fa
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

رفتن به کانال در Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

نمایش بیشتر
2 639
مشترکین
-224 ساعت
+37 روز
+5630 روز
آرشیو پست ها
🔴ስንክሳር #መጋቢት_9 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ዘጠኝ በዚህች ቀን ተጋዳይ የሆነ ጽኑዕ አባት #ቅዱስ_ኩትን አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_እንድርያኖስና_ሚስቱ_አውሳብዮስና_አርማ በሰማዕትነት አረፉ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኩትን_ሐዋርያ መጋቢት ዘጠኝ በዚህች ቀን ተጋዳይ የሆነ ጽኑዕ አባት ኩትን አረፈ። እርሱም በሶርያ አገር ስሟ በንጣንዮስ ከምትባል ቦታ የሚኖር ነው። አባቶቹም ከዋክብትን ያመልኩ ነበር የአባቱ ስም ንስጣር የእናቱም ስም ቴዎድራ ይባላል። በአደገ ጊዜም ወላጆች ሊአጋቡት ፈለጉ እርሱ ግን አልወደደም ግድ ብለው ያለውዴታው ሚስትን አጋቡት ሊገናኛትም አልፈለገም ስለ ሥጋ ድካም ወይም ስለ ጽድቅ ሳይሆን የሥጋ ፍትወትን ስለሚጠላት ነው እንጂ። ደናግልም እንደሆኑ ሁለቱ ሁሉ ከሚስቱ ጋራ በአንድነት ኖረ። አምላክ ሆይ ወደ ዕውቀትህ ምራኝ በማለት ጸሎትና ምልጃን ያዘወትር ነበር። ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ ለቆርኔሌዎስ እንደተገለጠ ተገልጦ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን አስተማረው ከሐዋርያትም ወደ አንዱ ሔዶ የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቅ አዘዘው። የሐዋርያት የስብከታቸው ወራት ነበረና ሒዶ ተጠመቀ የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት ሁሉ ሕጉን ሥርዓቱንም ሁሉ ተማረ መለኮታዊ ምሥጢርንም ተቀበለ። በየቀኑ ሁሉ የሐዋርያ ጳውሎስን ትምህርት ይሰማ ነበር የጽድቅን ሥራ መሥራትና ንጽሕና ለበጎ ሥራ መጠመድ ትጋት ቅንነት የዋህነት ጾም ጸሎት ሰጊድ በላዩ ተጨመረ። በእነዚህ ሁሉ የሚተጋ ሆነ እግዚአብሔርም አስደናቂ ተአምራቶችን እንዲአደርግ በርኲሳን አጋንንት ላይ ሥልጣንን ሰጠው። በሚያደርገው ተአምራትም ወላጆቹን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደማመን ስቦ አስገባቸው ደግሞ ሚስቱንና ወላጆቿን አስገባቸው። ከከሀድያን አንዱ ለሰይጣን ሊሠዋ ወደ ጣዖቱ ቤት በገባ ጊዜ ቅዱስ ኩትን አውቆ በሰይጣን ላይ ጮኸ እርሱ ሰይጣን እንጂ አምላክ እንዳልሆነ በሰው ፊት ያምን ዘንድ አዘዘው። ሰይጣንም እንዳዘዘው ራሱን ገለጠ በዚያ የነበሩ ሁሉም የቅዱስ ኩትን አምላክ አንድ እርሱ ብቻ ነው እያሉ ጮኹ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ። ከዚህ በኋላ ከቀላውዴዎስ ቄሣር የተላከ መኰንን የቅዱስ ኩትንን