ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Открыть в Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Больше637
Подписчики
Нет данных24 часа
-37 дней
-1130 день
Архив постов
❤ እግዚአብሔርም በዚህ በከሀዲ ንጉሥ ላይ የበርበርን ሠራዊት አስነሳበት ከእርሳቸውም የተነሣ ፈራ ገደሉትም መንግሥቱንም ብህልና አዋቂ የሆነ ልጁ ወረሰ። አባቱ ያሠራቸውን ሁሉ ፈታቸው ከተሰደዱበትም መለሳቸው ወደ ሊቀ ጳጳሳትና ወደ ኤጲስቆጶሳት ሁሉ "ቤተ ክርስቲያናችሁን ክፈቱ መብራቶቻችሁንም አብሩ በእናንተ ላይ ምንም ምን የሚያደርስባችሁ ክፉ ነገር የለም" ብሎ ደብዳቤዎችን ጻፈ። ይህም አባት ቀሪ በጸጥታና በሰላም ኖረ።
❤ ደግሞ በዚህ አባት በዲዮናስዮስ ዘመን ከዓረቢያ አገር በኵል የመጡ "ነፍስ ከሥጋ ጋር ትሞታለች ከዚያም በትንሣኤ ቀን ትነሣለች" በማለት የሳቱ ዝንጉዎች ሰዎች ተነሡ። በእነርሱ ላይም የኤጲስቆጶሳትን ጉባኤ ሰብስቦ አውግዞ ለያቸው ሌሎችም የረከሱ የአርዮስንና የሰባልዮስና እምነት ይዘው የተነሡ አሉ።
❤ ይህ አባት ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ ወልድን የካደ ሳምሳጢ ጳውሎስ ተነሥቶ አሳተ። አንጾኪያ ኤጲስቆጶሳት በአንድነት ተሰበሰቡ ይህ አባት ግን ስለ እርጅናው አብሮ አልተሰበሰበም በውስጥዋ የቀናች ሃይማኖትን የምትገልጥን ሀብቱ የሆነ ጥበብን ዕውቀትን የተመላች መልካም ምክርን የያዘ ደብዳቤ ጽፎ ላከ ወደ በጎ ሽምግልናም ደርሶ ወደ ወደደው እግዚአብሔር መጋቢት13 ከዓለም ተለይቶ መሔድን አገኘ። ከቅዱስ ዲዮናስዮስ በጸሎቱ የምትገኝ በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ምንጭ የመጋቢት 13 ስንክሳር።
❤ በገዳም ወይም በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ወይም በአገር ውስጥ ይህ ዜናችሁ በሚነበብበት እኔ አድራለሁ በረከቴንና ሰላሜንም እስከ ዓለም ፍጻሜ በውስጥዋ አደርጋለሁ። ለዚህ ለስደታችሁ ዜና ተቃራኒ የሚሆን ባልተወለደ በተሻለው ነበር። በእውነት እነግራችኋላሁ በሰው ፊት እንደአመናችሁብኝ በሰማያት በአለው አባቴ ፊትና በከበሩ መላእክቶቼ ፊት አምንባችኋለሁ። አሁን ግን ወደ ሀገራችሁ የምትመለሱበት ጊዜ ደረሰ ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጥቷቸው ወደ ሰማይ በክብር ዐረገ።
❤ ከዚህ በኋላ ሕዝቡን ሁሉ ንጉሡንም ሰበሰቧቸው ወደ አገራቸውም እንደሚመለሱ ነገሩአቸው የክርስቶስንም ሕጉን ሁሉ እንዲጠብቁ ለሊቀ ጳጳሳቱ ዮሐንስም እንዲታዘዙ አዘዙአቸው።ከቀናች ሃይማኖት ወደ ቀኝም ቢሆን ወደ ግራም ፈቀቅ እንዳይሉ በብዙ አማፀኑአቸው አስጠነቀቋቸውም። ሕዝቡም ሰምተው ደነገጡ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ ቅዱሳን አባቶቻችንም ከእሳቸው ጋራ በአንድነት አለቀሱ ከእዚህም በኋላ እየአንዳንዳቸውን ባረኳቸውና ተሰናበቷቸው።
❤ ያን ጊዜም ከኪሩቤል ወገን የሆነ መልአክ መጣ አውጥቶም በክንፎቹ ተሸከማቸው ወደ እስክንድርያም አድርሶ በሊቀ ጳጳሳቱ ደጅ እሑድ ጥዋት አወረዳቸው።ሊቀ ጳጳሳቱ አባ ጢሞቴዎስም ሰምቶ እጅግ ደስ አለው።ሁለተኛም በአያቸው ጊዜ አለቀሰ ሰገደላቸውም እነርሱም ሰገዱለት እርስ በርሳቸውም እጅ ተነሣሥተው ሰላምታ ተለዋወጡ። ጤንነታቸውንም ተነጋገሩ ደግሞም ልዩ የነበሩ የአሕዛብን ወደ እግዚአብሔር ስለመመለሳቸውና ስለ ተደረጉት ድንቆች ተአምራት ነገሩአቸው።ሊቀ ጳጳሳቱ አባ ጢሞቴዎስና ይህን የሰሙ ሁሉም ሕዝብ አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት አባቶቻቸንም በዚያ ስምንት ቀን ተቀመጡ።
❤ ከዚህም በኋላ ያ መልአክ ተገልጦ በክንፎቹ ደግሞ ተሸከማቸው ወደ ደብረ ሲሐትም አደረሳቸው አንዱ ኪሩብም ከአየር ሁኖ የአባት መቃርስ ልጆች ሆይ አባታችሁ የመንፈስ ቅዱስን ፍሬዎች ተሸክሞ ከስደት ተመልሶ መጥቷልና ወጥታችሁ ተቀበሉ እያለ ጮኸ፡፡ ይህንንም በሰሙ ጊዜ ከታላላቆች እስከ ታናናሾች ወጡ ቁጥራቸውም አምሳ ሺህ መነኰሳት ሆኑ። ከውስጣቸውም በዚያን ጊዜ አባ ዮሐንስ ሐፂርና አባ ብሶይ አሉ የደረሰባቸውንም ሥቃይ በነገራቸው ጊዜ እጆቹንና እግሮቹን እየሳሙ መሪር ዕንባ አለቀሱ። ደግሞ ፊቱን ስለአዩ ደስ አላቸው እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ባረካቸው።
❤ የክርስቶስ ወገን የሆናችሁ በዓለሙ ሁሉ የምትገኙ ምእመናን ሆይ በዘመናት ሁሉ በዓል እያደረጋችኋት በዚች ዕለት ደስ ሊላችሁ ይገባል።ይህም ለአምላካችን ክርስቶስ ስለ ስሙ ደማቸውን እንዳፈሰሱ እንደ ጴጥሮስና እንደ ጳውሎስ መታሰቢያ ለእሊህ ታጋዮች አባቶች ለመከራቸው መታሰቢያ እንዲሆን።
❤ እሊህም ታላቁ አባ መቃርስና ባልንጀራው የእስክንድርያው አባ መቃርስ ናቸው በዚች በመጋቢት ወር በዐሥራ ሦስተኛ ቀን ሉክዮስ ከእስክንድርያ አስቀድመን ወደ አወሳናት ደሴት አጋዛቸው ደግሞ በዚሁ ቀን ተመልሰው ወደ እስክንድርያ ደረሱ፡፡ የታላቁ መቃርስና የእስክድርያው መቃርስ በጸሎታቸው የሚገኝ በረከት በሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ላይ ለዘላለሙ አድሮብን ይኖርብን ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ዲዮናስዮስ፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ እምነት የሌላቸው አረማውያን ናቸው። እርሱ ግን ብዙ ትምህርቶችን ተማረ አባቱ በዘመድ የከበረ ስለነበር ከታናሽነቱ ጀምሮ አስቦለት ለአረማውያን መምህራን መምህራቸው እስኪሆን ጥበብን ሁሉ አስተማረው።
❤ በአንዲት ቦታ ተቀምጦ ሳለ አንዲት አሮጊት ክርስቲያን ሴት በፊቱ አለፈች። ከሐዋርያ ከቅዱስ ጳውሎስ መጽሐፍም አንድ ጥራዝ ይዛ ነበር እርሱም "እስቲ ስጪኝ ልየው" አላት እርሷም ሰጠችውና አነበባት። በውስጧም ልዩ የሆነ ቃልንና የሚያስደንቅ ዕውቀትን አገኘ "በምን ያህል ትሸጪዋለሽ" አላት። "በአንድ አላድ" አለችው እርሱም "ከዚህ መጽሐፍ የቀረ አለ ከአገኘሽ ሒደሽ አምጭልኝ" አላት አሮጊቷም ሒዳ ሌሎች ሦስት ጥራዞች አመጣች እርሱም አራት የወርቅ አላድ ሰጣት ከአነበባቸውም ጊዜ መጽሐፋ ጎደሎ ሆኖ አገኘው። ዳግመኛም "ከዚህ መጽሐፍ የቀረ አለ ብታገኚ ሒደሽ ፈልጊ" አላት እርሷም "በአባቶቼ መጻሕፍት ውስጥ እሊህን ብቻ አገኘሁ ምሉውን የቅዱስ ጳውሎስን መጽሐፍ ከፈልግህ ወደዚያች ቤተ ክርስቲያን ሒደህ ጠይቅ" አለችው። እርሱም "ከቤተ ክርስቲያኒቱ ብፈልግ ከእርሷ ይሰጡኛልን" አላት። "አዎን ይሰጡሃል" አለችው። ሒዶም ወደ ቤተ ክርስቲያን ጠየቀ እነርሱም የጠየቀውን መጽሐፍ ሰጡት አነበበውም በልቡም አጸናው። ያለ መጽሐፍም በቃሉ ያነበው ነበር በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመነ።
❤ ከዚም በኋላ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ድሜጥሮስ ዘንድ ሒዶ ያጠምቀው ዘንድ ለመነው እርሱም ሕግና ሥርዓትን ትምህርትን ሁሉ አስተምሮ ከዚያ በኋላ አጠመቀው። አባ ድሜጥሮስም ለቤተ ክርስቲያን ልጆች ሁሉ አስተማሪ አደረገው።
❤ አባ ያሮክላ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ ይህን አባት ዲዮናስዮስን በእስክንድርያ አገር ውሰጥ በወንዶችም በሴቶችም ምዕመናን መካከል እንዲፈርድላቸው እንደ ራሴ አድርጎ ሾመው በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ላይ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው።
