cookie

ما از کوکی‌ها برای بهبود تجربه مرور شما استفاده می‌کنیم. با کلیک کردن بر روی «پذیرش همه»، شما با استفاده از کوکی‌ها موافقت می‌کنید.

avatar

ዲያቆን ወልደ ሰንበት መጣጥፎች ፣ ትምህርቶች

ይህ መንፈሳዊ ቻናል ትምህርቶች ፣መጣጥፎችን ፣ወጎች የሚተላለፉበት ነው። እንዲሁም የበአላት ወረቦች ፣ምስባክ ያገኙበታል ይህ ቻናል በባለቤቱ የተከፈተ ቻናል ነው

نمایش بیشتر
پست‌های تبلیغاتی
1 148
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-17 روز
-2830 روز

در حال بارگیری داده...

معدل نمو المشتركين

در حال بارگیری داده...

🕊 [  † እንኳን ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥንተ በዓለ ዕርገት እና ለጻድቁ አባ ዳንኤል ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። †   ] † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ! †  †  🕊   ዕርገተ እግዚእ   🕊  †   † ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓለ ዕርገትን ፪ [2] ጊዜ ታከብራለች:: አንዱ "ጥንተ በዓል" : ሁለተኛው ደግሞ "የቀመር በዓል" ይሠኛል:: ጥንተ በዓል ማለት ጌታችን በትክክል ያረገበትን ቀን ያመለክታል:: የክብር ባለቤት መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በኪነ ጥበቡ [በሕማሙ : በሞቱ] ዓለምን አድኖ: ፵ [40] ቀን ለሐዋርያቱ መጽሐፈ ኪዳንን: ትምሕርተ ኅቡዓትን አስተምሯቸዋል:: በ፵ [40] ኛው ቀን ፻፳ [120] ውን ቤተሰብ ይዟቸው ወደ ቢታንያ ወጣ:: በዚያም እስከ ሊቀ ዽዽስና ድረስ ሾሟቸው : ከኢየሩሳሌም እንዳይወጡም አዟቸው የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ጠብቁ ብሏቸዋል:: እየባረካቸው በተዋሐደው ሥጋ ወደ ሰማያዊ ዙፋኑ አርጓል:: ሰማያት: ምድር: ደመናት: ነፋሳት: መባርቅትና መላእክት: ፍጥረት በሙሉ አመስግኗል:: አይሁድ መናፍቃን ዕርገቱን ምትሐት ነው እንዳይሉ: ጌታችን ትንሳኤውን አማናዊ እንደሆነ ለማስረዳት በ፵ [40] ኛው ቀን ዐረገ:: አንድም ራስ ባለበት ሌሎች የሰውነት ክፍሎች ሊኖሩ ይገባልና ጌታችን ዕርገቱን በገሃድ አደረገው:: "ዐርገ እግዚእ ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን ንጹሐን" እንዲል:: † ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ:: ወእግዚእነ በቃለ ቀርን:: ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ:: † [መዝ.