ነገረ ክርስቶስ ምዕራፍ ፪ ክፍል ፭
#የምዕራፍ #ሁለት #መጨረሻ
፯) ንስጥሮስ:- የንስጥሮስ ክሕደት አንዱን ክርስቶስን ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ የሚል ነው። መጻሕፍት ኢየሱስ ክርስቶስ አንድ እንደሆነ ነገሩን እንጂ ከየትኛውም ቦታ ላይ ሁለት እንደሆነ አልነገሩንም። "ቃልም ሥጋ ሆነ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ ዐደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን" እንዲል (ዮሐ. ፩፣፲፬)። ንስጥሮስ አያዋሐድም አያገናዝብም። በተዋሕዶ የቃል ገንዘብ ለሥጋ የሥጋ ገንዘብ ለቃል እንደሆነ አያምንም። "ቃል እውነትን ተመልቶ በእኛ አደረ" የሚለውን መነሻ አድርጎ ምንታዌን (ሁለትነትን) አስተምሯል። ማደር ማለት እኛ በቤት ውስጥ እንደምናድረው ያለ ነው። እንደምታውቁት እኛ በቤት ስናድር የቤቱ የራሱ አካል እንዳለው የእኛም የራሳችን አካል አለን። በቤቱ እናድራለን እንጂ ቤቱን አንሆንም። ቤቱ የእኛ ገንዘብ ነው። እኛ ግን የቤቱ ገንዘብ አይደለንም። ምንም ዓይነት መገነዛዘብ ስለሌለን ተዋሕዶ የለንም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ከሁለት አካል አንድ አካል፣ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ የሆነ ስለሆነ አብሲማዳኮስ እየተባለ ይጠራል። ቅዱስ ጳውሎስም አዋሕዶ "በኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታንም ባነሣው በእግዚአብሔር አብ ሐዋርያ የሆነ እንጂ ከሰዎች ወይም በሰው ያልሆነ__" ብሎታል (ገላ. ፩፣፩-፪)። አንዱ ክርስቶስ አምላክም ሰውም ስለሆነ መካከለኛ እየተባለ ይጠራል። "አንድ እግዚአብሔር አለና፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ፥ ርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው" እንዲል (፩ኛ ጢሞ. ፪፣፭)። ከዚህም እንደምታዩት ክርስቶስን አንድ አለው እንጂ ሁለት አላለውም። ስለዚህ የንስጥሮስ ክሕደት ልብ ወለድ መሆኑ ታወቀ። እኛስ ከተዋሕዶ በኋላ ክርስቶስን ሁለት አንለውም። "ንሕነሰ ኢንቤ ክልኤቱ እምድኅረ ትድምርት" እንዳለ መምህረ ዓለም ቅዱስ ቄርሎስ (ድርሳን ፳፫)። የተሰቀለው የማርያም ልጅ፣ ያልሰተቀለው የአብ ልጅ ብለን ሁለት አናደርገውም። ቅዱስ ጳውሎስ አዋሕዶ "ዐውቀውስ ቢሆኑ የክብርን ጌታ ባልሰቀሉትም ነበር" ብሏል እንጂ ወልድን ከመሰቀል ውጭ አላደረገውም (፩ኛ ቆሮ. ፪፣፰)። ምራቁን እንትፍ ብሎ ጭቃ ያደረገውም፣ ዕውሩን ያዳነውም ያው አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው (ዮሐ. ፱፣፮-፯)። ክርስቶስን አምላክ ብቻ (ዕሩቅ ቃል) ነው እንዳንለው ለአምላክ ምራቅ የለውም። ሰው ብቻ (ዕሩቅ ብእሲ) ነው እንዳንለው ደግሞ ሰው በምራቁ ዕውርን ማዳን አይችልም። ስለዚህ አንዱን ክርስቶስን ለሁለት አንከፍለውም። እንደ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ አዋሕደን "ሞተ በሥጋ ወሐይወ በመንፈስ" እንለዋለን እንጂ (፩ኛ ጴጥ. ፫፣፲፰)። ሁለትነት በተዋሕዶ ጠፍቷል። እስመ ተዋሕዶ አእተታ ለምንታዌ እንዲል። ንስጥሮስ በ431 ዓ.ም በኤፌሶን በተደረገው አለማቀፋዊ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ተወግዟል። ይህ ጉባዔ ሲደረግ አፈ ጉባኤው መምህረ ዓለም ቅዱስ ቄርሎስ ሲሆን በዘመኑ የነበረው ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ዘይንእስ ነበር።
፰) ከፍሎ ተዋሐደ የሚሉ:- እነዚህ ደግሞ ሥጋ ቃልን ገንዘብ ሲያደርግ በምልዐት አይደለም። የፀሐይ ብርሃን በመስኮት ተከፍሎ እንደሚገባ ከፍሎ ተዋሐደ የሚሉ አሉ። ነገር ግን ቅዱስ ማር ኤፍሬም "ወኢተዋሐደ በመንፈቀ ህላዌ" ብሎ ስለሚናገር ክሕደታቸው መሠረት አልባ መሆኑ ታወቀ (ሃይ.አበ.፵፯፣፴፪)። ቃል ሥጋን ሲዋሐድ ከሥጋ የተከፈለ ነገር የለም። ኩለንታ አካለ ሥጋን ኩለንታ አካለ ቃል ገንዘቡ አድርጎታል። ሥጋም ቃልን ገንዘቡ ሲያደርግ ኵለንታ አካላ ቃልን ኩለንታ አካለ ሥጋ ገንዘቡ አድርጎታል።
