ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
رفتن به کانال در Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
نمایش بیشتر636
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-47 روز
-1230 روز
آرشیو پست ها
በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የቅዱስ_ኤጲፋንዮስ_ሥጋው_ወደ_ቆጵሮስ መመለስ፦ ይህም እንዲህ ነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ወደ መንበረ ሢመቱ እንደማይደርስ ትንቢት እንደተናገረለት ወደ ቆጵሮስ ሳይደርስ በመርከብ ውስጥ ሳለ ግንቦት ዐሥራ ሰባት ቀን ዐረፈ። በዐረፈም ጊዜም በመርከብ ጭነው ወደ ቆጽሮስ ከተማ አደረሱት። ካህናቱና ሕዝቡ ሁሉ መጡ ከሳቸውም ጋር ወንጌሎች መስቀሎች መብራቶችና ማዕጠንቶችም የሐዋርያት ጉባኤ ከታላቂቱ ቤተ ክርስቲያን እስኪያደርሱት በዝማሬ በማኅሌት በሚገቡት ጸሎቶች ሁሉ እያመሰገኑ ሥጋውን ተሸክመው ካህናቱም መቃብሩን በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ሊያዘጋጁ ወደዱ። ቀድሞ ስለ ክፉ ሥራቸው ቅዱስ ኤጲፋንዮስ አውግዞአቸው የነበሩ ሁለት ዲያቆናት ተቃወሟቸው። ስለዚህም አርባ ቀን ተቀመጠ ነገር ግን ሽታው እንደ ሙታኖች ሽታ አልተለወጠም እንደ አንቀላፋ ሰው እንጂ።
❤ ከዚህም በኋላ አንድ ደግ ዲያቆን ወደ ቅዱስ ሥጋ ቀርቦ "አባቴ ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ አንተ ባለሟልነት እንዳለህ እኔ አውቃለሁ። ብትፈቅድስ ክፉዎች ተቃዋሚዎችን ልታሸንፋቸው ትችላለህ" አለ። የቅዱስ ኤጲፋንዮስንም እጅ ይዞ ምድርን መታባት በዚያንም ጊዜ ሁለቱ ዲያቆናት በግምባራቸው ተደፉ። ለመሞትም ደረሱ ወደ ቤታቸውም ወስደዋቸው ሞቱ።
❤ ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ካህናቱ በሚጣፍጡ ሽቱዎች ገንዙት። በከበሩ ልብሶችም ጠቅልለው ከከበረ ደንጊያ በተሠራ ሣጥን ውስጥ ጨምረው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ቀበሩት። ቀድሞ በሕይወቱ ሳለ እንደሚሠራው ከሥጋው ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ #የግንቦት_28_ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰአሉ_ለነ_አብርሃም_ይስሐቅ_ወያዕቆብ_አበወ ሕዝብ ወአሕዛብ ወዘመሐይምናን መክብብ ሰአሉ ለነ አስተምሕሩ ለነ"። ትርጉም፦ የምዕመናን ሹሞች የአሕዛብና የሕዝብ አባቶች #ቅዱሳን_አብርሃም_ይስሐቅ_ያዕቆብ ፈጽማችሁ ለምኑልን አማልዱ፡፡ #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በሰዓታት_ላይ፡፡
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለአመተ_ክርስቶስ_መንበርተ_ዓለም መኒና። እንተ ረሰየት ይእቲ ንቅዓተ ኰኵሕ መካና። ሠላሳ ወስምነ ዓመታት እስከ ኮና። ይቤሉ ነጋድያን ሶበ ምውተ ረከብና። ውሳጤ በዓት በህየ ቀበርና"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የግንቦት_28።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "የሐዩ ወይሁብዎ እምወርቅ ዓረብ። ወዘልፈ ይጼልዩ በእንቲአሁ። ወኵሎ አሚረ ይድኅርዎ"። መዝ 71፥15 ወይም መዝ 4፥4። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ2፥1-21 ወይም ሉቃ 9፥18-23።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አሌ ሎን ለከናፍረ ጒሕሉት። እለ ይነባ ዓመፃ ላዕለ ጻድቅ። በትዕቢት ወበመንኖ"። መዝ 30፥18 ወይም መዝ 50፥14-15። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 7፥29-ፍ.ም፣ ያዕ 2፥19-ፍ.ም እና የሐዋ.ሥራ 5፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 12፥22-39 ወይም ማቴ 9፥9-18። የሚቀደሰው የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ዐማኑኤል በዐልና የበዐለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን.
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት_፳፰ (28) ቀን።
❤ እንኳን #ለቅዱስ_ዐማኑኤል_ዓመታዊ_የንግሥ በዓል #ለአርስተ_አበው_ቅዱሳን_ለአብርሃም፣ #ለይስሐቅና_ለያዕቆብ_ለመታሰቢያቸው_በዓል፣ ተጋዳይ ለሆነች ዓለምን ንቃ ለተወች፤ አባ ዳንኤል ስርሷ እንደተናገረ የዓለምን ፍላጎት ሁሉ ድል ለነሣች፤ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት አንዴ ወደ ገዳም ይዛ በሔደች ሽንብራና የጽዋ ውኃ ሳያልቅባት በተሰነጠቀ ዐለት ውስጥ ስትጋደል ለነበለች #ለቅድስት_አመተ_ክርስቶስ_ለዕረፍት_በዓል፣ #ለአባ_ጳኵሚስ_ገዳም ለሆነ በዕረፍቱ ጊዜ ሥጋው አጋዘን ተሸክመው ወደ ሚቀበርበት ቦታ ላመጡቱ #ለአባ_መርቆሬዎስ_ለዕረፍት_በዓልና ለታላቁ #ለቆጵሮስ_አገር_ሊቀ_ጳጳስ_ለቅዱስ_ኤጲፋንዮስ #ሥጋው_ወደ_ቆጵሮስ_ለደረሰበት_በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚህ ከሚታሰቡ፦ በሰማዕትነት ከዐረፉ #ከአባ_ጌርሎስና #ከአርባ_አምስት_ልጆቹ፣ #ከአባ_ስንጣና_ከሰማዕት_አጋቦስ_ከመታሰቢያቸው ረድኤና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_አመተ_ክርስቶስ፦ አባ ዳንኤል እንዲህም አለ "በረሀም ሳለሁ በሌሊት ተነሥቼ በጨረቃ ብርሃን ተጓዝኹ በተራራ ላይ የተቀመጠ ሰውንም አየሁ ጠጉሩም ሁለመናውን ሸፍኖታል በልቤም ወደርሱ ሔድሁ። በአየችኝም ጊዜ ወደ ተሠነጠቀው አለት ውስጥ ገባች "ሰው ሆይ ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ በረከትህን እንድቀበል እማልድሃለሁ" አልሁ እጅግም አብዝቼ ለመንሁ። ከዚህም በኋላ "አባት ሆይ አልወጣምና ይቅርታ አድርግልኝ" አለችኝ። እኔም "ስለምን አልኋት" እርሳም "እኔ ሴት ነኝ ራቁቴን ስለሆንኩ" አለችኝ። ይህንንም ሰምቼ የለበስኩትን ዐጽፍ ጣልሁላት ለብሳም ወጣች በአንድነትም ጸለይን።
❤ ከዚህ በኋላ "እናቴ ሆይ ከዓለም ወደዚህ ስለመውጣትሽ ይኸንን የተሠነጠቀ ዐለት እንዴት እንዳገኘሽ ንገሪኝ አልኋት"። እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችልኝ በወላጆቼ ቤት ድንግል ሁኜ በኢየሩሳሌም የምኖር ነኝ ሁል ጊዜ የሚጎበኘኝ ከእኔ ጋራ የሚነጋገር አንድ መነኰስ ነበር። ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ወደርሱ ሔድኹ በእግዚአብሔር ፊትም ኃጢአቴን እየታመነ ሲአለቅስ አገኘሁት። ደጅንም በአንኳኳሁ ጊዜ አልከፈተልኝም እየተጸጸተ ልቅሶን አበዛ እንጂ። በዚያን ጊዜ በልቤ እንዲህ አልኩ እኔስ ስለ ጒስቍልናዬና ስለ ኃፍረቴ የማላለቅስና የማልጸጸት ለምድነው ወደ ማደሪያዬም ፈጥኜ ሔድኹ ማቅ ለበስኩ በዘንቢልም ሽምብራ በጽዋ ውኃን ያዝሁ። በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ዘንድ እንዲህ ብዬ ጸለይኩ "አቤቱ ጽኑዕ ኃያል ለዘላለሙ ድንቅ የሆንክ የጠፋትን የምታድን የወደቁትንም የምታነሣቸው ወደ አንተ የሚጮኹትንም የምትሰማቸው የታመነችብህ ባሪያህን ታድናት ዘንድ ይቅርታህንና ምሕረትህን ላክ። ከምግባር ድኃ የሆንኩ ባሪያህን ጐብኘኝ ንስሐዬንም ተቀበል። ለረጅም ዘመን ስንቅ ይሆነኝ ዘንድ ይህን ሽምብራና ይህን የጽዋ ውኃ ባርከው ስለ ነፍሴ ድኅነት የአሰብኩትን እንዳላቃልል ለሆዴ ምግብ ስለሚአሻኝ"።
❤ ከዚህ በኋላ ነፍሴን በእግዚአብሔር ላይ በመጣል ወጥቼ ወደ በረሀ ሔድኹ እስከ ኤርትራ ባሕርም ደረስኩ። ከዚያም ወደዚህ በረሀ መጥቼ ይህን የተሠነጠቀ ዐለት አገኘሁ ይህ እግዚአብሔር ያዘጋጀልኝ መኖሪያዬ ነው አልሁ። "እንሆ በዚህ በረሀ ውስጥ ሠላሳ ስምንት ዓመት ሆነኝ ያለ አንተ ሰው አላየሁም። ይህም የዘንቢል ሽምብራና የጽዋ ውኃ ሠላሳ ስምንት ዓመት ከእርሳቸው ስመገብ አልጎደሉም ልብሴ ግን አለቀ ነገር ግን ይህ ቦታ ስለ ልብስ መከለያ ሆነኝ። የበጋ ፀሐይ ትኵሳትም አላስቸገረኝም ቊር ቢሆንም በዕድሜዬ ዘመን ሁሉ አላስጨነቀኝም"። ከዚህ በኋላም ከዘንቢል ካለው ሽምብራ እንድመገብ ማለደችኝ ከሽምብራውም በላሁ ከውኃውም ጠጣሁ። ግን አልጐደለም እግዚአብሔርንም አመሰገንሁት ልብሴንም ልተውላት ወደዱሁ እርሷም "ከዚህ የተሻለ አምጣልኝ" ብላ ይህን እምቢ አለችኝ።
❤ ከዚህ በኋላም ከእርሷ ዘንድ ሔድኩ ወደ ገዳም ደርሼ ስርሷ ለአበ ምኔቱ ነገርኩት። "እርሱም ሁለት ልብስ ያለው ለሌለው አንዱን ይስጥ ብሎ ጮኸ ፈቃደኞች የሆኑም አመጡለት ያን ጊዜም ይዤ ሔድኩ ለአመተ ክርስቶስ ልሰጣት ብዙ ደከምኩ እርሷን በመፈለግ ዞርኩ አላገኘኋትም። ከጥቂት ቀኖች በኋላም አረጋውያን ወደ እኔ መጡ እንህም አሉኝ "ወደ ኤርትራ ባሕር የሚያደርሰውን መንገድ ይዘን በጣኔዎስ በረሀ ስንጓዝ ከዋሻ ዘንድ ሴት ተቀምጣ አይተን ከእርሷ በረከት ለመቀበል ሮጥን ሽሽታ ከዋሻው ገባች ወደ ዋሻውም አፍ ቀረብን ግን አላየናትም። ሽምብራ በዘንቢል ውኃም በጽዋ አግኝተን በላን ጠጣን ያን ጊዜም አለቀ እስከ ንጋትም አደርን።
❤ በነጋም ጊዜ በረከቷን ለመቀበል ቅድስቲቱን ፈለግናት ሙታም አገኘናት ጠጒሯም ሥጋዋን ሁሉ ሸፍኖአል። በዚያም ሰገድን በበዓቷም ውስጥ ቀበርናት የዋሻውንም አፍ በደንጊያ ዘጋን የቅድስቲቱን በረከት እንድንቀበል አድሎናልና እግዚአብሔርን እያመሰገን ወደ በዓታችን ገባን"። በሰማሁም ጊዜ አስቀድሜ ያገኘኋት እንደሆነች አወቅሁ የነገራችኝንም ሁሉ ነገርኳቸው። ጠላት ዲያብሎስን ድል ያደረገው ዘንድ ክፉዎች አጋንንትንም ደካማውን ድኃ የሚረዳ የተመሰገነ እግዚአብሔርን ፈጽመን አመሰገን ነው። ለእግዚአብሔር ይስጋና ይሁን እኛንም በዘመች ቅድስት አመተ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን በረከተበም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_መርቆሬዎስ፦ አባ እንጦንዮስ እንዲህ አለ "ለእኔ ገዳም አለኝ ይኸውም የወንድማችን የመርቆሬዎስ ዕረፍቱ ቀረበ" እያሉ ወደእኔ መነኰሳት የመጡበት ነው እኔም በረከቱን ለመቀበል ወደርሱ በሒድኩ ጊዜ ነፍሱ ከሥጋው ሳትለይ በተመሥጦ ላይ አገኘሁት። ከመነኰሳቱ ጋራ በእርሱ ዘንድ ሦስት ሌሊቶች ኖርን በሦስተኛዪቱም ዕለት ነፍሱ ተመልሳ ዐይኖቹን ገለጠ በአየንም ጊዜ "ከእኔ ዘንድ ምን ሰበሰባችሁ" አለን እኛም የሆነውን ሁሉ ነገር ነውና ከዚህም በኋላ ያየውን እንዲነግረን ለመነው እርሱም የሚያስፈራ ሰው ወደርሱ መጥቶ ነፍሱን እንደወሰደ የኃጥአንን ሥቃይ እንዳሳየው የጻድቃንንም ዋጋቸውንና ተድላቸውን እንዳየው ነገራቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ወዮ ብሎ በማልቀስ በግምባሩ ከምድር ላይ ተደፋ እንዲህም አለን "ወንድሞቼ ሆይ ወደ ሐራጺት ገዳም ወደ አባ ጊዮርጊስ ማደሪያ ሒዱ። ከእኔ ጋራ የነበረውን መለአክ መርቆሬዎስን መልሳችሁ በትንሽ በዓት ውስጥ ሲጋደል የኖረ ጊዮርጊስን አምጡት ሲል ሰምቼዋለሁና ይቺም ሥጋው አስቲቋጠር የተጋደለባት የጨው በረሀ ናት"። ወንድሞች መነኰሳትም በሔዱ ጊዜ ሙቶ አገኙት ወደዚህ ገዳምም አምጥተው ቀበሩት። ይህም ወንድም መርቆሬዎስ እንደ ደረቀ እንጨት እስቲሆን ሥጋውን እጅግ አሠቃየ።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ገዳም ይሔድ ዘንድ ተሰናበተኝ። ደግሞ "ግንቦት ሃያ ስምንት ቀን ወደኔ ና ታገኘኛለህና" አለኝ። በቀጠረኝም ቀን ወደርሱ ሒጄ አገኘሁደትና "እኔ ወደ አባቶቼ እሔዳለሁ" ወደ አንተም ሦስት አጋዘኖች ይመጣሉ ሥጋዬም በጀርባቸው ላይ ጫን እነርሱም ወደ ቦታዬ በእግዚአብሔር ፈቃድ ይመሩሃል። በዚያም በማደሪያዬ ውስጥ ድፈኑኝ" አለኝ። እንደ ቃሉም ሆነለት ከመቃብሩም ቍጥር የሌላቸው ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ አባ መርቆሬዎስ ጸሎት ይማረን