❤ አባ ያሮክላም በዐረፈ ጊዜ ሕዝቡና ካህናት ሁሉም ተስማምተው በእስክድርያ አገር ላይ ይህን አባት ዲዮናስዮስ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት መንጋውንም በበጎ አጠባበቅ ጠበቀ ነገር ግን በሹመቱ ዘመናት ብዙ መከራና ኀዘን አገኘው።
❤ በዘመኑም ከሀዲው ዳኬዎስ ተነሥቶ ክርስቲያንን ከሚወድ ከፊልጶስ ጋር ተዋጋ ድል አድርጎም ፊልጶስን ገደለው። በእርሱ ፈንታም ነገሠ በክርስቶስ የሚያምኑትን ምዕመናንን ሁሉ አሠቃያቸው። ከጳጳሳትና ከምዕመናንም ብዙዎች ሰማዕታትን ገደላቸው ከፍርሃትና ከድንጋፄም የተነሣ ወደ በረሃ ወደ ገዳም ሸሽተው በዚያው የሞቱ አሉ። የዚህም ዳኬዎስ ጭፍሮች ይህን አባት አግኝተው ያዙት ለብዙ ጊዜ አሠሩት።
❤ ከዚህ በኋላ በአምላክ ፈቃድ ይህ ከሀዲ ጠፋ በእርሱም ፈንታ ግርላዎስ ነገሠ ከክርስቲያንም ልጆች መከራው ጸጥ አለ በዘመኑም ሰላም ሆነ።
❤ ከዚህ በኋላ ግርላዎስ ሞተ በእርሱ ፈንታም ዋርልዮስ ነገሠ እርሱም ሁለተኛ በክርስቲያን ወገኖች ላይ እጅግም አሥነሣ የዚህ ከሀዲ ንጉሥም መኳንንቶች ይህን አባት ይዘው አሠሩት ታላቅ ሥቃይም አሠቃዩት እጅግም አስጨነቁት። ንጉሡም ይህ አባት ለጣዖት እንዲሰግድ ፈለገ እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኛስ ለክብር ባለቤት ለእግዚአብሔር አብ ለልጁ ለኢየሱስ ክርስቶስ ለመንፈስ ቅዱስ አንዲት ስግደትን እንሰግዳለን" አለው። ንጉሡም ሰምቶ እጅግ ተቆጣ ሊያስፈራራውም በፊቱ ብዙ ሰዎችን ገደለ ቅዱሱ ግን አልፈራውም ወደ ደሴትም አጋዘው በዚያም ብዙ ዘመናት ኖረ።
❤ ከዚህም በኋላ ከግዞት መልሶ "አንተ በሥውር ለብቻህ እንደምትቀድስ ስለ አንተ ሰማሁ" አለው። ቅዱሱም አባት መልሶ "እኛ ጸሎታችን ምስጋናችንን ቅዳሴያችንን በቀንም በሌሊትም ቢሆን አንተውም" ከእርሱ ጋርም ወደሆኑ ወገኖች ዘወር ብሎ "ሒዱ ቀድሱ በሥጋ ከእናንተ የራቅሁ ብሆን በመንፈስ ከእናንተ ጋር ነኝ" አላቸው። ንጉሡም ተቆጥቶ ወደ ስደት መለሰው።
❤ ከዚህም በኋላ የሀገሩን ምኵራብ አስፈርሰው ቦታውን አጸዱ አነፁ ቦታውም እጅግ ስፋት ያለው መልካም ስለሆነ ቤተ ክርስቲያን አሳነፁ ንጉሡም ስፍር ቁጥር የሌለው ወርቅና ብር የሐር ልብሶችንም ለእግዚአብሔር መቅደስ ለሚአሻውም ሁሉ አመጣ። የከበሩ አባቶቻችንም ጥበብ ያላቸው አንጣሪዎችን ሚዛኑ ለየአንዳንዱ ዘጠኝ ልጥር የሚሆን አሥራ ሁለት ጻህሎችን ሠርተው የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንና የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ሥዕል የሁለቱንም የመላእክት አለቆች የሚካኤልንና የገብርኤልን ሥዕል በውስጡ እንዲሥሉ ደግሞ አሥራ ሁለት መንበሮችን ለመሠዊያ የሚፈለገውንም ሁሉ አሥራ ሁለት ጽዋዎችና አሥራ ሁለት ዕርፈ መስቀልም እያንዳንዱ ሦስት ሦስት ልጥር የሆኑ ሃያ አራት መስቀሎችን እንዲሠሩ ሦስቱንም የመቅደስ ግድግዳ እንዲሥሉ አዘዙ።
❤ የቤተ ክርስቲያኒቱ የሕንፃዋ ሥራ ተፈጸመ። የተረፈውንም ገንዘብ ለድኆችና ለችግረኞች በተኑ። ጌታችን የተጠመቀባት ጥር ዐሥራ አንድ ቀን በሆነች ጊዜ ወደ ባሕር አጠገብ እንዲወርዱና እንዲሰበሰቡ የአገሩን ሰዎች አዘዙዋቸው። ከእስክንድርያም በተሰደዱ ጊዜ እግረ መንገዳቸውን የያዙትን የከበረ ሜሮንን አመጡ። ይህም ከሐዋርያዊ አትናቴዎስ ጊዜ ጀምሮ የተጠበቀ ሉክዮስም ያላገኘው ጌታችንም በዘመናት ሁሉ የጠበቀው ጥፋት ያላገኘው ነው።ይህ በመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ ሆኖአልና።
❤ በዚያንም ጊዜ አባት መቃሪ በከበረ ሜሮን በጥልቁ ባሕር ላይ ባረከ ባሕሩም ከእሳት ኃይል የተነሣ በድስት እንደሚያፈሉት ውኃ የሚፈላ ሆነ ዘይቱና ሜሮኑም በውኃው ላይ ተንሳፈው እንደሚያበሩ ከዋክብት ሆኑ ከእርሳቸውም እንደ ፀሐይ የሆነ ታላቅ ብርሃን ታየ። ንጉሡና የተሰበሰቡት ሕዝብ አይተው ፈሩ። የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠ። አጥማቂው ዮሐንስና ቅዱሳን መላእክትም ውኃው በመከብርበትና በሚለወጥበት ጊዜ ተገለጡ። ሕዝቡም ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠመቁ ያንጊዜ ከሽቱ ሁሉ መዓዛው የሚጣፍጥ ሽታ ሸተተ።
❤ በዚያን ጊዜም የከበሩ አባቶቻችን ይህን አይተው በምድር ላይ ወድቀው ሰገዱ በስግደታቸው እዚያው ዘገዩ። አባት መቃርስም ሰግዶ ሳለ ጌታችንን እንዲህ ሲል ለመነው። ጌታዬ እለምንሃለሁ ቸርነትህ ትድረሰኝ የዚች ታቦትና ንዋየ ቅድሳቷ ቡራኬ በአምላካዊት እጅህ እንዲሆን አለው።ጌታም እሺ በጎ ብሎ ሜሮኑን ከአባ መቃሪ እጅ ተቀብሎ ታቦቱንና ንዋየ ቅዱሳቱን አከበረ።
❤ ከዚያም በኋላ አባት መቃርስን ሦስቱን ደርብ ትባርክ ዘንድ እኔ አዝሃለሁ እኔም ካንተ ጋራ አለሁ ይህንንም ንጹሕና ክቡር የሆነ አገልግሎት ባልንጀራህ አብሮህ ያገልግል። በመጀመሪያም የመካከለኛውን ደርብ በሥጋ በወለደችኝ በድንግል ማርያም ስም ለይተህ አክብር ደግሞ በቀኝ በኩል ያለውን በከበረ መስቀል ስም ለይተህ አክብር በግራ በኩል ያለውን ደርብ በስምህ ለይተህ አክብር በከሀዲ ሉክዮስ እጅ ስለ ስሜ በዚች ደሴት ውስጥ ደምህን አፍሰሃልና አለው።
❤ እሊህም የተባረኩ አባቶች ጌታችን እንደ አዘዘ ሊሠሩ በጀመሩ ጊዜ ንጉሥ ዳዊት በመዝሙር ሊያመሰግን ጀመረ መላእክትም በመልካም ቃላት በቋንቋቸው ያመሰግኑ ጀመር ሕዝቡም አድንቀው እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
❤ ዳግመኛም ጌታችን አባ መቃርስን መሥዋዕቱን ተሸክሞ በመሠዊያ ላይ ይቀድስ ዘንድ አዘዘው አባ መቃርስም ጌታችንን የሐዋርያት አለቃ አባታችን ጴጥሮስን እንዲቀድስ እዘዘው ይኽቺ ዕለት በከበረ ስምህ በዚች ደሴት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ መሥዋዕት የተሠዋባት ናትና አለው።
ጌታም ላንተ ይገባል አንተ በዚች ደሴት ዘርተሃልና እኔም አሳደግሁ በደቀ መዝ ሙሬ በጳውሎስ አድሬ የተናገርኩትን አላስተዋልክምን የዘራና የደከመ እርሱ አስቀድሞ ፍሬውን ይብላ ያልሁትን አለው።
❤ አባት መቃርስም የቅዳሴውን ሥርዓት ከጌታ ተባርኮ በጀመረ ጊዜ ከእስክንድርያዊ መቃርዮስ ጋራ ይራዱት ዘንድ ጴጥሮስ በቀኙ ማርቆስ በግራው ሁሉም ሐዋርያት በዙሪያው ቆሙ።ጳውሎስና ዮሐንስም የየራሳቸውን መልእክት አነበቡ ሉቃስም የሐዋርያትን ሥራ አነበበ ዳዊትም መዝሙሩን ዘመረ ለስም አጠራሩ ምስጋና ገንዘቡ የሆነ ጌታችንም ወንጌሉን አነበበ።በነጭ ርግብ አምሳልም መንፈስ ቅዱስ በኅብስቱና በውይኑ ላይ ወርዶ የጌታችን ክርስቶስን ሥጋና ደም ወደመሆን ለወጣቸው።
❤ አባት መቃርስም ወደ ጽዋው ጣቱን በአስገባ ጊዜ ጣቱ በደም ታለለ።የመላእክት ሠራዊት ሁሉ በመሠዊያው ላይ ክንፋቸውን ዘርግተው ይራዱት ነበር ሚካኤልና ገብርኤልም መጡ የመላእክት አንድነት ሁሉም በእርሱ በአባት መቃርስ አምሳል ሁነው እየተራዱት ለሕዝቡ የከበረ ሥጋውንና ደሙን አቀበለ። ከቁርባን ሥርዓት ፍጻሜ በኃላ ጌታችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመቃርስ አምሳል ሁኖ ወንጌል በሚነበብበት አትሮንስ ላይ ተቀመጠ ፊቱም እንደ ፀሐይ ይበራ ነበር ለሕዝቡም ቡራኬ ሰጥቶ ወደ መሠዊያው ተመለሰ ሐዋርያትም ከርሱጋራ።
