ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Открыть в Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Больше638
Подписчики
-224 часа
-57 дней
-1130 день
Архив постов
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሰኔ ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው #የጌታችን_ወንድም_ለተባለው ለፀራቢው ለዮሴፍ ልጅ #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ይሁዳ_ለዕረፍት_በዐል፣ ለእስክድርያ አርባ አራተኛ ሊቀ ጳጳስ #ለአባ_ጴጥሮስ ለዕረፍት በዓልና #ለክረምት_መግቢያ_ቀን በሰላም አደረሰን። ከእነዚህ ቅዱሳን እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅዱስ_ይሁዳ፦ ይህም ቅዱስ ቁጥሩ ከሰባ ሁለቱ እርድእት የሆና የፀራቢው የዮሴፍ ልጅ የጌታችን ወንድም የተባለ ነው። ይህም ሐዋርያ በብዙ አገሮች ሰበከ ወደ አንዲት ደሴትም ገብቶ በውስጧም ሰበከ ሰዎቿንም በጌታ አሳመናቸው ቤተ ክርስቲያንም ሠራላቸው በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው።
❤ ከዚህም ወደ ሮሃ አገር ሒዶ የሮሃ ንጉሥ አውጋንዮስን ከደዌው ፈወሰው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቀው ከዚያም ደግሞ ሐራፒ ወደሚባል አገር ሒዶ በውስጧ ሰበከ ከሰዎቿ ብዙዎቹን አጠመቃቸው ቤተ ክርስቲያንም ሠራላቸው። የዚያችም አገር ገዥ ይዞ ጽኑዕ ሥቃይ አሠቃየው ችንካር ያለው ጫማ በእግሮቹ ውስጥ አድርጎ አንድ ምዕራፍ ያህል አስሮጠው ከዚህም በኋላ ሰቅሎ በፍላፃ ነደፈው ክብር ይግባውና በጌታችን እጅ ነፍሱን ሰጠ።
❤ ከመከረውም አስቀድሞ ለምእመናን መልእክት ጽፎ ላከ እርሷም ከሐዋርያት መልእክቶች ሰባተኛ የሆነች ምሥጢርን የተመላች ናት በእርሷም ብዙዎች አረማውያንን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን አስገባቸው። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ይሁዳ በጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #አባ_ጴጥሮስ፦ ይህም አባት ለእስክንድር ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ አራተኛ የሆነ ነው። ከመሾሙ በፊት የማርቆስ መንበር ያለ ጳጳሳት ለብዙ ዘመናት ኖረ የእስላሞች ንጉሥና መኳንንቶቹ አልፈቀዱላቸውም ነበርና።
❤ ከዚህም በኋላ ሃይማኖቱ የቀና ደግ መኰንን በእስክንድርያ ከተማ ላይ ተሾመ ያንጊዜም የአገር ሽማግሌዎች ወደ ርሱ ተሰብስበው ሊቀ ጳጳሳት እንደ ሌላቸው ኀዘናቸውን ነገሩት። እርሱም ደብረ ማሕው ወደሚባለው ወደ ደብረ ዝጋግ ወጥተው እንዲጸልዩ ለራሳቸውም ሊቀ ጳጳሳት እንዲሾሙ አዘዛቸው። በዚህም ነገር ደስ ብሏቸው ቀሲስ አባ ጴጥሮስን ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት በእርሱም ደስ አላቸው።
❤ በዚያም ወራት የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሳዊሮስ ሞተ የአንጾኪያ አገርም ያለ ሊቀ ጳጳሳት ትኖር ነበር የአንጾኪያ ምእመናንም ለእስክንድርያ ከተማ አባ ጴጥሮስ እንደ ተሾመ በሰሙ ጊዜ እነርሱም የተማረ ደግ ሰው ለአንጾኪያ ሾሙ ስሙም ታውፋንዮስ ይባል ነበር። እርሱም ስለ ቀናች ሃይማኖት በመልእክቶቻቸው ይገናኙ ነበር። ከእርሱም እያንዳንዱ በባልንጀራው ምክር በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜ ይሰብክ ነበር ወደ አገራቸውም መግባት አልተቻላቸውም ነበርና አባ ጴጥሮስም በግብጽ ደቡብ በአንባንያ ገዳምና በዝጋግ ገዳም ይኖር ነበር አባ ታውፋንዮስም ከአንጾኪያ ከተማ ውጭ በአፍቆንያስ ገዳም ይኖር ነበር።
❤ በዚያም ወራት ከእስክንድርያ ከተማ ውጭ ሰባት መቶ ገዳማትና ሃይማኖታቸው የቀና ምእመናንም ያሉባቸው ሠላሳ ሁለት መንደሮች ነበሩ በግብጽ አውራጃ ሁሉና በላይኛው ገብጽ በአስቄጥስ ገዳማት የሚኖሩ መነኰሳት እንዲሁም ኖባና ኢትዮጵያ በዚህ በአባ ጴጥሮስ ሥልጣን ሥር ነበሩ። እኒህ ሁሉ ሃይማኖታቸው የቀና ነበር። በትእዛዙም ጸንተው ይኖሩ ነበር። እርሱም በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ወደእርሳቸው መልእክቶችን መጻፍ አያቋርጥም ነበር።
❤ የእስክንድርያን ገዳማት ሁሉና መንደሮችንም እየዞረ ያስተምራቸውና ይመክራቸው ያጽናናቸውም ነበር። ከእርሱ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስና ዐዋቂ የሆነ ደቀ መዝሙር የነበረው እርሱም ሊቀ ጵጵስናው ሥራ ሁሉ ይራዳው ነበር።
❤ ይህም አባት ጴጥሮስ አንዳንድ ጊዜ ወደ እስክንድርያ ከተማ ይገባ ነበር የሰዎቿንም ሥራቸውን ተመልክቶ ያስተምራቸውና በሃይማኖት ያጸናቸው ነበር። በዐሥራ ሁለት ዓመት የሹመቱ ዘመን እንደ ሐዋርያት መንጋዎቹን እየጠበቀ እንዲህ በሹመቱ ኑሮ ሰኔ 25 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ጴጥሮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 25 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦"ወአንተ ገበርከ አድባረ ወምድረ ኵሎ። ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ። ወተዘከር ዘንተ ተግባረከ"። መዝ 73፥17-18። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 6፥7-13፣ ይሁ 1፥1-7 እና የሐዋ ሥራ 14፥16-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 14፥18-27። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ይሁዳ የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሰኔ ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ አስቀድሞ ገዳይ ቀማኛ፣ ዘማዊና ያላመኑ ለነበሩ በንስሐ ተመልሰው በአባ መቃርስ እጅ ከተጠመቁ ከመነኰሱ በኋላ በግብፅ በአስቆጥስ ገዳም ታላቅ ተጋድሎ አድርገው በሰማዕነት ለዐረፉ #ለአባ_ሙሴ_ጸሊም_ለዕረፍቱ በዓል መታሰቢያ፣ ለአባታችን ለአቡነ ተክለ ሃይማኖትና ለእናታች ለቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ለወራዊ መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #አባ_ሙሴ_ጸሊም፦ ሰዎች ከገድሉ የተነሣ ይህን ቅዱስ ያደንቁታል እርሱ አስቀድሞ መንግሥተ ሰማያትን ገፍቷት ነበርና እርሱ በሥጋው ጠንካራ በሥራውም ኃይለኛ ነበር ይበላና ይጠጣ፣ ይቀማና ያመነዝር ነበር ይገድልም ነበር ማንም ሊቋቋመው አይችልም ነበር። አንድ በግ በአንድ ጊዜ ጨርሶ እንደሚበላና አንድ ፊቀን ወይን ጠጅ እንደ ሚጠጣ ስለ እርሱ ተነግሮአል። እርሱም ፀሐይን ለሚያመልኩ ሰዎች አገልጋይ ነበር ብዙ ጊዜም ወደ ፀሐይ እያንጋጠጠ "ፀሐይ ሆይ አንተ አምላክ ከሆንክ አነጋግረኝ" ይል ነበር ደግሞም በልቡ "የማላውቅህ ሆይ ራስህን አሳውቀኝ" ይል ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ በአስቄጥስ ገዳም ያሉ መነኰሳት እግዚአብሔርን ያውቁታል ያዩታልም እያሉ ሲነጋገሩ ሰዎችን ሰማቸው። ያን ጊዜም ተነሣ ሰይፉንም ታጥቆ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ በደረሰም ጊዜ አባ ኤስድሮስን አገኘው። አባ ኤስድሮስም ፈራው ሙሴ ጸሊምም "እውነተኛውን አምላክ ታሳውቁኝና ታስረዱኝ ዘንድ ወደ እናንተ መጣሁ" አለው። አባ ኤስድሮስም ወደ አባ መቃርስ ወስዶ አገናኘው። እርሱም ተቀብሎ ሃይማኖትን አስተማረው እንዲለህም አለው "ታግሠህ የማስተምርህን ከጠበቅህ እግዚአብሔርን ታየዋለህ።
❤ ከዚህም በኋላ የክርስትና ጥምቀትን አጥምቆ አመነኰሰው ከብዙዎች ገድለኞች ቅዱሳን ይልቅ ብዙና ጽኑዕ ገድልን መጋደል ጀመረ። ሰይጣንም ቀድሞ ሲሠራው በነበረ በመብሉና በመጠጡ መዝሙቱም ይዋጋው ነበረ እርሱም በራሱ ላይ የሚደርስበትን ሁሉ ለአባ ኤስድሮስ ይነግረው ነበር እርሱም አጽናንቶ ሊሠራው የሚገባውን ያስተምረው ነበር።
❤ ከገድሉ ብዛትም የተነሣ አረጋውያን መነኰሳት በሚተኙ ጊዜ ቤቶቻቸውን በመዞር ውኃ መቅጃዎችን ወስዶ ውኃ መልቶ በየቤታቸው ደጃፍ ያኖር ነበር። ውኃው ከእርሱ ሩቅ ነበረና እንዲም እያደረገ በመጋደል በብዙ ዘመናት ኖረ። ሰይጣንም በእርሱ ቀንቶ በእግሩ ውስጥ አስጨናቂ የሆነ አመታትን መታው ተኝቶም እየተጨነቀ ብዙ ቀን ታመመ።
