🩸
ሰሙነ ሕማማት 🩸
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዕለተ ትንሣኤ በፊት ያለውን ሳምንት "
ሰሙነ ሕማማት" በማለት ታከብረዋለች። "ሕማማት" የሚለው ቃል "ሐመ" ከሚለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን የዚህ ስያሜ መነሻም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መከራው፣ሕማሙና ሞቱ የሚዘከርበት ከአዳም እስከ ክርስቶስ የነበረው የዓመተ ፍዳ የዓመተ ኩነኔ ወቅትም የሚታሰብበት ስለሆነ "ሰሙነ ሕማማት" ተብሏል።
በዚህ ልዩ በሆነ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ያዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ሆኖ ሳለ ሕማማትን መቀበሉ ስለምን ነው ቢሉ፡-
☞ፍቅሩን ለመግለጽ፡- ለፍጥረቱ ይልቁንም ለሰው ልጆች ያለውን ፍቅሩን ይገልጽ ዘንድ(ዮሐ ፫÷፲፮) ምንም በደል ሳይኖርበት ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ(ዮሐ ፲፭÷፲፫)
☞የኃጢአትን ፍዳ ከባድነት ለማሳየት፡- እርሱ ጻድቅና ንጹህ ሆኖ ሳለ ሰውን ወዶ ይህን ያህል መከራ ከተቀበለ ሰው ኃጢአት በመሥራት ቢመላለስ የኃጢአትን ውጤት ከባድነት ያስተምረናል፡፡ ራሱ ጌታችንም ከጲላጦስ ግቢ እስከ ቀራንዮ አደባባይ መስቀል ተሸክሞ ሲንገላታ ላለቀሱለት የኢየሩሳሌም እናቶች <<በእርጥብ እንጨት የሚያደርጉ ከሆነ በደረቀውስ እንዴት ይሆን>> በማለት ገልጾለታል፡፡ (ሉቃ ፳፫÷፳፪)
☞ቤዛ ለመሆን፡- በኦሪት ዘመን ሰዎች ለሠሩት ኃጢአት ኃጢአታቸውን ለማስተሰርይ ነውር የሌለበትን በግ ቤዛ እንዲሆናቸው መስዋዕት ያቀርቡ ነበር ይህ ግን ከአዳም የተሰወረውን ኃጢአት ማስቀረት ስላልቻሉ ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሁኖ መጣ <<እነሆ የእግዚአብሔር በግ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ>>(ዮሐ ፪÷፳፮)
☞እርግማናችንን ለማስቀረት፡- <<በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፏልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን>>(ገላ ፫÷፲፫) በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንደጻፈው እርግማናችንን ተሸክሞ ሕማማትን መቀበሉ የቀድሞው ኃጢአት ምንም ያህል ከባድ ቢሆን በታላቅ መስዋዕትነት እንዳስቀረልን ሊያስተምረን ነው፡፡ (ዘዳ ፳፩÷፳፫)
☞የድኅነታችንን ክቡርነት /ውድነት/ ሊያስረዳን ፡- ድኅነታችንን የእግዚአብሔር ልጅ ደሙን እስኪያፈስለት ድረስ እጅግ ውድ መሆኑን ሊያስተምረን፡፡ (ራዕ ፭÷፱)
@Ethiopian_Orthodox
ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡
በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት :
ሊሰሩ ያልተፈቀዱ በርካታ ናቸው:: በመስቀል መባረክ፣ ማማተብ፣ መሳቅ፣ መሳሳም፣ ከሴት ጋር መገናኘት(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ቁጥር 593)፣ ኑዛዜ መፈጸም ፈጽሞ የተከለከለ ሲሆን የ5500ው የጨለማ ዘመን መታሰቢያ በመሆኑ መንበሩ በጥቁር ልብስ ይሸፈናል ካሕናትም ጥቁር ይለብሳሉ:: በዚህ ሳምንት ለሞተ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይለትም፣ ክርስትናም እንዲሁ አይፈጸምም:: "እግዚአብሔር ይፍታህ" አይባልም(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ቁጥር 600)፤ ሳምንቱ የሚታሰበው ሕማሙን ሞቱን በማሰብና በስግደት ነው::
የግዝት በዓላት(12፣21 እና 29) እንኳ ይሰገድባቸዋል:: የዚህ ሳምንት ጾም የቻለ ሁለት ሁለት ቀን ያልቻለ
