Unity Digital Agency
Открыть в Telegram
የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያዎችን መግዛትም ሆነ መሸጭ ስትፈልጉ Unity Digital Agency ምርጫዎ ያድርጉ።
Больше191
Подписчики
Нет данных24 часа
-17 дней
-730 день
Архив постов
“አርሰናል በመጨረሻ ሻምፒዮን ሆኗል! ❤️🤍 ይህ ድል የትዕግስት፣ የእምነት እና የአንድነት ውጤት ነው። ለሁሉም የአርሰናል ደጋፊዎች እንኳን ደስ አላችሁ! 🏆”
የሀዋሳ ሀይቅ ትዝታዬ
በሀይቁ የተቀጣው የልጅነት ፍቅር
የሰው ልጅ በቅዠትና በእውነት መካከል የሚመላለስባት፣ የደስታ ጥጉን የምታሳይ፣ ኋላ ላይ ዞሮ ሲያያት ደግሞ በናፍቆት የምታስለቅስ አንዲት ውብ ዓለም አለችው። እሷም… የልጅነት ዘመን ናት! የልጅነት አእምሮ ድንበር የለውም፤ ፍርሃት አያውቅም፤ የነገ ጭንቀት አይገዛውም። ዛሬን መኖር፣ ዛሬን መሳቅና ዛሬን መጫወት ብቻ ነው ህጉ።
እስኪ ዛሬ ወደ ኋላ ልመልሳችሁ። እኔና የሰፈሬ ጓደኞቼ ሁል ጊዜ ቅዳሜ ቅዳሜ ከምሳ በፊት "የመገረፍ" ቋሚ ቀጠሮ ነበረን። አዎ… አልተሳሳታችሁም፣ ግርፋት! ለቤተሰቦቻችን የሁልጊዜ ተግባር፣ ለእኛ ደግሞ የለመድነው የቅዳሜ ስርአታችን ነበር። እንዴት ሆኖ? ትሉኝ ይሆናል… ታሪኩ እንዲህ ነው።
ከሰኞ እስከ አርብ ህይወታችን በትምህርት ቤት አጥር ውስጥ የተገደበ ነበር። የደወል ድምፅ፣ የደብተር ገጾችና የደከሙ የእርሳስ ጫፎች። ነገር ግን ከትምህርት ቤት መልስ፣ የሰፈራችን ሜዳ የእኛ የነፃነት አደባባይ ትሆን ነበር። ዩኒፎርማችንን ወርውረን፣ መክሰስ የሚባለውን ነገር በአፋችን ጠቅጥቀን ወደ ሜዳው እንገሰግሳለን።
እዚያ ሜዳ ላይ… አለም ማለቂያ የሌላት ትመስለናለች። የኳስ ጨዋታችን ትዝታና ሳቁ እጅግ ብዙ ነው። ነገር ግን በወቅቱ ያበሳጨኝ፣ ዛሬ ላይ ግን ሳስበው በሳቅ የሚያፈርሰኝ አንድ ህግ ነበረን። የጨዋታችን ፍፃሜ የሚወሰነው በዳኛ ወይም በሰዓት ሳይሆን፣ በኳሷ ባለቤት ልጅ ስሜት ነበር! እርሱ "ደከመኝ፣ ልግባ" ካለ ወይም ተኳርፎ ኳሱን ካቀፈ ጨዋታው በዚያው ያበቃል። "የኳስ ባለቤት ካልተጫወተ ሜዳው ይበተናል" እንዲሉ!
ነገር ግን... ቅዳሜ ሲመጣ ታሪኩ ይለወጣል። ቅዳሜ የእኛ የነፃነት ቀን ናት። ትምህርት የለም፤ ጥዋት ከቁርስ በኋላ የምንገናኝበት ሰዓት ነው።
ገና ከጠዋቱ መሬቱ ሳይሞቅ እንገናኛለን። ከዚያማ… ሰውነታችን አፈር እስኪመስል፣ ልብሳችን በላብና በጭቃ እስኪጠረቅ፣ ጠረናችን እስኪቀየር ድረስ እንሮጣለን። ኳሷን ሳይሆን አቧራውን የምናሳድደው ነው የሚመስለው። አፈር እየበላን፣ አፈር እየለበስን… ጨዋታው ልክ አራት ሰዓት ሲል ያበቃል።
ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ… ቅዳሜ በመጣ ቁጥር ከምሳ በፊት ለግርፋት የሚጋብዘንን ያንን ታላቅ ወንጀል የምንፈፅመው!