❤ ከዚህም በኋላ የመታውና የሚፈታተነው ሰይጣን እንደሆነ ዐውቆ ሥጋው በእሳት ተለብልቦ እንደ ደረቀ ዕንጨት እስቲሆን ድረስ ተጋድሎውንና አገልግሎቱን አበዛ። እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ ከደዌው ፈወሰው የሰይጣንንም ጦር ከእርሱ አራቀለት የመንፈስም ጸጋ አደረበት ወደርሱም አምስት መቶ ወንድሞች መነኰሳት ተሰበሰቡ በእነርሱም ላይ አበ ምኔት ሆነ።
❤ ከዚህም በኋላ ቅስና ሊሾሙት መረጡት በቤተ መቅደስም ሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ በአቆሙት ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱም አልፈቀደም ነበር አረጋውያኑንም "ይህን ጠቋራ ለምን አመጣችሁት ከዚህ አውጡት" አላቸው እነርሱም "መልክህ የከፋ ጠቋራ ሆይ መካም አደረጉብህ" በማለት ራሱን እየገሠጸ ወጣ ከዚህ በኋላ ዳግመኛ ሊቀ ጳጳሳቱ ጠራውና እጁን በላዩ ጭኖ ቅስና ሾመው እንዲህም አለው "ሙሴ ሆይ እነሆ በውስጥም በውጭም ሁለመናህ ነጭ ሆነ"።
❤ በአንዲትም ዕለት ቅዱሳን አረጋውያን ወደርሱ መጡ በእርሱም ዘንድ ውኃ አልነበረም እርሱም ከበዓቱ ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ይል ነበር ከዚህም በኋላም ብዙ ዝናም ዘንሞ ጒድጓዶችን ሁሉ ሞላ። አረጋውያንም ለምን ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ትል ነበር ብለው ጠየቁት እርሱም "እግዚአብሔርን ውኃ ካልሰጠኸኝ ቅዱሳን አገልጋዮችህን ምን አጠጣቸዋለሁ እለው ነበር በቸርነቱም ዝናምን ልኮልን ውኃን አገኘን" አላቸው።
❤ በአንዲት ዕለት አባ ሙሴ ከአረጋውያን ጋር ወደ አባ መቃርስ ሔደ አባ መቃርስም የሰማዕትነት አክሊል ያለው ከእናንተ ውስጥ አንዱን እነሆ አያለሁ" አላቸው አባ ሙሴም "አባቴ ሆይ ምናልባት እኔ እሆናለሁ በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደል ዘንድ አለው የሚል ጽሑፍ አለና" ብሎ መለሰ።
❤ ከዚህም በኋላ የበርበር ሰዎች መጡ አባ ሙሴም ከእርሱ ጋራ ያሉትን መነኰሳት "እነሆ የበርበር ሰዎች ደረሱ መሸሽ የሚፈልግ ይሽሽ" አላቸው እነርሱም "አባታችን አንተስ አትሸሽምን" አሉት እርሱም "በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደላል ስለ ሚለው የእግዚአብሔር ቃል እነሆ ያቺን ቀን ለብዙ ዘመናት ስጠብቃት ኖሬአለሁ" አላቸው። ወዲያውኑም የበርበር ሰዎች ገብተው በሰይፍ ገደሉት መሸሽ ስለ አልፈለጉ ከእርሱ ጋር ሰባት መነኰሳትም ተገደሉ አንዱ ግን ከምንጣፍ ውስጥ ተሠወረ የእግዚአብሔርንም መላአክ አየ በእጁም አክሊል ነበር እርሱም ቆሞ ይጠብቅ ነበር። ይህንንም በአየ ጊዜ ከተሠወረበት ወጣ የበርበር ሰዎችም ገደሉት የሰማዕታትንም አክሊል ተቀበለ።
❤ ወንድሞች ሆይ ከሀዲና ነፍሰ ገዳይ ቀማኛና ዘማዊ የነበረውን ለውጣ ደግ አባት መምህርና የሚያጽናና ለመነኰሳትም ሥርዓትን የሠራ ካህን እንዳደረገችው በሁሉም አብያተ ክርስቲያን ስሙ እንዲጠራ እንዳደረገችው የንስሐን ኃይሏን ተመልከቱ።
❤ ሥጋው በአስቄጥስ ገዳም ደርምስ በተባለ ቦታ ለዘላለም ይኖራል ከእርሱም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ይታያሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ሙሴ ጸሊም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 24 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ኃጢአትየ ነገርኩ ወአበሳየ ኢኀባዕኩ። ወእቤ አስተዋዲ ርእስየ ኀበ እግዚአብሔር በእንተ ኃጢአትየ። ወአንተ ኅድግ ጽልሑቶ ለልብየ"። መዝ 31፥5። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 10፥46-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 1፥4-ፍ.ም፣ የሐዋ ሥራ 14፥1-7። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 12፥20-27። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ሙሴ ጸሊም የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ ሁላችንም ይሁንልን።
ነበር። ወደ ንጉሡ ከተማም በደረሱ ጊዜ ወደ ንጉሡ ከመግባታቸው በፊት በውኃ ያጥቧቸውና አዳዲስ ልብሶችን ያለብሷቸው ጀመሩ እንዲሁም ለሁሉ አደረጉ ቅዱስ አባ ኖብ ግን አልታጠበም ልብሱንም አልለወጠም።
❤ ወደ ንጉሡም በገቡ ጊዜ ከእነርሱ ቡራኬ ተቀበለ ቁስላቸውንም ሳመ እጅግም አከበራቸው ብዙ ገንዘብም ሰጣቸው እነርሱ ግን ለቤተ ክርስቲያን ከሚሆን ንዋየ ቅዱሳት በቀር ምንም ምን አልተቀበሉም ከዚህም በኋላ ሰላምታ ሰጥቶ ወደየአገራቸው በሰላም አሰናበታቸው። አባ ኖብም ወደ ቦታው ተመልሶ ዐረፈና ወደ ወደደው ክርስቶስ ሔደ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ኖብ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 23 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እግዚኦ ኵነኔከ ሀቦ ለንጉሥ። ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ። ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ"። መዝ 71፥1-2። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 12፥38-42።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "በጽሑ መላእክት ወቦሙ መዘምራን። ማዕከለ ደናግል ዘባጥያተ ከበሮ። በማኅበር ባርክዎ ለእግዚአብሔር"። መዝ 67፥25-26። የሚነበበው መልዕክታት ሮሜ 13፥1-11፣ 1ኛ ጴጥ 2፥13-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 7፥44-54። የሚነበበው ወንጌል ማቴ11፥12-30 ወይም ማቴ12፥38-43። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች ማርያም ወይም የወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
አጠባ ዘንድ በጧት በነቃሁ ጊዜም ያንን የሞተ ልጅ አገኘሁ በነጋም ጊዜ አየሁት እነሆ የወለድሁት ልጄ አይደለም አለች። ያቺ ሁለተኛዋ ሴትም አይደለም ይህ ደኅነኛው የኔ ልጅ ነው እንጂ ያንቺ ልጅ አይደለም ያንቺስ የሞተው ነው አለች። በንጉሡም ፊት እንዲህ ተባባሉ።
❤ ንጉሡም "ሰይፍን አምጡ ደኅነኛውንም ልጅ ከሁለት ቆርጣችሁ እኵሌታውን ለዚች እኵሌታውን ለዚያች ስጡ" አለ። ስለ ልጅዋ ማሕፀኗ ታውኳልና ልጅዋ ደኅና የሆነ ያቺ ሴት መልሳ "ንጉሡን ጌታዬ አይደለም መግደልስ አትግደሉት ደኅነኛውን ልጅ ለሷ ስጧት" አለችው ያቺ ሴት ግን "አካፍሉን እንጂ ለእኔም ለእሷም አይሁን" አለች። ንጉሡም "መግደልስ አትግደሉት እሱን ለእሷ ስጧት ላለችው ለዚች ሴት ደኅነኛውን ሕፃን ስጧት እርስዋ እናቱ ናትና" አለ። እስራኤልም ሁሉ ንጉሡ የፈረደውን ይህን ፍርድ ሰምተው ቅን ፍርድን ይፈርድ ዘንድ የእግዚአብሔር ጥበቡ በሱ ላይ እንዳለ አይተዋልና በንጉሡ ፊት ፈሩ።
❤ ከዚህም በኋላ የእስራኤል ልጆች ከግብጽ ከወጡ አራት መቶ ሰማንያ አራት ዘመን በሆነ ጊዜ ሰሎሞን በእስራኤል ላይ በነገሠ በአራተኛው ዓመት በሁለተኛው ወር የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ሊያንፅ ጀመረ። በዐሥራ አንደኛውም ዘመነ መንግሥቱ ወሩ ባዕድ በሚባል በስምንተኛው ወር ቤቱንና ሥርዓቱን ሁሉ ፈጸመ በሰባት ዓመትም ውስጥ ሠራው የራሱንም ቤት በዐሥራ ሦስት ዓመት ሠርቶ ጨረሰ። ከዚህ በኋላ ሰሎሞን የእግዚአብሔርን ቤትና የራሱን ቤት በሃያ ዘመን ሠርቶ በጨረሰ ጊዜ የእግዚአብሔርን ታቦተ ሕግ ከዳዊት ከተማ ከጽዮን ያመጣት ዘንድ ያን ጊዜ የእስራኤልን ሽማግሌዎችና የነገድ አለቆች የአባቶቻቸውንም ቤት አለቆች ሁሉ በኢየሩሳሌም ሰበሰባቸው።
❤ የእስራኤልም ሰዎች ሁሉ ወደ ንጉሡ ወደ ሰሎሞን በሰባተኛው ወር በጥቅምት ተሰበሰቡ። የእስራኤልም ሽማግሌዎች ሁሉ መጡ ካህናቱም ታቦትዋንና የምስክሩን ድንኳን በምስክሩ ድንኳን ውስጥ ያለ ንዋየ ቅድሳቱንም ሁሉ ተሸከሙ። ንጉሡና እስራኤል ሁሉ በታቦትዋ ፊት ሥፍር ቍጥር የሌላቸው በጎችና ላሞችን ይሠዉ ነበር። ካህናቱም ታቦቷን ከኪሩቤል ክንፎች በታች በቤቱ ውስጥ ወዳለው ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ቦታዋ አገቧት። ኪሩቤል በታቦትዋ ቦታ ላይ ክንፋቸውን ጋርደዋልና ኪሩቤልም በስተላይ በኩል በቅድስተ ቅዱሳን ላይ ታቦትዋን ጋርደዋት ነበር። ከቅድስተ ቅዱሳንም ጋራ የተያያዙ ነበሩ። ቅዱሳን ኪሩቤል ከፍ ብለው ከቅድስተ ቅዱሳኑ አንጻር ላይ ሁነው ያያሉ በውጭ ግን አይታይም ነበር። ከግብጽ አገር በወጡ ጊዜ እግዚአብሔር ከእስራኤል ልጆች ጋራ ቃል ኪዳን ከገባባቸው ሙሴም በዚያ በኮሬብ ከአኖራቸው ከሁለቱ ጽላቶች በቀር በታቦቱ ውስጥ ሌላ አልነበረም።