+9
በደብራችን በዚህ ሳምንት የተካሄዱ ጉባኤዎች እና የንግስ በዓል እግዚአብሔር በፈቀደው በመልካም ሁኔታ ተከውነው አልፈዋል
እነሱም
የእሕቶች ጉባኤ
የዝክረ ያሬድ
የ፳፭ ጉባኤ
የ፳፮ ንግስ በዓል ናቸው
ከሚዲያና ዕቅበተ እምነት ክፍል የምስል ማህደር በጥቂቱ።
❤ በአረጀና በሸመገለም ጊዜ የእስራኤል ልጆች ከተማረኩበት ተመልሰው ቤተ መቅደስን ሠሩ። ቅዱስ ዕንባቆምም ኢየሩሳሌም ደርሶ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ በታላቅ ደስታም ተቀበሉት ትንቢቱንም ሊሰሙ ወደርሱ ተሰበሰቡ አፉንም ከፍቶ በመንፈስ ቅዱስ እንዲህ አለ "አቤቱ ድምፅህን ሰማሁ ሰምቼም ፈራሁ ሥራህንም አይቼ አደነቅሁ" አለ። ስለ መድኃኒታችንም መውረድና በይሁዳ ክፍል በሆነች በቤተ ልሔም ስለመወለዱ ሲናገር "የተመሰገነ እግዚአብሔር ግን ከፋራን ተራራ ከቴማን ከይሁዳ አውራጃ ይመጣል" ብሎ እስከ መጨረሻው ተናገረ ከነቢያት መጻሕፍትም ጋራ ደመርዋት።
❤ ከዚህ በኋላ ከእስራኤል ልጆች አንዲት ሴት ወደርሱ መጣች እያለቀሰችም እንዲህ አለችው "ሁለት ልጆች ነበሩኝ ጣዖት እንዲአመልኩ ፈለጉአቸው እምቢ በአሉ ጊዜም ገድለው በጐዳና ላይ ጣሉአቸው"። ተገድለው ወደአሉበትም አብሮዋት ሔደ ነፍሳቸውንም ይመልስላቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው ልመናውንም ተቀብሎ በሕይወት አነሣቸው"።
❤ ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ዘመዶቹን ጠራቸው። እንደሚሞትም ነገራቸውና አንዲት ሰዓት ያህል ወደላይ እየተመለከተ ተቀመጠ። እንሆ እንደ ሰው ክንድ ያለች ታላቅ ክንድ የቤቱን ጣሪያ ሠንጥቆ ወረደች ወደ አፉም ተዘርግታ ነፍሱን ወሰደች ያን ጊዜም ዐረፈ። በክርስቲያን ንጉሥ በአንስጣስዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ ገድሉን በአነበበ ጊዜ አድንቆ በግብጽ ደቡብ ቀርጣስ በሚባል ቦታ በስሙ ቤተ ክርስቲያን ሠራለት እርሷም በዚች ቀን ከበረች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የነቢዩ ቅዱስ ዕንባቆም በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቀሲስ_ቅዱስ_አብቊልታ፦ ይህ የእንጽና አገር የሆነ ባለ መድኃኒት ነው በሽተኞችን በጎ ሥራ በመሥራት ያለ ዋጋ ያክማቸዋል ደግሞም የሚበሉትን፣ የሚጠጡትን፣ የሚለብሱትን የሚሹትን ሁሉ ይሰጣቸዋል።
❤ በዚያም ወራት ወደ ሰዒዲ አውራጃ ወደ መኰንኑ አርያኖስ ዲዮቅልጥያኖስ ላከ የዚያችን አገር ሰዎች ለጣዖታት እንዲሰግዱ ያስገድዳቸው ዘንድ። በዚያንም ጊዜ ይህን ቅዱስ ያዙት ወደ እስሙናይንም ወስደው በመኰንኑ ፊቱ አቆሙት መኰንኑም ወደርሱ ይመልሰው ዘንድ በጎ ቃልን ተናገረው ሊመለስም ባልቻለ ጊዜ ቆዳው እስቲሠነጣጠቅ እንዲገርፉት አዘዘ ከዚያም በኋላ በሕይወት እያለ በእሳት አቃጠሉት ገድሉንም በዚህ ፈጸመ ምዕመናን ወጥተው በድኑን ወሰዱ ከከተማው ደብባዊ በሆነ ተራራ ላይ ገንዘው በክብር ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የቅዱስ አብቊልታ በረከቱም ከእኛ ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ምንጭ፦ #የግንቦት_24 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለአልዓዛር_ወፊንሐስ ካህናት ዐበይት እለ ቅቡዓን በቅብዐ ዕረፍት"። ትርጉም፦ በጣፈጠ ቅብዐ ክህነት ለተቀቡ ለታላላቆች ካህናት አልዓዛር ና ፊንሐስ ሰላምታጨይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦"ዘገብረ ተአምረ በግብጽ። ወመንክረ በሐቅለ ጣኔዎስ። ወረሰየ ደመ ለአፍላጊሆሙ"። መዝ 77፥43-44 ወይም መዝ 36፥18። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 2፥13-16 ወይም ማቴ 10፥40-ፍ.ም
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ለክብር_ባለቤት_ለጌታችን_ኢየሱስ ክርስቶስ #ከእናቱ_ከእመቤታችን_ከቅድስት_ድንግል ማርያም #ከአረጋዊው_ቅዱስ_ዮሴፍና_ከቅድስት_ሰሎሜ ጋራ ወደ #ግብጽ_ምድር_በስደት_ለወረዱበት ዓመታዊ በዓል፣ #ከዐሥራ_ሁለቱ_ደቂቅ_ነቢያት አንዱ ለሆነው #ለነቢዩ_ዕንባቆም_ለዕረፍት መታሰቢያ በዓል፣ #ለአሮን_ልጅ #ለካህኑ_ለቅዱስ_አልዓዛር ለዕረፍት በዓልና #ከእንጽና_አገር ለሆነ ለከበረ ለቀሲስ #ቅዱስ_አብቊልታ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚህ ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከቅዱሳን_አርከሌድ፣ #ከቴፍላስና_ከማርዩ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን፡ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #በዚች_ቀን_የክብር_ባለቤት_ጌታችን_ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍና ከቅድስት ሰሎሜ ጋራ ወደ ግብጽ ምድር ወረደ።
❤ ያን ጊዜም እርሱ ጌታ የሁለት ዓመት ሕፃን ነበር። ወንጌላዊ እንዳለ የእግዚአብሔር መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ተገልጦ "ተነሥተህ ሕፃኑና እናቱ ን ይዘህ ወደ ግብጽ ምድር ሽሽ ተመለስ ብዬ እስምነግርህም በዚያው ኑር"።
❤ ጌታችንም ወደ ግብጽ መምጣት ስለ ሁለት ሥራዎች ነው። አንዱ ኄሮድስ ቢያገኘው ሊገድለው እንደአይችል። ስለዚህ ሌሎች ትስብእቱ ምትሐት ነው ብለው አንዳያስቡ። ሁለተኛው የግብጽ ሰዎች በመካከላቸው በመመላለሱ ጸጋውን እንዲያገኙ ጣዖታትንም ቀጥቅጦ ለማጥፋት "እንሆ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና ተቀምጦ ወደ ግብጽ ይወርዳል ጣዖታትም በፊቱ ይወድቃሉ" ያለው የነቢይ ኢሳይያስ ትንቢት ይፈጸም ዘንድ።
❤ የክብር ባለቤት ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ ሸሸ በመጀመሪያም የደረሰበት አገር ስሙ በስጣ ይባላል አልተቀበሏቸውም በዚያም የውኃ ጒድጓድ ቆፈሩ ያቺም ውኃ ለሩቆች ፈዋሽ ስትሆን ለዚያች አገር ሰዎች ግን መራራ ሆነች። ከዚያም በጉምኑዲ መንገድ ተጒዘው ወንዝ ተሻግረው ወደ ምዕራብ ደረሱ። የክብር ባለቤት ጌታችንም ተረከዙን በአለት ላይ አደረገ በተረከዙም አምሳል በአለቱ ላይ ተቀረጸች እስከ ዛሬ ያም ቦታ የጌታችን የተረገዝ ቅርጽ ተባለ። ጌታችንም እመቤታችን ድንግል ማርያምን "እናቴ ሆይ በዚህ ቦታ ቤተ ክርስቲያን በስምሽ ይሠራ ዘንድ እንዳለው ዕወቂ። በውስጡም ድንቅ ተአምራትን አደርጋለሁ ስሙም ደብረ ምጥማቅ ይባላል" አላት።
❤ ከዚያም ወደ ፀሐይ መግቢያ ወዳለ ባሕር ሔዱ የአስቄጥስንም በረሀ ዱር ከሩቅ አዩ። ጌታም በላዩ ባረከ እናቱንም "እናቴ ማርያም ሆይ በዚህ ዱር ውስጥ ብዙዎች ሰዎች መነኰሳትን ሁነው በገድልም ተጸምደው በመላእክት አምሳል ያገለግሉኛል"።
❤ ከዚያም በፀሐይ መውጫ በኵል ወደአለ ተራራ ሒዱ ዮሴፍም የሚመረኰዘው በትር በእጁ ነበር ጌታችንም "ይህ ቦታ የሚቃጥል በረሀ ነውና እንቀመጥ" አለ። ጌታችንም የዮሴፍን በትር አንሥቶ ሰበራት ጥቃቅን ስብርባሪዎች አድርጎ በዚያ ቦታ ተከላቸው። በከበሩ እጆቹ ጒድጓድ ማሰ መዓዛው የሚጣፍጥ ውኃ ፈልቆ ፈሰሰ ከእዚያ ውኃም በመሐል እጁ እየዘገነ የተከላቸውን ስብርባሪዎች አጠጣቸው። ወዲያውኑ በቀሉ አድገውም ታላላቅ ዛፎች ሆኑ ከእርሳቸውም ጣፍጭ ሽታ ሸተተ። እርሱም ከሽቱዎች ሁሉ እጅግ የሚጣፍጥ ነው በለሳንም ብሎ ጠራቸው። እናቱን ድንግል እመቤታችንንም "እናቴ ሆይ ይህ የተከልኩት በለሳን እስከ ዓለም ፍጻሜ ከዚህ ይኖራል የክርስትና ጥምቀትንም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ለሚጠመቁ ከእርሱ ቅባት ይገኛል" አላት የዚያም ቦታ ስም መጠሪያ ነው።
❤ ከዚያም ብንህሳ ወደሚባል አገር ሔዱ ትርጓሜው ቤተ ኢየሱስ የሆነ በይሱስ ወደሚባልም ቦታ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሽታውን ደዌውን ሁሉ የሚፈውስ የጒድጓድ ውሃ አደረገ። ሁለተኛም በአንዲት የጒድጓድ ውኃ ምልክትን በየዓመቱ አደረገ ይኸውም ከቀኑ እኵሌታ በማዕጠንትና በጸሎት ጊዜ ለእግዚአብሔር በዚያች ውኃ ጒድጓድ ዕጣንን ሲያሳርጉ የከበረ የወንጌል ንባብም ሲፈጸም በዚያች ጒድጓድ ውስጥ ያለ ውኃ ወደ ላይ ወጥቶ እስከ ጒድጓዱ አፍ ይደርሳል። ከእርሱም ይባረካሉ ከዚያም በኋላ እንደ ቀድሞው ወደ ቦታው ይመለሳል። ውኃው ከነበረበት እስከ ደረሰበት ይሰፍሩታል። ሃያ ክንድ የሆነ እንደሆነ የጥጋብ ዘመን ይሆናል ዐሥራ ሰባት ክንድ ከሆነ ግን በግብጽ አገር ታላቅ ረኃብ ይሆናል።
❤ ከዚያም ወደ እስሙናይን አገር ሔዱ በዚያ ያሉ ጣዖታትም ወድቀው ተሰባበሩ። እነርሱም ስሙ አፍሎን ከሚባል ሰው ዘንድ ተቀመጡ። በዚያም የእሸ እንጨት ዛፎች አሉ ለጌታችንም ሰገዱ እስከ ዛሬም እንደ ሰገዱ ናቸው። ከዚያም ወደ ደብረ ቊስቋም ሒደው በውስጧ ስድስት ወር ተቀመጡ በዚያም በሽታን ሁሉ የሚያድን የጉድጓድ ውኃ አደረገ።
❤ ጌታችንም የፈቀውን በግብጽ የሚኖርበት ወራት በፈጸመ ጊዜ ይኸውም ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ነው። ኄሮድስም ከሞተ በኋላ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ "የሕፃኑን ነፍስ የሚሹት ሙተዋልና ተነሣ ሕፃኑን እናቱንም ይዘህ ወደ እስራኤል አገር ተመለስ" አለው። ያንጊዜም ተመልሰው ወደ ምስር ደረሱ ወደ መዓልቃም በዚያ በዋሻ ውስጥ አደሩ እርሷም እስከ ዛሬ የቅዱስ ሰርጊስ ቤተ ክርስቲያን ናት። ከዚያም ወጥተው ወደ መጣርያ ደርሰው በውስጧ ታጠቡ። ይቺም የውኃ ምንጭ አስቀድመን እንደተናገርን ጌታችን ያፈለቃት ከዚያች ሰዓት ጀምሮ የተባረከችና የከበረች ሆነች። ከዚያም ጌታችን የተከለው የክርስትና ጥምቀት የሚፈጸምበት በለሳን ቅባት የሚመጣው ነው። በእርሱም ደግሞ አብያተ ክርስቲያናት ንዋየ ቅዱሳትና ታቦተ ሕጉም የሚከበርበት ድኅነትም የሚደረግበት ለክርስቲያኖች ሁሉ መመኪያቸው ነው።
