🔎ሳምንታዊ የቢዝነስ ዜናዎች🔍
📝ከአፍሪካ አገሮች ጋር የንግድ ልውውጥ ለማካሄድ የታሪፍ ማሻሻያ እየተዘጋጀ መሆኑ ተነገረ
ስምምነቱ ተግባራዊ ሲደረግ ኢትዮጵያ ልታጣ የምትችለው ገቢ እየተጠና ነው ተብሏል
ኢትዮጵያ በፈረመችው የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነት መሠረት፣ ምርቶች ወደ አገር ውስጥ ሲገቡ፣ ከታሪፍ ነፃ የሚደረጉበት የሕግ ማዕቀፍ ማሻሻያ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ለማፀደቅ እየተሠራ መሆኑ ተገለጸ፡፡ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነትን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ብሔራዊ የመተግበሪያ ስትራቴጂን በተመለከተ፣ ሰኔ 22 ቀን 2016 ዓ.ም. ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ተደርጎ ነበር፡፡
ለአፍሪካ አገሮች የገበያ ትስስር ለመፍጠር ከስድስት ዓመታት በፊት እ.ኤ.አ. 2018 በሩዋንዳ ኪጋሊ የተደረገውን የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነት እ.ኤ.አ. በ2019 የፈረመችው ኢትዮጵያ፣ ከ5,800 በላይ የአፍሪካ አገሮች ምርቶችን ከታሪፍ ነፃ ገብተው እንዲሸጡ መስማማቷ ይታወሳል፡፡
ይህንን የስምምነት ክፍል ተግባራዊ ለማድረግ የገንዘብ ሚኒስቴር የታሪፍ ማሻሻያውን በሕግ ደረጃ በማዘጋጀት፣ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ለማፀደቅ እየሠራበት መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነትን ተግባራዊ የማድረግና የመደራደር ኃላፊነት የተሰጠው የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ የታሪፍ ማሻሻያው የሕግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ በጋዜጣ እንዲታተምና በአፋጣኝ ተግባራዊ እንዲረዳ ፍላጎት መኖሩን በሚኒስቴሩ የዓለም አቀፍና ቀጣናዊ የንግድ ትስስር መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታገስ ሙሉጌታ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ሆኖም የታሪፍ ማሻሻያውን የማዘጋጀት ሥልጣን የተሰጠው የገንዘብ ሚኒስቴር በሕግ ማዕቀፍ ደረጃ እያዘጋጀው መሆኑን፣ ይህም ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ እንዲፀድቅ እየተሠራበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
አገሪቱ ከዚህ ቀደም ከሱዳንና ከደቡብ ሱዳን ጋር የነፃ ንግድ ቀጣና መሰል ስምምነቶችን ፈርማ እንደነበር፣ እ.ኤ.አ. ከ2016 ጀምሮ ግን በነፃ ንግድ ቀጣና ድርድር ውስጥ መቆየቷን የገለጹት አቶ ታገስ፣ በአሁኑ ወቅት አብዛኞቹ የስምምነቱ ሒደቶች አገሪቱ ካሏት የንግድ አሠራር ሥርዓቶች ጋር የተጣጣሙ እንዲሆኑ ለማድረግ ጥረቶች እየተካሄዱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በአሥር ዓመታት ውስጥ በአፍሪካ አገሮች የተመረቱ 97 በመቶ ምርቶች ከታሪፍ ነፃ ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ስምምነት ላይ የተደረሰ ቢሆንም፣ ይህን ግን በየዓመቱ በሚደረግ የማሻሻያ ሒደት ተግባራዊ እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡
በነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቱ ሦስት በመቶ በሚሆኑ ምርቶች ላይ የታሪፍ ማሻሻያው ተግባራዊ እንደማይደረግ፣ ወይም ከታሪፍ ነፃ እንደማይደረጉ ስምምነት ላይ መደረሱ አይዘነጋም፡፡ እነዚህ ምርቶች 193 ያህል ሲሆኑ ሲመረጡም በዋናነት የመንግሥትን የገቢ ግብር ከማስጠበቅ፣ በአገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች ተወዳዳሪ የሆኑ ምርቶች ከመሆናቸው፣ እንዲሁም ለጤና ያላቸውን ጉዳት ታሳቢ በማድረግ መሆኑን መሪ ሥራ አስፈጻሚው አብራርተዋል፡፡
ከአፍሪካ አገሮች ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶች መጠን አምስት በመቶ ሲሆን፣ ለአፍሪካ አገሮች የሚላከውም አገሪቱ በአጠቃላይ ለውጭ ገበያ ከምታቀርባቸው 20 በመቶ ያህሉ ብቻ መሆናቸው ይገለጻል፡፡ ሆኖም ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነቱ ተግባራዊ ሲደረግ በተወሰነ ደረጃ የግብር ገቢ ልታጣ እንደምትችል ይነገራል፡፡ ምን ያህል ታጣለች በሚል ሪፖርተር ጥያቄ ያቀረበላቸው አቶ ታገስ፣ መጠነኛ ገቢ ልታጣ እንደምትችል ቢገመትም በሚኒስቴሩ በኩል ጥናት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
ምንጭ፡ Ethiopian Reporter ሪፖርተር