❤ ዳግመኛም ከሰባት ቀኖች በኃላ አባታችን መቃርስ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሹመት ማዕርግ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ የክብር ባለቤት እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስም ተገልጦ በእኔ ዘንድ ለዚህ ታላቅ ክብር የምትገባ አንተ ነህና አለው።
❤ ሽማግሌውም ሰምቶ አለቀሰ በእግዚአብሔርም ፊት ሰገደ አቤቱ በሲሐት ገዳም ወዳሉ መነኰሳት ልጆችህ ጊዜው ሲደርስ እመልስሃለሁ ከዚህ ከሥጋህ ሳትለይ ያልከኝን አስብ።ይህ ካልሆነ መቃራ የምንኲስናውን ሥራ ትቶ ፓትርያርክ ሆነ ይላሉ አለ። ጌታችንም የመረጥኩህ መቃርስ ሆይ እኔ የልብህን ፍላጎት ሁሉ እፍጽምልሃለሁ ግን ፓትርያርክ ትሾም ዘንድ ከልጆችህ የመረጥከውን አንድ አቅርብ አለው። ቅዱስ መቃርስም አቤቱ አንተ ልብ ያሰበውን የምታውቅ ነህ እኔ ግን ወደዚህ አንጥረኛ ሽማግሌ ሰው ተመለከትኩ። እርሱ በቀናች ሃይማኖት የጸና ከሴቶችም ጋር ግንኙነት የማያውቅ ነው አለው ጌታችንም አንተ እንዳልክ ደግ ነው አለ። ቅዱስ መቃርስም ያንን አንጠረኛ ጠርቶ ወደ ታቦተ ሕጉ አቀረበው ያን ጊዜም ወንጌላዊው ማርቆስ መጣ እጁንም በአንጠረኛው ራስ ላይ ጭኖ ዲቁና ሾመው። ደግሞ ቅስና ሾመው ከዚያም የሊቀ ጵጵስና ሹመት እስከ ሚፈጽም በየመዐርጉ ሾመው ስሙንም ዮሐንስ አለው የሰማይ ሠራዊትም ሁሉም የወንጌላዊ ማርቆስ አዲስ ተክል የሆነ ለመቃርስ ልጅ ለዮሐንስ ሊቀ ጵጵስና ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል እያሉ ሦስት ጊዜ ጮኹ በዚያ ያሉ ሕዝብም እሊህን ቃሎች ይሰሙ ነበር።
❤ ጌታችንም የሊቀ ጳጳሳት የዮሐንስን ዓይነ ልቡናውን ገልጦለት በሚቻለው መጠን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አየው።ብዙ ቃላትንም ተናገረ ደግሞ ረቂቃን በሆኑ በሰማይ ሠራዊት ቤተ መቅደሱ ተመልቶ አየ የከበሩ ነቢያትና ሐዋርያትም በዚያ አሉ።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታላቁ አባ መቃራንና የእስክንድርያውን አባ መቃራን ጠራቸው እንዲህም አላቸው በምድር ሳሉ መታሰቢያችሁን የሚያደርጉ ሰዎች የተመሰገኑ ናቸው የዘላለም ሕይወትን ይወርሳሉና በራሴ እምላለሁ ስለ ስሜ የተቀበላችሁትን መከራ በትጋት የሚአስበውና የሚጽፈው የሚሰማው ሁሉ ያመሰግነኝ ዘንድ በቤተ ክርስቲያን የሚያነበው እኔ በጎ ነገርን ሁሉ እሰጠዋለሁ። ከበጎ ነገርም ምንም አላሳጣውም ከመከራውም ሁሉ አድነዋለሁ ኃጢአቱንም ሁሉ አስተሠርይለታለሁ። ከዚህ ዓለምም በሚለይለት ጊዜ ነፍሱን ወደ ዘላለም ተድላ ደስታ ይወስዱ ዘንድ እናንተ ወደም ታስቡትም መንግሥቴ ሊአስገቡት የምሕረት መላእክትን እልካለሁ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፫ (13) ቀን።
❤ እንኳን #ለከበሩ_አርባ_ሐራ_ሰማይ ልብስጥያ በሚባል አገር ለሆኑ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል፣ #ለታላቁ_አባ_መቃርስና #ለእስክድርያው_አባ_መቃርስ ለስደታቸው መታሰቢያ በዓልና ለእስክድርያ 14ኛ ሊቀ ጳጳሳት #የቅዱስ_ጳውሎስ መልክትን አንብቦ በመመርመር አምኖ ለተጠመቀ #ለአባ_ዲዮናስዮስ ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_አርባ_ሐራ_ሰማይ፦ እሊህ ቅዱሳንም በአልፊያኖስ ዘመን ተጋደሉ እርሱም ከንጉሠ ነገሥት ቈስጠንጢኖስ ከመኳንንቶቹ አንዱ ነው። ከአይሁድ አገሮችም በአንዱ ላይ አነገሠው ክርስቲያኖችንም እንዲጠብቃቸውና እንዲያከብራቸው አዝዞት ነበር።
❤ እርሱ ግን ወደዚያ አገር በደረሰ ጊዜ ጣዖትን አመለከ ሰዎችንም ሁሉ ጣዖት እንዲአመልኩ አስገደዳቸው ብዙዎች ምእመናንም ተነሥተው እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገሙ። በዚችም ሌሊት እሊህ አርባ ጭፍሮች ወደ መኰንኑ ደርሰው በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ምስክር ይሆኑ ዘንድ እርስ በርሳቸው ተስማሙ። በእንቅልፋቸውም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ለሰውነታቸው ብርታትን ሰጣቸው በጥዋትም ተነሥተው የጭፍራ አለቃ በሆነ በአግሪጎላዎስ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ። በላያቸውም ተቆጥቶ አስፈራራቸው እነርሱ ግን አልፈሩም በደንጊያም እንዲወግሩአቸው አዘዘ። በቅራቢያቸውም የውሽባ ቤት በአጠገቧ ያለ የውኃ ጒድጓድ ከውርጭ ጽናትም የተነሣ ትረጋለች በውስጥዋም ይጥሏቸው ዘንድ መኰንኑ አዘዘ። በውስጥዋም በጣሉአቸው ጊዜ ከውርጭ ጽናት የተነሳ ሕዋሳታቸው ተቆራረጠ ከእሳቸውም አንዱ ፈራ ከዐዘቅቱም አወጡኝ ብሎ ወጣ ወደ ወሽባው ቤትም ገባ ፈጥኖም ሞተ ዋጋውንም አጠፋ የፈለገውንም አላገኘም።
❤ አርባ አክሊላትም ከሰማይ ሲወርድ በሠላሳ ዘጠኙ ሰማዕታት ላይም ሲቀመጡ አንዱ አክሊልም በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ ሲቀር ከወታደሮች ይህን ያየ ከዚያ ተነሥቶ ቅዱሳን ወደአሉበት ወደ ዐዘቅቱ ወረደ በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ የቀረውንም አክሊል ወሰደ።
❤ እሊህም ጐልማሶች ሰማዕታት በዚያች ዐዘቅት በነበሩበት ጊዜ እናቶቻቸው ያጽናኗቸውና ያስታግሷቸው ነበር። እርሱም ብዙ ጊዜ ቆዩ እንጂ ቶሎ አልሞቱም። ከሀድያንም ጭኖቻቸውን ሊሰብሩ ፈለጉ ፈጥነው እንዲሞቱ እግዚአብሔርም ወዲያውኑ ነፍሳቸውን ወሰደ ጭኖቻቸውን መስበር አልተቻላቸውም። ከዚህ በኋላ በእሳት ሥጋቸውን እንዲያቃጥሉ በተሽከርካሪም ጭነው ወስደው ወደ ባሕር እንዲጥሏቸው መኰንኑ ወታደሮችን አዘዘ።
❤ ሲጭኑአቸውም ያልሞተ ሕፃን አገኙና ተዉት እናቱም ከሠረገላው ውስጥ ልትጥለው ተሸክማው ሮጠች ወታደሮችም ስለአልሞተ ከለከሉአት ወዲያውኑ በጫንቃዋ ላይ ሙቶ ከቅዱሳን ጋር እንዲሆን ወደ ተሽከርካሪው ጣለችው። ወደ ስብስጥያ ከተማ ጭነው ወስደው በእሳት አቃጠሉአቸው ወደ ባሕርም ጣሏቸው።
❤ ከዚህም በኋላ በሦስተኛ ቀን ለስብስጥያ አገር ኤጲስቆጶስ ተገለጡለት። እንዲህም አሉት "ወደ ዕገሌ ወንዝ ሒድ ሥጋችንንም ታገኛለህና አሸክመህ አምጣው" ኤጲስቆጶሱም ከካህናት ጋርራ በሌሊት ተነሥቶ ወደ ወንዙ ሔዱ የቅዱሳንንም ሥጋቸውን በአንድ ቦታ ተሰብስቦ እንደ ከዋክብት እያበራ አገኙት ከእርሳቸውም አንድ እንኳን አልጐደለም በክብር ተሸክመው ወስደው በመልካም ቦታ በክብር አኖራቸው።
❤ ዜናቸውም በአራት ማዕዘን ተሰማ መታሰቢያቸውንም አደረጉ በዓለም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን ታነፀላቸው ከሥጋቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። የቅዱሳን የአራባ ሐራ ሰማዕታት በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ታላቁ_አባ_መቃርስና የእስክድርያው #አባ_መቃርስ_ስደታቸው፦ ይህም ከሀዲ ሉክዮስ ታላቁን አባት አባ መቃሪን እስክንድርያዊውን አባት መቃርዮስን ፈልጎ በንጉሥ ትእዛዝ ወደርሱ ከገዳማቸው አስመጣቸው። ወደርሱም በደረሱ ጊዜ ለያይቶ በለሰለሰ አንደበት በመሸንገል ወደረከሰ የአርዮስ ሃይማኖት ይገቡ ዘንድ አግባባቸው። እነርሱ ግን ወደ ነገሩ አልተመለሱም ሳይፈሩትም መለሱለት በቅንነትና በትዕግሥትም መከሩት ገሠጹት እንጂ የአርዮስንም ሃይማኖት ብላሽነት የባህሉንም አስከፊነት ከቅዱሳት መጻሕፍት ለይተው አስረዱት።