❤ ከዚህ በኋላ ካህናቱ ከቤተ መቅደስ በወጡ ጊዜ ቤተ መቅደሱን ሁሉ ብርሃን መላው። የእግዚአብሔር ብርሃን በማደሪያው ቤተ መቅደስ መልቷልና ከብርሃኑ መገለጥ የተነሣ ካህናቱ ሥራቸውን መሥራትና ከፊቱ መቆም ተሳናቸው። ያን ጊዜ ሰሎሞን "እግዚአብሔር በደመና ውስጥ እኖራለሁ" ብሏል። "እኔም ለዘላለም የምትኖርበት ማደሪያህ ቤተ መቅደስን በእውነት ሠራሁልህ" አለ። ንጉሡም ፊቱን መልሶ የእስራኤልን ጉባኤ ሁሉ መረቃቸው ወደ እግዚአብሔርም ረዥም ጸሎትን ጸለየ። ሰሎሞንም ይህን ሁሉ ልመና ወደ እግዚአብሔር ለምኖ በጨረሰ ጊዜ በጉልበቱ ተንበርክኮ ከሰገደበት እጆቹንም ከዘረጋበት ከመሠዊያው ፊት ተነሣ። ቆሞም የእስራኤልን ማኅበር "እንደተናገረው ሁሉ ለወገኖቹ ለእስራኤል ዕረፍትን የሰጣቸው እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን" ብሎ በታላቅ ቃል መረቃቸው። ከዚህ በኋላ ንጉሡና የእስራኤል ልጆች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መሥዋዕትን ሠዉ።
❤ ንጉሡ ሰሎሞንም ለእግዚአብሔር ስለ ሰላም መሥዋዕት የሠዋቸው ሃያ ሁለት ሽህ ላሞችና አንድ መቶ ሃያ ሽህ በጎች ናቸው ንጉሡ ሰሎሞንና የእስራኤል ልጆች ሁሉ ያንጊዜ ለእግዚአብሔር ማደሪያ ለቤተ መቅደስ ቅዳሴ ቤት አደረጉ። ቀድሞ በገባዖን እንደታየው ዳግመኛ እግዚአብሔር ለሰሎሞን ታየው "በፊቴ የለመንኸኝ ልመናህንና ጸሎትህን ሰማሁ። እንደ ልመናህም ሁሉ አደረግሁልህ ስሜ በዚያ ለዘላለሙ ጸንቶ ይኖር ዘንድ የሠራኸውንም ቤተ መቅደስ አከበርሁት ልቡናዬም ዐይኖቼም በዘመኑ ሁሉ በዚያ ጸንተው ይኖራሉ" አለው። ሰሎሞንም አርባ ዘመን ነገሠ ከመንገሡም በፊት ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ መላ ዕድሜውም ሃምሳ ሁለት ዓመት ነበር በሰላም አረፈ።
ይህም ጥበብ የተሰጠው ንጉሥ ሰሎሞን ጥቅም ያላቸው ብዙዎች መጻሕፍትን ደርሶአል። እሊህም ትንቢትና ትምህርት ያለባቸው ምሳሌዎችና መኃልዮች ናቸው።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅዱስ_አባ_ኖብ፦ ይህም ቅዱስ መነኰስ በላይኛው ግብጽ ከሚገኙ ገዳማት በአንዱ ገዳም ውስጥ የሚጋደል ጽሙድ ነበር። ዲዮቅልጥያኖስም ብዙዎች ሰማዕታትን ሊአሠቃይና ደማቸውን ሊያፈስስ በጀመረ ጊዜ በአንዲት ቀን ሰማንያ ሰማዕታትን አቅርቦ ደማቸውን አፈሰሰ። በዚያን ጊዜ አባ ኖብን አስታወሱት የእንዴናው ገዥ ወደሆነው ወደ አርያኖስ አቀረቡት። እርሱም "ለአማልክት ዕጠን ሠዋ ይህንንም የምንኵስና ልብስ ከላይህ አውጥተህ ጣል" አለው። አባ ኖብም "ይህ ሥራ ከቶ ከእኔ ዘንድ አይደረግም የክብር ባለቤት ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስንም አልተውም የረከሱ ጣዖታትንም አላመልክም" አለ። መኰንኑም በየራሱ በሆነ ሥቃይ እጅግ አሠቃየው ያም አባ ኖብ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ኃይል ታግሦ ተቀበለ።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ አምስቱ አህጉር ሰደደው በዚያም በጉድጓድ ውስጥ ጣሉት በውስጡም ጌታችን ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስን አጥፍቶ ደግ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስን እስከሾመው ድረስ ሰባት ዓመት ኖረ። ቈስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ ክብር ይግባውና ስለ ክርስቶስ የታሠሩትን ሁሉ ፈትተው ወደርሱ እንዲአቀርቧቸውና ከእርሳቸው እንዲባረክ ወደ አገሮች ሁሉ ደብዳቤዎችን ላከ። ለመልእክተኞችም እንዲህ አላቸው "ሁሉንም ወደ እኔ ማድረስ ካልተቻላችሁ እጆቻቸውን በራሴ ላይ ጭነው ይባርኩኝ ዘንድ ክብር ያላቸውን ታላላቆችንና መምህራኑን አምጡአቸው"።
ከእነርሱም ውስጥ የታወቁ አህናህ ከተባለ አገር አባ ዘካርያስ ከፍዩም መክሲሞስ ከሀገረ ድኂን አጋብዮስ ከሀገረ በላኦስ አባ ኖብ ናቸው የንጉሥ መልእክተኞችም በየአገሮች ሁሉ እየዞሩ የታሠሩ ቅዱሳንን ከእሥር ያወጡአቸው ነበር እነርሱም ደስ ይላቸው ነበር የተመሰገነ እግዚአብሔርንም ያመሰግኑት ነበር ይዘምሩለትም ነበር።
❤ የንጉሥ መልእክተኛም አባ ኖብን ከአምስቱ አገሮች ፈልጎ የአገሩ አንጻር ወደ ሆነች ወደ ሀገረ በሰላ ወሰደው። በዚያም የብረት ልብስ ለብሶ ተቀምጦ ነበር የንጉሡ መልእከተኛም አገኘውና ከእርሱ ጋራ ወሰደው ወደ እንዴናውም እስከ ደረሱ በመርከብ ተሳፈሩ ክርስቲያኖችም ተሰበሰቡ ከውስጣቸውም አራት ኤጲስቆጶሳት ነበሩ አባ ኖብንም ያለ ውዴታው ቅስና ሾሙትና የቊርባን ቅዳሴን ቀደሰ።
❤ በቅዳሴውም ፍጻሜ ቅድሳት ለቅዱሳን ብሎ ጮኸ ይህም ማለት ንጹሕና ቅዱስ የሆነ ከሥጋው ከደሙ ይቀበል ማለት ነው በዚያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በመሠዊያው ላይ ተቀምጦ ንስሐ የገቡትን ኃጢአታቸውን ይቅር ሲላቸው አየው ሥጋውንና ደሙንም ከአቀበላቸው በኋላ ወደ ንጉሡ ለመሔድ ተዘጋጁ ቍጥራቸውም ሰባ ሁለት ነበር ሠላሳ ሰባት ሠረገላም አዘጋጅተውላቸው እየአንዳንዳቸው በሠረገላው ተቀመጡ። በአለፉም ጊዜ የደናግል ገዳማት ካሉበት ደረሱ ደናግሎም ወጥተው ተቀበሏቸው ቊጥራቸው ሰባት መቶ ነበር ከእነርሱ ጋራም እስከሚሰበሰቡ በቅዱሳን ፊት ይዘምሩ
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሰኔ ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ለንጉሥ_ለቅዱስ_ዳዊት_ልጅ ለጥበበኛው ንጉሥ #ለቅዱስ_ሰሎሞን_ለዕረፍቱ መታሰቢያ ቀን በዓል፣ በክብር ባለቤት #በኢየሱስ_ክርስቶስ ለታመነ #ለአባ_ኖብ ለዕረፍት መታሰቢያ በዓልና ለሊቀ ሰማዕታት ለቅዱስ ጊዮርጊስ ለወራዊ በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከቅዱሳን ሰማዕታት #ከመርቆሬዎስ_ከቶማስና_ፊልጶስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከት ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የልበ_አምላክ_የቅዱስ_ዳዊት_ልጅ_ንጉሥ_ሰሎሞን፦ የዚህ የሰሎሞንም እናት ስም ቤርሳቤህ ነው ዳዊትም ሕግ ተላልፎ ከእርሷ ጋራ ስለ መበደሉ ባሏንም ስለ ማስገደሉ ጌታ በገሠጸው ጊዜ ንስሓ ገብቶ መሪር ልቅሶን አለቀሰ ጌታም ንጹሕ ስለሆነ ንስሓው ይቅር አለው። ከዚህም በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ እርሷን አገባትና ሰሎሞንን ወለደው ንጉሥ ዳዊትም ከእርሱ በኋላ ልጅዋ ሰሎሞን እንዲነግሥና በዙፋኑ ላይ እንዲቀመጥ ቃል ገባለት።
❤ እንዲህም ሆነ ሰሎሞን ዐሥራ ሁለት ዓመት በሆነው ጊዜ አዶንያስ እነግሣለሁ ብሎ ተነሣ ምክሩም ሁሉ ከሶርህያ ልጅ ከኢዮአብና ከካህኑ አብያታር ጋር ሆነ። እርሱም አዶንያስን ተከትለው ሰደዱት። አዶንያስም በሮጌል ምድር ምንጭ አጠገብ ባለ በኤልቲ ዘዘኤልቲ ላይ ፍየሎችን በጎችንና ላሞችን አርዶ የንጉሥ አሽከሮች የሆኑ የይሁዳ አርበኞችን ሁሉና የንጉሡን ልጆች ወንድሞቹን ሁሉ ጠራ።
❤ ከዚህም በኋላ አዶንያስ ይህን እንዳደረገ ለቤርሳቤህ በነገሩዋት ጊዜ ወደ ንጉሥ አዳራሽ ውስጥ ገብታ ለንጉሡ ሰገደች ንጉሥ ዳዊትም "ምን ሆነሽ" አላት። "ጌታዬ ንጉሥ ሆይ ልጅሽ ሰሎሞን ከእኔ በኋላ ይነግሣል በዙፋኔም ላይ ይቀመጣል ብለህ ለእኔ ለባርያህ በፈጣሪህ በእግዚአብሔር ስም አንተ ማልክልኝ እነሆ ዛሬ አዶንያስ ነገሠ ጌታዬ ንጉሥ ሆይ አንተ ግን አላወቅህም" አለችው። ከንጉሥም ጋራ ገና ስትነጋገር ነቢዩ ናታን መጣ ለንጉሡም "ናታን መጣ" ብለው ነገሩት። ወደ ንጉሡም ገባ በምድር ላይም በግምባሩ ተደፍቶ ሰገደ። ነቢዩ ናታንም "ከእኔ ቀጥሎ አዶንያስ ይንገሥ በዙፋኔም ላይ ይቀመጥ ያልክ አንተ ነህን? ዛሬ ወርዶ በጎችንና ብዙ ፍየሎችን አርዶ የሠራዊቱ አለቆችንና የንጉሥ አሽከሮችን ሁሉ ካህኑ አብያታርንም ጠርቷልና በፊቱም ይበላሉ ይጠጣሉ አንዶንያስ ሽህ ዓመት ያንግሥህ ይሉታል" አለው።
❤ ዳዊትም መልሶ "ቤርሳቤህን ጥርዋት" አለና ጠሩዋት ገብታም በንጉሡ ፊት ቆመች። "በእግዚአብሔር ፊት እንደማልኩልሽ አሁንም በዚች ቀን እንደዚሁ እንዳደርግ ሰውነቴን ከመከራዬ ሁሉ ያዳናት የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሕያው ነው" ብሎ ማለ። በቤርሳቤህም አንገቷን ደፍታ በግምባርዋ በመሬት ወድቃ ለንጉሡ ሰገደች "ጌታዬ ንጉሥ ዳዊት ለዘላለም ኑር" አለች።
