ኅዳር 11
#የክርስቶስ_አያት
#ቅድስት_ሐና
በዚህችም ቀን ፀሐይን እና ጨረቃን ለሚገዛ፣ ሰውን በአርያውና በመልኩ ለፈጠረ ፈጣሪያችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ #አያት የሆነች፤ ለእመቤታችን ለቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያምም #እናቷ የሆነች የተመሰገነች እና የከበረች #ቅድስት_ሐና ዕረፍቷ ነው፡፡
#ቅድስት_ሐና በኢየሩሳሌም ከሌዊ ነገድ
ከካህኑ አሮን ትውልድ የሌዊ የሚልኪ ልጅ ለሆነው ማጣት ለተባለ ሰው ልጁ ናት፡፡
#ማጣትም 3 ልጆች አሉት፤ እነርሱም፦
1) የመጀመሪያይቱ ስሟ
ማርያም ነው፤ አዋላጅ የነበረች ስትሆን ቅድስት ሰሎሜን ወልዳለች፤ ሰሎሜም እመቤታችን መድኃኒታችንን ከወለደችው ጀምሮ በስደቷም ወራት ከአረጋዊ ዮሴፍ ጋር እመቤታችንን ያገለገለቻት ናት፡፡
2) ሁለተኛይቱ ስሟ
ሶፍያ ነዉ ፤ ይህቺ ቅድስት ለመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እናት የሆነችውን
ቅድስት ኤልሳቤጥን ወለደች፡፡
3) ሦስተኛይቱም ስሟ
ሐና ነው፤ ይህች
ቅድስት ሐናም የአምላክን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ወለደቻት፡፡
ቅድስት ሰሎሜ፣ ቅድስት ኤልሳቤጥ እና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የእኀትማማች ልጆች ናቸው፡፡
የሐና ወላጆች ልጃቸውን በሥርዓት አሳደጓት፡ለአካለ መጠን ስትደርስም ከይሁዳ ነገድ ለሆነ ጻድቅ ስሙም
ኢያቄም የተባለውን ጻድቅ ሰው አጋቧት፡፡ ሐና ግን ልጅ መውለድ አልቻለችም ነበር፡፡
ከዕለታት አንድ ቀንም ቅድስት ሐና ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ሲጫወቱ ተመልክታ «ፈጣሪዬ ሆይ! የእንስሳትን ማኅፀን የምትከፍት ዕፅዋትንም ከባሕርያቸው እንዲያፈሩ የምታደርግ እውነትም ሐናን ድንጋይ አድርገህ ፈጥረሃታልን?» ስትል አለቀሰች። ቅዱስ ኢያቄምም ወደ ተራራ ወጥቶ ለዐርባ ቀናት አለቀሰ። ይህ ሲሆን ሁለቱም አርጅተው ነበር። ፈጣሪ ልጅ ከሰጣቸው ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ እንዲሆን ለመስጠት ስእለት ተሳሉ፡፡
በሐምሌ ፴ ቀን ኢያቄም ለሐና ራእይ አየ፤ ነጭ ርግብ ፯ቱን ሰማያት ሰንጥቃ ወርዳ በራሷ ስታርፍ በቀኝ ጆሮዋ ገብታ በማኅፀኗ ስታድር አየ፤ ሐናም ለኢያቄም <<ፀምር ሲያስታጥቁህ መቋሚያህ አብባ አፍርታ ፍጥረት ሁሉ ሲመገባት አየሁ>> ብላ ነገረችው፡፡ ከዚህም በኋላ በነሐሴ ፯ በዕለተ እሑድ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ፀነሰቻት፤ ይህም ለእነርሱም ለወገኖቻቸውም ታላቅ ተድላ ሆነ።
ብፅዕት ሐና ግን ፈጣሪዋን ታከብረው ዘንድ በጐነትንና ንጽሕናን አበዛች። ፀንሳ ሳለም ዕውራንን አበራች፤ ድውያንን ፈወሰች። የጦሊቅ ልጅ በሞተ ጊዜም እያለቀሰች ስትዞረው ጥላዋ ቢያርፍበት አፈፍ ብሎ ተነሥቶ፦
«ሰላም ለኪ እሙ ለፀሐየ ጽድቅ» ብሎ ድንግል ማርያምን «ወሰላም ለኪ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ» ብሎ ቅድስት ሐናን አመስግኗል። ትርጉሙም ድንግልን «የፀሐየ ጽድቅ እናቱ» ሐናን «ሰማይና ምድርን ለፈጠረ አያቱ» ማለት ነው። ይህንን ያዩ አይሁድ ቅድስት ሐናን ሊገድሉ ብዙ ጊዜ ሞክረዋል። ነገር ግን መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል አልፈቀደላቸውም።