፱) አርዮስ:- አርዮስ ወልድ ፍጡር በመለኮቱ ያለ ከሓዲ ነው። ይኽውም ማንም ያልፈጠረው ፈጣሪ አብ ብቻ ነው። አብ መጀመሪያ ወልድን ፈጠረ ከዚያ በወልድ ፍጥረታትን ፈጠረ የሚል ክሕደትን አስተማረ። ነገር ግን አርዮስ በዮሐንስ ወንጌል ይሸነፋል። ዮሐንስ መጀመሪያ ቃል ነበር። ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበር ብሏል። ወልድ የአብ ቃል ከሆነና ወልድ ሳይኖር አብ ነበረ ካለ ቃል የሌለው (መናገር የማይችል) አብ ነበረ ያሰኝበታል። ይህ ደግሞ ትልቅ ስድብ ነው። በኒቅያ የተሰበሰቡ ፫፻፲፰ቱ ቅዱሳን ሊቃውንት ወልድ ከአብ ተወለደ እንጂ አልተፈጠረም አሉት። አርዮስ ግን ተወለደ ማለት ያው ተፈጠረ ነው አለ። ሊቃውንቱ ደግሞ አይ እኛ የምንወልደውን አልፈጠርነውም ብለውታል። "ሁሉ በእርሱ ሆነ" ስለሚል ፍጥረታትን ሁሉ የፈጠረ ስለሆነ ወልድን ፍጡር በመለኮቱ አንለውም ሲሉት አርዮስ ግን ፈጥሮ ፈጠረበት አለ። እንደዚያማ እንዳትል "ያለ እርሱ ምንም ምን የሆነ የለም" ይልብሀል ብለው መፈናፈኛ አሳጥተው ኃይለ ቃል ጠቅሰው አሸንፈው አውግዘውታል (ዮሐ. ፩፣፩-፫)። በዘመኑ የነበረው ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ሲሆን የጉባኤው ሊቀመንበር እለእስክንድሮስ ነበረ።
፲) አርሲስ:- እነዚህ ከሓድያን ደግሞ ጌታ ነፍሳትን ለማዳን በነፍስም በሥጋም ወደሲኦል ሄዷል ብለው የሚናገሩ ናቸው። ነገር ግን ወንጌል እንደሚነግረን ነፍሱ ከሥጋው በዕለተ ዓርብ መጋቢት ፳፯ ቀን እንደተለየችና ሥጋውንም ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ገንዘው እንደ ቀበሩት ስለተጻፈ ክሕደታቸው መሠረት የለሽ ነው (ዮሐ.፲፱፣፵)።
፲፩) አውጣኪ:- መለኮት ሥጋን ውጦታል ያለ ከሓዲ ነው። ስለዚህ ሥጋ ወደመለኮትነት ስለተለወጠ አልታመመም የሚል ነው። ነገር ግን ቃል ሥጋ ሲሆን የሥጋ ገንዘብ ለቃል፣ የቃል ገንዘብ ለሥጋ ሆኗል። በዚህ ጊዜ መጠፋፋት ስለሌለ ሥጋ ግዙፍነትን፣ ውስንነትን እንደያዘ ቃልን ገንዘቡ በማድረጉ ረቂቅነትን፣ ምሉዕነትን ገንዘብ አደረገ። ቃልም ረቂቅነትን፣ ምሉዕነትን እንደያዘ ሥጋን ገንዘቡ በማድረጉ በድንግል ማኅፀን ተወሰነ፣ ታየ፣ ተዳሰሰ። ቃልና ሥጋ ሲዋሐዱ ያለ መጠፋፋት፣ ያለ መለወጥ ስለሆነ መለኮት ሥጋን ዋጠው የሚለው ትምህርት አያስኬድም። መለኮት ሥጋን ውጦት ቢሆን ኖሮስ ባልተራበ ባልተጠማ ባልተሰቀለ ነበር። ነገር ግን መለኮት ሥጋን ስላልዋጠው ክርስቶስ በሥጋ ተራበ፣ ተጠማ፣ ተሰቀለ እየተባለ ተገልጿል (ሉቃ. ፬፣፪፣ ዮሐ. ፲፱፣፳)።
፲፪) ሰባልዮስ:- ሰባልዮስ እንደ እስልምና እምነት ለፈጣሪ አንድ አካል አለው የሚል የነበረ ከሓዲ ነው። ይህ አንዱ አካል በብሉይ ኪዳን አብ፣ በሐዲስ ኪዳን ወልድ ከዚያ መንፈስ ቅዱስ ተባለ ይላል። ነገር ግን እግዚአብሔር በአካል ሦስት መሆኑን "እኔም አብን እለምናለኹ ለዘለዓለምም ከእናንተ ጋራ እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል" ብሎ ገልጿል (ዮሐ. ፲፬፣፲፮)። በዚህ ጊዜ አብን እለምናለሁ ያለ ወልድ ሌላ፣ አብ ሌላ፣ አጽናኝ የተባለው ሌላ መሆኑ በግልጽ ተጽፏል። አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ የአካላት ስም ነው። እግዚአብሔርን አንድ ነው የምንለው በባሕርይው ነው እንጂ በአካል ሦስት ነው።
፲፫) መቅዶንዮስ:- ይህ ከሓዲ ከሥላሴ አንዱ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን ፍጡር ያለ ነው። በዚህም ክፉ ትምህርቱ በ381 ዓ.ም በቴዎዶስዮስ ዘየዐቢ ዘመን በጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት ሊቀ መንበርነት በቁስጥንጥንያ አለማቀፋዊ የቤተ ክርስቲያን ጉባዔ ተወግዟል። መንፈስ ቅዱስ ፈጣሪ እንደሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ተገልጿል። "የእግዚአብሔር መንፈስ ፈጠረኝ፥ ሁሉንም የሚችል የአምላክ እስትንፋስ ሕይወት ሰጠኝ" እንዲል (ኢዮ. ፴፫፣፬)።