ ውስጥ የንጉሡንና የመኳንንቱን ትእዛዝ አሳወጀ፤ እንዲህም አለ ሰዎችና እንስሶች፤ ላሞችና በጎች አንዳችን አይቅመሱ፣ አይሰማሩ፣ ውኃንም አይጠጡ፤ ሰዎችና እንስሶችም በማቅ ይከደኑ፣ ወደ እግዚአብሔርም በብርቱ ጩኸት ይጩኹ፤ ሰዎችም ሁሉ ከክፉ መንገዳቸውና በእጃቸው ካለው ግፍ ይመለሱ፡፡ እኛ እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ተመልሶ ይጸጸት እንደሆነ ማን ያውቃል፡፡ እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውንም አየ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም” ትንቢተ ዮናስ ፫፡ ፭-፲ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህን የነነዌ ሰዎች ፆም መነሻ በማድረግ የነነዌ ሰዎችን በምሕረቱ የጎበኘ አምላክ እኛንም በምሕረቱ ይቅር ይለን ዘንድ በየዓመቱ በአዋጅ በመፆም አምላካችንን ስንማጸንበት ኖረናል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባዔ በጥር ፳፮ ቀን ፳፻፲፭ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በወሰነው መሠረት የካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የተጠናቀቀው የነነዌ ፆምና ምሕላ ልዩ በሆነ በመንፈሳዊ የንስሐ ጸሎት በሰላም ተጠናቋል፡፡ በምሕላውም ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ጀምሮ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ ካህናት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ አገልጋዮች እና ምእመናን እንደነነዌ ሰዎች ጥቁር ለብሰን ጠዋትና ማታ በጸሎት ፤ በምሕላ፤ ቀን በቅዳሴ እንዲሁም በሰባቱ የጸሎት ጊዜያት ፈጣሪያችንን ስንለምን እና ስንማጸን የቆየንበት ምክንያት በቤተክርስቲያናችን ላይ የመጣው ፈተና እጅግ በጣም ከባድ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ የጾምና የንስሐ ወቅት ምእመናን ልጆቻችን የአባቶቻችሁን ጥሪ ሰምታችሁ፤ የሹመኞችን ማዋክብና እስር ሳትፈሩ ጥቁር ለብሳችሁ ጠዋትና ማታ በጾምና በምሕላ፣ ቀን በቅዳሴ በቤተክርስቲያን ቅጥር እየተገኛችሁ ለአምላካችን ያቀረባችሁትን ጸሎት እና ምሕላ እግዚአብሔር ሰምቶ ለችግራችን መፍትሄ፣ ለሀገራችን ሰላምን እንደሚሰጠን እምነታችን ጽኑ ነው፡፡ እናንተም ምእመናን የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ሰምታችሁ ለሃይማኖታችሁ፣ ለሀገራችሁ አንድነትና ሰላም ያላችሁን ጥልቅ ፍቅር ስለገለፃችሁም ያገኘነው መንፈሳዊ ብርታት ሳንገልፅላችሁ አናልፍም፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም እና በቅዱሳን አማላጅነት፣ በመላእክት ተራዳኢነት በፍፁም ፍቅርና አንድነት የያዝነውን ጸሎት እና ምሕላ አጠናቀናል፡፡ ችግራችንን ለአምላካችን በለቅሶ እና በጩኸት ነግረናል፡፡ ከዚህ በኋላ መከራው ቢጸና፣ የመከራው ጊዜ እንኳን ቢረዝም እግዚአብሔር በመከራ ውስጥ ሊያፀናን እና ሊያበረታታን አስቦ በመሆኑ በፍፁም አንናወጽም፡፡ ከእነኚህ መከራዎች በኃላም ታሪክን ጽፈን ሃይማኖታችንን ጠብቀን እና አስጠብቀን በመንፈሳዊ ጽናት እና ተጋድሎ እንሻገራለን፡፡ ጥቃቱ የቤተ ክርስቲያንን እውነት በካዱና በእውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን መካከል ነው፡፡ ይህም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖት፤ ቀኖና እና አስተዳደራዊ ሕግጋትን ጥሰው ሕገወጥ የጳጳሳት ሢመት በመደረጉ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ቤተ ክርስቲያንና በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት በጥር ፲፰ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ይህን ጥሰት የፈፀሙትን ግለሰቦች አውግዛ ከቤተ ክርስቲያን ኅብረት የለየቻቸው ቢሆንም ጉዳዩ ከግለሰቦቹ በላይ በመንግሥት ስልጣን ላይ ባሉና ጽንፈኛ በሆኑ ፖለቲከኞች እንዲሁም የሌላ እምነት ተከታዮች ጭምር የሚደገፍ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያንን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈላት ይገኛል፡፡ እየተፈጸመ ያለው ድርጊት በሰማያዊ መንፈሳዊ ዓለምና በምድራዊ ሥጋዊ ዓለም መካከል ስለሆነ በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥም የቤተ ክርስቲያን ክብርና ተቋማዊ ልዕልና ተደፍሯል፡፡ የቤተክርስቲያን ቅጥሮች መሣሪያ በያዙ አካላትና በመንግሥት የጸጥታ መዋቅር በኃይልና በጉልበት ተወሯል፡፡ ሊቃነ ጳጳሳት አባቶች ለብዙ ዓመታት ከኖሩበት አህጉረ ስብከት ያለአንዳች የሕግ መሠረት በጸጥታ መዋቅሮች ተባረዋል፡፡ በነጻነት የመንቀሳቀስ መብቶቻቸው ተገድቦም በግዞት ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ወደ አህጉረ ስብከታቸውም ተመልሰው መግባት እንዳይችሉ እቀባ ተደርጎባቸዋል፡፡ ካህናት አባቶች እና ምእመናንም ያለአንዳች የሕግ መሠረት በየእስር ቤቱ ያለበቂ ምክንያት በሕገወጥ መንገድ ታጉረዋል፡፡ በጸጥታ ኃይል ከመጠን በላይ ከመደብደባቸው የተነሳ የሞት፣ የከባድ እና ቀላል አካል ጉዳት እንዲደርስባቸው ምክንያት ሆኗል፡፡ በአጠቃላይም በመንግሥት ኃይሎች ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተፈፅሞባቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህ ሁሉ በደል ቢፈጸምባትም ናዛዜ ሕዙናን የሆነው አምላካችን ለቤተ ክርስቲያናችን እና ለሀገራችን መፍትሔ እንዲያመጣልን፣ መንግሥትም ወደ ልቡ ተመልሶ ቤተክርስቲያንን እንዲያከብርና እንዲጠብቅ በሚል ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ ይህን ጾም የነነዌ ሰዎች እንዳደረጉት ጥቁር ለብሰን በፍፁም ኃዘን ወደ አምላካችን እንድንጮህ ቅዱስ ሲኖዶስ ትእዛዝ ባስተላለፈበት ማግስት በሻሸመኔ ደብረ ስብሐት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ሕገወጡን ቡድን በኃይል ለማስገባት በመንግሥት የጸጥታ መዋቅሮች በተወሰደ አሰቃቂ እርምጃ እስከ አሁን በደረሰን መረጃ ቁጥራቸው ከ፴ በላይ የሚሆኑ ካህናትን እና አገልጋዮችን ጨምሮ የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች ቅጥሯ አይደፈርም፣ ቤተክርስቲያን በተወገዙ ግለሰቦች አትረክስም በሚል ለሃይማኖታቸው ሰማእትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆኑ ልጆቿም በደረሰባቸው ከባድ እና ቀላል የአካል ጉዳት ምክንያት በሕክምና ላይ ይገኛሉ፡፡ ከዚህ ሁሉ በደል በኋላም እስከ አሁን ድረስ የሞቱትን በአግባቡ መቅበርና የተጎዱትን በበቂ ሁኔታ ማሳከም ሳንችል ቀርተናል፡፡ እነዚህ ሰማዕታት በዚህ ኃጢያት በበዛበት ዘመን ለቤተክርስቲያን እስከሞት ድረስ በመታመን ለቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን የጽናት ተምሳሌት በመሆናቸው ቤተክርስቲያን ስትዘክራቸው ትኖራለች፡፡ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን በልጆቿ ላይ እየደረሰ ባለው ሞት፤ እርዛት፤ እስራት እና መልከ ብዙ በሆነው መከራ ብታዝንም ለክርስትና እውነተኛነት ምስክሮች የሆኑ አዳዲስ ቅዱሳን ሰማእታትን በማግኘቷም እጅግ ደስ ትሰኛለች፡፡
Показати все...