ቅድስት ሐናም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በፀነሰች በ፱ኛው ወር ግንቦት ፩ ቀን ነቢያት የተናገሩት ትንቢት ይፈጸም ዘንድ በአምስት ሺህ አራት መቶ ሰማንያ አምስት ዓመተ ዓለም በፈቃደ እግዚአብሔር ወለደቻት።
ይህችም ቅድስት ሰማይና ምድርን ለፈጠረ ማደሪያ ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ለመረጣት ከፍጥረት ሁሉ የተለየችና የከበረች ቅድስት ድንግል ማርያምን ለመውለድ የተገባች ሆናለች፡፡
ቅድስት ሐና ልጇ ሦስት ዓመት እስኪሆናት ከክንዷ አውርዳት አታውቅም ነበር። አንድ ጊዜም መላእክት ወስደውባት ፍጹም አልቅሳለች። ከዚህም ግን መልሰውላታል። ነገር ግን ስእለታቸውን የሚሰጡበት ጊዜ በደረሰ ጊዜ ሳይሰስቱ ለእግዚአብሔር ቤት እንድታገለግል ሰጧት፤ ቅድስት ሐናም ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ ከገባች በኋላ የእናትነት ፍቅሯ እያገበራት ለአምስት ዓመታት እየተመላለሰች ትጐበኛት ትስማትም ነበር።
እመቤታችን ስምንት ዓመት በሞላት ጊዜ ግን የእግዚአብሔር ጥሪ ወደ ቅድስት ሐና ደረሰ። ከክርስቶስ ልደት ስምንት ዓመታት አስቀድማ ብፅዕት እናት ቅድስት ሐና በኅዳር ፲፩ ቀን ዐረፈች።
በጌታ የዘር ሐረግ ውስጥ የተቆጠሩ ሁሉ ክቡራን ናቸው የመጨረሻዎቹ አያቶቹ ደግሞ የመጨረሻው ክብር ይገባቸዋል እነርሱም ሐና እና ኢያቄብ ናቸው፤ አምላካችንን የልጅ ልጃችን ነው ለማለት ተገብተዋልና።
ቅድስት ሐና ከሴቶች ሁሉ የምትከብርና የምትበልጥ መሆኗን አምላክን ለወለደችልን ለቅድስት እናታችን ድንግል ማርያም እናት ሆና አይተናል፤ ከሴቶች ሁሉ የሚበልጥ ትሩፋትና ተጋድሎ ባይኖራት ይህ ጸጋ ባልተገባት ነበር፡፡ አባቶችም ታጋድሎዋ እጅግ ብዙ እንድሆነ ነግረውናል፡፡
ምልጃዋ አይለየን፤
ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!
ሃገራችንን ቅድስት ኢትዮጵያን እና ቅድስት ቤተክርስቲያናችንን ትጠብቅልን
አሜን!
አርኬ
ሰላም ለኪ ለጸሎተ ኵሉ ምዕራጋ፡፡
ከመ አስካለ ወይን ዲበ ሐረጋ፡፡
ሐና ብፅዕት ተፈሥሒ እንበለ ንትጋ፡፡
እስመ ረከብኪ ሞገሰ ወአድማዕኪ ጸጋ፡፡
እምሔውተ አምላክ ትኵኒ በሥጋ፡፡
በቦታው ሄዳቹ በዓሉን ማክበር ለምትፈልጉ
(ፎቶዎቹ፤ በአዲስ አበባ እና በሌሎች የሚገኙ
የቅድስት ሐና አብያተ ክርስቲያናት እነሆ ...)
👉 ኮተቤ መካነ ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና ቤ/ክ
👉 ፉሪ መንበረ ንግስት ቅድስት ሐና ቤ/ክ
👉 ደብረ ንግስት መንዝ ቅድስት ሐና
👉 በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት በደብረ መንክራት ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በድርብነት ትገኛለች
ሌሎች በዓሉ የሚከብሩባቸውን ቦታዎች ኮሜንት ላይ ያጋሩን
/በቀጨኔ ደ.ሰላም መድኀኔዓለምና ደ.ት.ቅ.ገብርኤል ቤ.ክ
ፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚዲያ እና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ክፍል የተዘጋጀ/
#share
፨
Facebook
https://www.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
፨
YouTube https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w
፨
Telegram
https://t.me/Finotehiwott
፨
Tiktok
http://tiktok.com/@finotehiwot
፨
Website www.finotehiwotsundayschool.com
#Share #like