ዜናውን በሰማ ጊዜ ወታደር ልኮ አስቀረበው ስለ ሥራውም ጠየቀው እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ መኰንኑም ጽኑ ግርፋት ገርፈው እንዲአሥሩት አዘዘ ይህንንም አደረጉበት። የአገር ሰዎችም ቅዱስ ኩትንን አሠቃይተው እንዳሠሩት በሰሙ ጊዜ ሁሉም ወደርሱ ተራወጡ መኰንኑንም ሊገሉት ወደዱ መኰንኑም ሸሸ። ቅዱስ ኩትንንም ከማሠሪያው ፈትተው ከደሙም አጥበው ተሸክመው ወደቤቱ ወሰዱት ከዚያም በኋላ ብዙ ዘመናት ኑሮ የወደደውን እግዚአብሔርን አገልግሎ ደስ አሰኝቶ በፍቅር አንድነት አረፈ። ከዕረፍቱም በኋላ ቤቱን ቤተ ክርስቲያን አድርገው ሥጋውን በውስጥዋ አኖሩ ጌታችንም ከሥጋው ብዙዎች ታላላቅ ተአምራቶችን አሳየ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_እንድርያኖስ በዚህች ቀን የከበረ እንድርያኖስና ሚስቱ አውሳብዮስና አርማ ሌሎች አርባ ሰዎችም በሰማዕትነት አረፉ። እሊህንም ምርጦች ለረከሰ ከወርቅና ከብር ለተሠራ ጣዖት ማምለክን እምቢ ስላሉ የክብር ባለቤት ለሆነ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለስሙ ዐላውያን ጽኑ የሆነ ሥቃይን አሰቃዩአቸው። ከዚህም በኋላ ራሶቻቸውን በሰይፍ ቆረጡ የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)https://t.me/finotebirhan12

🔴ስንክሳር #መጋቢት_8 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ስምንት በዚህች ከአስራ ሁለቱ ሀዋርያት የአንዱ #የሀዋርያ_ቅዱስ_ማትያስ የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣የእንዴናው መኰንን #ቅዱስ_አርያኖስ በሰማእትነት አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_አባት_አባ_ዮልዮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ማትያስ_ሐዋርያ መጋቢት ስምንት በዚህች እለት በአስቆሮቱ ይሁዳ ፈንታ የተሾመ ከአስራ ሁለቱ ሀዋርያት የአንዱ ሀዋርያ የማትያስ የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ወንጌልን ይሰብክላቸው ዘንድ በሄደ ጊዜ ወዲያውኑ ይዘው አይኖቹን አውልቀው አሰሩት ምግባቸው የመፃተኛ ሰው በድን ስለሆነ ልማዳቸውም እንዲህ ነው። መፃተኛ ሰው ሲይዙ አይኖቹን አውልቀው በእስር ቤት ያኖሩታል።የያዙበትንም ቀን ይፅፋሉ ሰላሳ ቀንም እስቲፈፀም ሳር ያበሉታል ከዚያ በኃላም አውጥተው አርደው ይበሉታል። ሀዋርያ ማትያስም ታስሮ ሳለ ሰላሳው ቀን ሳይፈፀም በጌታችን ትእዛዝ ሀዋርያው እንድርያስ ወደርሱ ደረሰ የአገሩ ሰዎች የሚሰሩትን ክፉ ስራ አይቶ አደነቀ እጅግም አዘነ እስረኞችንም ሁሉ አውጥቶ የአገር ሰዎች ወደማያገኙአቸው ቦታ አኖራቸው።