ሁላችንም በኩራት ያንን የአቧራ ካፖርት እንደለበስን ወደ ሀይቁ እንገሰግሳለን። ሀይቁ ጋ ስንደርስ ልብሳችንን አውልቀን፣ ፍርሃትን አውርደን፣ በዚያ በቀዝቃዛው ውሃ ውስጥ እንተረማመሳለን። እንዋኛለን፣ እንታጠባለን፤ እስኪበቃንና አካላችን እስኪዝል ድረስ ውሃውን እንቀዝፋለን።
ቤተሰቦቻችን ሀይቅ እንድንሄድ በፍጹም አይፈቅዱም ነበር። "ውሃ ይወስዳችኋል! ክፉ ነገር ያጋጥማችኋል!" የሚል የሁልጊዜ ስጋትና ማስጠንቀቂያ ነበራቸው። የወላጅ አንጀት አያርፍም አይደል?
ነገር ግን ከሀይቁ ስንወጣ፣ ወንጀላችንን መደበቅ የማይችል አንድ ተፈጥሯዊ የምስክር ወረቀት በሰውነታችን ላይ ይታተማል። ከሀይቁ ወጥተን ፀሀዩ ሲመታን… ሰውነታችን ድርቅ ይላል። ነጭ ይሆንና ቡላ እንመስላለን። "አመድ የወረሰው" የሚባለው አይነት! ምንም ብናደርግ፣ ቅባት ካልተቀባን በስተቀር ያንን ንጣትንና የሀይቁን ምስክርነት ልንደብቀው አንችልም።
ሰዓቱ ወደ ስድስት ሰዓት ሲቃረብ፣ ልባችን እየራደች ወደየቤታችን እናመራለን። ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ… እውነተኛው የቅዳሜ ፍርድ ቤት የሚከፈተው። ቤት ስንገባ ዱላው ዝግጁ ሆኖ ይጠብቀናል።
ስቃዩን ልነግራችሁ አልችልም! የኳሱ ድካም፣ የሆድ ረሃብ፣ የፀሀዩ ንቅሳት… በዚያ ላይ ደግሞ የቅዳሜው የግርፋት ውርጅብኝ! "ለማይሰማ ጆሮ፣ ባዶ ዱላ" ይባል የለ? እየጮህን፣ እየለመንን… የቅዳሜ ግብራችንን እንቀበላለን።
ነገር ግን ያ ግርፋት በቁጣ ብቻ የተሞላ አልነበረም፤ ከጀርባው ፍቅርና ስጋት ነበረበት። ከተገረፍን በኋላ ሰውነታችንን እንታጠባለን፤ እናቶቻችን ቆዳችን እንዳይሰነጠቅ ቅባት ይቀቡናል፤ ከዚያም ያንን ናፍቆት የሆነውን የቅዳሜ ምሳችንን በጉልበት እንበላለን። ሆዳችን ሲሞላ፣ አይናችን በረሃብና በድካም ይከብዳል፤ ወዲያውኑ እንቅልፍ ውስጥ እንሰምጣለን። የሚያገርመው ነገር… በሁሉም ጓደኞቼ ቤት የሚደገመው ድራማ ይሄው ተመሣሣይ መሆኑ ነው።
እንግዲህ አመሻሽ አከባቢ ሲሆን… ሌላኛው ውብ ትዕይንት ይጀምራል። ሁላችንም ከተገረፍንበት፣ ከታጠብንበትና ከበላንበት ቤት ወጥተን ሰፈር ውስጥ እንገናኛለን። ሰብሰብ ብለን ቁጭ እንላለን። ሰውነታችን በቅባት አብሪቶ፣ የግርፋቱ ህመም ገና ሳይጠፋ… ቤት ውስጥ ስለደረሰብን ዱላ ማውራት እንጀምራለን።
"እኔማ በጭራሽ ነው የተገረፍኩት…" "እኔስ እናቴ በእንጨት ነው የመታችኝ…" እያልን እርስ በርስ እንሳሳቃለን፣ እንበሻሸቃለን። የደረሰብንን መከራ ወደ ታላቅ ደስታና ሳቅ እንቀይረዋለን።
በቃ… መሽቶ ጨለማው ሰፈሩን ሲያቅፈው ቅዳሜ በዚህ መልኩ ያልቃል። ነገ… ሌላ ቀን ነው፤ እሁድ ይመጣል……
የልጅነት ዱላ ዛሬ ላይ ጠባሳ የለውም፤ ትዝታው ግን በልባችን ውስጥ የማይጠፋ የደስታ ቀለም ጥሎ አልፏል። ያንን ንጹህ ዘመን፣ ያንን የሳቅና የዱላ ማስታወሻ ሁሌም ሳስበው በናፍቆት እሞላለሁ።
Уже доступно! Исследование Telegram 2025 — ключевые инсайты года 
