fa
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

رفتن به کانال در Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

نمایش بیشتر
638
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-37 روز
-1130 روز
آرشیو پست ها
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_ስድስተኛ_ቀን_ለቅድስት_ቤተ_ክርስቲያን መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                          ✝ ✝ ✝ ❤ "#ዘበእንቲአሃ_ለቤተክርስቲያን_ተጸፋእከ በውስተ ዐውድ ከመ ትቀድሳ በደምከ ክቡር ዘበእንቲአሃ ዝግሐታተ መዋቅሕት ፆረ ወተዐገሰ ምራቀ ርኩሰ እንዘ አልቦ ዘአበሰ #አምላክ_ዲበ_ዕፀ_መስቀል_ተሰቅለ። ትርጉም፦ #ለቤተክርስቲያን_ብለህ_ልትቀድሳት በደምህ በአደባባይ በጥፊ ተመታህ ንጹሕ ክርስቶስ በአዳም ጥፋት ልትወቀስ በከንቱ ልትከሰስ አመላለሱህ ከጲላጦስ ወደ ሄሮድስ ሁሉን ቻይ ሳለህ ምንም ማድረግ ሳይሳንህ በአይሁድ እጅ ተገረፍህ ወዮ ወሰን ለሌላት ትዕግስት ስለኛ ብለህ መከራ ተቀበልህ ምንም በደል ሳይኖርብህ #አምላክ_በእንጨት_መስቀል_ላይ_ሰቀሉህ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ።               ❤ #ዕለተ_አርብ።                          ✝ ✝ ✝ ❤ #አርብ_ቅድስት_ቤተ_ክርስቲያን_ይባላል፦ በክርስቶስ ደም ተዋጅታ በተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታላቅ መታሰቢያ በመሆኗ በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ዐርብ "ቤተ ክርስቲያን" ተብላ ትጠራለች፡፡ ማቴ. 26-26-29 የሐ ሥራ 20፥28። ❤ በዚህ ዕለት ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሷ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ እንዳከበራት ይነገራል፡፡ ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡ ❤ #ምስባክ_መልዕክታት_ወንጌልና_ቅዳሴ እንደ ብርሃነ ትንሣኤ። መልካም የበዐለ ትንሣኤ ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሚያዝያ ፱ (9) ቀን። ❤ እንኳን #ብሔረ_ብፁዓን በመሔድ ገድላቸው ለጻፈ ሥራቸውንና ጽድቃቸውን ለገለጠ ለታላቁ አባት ለከበረ #ለቀሲስ_ለቅዱስ_ዘሲማስ_ዞሲማስ) ለዕረፍት በዓል፣ ለዐሥር ወር ሕፃን ለሆነ #ለቅዱስ_ኤስድሮስ ማኅበርና #ለብሔረ_ብፁዓን_ጻድቃን ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #በአባ_ስንትዩ እጅ ታላቅ ምልክት ከታየበት ረድኤትና በረከትን ያሳትፈ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ቀሲስ_ቅዱስ_ዘሲማስ (ዞሲማስ)፦ ይህም ጻድቅ ከፍልስጥዔም ሰዎች ወገን ነው። ወላጆቹም ደጋጎች ክርስቲያኖች ናቸው ይህንን ጻድቅ በወለዱት ጊዜ አምስት ዓመት አሳደጉት። ከዚያም የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን የሃይማኖትንም ምሥጢር ሕግና ሥርዓትንም እያስተማረ እንዲያሳድገው ለአንድ ሽማግሌ መምህር ሰጡት። ያ ሽማግሌም ተቀብሎ ልጁ አደረገው ትምህርቱንም ሁሉ አምላካዊ ጥበብ ሃይማኖትንም አስተምሮ አመነኰሰው ዲቁናም አሾመው በበጎ ሥራም አደገ ትሩፋት መሥራትንም አበዛ እግዚአብሔርንም ሁል ጊዜ ያመሰግነዋል በቀንና በሌሊትም መጻሕፍትን ያነባል። ሥራ ሲሠራ ሲበላም ቢሆን ሁል ጊዜ ከአፋ ምስጋዎችን አያቋርጥም። በዚያ ገዳም አርባ አምስት ዓመት በተፈጸመለት ጊዜ ቅስና ተሾመ ተጋድሎውንም ጨመረ። ❤ ከዚያም በኋላም እየተጋደለና አገልግሎት በመጨመር በቅስና ሹመት ዐሥራ ሦስት ዓመት ሲሆነው በዘመኑ ካሉ ተጋዳዮች ሁሉ እርሱ በገድሉ ከፍ ከፍ እንዳለ ተቃራኒ ጠላት ዲያብሎስ በልቡ ክፉ ሀሳብ አሳደረበት በልቡም "ከበጎ ሥራ እኔ ያልሠራሁት የቀረኝ አለን" ይል ጀመረ። ነገር ግን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አልተወውም መልአኩን ልኮ በዮርዳኖስ ወንዝ አቅራቢያ ወደ አለ ገዳም ይሔድ ዘንድ እንጂ። ያን ጊዜም ተነሥቶ ሒዶ ወደዚያ ገዳም ደረሰ በገድላቸው ፍጹማን የሆኑ ዕውነተኞች አረጋውያንን አገኘ እርሱ ከእርሳቸው እንደሚያንስ አወቀ እርሱ በዓለም ውስጥ ነው የኖረውና ስለዚህ ከእርሱ ይሻላሉ። በዚያ ገዳም ከሳቸው ጋራ ኖረ ብዙ ዘመናትም አብሮቸው ሲጋደል ኖረ። ❤ በዚያ ገዳም መነኰሳትም ልማድ አላቸው ታላቁ ጾም በደረሰ ጊዜ የመጀመሪያውን አንድ ሱባዔ በአንድነት ይጾማሉ በቅድስት እሑድ ሥጋውና ደሙን ይቀበላሉ በማግሥቱም ሰኞ ጥዋት ሃያ ስድስተኛ መዝሙር እግዚአብሔር ብርሃነ ረድኤቱን ሰጥቶ ያድነኛል የሚያስፈራኝ ምድንነው የሚለውን እስከ መጨረሻው እየዘመሩ ይወጣሉ በሚወጡም ጊዜ ወደ በሩ ተሰብስበው በአንድነት ጸልየው እርስበርሳቸው ሰላምታ ይሰጣጣሉ የገዳሙ አበ ምኔትም ይባርካቸዋል። ከዚያም በኋላ እየአንዳንዱ ወደ በረሃ ይበተናሉ አንዱ አንዱ ባልጀራውን ያየ እንደሆነ እንዳያየው ወደ ሌላ ቦታ ይሔዳል። ❤ ቅዱስ ዘሲማስም በዓመቱ ከሳቸው ጋራ ወጥቶ በበረሀው ውስጥ ይዘዋወራል የሚጽናናበትንም ይገልጥለት ዘንድ እግዚአብሔር ይለምነው ነበር። ሲዘዋወርም በበረሀ የምትኖር ግብጻዊት ማርያምን አገኘ ከእርሷም በልጅነቷ ወራት በእርሷ ላይ እንዴት እንደሆነና በበረሃም የሆነውን ኑሮዋን ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተረዳ። ከዚህ በኋላ በሁለተኛው ዓመት ሥጋውንና ደሙን ያመጣላት ዘንድ ፈለገች እንዳለችውም አደረገላት። ❤ ለዚህም ጻድቅ ብሔረ ብፁዓን ይገባ ዘንድ ተገባው እርሱም ገድላቸው ጻፈ ሥራቸውንና ጽድቃቸውን ገለጠ። ዘጠና ሦስት የሚሆን መላ ዕድሜው በተፈጸመለት ጊዜ ሚያዝያ 9 ቀን በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ በዚችም ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #በአባ_ስንትዩ_እጅ_ታላቅ_ምልክት_ታየ፦ ይኸውም የከበረች የጌታን ጾም ከመነኰሳት ጋራ ይጾም ዘንድ ወደ አስቄጥስ ወደ አባ መቃርስ ገዳም ወጣ። ሰመነ ሕማማትም በሆነ ጊዜ ገዳማቱንና አድባራቱን ሊዘርፉና ሊማርኩ የዐረብ እስላሞች ተሰበሰቡ። በቤተ ክርስቲያኒቱ በስተ ምስራቅ ሰዎችንም ይገድሉ ዘንድ ሰይፎቻቸውን መዝዘው በእጆቻቸውም ይዘው በአለት ላይ ቆሙ። ❤ ኤጲስቆጶሳትና መነኰሳትም ወደ አባ ስንትዩ ተሰብስበው ከዐረብ እስላሞች እንዴት እንደሆነ ነግረው ከዚያ ገለል እንዲል ለመኑት። የከበረ አባ ስንትዩም "ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግራቸውን አጥቦ ሐዲስ ሥርዓት የሠራበት የፋሲካ ፍሥሕ በዓል ሳይፈጸም እኔ ከዚህ አልለይም" አላቸው። እነዚህ እስላሞችም እየደነፉ ጨኸታቸው ተጨመረ። አባ ስንትዩም የወገኖቹን ድንጋፄ በአየ ጊዜ በላዩ የመስቀል ምልክት ያለበት በትሩን ይዞ ከእግዚአብሔር ወገኖች ጋራ ብሞት ይሻለኛል እያለ ወደ እነርሱ ሊወጣ ተነሣ። ኤጲስቆጶሳቱም እንዳይወጣ ያዙት እርሱ ግን ልባቸውን በማጽናናት አረጋጋቸውና ወደ ዐረብ እስላሞች ወጣ። እስላሞች መስቀል ያለበት በትር በእጁ ይዞ በአዩት ጊዜ ብዙ ሠራዊት እንዳሳደዳቸው ሁነው ወደ ኋላቸው ተመልሰው ሸሹ። ከዚያችም ዕለት ወዲህ ወደ ቅዱሳት መካናት እስላሞች አልተመለሱም። ❤ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በመስቀሉ ኃይል ሕዝቡን ያዳነ ልዕልና ክብር ገንዘቡ የሆነ ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦የሚያዝያ9 ስንክሳር።                                      ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ዕብል_ዕደወ_ብፁዓነ። ዘነጸሮሙ ዘሲማስ ወከመ ስምዐ ጽድቅ ኮነ። እንበይነ ኢበልዑ ሥጋ ወእንበይነ ኢሰቴዩ ወይነ። በሥምረተ አምላክ ክርስቶስ አድምዑ መካነ። ኀበ አልቦ ሕማመ ወአልቦ ኀዘነ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_9።

❤ ጌታችንም ለስምህ አጠራር መታሰቢያ ይሆንህ ዘንድ ቃል ኪዳን ልሰጥህ መጣሁ ብዙ ኃጢአት የሠራ አረመኔም ቢሆን መታሰቢያህን ያደረገው እምርልሃለሁ፣ ዝክርህን የሚዘክር በዓልህን የሚያከብር ሰው ቢኖር እናትና አባቱ ሞተው ወደ ሲኦል ከወረዱ በኋላ መውጫ ከሌለው ከሥቃይ ቦታ ከሲኦል ስለ አንተ ብሎ አወጣቸዋለሁ፣ ማኅበርህን የሚጠጡ ሰዎች ቢኖሩ እንደ ሙሴ ሆኜ ማኅበራቸውን እኔ እራሴ እባርከዋለሁ፣ ዝክርህን የዘከረ፣ ስምህን የጠራ፣ በዓልህን ያከበረ የገድልህን መጽሐፍ የጻፈ፣ ያጻፈ መነኰሴ በዓለም ኃጢአት ሐመረ ሥጋው ቢሰበርበት ክንፈ ድንግልናውን እመልስለታለሁ፣ የገድልህን መጽሐፍ በቤቱ ያስቀመጠ የተለያዩ በሽታዎች፣ ችግር፣ ረኃብ፣ የሰው