እነርሱ ግን ሁለቱ ሀዋርያት እንድርያስና ማትያስ ተገለጡላቸው የአገሩም ሰዎች ያዙአቸው በዘንገታቸውም ገመድ አስገብተው እስከሶስት ቀን በአገሩ ጥጋጥግ ጎተቱአቸው ሀዋርያት ስለዚያች አገር ሰዎች ስለድኅነታቸው ወደ እግዚአብሄር ፀለዩ ያንጊዜ ከወህኒ ቤቱ ምሰሶ ስር ውኃን አፈለቁ ውኃውም ከፍ ከፍ ብሎ በሀገር ውስጥ እሰከሚአጥለቀልቅና ወደ ሰዎች አንገት እስከ ደረሰ እየበዛ ሄደ። በተጨነቁና የህይወታቸውን ተስፋ በቆረጡ ጊዜ ወደ ሀዋርያት መጡ በፊታቸውም ኃጢአታቸውን እየተናዘዙ አለቀሱ ሀዋርያትም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ እናንተም ትድናላችሁ አሉአቸው እሊያ ሁሉም በክብር ባለቤት በጌታችን አመኑ። ሀዋርያትም አስተማሩአቸው ገሰፁአቸውም የአንድነትን የሶስትነትን የመድኃኒታችን ሰው የመሆኑን ምስጢር ገለጡላቸው ደግሞም ይህን የአራዊት ጠባይ ጌታችን ከእነርሱ ያርቅ ዘንድ ፀለዩላቸው ከዚህ በኃላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው ያ የአውሬ ጠባይ ከእርሳቸው ርቆ ሰው የሚመገበውን የሚመገቡ የዋሆች ቅኖች ሆኑ። ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾሙላቸው በቀናች ሀይማኖትም እያፀኑአቸውና እያስተማሩአቸው ሰላሳ ቀኖች ያህል ከእሳቸው ጋራ ኖሩ ከዚያም ወጥተው ሄዱ የአገር ሰዎች ግን በሌላ ጊዜ ወደ እነርሱ እንዲመለሱላቸው ሀዋርያትን ለመኑአቸው። ሀዋርያ ማትያስ ግን ወደ ደማስቆ ከተማ ገብቶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከ።የአገርም ሰዎች ይዘው በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው በበታቹ ስድስት ቀን ስድስት ሌሊት እሳት አነደዱ ሊአዩትም ወደርሱ በመጡ ጊዜ ፊቱ እንደ ፀሀይ ሲበራ አገኙት ስጋውንም ሆነ የራስ ጠጉሩን ወይም ልብሶቹን ምንም ምን እሳት አልነካውም እጅግም አደነቁ።አሁንም ዳግመኛ ሀያ አራት ቀን እስኪፈፀም ድረስ ሀዋርያ ቅዱስ ማትያስ በተኛበት በዚያ የብረት አልጋ በታች እሳትን አነደዱ። ከዚህ በኃላም ከእሳቱ ባወጡት ጊዜ ያለ ምንም ጉዳት ጤነኛ ሆኖ አገኙት እጅግም አደነቁ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ።እርሱም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ካህናትንም ሾመላቸው በቀናች ሀይማኖትም እያፀናቸው ከእርሳቸው ጋራ ኖረ። ከዚያም ተነስቶ ስሟ ፊላዎን ወደሚባል ከአይሁድ አገሮች ወደ አንዲቱ ሄደ በዚያም በጎ እረፍትን አረፈ ስጋውንም በመልካም ቦታ አኖሩ ከስጋውም በሽተኞችን በመፈወስ ታላላቅ የሚያስደንቁ ተአምራት ተገለጡ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አርያኖስ_ሰማዕት በዚህች እለት የእንዴናው መኰንን ቅዱስ አርያኖስ በሰማእትነት አረፈ። ይህም እንዲህ ነው የከበሩ ፊልሞንና አብለንዮስ በእርሱ እጅ በሰማእትነት ከሞቱ በኃላ እርሱም በስቃይ ውስጥ ሳለ ከአማንያን አንዱ ከቅዱሳን ከደማቸው ወስደህ አይንህን ብትቀባ በዳንክ ነበር አለው ያን ጊዜም ከደማቸው ወስዶ አይኑን ቀባ ወዲያው ድኖ ፈጥኖ አየ። ከዚያም በኃላ በቅዱሳን ላይ በአደረገው ክፉ ስራ ሁሉ በድንቁርናውም ምህረት የሌለው ስቃይ ስለአሰቃያቸው ታላቅ ፀፀት ተፀፅቶ አዘነ ተነስቶም ጣኦታቱን ሰበረ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምኖ ምእመናንን ማሰቃየቱንም ተወ። ዲዮቅልጥያኖስም ወሬውን በሰማ ጊዜ ጭፍሮቹን ልኮ ወደርሱ አስመጣው በምን ምክንያት አማልክትን ማምለክ እንደ ተው ጠየቀው።