❤ ንጉሥ ዳዊትም "የዮዳሄ ልጅ ብንያስና ካህኑ ሳዶቅን ነቢዩ ናታንንም ግራዝማቹንና ቀኝ አዝማቹን ጥሩልኝ" አለ። ንጉሡም ከእናንተ ጋራ የጌታችሁ አሽከሮችን ይዛችሁ ልጄ ሰሎሞንን በበቅሎዬ ላይ አስቀምጣችሁ ወደ ግዮን አውርዱት"። በዚያም ነቢዩ ናታንና ካህኑ ሳዶቅ "ቀብታችሁ በእስራኤል ላይ አንግሡት" አላቸው። ቀንደ መለከት ንፉ "ሰሎሞን ሺህ ዓመት ያንግሥህ በሉ። ተከትላችሁም ውጡ ገብቶም በዙፋኔ ላይ ይቀመጥ እርሱም ስለ እኔ ፈንታ ይንገሥ በሁሉቱ ነገድና በዐሥሩ ነገድ ይነግሥ ዘንድ እኔ አዝዣለሁ"።
❤ ካህኑ ሳዶቅም ከድንኳን ቀርነ ቅብዑን ወስዶ ሰሎሞንን ቀባው ቀንደ መለከትንም ነፉ ሕዝቡም ሁሉ ተከትለውት ወጡ ከበሮም መቱ ታላቅ ደስታም አደረጉ ከድምፃቸውም የተነሣ ምድሪቱ ተናወጸች።
❤ ሰሎሞንም በመንግሥት ዙፋኑ ተቀመጠ። የንጉሡም አሽከሮች ጌታቸው ንጉሡ ዳዊትን ሊአመሰግኑ ገቡ። "እግዚአብሔር የሰሎሞንን ስም ከስምህ ይልቅ መልካም ያደርገው ዙፋኑንም ከዙፋንህ ይልቅ የበለጠ ያድርገው" አሉት። ንጉሡም በዐልጋው ሁኖ ሰገደ። እንዲህም አለ "ዐይኖቼ ሲያዩ በዙፋኔ ላይ የሚቀመጥ ልጅን ለኔ ለባሪያው ዛሬ የሰጠ የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን" አለ።
❤ ዳዊትም የሚሞትበት ወራት በደረሰ ጊዜ ልጁ ሰሎሞንን እንዲህ ሲል አዘዘው። "እኔ ሰው ሁሉ በሚሔድበት በሞት ጎዳና እሔዳለሁ አንተ ግን ጽና ብልህ ሰውም ሁን። በሕጉ ጸንተህ ትኖር ዘንድ የፈጣሪህ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝን ጠብቅ እኔ እንዳዘዝሁህ እንዴት እንደምታደርግ ታውቅ ዘንድ በመሴ ሕግ የተጻፈውን ትእዛዙንና ሕጉን ፍርዱንም ጠብቅ ልጆችህ ሕጌን ቢጠብቁ በፊቴም በፍጹም ልቡናቸው በፍጹም ሰውነታቸው በዕውነት ጸንተው ቢኖሩ ከእስራኤል ዙፋን ላይ ሰው አይጠፋብህም ብሎ እግዚአብሔር ለእኔ የነገረኝ ቃሉን ያጸና ዘንድ ጠብቅ" ብሎ አዘዘው። ዳግመኛም ከኢዮአብና በሳሚ ወልደ ጌራ ላይ በቀል እንዲአደርግ አዘዘው እነርሱ እጅግ የከፋና ብዙ ክፋት የሠሩ ነበሩና።
❤ ከዳዊት ዕረፍትም በኋላ ሰሎሞን ከዚያ መሥዋዕትን ይሠዋ ዘንድ ተነሥቶ ወደ ገባዖን ሔደ ገባዖን ፈጽማ ትሰፋ ነበርና ሰሎሞንም በገባዖን በዚያው መሠዊያ ውስጥ ሽህ መሥዋዕትን ሠዋ።
❤ እግዚአብሔርም ለሰሎሞን በሌሊት በሕልም ተገለጠለት "ለአንተ እሰጥህ ዘንድ በልብህ ያሰበውን ልመናን ለምን" አለው። ሰሎሞንም "በቅንነትና በእውነት በንጹሕ ልቡናም ከአንተ ጋራ በፊትህ ጸንቶ እንደኖረ ከአባቴ ከዳዊት ጋራ ታላቅ ቸርነትን አድርገሃል በዚችም ቀን ልጁን በዙፋኑ ላይ ታስቀምጠው ዘንድ ይህን ታላቁን ቸርነት አጽንተህለታል" አለው። "አሁንም አቤቱ አንተ ፈጣሪዬ ስለ አባቴ ስለ ዳዊት ፈንታ እኔን ባሪያህን አነገሥኸኝ እኔም መግቢያዬንና መውጫዬን የማላውቅ ታናሽ ብላቴና ነኝ። እኔ ባሪያህ ግን የማይቈጠር ብዙ ሕዝብ በሆነ በመረጥከው ወገንህ መፍረድ የሚችል የለምና ሰምቶ ለወገኖችህ በእውነት ፍርድን ይፈርድ ዘንድ ከክፉ ነገርም ለይቶ በጎውን ነገር ያውቅ ዘንድ ለባሪያህ ዕውቀትን ስጠው"። ሰሎሞን ይህንን ነገር ለምኖታልና ይህ ነገር እግዚአብሔርን በፊቱ ደስ አሰኘው።
❤ እግዚአብሔርም "ይህንን ነገር ከእኔ ለምነሃልና ለአንተም ብዙ ዘመንንና ባለጸግነትን አለመንህምና ጠላቶችህንም አጥፋልኝ ብለህ አልለመንህምና ነገር ግን ፍርድ መስማትን ታውቅ ዘንድ ለምነሃልና እነሆ እንዳልህ አደረግሁልህ። እነሆ ከአንተ አስቀድሞ እንዳልነበረ ከአንተም በኋላ እንዳንተ ያለ እንዳይነሣ አድርጌ ብልህና አስዋይ ልቡናን ሰጠሁህ። ሰው በመንግሥቱ እንዳንተ እንዳልሆነ አድርጌ ያልለመንኽኝን ባለጠግነትንና ክብርንም በዘመንህ ሁሉ እሰጥሃለሁ" አለው። ሰሎሞንም ከእንቅልፋ በነቃ ጊዜ እውነተኛ ሕልም እንደ ሆነ ዐወቀ ተነሥቶም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደ በጽዮንም በእግዚአብሔር ታቦት ሕግ አንጻር ባለ በመሠዊያው ፊት ቆሞ የሰላም መሥዋዕትን አቀበረ ለሰዎቹና ለሱም ታላቅ ግብዣ አደረገ።
❤ በዚያን ጊዜም ሁለት አመንዝራ ሴቶች ወደ ንጉሡ መጥተው በፊቱ ቆሙ አንዲቱም ሴት "ጌታዬ ስማኝ እኔና ይህች ሴት በአንድ ቤት እንኖራለን በአንድ ቦታም ወለድን እኔ በወለድሁ በሦስተኛው ቀን ይህች ሴት ወለደች በአንድነትም እንኖራለን በዚያም ቤት ከሁለታችን በቀር ከኛ ጋራ ማንም አልነበረም። በላዩ ላይ ተጭናዋለችና የዚያች ሴት ልጅ በሌሊት ሞተ። በሌሊት እኩሌታም ተነሥታ ተኝቼ ሳለሁ ልጄን ከአጠገቤ ወስዳ በብብቷ አስተኛችው። የሞተውን ልጅዋንም በአጠገቤ አስተኛችው። ልጄን
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን" ❤
❤ #ሰኔ ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ አራዊትና እንስሳት እንደሰው በድምፅ ያነጋግሯቸውና ይታዘዙላቸው ለነበረው፤ ይጠብቋቸው የነበሩትን በጐችና ፍየሎችን በነብርና በተኩላ ያስጠብቁ ለነበሩት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ተጠምቀ_መድኅን_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #አቡነ_ተጠምቀ_መድኀን፦ በጐጃም ከሚታወቁ ታላላቅ ቅዱሳን ውስጥ እንዱና ዋነኛው ናቸው። እርሳቸውም እንደነ አቡነ አብራንዮስ ላሉ ቅዱሳን ገዳማቸውን እንዲመሠርቱ ያደረጉ ታላቅ አባት ናቸው" አቡነ አብራንዮስ በነፋስ ሠረገላ እየሔዱ ሲታዩ እንዲሁም ሌሎች ተኣምራትን ሲያደርጉ ይኽንንም ድንቅ ሥራቸውን ሰዎች ቢያውቁባቸው ውዳሴ ከንቱን ንቀው ወደ አቡነ ተጠምቀ መድኅን ዘንድ ሔደው በዚያ በታላቅ ተጋድሎ ከኖሩ በኋላ አቡነ ተጠምቀ መድኀን "በአንተ ምክንያት ብዙ ነፍሳት ይድናሉ ክፍልህ በዚያ ነው" በማለት ዛሬ ላይ ኤርትራ ውስጥ ወደሚገኘው ደብረ ጥሉል ልከዋቸዋል። እርሳቸውም ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል እየመሯቸው መጥተው አስደናቂውን እንዳ ኣቦና ደብረ ጥሉል ገዳምን መሥርተዋል።
❤ አቡነ ተጠምቀ መድኅን በጻድቁ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት የነበሩ ሲሆን የታላቁ የጉሐንቻ አንድነት ገዳም መሥራች ናቸው። በ17ኛው መ/ክ/ዘ የነበሩት አቡነ ተጠምቀ መድኅን በርካታ ገዳማትን መሥርተዋል። ከእነዚኸም ውስጥ፡- አውሽካን ኢየሱስ ገዳም፣ ካጋና ኤዎስጣቴዎስ ገዳም፣ ወገዳ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም እና ሌሎችንም በርካታ ገዳማትን ጻድቁ እንዳቋቋሙ ከጎሐንቻ ቅድስት ማርያም ገዳም የተገኘ ጽሑፍ ይገልጻል። እነዚኸም ገዳማት አሁን ላይ የት እንዳሉ ማወቅ አልተቻለም፣ ምናልባትም በእነ ግራኝ አህመድ የጠፉ ይሆናሉ።
❤ ሌላኛዋ በአቡነ ተጠምቀ መድኅን የተመሠረተችው ሐረጽ ማርያም ገዳም ናት። ይኸችም ገዳም የምትገኘው በአዊ ዞን ሀገረ ስብከት መተከል ውስጥ በጓንጓ ወረዳ ውስጥ ነው። ሌላው የጻድቁ ገዳም ቻግኒ የሚገኘው የስጋዲ ቅዱስ ሚካኤል አቡነ ተጠምቀ መድኅን አንድነት ገዳም ነው። ይኸም የጻድቁ ገዳም በርካታ መነኰሳት የሚገኙበት ታላቅ የአንድነት ገዳም ሲሆን በተለያዩ የልማት ሥራዎች ይታወቃል። አቡነ ተጠምቀ መድኀን አባታቸው ወልደ ክርስቶስ እናታቸው ወለተ ማርያም የተባሉ ደጋግ ክርስቲያኖች ሲሆኑ ጻድቁ የተወለዱት ታኅሣሥ 2 ቀን ነው። በጥምቀት ሀብተ ውልድና የተቀበሉት ደግሞ ጌታችን በተጠመቀበት ዕለት ጥር 11 ቀን ስለሆነ "ተጠምቀ መድኅን" ተብለው መጠራታቸውም ከዚህ ከክርስትና ቀናቸው በመነሣት ነው።
❤ አቡነ ተጠምቀ መድኅን አስተዳደጋቸው እንደማንኛውም የገጠር ልጅ እረኛ ሆነው ያደጉት። እርሳቸው ግን ከልጅነታቸው ጀምረው መንፈሳዊ ትምህርት ለመማር ካላቸው ጽኑ ፍላጎት የተነሣ ያግዷቸው (ይጠብቋቸው) የነበሩትን በጐችና ፍየሎችን በነብርና በተኩላ አስጠብቀውና አደራ ሰጥተው ወደ አባቶች ዘንድ በመሔድ ከመነኰሳት እግር ሥር ተቀምጠው ዳዊት ደግመው ወንጌል ተምረው ማታ ይመለሳሉ። ተምረው ጨርሰው ሲመለሱም በጐቹና ፍየሎች ከነብርና ከተኩላ ከአራዊት ጋር ሲቦርቁ ያገኟቸዋል።