፵፮፥፮] (46:6) 🕊  †  ታላቁ አባ ዳንኤል  †  🕊 † ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ ክቡር ነው:: በሁሉ ነገሩ የተቀደሰ የገዳማውያን መብራትም ነው:: ከተረፈ ንጹሕ ሕይወቱ ጣዕመ መንግስተ ሰማያትን አይቷልና:: አባ ዳንኤል በትውልድ ግብጻዊ ሲሆን ዓለምን ንቆ [መንኖ] ገዳም የገባው ገና በወጣትነቱ ነው:: ጊዜውም ዘመነ ጻድቃን [በ፭ [5] ኛው መቶ ክ/ዘመን] ነበር:: በገዳመ አስቄጥስ እና በደብረ ሲሐት ይታወቃል:: ታላቋ መካነ ቅዱሳን ገዳመ ሲሐት ዛሬም ድረስ በስሙ የምትጠራ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ እጅግ ለብዙ ዘመናት በውስጧ ተጋድሎ ፍሬ ስላፈራባት : ደቀ መዛሙርትን በቅድስና ስለ ወለደባት ነው:: ስለዚህም ዛሬም ድረስ "አባ ዳንኤል ዘደብረ ሲሐት" ተብሎ ሲጠራ ይኖራል:: ሌላኛው ስሙ ደግሞ "ዘገዳመ አስቄጥስ" ይሰኛል:: ገዳመ አስቄጥስ የታላቁ ቅዱስ መቃርስ ርስት ሲሆን በዓለም በስፋትም : ብዙ ቅዱሳንን በማፍራትም አንደኛ የሆነ ገዳም ነው:: በዚህ ገዳም ላይ አበ ምኔት ሆኖ የሚሾሙ አበው ሁሌም የብቃት መዓርግ ላይ የደረሱ ሲሆኑ ክብራቸው ከፓትርያርክ በላይ ነው:: አባ ዳንኤልም ከብዙ የቅድስና ዓመታት በኋላ በአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ሆኖ ተሹሞ እልፍ አእላፍ መነኮሳትን በጽድቅ መንገድ መርቷል:: ቅዱሱ ከትጋቱ የተነሳ ለምግብና ለእንቅልፍ ጊዜ አልነበረውም:: ቀን ቀን መነኮሳቱን ሲናዝዝ : ድውያንን ሲፈውስ : ሥርዓተ ገዳምን ሲቆጣጠር ይውላል:: ልክ ሲመሽ ጭው ወዳለውና ስውራን ወደ ሚገኙበት በርሃ ይወጣል:: በዚያም ሙሉውን ሌሊት የተሰወሩ አባቶችን ሲፈልግ ያድር ነበር:: በዚህም ምክንያት የብዙ ስውራንን ገድል የጻፈ ሲሆን ባረፉ ጊዜም ገንዞ በመቅበር በረከታቸውን ተሳትፏል:: ታላቅ ሙያንም ፈጽሟል:: እርሱ ገንዞ ቀብሮ : ዜናቸውን ከጻፈላቸው ሥውራን ቅዱሳንም እንደ አብነት እሥራኤላዊቷን ቅድስት ዓመተ ክርስቶስን [ለ፴፰ [38] ዓመት ራቁቷን በሥውር የኖረች] እና ቅድስት በጥሪቃ ንግሥትን [መንግስቷን ትታ በሥውር የኖረች ናት] መጥቀስ እንችላለን:: ከዚህ ባለፈም አባ ዳንኤል በሰው ዘንድ የተናቁትንም ማክበርን ያውቅበታል:: ለምሳሌ በሴቶች ገዳም እብድ ናት ተብላ በበር የተጣለችውን ቅድስት አናሲማን : በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ዻዻሳቱ ሳይቀር "እብድ ነው" ብለው የናቁትን ቅዱስ ምሕርካን: እብድ ሳይሆኑ ራሳቸውን የሠወሩ ቅዱሳን መሆናቸውን ገልጧል:: አባ ዳንኤል ሐዋርያዊም ነበር:: በጊዜው ጦማረ ልዮን የሚባል የኑፋቄ ደብዳቤ ይላክ ነበርና ለዚህ ኬልቄዶናዊ ኑፋቄ በትጋት ምላሽ ይሰጥ ነበር:: አንድ ቀንም በንጉሥ ትዕዛዝ ኑፋቄው በእርሱ ገዳም ሊነበብ ሲል ቅዱሱ ከወታደሩ ቀምቶ ስለ ቀደደው ለሞት እስኪደርስ ደብድበውታል:: ጻድቁ አባ ዳንኤል አንዴ አውሎጊስ የሚባልድሃ ድንጋይ ጠርቦ እንግዳ ሲቀበል ተመልክቶ "ጌታ ሆይ! ይህንን ደግ ሰው ለምን ድሃ አደረከው?" ሲል በፈጣሪ ሥራ ገባ:: ጌታም እንደ ወትሮው በገሃድ ተገልጦ "በነፍስህ ትዋሰዋለህ?" አለው:: "አዎ ጌታየ" ስላለው ጌታችን ለአውሎጊስ ሃብትን ሰጠው:: ግን ወዲያው የጦር አለቃና ጨካኝ ሰው ሆነ:: ጻድቁ ወሬውን ሰምቶ ሊጠይቅ ቢሔድ የአውሎጊስ ወታደሮች ደበደቡት:: ጌታችንም አባ ዳንኤልን ወደ ፍርድ ዙፋኑ አቅርቦ "ወዳጄን መልስልኝ" አለው:: እመ ብርሃን ግን ቀርባ የልጇን እግር ሳመች:: "ልጄ ሆይ ማር!" አለችው:: ጌታም "እሺ" ብሎ ጻድቁን ወደ በአቱ: አውሎጊስን ወደ ቀደመ ግብሩ መለሳቸው:: የአባ ዳንኤል ድንቁ ብዙ ነው:: ሌላው ቢቀር ሽፍታ አባ ዳንኤልን መስሎ ወደ ደናግል ገዳም ሊዘርፍ : በማታለል ገባ:: ደናግሉም ጻድቁ መስሏቸው እግሩን አጥበው ዐይነ ስውሯን ቢቀቧት ዐይኗ በርቷል:: ሽፍታውም ደንግጦ ንስሃ ገብቷል:: አባ ዳንኤል ግን ተጋድሎውን ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል:: † በተረፈው ግን ከቅድስና ሕይወቱ ባሻገር :- ፩. በገዳመ አስቄጥስ [ግብጽ] አበ ምኔት ሆኖ ተሹሞ ባሳየው ትጋት:: ፪. በሃይማኖት ጠበቃነቱ በደረሰበት ድብደባና ስደት:: ፫. ብዙ የበርሃ ቅዱሳንን በየበአታቸው እየዞረ በመቅበሩ:: ፬. የብዙ ስውራን ቅዱሳንን ዜና ሕይወት በመሰብሰቡ:: ፭. በየጊዜው በእግዚአብሔር ኃይል ይፈጽማቸው በነበሩ ተአምራት:: እና ፮. ለድንግል እመቤታችን ማርያም በነበረው ልዩ ፍቅር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታከብረዋለች:: † ቸር አምላክ ክርስቶስ ከዕርገቱና ከጻድቁ በረከት አይለየን:: 🕊 [  † ግንቦት ፰ [ 8 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ] ፩. ቅዱሳን የጌታ ቤተሰብ [፻፳ (120) ው] ፪. ቅዱስ አባ ዳንኤል ጻድቅ ፫. ቅዱስ ዮሐንስ ሰማዕት ፬. ቅዱስ መክሲሞስ መስተጋድል ፭. አቡነ ዮሐኒ ዘደብረ ዳሞ [አቡነ ተክለ ሃይማኖትንና አቡነ ኢየሱስ ሞዐን ለምንኩስና ያበቁ] [    † ወርሐዊ በዓላት    ] ፩. ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት ፪. ኪሩቤል [ አርባዕቱ እንስሳ ] ፫. አባ ብሶይ [ ቢሾይ ] ፬. አቡነ ኪሮስ ፭. አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን ፮. ቅዱስ ማትያስ ሐዋርያ [ከ፲፪ [12] ቱ ሐዋርያት] † " እስከ ቢታንያም አወጣቸው:: እጆቹንም አንስቶ ባረካቸው:: ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ:: ወደ ሰማይም ዐረገ:: እነርሱም ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ:: ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ:: " † [ሉቃ.፳፬፥፶-፶፫] [24:50-53] † ወስብሐት ለእግዚአብሔር † † ወለወላዲቱ ድንግል † † ወለመስቀሉ ክቡር † [ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]          †              †               † ▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬ 💖                   🕊                    💖
نمایش همه...