እርሱም በቅዱሳን ሰማእታት እጅ እግዚአብሄር የሚሰራቸውን አስደናቂዎች ተአምራት ሊነግረው ጀመረ ህዋሳታቸውን እንዴት እንደሚቆራርጡአቸው በየአይነቱ በሆነ ስቃይም ሲያሰቃዩአቸው ያለምንም ጉዳት ጤነኞች ሆነው ተመልሰው እንደሚነሱ። ዲያቅልጥያኖስም የተአምራትን ነገር ስለ ነገረው ተቆጣ ፅኑ የሆነ ስቃይም እንዲአሰቃዩት አዘዘ። ሁለተኛም ከጉድጓድ እንዲጨምሩትና እስኪሞትም የጉድጓዱን አፍ እንዲዘጉ አዘዘ እንዲሁም አደረጉ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልአኩን ልኮ ከጉድጓዱ አውጥቶ በንጉስ ዲዮቅልጥያኖስ መኝታ ላይ አቆመው።ንጉሱም በነቃ ጊዜ አይቶ ደነገጠ ፈራ ማነህ አንተ አለው። እርሱም እኔ የእንዴናው ገዥ አርያኖስ ነኝ ብሎ መለሰለት ንጉሱም ደንግጦ እየተንቀጠቀጠ በማቅጠቅልለቅ ከባህር እንዲአሰጥሙት አዘዘ በባህሩም ውስጥ ነፍሱን በጌታችን እጅ ሰጠ። እንዲህም ሆነ ቅዱስ አርያኖስ ዘመዶቹንና አገልጋዮቹን ሲሰናበታቸው እንዲህ ብሎ ነገራቸው ለስጋዬ እርሱ እንደሚአስብና ወደአገሬ ወደእንዴናው እንደሚመልሰው በሌሊት ራእይ እግዚአብሄር አስረድቶኛልና እናንተም በእስክንድርያ ወደብ ስጋዬን ጠብቁ አላቸው። በአሰጠሙትም ጊዜ ጌታችን አሳ አንበሪን አዘዘ አንበሪውም ተሸክሞ ወስዶ በእስክንድርያ ወደብ አውጥቶ በየብስ ላይ አኖረው።አሽከሮቹ ከዚያ እየጠበቁት ነበር ወደ አገሩ ወደ እንዴናው አድርሰው ከቅዱሳን ሰማእታት ከፊልሞንና ከአብላንዮስ ከስጋቸው ጋራ በአንድነት አኖሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዮልዮስ_ሊቀ_ዻዻሳት በዚችም ቀን ደግሞ በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አስራ አንደኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት አባ ዮልዮስ አረፈ። ይህም አባት አስቀድሞ በእስክንድርያ ቄስ ሆኖ ነበር እርሱም በአለበት ዘመን በግብፅ አገር እንደርሱ ያለ የሌለ አዋቂ ብልህ የሆነ ምሁር ነበር። የክብር ባለቤት በሆነ በእግዚአብሄርም ፈቃድ በእስክንድርያ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ብዙዎች ድርሳናትንና ተግሳፃትን ደረሰ። የሹመቱም ዘመን ሰላም የሰፈነበት ነበር በቀናች ሀይማኖትም ይፀኑ ዘንድ ህግና ስርአትንም ሁሉ እንዲጠብቁ ህዝቡን ሁልጊዜ ይመክራቸውና ያስተምራቸዋል። በወንጌላዊው ማርቆስ ወንበር አስር አመት ከኖረ በኃላ በሰላም በፍቅር አረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