❤ በጌታችን መመለስም "ልጄን ከግብጽ ጠራሁት" ያለው የኦዝያን ትንቢት ተፈጸመ። ስለዚህም ተአምራትን በግብጽ ድንቅ ሥራንም በጣኔዎስ በረሀ ያደረገ በማለት እየዘመርን በዚች ዕለት መንፈሳዊ በዓልን ልናደርግ ይገባናል። ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ስለ እኛ ለተሰደደ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በእኛ ላይም ይቅርታውና ምሕረቱ ይሁን። አምላክን የወለደች የተባረከች የድንግል እመቤታችን ማርያም በረከቷ የቅዱስ ዮሴፍና የቅድስት ሰሎሜም በረከታቸው ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_ዕንባቆም፦ ይህም ቅዱስ በአንዲት ዕለት እህሉን ለሚያጭዱለት ምሳቸውን አዘጋጅቶ ተሸክሞ ሲሔድ መልአክ ተገልጾለት "ይህን መብል በባቢሎን አገር በአንበሶች ጒድጓድ ውስጥ ላይ ለነቢዩ ቅዱስ ዳንኤል ውሰድ" አለው። ዕንባቆምም "ጌታዬ ሆይ ባቢሎንን አላየኋት ጒድጓዱንም አላውቀው" አለው። የእግዚአብሔር መልአክም በራሱ ጠጉር ያዘው ምግቡን በእጁ እንደያዘ ወሰደውና ጒድጓዱ እንደተዘጋ አስገባው ምግቡንም ሰጥቶ መገበው ወዲያውኑ ዕንባቆምን ወደ ይሁዳ አገር መለሰው።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለሆኑ #ለሐዋርያው_ቅዱስ_ዮልዮስ ለዕረፍት በዓል፣ #ለሐዋርያው_ቅዱስ_አፍሮዲጡ ለመታሰቢያ በዓሉና #በደብረ_ምጥማቅ_ለእመቤታችን_መገለጥ_ለሦስተኛ ቀን መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤነሠ አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ ሰማዕታት ከሆኑ #ከአንስያ_ከዮልያና_ከቀሲስ_ታኦድራጦስ፣ #ከጳጳስ_ታድሮስ_ከዮልያኖስና_ከእናቱ_ከእስክንድርያ፣ #ከኤስድሮስ፣ #ከሚስቱና_ከሁለት ወር ልጅዋ እኔ ከእናቴ ጋራ ክርስቲያን ነኝ ብሎ ከተናገረና ዲዮቅልጥያኖስ ከገደላቸው ለእነርሱም ማኅበር ከመታሰቢያቸው ከሆነ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ-ዮልዮስ፦ የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ከይሁዳ ነገድ ከእስራኤል ልጆች ከቤተ ገብርኤል ነው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መረጠው። ከሰባ ሁለቱ አርድእትም የተቆጠረ ሆነ የመንፈስ ቅዱስንም ሀብት ከሐዋርያት ጋራ ተቀበለ ከእርሳቸውም ጋራ ታላቅ መከራ ደርሶበታል።
❤ ከዚህ በኋላ ሐዋርያት በአንብሮተ እድ ኤጲስቆጶስነት ሹመው ከቅዱስ እንድራኒቆስ ጋራ በአገሮች ውስጥ እንዲሰብክ ላኩት። ቅዱስ እንድራኒቆስም በአለፈው ዕለት በዐረፈ ጊዜ ይህ ቅዱስ ዮልዮስ ገንዞ ቀበረው። ከዚህ በኋላ ከርሱ እንዳይለይ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ በማግሥቱ ዛሬ ግንቦት 23 ቀን ዐረፈ።
❤ እንሆ የከበረ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም እሊህን ሐዋርያ በሮሜ ክታቡ ቅዱስ እንድራኒቆስንና ቅዱስ ዮልዮስን ሰላም በሏቸው ሲል አስታውሷቸዋል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባቶቻችን ሐዋርያት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 23 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለዮልዮስ እምቤተ ገብርኤል ልደቱ። ዘተወክፈ ጸጋ ለመንፈስ ቅዱስ ጊዜ ርደቱ። ለእንድራኒቆስ ረድእ ሳኒታ ዕረፍቱ። እግዚአብሔር አግዐዞ እምቅኔ ዓለም ዝንቱ። በከመ ሰአለ ኢይፍልጦ ሎቱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ(አርኬ) #የግንቦት_23።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን። በዘአዝፋረ ወርቅ ዑፅፍት ወኊብርት"። መዝ 44፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16፥19።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወትቀውም ንግሥት በየማንከ። በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኊብርት። ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአጽምዒ ዕዝነኪ"። መዝ44፥9-10። የሚነበበው መልዕክታት ሮሜ 16፥7-10፣ ይሁ 1፥20-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 21፥15-21። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ10፥17-25። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ዮልዮስ፣ የብርሃነ ዕርገቱና የእመቤታች የደብረ ምጥማቅ በዓል ሰሞን። ለሁላችንም ይሁንልን፡፡
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፳፪ (22) ቀን።
❤ እንኳን ##ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለአንዱ ለከበረና ለተመሰገነ #ለሐዋርያው_ቅዱስ_እንድራኒቆስ ለዕረፍቱ በዓል፣ #በደብረ_ምጥማቅ_ለእመቤታችን መገለጥ #ለሁለተኛ_ቀን መታሰቢያ ቀን እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከምሥራቃዊ_ከቅዱስ_ያዕቆብ ከመታሰቢያው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_እንድራኒቆስ፦ ይህንንም ሐዋርያ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መረጠው። እርሱም የእግዚአብሔር መንግሥት እንዲሰብኩ ጌታ ከመከራው በፊት ከላካቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቆጠረ ነው።