❤ በዚያን ጊዜም ተቆጣ ከቊስጥንጥንያ መካከል ወደምትርቅ ደሴት አጋዛቸው ከእስክንድርያም መርከብን የሚጠብቋቸውንም ወታደሮችን በእነርሱ ላይ በሚያደርጉት ሥራ ሁሉ አጫንቀው በብረት አሥረው ይወስዱአቸው ዘንድ አዘጋጁ። ወደዚች ደሴት በደረሱ ጊዜ በደሴቱ ንጉሥ ፊት አቆሙአቸው ንጉሡም ሰይጣንን የሚያመልክ የከፋ ሰው ነበር የደሴቱም ሰዎች አምላክ ነው ብለው እስቲ አምልኩትና እስቲሰግዱለት ድረስ በሥራዩ አስቷቸው ነበር።
❤ እሊህ አባቶቻችንም ከስሕተቱ እንዲመለስ አስተማሩት ለመኑትም አልሰማቸውም ከብዙ ሥቃይ ጋር በወህኒ ቤት ዘጋባቸው እንጂ በጽኑዕ ሥቃይም አሠቃያቸው ጌታችንም ተገልጦ የሚያጸናቸውና የሚያስታግሣቸው ሆነላቸው። የክብር ባለቤት ጌታችንም ጽድቃቸውንና ትሩፋታቸውን ሊገልጥ በወደደ ጊዜ የንጉሡን ልጅ ሰይጣን ያዛት። አባትና እናቷም በታላቅ ኀዘን ላይ እስቲሆኑ አብዝቶ አሠቃያት በከተማ ውስጥም ሰይጣናት ተገልጠው መቃርስና ባልንጀራው ሆይ እኛ ከእናንተ እናንተ ከኛ ምን አላችሁ ከአገራችሁ ያሰደዳችሁን እያሉ ተገልጠው ይጮኹ ጀመር።በንጉሡ ልጅ ያደረውም ሰይጣን ንጉሥ ሆይ መቃርስና ባልንጀራው ካልመጡ ከልጅህ ላይ አልወጣም ብሎ ጮኸ ንጉሡና አብረውት ያሉ አደነቁ ወደ ንጉሡም ቅዱሳንን አመጡአቸው።
❤ እሊህ ቅዱሳን መቃርስና ባልንጀራው ወደ ንጉሥ በደረሱ ጊዜ በንጉሡ ልጅ ያደረ ሰይጣን እንዳያሠቃዩት ለመነ። ንጉሡና አብረውት ያሉትም ስለ ሥራቸው ቅዱሳንን መረመሩአቸው፡፡ እነርሱም የሆነውን ሁሉ ነገሩአቸው ስለ ንጉሡም ልጅ ያድኑዋት ዘንድ ለመኑዋቸው። እነርሱም ንጉሡን ገሠጹት እንዲህም አሉት አንተ ሰው ስትሆን ለምን ራስህን አምላክ ታደርጋለህ ዓለምን የፈጠረ አምላክ ከሆንክ ራስህንና ልጅህን ማዳን ይገባህ ነበር። ያን ጊዜም ወደ ክብር ባለቤት ጌታችን ጸልየው ጋኔኑም በወጣ ጊዜ ስለ ክፉ ሥራቸው ንጉሡንና የዚያችን ደሴት ሰዎች ዘለፋቸው።
❤ ንጉሡና በዚያ የተሰበሰቡት ይህን አይተው በእሊህ ቅዱሳን አምላክ እናምናለን ከእሊህ ቅዱሳን አምላክ ከእግዚአብሔር በቀር በሰማይና በምድር ሌላ አምላክ እንደሌለ ተረድተናልና እያሉ ጮኹ። የከበሩ አባቶቻችንም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን አሰተማሩአቸው እነርሱም በሽተኞቻቸውን ሁሉ ሰበሰቡ አባቶቻችንም በዘይት ላይ ጸልየው በመስቀል ምልክት አማትበው ቀብተው በሽተኞችን ሁሉ አጋንንት ያደሩባቸውንም ሁሉንም አዳኑአቸው እንዲሁም እያደረጉ እያስተማሩዋቸውም ብዙ ቀን ኖሩ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፪ (12 ) ቀን።
❤ እንኳን #ለሊቀ_መላእክት_ለቅዱስ_ሚካኤል ወደ #ፈላስፋው_በለዓም ለተላከበት ወራዊ መታሰቢያ በዓልና ለከበረና ለተመሰገነ ለእስክንድርያ ዐሥራ ሁለተኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለአባ_ድሜጥሮስ ለልደቱና ድንግልናውን ለገለተለጠበት ቀን መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከፍልስጥዔም አገር ከሆነ #ከቅዱስ_መላዚ በሰማዕትነት ከዐረፈ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅዱስ_ሚካኤል_ወደ_በለዓም_መላክ፦ በለዓምን እስራኤልንም ይረግማቸው ዘንድ ባላቅ በጠራው ጊዜ። በጐዳናም በፊቱ ቅዱስ ሚካኤል ቆሞ ስለተገለጠ አስደንግጠው አህያው በሰው አንደበት እስተናገረች ድረስ። መርገሙንም ወደ በረከት መለሰው። በቅዱስ ሚካኤል በአማላጅነቱ ለዘላለሙ ይጠብቀን አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅዱስ_ድሜጥሮስ፦ ድንግልናው የመገለጡ ምክንያት እንዲህ ነው ከእርሱ በፊት ሊቀ ጳጳሳት ለነበረው ለቅዱስ ዮልያኖስ መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገልጦለት "አንተ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ክርስቶስ ትሔዳለህ የወይን ዘለላ ይዞ ነገ ወደ አንተ የሚገባ ሰው ከአንተ በኋላ ሊቀ ጳጳስ ሊሆን የሚገባው እርሱ ነው" አለው።
❤ ማግስት በሆነ ጊዜም የከበረና የተመሰገነ ድሜጥሮስ የወይን ዘለላ ይዞ ወደ ከበረ ዮልያኖስ ዘንድ ገባ ቅዱስ ዮልያኖስም ያዘው "ከእኔ በኋላ ሊቀ ጳጳሳታችሁ እንሆ" ብሎ ለሕዝብ አስረከባቸው ስለእርሱም የእግዚአብሔር መልአክ እንደተገለጠለት ነገራቸው።
❤ አባ ዮልያኖስም በዐረፈ ጊዜ በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበር ላይ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ሾሙት በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበር ከእርሱ በቀር ሚስት ኑራው የተሾመ የለም።
❤ ሰይጣንም በሰዎች ልቡና አደረ። በእርሱ ላይም በመናገር የሚያሙት ሆኑ። ስለዚህም ነገር ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለቅዱስ ድሜጥሮስ ተገልጦ እንዲህ አለው "ከሕዝቡ የሚያሙህ አሉና ከልባቸው ጥርጥርን ልታርቅ ይገባሃል። ከሚስትህም ጋር ያለውን የገድልህን ምሥጢር ልትገልጥላቸው ይገባሃል አንተ ራስህን አድነህ በአንተ ምክንያት ሌሎች ይጠፉ ዘንድ አይገባህም ቸር ከሆንክስ ወገኖችህን ለማዳን ትጋ" አለው።
❤ ማግስት በሆነ ጊዜም ይህም መጋቢት ዐሥራ ሁለት ቀን ነው የቁርባንን ቅዳሴ ቀደሰ። ሕዝቡንም እንዲጠብቁ እንጂ ከቤተ ክርስቲያን እንዳይወጡ አዘዛቸው። ደግሞ እሳትን እንዲያነዱ አዘዛቸው ወደ ሴቶች መቆሚያም ልኮ ሚስቱን አስመጣት ከሥራው የተነሣ ሕዝቡ ያደንቁ ነበር ምን ሊሠራ እንደፈለገ ሕዝቡ አላወቁምና።
❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ድሜጥሮስ ተነሥቶ ተንቀሳቀሰ ከእሳቱ መካከል ገብቶ በመቆም በእሳቱ እየነደደ በውስጡ ጸለየ ከእሳቱም ፍም በእጁ ዘግኖ በልብሰ ተክህኖው ላይ አኖረ በእሳቱ ውስጥም ቁሞ ለረጅም ጊዜ ጸለየ በልብሰ ተክህኖው ውስጥ ያለ እሳቱንም አይቀጣጠልም። ከዚህም በኋላ ሚስቱን ጠርቶ ያንን እሳት በመጐናጸፊዋ ውስጥ ጨመረ ረጅም ጸሎትም ጸለየ ከልብሶቻቸው ምንም ምን አላቃጠለም። ሕዝቡም አድንቀው እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
❤ ሕዝቡም ይህን ሥራ በምን ምክንያት እንደሠራ ያስረዳቸው ዘንድ የከበረ ቅዱስ ድሜጥሮስን ለመኑት። እርሱም ከሚስቱ ጋራ ያለውን ገድሉን ገለጠላቸው "ያለውዴታው እርሷም ጋብቻ ሳትሻ እንዳጋቡት እንዲህም አለ እነሆ በአንድነት እኛ አርባ ስምንት ዓመት ስንኖር በጋብቻ ሥርዓት ከተገናኘንበት ጊዜ ጀምሮ በአንድ አልጋ አንድ ልብስን እንተኛለን ግን ወንዶች ሴቶችን በግብር እንደሚአውቋቸው ሴት እንደሆነች አላውቃትም። በዚህ ሁሉ ዘመን በየሌሊቱ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ እየወረደ በክንፎቹ ይሸፍነናል። ይህንንም በዚህ ሁሉ ዘመን ከሰው ወገን ለማንም ከቶ አልገለጥኩም። ልገልጠውም ከቶ አልሻምና ግን እናንተ ከበደል ትድኑ ዘንድ እርሱ እግዚአብሔር አዘዘኝ እንጂ" አላቸው።