መንግስት ከአጉል እልከኝነቱ ወጥቶ ከሕገ ወጦቹ ግለሰቦች ጋር በመተባበር በአደባባይ እየፈጸመ ያለውን የሕግ ጥሰት ዛሬን ጨምሮ በቀጣዮቹ ፪/ሁለት/ ቀናት ውስጥ እንዲያቆም እና ሕግ እና ሥርዓትን እንዲያስከብር፣ በኃይል የወረራቸውን መንበረ ጵጵስና እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለቆ ለቤተክርስቲያኒቱ ሕጋዊ መዋቅር እንዲያስረክብ፣ ያለአግባብ ያሠራቸውን ካህናት እና ምእመናን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቅ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ለፈፀመው በደል በአደባባይ ይቅርታ እንዲጠይቅ፤ በካህናት እና ምእመናን ላይ ለደረሰው ሞት እና የአካል ጉዳት ተገቢውን ካሳ እንዲክስ እና የወደሙ ንብረቶቿን እንዲጠግን በጥብቅ እንጠይቃለን ፡፡ መንግሥት በዚሁ አካሄድ ሕግ እየጣሰ እና የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር እና ልእልና እያዋረደ የሚቀጥል ከሆነ ቤተ ክርስቲያን መንግሥት የጣሰውን ሕግ መሠረት በማድረግ መብቷን ለማስከበር እስከአሁን ድረስ ፍጹም ሰላማዊ የሆነውን እንቅስቃሴዋን አድማሱን በማስፋት በየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለማድረግ ያቀደችውንና ያሳወቀችውን ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ ያለማንም ከልካይነት በራሷ አደባባይ የምታከናውን መሆኑን እያሳወቅን መንግሥትም ድርሻው ሰልፉ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት ብቻ መሆኑን እያሳሰብን ዛሬም ቢሆን መንግሥት ቆም ብሎ በማሰብ ከእኛ ከአባቶች ጋር ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና መንፈሳዊ የአስተዳደር ሥርዓታችንን ባልጣሰ መልኩ ለመነጋገር እና ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ጥረት ካደረገ በውይይት ለመፍታት መንፈሳዊ በራችን ክፍት መሆኑንም እናሳውቃለን፡፡ ከዚህ ውጭ ግን በሁለቱ አባቶች መካከል የተፈጠረ ችግር እየተባለ የሚነገረው ፖለቲካዊ ጨዋታ የመንግሥት እንጂ በሀገሪቱ ሕጋዊ ሰውነት የሌላቸውና ከቤተ ክርስቲያን የተለዩ ግለሰቦች ጋር ማነጻጸር ሕገ መንግሥታዊም ሆነ ሞራላዊ የሕግ መሠረት የለውም፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችን የጠራችውን ሰላማዊ እና ሕጋዊ የሆነ የመብት ጥያቄ የማፈን ሂደትን በጥብቅ እንቃወማለን፡፡ የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን እስከአሁን ባደረጋችሁት ጽናትና ተጋድሎ ሃይማኖታችሁንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንችሁን እንዳላሳፈራችሁ ሁሉ አሁንም ከስሜታዊነት በወጣ ሁኔታ በከፍተኛ ጽናት እና ጥንካሬ የአባቶቻችሁን ድምጽ ብቻ እንድትሰሙ፣ ቤተ ክርስቲያንን በየአጥቢያችሁ ተደራጅታችሁ እንድትጠብቁ፤ ለአባቶቻችሁ መንፈሳዊ ጥሪ ፈጣን ምላሽ እንድትሰጡ፣ እየመጣው ላለ መከራና ስደት ለመንፈሳዊ ተጋድሎ እንድትዘጋጁና በፍፁም መንፈሳዊ ጨዋነት በአንድነት የመጣብንን ፈተና እንድትወጡ አደራ እያልን አባታዊ መልእክታችንን እያስተላለፍን ሰላማዊ ሰልፉን በተመለከተም በአጭር ጊዜ ውስጥ ዝርዝር መግለጫ የምንሰጥ መሆኑን እያሳውቅን በዚህ ጥቃት መስዋእትነት የከፈሉ እና ያረፉ ልጆቻችንን ነፍሳቸውን በአጸደ ገነት በክብር ያሳርፍልን እያልን ጸሎተ ፍትሐትም በየደረጃው የሚከናወን መሆኑን እያሳወቅን በተለያዬ ጊዜ ዛሬን ጨምሮ በወለቴ እና በሰበታ ከተሞች የደረሰውን የአካል ጉዳት እና ሞት እግዚአብሔር ምህረት እና መጽናናቱን ያድልልን፡፡ እግዚአብሔርም ገድላችሁን፣ ጽናታችሁንና ጸሎታችሁን ይቀበል፤ የቅዱሳን አምላክ ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር “እግዚአብሔር ሀገራችንን ይባርክ” የካቲት ፪ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም. አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
Показати все...
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን “….. በእኔ ምክንያት…..” (ትንቢተ ዮናስ ፩፥፲፪) የሰው ልጆች በኃጢአታቸው ምከንያት በእራሳቸው ላይ በሚያመጡት መከራ ይጠፉ ዘንድ የማይፈቅድ የምሕረት አምላክ ልዑል #እግዚአብሔር የነነዌ ሰዎችን ከክፋታቸው ይመልስ እና ያስተምር ዘንድ ነቢዩ ዮናስን ሄዶ እንዲሰብክ አዘዘው፡፡ ነቢዩ ዮናስ ግን የታዘዘበትን ቦታ ትቶ #ከእግዚአብሔር ፊት ኮብልሎ ወደ ተርሴስ ለመሄድ በኢዮጴ መርከብን ተሳፈረ፡፡ የጉዞውንም ዋጋ ከከፈለ በኋላ ወደ መርከቢቱ የታችኛው ክፍል ወርዶ ከባድ እንቅልፍን ተኛ፡፡ መርከቢቱ ጉዞ ስትጀመርም #እግዚአብሔር አምላክ በባሕሩ ላይ ታላቅ ነፋስን ላከ፤ ከባድ ማዕበልም ተነስቶ መርከቢቱን ያንገላታት ያዘ፡፡ ከማዕበሉም ጽናት የተነሳ መርከቢቱ ልትሰበር በተቃረበች ጊዜ ክብደቷ እንዲቀንስ በውስጧ የነበረውን ጭነት እያወጡ ወደ ባሕር ጣሉት ነገር ግን መርከቢቱ ከመናወጥ አላረፈችም ነበር፡፡ የመርከቡ አለቃ የሆነው መናወጥ አስጨንቆት ላይ ታች ሲጣደፍ በታችኛው ክፍል በዛ በጭንቅ ሰዓት በከባድ እንቅልፍ ተኝቶ ዮናስን አገኘው፡፡ ወደ እርሱም ቀርቦ  ቀስቆሶ “ምነው ተኝተሃል እንዳንጠፋ #እግዚአብሔር ያስበን አንደ ሆነ ተነስተህ አምላክህን ጥራ” አለው፡፡ የማዕበሉ ጽናት ያስጨነቃቸው በመርከቡ ያሉ ሰዎች ማዕበሉ ከፈጣሪ የታዘዘ መሆኑን ሲገነዘቡ " ይህ ሁሉ መከራ በማን ምክንያት አንዳገኘን እናውቅ ዘንድ ዕጣ እናጣጣል" ተባብለው ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜ በዮናስ ላይ ወደቀ፡፡ መርከበኞቹም “ይህ ሁሉ መከራ በምን ምክንያት አንዳገኘን እባክህ ንገረን? ሥራህ ምንድነው? ከወዴትስ መጣህ?  