ru
Feedback
Sinksar tube(ስንክሳር)

Sinksar tube(ስንክሳር)

Открыть в Telegram

እኔ ቅዱስ ነኛና ቅዱሳን ሁኑ 1ጴጥ 1:15

Больше
Страна не указанаКатегория не указана
2 497
Подписчики
-1424 часа
+1087 дней
+38330 дней
Архив постов
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞ ❖ ሰኔ ፬ ❖ ✞✞✞ እንኩዋን ለታላቁዋ ሰማዕት "ቅድስት ሶፍያ" እና ለቅዱስ "ዮሐንስ ዘሐራቅሊ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞ +*" #ሶፍያ (SOPHIA) "*+ =>ሶፍያ ("ያ" የሚለው ላልቶ ይነበብ) በቀደመው ዘመን በነበሩ ክርስቲያኖች ዘንድ ተወዳጅ ስም ነበር:: ዛሬ ብዙ አሕዛብ ሲጠሩበት ብንሰማም ትርጉሙ "ጥበበ ክርስቶስ" የሚል ነው:: በዚህ ስም የሚጠሩ አያሌ ቅዱሳት አንስት ሲኖሩ አንዷ ዛሬ ትከበራለች:: +*" ቅድስት ሶፍያ ተጋዳሊት "*+ =>ቅድስቷ የተወለደችው በምሥራቅ ሮም ግዛት ውስጥ በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: ዘመኑ የጭንቅ : የመከራ በመሆኑ ሕዝቡ በስደት ይኖር ነበር:: +የቅድስት ሶፍያ ወላጆች ክርስቲያኖች ናቸውና በመልካሙ መንገድ በንጽሕና አሳድገዋታል:: ባለጠጐች በመሆናቸው አገልጋይ ቀጥረውላት : ያማረ ቤት ሰርተውላት በዚያ ትኖር ነበር:: ሁሉ ያላት ብትሆንም ሁሉን ንቃ በጾምና በጸሎት ትኖር ነበር:: +ለዐቅመ ሔዋን በደረሰች ጊዜ ወላጆቿ ለከተማው መኮንን (ገዢ) ሊድሯት መሆኑን አወቀች:: ወደ ቤቷ ገብታ 100 ጊዜ ሰገደች:: ወደ ፈጣሪዋም ጸለየች:- "ጌታየ ሆይ! የዚህን ዓለም ቀንበር አታሸክመኝ:: አልችለውምና:: ያንተው ቀንበር ግን የፍቅር ነውና እችለዋለሁ" አለች:: +አገልጋዩዋን ጠርታ ብዙ ወይን አጠጥታት ልብስ ተቀያየሩ:: በሌሊትም ወጥታ ወደ በርሃ ሔደች:: ዓላማዋ ምናኔ ቢሆንም የእግዚአብሔር ፈቃዱ ግን ሌላ ነበር:: በመንገድ ብዙ ክርስቲያኖች በመከራ ብዛት ሲሰደዱ አገኘቻቸው:: እርሷ ስደትን አልመረጠችም:: +እያጠያየቀች "ሰው በላ" ከተባለው አረመኔ ንጉሥ ዲዮቅልጢያኖስ ደረሰች:: በንጉሡ ፊት ቀርባ "እኔ ክርስቲያን ነኝ" አለችው:: ንጉሡ ከመልኩዋ ማማርና ከድፍረቷ የተነሳ አደነቀ:: +ሊያባብላት: ሊያስፈራራትም ሞከረ:: ግን አልተሳካለትም:: ወታደሮቹ መሬት ላይ ጥለው ጦር ባለው የብረት ዘንግ ደብድበዋታልና ደም አካባቢውን አለበሰው:: መሬት ለመሬት እየጐተቱ እሥር ቤት ውስጥ ጣሏት:: ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ፈውሷት ሔደ:: +አንዴ በእሳት: አንዴም በስለት: ሌላ ጊዜም በግርፋት አሰቃዩዋት:: ከሃይማኖቷ ግን ሊያነቃንቁዋት አልቻሉም:: በመጨረሻ አንገቷን እንድትሰየፍ ንጉሡ አዘዘ:: ወታደሮቹም ፈጸሙት:: ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወርዶ ቅድስት ሶፍያን በክብር አሳረጋት:: "ስምሽን የጠራ: መታሰቢያሽን ያደረገ ምሕረትን ያገኛል" አላት:: +"+ ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ +"+ =>ቅዱሱ የነበረው በተመሳሳይ በዘመነ ሰማዕታት ነው:: አባቱ ዘካርያስ: እናቱ ኤልሳቤጥ: እርሱ ደግሞ ዮሐንስ ይባላል:: የሚገርም መንፈሳዊ ግጥጥሞሽ ነው:: የቅዱሱ ወላጆች የሃገረ ሐራቅሊ አስተዳዳሪዎች ሲሆኑ የተመሰከረላቸው ደጐች ነበሩ:: +ዘካርያስ አርፎ ዮሐንስ በመንበሩ የተቀመጠው ገና በ20 ዓመቱ ነበር:: በወቅቱ ከ2 አንዱን መምረጥ ነበረበት:: 1.ለጣኦት ሰግዶ በምድራዊ ክብሩ መቀጠል 2.ወይ ደግሞ በክርስትናው መሞት +ቅዱስ ዮሐንስ ግን ልቡ በክርስቶስ ፍቅር የተሞላ ነውና 2 ከባባድ ነገሮችን ፈጸመ:: በመጀመሪያ በአካባቢው ያሉ ጣዖት ቤቶችን አወደመ:: ቀጥሎ ወደ ንጉሡ ሔዶ በመኩዋንንቱ ፊት "ክርስቶስን የተውክ ሰነፍ" ብሎ ገሠጸው:: +ከዚህ በኋላ በቅዱሱ ላይ የተፈጸመው መከራ የሚነገር አይደለም:: ያላደረጉት ነገር አልነበረም:: እሳቱ: ስለቱ: ሰይፉ: መንኮራኩሩ . . . ከሁሉ የከፋው ግን ቆዳውን ገፈው በእሳት ጠብሰውታል:: እርሱ ግን ስለ ሃይማኖቱ ይሕንን ሁሉ ታግሶ በዚህች ቅን አንገቱን ተሰይፏል:: =>አምላካችን እግዚአብሔር ግፍዐ ሰማዕታትን አስቦ እኛን ከሚመጣው መከራ ሁሉ ይሰውረን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን:: =>ሰኔ 4 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅድስት ሶፍያ ተጋዳሊት ወሰማዕት 2.ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ (ሰማዕት) 3.ቅዱስ ሳኑሲ ሰማዕት 4.ቅድስት ማርያ ሰማዕት 5.ቅዱስ አርቃድዮስና ባልንጀሮቹ (ሰማዕታት) 6.ቅዱስ አሞን ሰማዕት ❖ወርኃዊ በዓላት 1፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ 2፡ ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ =>+"+ እንግዲሕ አትፍሯቸው:: የማይገለጥ የተከደነ: የማይታወቅም የተሠወረ ምንም የለምና:: በጨለማ የምነግራችሁን በብርሃን ተናገሩ:: በጀሮም የምትሰሙትን በሰገነት ላይ ስበኩ:: ሥጋንም የሚገድሉትን: ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ:: ይልቅስ ነፍስንም: ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ:: +"+ (ማቴ. 10:26) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች ይሄ በመንፈሳዊ ህይወታችን ለዛልን መንገድ ለሚጠፋን ክርስቲያኖች ማንነታችንን የምናስታውስበት የተግባራዊ ክርስትና እና በጉዞአችን የሚረዱን እና አርአያ የሚሆኑን የቅዱሳን ታሪክ የሚጻፍበት ቦታ ነው