ሞት፣ የእንስሳ ሞት ሁሉ አይገቡም፣ ከቤቱ የእህል በረከት አይታጣም፣ በመቃብርህ ቦታ (ዳውንት) የተቀበረውን ሰው ኃጢያቱን ሳላስብበት ወደገነት አስገባዋለሁ፣ ያላመነ ሰውን ቦታህን አላስረግጠውም፣ ዝክርህን የዘከረውን፣ መታሰቢያህን ያደረገውን፣የገድልህን መጽሐፍ የጻፈው፣ ያጻፈውን እስከ ሃያ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ ልጅ የሌለውን መሐን ቢሆን ልጅ እሰጠዋለሁ ብሎ ቃል ኪዳን ከገባላቸው በኋላ በእብራውያን አቆጣጠር ኒሳን በሚባል ወር ሚያዝያ 8 ቀን በኢትዮጵያውያን አቆጣጠር በግዕዝና በአማረኛ ቋንቋ ሚያዝያ 9 ቀን በእግዚአብሔር ፈቃድ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች በሰላም ዐረፉ። ጌታችን የቅዱስ የክብር አባታችን የእስትንፋስ ክርስቶስ ነፍስ በከበሩ እጆቹ ይዞ አቅፍ አድርጎ ሳማት በመንግሥተ ሰማያትም እንደ መብረቅ በሚብለጨለጭ በሰማያዊ ልብስም አጎናፀፋት ከእርሱ ጋርም ወደ ጽርሐ አርያም አሳረጋት። ጌታችንም እንደ ፀሐይ የሚያበሩ የብርሃናትንም ልብስ አለበሳቸው ከዚህ ዓለም የተለየ ባሕርይ ከሚባል በጠራ እንቊ የተለበጠ የወርቅ መስቀል ያለበትን በዕፀ ሕይወት አበባ መልክ የተሠሩ ስምንት አክሊል አቀዳጃቸው። ❤ ጌታችንም ሰማያዊያን መላእክትን ሁሉ ቅዱሳን ጋር ከፍ ባለ ከሁሉ በተመረጠ በጻድቃን ዙፋን ላይ ያስቀምጡት ዘንድ አዘዛቸው በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም የዕረፍቱን በዓል ያከብሩለት ዘንድ መላእክትን እና ቅዱሳንን አዘዘ። ከአባታችን አቡነ እስትፋሰ ክርስቶስ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስና መዝገበ ቅዱሳን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሚያዝያ ፱ (9) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ለዘጠኝ ዓመት በዓባይ ባሕር ውስጥ በራሳቸው ተዘቅዝቀው በመቆም ስለ ኢትዮጵያውያ ሕዝብ ለጸለዩ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_እስትፋሰ_ክርስቶስ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                                                     ✝ ✝ ✝ ❤ #አቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ፦ የልደታቸው (የተወለዱበት) ቦታ ዳውንት ፀወን ዓባይ ይባላል። በአካባቢውም በገዳሙ አንፃር በሰሜን በኩል የእናታቸው አገር ደብረ ድባ የቄርሎስ ቦታ ይባላል የአባታቸውም አገር የእግዚአብሔር አብ ደብር አጠገብ ዳውንት ወይም ደብረ አስጋጅ ይባላል። ❤ አባታቸው ስም ቅዱስ መልአከ ምክሩ ሲሆን የእናታቸው ስም ቅድስት ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ ሁለቱም ደጋጎች እግዚአብሔር እንዳዘው በሕጉ ጸንተው ተስማምተው የሚኖሩ መልካም ሥራን በመሥራት እንደ ዘካርያስና እንደ ኤልሳቤጥ እውተኞች ነበሩ። እነርሱም ሁለት ደጋጎች ልጆች አሏቸው፤ የተባረከ መልካም ፍሬ በመጾምና በመጸለይ እግዚአብሔር የሚያገለግል በጸሎቱ ሰውን የሚጠቅም በጻድቃንም ዘንድ የተመረጠ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ ዘወትር ወደ እግዚአብሔር እና ወደ ድንግል ማርያም ይለምኑ ነበር እግዚአብሔር በዓይነ ምሕረት ተመለከታቸው ልመናቸውንም ሰምቶ አባታች አቡነ እስትንፋስ ክርስቶስ ሚያዝያ8 ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ8 ቀን ተወለዱ፤ በተወለዱበትም ዕለት ተነሥተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብለው ጣዕም ባለው አንደበትም አመሰገኑ ዘጠኝ ጊዜም ሕፃናትን ለሚያናግሩ ገዢ ለሚሆኑ ለሥላሴ፣ ለእመቤታችንና ለመስቀሉ ሰገዱ፡፡ ❤ የስማቸው ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡ ❤ በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባሕሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን አገባቸው፡፡ ለ3 ዓመታት ያህል በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኰሳት ምግብ የሚሆናቸው ዓሣ ከባህር ውስጥ በማውጣት አገልግለዋል፡፡ አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመሥዋዕት ወይኑን ለቍርባን በተአምራት አድርሰዋል፡፡ ❤ አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡ ጌታንም በቅዱሳኑ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን "ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው" ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡ አባታችን ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትን ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡ ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያሥነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በዓባይ በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ "ከመነኰሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ  በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡ ❤ ጻድቁ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ፀሐይ ልትገባ ስትል "በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁንም ቀጥ ብለሽ ቁሚ" ብለው ገዝተው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አሰጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ "አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ" ስትላቸው "እግዚአብሔር ይፍታሽ" ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡ በአምላክ ልቡና የሚገኝ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሚገኝ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ መድኃኔዓለም ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡ ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡ ይህንን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት የምናገኘው ከገድላቸው ላይ ነው፡፡ ❤ አቡነ እስትክሰ ክርስቶስ ሲያርፋ ቅዳሜ ማታ ለእሑድ አጥቢያ ሆኖ መሽቶ ከምሽቱም ሦስት ሰዓት በሆነ ዕለቱም ሰንበት ነበር። ያን ጊዜ እንደ ነጋሪት ቃልና እንደ ነጐድጓድ ያለ ድምጽ በሰማይ እንደ ፀሐይ እና እንደ ጨረቃ እንደ ከዋክብት የሚያበሩ የተለያዩ መብራቶች ታዩ ተገለጹ። ከዚህ በኋላ እነሆ በታላቅ መፈራትና በታላቅ ግርማ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ በአንድነት በሦስትነት እየተመሰገኑ መጡ፣ እመቤታችን ደናግላንን አስከትላ መጣች፣ አራቱ ኪሩቤል፣ ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ከማዕጠንታቸው ጋር፣ ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ቁጥራቸው ከማይታወቅ የእልፍ እልፍ ከሚሆኑ መላእክት ጋር እየዘመሩ እልል እያሉ መጡ፣ ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት፣ ዐሥራ አምስቱ ነቢያት፣ ከእስጢፋኖስ እስከ ተፈጻሜተ ሰማዕት ሊቀ ጳጳስ ጴጥሮስ ድረስ ያሉት ሰማዕታት ሁሉ፣ ቅዱሳን መነኰሳትም ከአባታቸው ከእንጦንስ ጀምረው እንዳለ፣ አንድ መቶ አርባ አራት ሺህ ሄሮድስ በቤተልሔም ያስፈጃቸው ሕፃናት፣ ከአዳም እስከዚያ ቀን ያሉ ቅዱሳን አባቶች ሁሉ መጡ።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_አምስተኛ_ቀን_ለቅዱስ_አዳም መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                       ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ጽፍት፦ ሃሌሉያ "ፀውኦ እግዚኡ ለአዳም ወይቤሎ ነዐ ውጻእ ምስለ ነፍሰ ጻድቃን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን ይቤሎ እግዚኡ ለአዳም አበ ኩሉ ዓለም። ትርጉም፡- አዳምን ጌታ ጠራው አለውም ከጻድቃን ነፍስ ጋር በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ና ውጣ/ግባ/ አለው፡፡ የዓለም ሁሉ አባት የአዳም ጌታው አለው፡፡                                      ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_መዝሙር፦ "ይቤሎ እግዚኡ ለአዳም ተፈሣሕ ዮም/፪/"። ትርጉም፦ ጌታ አዳምን ዛሬ ተደሰት አለው። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ።                 ❤ #ዕለተ_ሐሙስ።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #ሐሙስ_አዳም_ሐሙስ_ይባላል፦ በዚህ ዕለት ለአዳም የተሰጠው ተስፋ እና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን እናስባለን፡፡ የአዳም ተስፋው ተፈጽሞለት ከነልጅ ልጆቹ ወደቀደመ የገነት ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ሆና "የአዳም ኀሙስ" ተብላ ይኸው ትከበራለች፡፡ ሉቃ 24-25-49። ❤ #ምስባክ_መልዕክታት_ወንጌል_ቅዳሴ እንደ ብርሃነ ትንሣኤ። መልካም የበዓለ ትንሣኤ ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፰ (8) ቀን። ❤ እንኳን ለከበሩ ለሦስቱ ደናግል #ቅዱሳን_ለአጋቢስ_ለኤራኒና_ለሱስንያ ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለዕረፍታቸው በዓልና #ለመቶ_ሃምሳ_ሰዎች_በፋርስ_ንጉሥ እጅ በአንዲት ቀን ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከከበረ ሊቀ ጳጳሳት #ከአባ_ጢሞቴዎስ ከመታሰቢያው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                   ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱሳን_ደናግል_አጋቢስ_ኤራኒና_ሱስንያ፦ እሊህም ከሰሎንቄ አገርም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመልኩ ናቸው። ወላጆቻቸው እግዚአብሔር የሚፈሩ ነበሩ። ❤ እሊህም ደናግል በድንግልና በንጽሕና መኖርን ወደው በአንድ ምክር ተስማሙ ጽኑዕ በሆነ ገድልም ተጠመዱ ይልቁንም ያለማቋረጥ ተግተው ይጸልዩና ይጾሙ ነበር። ወደ ገዳሙም ተመልሰው ከመነኰሳት ጋራ ያገለግላሉ። ❤ ከሀዲ መክስምያኖስም በነገሠ ጊዜ የጣዖታትን አምልኮ አቁሞ የንጹሆችን ደም አፈሰሰ። እሊህም ደናግል በአዩ ጊዜ ፈርተው ወደ ተራራ ሸሹ በዚያም በዋሻ ውስጥ ተሸሸጉ በጾምና በጸሎት በመጸመድ ሳይወጡ በዋሻው ውስጥ ኖሩ። ❤ አንዲት የክርስቲያን ወገን አሮጊት በየሰባት ቀን ትጐበኛቸውም ነበር የሚያሻቸውንም ትሰጣቸዋለች የእጅ ሥራቸውን ትሸጥላቸውና ከእነርሱ የሚተርፈውን ትመጸውታለች። አንድ ሰውም ከከተማ ወጥታ ወደ ተራራ ሁልጊዜ ስትሔድ አያት ሳታየውም ተሠውሮ በሩቅ ተከተላት ወደ ዋሻውም እስከምትገባ ተመለከተ ከዚያ እስከምት ወጣም ተሠውሮ ቆየ በዚያ ቦታ ብዙ ገንዘብ ያላት መስሎታልና። ያቺ አሮጊትም ከዋሻው በራቀች ጊዜ ያ ሰው ገባ ለክብር ባለቤት ሙሽሮቹ የሆኑ የከበሩ አዕናቊ ደናግልን ቁመው ሲጸልዩ አገኛቸው ተሰሎንቄ ከተማ እስኪያደርሳቸውም አሥሮ ጐተታቸው። ❤ መኰንኑም ሃይማኖቻውን በጠየቃቸው ጊዜ ስለ እርሳቸው የተሰቀለ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመልኩ ክርስቲያኖች እንደሆኑ በፊቱ አመኑ። መኰንኑም ተቆጥቶ ይገርፋቸው ዘንድ አዘዘ የሚአሠቃይ ጽኑ ግርፈትም ገረፋአቸው ባልታዘዙና ወደ ክህደቱ ባልገቡ ጊዜ ወደ እሳት እንዲጨምሯቸው አዘዘ። በእሳትም ውስጥ በጣሏቸው ጊዜ ነፍሳቸውን ሚያዝያ 8 ቀን አሳለፉ በመንግሥተ ሰማያትም የሕይወትን አክሊል ተቀዳጁ። የቅዱሳን ደናግል አጋቢስ፣ ኤራኒና ሱስንያ በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #መቶ_ሃምሳ_ሰዎች_ሰማዕታት፦ እርሱም (የፋርስ ንጉሥ) ለአገሩ ቅርብ የሆነ ክርስቲያንን አገር ከበበና ብዙ የሰው ምርኮ ማርኮ ወደ አገሩ ወሰዳቸው ፀሐይን፣ ጨረቃንና ከዋክብትንም ያመልኩ ዘንድ አስገደዳቸው አይሆንም ባሉትም ጊዜ ራሶቻቸው ሚያዝያ8 ቆረጧቸው በመንግሥተ ሰማያትን የሕይወትን አክሊል ተቀበሉ እግዚአብሔርም በጸሎታቸው ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ8 ስንክሳር።                         ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ዕብል አልዒልየ ቃለ። #ለጢሞቴዎስ_አብ እንተ ደቀሰ መርጡለ። #ለኢየሱስ_ክርስቶስ ከመ ተብህለ። ኀበ ውስተ ኰኵሕ መልክዑ ተሥዕለ። አመ ውስተ ግብጽ እም ሄሮድስ ተድህለ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_8።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_አራተኛ_ቀን_ለቅዱስ_አልዓዛር መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰ።                                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ጽፍት፦ "ተንሥአ ወአንሥአ ኵሎ ሙታነ ተንሥአ ወፈወሶሙ ለሙቁሐን ተንሥአ ወፈወሶሙ ለሙቁሐን። አዝ............... በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን ወአግዓዘ ነፍሰ ጻድቃን። አዝ………………… ለአልዓዛር ተንሥእ ዘይቤሎ ወእውርኒ ዘፈወሶ በቃሉ። አዝ…………………… ትንሣኤሁ ገብረ በሰንበት በሣልስት ዕለት"። ትርጉም፡- ሙታንን ሁሉ ያስነሳ የታሠሩትንም የፈወሳቸው በታላቅ ሥልጣን ተነሣ የጻድቃን ነፍሳትን አጋዘ አልዓዛን ተነሥ ያለው ዕውሩንም የፈወሰው ትንሣኤውን በሰንበት አደረገ።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_መዝሙር፦ "ዛቲ ፋሲካ ዕለተ በርህ ወዋካ ዛቲ ፋሲካ(፪)"። ትርጉም፦ ይህቺ ፋሲካ የብርሃን ቀን ናት። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ።                   ❤ #ዕለተ_ረቡዕ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ረቡዕ_አልአዛር_ይባላል፡- በዚህ ዕለት ትንሣኤና ሕይወት የሆነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አልዓዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን፡፡ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ በድልም ያረገ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡ ❤ #ምስባክ_መልክታት_ወንጌል_ቅዳሴ እንደ ብርሃነ ትንሣኤ። መልካም የበዓለ ትንሣኤ ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፯ (7) ቀን። ❤ እንኳን አምላክን ለወለደች ለእመቤታችን #ለቅድስት_ድንግል_ማርያም_አባት_ለጻድቁ_ቅዱስ_ኢያቄም ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ ከሰማዕታት #ቅዱሳን_ከአጋቦስና_ከቴዎድራ ደግሞ ከብልዮን ገዳም #ከአባ_ሙሴ_ልጅ_ከአባ_መቅሩፋ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #ጻድቁ_ቅዱስ_ኢያቄም፦ ይህም ጻድቅ በሦስት ስሞች ይጠራል እሊህም ኢያቄም፣ ዮናኪር፣ ሳዶቅ ናቸው እርሱም ከይሁዳ ነገድ ከዳዊት ዘር ነው። ይህም የአልዓዛር የኤልዩድ ልጅ ኢያቄም በትውልድ ሐረግ እስከ ሰሎሞንና እስከ ንጉሥ ዳዊት የሚደርስ ነው። ይኸውም በዙፋኑ የሚቀመጥና ለዘላለሙ በእስራኤል ዘሥጋ በእስራኤል ዘነፍስ ነግሦ የሚኖር ከዘሩ ሊሰጠው ጌታ የማለለት ነው። ❤ ሚስቱ ቅድስት ሐናም መካን ሆነች ሁለቱም ወደ እግዚአብሔር አዘውትረው ይጸልዩና ይማልዱ ነበር። እግዚአብሔር ልመናቸውን ተቀብሎ ይችን ጣፋጭ የሆነች መልካም ፍሬ ዓለሙን ሁሉ ከረኃበ ነፍስ ያዳነች ሰጣቸው። መሪር የሆነ ተግዢነትንም ከሁሉ በእርስዋ አስወገደ። ለዚህም ጻድቅ ኢያቄም ለክብር ባለቤት ለኢየሱስ ክርስቶስ አያት መሆን ተገባው ድንቅ ስለ ሆነ ሥጋዌው ከልጁ ስለመወለዱ ነው። ❤ እግዚአብሔር በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ደስ በአሰኘው ጊዜ በልቡናው ደስ ብሎት መሥዋዕቱን አቀረበ። ከላዩም ከወገኖቹም ልጆች ኀፍረትን አስወገደ። ❤ አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ጡት ከአስተዋት በኋላ ለእግዚአብሔር እንደተሳሉ ተሸክመው ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወስደው አስገቧት። ጻድቅ ኢያቄምም ጥቂት ዘመን ኑሮ ሚያዝያ7 በሰላም ዐረፈ። የከበረች በረከቱም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ7 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለኢያቄም_ዘኮኖ_እምሔወ። ለዘሰማየ ሰዘረ ወአድባረ ደለወ። ዕበየ ዝንቱ ጻድቅ ሶበ ተዜነው። እምእለ ወለዱ በዓለም አኃተ ወአኃወ። እምልበ ኵሉ ያንዕስ አበወ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_7።