🕊 †   🕊   በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡   🕊   † ❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖ ግንቦት ፯ [ 7 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 🕊 †  ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ †  🕊 በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከሐዋርያት ቀጥሎ የቅዱስ አትናቴዎስን ያሕል ስለ ሃይማኖት የተዋጋ ቅዱስ ፈልጐ ማግኘት አይቻልም:: †  ቅዱስ አትናቴዎስ ማን ነው ? ቅዱስ አትናቴዎስ በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት በዘመነ ሰማዕታት መጠናቀቂያ በ፫፻ [300] አካባቢ ፪፻፺፮ (296) እስክንድርያ ግብፅ ውስጥ ነው የተወለደው:: ወላጆቹ አረማውያን በመሆናቸው ክርስትናን አልተማረም ነበር:: ሕጻን እያለ ለጭዋታ ከቤቱ ሲወጣ የክርስቲያን ልጆች ሃይማኖታዊ ጨዋታ ሲጫወቱ ተመለከተ:: ሊቀላቀላቸው ቢፈልግም ክርስቲያን ባለመሆኑ ከለከሉት:: አትናቴዎስም ክርስቲያን ልሁንና አጫውቱኝ ብሏቸው እሺ ስላሉት ሕጻናቱ ዕጣ ተጣጣሉ:: ላንዱ ቄስ: ላንዱም ዲያቆን መሆን ሲደርሳቸው ለአትናቴዎስ ፓትርያርክ መሆን ስለ ደረሰው ሌሎቹ ሕጻናት ይሰግዱለት ጀመር:: በአጋጣሚ ሕጻናቱ ይሕንን ሁሉ ሲያደርጉ የወቅቱ ፓትርያርክ ቅዱስ እለ እስክንድሮስ በመገረም ያያቸው ነበርና ለሕጻኑ አትናቴዎስ ትንቢት ተናገረለት:: ከዚያም የአትናቴዎስ አባቱ ሲሞት ሊቀ ዻዻሳቱ ከእናቱ ወስዶ አጥምቆ: የሚገባውን መንፈሳዊ ትምሕርት ሁሉ በልቡናው ላይ ቀረጸበት:: ከዚሕ በኋላ ዲቁናን ሹሞ አስተምር አለው:: ምንም ሕጻን ቢሆንም ከሊቅነቱ: ከአመላለሱና ከአንደበቱ ጣፋጭነት የተነሳ የሰማው ሁሉ ይደነቅ ነበር:: ጸጋ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ አድራለችና:: ቅዱስ አትናቴዎስ ሊቀ ዲቁና በተሾመ ወራት አርዮስ ቤተ ክርስቲያንን በመረበሹ ኒቅያ ላይ ፫፻፲፰ [318] ቱ ሊቃውንት ሲሰበሰቡ ጸሐፊ አድርገው ሾሙት:: በጊዜውም በዕድሜ የስንት ጊዜ ትልቁ የሚሆነውን አርዮስን ተከራክሮ ምላሽ አሳጣው:: †  ቅዱስ አትናቴዎስ ከሊቃውንቱ ጋር ሆኖ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ወልደ አምላክ: እግዚአብሔር መሆኑን በአደባባይ መሠከረ:: ጸሎተ ሃይማኖትንም ያረቀቀው እርሱ ነው:: ከዚሕ በኋላ የእስክንድርያ [የግብፅ] ፳ [20] ኛ ፓትርያርክ ሆኖ ተሾመ:: ቤተ ክርስቲያንን በመልካም እረኝነት ለ፵፰ [48] ዓመታት ሲመግብ ብዙ መከራዎችን ተቀበለ:: ለ፭ [5] ጊዜ ከመንበሩ አፈናቅለው ወደ በርሃ ሲያግዙት በስደት ከ፲፭ [15] ዓመታት በላይ አሳልፏል:: በተሰደደባቸው ቦታዎች መከራን እየተቀበለ ያላመኑትን አሳምኗል:: በጎቹ እንዳይባዝኑበት ደግሞ በጦማር [በደብዳቤ] ይጠብቃቸው ነበር:: ዛሬ በሃይማኖተ አበው የምናገኘው ቃለ ሃይማኖት በዚሕ ዘመን የተጻፈ ነው:: በወቅቱ የነበረው ንጉሥ [ትንሹ ቆስጠንጢኖስ] የአባቱን [ታላቁ ቆስጠንጢኖስን] ዕረፍት ተከትሎ ነገሠ:: ወዲያውም አርዮሳዊ መናፍቅ ሆነ:: ሃይማኖታቸው የቀና አባቶችንም ያሳድድ ገባ:: ከአበው ቅዱሳን መካከል ግንየዚህ መከራ ቀዳሚው ገፈት ቀማሽ ታላቁ ሊቅ ቅዱስ አንትናቴዎስ ነበር:: በተለይ አንድ ጊዜ ንጉሡ ቅዱሱን ወደ በርሃ አግዞ: መናፍቅ ዻዻስ በግብጽ ሹሞ: ብዙ ክርስቲያኖችን በግፍ ሲያስገድል: ቅዱሱን ለ፮ [6] ዓመታት አሰቃየው:: የወገኖቹ [የልጆቹን] ስቃይ የሰማው ቅዱስ አትናቴዎስ ግን በድፍረት ወደ ቤተ መንግስት ገብቶ ተናገረው:: ፪ [2] አማራጭን አቅርቦ "ወይ ግደለኝና እንደ አባቶቼ ሰማዕት ልሁን: ካልሆነ ግን ወደ መንጐቼ [ምዕመናን] መልሰኝ" አለው:: መናፍቁ ንጉሥም ቢገድለው ብጥብጥ እንደሚነሳ ስለሚያውቅ በስልት ሊያጠፋው ወሰነ:: ቀዛፊ: መቅዘፊያ: ምግብና ውሃ በሌላት ጀልባ ውስጥ ከቶም ሜዲትራኒያን ባሕር ውስጥ ጣለው:: ድንገት ግን ከሰማይ ጌታችን መላእክቱን አስከትሎ ወረደ:: ሚካኤልና ገብርኤል ባሕሩን እየቀዘፍ: ሌሎች መላእክት እየመገቡት በዚህች ቀን እስክንድርያ [ግብጽ] አድርሰውት ተሠውረዋል:: ሕዝቡም በታላቅ ሐሴት እየዘመሩ አባታቸውን ተቀብለውታል:: ሐዋርያዊው ቅዱስ ስለ ኦርቶዶክስ ተዋግቶ: ብዙ ስቃይንም ተቀብሎ በ፫፻፹፫ [373] ዓ/ም አካባቢ አርፏል:: ቤተ ክስርቲያን ፦ - "ሊቀ ሊቃውንት: - ርዕሰ ሊቃውንት: - የቤተ ክርስቲያን - [ የምዕመናን ] ሐኪም [ Doctor of the Church ]: - ሐዋርያዊ" ብላ ታከብረዋለች:: አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሊቁ በረከት አይለየን:: በምልጃውም ሃይማኖታችንን ይጠብቅልን:: 🕊 [ † ግንቦት ፯ [ 7 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ] ፩. ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ፪. የባሕታውያን አለቃ ታላቁ አባ ሲኖዳ [ጽንሰቱ] ፫. ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ [ሃብቱን: ንብረቱን: ልብሱን ሳይቀር መጽውቶ ራቁቱን የተገኘ ደግ ሰው ነው] ፬. አባ ሐርስዮስ ገዳማዊ [ †  ወርሐዊ በዓላት ] ፩. ሥሉስ ቅዱስ [አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ] ፪. አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ፫. አባ ሲኖዳ [የባሕታውያን አለቃ] ፬. አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት ፭. አባ ባውላ ገዳማዊ ፮. ቅዱስ አግናጥዮስ [ለአንበሳ የተሰጠ] " ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብጹዐን ናቸው:: መንግስተ ሰማያት የእነርሱ ናትና:: ሲነቅፉአችሁና ሲያሳድዱአችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብጹዓን ናችሁ:: ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ:: ሐሴትም አድርጉ:: ከእናንተ በፊት የነበሩ ነቢያትን እንዲሁ አሳደዋቸዋልና። " [ማቴ.፭፥፲] (5:10) [ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ] † ወስብሐት ለእግዚአብሔር † † ወለወላዲቱ ድንግል † † ወለመስቀሉ ክቡር † [ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]          †              †               † ▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬ 💖                   🕊                    💖
نمایش همه...