❤ አባታቸውም ሳያውቁባቸው ከእረኝነታቸው እንደተመለሱ ሆነው ማታ ወደቤታቸው ይመለሳሉ። ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አንድ ባሕታዊ አባታቸውን ወልደ ክርስቶስን አግኝቶ "ልጅህን ስጠኝ ላስተምረው" ሲላቸው አባታቸውም "በጎቹንና ፍየሎቹን ማን ይጠብቃቸዋል?" በማለት እምቢ አሉ። አባታቸውም ተጠምቀ መድኅንን ዳዊት አንግበው ስላዩዋቸው ይኸንን ሁኔታ ለማረጋገጥ ልጃቸው እያገዱ በእረኝነት ከሚውሉበት ቦታ ቢሔዱ በሚያስገርም ሁኔታ በጎቹና ፍየሎቹ ከነብርና ከተኩላ ጋር ሲጫወቱ ሲቦርቁ ተመለከቱ። ሲመሽም አውራዎቹ እንስሶቹን ሲሸኟቸው አዩ" ማታም ልጃቸውን ተጠምቀ መድኅንን "ልጄ የት ዋልህ?" ብለው ሲጠቋቸው "ከብት ሳግድ ዋልሁ" ሲሉ አባታቸውም "ልጄ ሆይ! ነገሩን ተረድቼዋለሁ፣ ከዛሬ ጀምሮ እረኛ አትሆንም፣ ከባሕታውያን ዘንድ ሔደህ ተማር" ብለው ወደ ገዳም ላኳቸው።
❤ ከዚህም በኋላ አቡነ ተጠምቀ መድኅን መንፈሳዊ ትምህርት እየተማሩ የአባቶችን መንገድ እየተከተሉ በተጋድሎ መኖር ጀመሩ። ገና ከሕፃንነታቸው ጀምረው ቁርስና ምሳቸውን ለነዳያን በመስጠት እርሳቸው ግን ሲጾሙ ውለው በቀን እንድ ጊዜ ብቻ ይቀምሱ ነበር። ተጋድሏቸውንም ለማጽናት ወደ ታላቋ መርጡል ማርያም በመሔድ በ23 ዓመታቸው አባ ዝክረ ማርያም በሚባለ አባት እጅ መነኰሱ። ከመነኰሱም በኋላ ከሚለብሱት የፍየል ቆዳ ሥር ሰውነታቸውን በሰንሰለት አሥረው ከመኖራቸውም በላይ ቅዳሜና እሑድ ከሚቀምሱት ዳቤ በቀር እህል አይቀምሱም ነበር። ስግደታቸውም በቀን አንድ ሺህ እንደነበር ገድላቸው ይናገራል።
❤ ጻድቁ ከተሰጣቸው ጸጋ የተነሣ አራዊትና እንስሳት እንደሰው በድምፅ ያነጋግሯቸውና ይታዘዙላቸው ነበር። እንደ ረድእ ሆኖ የሚታዘዛቸው ጸዋሬ መስቀል የሚባል አንድ አህያ ነበራቸው፤ እርሱም መልእክት በማድረስና በመቀበል አባታችንን ያገለግላቸው ነበር፣ አምጣ ያሉትን ያመጣል፣ ውሰድ ያሉትን ይወስዳል። እርሳቸውም ከጐጃም እስከ ሱዳን ጠረፍ ድረስ ወንጌልን ሰብከው በርካታ ከሃዲያንን አስተምረው በማጥመቅ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከጌታችን ቃልኪዳን ተቀብለው በጻድቁ ዮሐንስ ዘመን በ1670 ዓም በክብር ዐርፈዋል።
❤ አቡነ ተጠምቀ መድኀን ያረፉት ሰኔ 23 ሲሆን በዓለ ዕረፍታቸው ዐፅማቸው በክብር ተቀምጦ ባለበት በጋሾላ ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድነት ገዳም ውስጥ በታላቅ ድምቀት ይከበራል። ያረፉትም ለአገልግሎት ወደ ጋሾላ ቅዱስ ጊዮርጊስ የእናቶች ገዳም በሔዱበት ወቅት ስለነበር ዛሬም የከበረ ዐፅማቸውም በዚያው ይገኛል። ከአቡነ ተጠምቀ መድኅን እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን፣ በጸሎታቸው ይማረን። ምንጭ፦ በእንተ ቅዱሳን ኅሩያን መጽሐፍ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለሐዋርያት_ሰኔ_ጾም_አራተኛ_ሳምንት #ዘመነ_አስተምሕሮ_ለሚታሰብበት_ሰንበት (እሑድ) ቀን እግዚአብሔር አምላክ በሰላም በጤና አደረሰን። እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ሁለተኛ ዘመን አስተምህሮ #ከሰኔ_18_እስከ_ሰኔ 24 ይታሰባል።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ "ናክብር ሰንበቶ በጽድቅ ወኢንኅድግ ሥርዓቶ ለዘውእቱ ባሕቲቱ ሃሌ ሉያ ጻድቅ ውእቱ ጽድቅ ይኴንን በመንግሥቱ ሃሌ ሉያ ይገብር ነግሀ እንተ ጸብሐት የሀበነ ምሕረቶ ወንሕነኒ ርቱዓ ነአኵቶ ለእግዚአብሔር ሃሌ ሉያ አምላክነሰ አምላክ አድኅኖ ይክል ኵሎ ወአልቦ ዘይሰዓኖ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ጽድቅ ቃሉ ወእሙን ነገሩ። ትርጉም፦ ብቻውን ቅድመ ዓለም ለነበረ ዛሬም ላለ ወደፊትም ዓለምን አሳልፎ ለዘላለም ለሚኖር ምስጋና ይገባል፤ መልካም ሥራ በመሥራት በእውነት ሰንበቱን እናክብር፤ ሥርዓቱንም አንተው፤ እርሱ ጻድቅ ነው፤ በመንግሥቱ እውነትን ይፈርዳል፤ ቅድመ ዓለም ለነበረ ዛሬም ላለ ወደፊትም ዓለምን አሳልፎ ለዘላለም ለሚኖር አምላካችን የሚሳነው ነገር የሌለ ሁሉን ማድረግ የሚችል አዳኝ አምላክ ነው፤ ቅድመ ዓለም ለነበረ ዛሬም ላለ ወደፊትም ዓለምን አሳልፎ ለዘላለም የሚኖር አምላካችን ቃሉ የታመነ ነው፤ ነገሩም እውነት ነው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዚህ_ሳምንት_የዕለቱ_ምስባክ፦ "አንተሰ እግዚኦ መሐሪ ወመስተሣህል። ርኁቀ መዓት ወብዙኀ ምሕረት ወጻድቅ። ነጽር ላዕሌየ ወተሣሃለኒ"። መዝ 85፥15-16። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 5፥12-ፍ.ም፣ 3ኛ ዮሐ 1፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 16፥1-14። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 22፥1-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ነው። መልካም በዓለ ዕለተ ሰንበትና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ ዐፄ ፋሲልም "ድንግል መነኲሴ ፈልጎ ላመጣልኝ እሸልማለሁ" ብለው አወጁ፡፡ አቡነ ምእመነ ድንግል ባሉበት አካባቢ የሚኖሩ ይጉይታና ባጅር የሚባሉ ባላባቶች ውሾቻቸውን አስቀድመው ሲያፈላልጉ ጻድቁም እንደሚፈለጉ ስለሚያውቁ አርድእቶቻቸውን "ሰው ሲመጣ በበሩ እየተመለከታችሁ እንድትነግሩኝ" ብለው ዳዊታቸውን እየደገሙ ሳሉ ረዳታቸው ውሻ አዩና "አባ ውሻ መጣ" አሏቸው፡፡ አባም "እ! ብለው ውሻ መጣ ሰው መጣ፤ ሰው መጣ ነገር መጣ" ብለው ወደ ባሕር ገቡ፡፡ በገቡም ጊዜ እዚህ ነበር የማይባል ድንጋይ ከውኃው ወደ ላይ ገፍቶ (አንሥቶ) አወጣቸው፡፡ ይህ ድንጋይም በአሁኑ ሰዓት በዚያው ይታያል፡፡ ባላባቶችም "አባ ከዐፄ ፋሲል ተልከን ነው፡፡ "የአባቴን ምላስ ግዝቱን ፈቶ የሚመልስ መነኲሴ ካገኘሁ ተዋሕዶ ሃይማኖትን እመልሳለሁ" ብለው ቃል ስለገቡ ነውና ማስረጃ የንጉሡ ማኅተም ይኸው" ብለው ባሳይዋቸው ጊዜ በደስታ አብረዋቸው በመሄድ ከእነ አባ ዓምደ ሥላሴ ጋር በመጸለይ አዋጅ አስነግረው "ፋሲል ይንገሥ፣ ካቶሊክ ይፍለስ፣ ተዋሕዶ ይመለስ፣ የዐፄ ሱስንዮስ ምላስ ይመለስ፣ እግዚአብሔር ይፍታህ" ሲሉ ተጎልጉሎ የነበረው ምላሳቸው ተመለሰ በዚያን ጊዜ ዐፄ ሱስንዮስ "ብቆይ ዓመት ብበላ ገአት/ገንፎ/" ብለው በመናገር ምላሳችው፤ እንደ ቀድሞው ሆነላቸው፡፡ ዐፄ ሱስንዮስም ለንሰሓ ሞት በቅተው፣ መንግሥታቸውን ለልጃቸውን አውርሰው በክብር አርፈው በታላቁ ገዳም ዳጋ እስጢፋኖስ አፅማቸው ከብዙ ነገሥታት አፅም ጋር ይገኛል፡፡
❤ በዚያን ጊዜ ያች ደገኛ አገልጋይ ጎንደር የዐፄ ግንብ እንደሚሠራ ለዐፄ ፋሲል ትንቢት ተናግራለች፡፡ይህ ቦታ ብዙ ዘመናትን ያስቆጠረና ዛሬም ድረስ ድንቅ ተአምራት እየገለፀበት ይገኛል፡፡ ከነዚህም ውስጥ ለግንዛቤ ያህል የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
፩) ንጉሡ ዐፄ ፋሲልም የጻድቁን ቦታ ሳይረሱ መንግሥታቸው ከጸናላቸው በኋላ ለገዳሙ ርስት ጉልት ሊሰጡ በተጓዙ ጊዜ ከአፋፍ ቆመው “የት ነው የጻድቁ በዓት?” ሲሉ “ይህ ወይራና ጽድ የበዛበት በፊታችን የምናየው ነው” ሲሏቸው “ይህ ጭው ያለው ዱር ነው?” ሲሉ “አዎ” አሏቸው፡፡ በዚህ የተነሳ የቦታው ስያሜ “ጩጊ” ለመባል በቃ፡፡ የጻድቁ በኣት መጸለያ ዋሻም በስማቸው “ምእመነ ድንግል” እንደተባለ አለ፡፡ ጻድቁም በሕይወት እንደነ ሄኖክ፣ ኤልያስ፣ ቅዱስ ያሬድ እና አባ ዮሃኒ ሰኔ 21 ቀን ከሞት ተሰውረዋል በህቡእ አሉ፡፡
፪) የጻድቁ መጸለያ ቦታ በተፈጥሮው የተሸነቆረ መስኮት አለው፡፡ በዚህ ቦታ ላይ መኻን የሆኑ ሁሉ በመስኮቱ ወጥተው ሲመለሱ ማየ ዮርዳኖሱን ጠጥተው ሲሳሉ ልጅ ለማግኘት ይበቃሉ፡፡ ይህን ቃል ኪዳን የሚያውቁ ጳጉሜን በሙሉ በማየ ዮርዳኖሱ በመጠመቅ ትልቅ ሐብተ ፈውስ ያገኛሉ፡፡
፫) የዮርዳኖሱን ጠበል የጠጣ ሲሞት ሥጋው አይፈርስም፣ አይበሰብስም፡፡ እንኳን በአርአያ ሥላሴ የተፈጠረው ሰው እንስሳቱ እንኳን አካላቸው ሳይፈርስ ይቆያል፡፡ ለማስረጃ ያህል እንኳን 16 የሚሆኑ ፍየሎች አካላቸው ሳይፈርስ 400 ዘመን ያስቆጠሩ አሉ፡፡
፬) በ1968 ዓ.ም. አንድ ዛፍ ከወንዝ ዳር ወድቆ አንድ ገበሬ ለማገዶ ሲፈልጠው እስከነ ምሳሩ ተነሥቶ ቆሞ በሥሩም ሰባት ጸበል ፈልቶ ብዙ ህሙማንን ፈውሰዋል፡፡
፭) ሰኔ 21 ቀን 1988 ዓ.ም አንድ ዛፍ በእርሻ መካከል ስለወደቀ ለማስወገድ ከሥሩ በእሳት ቢያቃጥሉት ሥሩን ትቶ ከጫፍ እየነደደ ከወደቀበት ተነሥቶ ቆሟል፡፡
፮) በቦታውም ላይ የብዙ ቅዱሳን አፅም ይገኛል፡፡