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_ሦስተኛ_ቀን_ለቅዱስ_ቶማስ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን።             ❤ #ዕለተ_ማክሰኞ። ❤ #ቶማስ፦ ማለት "ፀሐይ" ማለት ነው፡፡ ይኸውም ሐዋርያ በቀድሞ ስሙ ዲዲሞስ እየተባለ ይጠራል፡፡ዲዲሞስ ማለት ጨለማ ማለት ነው፡፡ በኋላ ግን ስሙ ተውጦ ቶማስ ፀሐይ ተባለ፡፡ ❤ #ማክሰኞ_ቶማስ_ይባላል፦ በዚህ ዕለት ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ፤ ጌታዬና አምላኬ ብሎ መመስከሩ ይዘከራል፡፡ ዮሐ 20፥27-29። የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ሐዋርያ አልነበረም ኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት። ትንሣኤ ሙታን ከማያምኑ ከሰዱቃውያን ወገን ስለነበር እኔ ሳላይ አላምንም በማለቱ በዚህ ጥያቄው መሠረት በሳምንቱ ጌታችን በድጋሚ ስለተገለጸ ለዚህ መገለጹ መታሰቢያ ሆና ዕለቲቱ "በቶማስ" ተሰየመች፡፡ ዮሐ 20-24-30። ❤ ሐዋርያው ቶማስ የእመቤታችንን ዕርገቷን አስቀድሞ በብቸኝነት ያየው እርሱ ነው፡፡ በአፍሪካና አካባቢዋ እስከ ቻይና ድረስ ሄዶ ወንጌልን ሰብኳል፡፡ ❤ ዛሬም ሕንድ ውስጥ በመንበሩ ላይ የቅዱስ ቶማስ ቀኝ እጁ በሕይወት እንዳለች ሆና ትታያለች፡፡ መለኮትን (የጌታችንን የተወጋ ጎኑን) የዳሰሰች ቅድስት እጅ ናትና ዛሬም ድረስ ሕያው ናት፡፡ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ሲሾሙም የቅዱስ ቶማስን ቀኝ እጅ በሚሾመው ፓትርያርክ ላይ ጭነው ነው፡፡ ❤ #ምስባክ_መልክታት_ወንጌል_ቅዳሴ እንደ ብርሃነ ትንሣኤ። መልካም የበዐለ ትንሣኤ ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሚያዝያ ፮ (6) ቀን። ❤ እንኳን አስቀድማ ዘማዊ ለነበለች በኋላ ግን በንስሐ ተመልሳ በዮረዳኖስ በረሃ ብቻዋን ለ47 ዓመት ስትጋደል ለኖረችው ለከበረች #ለግብጻዊት_ቅድስት_ማርያም ለዕረፍቷ መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                              ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅድስት_ማርያም_ግብጻዊት፦ ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ሁና ወላጆቿ ክርስቲያን ናቸው። ዕድሜዋ ዐሥራ ሁለት ዓመት በሆናት ጊዜ የመልካም ሥራና የሰው ሁሉ ጠላት ሸንግሎ አሳታት በእርሷም የማይቆጠሩ የብዙዎችን ነፍስ አጠመደ እርሱ ሰይጣን ስለ ዝሙት ፍቅር ያለ ዋጋ ሥጋዋን እስከ መስጠት አድርሷታልና። በዚህም በረከሰ ሥራ ውስጥ ኖረች በየዕለቱም የኃጢአት ፍቅር በላይዋ ይጨምርባት ነበር። ❤ ሰውን የሚወድ የእግዚአብሔርም ቸርነት ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ሊባረኩ ወደ ኢየሩሳሌም ለመሔድ የሚሹ ሰዎችን ገለጠላት። ከእርሳቸው ጋራ ትሔድ ዘንድ ልቧ ተነሣ ከብዙ ሰዎችም ጋራ በመርከብ ተሳፈረች። ባለ መርከቦችም የመርከብ ዋጋ በጠየቋት ጊዜ ስለ መርከብ ዋጋ ያመነዝሩባት ዘንድ ሰውነቷን ሰጠቻቸው ኢየሩሳሌም እስከ ደረሰች ይህን ሥራ አልተወችም። ❤ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ወደ አለች ቤተ ክርስቲያን ትገባ ዘንድ በወደደች ጊዜ መለኮታዊ ኃይል መግባትን ከለከለቻት። እርሷም ከሚገቡ ሰዎች ጋራ ትገባ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደከመች ነገር ግን ከለከላት እንጂ የጌታ ኃይል አልተዋትም። ❤ ከዚህም በኋላ ስለ ረከሰ ሥራዋ አሰበች በልቧም እያዘነችና እየተከዘች ወደ ሰማይ ወደ እግዚአብሔር ዐይኖቿን አቀናች በማንጋጠጥዋም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል አየች። በፊቷም አለቀሰች "ፍጥረቶችን ሁሉ የምትረጅአቸው አምላክን የወለድሽ እመቤቴ ተዋሽኝ ከሁሉ ሰዎች ጋራ ገብቼ የመጣሁበትን ሥራዬን የፈጸምኩ እንደሆነ ያዘዝሽኝን ሁሉ እኔ አደርጋለሁ" ብላ በማመን ለመነቻት። እንዲህም ስትል ወደ ጌታችን መቃብር