🕊 † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ † [ † ግንቦት ፮ [ 6 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ] †  🕊  አባ መቃርስ ካልዕ  🕊  † ይህ ቅዱስ "መቃርዮስ: መቃርስ: መቃሬም" ይባላል:: ትርጉሙ በ ፫ [3]ቱም መንገድ አይለወጥም:: ምክንያቱም ሥርወ ቃሉ በዮናኒ ልሳን "ብጹዕ: ንዑድ: ክቡር" ማለት ነውና:: ከስሙ ቀጥሎ "ካልዕ-፪ [2] ኛው": አንዳንዴ ደግሞ "እስክንድርያዊ" እየተባለ ይጠራል:: "ካልዕ-፪ [2] ኛው" የሚባለው ከቀዳሚው [ታላቁ መቃርስ] ለመለየት ሲሆን "እስክንድርያ" ደግሞ ተወልዶ ያደገባት ሃገር ናት:: አባ መቃርስ በ ፬ [4]ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረ ገዳማዊ: ጻድቅና ትሩፈ-ምግባር ነው:: በዓለም ለ ፵ [40] ዓመት ሲኖር እንደ ሕጉ ፈጣሪውን ደስ ያሰኘ ሰው ነው:: ጻድቃን እንደ ከዋክብት በበዙበት በዚያ ዘመን የታላቁ መቃርስን ዜና ሰምቷልና ይህቺን ክፉ ዓለም ከነግሳንግሷ ንቋት በርሃ ገብቷል:: እንደሚገባ ሥርዓተ ገዳምን ጠብቆ: ለአበው ታዞ: በጾም: በጸሎት: በትሕትናና በስግደት ተጠምዶ ቢያገኘው ፈጣሪ አከበረው:: በዚያ ጊዜም ለታላቁ ገዳመ አስቄጥስ መናንያን አበ ምኔት ሊሆን መረጡት:: እርሱም እረኝነትን ያውቃልና በጐቹን [መነኮሳትን] ከተኩላ [ሰይጣናት] ይጠብቅ ዘንድ ብዙ ተጋ:: ከብቃቱ የተነሳም ሳያስታጉል: ሳይበላ: ሳይጠጣና ሳይቀመጥ እስከ ፵ [40] ቀን ይጸልይ ነበር:: ሲጸልይ ደግሞ በልቡ እየተቃጠለ በፍቅረ ክርስቶስ ነበርና አጋንንት ይርዱለት ነበር:: እርሱ ጸሎት ሲጀምርም በገዳሙ ዙሪያ ያሉ አጋንንት እየጮሁ ይሸሹ ነበር:: ከተጋድሎው ጽናትና ከትሕትናው ብዛት የተነሳ ያዩት ትዕቢተኞች ሁሉ ይገሠጹ ነበር:: በዘመኑም ብዙ ተአምራትን ሠርቷል:: አንድ ቀን በበዓቱ ሳለ ጅብ መጥታ ተማጸነችው:: አብሯት ወደ ዋሻዋ ቢሔድ ልጆቿ በሙሉ ዓይነ ሥውራን ሆነው አገኛቸው:: እርሱም ወደ መሬት ምራቁን እትፍ ብሎ በጭቃ ለውሶ ቢቀባቸው የሁሉም ዐይናቸው በርቷል:: ስለ ውለታውም ጅቢቱ የበግ ቆዳ እየጐተተች አምጥታ ሰጥታዋለች:: [ከሰው ልጅ በቀር እንስሳት ውለታን አይረሱምና] ቅዱስ መቃርስም ለወትሮው ባዶው መሬት [አፈር] ላይ ይተኛ የነበረው ከዚያ ቀን በኋላ በአጐዛው ላይ የሚተኛ ሁኗል:: በሃገሩ እስክንድርያም ለ ፪ [2] ዓመታት ዝናብ በመጥፋቱ ሕዝቡ ተጨንቆ ነበርና "ናልን" ሲሉ መልዕክት ላኩበት:: እርሱ መጥቶ ሲጸልይም መብረቅ የቀላቀለ ዝናብ ጣለ:: ዝናቡም ያለ ማቆም ለ ፪ [2] ቀናት በመዝነቡ ሕዝቡ ፈርተው "አባታችን ስለ ኃጢአታችን እንዳንጠፋ ለምንልን?" አሉት:: እርሱም በጸሎቱ [በፈጣሪው ኃይል] እንደ ወደዱት ዝናቡን አቁሞላቸዋል:: የአባ መቃርስን ዜና ሕይወትና ተአምራት ተናግሬ አልፈጽመውም:: ግን አንዲት ብቻ ላክል:: ሁሌ ሳስበው ስለሚገርመኝም ነው:: ብዙዎቻችን የጌታችን ሥጋና ደም አንቀበልም:: ለምን ያከበርነውና የፈራነው አስመስለን ኃጢአትን ለመጥገብ ቦታን [አጋጣሚን] ስለምንፈልግ:: በተቃራኒው ደግሞ አንዳንዶቻችን መለኮት የተዋሐደውን የጌታ ሥጋና ደም እንደ ተርታ ነገር [ያለ ጥንቃቄ] ስንቀበል ይታያል:: ፪ [2] ቱም ግን ስሕተት ነው:: ፈርተን [ፍርሃቱ ጤነኛ ባይሆንም] ስለ ራቅን በፍርድ ቀን ማምለጥ አንችልም:: "ሥጋየን ያልበላ: ደሜንም ያልጠጣ የዘለዓለም ሕይወት የለውም" ይለናልና:: [ዮሐ.