❤ በጽርሐ ጽዮንም መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ መንፈስ ቅዱስን ስጦታ ተቀብሎ በብዙ አገሮች ውስጥ ሰበከ። በኒውብያ አገር ላይም ሐዋርያት በአንብሮተ እድ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት በውስጧም ሰበከ በጨለማ በድንቁርና የሚኖሩ ብዙዎች አረማውያንንም የክብር ባለቤት ወደሆነ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት አስገባቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ሐዋርያ ቅዱስ ዮልዮስን ወሰደው በአንድነትም በብዙ አገሮች ዙረው አስተማሩ። ብዙ ሰዎችንም አጠመቁ ተአምራትንም በማድረግ ከሰዎች ላይ አጋንንትን አባረሩ። ብዙዎች በሽተኞችንም ፈወሱአቸው የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሰው የክብር ባለቤት የሆነ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አብያተ ክርስቲያናትን አነፁ። አገልገሎታቸውንም በፈጸሙ ጊዜ ጌታችን ከድካም ወደ ዕረፍት ከኀዘንም ወደ ደስታ ሊወስዳቸው ወደደ።
❤ ከዚህም በኋላ ሐዋርያ ቅዱስ እንድራኒቆስ ታመመና በዚች ቀን ግንቦት 22 ቀን ዐረፈ ቅዱስ ዮልዮስም ገንዞ በመቃብር አኖረው። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባቶቻችን ሐዋርያት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 22 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ሰላም_ለእንድራኒቆስ ዕብሎ። ውኂዝ መንፈስ ዘሰትየ ምስለ ሐዋርያት በአመ ድብሎ። ኀበ ሖረ ይስብክ አህጉራተ አድያም ኵሎ። አብያተ ክርስቲያን ሐኒፆ ወአብያተ ጣዖት አንሒሎ። ዕሴተ ተስፋሁ አድምዐ በሰማይ ዘሀሎ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የግንቦት_22።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "በትርከ ወቀስታምከ አማንቱ ገሠፀኒ። ወሠራዕከ ማእደ በቅሜየ። በአንፃሪሆሙ ለእለ ይሣቅዩኒ"። መዝ 22፥4-5 የሚነበበው ወንጌል 27፥27-31።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 16፥6-10፣ 1ኛ ዮሐ 2፥27-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 21-15-21። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ እንድራኒቆስ የዕረፍት በዓልና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን፡፡
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።❤
❤ እንኳን #ለክብር_ባለቤት_ለጌታችን_ለአምላካችን #ለመድኃኒታችን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ_ለብርሃነ_ዕርገቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የጌታችን_የአምላካችን_የመድኃኒታችን_የኢየሱስ+ክርስቶስ_ዕርገት፦ እርሱም በረቀቀ ጥበቡ በመከራው በሞቱና በመነሣቱ ሥራውን ከፈጸመ በኋላ አርባው ቀን ሲፈጸም በነፋሳት ክንፍ ላይ ሁኖ ዐረገ። ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ሁኖ ወጣ ያለው የዳዊት ትንቢት ተፈጸመ።
❤ በዚህም ዕርገቱ የሚያምኑበት በልዕልና ወደሚኖሩበት የሚዐርጉ መሆናቸው ተረዳ ተረጋገጠ ራስ በአለበት ሕዋሳት ሊኖሩ ይገባልና። አዳም አስቀድሞ በምድራዊ ርስቶች በሲኦልም እንደኖረ መኖርንም እንደቀደመ እንዲሁ ዳግማዊ አዳም ጌታ በመንግሥተ ሰማያት ርስት መኖርን ቀደመ።
❤ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዕርገቱን ከትንሣኤው አከታትሎ ወዲያውኑ አላደረገም መናፍቃን ዕርገቱ ምትሐት ናት ብለው እንዳያስቡ። ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ የደቀ መዛሙርቱን ተሽብሮ የነበረ ልቡናቸውን እያጽናና መነሣቱንም እያስረዳቸው ከትንሣኤው በኋላ አርባ ቀን ኖረ።
❤ በጌታችንም ዕርገት የቅዱስ ዳንኤል ትንቢት ተፈጸመ እንዲህ የሚል "ሌሊት በራእይ አየሁ እንሆ ታላቅ እንደ ሰው ልጅ የሆነ መጣ ዘመናትን ወደሚያስረጃቸው ደረሰ ከፊቱም አቀረቡት። የዘላለም አገዛዝ፣ ጌትነት፣ መንግሥት፣ የዘላለም ሥልጣን ተሰጠው ሕዝቡና አሕዛቡ ሁሉ መንደር መንድረው የሚኖሩትና ነገዱም ነገሥታቱም ሁሉ ይገዙለታል አገዛዙም የዘላለም አገዛዝ ነው መንግሥቱም የሚያልፍ የማይጠፋ ነዋሪ ነው"። ለእርሱም ምስጋና ይሁን ከቸር አባቱ ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት8 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘዐርገ ውስተ ሰማይ። ሰማይ ዘመንገለ ጽባሕ። ናሁ ይሁብ ቃሎ ቃለ ኃይል"። መዝ 67፥32-33። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 24፥45-ፍ.ም።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ። ወእግዚእነ በቃለ ቀርን። ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ"። መዝ 46፥5-6። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 1፥1-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥18-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 1፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ማር 16፥14-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ነው። መልካም የብርሃነ ዕርገቱ በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፳፩ (21) ቀን።