❤ ከታላቁ አባታችን ከአቡነ ምዕመነ ድንግል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን፣ ምስለ አድባራት ወገዳማት።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሰኔ ፳፩ (21) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ታላቋን #ጩጊ_ቅድስት_ማርያም_ገዳም_ለመሰረቱት፣ ዐፄ ሱስንዮስ የካቶሊክ እምነት በተቀበለ ጊዜ ምላሱ ተጎልጉሎ ሲሰቃይ ተፈልገው መጥተው ለፈወሱት፣ ጠበላቸው የጠጣ ሲሞት ሥጋው እንዳይፈርስ ቃል ኪዳን ላላቸው (እንኳን በአርአያ ሥላሴ የተፈጠረው ሰው እንስሳቱ እንኳን አካላቸው ሳይፈርስ) ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ምዕመነ_ድንግል እንደ #ቅዱስ_ሄኖክና_ቅዱስ_ዕዝራ_ከሞት_ለተሰወሩበት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #አቡነ_ምዕመነ_ድንግል፦ አስደናቂውን የጩጊ ማርያም ገዳምን የመሠረቱት አቡነ ምዕመነ ድንግል የተወለዱት በወገራ አውራጃ ሲሆን ገና በሕፃንነታቸው በእናት በአባታቸው ቤት እያሉ ጀምሮ መንፈሳዊ ትሩፋቶችን በመሥራት በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡ አባታችን ምእመነ ድንግል የምንኲስና ልብስና የእግዚአብሔር ጸጋ በመፈለግ አዳጋት ማርያም ወደ ምትባል ገዳም በመሄድ ብዙ ተጋድለዋል፡፡ ከዚያም ወደ ዋልድባ ገዳም በመሄድ ብዙ ተጋድለዋል፤ ጽናታችውን ያዩ የዋልድባ ገዳም መነኰሳት አባትና መምህር እንዲሆኗቸው ቢጠይቋቸው እራሳቸውን ዝቅ በማድረግ "እኔ መምህርና አባት ልሆን አይገባኝም" በማለት እንቢ ቢሉም መነኰሳቱ አበምኔት አድርገው ሾመዋቸዋል፡፡ አባታችንም በተሾሙበት በዚህ ገዳም በከፍተኛ ተጋድሎና በእግዚአብሔር ጸጋ ብዙ መንፈሳዊ መነኰሳትንና መምህራንን በትምህርታቸው አፍርተዋል፡፡
❤ ከዚህ በኋላ በጊዚው በዐፄ ሱስንዮስ ዘመነ መንግሥት በሃይማኖት ምክንያት በርካታ ቅዱሳን መነኰሳት ሰማዕትነትን እየተቀበሉ ስለነበረ እሳቸውም ስለ ትክክለኛይቱ ሃይማኖት መስክረው ሰማዕትነትን ሊቀበሉ ሲመጡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል "ጊዜህ ገና ነው፤ የተዋሕዶ ሃይማኖት መመለሷን ሳታይ ሰማዕትነትን አትቀበልም" ብሏቸው አሁን በስማቸው በሚጠራው ተራራ ዋሻ ፈልፍለው እንዲጸልዩና እንዲያስተምሩ እስከመቼም ቢሆን በረድኤት እንደማይለያቸው አስረድቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ዋሻው ውስጥ እያሉ የኢትዮጰያን ቤተክርስቲያንና ሃይማኖት ለማጥፋት ያቀደ አረመኔ ካቶሊክ ፈረንጅ መጥቶ፤ "ክርስቶስን አንድ አካል ሁለት ባሕርይ" ብላችሁ እመኑ እያለና ሕዝቡን እየጨፈጨፈ በሚያስቸግርበት ጊዜ በመቃወም "ክርስቲያን ሁሉ በአበው ሃይማኖት ጽኑ፣ እግዚአብሔር በአካል ሦስት በመለኰት፣ በአገዛዝ፣በሥልጣን፣ … አንድ ነው እንጂ ከዚህ ውጭ አይደለም፤ በሃይማኖታችሁ ጽኑ" እያሉ ቀን ከሠራዊቱ ጋር እንደሠራዊት እያስተማሩ፣ ያመኑትን እያጠመቁ፣ ቀድሰው ሥጋወደሙን እያቀበሉ፣ በትግሃ ሌሊት በጸሎትና በስግደት የክርስቶስን መከራ በማሰብ ፊታቸውን እየጸፋ በከፍተኛ ተጋድሎ የሃይማኖትን መንገድ በፋናቸው አሳይተዋል (ኤፌ. 4÷5-6)፡፡ አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ እያሉም አስተምረዋል፡፡
❤ በዚያን ዘመን ዐፄ ሱስንዮስ ነግሠው በነበሩበት ወቅት ከፖርቹጋል ጋር ግንኙነት ነበራቸው፡፡ ይህንንም ግንኙነታቸውን ለማዳበርና ለማጠናከር የፖርቹጋል ሴት እንዲያጩ ተገደዱ፤ ዐፄ ሱስንዮስ በዚህ ምክንያት ሃይማኖታቸውን ለውጠው ሲኖሩ በገዳማት የሚኖሩ መነኰሳትና በኢትዮጰያ አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት የሚኖሩ ሊቃውንተ ቤተ ክርስትያን ስለተቃወሟቸው መነኰሳት ካሉበት ከበኣታቸው ሊቃውንትን ከተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት እና አድባራት እያደኑ ያስፈጇቸው እንደነበር ታሪክ ያስረዳናል፡፡ ለምሳሌ ከቅዱሳት አንስት እነ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን የመሳሰሉ ቅዱሳን በዚያን ጊዜ ነው የተሠውት፡፡
❤ በዚህን ጊዜ ጻድቁ አባ ምእመነ ድንግል ከ40 ልጆቻቸውና ደቀ መዛሙርቶቻቸው ጋር ጩጊ ቅድስት ማርያም ገዳምን ጥግ ከለላ አድርገው መኖር ጀመሩ፡፡ በዚህም ቦታ ዋሻ ፈልፍለው በጸሎትና በተጋድሎ በሚኖሩበት ወቅት የነገሩትን የማይረሳ የለመኑትን የማይነሳ ምስጋና የባህርይ ገንዘቡ የሆነ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ በታላቅ ቦታ እናቱን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክትን፣ ነቢያትን፣ ሐዋርያትን፣ ሰማዕታትን እና ቅዱሳን አበውን፣ አስከትሎ "ወዳጄ የአባቴ ወዳጅ የመንፈስ ቅዱስ ወዳጅ ሰላም ላንተ ይሁን" አላቸው፡፡ ጻድቁ ይህን የመሰለ ብርሃንና ልዩ ንውጽውጽታ በማየት ተደንቀው አምላካቸውን እጅ ነስተው (ሰግደው) ለእመቤታችን ለቅድስት ማርያም ሰግደውና እጅ ነስተው ድንቅ ነገር በማየታቸው በሚደሰቱበት ጊዜ ጌታችን በእጅ አንሥቶ አቅፎ ስሟቸው የሚከተለውን ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡
"በዚህ ቦታ አንተ በተጋደልክበት ማኀበር መሥርቶ የሚኖረውንና የሚማፀነውን ሁሉ አኗኗኑ እንደ ሰማይ መላእክት ይሆንለታል፡፡ ወደዚህ ቦታ ሥጋዬንና ደሜን አምኖ የተቀበለውን ከቅዱሳን መላእክት ጋር በአባቴ ክብር በመምጣበት ጊዜ ፍጹም ገሃነመ እሳትን አላሳየውም፡፡ ምንም ኃጥያት ቢሠራ አምላከ ምዕመነ ድንግል ይምረኛል ብሎ በፍጹም እምነት የመጣውን ወደ ተወለድኩባት ቤተልሔም፣ ወደ አደኩባት ናዝሬት፣ ወደ አስተማርኩባት ደብረዘይት፣ ወደተጠመኩባት ዮርዳኖስ እና ወደተሰቀልኩበት ቀራንዮ እንደሄደ እቆጥርለታለሁ" በማለት ይህን አማናዊ ቃል ኪዳን ከሰጣቸው በኋላ ካሉበት ከበኣታቸው በስተቀኝ በኩል የኪዳነ ምሕረትን ጸበል በስተግራ የዮርዳኖስ ጸበል አፍልቆላቸዋል፡፡(ገላ.3÷15-18)
❤ ታላቁ ጻድቅ አቡነ ምእመነ ድንግል ይህን ቃልኪዳን በተቀበሉበት በዚህ ቅዱስ ሥፍራቸው ተጋደሎአቸውን በበለጠ ሲጋደሉ "ፈዋሴ ድውያን" ተብለዋል፡፡ ይኽውም ዐፄ ሱስንዮስ ሃይማኖታቸውን ወደ ካቶሊክ ለውጠው እንዲሁም "የሃገሪቷ ሃይማኖት እንዲለወጥ" በማለታቸው ምክንያት 140 ሺህ ቅዱሳን አባቶች ይህን ተቃውመው መስቀል እንደጨበጡ ስለሃይማኖታቸው በሰማዕትነት ሲጋደሉ ንጉሡ በቅዱሳኑ ላይ ባደረሱት ጭቃኔ የተሞላበት ጥፋት ምላሳቸው ተጎልጉሎ ነበር፡፡ በዚሁ ጊዜም በጣም ደግና ብልህ የነበሩት ልጃቸው ዐፄ ፋሲል ስለ አባታቸው መዳን በጣም ተጨንቀው መፍትሔ ለማግኘት የሚነግራቸው ብቁ ሰው ሲያፈላልጉ አንድ የበቁ አባት ከሞት የተረፉ፣ ከጥላ ያረፉ፣ በዕድሜ የገፉ፣ ግዝቱን ለመፍታት የማይችሉ ፣ አንድም ወለቴ የተባለችው አገልጋያቸውና የአቡነ ምእመነ ድንግል ክብር እንዲገለጽ የተረዱ ታላቅ ባሕታዊ ተገኙና "ከዚያው ከቤትህ ከሴት ሠራተኛ አገልጋዮችህ ውስጥ አንዲት የበቃች አለችና እርሷ መፍትሄውን ትነግርሃለች" ብለው አመላከቷቸው፡፡
ይህችውም ወለቴ የተባለች ስትሆን ከብቃቷ የተነሳ በክንፍ እንደ መላእክት እየበረረች ስትሄድ ያያት ሁሉ "አሞርዬ" ይሏታል፡፡ እሷም እስከ ዛሬ ድረስ በሕቡዕ ተሰውራ ትኖራለች፡፡ የመጸለያ በኣቷ እና ገዳሟ ባሕርዳር ዙርያ አዴት አካባቢ አዳማ ጊዮርጊስ አጠገብ ነው፡፡
ዐፄ ፋሲልም በየበሩ ወታደሮችን አሰልፈው ሲያስጠብቁ ይህችው አገልጋይ በጸሎት አድራ ስትመለስ አግኝታው ይዘው አቀረቧት፤ በዚህ ጊዜ በብዙ ማግባባት ቢጠይቋት ምንም እንደማታውቅ ተራ ኃጢያተኛ እንደሆነች ገለጠችላቸው፡፡ ሆኖም በብዙ ልመና ሲማጸኗት "ድንግል መነኲሴ ቢገኝ አባታቸውን እንደሚፈውስላቸውና ዐፄ ፋሲልም እንደሚነግሡ" ነገረቻቸው፡፡
❤ እኛ ሁላችን የክርስቲያን ወገኞች አምላክን ለወለደች ለእመቤታችን ለከበረች ድንግል ማርያም ለመታሰቢያዋ መንፈሳዊ በዓልን ልናደርግ ይገባናል ስለ እርሷ ለአዳምና ለሁላችን ለልጆቹ ድኅነት ሁኖአልና ይህንንም በዓል ለማድረግ የሚተጋ የተመሰገነ ነው። እርሷን ለመረጣትና ለወደዳት በሥጋም እንድትወልደው ላደረገ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእርሷ በእመቤታችን ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_ጢሞቴዎስ፦ ይህም ቅዱስ አስቀድሞ ከእንዴናው ገዥ ከአርያኖስ ጭፍራዎች ውስጥ ነበር ሰው ሁሉ ጣዖታትን እንዲያመልክ የሚያዝ የዲዮቅልጥያኖስ የመልእክት ደብዳቤ በተነበበ ጊዜ ይህም ቅዱስ ከሕዝቡ መካከል ተነሥቶ የንጉሡን ደብዳቤ ወስዶ "ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም" ብሎ የከሀዲውን ንጉሥ የመልክት ደብዳቤ ቀደደ።