🔴 ስንክሳር #መጋቢት_7 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሰባት በዚህች ቀን የከበሩ #ቅዱሳን_ፊልሞንና_አብላንዮስ በሰማዕትነት አረፉ፣ #ቅዱስ_ቴዎዶጦስ በሰማዐትነት ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_ፊልሞንና_አብላንዮስ መጋቢት ሰባት በዚህች ቀን የከበሩ ፊልሞንና አብላንዮስ በሰማዕትነት አረፉ። ይህ ፊልሞንም የእንዴናው ገዥ በሆነ በአርያኖስ ፊት በአዝማሪነት ይጫወት ነበር ከአዝማሪው አብላንዮስም ጋራ እርስ በርሳቸው ወዳጆች ሆኑ ለክብር ባለቤት ክርስቶስም ስለ ስሙ ምስክሮች ሊሆኑ ተስማሙ። አዝማሪው ፊልሞንም ልብሱን ወስዶ ለአብላንዮስ ሰጠው እርሱም የአብላንዮስን ልብስ ለብሶ ወደ መኰንኑ ወደ አርያኖስ ገብቶ በፊቱ ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኰንኑም ተመልክቶ አዝማሪው አብላንዮስ እንደሆነ አሰበ በፍላጻም እንዲነድፉት አዘዘ ያንጊዜም አዝማሪው ፊልሞን መሆኑን አውቆ እጅግ ተቆጣ። ደግሞ አብላንዮስን እንዲነድፉት አዘዘ ሁለቱንም ነደፉአቸው አንዲት ፍላጻም ወደ መኰንኑ ተመልሳ ዐይኑን አወጣቻት እጅግም አሠቃየችው። የከበሩ ፊልሞንና አብላንዮስ ግን ገድላቸውን ፈጽመው የሕይወት አክሊልን ተቀበሉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስቴ_ቴዎዶጦስ በዚህችም ዕለት ደግሞ ቅዱስ ቴዎዶጦስ በሰማዕትነት አረፈ። እርሱም ከገላትያ አገር የሆነ በምክርና በተግሣጽ አምልኮተ እግዚአብሔርንም በማጽናት ያደገ ነው። ወደ ከሀዲ መኰንንም ሒደው የክርስቲያን ወገን እንደሆነ ነገር ሠሩበት መኰንኑም አሥረው እንዲአመጡት አዘዘ። ቅዱሱም ይህን በሰማ ጊዜ ሳይዙት ወደ መኰንኑ ሔዶ መኰንኑንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገመ ዘለፋቸውም መኰንኑ እሱን በማስፈራት ሁኖ የሥቃይ መሣሪያዎችን ሁሉ አሳየው ለጣዖት እንዲሠዋ በመሸንገል አስገደደው ቅዱሱም ስለ ድንቁርናው ረገመው ዘለፈውም። ከዚህ በኋላም የውስጥ ዕቃው እስከሚታይ ሰቀለው ጐኖቹን ይሠነጣጥቁ ዘንድ መኰንኑ አዘዘ። ከዚያም ወደ ወህኒ ቤት ይጨምሩት ዘንድ ደግሞ አውጥተው በዕንጨት እንዲሰቅሉት ቊስሎቹንም እንዲአድሱ ጐኖቹንም እንዲሠነጣጥቁ አዘዘ። እርሱ ግን መኰንኑ የሚያመጣውን ሥቃይ እንደ ኢምንት አደረገው በክብር ባለቤት በጌታችን ክርስቶስ በፍቅሩ ፍላጻነት ልቡ ተነድፏልና ዐይኖቹም ወደላይ ይመለከቱ ነበር። መኰንኑም ብርታቱን በአየ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ቅዱስ ቴዎዶጦስም የራሱን መቆረጥ ሰምቶ እጅግ ደስ እያለው ወጣ። ወደ እግዚአብሔርም ሲጸልይና ሲማልድ እንዲህ አለ። የክብር ባለቤት ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ አመሰግንሃለሁ ከተከታተለኝ ክፉ ነገር ሁሉ አድነኸኛልና በጠላትነት የተነሡብኝንም ወደ ገሃነም አውረድካቸው እኔንም ከሞት በር ከፍ ከፍ አድረግኸኝ። ይህንንም ብሎ በሰገደ ጊዜ ወታደሩም የቅዱሱን ዐይን ይሸፍን ዘንድ መሸፈኛ አመጣ። ቅዱሱም ይህ ሞትን ለሚፈሩ ነው እኔ ግን በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሞትን አልፈራም አለ። ወታደሩም ሰይፉን መዝዞ የከበረች ራሱን ቆረጠ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢትና #ከገድላት_አንደበት) https://t.me/finotebirhan12