❤ እንኳን #አምላክ_ለወለደች_ለእናታች ለእመቤታችን #ለቅድስት_ድንግል_ማርያም #በደብረ_ምጥማቅ በስሟ በተሰራች ቤተ ክርስትያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ #ለአምስት_ተካታታይ_ቀን_ለታየችበት ዓመታዊ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #በዚች_ዕለት_አምላክን_የወለደች_እመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም_በደብረ_ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ስመታየቱ የክርስቲያ ወገኖች ሁሉም በታላቅ በዓልን ያደርጋሉ።
❤ እርሷም በልጅዋ የመለኮት ብርሃን የተጐናጸፈች ናት በዙሪያዋም የመላእክት ሠራዊት የመላእክት አለቆችም በየማዕርጋቸው ክንፋቸውን ዘርግተው ይቆሙ ነበር ይጋርዷታልም። ሱራፌልም ማዕጠንታቸውን ይዘው ለንግሥናዋ ገናናነት ይሰግዳሉ ስግደታቸውም እንዲህ እያሉ ያመሰግኗታል "አብ በሰማይ ሁኖ ተመለከተ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም አንድ ልጁንም ልኮ ከአንቺ ሰው ሆነ"።
❤ ሁለተኛም ሰማዕታትም በየማረጋቸው ረቂቃን በሆኑ ፈረሶቻቸው ተቀምጠው እየመጡ መጀመሪያ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአምባላይ ፈረሱ ወርዶ ይሰግድላታል እንዲሁም ባልጀሮቹ ሰማዕታት መጥተው ይሰግዱላታል። ከእርሱ በኋላ የሚመጣው በዱሪ ፈረስ የሚቀመጠው ይህ ቅዱስ መርቆሬዎስ ነው። ከዚህም በኋላ ሰማዕታት ሁሉ በመከታተል መጥተው ይሰግዱላታል ምስጋና ያቀርብላታል።
❤ ሁለተኛም ደግሞ የጻድቃን አንድነታቸው መጥተው በፊቷ ሰግደው ይመላለሳሉ። ኄሮድስ የገደላቸው ሕፃናትም መጥተው ይሰግዱላታል በፊቷም እየዘለሉ አንዱ በአንዱ ላይ እየዘለለ በመታቃቀፍም ይጫወታሉ የተሰበሰብትም በአዩ ጊዜ ደስታ ይመላቸዋል በሰማይም ያሉ ይመስላቸው ነበር።
❤ እናትና አባቱም የሞቱበት ቢኖር ወይም ከዘመዶቹ ወይም ባልጀራው "ቅድስት ድንግል እመቤቴ ሆይ ዕገሌን አሳዪኝ ብሎ በሚለምናት ጊዜ ቀድሞ በነበረበት መልኩ ያን ጊዜ ታመጣዋለች። ደግሞ መሀረባቸውን ወደላይ ይወረውሩላታል የወደደችውንም በእጅዋ ተቀብላ መልሳ ትጥልላቸዋለች ለበረከትም በየጥቂቱ ይካፈሉታል።
❤ እንዲህም አምስት ቀን ሁሉ ክርስቲያንም እስላሞችም አረማውያንም ያይዋታል። ወደ ቤታቸውም ለመሔድ ሲሹ በፊቷ ሰግደው ይሰናበቷታል እርሷም ትባርካቸውና ይመለሳሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም አምላክ በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 21 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን። በዘአዝፋረ ወርቅ ዑፅፍት ወኊብርት"። መዝ 44፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥39-57።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ሰወረከኒ በዕለተ ቀትል መልዕልተ ርእስየ። ኢትመጥወኒ እግዚኦ እምፍትወትየ ለኃጥአን። ተማከሩ ላዕሌየ ኢትኅድገኒ ከመ ኢይዘኀሩ"። መዝ 139፥7-8 ወይም መዝ 140፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 7፥9-ፍ.ም፣ ራእ.ዮሐ 12፥1-5 እና የሐዋ ሥራ 7፥44-51። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 18፥6-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች የማርያም ቅዳሴ ነው፡፡ መልካም የደብረ ምጥማቅ በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለአሮን ዕጓላተ ርግብ ዘአሥረረ። ድኅረ ተበስሉ በእሳት ከመ ይኩኑ ድራረ። ኢያንጥሙ ፍኖቱ ወኢያድክሞሙ ወትረ። ማየ ታሕቲት ኀበ ሐነፀ ማኅደረ። በማዕተበ እዱ ስሒቦ አዕረገ ደብረ። ትርጉም፦ እራትን እንዲኾኑ በእሳት ከተበሰሉ በኋላ የርግብ ልጆችን እንዲበርሩ ላደረገ ለአሮን ሰላምታ ይገባል፤ ጎዳናው አስቸግሮ ዘወትር እንዳያዳክማቸው በታች ያለ ውሃን ወዳነጸው በኣቱ በእጁ ማማተብ ስቦ ወደ ተራራ አወጣ። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የግንቦት_21::
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፳፩ (21) ቀን።
❤ እንኳን ለከበሩ #በአንድ_ገዳም_ስልሳ_ሰባት_ዓመት ለተጋደሉ አባት ገሃነመ እሳት በማሰብ በዝሙትም ላለመውደቅ ብለው ሰውነታቸውን የሚነድ እሳት ውስጥ በመጨመር ዘማዊቷን ሴት ለንስሓ ላበቋት #ለአባ_መርትያኖስና #አንበሶች_ውሃ_ይቀዱላቸው ለነበረ፤ ሊፈታተናቸው የመጣውንሰይጣንበዓታቸው ውስጥ አስገብተው በላዩ ዋሻውን ደፍነው ታላቅ የቋጥኝ ደንጊያም ለዘጉበት #ለአባ_አሮን_ሶርያዊ ለዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚህ ከሚታሰቡት፦ #ከነቢዩ_አሞጽ_ከመርዶላ ከመታሰቢያ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_መርትያኖስ፦ ይህም አባት በልጅነቱ ከአንድ ቅዱስ የሆነ አረጋዊ አባት ዘንድ መንኵሶ ታላቅ ገድልን ተጋደለ። ከዚህም በኋላ ሐመረ ኖኅ ወደምትባል በቂሣርያ ወደአለች ገዳም ሔደ በዚያም እጅግ በጣም የበዛ ገድልን ተጋደለ። በጸሎት በጾም በስግደትም በሌሊትና በመዓልት በመትጋት እየተጋደለ ስልሳ ሰባት ዓመት በኖረ ጊዜ የገድሉና ትሩፋቱ ወሬ በቦታው ሁሉ ተሰማ።
❤ እንሆ አንዲት በክፉ ሥራዋና በዝሙቷ የታወቀች ኃጢአተኛ አመንዝራ ሴት ሰማች። ጽድቁንና ቅድስናውን በመናገር የሚያመሰግኑትን እንዲህ አለቻቸው "እናንተ ታመሰግኑታላችሁ እርሱ የሚኖረው በዱር ነው የሴት ገጽ ከቶ አያይም እኔን ቢያይ ድንግልናውን አጥፍቼ ቅድስናውን በአረከስኩት ትኅርምቱንም ባፈረስኩት ነበር"። እነርሱ ግን ጥንክርናውን ስለ ሚያውቁ ተከራከሩዋት። ስለዚህም በመካከላቸው ክርክር ሆነ "ሒጄ ከእኔ ጋራ በኃጢአት ብጥለው ምን ትሰጡኛላችሁ" አለቻቸውና ገንዘብ ሊሰጡአት ተስማሙ።