❤ ከአዩትና ከሰሙት የተነሣ ሕዝቡ እጅግ አደነቁ እግዚአብሔር አመሰገኑት እርሱን ስለማማታቸው የበደሉትን በደል ይቅር ይላቸው ዘንድ እያለቀሱ ቅዱስ ድሜጥሮስን ለመኑት። እርሱም ስሕተቻቸውን ይቅር ብሎ "በጎ ሥራን ከሚጠላ ከሰይጣን እንጂ ከእናንተ አይደለምና አትዘኑ" አላቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ባረካቸው ወደ ቤታቸውም ይገቡ ዘንድ በሰላም በፍቅር አሰናበታቸው ከሊቀ ጳጳሳቱ ከቅዱስ ድሜጥሮስ ከአዩት ተአምራት የተነሣ እግዚአብሔር እያመሰገኑ ወደ ቤታቸው ገቡ። ከቅዱስ ድሜጥሮስ በጸሎቱ የምትገኝ በረከት ከእኛ ጋር ለዘላለም ትኑር። ምንጭ፦ የመጋቢት12 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለድሜጥሮስ እንተ በእዴሁ ተጽሕፋ። ሐሳበ አዝማን ዘድኅር ወእለ ኀለፋ። አርአየ ዮም ኃይለ ድንጋሌሁ በሥምረተ አምላክ አልፋ። ዐቊሮ እሳት በኵፋሩ ወለብእሲቱ በዓጽፋ። ለእለ ናፈቁ ሕዝብ ከመ ይኩን ተስፋ"።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለከ_ሰማዕት_መላዚ። ዘምድረ ፍልስጥዔም ወልደ አግአዚ። ምሕረተ ነድያን እለቡ እንዘ ኢይሴዚ። ከመ ታምክረኒ ነዓ ናዛዚ። ቅድመ ይዳደቀኒ ሊተ እደ ሞት አኀዚ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢ_12።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "አእይንትየሰ ኀበ መሃይምናን ምድር። ከመ አንብሮሙ ምስሌየ። ዘየሐውር በፍኖት ንጹሕ ውእቱ ይትለአከኒ። መዝ 100፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥1-17።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ_ምሰባክ፦" ይትዐየን መልአከ እግዚአብሔር ዓውዶሙ። ለእለ ይፈርህዎ ወያድኅኖሙ። ጠዐሙ ወታምእሩ ከመ ኄር እግዚአብሔር"። መዝ33፥7-8። የሚነበበው ወንጌል ማቴ18፥10-21። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 7፥1-8፣ 2ኛ ጴጥ 2፥9-ፍ.ም እና የሐዋ 27፥1-11። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ሚካኤል ወራዊ በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፪ (12 ) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ "በዓለም ነግሦ መኖር አልፈልግም" ብለው ለመነኑ፤ #ለንጉሡ_ዐፄ_ዳዊት_ልጅና_ለዐፄ_ዘርዓያዕቆብ_ወንድሜ_ለሆኑት፤ በመስቀላቸው በመባረክ በሐምሌ ወር የዠማን ወንዝ አቁመው ለተሻገሩ ለታላቅ አባት #አቡነ_ተስፋ_ጽዮን_ዘሸዋ ለዕረፍቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ተስፋ_ጽዮን፦ የተባሉት ጻድቅ አገራቸው ሸዋ ሲሆን የንጉሡ የዐፄ ዳዊት ልጅና የዐፄ ዘርያቆብ ወንድሜ ናቸው። ስንክሳሩ መናኔ መንግሥት ወብእስት በማለት ይጠራቸዋል። "በዓለም ነግሦ መኖር አልፈልግም" በማለት የዓለምን ጣዕም ንቀው በመተው ገዳም ገብተዋል። በታላቅ ተጋድሎ እየኖሩ አጠቃላይ የመርሐ ቤቴ ገዳማትን ሲመሩና ሲያስተዳድሩ ነበር።
❤ ጻድቁ በመስቀላቸው በመባረክ በሐምሌ ወር የዠማን ወንዝ አቁመው የተሻገሩ ታላቅ አባት ናቸው። ብዙ ሙታንን በማስነሣትና ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ነው ወንጌልን ሲሰብኩ የነበረው። በተለያየ አገር የሚኖሩ ቢሆኑም ከወለቃው አቡነ ዘአማሩኤል ጋር በመንፈስ ቅዱስ መሪነት እየተገናኙ ስለ ገዳማት ይወያዩ ነበር። ጻድቁ በትግራይ ትልቅ ገዳም ያላቸው ሲሆን በደብረ በግዕና በዜና ማርቆስ ገዳም ደግሞ ቅዱስ ገድላቸው ይገኛል። ጻድቁ ከብዙ ተጋድሎ በኋላ ጌታችን ተገልጦላቸው ታላቅ ቃልኪዳን ከሰጣቸው በኋላ መጋቢት12 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል። ከአባታች አቡነ ተስፋ ጽዮን ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦መዝገበ ቅዱሳን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፩ (11) ቀን።
❤ እንኳን #ለቅዱስ_ቴዎቄጤኖስ፣ ለብፅዕት #ቅድስት_እስክንድራ በንጉሥ መክስምኖስ ዘመን ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓልና #ለተጋዳይ_ለሆኑ_ለኤጲስቆጶስ በመኰንኑ ልጅ መቃብር ላይ ጸሎት አድርገው ልጁን ከሞት ላስነሱና ሕዝቡን አሳምነው ላጠመቁ #ለአባ_ባስሊዖስ ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱሳን_ከአውሳብዮስ_ከኤፍሬም_ከአርቃድዩና ከሰማዕቱ ኤልያስ ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ቴዎቄጤኖስ፦ ይህ ቅዱስ አስቀድሞ ወታደር ነበር። ትጥቁን በንጉሡ ፊት ጥሎ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ታመነ ከርሱም ጋር ብፅዕት እስክንድራ አለች።
❤ ንጉሡም ሰምቶ ተቆጣ ልብሱን አስወልቀው የሴቶች ልብስ አልብሰው ከሚፈትሉ ሴቶች ጋር እንዲጨምሩት ከዚያም የጋለ የብረት መንኰራኵር በላዩ አድርገው ዘቅዝቀው ቊልቊል እንዲሰቅሉት አዘዘ። ሁለተኛም እንዲህ ብሎ አዘዘ "የፈላ ቅጥራን የተመላ ወጭት አምጥታችሁ ወደ ጆሮው እስቲደርስ በራሱ ላይ ድፉበት ደግሞ ከተሰቀለበት አውርደው ከእሥረኛዋ እስክንድራ ጋር በፊቱ እንዲያቆሙት" አዘዘ። ከዚህም በኋላ ምላሱን እንዲቆርጡ አዘዘ በእሊህ ቅዱሳን በአንገቶቻቸው የሚካበዱተጋድሎአቸውንና ድንጊያዎችን አሥረው በኤፍራጥስ ወንዝ ውስጥ እንዲጥሉአቸው አዘዘ። በዚያም ምስክርነታቸውን መጋቢት11 ፈጸሙ ሥጋቸውንም ምእመናን አግኝተው በሥውር ቦታ ቀበሩት። የቅዱስ ቴዎቄጤኖስ በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ባስሊዖስ፦ ይህንንም ቅዱስ የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት አባ አርሞን ከሌሎች ኤጲስቆጶሳት ጋር ሾመው። በታወቀና በተወሰኑ ቦታ ላይ አይደለም። በእምነት በሌላቸው በአረማውያን አገር ይሰብክ ዘንድ ላከው እንጂ።
❤ ይህም ቅዱስ ወደ ከሀድያን አገር ገብቶ የከበረ ወንጌልን ሰበከ። እነርሱም እየደበደቡ በአገራቸው ሁሉ አዞሩት። ደግሞ ወደ ሠርዑና አገርሮች ገብቶ የከበረ የወንጌል ትምህርትን አስተማረ። እኩሌቶቹ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ያላመኑት እኩሌቶቹ ከሀዲያን አስደዱት ከከተማው ውጭ ወጥቶ በዋሻ ውስጥ ተቀመጠ። የዚያች አገር ስዎች እግዚአብሔር ወደ ማወቅ ይመለሱ ዘንድ በአንድ ልጁም ያምኑ ዘንድ ስለዚያች አገር ሰዎች አዘወትሮ እግዚአብሔር ማለደ።
❤ በዚያንም ሰሞን ለእርሱ ለአባቱ አንድ ብቻውን የሆነ የመኰንኑ ልጅ ሞተ። አባቱም ታላቅ ኀዘንን አዘነ መኰንኑ አባቱም በሕልምሙ ልጁን አየው። እርሱም በፊቱ ቁሞ "አባቴ ሆይ እንሆ እኔ በታላቅ ጨለማ ውስጥ ነኝና ወደ ክርሰቶስ ስለ እኔ ይጸልይ ዘንድ ኤጲስቆጶሱ አባ ባስሊዖስን ጠርተህ ለምነው ሲለው ነበር"። ከእንቅልፋም በነቃ ጊዜ ደንግጦ ተነሣ ከእርሱም ጋር የአገር ታላላቆችን ይዞ ወደ ቅዱስ ባስሊዖስ በዓት ሔዶ። ከእርሱ ጋራም ወደ ከተማ ገብቶ ስለ ልጁ እንዲጸልይ ለመነው። እርሱም ልመናውን ተቀብሎ። ወደ ከተማ ገባ በመኰንኑ ልጁ መቃብር ላይም ጸለየ ያንጊዜም የመኰንኑ ልጅ ድኖ በሕዝቡ ሁሉ ፊት ተነሣ መኰንኑ ሕዝቡም ሁሉ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ከአገርም ሰዎች ብዙዎች አምነው የክርስትና ጥምቀትን በቅዱስ ባስሊዖስ እጅ ተጠመቁ በዚያቺም አገር ታላቅ የክርስቲያኖች ጉባኤ ሆነ።