❤ መኰንኑም ድፍረቱን አይቶ ወደርሱ ገሥግሦ ሔደና የራሱን ጠጉር ይዞ አንሥቶ በምድር ላይ ጣለው ታላቅ ድብደባም እንዲደበድቡት አዘዘ ሁለተኛም ሁለመናው እስቲደቅ እንዲደቁሱት አዘዘ እርሱም "የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እርዳኝ" እያለ ይጮኽ ነበር። ጌታችንም ትዕግሥቱን አይቶ መልአኩን ልኮ ከሥቃዩ አድኖ ጤነኛ አደረገው ወደ መኰንኑም ቀርቦ "ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከአንዱ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለምና አንተ ከሀዲ እፈር" አለው። ያን ጊዜም ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው በመጋዝም መግዞ ሰቀለው ከዚያም በኋላ ሥጋው እንደ ሰም ቀልጦ እንደ ውኃ እስቲፈስ በብረት ምጣድ ውስጥ አበሰለው ከከተማ ውጪም ጣሉት።
❤ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለምንም ጉዳት አንሥቶ ጤነኛ አደረገው። ወደ መኰንኑም ተመልሶ "ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለምና አንተ ከሀዲ እፈር" ብሎ ጮኸ። ይህንንም ድንቅ ተአምር አይተው ቁጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ሞቱ።
❤ መኰንኑም ማሠቃየቱ በሰለቸው ጊዜ ሰኔ 21 ቀን ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። የድል አድራጊነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በድል አድራጊ ሰማዕት በቅዱስ ጢሞቴዎስ አማላጅነት ይማረን በረከቱ ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የእስክንድር_አራተኛ_ሊቀ_ጳጳሳት
#አባ_ከላድያኖስ፦ ይህም ቅዱስ በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቀ እርሱም ዲቁናን ሾመው ደግሞም ቅስና ሾመው የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርትና ሕግ ጠንቅቆ ተማረ።
❤ አባ ሜልዮስ በዐረፈ ጊዜ ይህን አባት መርጠው በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ዐሥራ አንድ ዓመት ያህል በቀናች ሃይማኖት እያጸናቸው በትምህርት በምክር ሁሉ እንደሚገባ የክርስቶስን መንጋዎች ጠበቀ። ልዑል እግዚአብሔርም አገልግሎ ሰኔ 21 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ከላድያኖስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 21 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወንሰግድ ውስተ መካነ ኀበ ቆመ እግረ እግዚእነ። ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ። አንተ ወታቦተ መቅደስከ"። መዝ131፥7-8። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥39-57።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል። እግዚአብሔር ውስተ ማእከላ ኢትትሀወክ። ወይረድኣ እግዚአብሔር ፍጽመ"። መዝ 44፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፊ 2፥13-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 2፥4-11 እና የሐዋ ሥራ 1፥12-15። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 16፥13-20። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ። መልካም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሰኔ ፳፩ (21) ቀን።
❤ እንኳን #ለአዳም_ለዘር_ሁሉ_ድኅነት ለተደረገባት #አምላክን_ለወለደች_ለእመቤታችን_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም በስሟ የተሠራችው የመጀመርያ #ቤተ_ክርስቲያን_በልጇ_በወዳጇ_እጅ #ለተቀደሰችበት_ለከበረችበት_ዓመታዊ_በዐሏና በዓለም ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን መታነጽ መታሰቢያ ታላቅ በዐል፣ እመቤታችን በጌታችን መቃብር በጎልጎታ ለሰው ልጆች በሙሉ ምሕረት ለጸለየችበት፣ #እመቤታችን_ለቅዱስ_ባስልዮስ_ዘቂሣርያ ለተገለጠችለትና ሥዕሏን እንዲያሠራላት ለነገረችውና ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ላደረገች፣ ለሐዋርያው #ቅዱስ_ቶማስ በመሸታ ቤት ባረድዋት በአንዲት ሴት ላይ ላደረገው ተአምር መታሰቢያ በዐል፣ ለምስር አገር ለሆነ #ለቅዱስ_ጢሞቴዎስ_ሰማዕትነት_ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና #ለእስክድርያ_አራተኛ_ሊቀ_ጳጳስ #ለአባ_ከላድያኖስ_ለዕረፍት_በዐል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ሜሮን_ከተገኘችበትና_የአስታፍን_ዐፅም ከተገኘችበት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #በዚች_ዕለት_የአዳምና_የዘሩ_ድኅነት የተደረገባት #አምላክን_የወለደች_የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የታላቁ በዓል መታሰቢያና በዓለም ሁሉ የቤተ ክርስቲያን መታነፅ መታሰቢያ ነው። ከሁሉ አስቀድሞ ያቺ ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያት ዘመን ብቻዋን ታነፀች።
❤ ይኸውም ቅዱሳን ጳውሎስና በርናባስ በአሕዛብ ውስጥ በሰበኩ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ከሰዎች ቤቶች በቀር ቅዱስ ቊርባንን የሚቀበሉበት ቤተ ክርስቲያንም አልነበራቸውም ነበር። ስለዚህም ወደ ቅዱሳን ጴጥሮስና ወደ ሐዋርያት ሁሉ ስለ ቤተ ክርስቲያን መታነፅ ጉዳይ እየለመኑ መልእክትን ላኩ። ሐዋርያትም እንዲ ብለው መለሱላቸው "ክብር ይግባውና ያለ ጌታችን ፈቃድ እኛ ምንም ምን አንሠራም። ነገር ግን የምንሠራውን እስኪያስረዳን ድረስ ወደ እግዚአብሔር እየጸለዩና እየማለዱ አንድ ሱባኤ ይጾሙ ዘንድ ወደ ሃይማኖት የተመለሱ አሕዛብን እዘዙአቸው" እንዲህም አዘዙአቸው።
❤ በሱባኤውም ፍጻሜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾላቸው ሐዋርያትም ሁሉ ከየአገሮች ሁሉ እስከ ፊልጵስዩስ በደመና ሰበሰባቸው ከእርሳቸውም ጋር ቅዱሳን ጳውሎስና በርባስ ነበሩ ጌታችንም ባረካቸው እንዲህም ብሎ ነገራቸው "ይቺ ዕለት በእናቴ በማርያም ስም በአራቱ ማእዘነ ዓለም አብያተ ክርስቲናት እንዲታነፁ የፈቀድኩባት ናት"። ይህንንም ብሎ በከተማዋ በስተ ምሥራቅ በኵል አወጣቸው የቤተ ክርስቲያኒቱም ቦታና መሠረቷን ወሰነላቸው ከእርሳቸውም ጋራ የእግዚአብሔር ኃይል ነበረ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃዋ እስከ ተፈጸመ ድረስ ሦስቱ ደንጊያዎች በሐዋርያት እጆች ውስጥ ይለመልሙ ነበር ጌታችንም ንዋየ ቅዱሳቷን አልባሳትዋንና መሠዊያዋን አዘጋጀ።
❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን እጁን በቅዱስ ጴጥሮስ ራስ ላይ ጭኖ በአራቱ ማዕዘነ ዓለም ውስጥ "አርሳይሮስ" ብሎ ሾመው ይህም ሊቀ ጳጳሳት ማለት ነው "ለሐዋርያት አለቃ ለቅዱስ ጴጥሮስ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የጳጳሳት አለቃ ይሆን ዘንድ ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል" እያሉ ሰማያውያን መላእክትና ምድራውያን ሰዎች ሦስት ጊዜ አሰምተው ተናገሩ።
❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን ሐዋርያትን የቊርባኑን ቅዳሴ ሥርዓት ያከናውኑ ዘንድ ለሕዝቡም ሥጋውን ደሙን ያቀብሏቸው ዘንድ አዘዛቸው እንዲህም የሚል አለ ራሱ መድኃኒታችን ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ለሐዋርያት አቀበላቸው። እንዲህም አላቸው "በዚች ቀን የእጃቸውን ሥራ እንዳይሠሩ ሕዝቡን ሁሉ እዘዙአቸው ይኸውም በሰኔ ወር ሃያ አንድ ቀን ነው"። ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ከእርሳቸው ዘንድ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ከዚያች ቀን ጀምሮ አባቶቻችን ሐዋርያት በዓለሙ ሁሉ ውስጥ አምላክን በወለደች በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን የሚያንሳንፁ ሆኑ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #በቂሣርያው_ሊቀ_ጳጳሳት_በአባ_ባስልዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን በሠራ ጊዜ በውጡ የእመቤታችን የማርያምን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ሠሌዳ ፈለገ ሰዎችም በአንድ ባለጸጋ ዘንድ ስለ አለ አንድ መልካም ሠሌዳ ነገሩት።