❤ ያን ጊዜም ተነሥታ ጌጦቿን ልብሶቿንና ሽቱዎቿን ያዘች መልኳም እጅግ ውብ ነበረች ፊቷንም ተከናንባ ጨርቅ ለብሳ ወደ በዓቱ ሔደች። ልብሷንና ጌጦቿንም ለብቻቸው በከረጢት አሥራ ያዘች። ከበዓቱም ቅርብ በሆነ ቦታ ተሠውራ እስከ ሚመሽ ቆይታ የበዓቱን ደጃፍ አንኳኳች። "አራዊት እንዲበሉኝ በውጭ አትተወኝ እኔ መጻተኛ ነኝና መንገድንም ተሳስቼ ወደዚህ ደረስኩ" አለችው። እርሱም በልቡ አሰበ "በውጭ ብተዋት አራዊት ይበሏታል ባስገባትም ስለርስዋ ጦር በኔ ላይ ይነሣብኛል" አለ።
❤ ከዚህም በኋላ ከፈተላት በዚያች በዓት ውስጥ ትቷት ወደ ሌላ ቦታ ፈቀቅ አለ። እርሷ ግን ልብሶቿን ለብሳ ጌጦቿንም ተሸልማ ሽቱዎቿን ተቀብታ ወደርሱ ገባች ከርሷ ጋራም እንዲተኛ ፈልጋ "ከዚህ ማንም የሚያየን የለም" አለችው። ቅዱሱም የሰይጣን ማጥመጃው እንደሆነች አውቆ "ጥቂት ታገሺኝ መንገድን እስታይ እግዚአብሔርን የማንፈራው ከሆነ እንደእኛ ያሉ ሰዎችን ላንፈራቸው ይገባናል" አላት። ይህንንም ብሎ ከእርሷ ዘንድ ወጣ ታላቅ እሳትም አንድዶ እግሩን ከውስጡ ጨምረ ነፍሱንም "የሲዖልን እሳት የምትችዪ ከሆንሽ ኃጢአትን ሥሪያ" አላት። በዘገየ ጊዜ ወደርሱ ሔደች በእሳት ውስጥም እግሩን ሲያቃጥል አይታው እጅግ ደነገጠች። ከእሳትም ውስጥ ጐትታ አወጣችው ልቧም ወደ ንስሓ ተመለሰ። ልብሷንና ጌጦቿን ከላይዋ አውጥታ ጣለች ከእግሩ በታች ሰግደች ስለነፍሷ ድኅነትም እንዲረዳት ለመነችው። እርሱም ይህ ዓለም ፍላጎቱ ሁሉ ኀላፊ እንደ ሆነ ያስተምራትና ይመክራት ልብ ያስደርጋትም ጀመር እርሷም በጨከነ ልብ ንስሓ ገባች።
❤ ከዚህም በኋላ "በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም" ብሎ ወደ ደናግል ገዳም ወሰዳት ትጠብቃትም ዘንድ እመ ምኔቷን አደራ አላት። በቀረው ዕድሜዋም በገድል ተጠምዳ እግዚአብሔርን አገለገለችው ወደ በጎ ሽምግልናም ደረሰች የመፈወስ ሀብትም አድሮባት ብዙዎች በሽተኞችን አዳነች።
❤ የከበረ አባ መርትያኖስ ግን ሌላ ሴት እንዳያመጣበት ፈርቶ በባሕር መካከል ወዳለች ደሴት ገብቶ በዚያ የሚኖር ሆነ። አንድ ባለ ታንኳም የእጅ ሥራውን እየሸጠ ምግብ ያመጣለት ነበር። ከብዙ ዘመናትም በኋላ መርከብ ተሰብራ ሰጠመች አንዲት ሴትም በመርከብ ስባሪ ተጣብቃ አባ መርትያኖስ ወደ አለበት ደሴት የባሕሩ ማዕበል አደረሳት በአያትም ጊዜ ደነገጠ አደነቀም። ከእርሷ ጋራ በአንድነት ስለ መኖሩም አዘነ የእግዚአብሔርንም ቃል አስተምሮ የምንኵስና ልብስ አለበሳት ምግቧንም አዘጋጀላትና "ለእኛ በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም" አላት። ያንንም ደሴት ትቶላት ወደ ባሕሩ ተወርውሮ ገባ አንበሪም ተሸክሞ ወደ የብስ አወጣው። መቶ ስምንት አገሮችንም እስቲአዳርስ በአገሮች በአሉ ገዳማት ሁሉ ከዚያች ቀን ጀምሮ የሚዞር ሆነ በአንድ ቦታ እንዳይቀመጥ አስቦ ነው።
❤ ከዚህ ኋላም የዕረፍቱ ጊዜ እንደ ቀረበ አውቆ በበዓት ውስጥ ራሱን እሥረኛ አደረገ። ኤጲስቆሱንም ጠርቶ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ገድሉን ሁሉ ነገረው ኤጲስቆሱም ከጸጋው ገናናነት የተነሣ አደነቀ። ከዚህም አስቀድሞ የእግዚአብሔር መልአክ ለኤጲስቆጶሱ ስለ አባ መርትያኖስ ሥጋ እንዲአስብ ነግሮት ነበር። ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ግንቦት21 ቀን ሰጠ ኤጲስቆጶሱም በታላቅ ክብር ገንዞ ቀበረው።
❤ ያቺ ሴት ግን እስከ ዕረፍቷ ቀን ባለ መርከብ የሚጐበኛት ሆነ በዐረፈችም ጊዜ ሥጋዋ እንደ በረዶ ነጥቶ አገኛት ሥጋዋንም ወደ አገሩ ተሸክሞ ወስዶ ቀበራት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን በአባ መርትያኖስ እና ለቅድስና ባበቃቸው ቅዱሳን ሴቶች ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለአባ_አሮን_ሶርያዊ ዘአሰረ ሰይጣን ወአጾሮ እብነ፤ በንጹሕ ዘተክህነ"። ትርጉም፦ በንጹሕ ያገለገለ ሰይጣንን አስሮ ደንጊያን ያሸከመ ለኾነ #ለሶርያዊው_ለአባ_አሮን_ሰላምታ_ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በተአምኆ_ቅዱሳን ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_አሮን_ሶርያዊ፦ ለዚህ ቅዱስም የመፈወስና ድንቆች ተአምራትን ማድረግ ሀብት ተሰጥቶታል። ይኸውም እግዶች መነኰሳት ወደ ርሱ በመጡ ጊዜ የርግብ ግልገሎችን አብስሎ አቀረበላቸው። ሥጋ አንበላም ባሉት ጊዜ በላያቸው አማትቦ ርግቦቹን አድኖ እንዲበሩ አደረጋቸው። ደግሞ በተራራ ላይ ገዳም ሠራ ውኃው ከተራራው በታች የራቀ ነበረ በጸለየና በእጁ ባማተበ ጊዜ ስቦ ከተራራው ላይ አወጣው።
❤ በአንዲት ቀንም ሰይጣን በክፋቱ ሊአስጠፋው ወደርሱ መጣ እርሱ ግን በላዩ በአደረ መንፈስ ቅዱስ ተንኰሉን አውቆ "ና ወደ በዓት ግባ" አለው። በገባ ጊዜም በላዩ ዋሻውን ደፈነው ታላቅ የቋጥኝ ደንጊያም ጫነበት ሰይጣንም አፈረ። ደግሞም ሁለተኛ የአካ አገረ ገዥ በሞተ ጊዜ በጸሎቱ አስነሣው። ደግሞ ውኃ የሚቀዳባቸውን አራት እንስራዎችን በአንበሳ እየጫነ በመውሰድ ዐሥር ዓመት ያህል ኖረ። ከዚህም በኋላም ግንቦት21 ቀን ወደ ዘላለም ሕይወት ሔደ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበረች በአባ አሮን ሶርያዊ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት21 ስንክሳር።