❤ ክፉዎች ሰዎችም ባስሊዖስን ቀንተውበት በጠላትነት ተነሡበት በክርስቶስ ከማያምኑ ጋር ተሰባስበው ወደ ሸንጓቸውም አደረሱት ይህን ቅዱስ ታላቅ ግርፋትን ገረፉት ነፍሱንም በጌታችን እጅ እስከሰጠ ድረስ እያሠቃዩ በዚያች አገር አዋሉት። የቅዱስ ባስሊዖስ በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘላሙ ይሁን አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት11 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለቴዎቄጤኖስ_ዘአድኀኖ°አምተኃጒሎ። ተመትሮ ልሳኑ ኢክህለ ለነቢበ ቃሉ ያብጥሎ። ለእስክንድራ ብፅዕት እንተ ተሳተፈት ገድሎ። ዕብንኒ ዘመኰንን ሰቀሎ። ከመ ልጥረ ፀምር ለክሣዱ ቀሎ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_10።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ፍታሕ ሊተ እግዚኦ እስመ አንሰ በየዋሃትየ (በየውሃትየ) አሐውር። ወተወከልኩ በእግዚአብሔር ከመ ኢይድክም። ፍትነኒ እግዚኦ ወአመክረኒ"። መዝ 25፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 1፥1-6፣ ያዕ 214-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 27፥22-27። የሚነበበው ወንጌል ማቴ18፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ አሌፍ የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፩ (11) ቀን።
❤ እንኳን #ከተስዓቱ_ቅዱስ ለአንዱ ኤርትራ ጠረፍ አካባቢ የሚገኘው ደብረ ብኅዛን (አኅሰአ) ለመሰረቱት #ለአቡነ_አሌፍ_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_አሌፍ፦ ጻድቁ ገድላቸውን የፈጸሙት በኢትዮዽያ ቢሆንም ሃገረ ሙላዳቸው የጥንቱ የሮም ግዛት የሆነችው ታናሽ እስያ ናት። አባ አሌፍ ከዘጠኙ (ተስዓቱ) ቅዱሳን አንዱ ናቸው። ዘጠኙ ቅዱሳን ተወልደው ያደጉት ምንም በአንድ የሮም ግዛት ሥር ቢሆንም መነሻ ቦታቸው ግን የተለያየ ነው።
❤ ሁሉንም አንድ ያደረጋቸው መንፈስ ቅዱስ በኪነ ጥበቡ ነው። በምክንያት ደረጃ እንግለጸው ከተባለ ደግሞ የአንድነታቸው ምሥጢር:-
1.የቀናች ሃይማኖታቸው ተዋሕዶ።
2.ዓላማ (የእግዚአብሔር መንግስት) እና
3.ገዳማዊ ሕይወት ነው።
❤ አባ አሌፍን ጨምሮ ሁሉም ቅዱሳን ዘራቸው ከቤተ መንግስት ነው። እነርሱ ግን ምድራዊውን ክብር ንቀው ሰማያዊውን ክብር ገንዘብ ማድረግን መርጠዋል። አስቀድመው ቅዱሳት መጻሕፍትን ያጠኑት አበው በተለያየ ጊዜ እየመነኑ ከሮም ግዛት ወደ ግብጽ በርሃዎች ወርደዋል።
❤ በምናኔ ቅድሚያውን አባ ዸንጠሌዎንና አቡነ አረጋዊ ይይዛሉ። ዘመኑ የተዋሕዶ አማኞች የሚሰደዱበት 5ኛው መቶ ክ/ዘመን ነበርና እምነትን ላለመለወጥ ዘጠኙ ቅዱሳን ስደትን መረጡ።
❤ በወቅቱ ደግሞ ለስደት መጠለያ የምትሆንና ከኢትዮዽያ የተሻለች ሃገር አልነበረችም። ስለዚህም በ470ዎቹ ዓ.ም አልዓሜዳ በኢትዮዽያ ነግሦ ሳለ ቅዱሳኑ በአረጋዊ መሪነት መጡ።
❤ ንጉሡም ሲጀመር የእግዚአብሔር እንግዳ ስለሆኑ ሲቀጥል ደግሞ ቅድስናቸውን ተመልክቶ መልካም አቀባበልን አደረገላቸው። ማረፊያ ትሆናቸውም ዘንድ አክሱም ውስጥ አንዲት ቦታን ወስኖ ሰጣቸው። ይህች ቦታ ቤተ ቀጢን ትባላለች። አባ አሌፍና 8ቱ ቅዱሳን ወደ ሃገራችን እንደ ገቡ የመጀመሪያ ሥራቸው ቋንቋን መማር ነበር።
❤ ልሳነ ግእዝን በወጉ ተምረው እዛው አክሱም አካባቢ ሥራቸውን አንድ አሉ። በወቅቱ በአቡነ ሰላማ: በአብርሃ ወአጽብሐና በአቡነ ሙሴ ቀዳማዊ የተቀጣጠለው ክርስትና በተወሰነ መንገድ ተቀዛቅዞ ነበርና እነ አባ አሌፍ እንደ ገና አቀጣጠሉት።
❤ ሕዝቡን በራሱ ልሳን ለክርስትና ይነቃቃ ዘንድ ሰበኩት። የካደውን እየመለሱ፤ የቀዘቀዘውን እያሟሟቁ ለዓመታት ወንጌልን ሰበኩ። ቀጣዩ ሥራቸው ደግሞ መጻሕፍትን መተርጐም ሆነ::
❤ ከሃገራቸው ያመጧቸውን ቅዱሳት መጻሕፍት ተከፋፍለው ወደ ግዕዝ ልሳን ተረጐሟቸው። በዚህም ለሃገራችን ትልቁን ውለታ ዋሉ። ይህ ሁሉ ሲሆን እነ አባ አሌፍ የሚመገቡትም ሆነ የሚጸልዩት በማሕበር ነበር። በመካከላቸውም ፍጹም ፍቅር ነበር። ጸጋ እግዚአብሔር አልተለያቸውም::
❤ የነ አባ አሌፍ ቀጣዩ ተግባራቸው ደግሞ ገዳማዊ ሕይወትን ማስፋፋት ሆነ። ይህንን ለማድረግ ግን የግድ መለያየት አስፈለጋቸው። እያንዳንዱም መንፈስ ቅዱስ ወደ መራው ቦታ ሔደ።
*ዸንጠሌዎን በጾማዕት::
*ገሪማ በመደራ::
*ሊቃኖስ በቆናጽል::
*አረጋዊ በዳሞ::
*ጽሕማ በጸድያ::
*ሌሎችም በሌላ ቦታ ገዳማትን መሠረቱ።
*አባ ይምዓታ ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ምርጫቸው ገርዓልታ (እዛው ትግራይ) ሆነ።
❤ አባ አሌፍ የተወለዱት አውሎግሶንና አትናስያ ከተባሉ ደጋግ ወላጆች ቂሳርያ ውስጥ በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው። ጻድቁ በሕጻንነታቸው ወደ አባ እንጦንስ ገዳም ገብተው ከዓመታት ተጋድሎ በሁዋላ ከ8ቱ ጉዋደኞቻቸው ጋር ወደ ኢትዮዽያ የመጡ ሲሆን ከተስዓቱ /9ኙ/ ቅዱሳን አንዱ ናቸው።
❤ በዐፄ አልዓሜዳ ዘመን አክሱም አካባቢ (ቤተ ቀጢን) የሃገራችንን ቋንቋ አጥንተው ቅዱሳት መጻሕፍትን ተርጉመዋል። ለሕዝቡም የወንጌልን የምሥራች ሠብከዋል።
❤ ከዚያም ገዳም መሥርተው፤ 500 መነኰሳትን ሰብስበው ለ70 ዓመታት በቅድስና ኑረዋል። ለዘጠኙ ቅዱሳን ሁሉ ስም ያወጡት የዘመኑ ሰዎች ቀድመው ወደ አክሱም ስለ ገቡ ጻድቁን "አሌፍ" ብለዋቸዋል። በዕብራይስጥኛ "አንደኛ" ማለት ነው። ጻድቁ ከፈጣሪያቸው የምሕረት ቃል ኪዳን ተቀብለው በዚሕች ቀን አርፈዋል። ከአባታችን ከአቡነ አሌፍ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ዝክረ ቅዱሳን ዘተዋሕዶ ከዲያቆን ዮርዳኖስ መጽሐፍ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲ (10) ቀን።
❤ እንኳን #ለክብር_ባለቤት_ለጌታችን_ለአምላካችን_ለመድኃኒታችን_ለኢየሱስ_ክርሰቶስ_ለመስቀሉ_በንግሥት_ዕሌኒ አማካኝነት ተቆፋሮ ለተገኘበት፣ በድጋሚ በፋርሶች ከኢየሩሳሌም ተወስዶ እንደገና #በሮሜው_ንጉሥ_ሕርቃል ለተገኘበት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የቅዱስ_መስቀሉ_መገኘት_ታሪክ፦ የዚህም የከበረ ዕፀ መስቀል መገለጡና መገኘቱ ሁለት ጊዜ ሁኖአል። መጀመርሪያ የጻድቁ ንጉሥ የቈስጠንጢኖስ እናት በሆነች በንግሥት ዕሌኒ እጅ ነው። እርሷ ለእግዚአብሔር ተስላ ነበርና ልጅዋ ቈስጠንጢኖስ ወደ ክርሰቲያን ሃይማኖት ቢገባ ወደ ኢየሩሳሌም ሒዳ መስቀሉን እስከ አገኘችው ድረስ ልትፈልገው በኢየሩሳሌምም ያሉ ቅዱሳን መካናትንና አብያተ ክርስያናትን ልታንፃቸው ነው።
❤ ከዚህ በኋላ ልጅዋ አምኖ የክርስትና ጥምቀትን በተጠመቀ ጊዜ ዕሌኒ ቅድስት ወደ ኢየሩሳሌም ሔደች ከእስዋ ጋራም ብዙ ሠራዊት ነበር ደርሳም ስለ ከበረ መስቀል መረመረች ቦታውንም የሚአስረዳት አላገኘችም የአይሁድ ወገን የሆነ ሽማግሌ ሰው አሥራ በረኃብና በጥማት አስጨነቀችው። በተጨነቀም ጊዜ ለንግሥት ዕለኒ የጎልጎታን ኮረብታ አስጠርጊ ብሎ ነገራት እርሷም ይጠርጉ ዘንድ አይሁድን አዘዘቻቸው። ቤቱን የሚጠርግ ሰው ሁሉ ጥራጊውን በውስጡ የከበረ መስቀል በአለበት በጌታችን መቃብር ላይ እንዲጥል አይሁድ አስቀድመው አዝዘው ነበርና ንግሥት ዕሌኒ እስከ ደረሰችበት ጊዜ ከሁለት መቶ ዓመት በላይ ጥራጊያቸውን ሲጥሉበት ኖሩ ኮረብታም ሆነ።