📝የኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን በ 2016 በጀት ዓመት ባለፉት 11 ወራት ከኢንዱስትሪ ኬሚካል ግብዓት ምርቶች 5 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱን አስታወቀ
ይህም ካለፈው አመት በተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ 28.9% ብልጫ እንዳለው ተገልጿል። የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሁንዴሳ ደሳለኝ ኮርፖሬሽኑ በፋብሪካዎቹ የሚያመርታቸው የኬሚካል ምርቶች ለሀገር ውስጥ እና ለውጭ ገበያ ያቀርባል። በተለይ በማዳበሪያ ግብዓት፣ በጎማ ዛፍ ውጤቶች እና በሲሚንቶና መሰል የኬሚካል ምርቶች ምርታማነቱን እና ትርፋማነቱን በማሳደግ በኢኮኖሚ ውስጥ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ እንደሆነ ጠቁሟል። ኮርፖሬሽኑ በጎማ ዛፍ ልማት ረገድ በከፊልም ሆነ በሙሉ ያቀነባበራቸው ምርቶችን ለደንበኞቹ እያቀረበ ሲሆን በዘርፉ አቅሙን ለማሳደግ የማያስፋፊያ ፕሮጀክት እየተገበረ እንደሚገኝም አንስቷል።
ምንጭ፡ EBC
📝በኢትዮጲያ በኤሌክትሪክ መኪኖች ዘርፍ እየተሰራ ያለው ስራ የሚበረታታ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክ ሚኒስቴር ገለፀ
ተቋሙ ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ጋር በመሆን ያዛጋጀውን የታዳሽ ሀይል ተሽከርካሪዎች ትግበራ ስትራቴጂ ሰነድም ለውይይት አቅርበዋል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክ ሚኒስቴሩ ዶ/ር አለሙ ስሜ በሰነዱ በዘርፉ የዓለም ተሞክሮች የኢትዮጵያ ውጥንና እናጋጠሙ ያሉ ተግዳሮቶች እንዲሁም በኤሌክትሪክ መኪኖች ትግበራ የባለድርሻ አካላት ሚና እና ቅንጅታዊ አሰራር ጥናቶች ቀርበው ግብዓት ተወስዶባቸዋል ብሏል ። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ዴኤታ ሀሰን መሀመድ በበኩላቸው መንግስት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ መገጣጠሚያዎች በሀገር ውስጥ አምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሸፈኑ እና በስፋት ጥቅም ላይ እንዲውሉ ለማድረግ ከፖሊሲ ቀረፃ ጀመሮ የመሰረተ ልማት አቅርቦት እና ሌሎች ድጋፎችን እያቀረበ መሆኑን ተናግረዋል። አምራች ኢንዱስትሪዎች ቴክኖሎጂውን በመጠቀም ረገድ ግንባር ቀደም ከሆኑ እና ልምድ ካላቸው ሀገራት ተሞክሮ የሚወስዱበት ሁኔታ እንደሚመቻች በመድረኩ ተጠቅሷል።
ምንጭ፡ EBC
📝የሸማቾች የህብረት ስራ ማህበራት የግብርና ውጤቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ሸማቾች ገለጹ
የከተማ አስተዳደሩ የህብረት ስራ ኮሚሽን በክረምት የምርት እጥረት እንዳይኖር ከክልሎች ብዛት ያለው ምርት እያስገባሁ ነው ብሏል።
ምንጭ፡ EBC
📝የኢትዮጵያና የብራዚልን የንግድ ሚዛን ለማሻሻል እንደሚሰራ ተገለፀ
ኢትዮጵያ ወደ ብራዚል የምትልካቸውን ምርቶች መጠን በማሳደግ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድ ሚዛን ለማሻሻል በቅንጅት እንደሚሰራ የንግድና ቀጣናዊ ትስስትር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ።
ሚኒስትሩ ከብራዚል ልኡካን ጋር የሁለቱን ሀገራት ግንኙነትና የንግድ ልውውጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል።
በውይይቱ ኢትዮጵያ እና ብራዚል የብሪክስ አባል እንደመሆናቸው የንግድ ግንኙነታቸውንና ወዳጅነታቸውን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
ወደ ብራዚል የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ እንዲሁም ኢትዮጵያ በንግድና ኢንቨስትመንት ባላት እምቅ ሀብት ብራዚላዊያን መጥተው መዋዕለ ነዋያቸውን በማፍሰስ የሁለትዮሽ የንግድ ግንኙነትን ይበልጥ ማጎልበት እንደሚያስፈልግም አስረድተዋል።
በውይይቱ በቁም እንሰሳት ንግድ ዘርፍ ከብራዚል ልምድ ለመውሰድ፣ በግብርናው እና ማኑፋክቸሪንግ ዘርፎች በጋራ ለመስራት እና ግንኙነታቸውን ለማጎልበት በቀጣይነት ለመመምከርና ስምምነቶችን ለመፈራረም መግባባት ላይ መደረሱን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል።
በተመሳሳይ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ እያሱ ኤልያስ (ፕ/ር) ከብራዚል የግብርናው ዘርፍ አመራሮች ጋር በዘርፉ በሁሉም መስኮች በተለይም በተፈጥሮ ሀብት ልማት በሚከናወኑ ተግባራት ላይ በትብብር ለመስራት በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል።
ምንጭ፡ EBC