❤ ቅዱስ ባስልዮስም ሠሌዳውን እንዲሰጠው ወደ ባለጸጋው ላከ፤ ባለጸጋውም "ይህ ሠሌዳ ለልጆቼ ነው" አለ እንጂ ፈቃደኛ አልሆነም ከዚያም አልፎ በመድፈር በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ላይ የስድብ ቃል ተናገረ ወዲያውኑም በድንገት ወድቆ ሞተ ልጆቹም ፈሩ ያንንም ሠሌዳ ከብዙ ወርቅና ዕንቊ ጋራ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አምጥተው የአባታቸውን በደል ያቃልልለት ዘንድ ለመኑት። ቅዱስ ባስልዮስም ያንን ሠሌዳ ወስዶ የእመቤታችንን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ለሠዒሊ ሰጠው።
❤ እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም በሌሊት ራእይ ለቅዱስ ባስልዮስ ተገለጸችለት ሥዕሏንም በዚያ ሠሌዳ እንዳይሥል ከለከለችው። ከዐመፀኛም ሰው እጅ ወስዶታልና። እጅግም ያማረ የእመቤታችን ሥዕሏ የተሣለበት የሁለት ደናግልም ሥዕል ያንዲቱ በቀኝ ያንዲቱ በግራ ሆኖ የተሣለበት ቀይ ሠሌዳ ያለበትን ቦታ ነገረችው። ቅዱስ ባስልዮስም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ አመለከተችው ወደዚያ ቦታ ሔደ ያንንም ሠሌዳ አገኘው ወደዚያች ቤተ ክርስቲያንም በታላቅ ደስታ አመጣው።
❤ ከዚህም በኋላ ዳግመኛ በአንድ ጣዖት ቤት ሁለት ምሰሶዎች እንዳሉ አስረዳችው እነርሱንም አምጥቶ በመቅደሱ ፊት ለፊት እንዲአቆማቸው በላያቸውም ሥዕሏን እንዲያኖር አዘዘችው። ቅዱስ ባስልዮስም እነዚያን ምሰሶዎች ያመጣቸው ዘንድ ሔደ መሠርያኑም ሊከለክሉት ፈለጉ ጌታችንም ኃይላቸውን ደመሰሰ እነዚያንም ምሰሶዎች አምጥቶ በቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት አቆማቸው በላያቸውም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕሏን አስቀመጠ እግዚአብሔርም ከእነዚያ ምሰሶዎች በታች የውኃ ምንጭ ጠበል አፈለቀ በውስጥዋም የሚታጠብ ሁሉ ከአለበት ደዌ ሁሉ የሚድን ሆነ። እንዲሁም ከእመቤታችን ማርያም ሥዕል በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውስ የዘይት ቅባት ፈሰሰ ይህ ሁሉ የሆነ የእመቤታችን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት በሰኔ ዘር በሃያ አንድ ቀን ነው።
❤ በዚያችም ቀን እንዲህ ሆነ አንዲት ሴት መጥታ ታጠበች ወዲያውኑም ሁለመናዋ በለምጽ ተሸፈነ ቅዱስ ባስልዮስም ወደርሱ አስቀርቦ በእርሷ ላይ የሆነውን ጠየቃት እርሷም የእኅቷን ባል እንደወደደችና እኅቷን በመርዝ ገድላ እንዳገባችው ነገረችው። ቅዱስ ባስልዮስም "ታላላቅ ሦስት ኃጢአቶችን ሠራሽ ግን ወደ እግዚአብሔር ንስሐ ግቢ ምንአልባት በደልሽን ይቅር ይልሽ እንደ ሆነ" አላት በዚያን ጊዜም ምድር ተሠንጥቃ እንደ ዳታን ዋጠቻት እርሷ የረከሰች ስትሆን ቤተ ክርስቲያን መግባትን ደፍራለችና።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሰኔ ፳ (20) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ መሰቀልህን በቅዱሳት መጻሕፍት ሰማሁ ይኽን በዐይኔ አሳየኝ በማለት #መድኃኔዓለምን_ለጠየቁት_እሱም ለገለጸላቸው፤ የንጉሡን መልዕክተኞች ከንጉሡ ቤት እንገናኝ በማለት መልዕክተኞቹ ዘጠኝ ቀን ተጉዘው ሲደርሱ እሳቸው ቀድመዋቸው ንጉሡ ቤት ለተገኙት #አቡነ_ዐሥራ_ወልድ_ለልደታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የአቡነ_ዐሥራተ_ወልድ_ልደት፦ የትውልድ ሀገሩ ከዳሞት አውራጃ ልዩ ስሟ እነሴ ትባላለች የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ፃማ ክርስቶስ የእናቱ ስሙ ጽጌ ማርያም ይባላል። ሁለቱም ደጋጎች በእግዚአብሔር ሕግና በበጎ ሥራም ተስማምተው ይኖሩ ነበር እንደ ካህኑ ቅዱስ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ዘወትር ወደ እግዚአብሔርና ወደ ድንግል ማርያም ይለምኑ ነበር። ያውም በጾምና በጸሎት ተወስኖ ለእግዚአብሔር የሚታዘዝ በጸሎቱ ሰው የሚጠቅም በጻድቃንም ዘንድ የተመረጠ ልጅ ይመኙ ነበር። እነርሱም እግዚአብሔር የሚፈሩ በሀብት የበለጸጉ ነበርሩ። ለድሆችና ለሚስኪኖች አብዝተው ይመጸውቱ ነበር እስከ ዘጠኝ ሰዓትም እየጾሙ ያለ ድሆችና ምስኪኖች ሁል ጊዜ አይበሉም ነበር።
❤ ከዕለታት በአንድ ቀን የእግዚአብሔር ሰው ለጽጌ ማርያም እንዲህ አላት "ዝናው በአራቱ መዓዘነ ዓለም ሁሉ የሚደርስ በሕይወተ ሥጋ እያለ የብዙ ሰዎች ነፍስን በጸሎቱ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የሚያወጣ ወደ ሰማይም ወጥቶ የሥላሴን የሚያይ ልጅ ትወልጂ ዘንድ አለሽና ደስ ይበልሽ" አላት ቅድስት ጽጌ ማርያም ከእግዚአብሔር ሰው ይህን በሰማች ጊዜ "የፈጣሪዬ ፈቃድ ከሆነ" ብላ በልቡናዋም ተደሰተች።
❤ ከጥቂት ቀናትም በኋላ ፀንሳ ሰኔ በባተ ሃያ (20) ቀን ወለደች በእናትና በአባቱ ቤትም ታላቅ ደስታ ሁኖ ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ለዘመዶቻቸውና ለጎረቤቶቻቸው ታላቅ የምሳ ግብዣ አደረጉ እነርሱም በልተው ከጠገቡ በኋላ እነርሱንም ሕፃኑንም መረቋቸው በ40ኛው ቀንም "ዐሥራተ ወልድ" አሉት። ሥራው ልዩና ድንቅ የሆነ እግዚአብሔር ግን በእርሱ ላይ የማያልቅ ይቅርታውን አሳድሮ በበረከት ፍፁም ያደረገው ይህ ቅዱስ ልጅ ዐሥራተ ወልድን ሰጣቸው በእነርሱም ዘንድ የጽድቅን ሥራ ገለጠ። እርሱም በተወለደ በስምንተኛ ቀን ተነስቶ በሰዎች መካከል አንድ ሰዓት ያህል ቆሞ እንዲህ አለ፦ "ለአብ ምስጋና ይገባል፣ ለወልድም ምስጋና ይገባል፣ ለመንፈስም ቅዱስ ምስጋና ይገባል" በዚህም በዘመኑ ሁሉ ለጽድቅ ሥራ እንደሚነሣሣ ያመለክታል የእናቱ ጡት ሲጠባም ከቀኝ በቀር አይጠባም በዚህም የመንፈሳዊ ውሃ በቀር እንደማይጠጣ ይገልጣል። ይኸውም የእግዚአብሔር ቃል ነው።
❤ ከተወለደም በኋላ ከእናት ከአባቱ ጋር በሁሉ ነገር ቀንና ሌሊት አየታዘዘ የኖረው ዐሥራ ሁለት ዓመት ብቻ ነው ከዱር ዕንጨት ለቅሞ የሚያመጣበት ጊዜ ነበር ውሃም ከወንዝ እየቀዳ የወላጆቹን እግር የሚያጥብበት ጊዜም ነበር። እንዲህ አድርገው እየመረቁ መልካም አስተዳደግ በምክርና በተግሣፅ አሳደጉት። የዚህም ቅዱስ አቡነ ዐሥራተ ወልድ ዕድሜው ዐሥራ ሁለቱ ዓመት ከሆነው በኋላ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሣሥታ ቀሰቀሰችውና ብሉያትንና ሐዲሳትን የዳዊትን መዝሙር ይማር ዘንድ ወደ አቡነ ተጠምቀ መድኅን ሄደ። ከአባታችን አቡነ ዐሥራተ ወልደ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ዐሥራተ ወልድ።
❤ ከዚያም በኋላ የሶርያ ንጉሥ ወልደ አዴር ሠራዊቱን ሁሉ ሰበሰበና ወጥቶ ሰማርያን ከበባት፡፡ በሰማርያም ታላቅ ራብ ሆኖ ነበር፤ እነሆም፥ የአህያ ራስ በአምሳ ብር፥ የርግብም ኩስ የጎሞር ስምንተኛ የሚሆን በአምስት ብር እስኪሸጥ ድረስ በሀገራቸው የሶርያ ሰዎች ሰፍረው ተቀመጡ፡፡ በዚህም ጊዜ እናት ልጇን ቀቅላ እስክትበላ ድረስ እጅግ አሠቃቂ ታላቅ ርሃብ ሆነ፡፡ ይህም ክፉ የርሃብ ዘመን በነቢዩ ኤልሳዕ ጸሎት በአንዲት ቀን ተለውጦ የጥጋብ ዘመን ሆኗል፡፡ 2ኛ ነገ 6፥8-33፣ 7፥1-20፡፡ ኤልሳዕም በዘመኑ ትንቢትን እየተናገረ እጅግ ታላላቅ ተአምራን እያደረገ እግዚአብሔርንም ሕዝቡንም ሲያገለግል ከኖረ በኋላ ሰኔ 20 ቀን ዐርፏል፡፡ ከሞተም በኋላ ዐፅሙ የሞተን ሰው አሥነቷል፡፡ 2ኛ ነገ 13፡21፡፡ ይኸውም የሞአብ ሰዎች አገራቸውን ከበው ሳለ አንድ ሰው ሞቶ ሊቀብሩት ሲወስዱት አደጋ ጣዮች አዩአቸው፡፡ እነርሱም ደንግጠው ሬሳውን በአልሳዕ መቃብር ላይ ጣሉት፡፡ በዚህም ጊዜ ሬሳው የአልሳዕ ዐፅም በነካው ጊዜ አፈፍ ብሎ ከሞት ተነሥቶ በእግሮቹ ቆሟል፡፡
❤ ይህም ነቢይ በአራት ነገሥታት ዘመን ትንቢት ተናገረ እሊህም ኢዮራም፣ አካዝያስ ኢዩና ዮአስ ናቸው የትንቢትም ዘመን ከሃምሳ ዓመት በላይ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም ከመምጣቱ አስቀድሞ ትንቢት ተናገረ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ በቅዱስ ኤሌሳዕ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 20 ስንክሳርና መዝገበ ቅዱሳን።