❤ አይሁድም በጠረጉ ጊዜ ሦስት መስቀሎች ተገለጡ የክቡር ባለቤት ክርሰቶስ የተሰቀለበት የትኛው እንደሆነ አላወቁም። የሞተ ሰውም አግኝተው አመጡ። አንዱንም መስቀል አምጥተው በሞተው ሰው ላይ አኖሩት አልተነሣም ደግሞ ሌላውን መስቀል አምጥተው በሙቱ ላይ አኖሩ አሁንም አልተነሣም ከዚህም በኋላ ሦስተኛውን መስቀል አምጥተው በሙቱ ላይ አደረጉት ያንጊዜ የሞተው ሰው ተነሣ ዕሌኒም የክርስቶስ መስቀል እንደሆነ አውቃ ሰገደችለት የክርስያንም ወገኖች ሁሉ ሰገዱለት። ለልጅዋ የላከችው ይህ መስቀል ነው የሚል መጽሐፍ ይገኛል የቀረው ግን ግንዱ በውስጡ ተተክሎበት የነበረው ከእርሱም እኩሌታውን ከቅንዋቱ ጋር ወደ ልጅዋ የላከችው ነው።
❤ ከዚህም በኋላ ሥርዓታቸውና የሕንፃቸው ነገር በመስከረም ወር በዐሥራ ሰባት ተጽፎ የሚገኝ አብያተ ክርስያናትንና የከበሩ ቦታዎችን አነፀች።
✝ ✝ ✝
❤ #ሁለተኛው_በሮሜ_ንጉሥ_በሕርቃል_ዘመን የሆነው ሲሆን የፋርስ ሰዎች በግብጽ አገር ሳሉ ወደ አገራቸው ሊመለሱ ወደዱ። ከሹማምንቶቻቸው አንዱ የጦር መኰንን ተነጥሎ ወደ ኢየሩሳሌም አልፎ ደረሰ ወደ ከበረ መስቀል ቤተ ክርስቲያንም ገባ። መስቀሉም በላዩ በተተከለበት ግንድ ፊት ታላቅ ብርሃን ሲበራ አይቶ ሊያነሣው እጁን ዘረጋ። እሳትም ወጥታ እጁን አቃጠለችው።
❤ ከክርስቲያን በቀር ማንም ሊነካው እንማይችል የመስቀልን የክብሩን ነገር ሰዎች ነገሩት። ሁለት ዲያቆናትንም ይዞ የከበረ መስቀልን እንዲሸከሙ አዘዛቸው። ከኢየሩሳሌምም ብዙ ሰዎችን ማርኮ ወደ አገሩ ተመለሰ።
❤ የፋርስ ሰዎች ኢየሩሳሌምን እንዳጠፏት ብዙዎች ሰዎችንም እንደማረኩና የከበረ የክርስቶስንም መስቀሉን እንደ ወሰዱ የሮም ንጉሥ ሕርቃል በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ። ስለርሱም እንዲጾሙ ምእመናንን አዝዞ ወደ ፋርስ ዘምቶ ወጋቸው ብዙዎችንም ገደላቸው የከበረ ዕፀ መስቀልንም እየፈለገ በአገራቸው ሁሉ ዞረ ግን አላገኘውም።
❤ ያ ዲያቆናቱንና መስቀሉን የወሰደ መኰንን ከቦታዎች በቤቱ አንጻር ባለ በአንድ ቦታ ላይ ወስዷቸው ጥልቅ ጉድጓድ እንዲቆፍሩ አዝዞ በዚያ የከበረ መስቀልን አስቀበረ እነዚያንም ዲያቆናት ገደላቸው። ነገር ግን ያ መኰንን የማረካት የካህናት ወገን የሆነች በእርሱ ቤት የምትኖር አንዲት ብላቴና ነበረች። እርሷ የከበረ መስቀልን ሲያስቀብርና ሁለቱን ዲያቆናት ሲገድላቸው በቤቱ ውስጥ ሁና በመስኮት ትመለከት ነበር ወደ ንጉሥ ሕርቃልም ሒዳ መኰንኑ ያደረገውን ሁሉ ነገረችው። ይህንም ንጉሥ ሰምቶ እጅግ ደስ አለው ያቺ ብላቴናም መራችው ከእርሱም ጋር ብዙ ሠራዊት ሁኖ ኤጲስቆጶሳትና ካህናትም ነበሩ። ወደ ቦታውም እስከምታደርሳቸው ያቺን ልጅ ተከተሏት ቆፍረውም የከበረ ዕፀ መስቀልን አገኙ ከዐዘቅቱም አወጡት ንጉሡና ሠራዊቱም ሰገዱለት። በልብስ መንግሥቱም አጐናጸፈው ታላቅ ክብርንም አከበረው እጅግም ደስ አለው ከሠራዊቱ ጋር።
❤ የዚህም መስቀል ሁለተኛ የተገለጠበትና የተገኘበት በዚች ቀን በመጋቢት ዐሥር ነው። ከዚህ በኋላ ንጉሡ የከበረ ዕፀ መስቀልን ተሸክሞ ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ ወሰደው። የመድኃኒታችን የመስቀሉ በረከት ከሁላችን የክርስቲያን ወገንኖች ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት 10 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥1-17።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወወሀብኮሙ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ። ከመ ያምሥጡ እምገጸ ቅስት። ወይድኀኑ ፍቁራኒከ"። መዝ 59፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 6፥1-ፍ.ም፣ ያዕ 4፥1-11 እና የሐዋ ሥራ 24፥1-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 16፥24-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቅዳሴ ነው። መልካም የመስቀለ ኢየሱስ በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲ (10) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያ_ጻድቅ ታላቁን ዲማ ጊዮርጊስን ለመሠረቱ #አቡነ_ተከስተ_ብርሃን_ዘደብረ_ድማኅ ለዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ተከስተ_ብርሃን፦ ትውልድ ቦታቸው መንዝ ከሚባለው አገር ነው። ይህች መንዝ የምትባለው አገር የምትገኘው በአገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ በተለየች በደብረ ብርሃን አውራጃ ውስጥ ነው። መንዝ ማለትም ነዝሀ ከሚለው ከግእዝ ቃል የተገኘ ነው። መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል እግዚአብሔር በሰጠው (በፈቀደለት) ስልጣን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳም በሰጠው ተስፋ በተወለደ በ33 ዓመት ከ3 ወር ወንጌልን አስተምሮ ለድኅነተ ዓለም መጋቢት 27 ቀን በዕለተ አርብ በተሰቀለ ጊዜ የፈሰሰ ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃን መነሳንስ ዓለምን ሲረጭ አስቀድሞ ይችን መንዝ የምትባልን አገር ከሁሉ አስቀድሞ ስለረጫት ደመ መለኮቱን እንደ አውድማ ስለለቀለቀው በዚህ ምክንያት መንዝ ተብላለች።
❤ በዚች ቦታ ብዙ ቅዱሳን ተፀንሰው ተወልደውባታል። ከነዚህም ቅዱሳን በአካባቢውና በዚች ቦታ የተወለዱ እነ ቅዱስ ፊልጶስ፣ እነ ቅዱስ አኖሬዎስ፣ እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፣ እነ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ እርሷ የመሰሉ ብዙዎች ቅዱሳን ተፀንሰው ተወልደው አድገውበታል። ይህች ቦታም የተባረከች የተቀደሰች መሆኗ ቅዱስ አባታች ተፀንሰው እዲወለዱ አድርጋለች።
❤ እኚህ አባታችን አቡነ ተከስተ ብርሃን የመጀመርያ ስማቸው አባ በኪሞስ ይባላል። እኚህ አባ በኪሞስ ከመንዝ መንኖ ደብረ ሊባኖስ ሲረዱ ቆይቶ ወደ ጎጃም ክፍለ ሀገር በ12ኛው ክፍለ ዘመን በአምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት እንደ መጡ ገድላቸው ይናገራል። መጥተውም የተቀመጡበት ቦታ ቢቸና አውራጃ ድማ ጊዮርጊስ ነው። ከዚያም አባታቸው አቡነ ፊልጶስ ወደ ትግራይ ሲሰደዱ እሳቸውም ተሰደው ብዙ ጊዜ ከቆዩ በኋላ መምህራቸው አቡነ ፊልጶስ "ወደጎጃም ክፍለ አገር ሂደህ አስተምር" አሉት።
❤ ከዚያ ተነስተው በግሸና አድርገው የዐባይ ባሕር ተከፍሎላቸው ወደ ጎጃም ክፍለ አገር ተሻግረው አስተምረው በአንድ ቀን ዘጠኝ ሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና ዘጠኝ (9999) ምዕመናንን ሲያጠምቁ አምደ ብርሃን ተተክሎ እያበራ ከዚያች ቦታ ስለታየ በኪሞስ ይባል የነበረ ስማቸው ተከስተ ብርሃን ተባሉ። ወንዚቱም እሳት ዙሪያዋን ስለከበባት ነድ ሐጸረ ተብላ ዛሬም ነድ አጥራ እየተባለች ትጠራለች። ከዚህ ተነስተው ወደ ቢቸና አውራጃ እነማይ ወረዳ ውስጥ አንድ ጫካ አገኘ። ከዚያም የያዙትን ታቦት በአንድ ዋሻ አኑረው። ስሟንም ዲማ ማርያም አሏት።
❤ ከዚህ በኋላ ተነስተው ገድ ወንዝ ላይ የነበረችቱን ብዙ ሕዝቦች ይሰግዱላት ያመልኳት የነበረችቱን ሙላድን ከዚያ አባረው ሰኔ 21 ቀን አገው ምድር እንጁባራ ላይ አድርሰዋት ተመልሰው ሲመጡ ዐባይን ተሻግረው ጉታ ሲደርሱ ከዚህ ናዳ ማርያም ገዳም ዐርፈው እንደሄዱ ገድላቸው ይናገራል። ከዚያ ተነስተውም ወደ ዲማ ሂደዋል። ከዚያም ድማ ማርያም የምትባል ተክለዋል። ድማ ማለት በኦሮምኛ ቋንቋ ቀይቱ ማርያም ማለት ነው።