እስከ ጀንበር ግባት ድረስ ነው:: ምግቡም ቆሎ ዳቦ የላመ የጣመ ያልሆነ ደረቁን በበርበሬ ነው፤ መጠጡም ንጹህ ውኃ ነው:: ጠጅ ያንቆረቆረ ጮማ የቆረጠ እድል ፈንታው ጽዋእ ተርታው በጌታ ሞት ከተደሰቱት ከአይሁድ ጋር ነው።(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ቁጥር 578)
ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም። ጸሎቱ ውዳሴማርያም፣ አንቀጸ ብርሃን፣ መልክአ ሕማማትና መዝሙረ ዳዊት ናቸው። የቅዱሳን መልክአ መልክእ አይጸለይም።
ስናጠቃልለው የተከለከሉ ነገሮች ምን ምን ናቸው ካሉ፡
1. እጅ ተጨባብጦ ሰላምታ መባባል፣ መሳሳም
2. ሩካቤ ሥጋ ማድረግ
3. መስቀል ማሳለም እና መሳለም
4. ክርስትና ማስነሣት
5. ለሙታን ፍትሐት ማድረግ
6. ክህነት መስጠት
7. የላመ የጣመ ምግብ መመገብ
8. መሳቅ መጫወት መጨፈር
9. አብዝቶ ጠግቦ መመገብ
10. መስከር ወዘተ ናቸው፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡
@Ethiopian_Orthodox
የሰሙነ ሕማማት ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ክንዋኔዎች:
፩. አለመሳሳም ፡- ከላይ እንዳየነው በሰሙነ ሕማማት የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች መስቀል እንደማይሳለሙት ሁሉ መጨባበጥ፣ መሳሳምን የትክሻ ሰላምታ መለዋወጥን አይፈጽሙም፡፡ ሰላምታ የማንለዋወጥበት ምክንያት አይሁድ ጌታን ለመስቀል ሰኞ እና ማግሰኞ መከሩ አልሰመረላቸውም፡፡ ምክራቸው የተፈጸመው ረቡዕ ነው፡፡ ስለዚህ አይሁድ እያንሾካሾኩ እንስቀለው ፤እንግደለው ብለው ይማከሩ ነበር፡፡ በዘመነ ፍዳ ወቅት ሠላምና ፍቅር አለመኖሩን የሚገልፅልን በመሆኑ ያንን ለማስታወስ ሰላምታ አንለዋወጥም፡፡
፪. ሕፅበተ እግር፡- ጌታ በፍጹም ትህትና የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጠበበት፣ ከሐዋርያት ጋር ግብር የገባበትና የክርስትና ህይወት ማሕተም የሆነውን ምስጢረ ቁርባን ያከናወነበት ዕለት ነው። ጸሎተ ሐሙስ ሕፅበተ እግር ጌታችን በዚህ ዕለተ እናንተ ለወንድማችሁ እንዲሁ አድርጎ ለማለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት የተሰጠ ምሳሌ ነው፡፡
፫. ጉልባን እና ቄጠማ ፡- ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጀና የጸሎት ሐመስ እለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ የጉልባን ትውፊት እስራኤላውያን ከግብጽ ተሰደው በሚነጡበት ጊዜ በችኮላ ስለነበር አቡክተው ጋግረው መብላት ያለመቻላቸውን ሁኔታ ያመለክታል፡፡ ያን ጊዜ ያልቦካው ሊጥ እያጋገሩ ቂጣ መብላት ንፎሮም ቀቅለው ስንቅ መያዝ ተግባራቸው ነበር፡፡ ይህን ለማሰብ በሰሙነ ሕማማት ቂጣና ጉልባን በማዘጋጀት በዓል ይታሰባል፡፡ [በጸሎተ ሐሙስ ዕለት በስፋት የምናየው ይሆናል።]
ቄጠማ (ቀጤማ)፡- በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱን ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለ አዋዲ/ እየመቱ "ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሳኤሁ አግሃደ" የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠ እና ትንሳኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመኑም ለቤተ ክርስቲን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ ቀጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሰሩበትን ድርጊት የሚያስተውስ ነው፡፡ በዚህ እለት ልብስ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲቆናትን ቄጠማ ተሸክመው ቃጭል ሲቃጭሉ መታየታቸው እለተ ትንሳኤውን ለምዕመናን ትልቅ ብስራት ነው።