አገርህስ ወዴት ነው? ከማን ወገን ነህ?” ሲሉ ዮናስን አከታትለው ጠየቁት፡፡ ዮናስም “እኔ ዕብራዊ ነኝ፡፡ ሥራዬም ባሕሩንና የብሱን የፈጠረውን የሰማዩን አምላክ #እግዚአብሔርን ማምለክ መሆኑን ገልጾ #ከእግዚአብሔርም ፊት እንደኮበለለ " ያደረገውን ሁሉ ነገራቸው። በዚህም ጊዜ እጅግ ፈርተው “ይህ ያደረግኽው ምንድነው? ባሕሩ ጸጥ አንዲል ምን እናድርግብህ” አሉት፡፡ እርሱም “ይህ ታላቅ ማዕበል በእኔ ምክንያት እንዳገኛችሁ ዐውቃለሁና አንሥታችሁ ወደ ባሕሩ ጣሉኝ ባሕሩም ጸጥ ይልላችኋል” አላቸው ፡፡ ሰዎቹ ግን ዮናስን ሊጥሉት አልወደዱም ይልቁንም ወደ የብሱ ሊመለሱ አጥብቀው ቀዘፉ ነገር ግን ባሕሩ እጅግ አብዝቶ ይናወጥባቸው ነበርና አልቻሉም፡፡ ስለዚህም  “አቤቱ አንተ እንደ ወደድህ አድርገሃልና አንለምንሃለን አቤቱ ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳናጠፋ ንጹሕም ደም በእኛ ላይ እንዳታደርግ እንለምሃለን” ብለው #እግዚአብሔርን ተማጽው ወስደው ወደ ባሕር ጣሉት ባሕሩም ከመናወጡ ጸጥ አለ፡፡ ዮናስም #እግዚአብሔር ባዘጋጀለት አሳ አንበሪ ሆድ ውስጥ ለሦስት ቀን እና ለሦስት ሌሊት ቆይቶ በነነዌ ያስተምር ዘንድ በዛ ተፋው፡፡   + ባሕሩንና የብሱን የፈጠረውን የሰማዩን አምላክ #እግዚአብሔርን ማምለክ የዘወትር ሥራችን የሆነን ክርስቲያኖች #ከእግዚአብሔር ፊት በመኮብለላችን እና ባለመታዘዛችን ምክንያት #መርከብ_ቅድስት_ቤተ ክርስቲያን #መርከብ_ሀገር ማዕበል ሲናወጹ በመርከቧ መናወጽ እንዳንገላታ ተቀስቅሰን /ታዝዘን ወደ #እግዚአብሔር እንድንለምን /ንሰሓ እንድንገባ/ እንድንመለስ ይህ የሆነው “በእነ እገሌ ምክንያት ነው ፤ ይህም የተፈጸመው በእነ እገሌ ኃጢአት ነው፣ ይህ የሆነው በዚህ ምክንያት ነው” ከማለት ተቆጥበን "ይህ የሆነው በእኔ ምክንያት ነው" በሚል ፍጹም ጸጸት በንሰሓ መመለስ ይገባል። + ከነቢዩ ዮናስ እንደምንማረው የመርከቧ መናወጽ “እኔ #ለእግዚአብሔር ባለመታዘዜ፣ እኔ ባልንጀራዬን ባለማክበሬ /ባለመውደዴ፣ እኔ ልክ በሌለው ግፍ ወንድሜን በመግፋቴ የመጣ ነው…. ይህ መናወጽ ይቆም ዘንድ እኔ ንሰሓ እገባለሁ፣ ወደ #እግዚአብሔር መንገድ እመለሳለሁ” በሚል የጸጸት ልቡና የተነሳብንን ማዕበል እና ሞገድ ጸጥ ማድረግ የ #እግዚአብሔርንም የምሕረት ዓይን መማጸን ይገባናል፡፡ ስብሐት ለ #እግዚአብሔር 🙏 @MAHIBESTRBARBARAMARINA @StBarbaraStmarinaYouths
Показати все...
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጥር 27 ቀን 2015 ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
Показати все...
Оберіть інший тариф

На вашому тарифі доступна аналітика тільки для 5 каналів. Щоб отримати більше — оберіть інший тариф.