❤ ከዚያም የወንዶችና የሴቶች ገዳም አቋቁመው ብዙ ጊዜ ከቆዩ በኋላ መጋቢት 9 ቀን ታመው ብዙ ቃል ኪዳን ተቀብለው ስምህን የጠራ፣ በዓልህን ያከበረ፣ ዝክር የዘከረ እስከ 22 ኛው ትውልድ እምርልህለሁ ብሎ ቃል ኪዳን ከሰጣቸው በኋላ መጋቢት 10 ቀን ዐርፈዋል። በዚያው ባቋቋሙት በድማ ማርያም ተቀብረዋል። ከአባታች አቡነ ተከስተ ብሃርሃን እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን! ምንጭ፦ ከገድለ አቡነ ተከስተ ብርሃን መቅድም።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_አንገርጋሪ_ግእዝ_ዜማ፦ ሃሌ ሉያ "#ወአንቲኒ_ቀራንዮ_መካነ_ጎልጎታ እስመ በኀቤኪ ተቀብረ #ኢየሱስ_ክርስቶስ ህየ ህየ ህየ ንሰግድ ኲልነ #ኀበ_ቆመ_እግረ_እግዚእነ ኀበ ተረግዘ ገቦሁ #ዮም_በዓለ_መስቀሉ"። ትርጉም፦ #የጎልጎታ_ቦታ #አንቺ_ቀራንዮ_ባንቺ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ተቀብሯልና፤ በዚያም #የጌታችን_እግር_ወደቆመበት፤ ጎኑ ወደ ተወጋበት ኹላችን እንሰግዳለን፤ #ዛሬ_የመስቀሉ_በዓል_ነው።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ__እግ_ነግ_ዓራራይ_ዜማ፦ "ይሰማዕ ሰማይ ወጽታምእ ምድር ወይትፌሥሑ #ተዓይነ_መላእክት_እስመ_ተረክበ_ዮም_ዕፀ_መስቀል_በዕደ_ዕሌኒ_ንግሥት"። ትርጉም፦ ሰማይ ይስማ ምድር ታድምጥ #የመላእክት_ከተሞች_ይደሰቱ፤ #ዛሬ_ዕፀ_መስቀል_በንግሥት_ዕሌኒ_አማካኝነት_ተገኝቷልና። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_ በድጓው_ላይ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። ❤
❤ #መጋቢት ፱ (9) ቀን።
❤ እንኳን #ለከበረ_ተጋዳይ_ለሆነ_ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገልጦ በጌታችን ማመን ላስተማለው በሐዋርያት እጅ ለተጠመቀ፤ ወላጆቹን በሚያደርገው ተዓምራት ላሳመነ፤ የጣዖት አምልኮን ላጠፋና ሰይጣንን ድል ላደረገ #ለጽኑ_አባት_ለአባ_ኩትን ለዕረፍት በዓል፣ ለከበሩ #ቅዱሳን_ለእድርያኖስና_ለሚስቱ፣
#አውሳብዮስና_አርማ_ሌሎች_አርባ_ሰዎችም ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከአባ_ኖብ ጋር በሰማዕትነት ከዐረፉ #ከሁለት_ሺህ_ሰዎች ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ኩትን፦ እርሱም በሶርያ አገር ስሟ በንጣንዮስ ከምትባል ቦታ የሚኖር ነው። አባቶቹም ከዋክብትን ያመልኩ ነበር የአባቱ ስም ንስጣር የእናቱም ስምp iቴዎድራ ይባላል። በአደገ ጊዜም ወላጆቹ ሊያጋቡት ፈለጉ እርሱ ግን አልወደደም ግድ ብለው ያለ ውዴታው ሚስትን አጋቡት ሊገናኛትም አልፈለገም ስለ ሥጋ ድካም ወይም ስለ ጽድቅ ሳይሆን የሥጋ ፍትወትን ስለሚጠላት ነው እንጂ። ደናግልም እንደሆኑ ሁለቱ ሁሉ ከሚስቱ ጋር በአንድነት ኖረ።
❤ "አምላክ ሆይ ወደ ዕውቀትህ ምራኝ" በማለት ጸሎትና ምልጃን ያዘወትር ነበር። ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለቆርኔሌዎስ እንደተገለጠ ተገለጦ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን አስተማረው ከሐዋርያትም ወደ አንዱ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቅ አዘዘው። የሐዋርያት የስብከታቸው ወራት ነበርና ሒዶ ተጠመቀ የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት ሁሉ ሕጉን ሥርዓቱንም ሁሉ ተማረ መለኮታዊ ምስጢርንም ተቀበለ። በየቀኑ ሁሉ የሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስን ትምህርት ይሰማ ነበር። የጽድቅን ሥራ መሥራትና ንጽሕና፣ ለበጎ ሥራ መጠመድ ትጋት፣ ቅንነት፣ የዋህነት፣ ጾም፣ ጸሎትና ሰጊድ በላዩ ተጨመረ። በእነዚህ ሁሉ የሚተጋ ሆነ እግዚአብሔርም አስደናቂ ተአምራቶችን እንዲያደርግ በርኵሳን አጋንንት ሥልጣንን ሰጠው።
❤ በሚያደርገው ተአምራትም ወላጆቹን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ማመን ስቦ አስገባቸው ደግሞ ሚስቱንና ወላጆቿን አሰገባቸው። ከከሀድያን አንዱ ለሰይጣን ሊሠዋ ወደ ጣዖቱ ቤት በገባ ጊዜ ቅዱስ ኩትን አውቆ በሰይጣን ላይ ጮኸ እርሱ ሰይጣን እንጂ አምላክ እንዳልሆነ በሰው ፊት ያምን ዘንድ አዘዘው። ሰይጣንም እንዳዘዘው ራሱን ገለጠ በዚያ የነበሩ ሁሉም "የቅዱሰ ኩትን አምላክ አንድ እርሱ ብቻ ነው" እያሉ ጮኹ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ።
❤ ከዚህ በኋላ ከቀላውዴዎስ ቄሣር የተላከ መኰንን የቅዱስ ኩትንን ዜናውን በሰማ ጊዜ ወታደር ልኮ አስቀረበው ስለ ሥራውም ጠየቀው እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ መኰንኑም ጽኑ ግርፋት ገርፈው እንዲሥሩት አዘዘ ይህንንም አደረጉበት።
❤ የአገር ሰዎችም ቅዱስ ኩትንን አሠቃይተው እንዳሠሩት በሰሙ ጊዜ ሁሉም ወደርሱ ተራወጡ መኰንኑንም ሊገሉት ወደዱ መኰንኑም ሸሸ። ቅዱስ ኩትንንም ከማሠሪያው ፈትተው ከደሙም አጥበው ተሸክመው ወደቤቱ ወሰዱት ከዚህም በኋላ ብዙ ዘመናት ኑሮ የወደደው እግዚአብሔርን አገልግሎ ደስ አሰኝቶ በፍቅር አንድነት መጋቢት 9 ቀን ዐረፈ።
❤ ከዕረፍቱም በኋላ ቤቱን ቤተ ክርስቲያን አድርገው ሥጋውን በውስጥዋ አኖሩ ጌታችንም ከሥጋው ብዙዎች ታላላቅ ተአምራቶችን አሳየ። አባ ኩትን በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘላለሙ ትሁን አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የከበሩ_ቅዱሳን_እድርያኖስና_ሚስቱ፣ #አውሳብዮስና_አርማ_ሌሎች_አርባ_ሰዎችም_ሰማዕትነት፦ እሊህንም ምርጦች ለረከሰ ከወርቅና ከብር ለተሠራ ጣዖት ማምለክን እምቢ ስላሉ የክብር ባለቤት ለሆነ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለስሙ ዐላውያን ጽኑ የሆነ ሥቃይን አሠቃዩአቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ራሶቻቸውን መጋቢት 9 ቀን በሰይፍ ቆረጡ የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ምንጭ፦የመጋቢት 9 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለኩትን_በእደ_ሐዋርያት_ዘተጠምቀ። እመልአከ ሰማይ ትምርተ ከመ ተጠየቀ። ሶበ አገበርዎ እንተ ሕሊናሁ ኢጽሕቀ። በፍትወተ ሥጋ ኢተሞዐ ወበሥምረቱ ኢወድቀ። ምስለ ብእሲቱ ሰኪቦ ዘአኮ ርኁቀ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_9።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ፈሪሃ እግዚአብሔር እምሀርክሙ። መኑ ውእቱ ብእሲ ዘይፈቅድ ሐይወ። ወያፈቅር ይርአይ መዋዕለ ሠናያት"። መዝ 33፥11-12። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 1፥1-11፣ ያዕ 2፥1-14 እና የሐዋ ሥራ 4፥13-19። የሚነበበው ወንጌል ማር 1፥23-29። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ቄርሎስ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ወራትና በዓል። በሁላችንም ይሁንልን።