፮፥፶፪] (6:52) በድፍረት ለምንቀበልም ሥጋው እሳት ሁኖ እንዳይበላን: ደሙም ባሕር ሆኖ እንዳያሰጥመን ልናከብረው ይገባናል:: "ሳይገባው ከጌታ ሥጋና ደም የተቀበለ የጌታ ሥጋ ዕዳ አለበት" ይለናልና::  [፩ቆሮ.፲፩፥፳፯] (11:27) "ታዲያ የሚሻለው ለሁላችንም ንስሃ ገብቶ: በፍርሃት ሆኖ መቅረቡ ነው::" ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና አባ መቃርስ ወደ በርሃ እንደ ገባ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎ ነበር:: ቅዱሱ ይህንን እያሰበ ለ ፷ [60] ዓመታት ምራቁን ሳይተፋ ኑሯል:: ለዚያ አይደል አበው "ብታከብሩት ያከብራቹሃል" ያሉት:: ሊቃውንቱም ይህንን ሲያደንቁ :- "ኢታስተማስልዎ ለቁርባን ከመ ሕብስት ዕራቆ:: አኮኑ ሥጋ መለኮት ዘይትላጸቆ:: መቃርዮስ አብ ዕበየ ቁርባን ለአጠይቆ:: ድኅረ ተወክፈ በአሚን እንበለ ያብዕ ናፍቆ:: መጠነ ዓመታት ስሳ ኢተፍአ ምራቆ::" ብለዋል:: ቅዱስ መቃርስም በ ፻ [100] ዓመቱ በ ፭ [5] ኛው ክ/ዘመን መጀመሪያ አካባቢ በዚህች ቀን ዐርፏል:: ጌታችን ከክብሩ : ከበረከቱ አይለየን:: 🕊 [ †  ግንቦት ፮ [ 6 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ] ፩. ቅዱስ አባ መቃርስ ገዳማዊ ፪. እናታችን ቅድስት ሰሎሜ ኢትዮዽያዊት ፫. አባ ይስሐቅ ጻድቅ ፬. ቅድስት ዲላጊና ፬ [4] ሴት ልጆቿ [ሰማዕታት] ፭. ቅዱስ ዳናስዮስ ሰማዕት ፮. ቅዱስ በንደላዖስ ሰማዕት [የታላቁ ኤስድሮስ አባት] ፯. አባ አሞን ጻድቅ [ዽዽስናን አልፈልግም ብሎ የሸሸ አባት] [ † ወርኀዊ በዓላት ] ፩. ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም ፪. አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን ፫. አባታችን ኖኅና እናታችን ሐይከል ፬. ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ ፭. ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ፮. ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ ፯. ቅድስት ሰሎሜ ፰. አባ አርከ ሥሉስ ፱. አባ ጽጌ ድንግል ፲. ቅድስት አርሴማ ድንግል " ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው:: እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሳዋለሁ:: ሥጋዬ እውነተኛ መብል: ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነውና:: ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል:: እኔም በርሱ እኖራለሁ:: "  [ዮሐ.፮፥፶፫-፶፮] (6:53-56) † ወስብሐት ለእግዚአብሔር † † ወለወላዲቱ ድንግል † † ወለመስቀሉ ክቡር † [ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]          †              †               † ▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬ 💖                   🕊                    💖
نمایش همه...