ቤተ ክርስቲያን ፈጥና ገባች በገባችም ጊዜ የበዓሉን ሥራ ፈጸመች። ❤ ከዚህም በኋላ አምላክን ወደ ወለደች ወደ እመቤታችን ወደ ከበረች ድንግል ማርያም ስዕል ተመልሳ ወደ እርሷ መሪር ልቅሶ እያለቀሰች ረጅም ጸሎትን ነፍስዋን ለማዳን እርስዋ ወደ ወደደችው ትመራት ዘንድ አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል "ከዮርዳኖስ በረሀ ብትገቢ አንቺ ዕረፍትንና ድኅነትን ታገኚአለሽ" የሚል ቃል ወጣ። ❤ ከእመቤታችን አምላክን ከወለደች ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ይህን ቃል ተቀብላ ወዲያውኑ ወጣች። በውጪም አንድ ሰው አግኝታ ሁለት ግብሽ ሰጣትና አምባሻ ገዛችበት። ከዚያም በኋላ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግራ ጽኑዕ ተጋድሎ እየተጋደለች በበረሀው ውስጥ አርባ ሰባት ዓመት ኖረች ሰይጣንም አስቀድማ በነበረችበት በዝሙት ጦር ይዋጋት ነበር። እርሷ ግን በተጋድሎ ጸናች ከዚያም ከገዛችው አምባሻ ብዙ ቀን ተመገበች። ሁለት ሁለት ቀን ሦስት ሦስት ቀን ጹማ ከዚያ አንባሻ ጥቂት ትቀምስ ነበር በአለቀም ጊዜ የዱር ሣር ተመገበች። ❤ በዚያችም በዮርዳኖስ በረሀ እየተዘዋወረች አርባ ሰባት ዓመት ሲፈጸምላት እንደ ገዳሙ ልማድ የከበረች አርባ ጾምን ሊፈጽም ቅዱስ ዞሲማስ ወደዚያች በረሀ መጣ። በሱ ደብር ላሉ መነኰሳት ልማዳቸው ስለሆነ በየዓመቱ ወደ በርሀ ወጥተው የከበረች የአርባ ቀን ጾም እስከምትፈጸም በጾምና በጸሎት ተጸምደው በገድል ይቆያሉ። ስለዚህም ዘሲማስ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ በወጣ ጊዜ የሚጽናናበትን ያሳየው ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው። በበረሀውም ውስጥ ሲዘዋወር ይቺን ቅድስት ሴት ከሩቅ አያት የሰይጣን ምትሐት መሰለችው በጸለየም ጊዜ ከሰው ወገን እንደሆነች ተገለጠችለት። ወደርሷም ሔደ እርሷ ግን ከእረሱ ሸሸች። ወደርሷም ይደርስ ዘንድ ከኋላዋ በመሮጥ ተከተላት። ከዚያም በኋላ "ዘሲማስ ሆይ ከእኔ ጋራ ለመነጋገር ከፈለግህ ጨርቅን በምድር ላይ ጣልልኝ እከለልበት ዘንድ" ብላ በስሙ ጠራችው። በስሙ በጠራችውም ጊዜ እጅግ አድንቆ ጨርቁን ጣለላት ያን ጊዜም ለብሳ ሰገደችለት እርሱም ሰገደላት እርስበርሳቸውም ሰላምታ ተሰጣጥተው በላዩዋ ይጸልይላት ዘንድ ለመነችው እርሱ ካህን ነውና ካህን ስለሆነ። ❤ ከዚህ በኋላ ገድሏን ታስረዳው ዘንድ ቅዱስ ዘሲማስን ለመናት ከእርሷ የሆነውን ሁሉ ከመጀመርያው እስከ መጨረሻው ነገረችው። እርሷም በሚመጣው ዓመት የክብር ባለቤት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋውና ደሙን ከእርሱ ጋራ ያመጣላት ዘንድ ለመነችው እርሱም እሺ አላት። ❤ ዓመትም በሆነ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን በጽዋ ውስጥ ያዘ ደግሞ በለስ ተምርን በውኃ የራሰ ምስር ይዞ ወደርሷ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ቅድስት ማርያምን በዮርዳኖስ ወንዝ ዳር ስትሔድ አያት ወደርሱም ደርሳ እርስበርሳቸው ሰላምታ ተሰጣጡ በአንድነትም ጸለዩ ከዚያም በኋላ ሥጋውንና ደሙን አቀበላት። በለሱን ተምሩንና ምስሩንም አቀረበላትና ትመገብለት ዘንድ ለመናት ስለበረከት ከምስሩ በእጅዋ ጥቂት ወሰደች። ደግሞም በሁለተኛው ዓመት ወደእርሷ ይመለስ ዘንድ ለመነችው። ሁለተኛ ዓመትም በሆነ ጊዜ ወደዚያ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ያቺ ቅድስት ሴት ሙታ አገኛት በራስጌዋም "ድኃዩቱን ግብጻዊት ማርያምን ከተፈጠረችበት አፈር ውስጥ ቅብራት" የሚል ጽሑፍ አገኘ። ከጽሑፍ ቃልም የተነሣ አደነቀ። ❤ ያን ጊዜም ከግርጌዋ አንበሳን ሲጠብቃት አየ እርሱ መቃብርዋን በምን እቆፍራለሁ ብሎ ያስብ ነበር በዚያም ጊዜ ያ አንበሳ በጥፍሮቹ ምድሩን ቆፈረ የከበረ ዘሲማስም በላይዋ ጸሎት አድርጎ ቀበራት። ወደ ገዳሙም ተመልሶ ለመነኰሳቱ የዚችን የከበረች ግብጻዊት ማርያምን ገድሏን እንዳስረዳችው ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ነገራቸው እጅግም አደነቁ ምስጉን ልዑል እግዚአብሔርም አመሰገኑት። መላው ዕድሜዋም ሰማንያ አምስት ሁኗታል። በቅድስት ማርያም ግብጻዊት እግዚአብሔር በእርሷ ጸሎት ለዘላለሙ ይማረን አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ6 ስንክሳር።