ወርሃዊ የሰንበት ት/ቤታችን ጸሎት መርሐግብር መጋቢት 11, 2014 ዓ.ም
ወርሃዊ የሰንበት ት/ቤታችን ጸሎት መርሐግብር መጋቢት 11, 2014 ዓ.ም

#መጋቢት_6 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ስድስት በዚች ቀን #ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ ታማኝ የሆነ ኤጲስቆጶስ #የቅዱስ_ቴዎዶስዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #የአቡነ_አርከሌድስ እረፍታቸው ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሰማዕት_ዲዮስቆሮስ መጋቢት ስድስት በዚች ቀን በእስ*ላሞች ዘመነ መንግሥት ዲዮስቆሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ከእስክንድርያ ሰዎች ወገን ነው በማግባባት በመገፋፋት ከክርስቲያን አውጥተው ወደ እስ*ልምና አስገቡት በእምነታቸውም ጥቂት ጊዜ ኖረ። ፍዮም በሚባል አገር ለአንድ ክርስቲያን ሰው የተዳረች አንዲት እኀት ነበረችው ወንድሟ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት እንደ ተወ በሰማች ጊዜ ታላቅ ኀዘንን አዘነች። ከዚህም በኋላ እንዲህ ብላ ወደርሱ መልእክትን ላከች የክብር ባለቤት ክርስቶስን አንተ እንደ ካድከው ከምሰማ በክርስትናህ ሳለህ የሞትህ መርዶ ቢመጣልኝ እወድ ነበር። ከዚያም ከቅዱሳት መጻሕፍት ጠቅሳ ጻፈችለት በደብዳቤዋ ፍጻሜም እንዲህ ብላ ጻፈች። "ከዛሬ ጀምሮ ወደ ክርስትናህ ካልተመለስክ ይህቺ ደብዳቤ በእኔና በአንተ መካከል የፍቅር ፍጻሜ እንደሆነች ዕወቅ ከቶ ፊትህንም እንዳታሳየኝ መልእክትም ቢሆን አትላክልኝ። የእኅቱንም የመልእክት ደብዳቤ በአነበበ ጊዜ መሪር ዕንባን አለቀሰ ተጸጸተ ፊቱን ጸፋ ጽሕሙንም ነጨ ተነሥቶም ወገቡን ታጠቀ ረጅም ጸሎትንም በመጸለይ ማለደ ፊቱንም አዳኝ በሆነ መስቀል ምልክት አማተበ ከቤቱም ወጥቶ በእስክንድርያ ከተማ ውስጥ ተመላለሰ። እስ*ላሞችም በአዩት ጊዜ ይዘው ወደ መኰንኑ አቀረቡት መኰንኑም ከእርሱ ስለሆነው ነገር ጠየቀው እርሱም ክርስቲያን ነኝ ሌላ ምንም ምን አላውቅም ብሎ መለሰ። መኰንኑም ደግሞ የክርስቲያንን ሃይማኖት ትተህ ወደእኛ እምነት ገብተህ አልነበረምን ብሎ መለሰለት። ቅዱስ ዲዮስቆሮስም መልሶ እንዲህ አለ በወልድ የማያምን ሕይወትን አያያትም የእግዚአብሔር የቁጣው መቅሠፍት በላዩ ይወርዳል እንጂ የሚል በከበረ ወንጌል ተጽፏል። ስለዚህ እኔ በክብር ባለቤት በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ እኔም ትውልዴ ከክርስቲያን ነው አሁንም በክርስትናዬ እሞታለሁ። መኰንኑም እጅግ ተቆጥቶ ከዚህ ምክርህ ካልተመለስክ እኔ የጸና ቅጣት እቀጣሃለሁ አለው። ቅጣቱንም ፈርቶ ከመልካም ምክሩ አልተመለሰም። ከዚያም በኋላ ታላቅ ግርፋት ገርፎ አሠረው በእሥር ጥቂት ቀናት ቆየ ከእሥር ቤትም አውጥቶ ከምክሩ ከሐሳቡ ቢመለስ ብዙ ገንዘብ ሊሰጠው ቃል ገባለት። ይህ ካልሆነ ግን በእሳት እንደሚአቃጥለው ነገረው። ቅዱሱም ሕያው በምታደርግ ከክርስቲያን ሃይማኖት በቀር በሌላ አልሞትም ብሎ መለሰለት። መኰንኑም በእሳት እንዲአቃጥሉት አዘዘ ከከተማም ውጪ ታላቅ ጉድጓድ ቆፈሩለት። ዕንጨትም መልተው አነደዱት ነበልባሉም እጅግ ከፍ ከፍ አለ ያን ጊዜም ብዙ ገርፈው ሥጋውን በሰይፍ ሰነጣጠቁ ። ወደ እሳትም ጨመሩት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጥቶ በመንግሥተ ሰማያት የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቴዎዶስዮስ በዚችም ዕለት ታማኝ የሆነ ኤጲስቆጶስ የቅዱስ ቴዎዶስዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። የዚህንም ቅዱስ ዜና ከዲዮቅልጥያኖስ የተሾመ የቆጵሮስ ገዥ ዮልዮስ ሰማ። ወደርሱም አስቀርቦ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክዶ ለረከሱ ጣዖቶች ዕጣን እንዲአጥን መሥዋዕትም እንዲአቀርብ ፈለገ፡፡ ቅዱስ ቴዎዶስዮስም እኔስ በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ ለእርሱም ዕሠዋለሁ በሎ መለሰ። ትእዛዙንም ባልሰማ ጊዜ ጽኑዕ ግርፋትን ከላም ቆዳ በተሠራ ጅራፍ ገረፈው። ከዚያም ሰቅሎ ሥጋውን ሁሉ ሰነጠቀ አውርዶም በእሳት በአጋሉት በብረት አልጋ ላይ አስተኛው ጌታችንም ከዚህ ሥቃይ ጠብቆ አዳነው። ከዚህ በኋላ እጆቹንና እግሮቹን በረጃጅም ችንካሮች ቸንክረው እስከ ወህኒ ቤት ጐትተው በዚያ ጣሉት። እግዚአብሔርም ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስን አጥፍቶ ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ እስከ ነገሠ ድረስ በወህኒ ቤት ኖረ። ቈስጠንጢኖስም የመንግሥት ሥልጣን በያዘ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን የታሠሩትን ሁሉ እንዲፈቷቸው አዘዘ። ከዚያም በኋላ ወደ አገሩ ተመልሶ በጵጵስናው ሹመት ላይ ሁኖ ምእመናንን በበጎ አመራር እየመራ ኖረ። ዕድሜውንም ፈጽሞ በሰላም አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_አርከሌድስ ዳግመኛም በዚህች እለት አቡነ አርከሌድስ እረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አርከሌድስ አገራቸው ግብፅ ሲሆን ከተሰዓቱ ቅዱሳ ቀጥሎ ነው ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት፡፡ የነበሩበትም ጊዜ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በነበሩበት ጊዜ ነበር፡፡ወደ አገራችን ከመጡ በኋላ ወሎ ውስጥ ያለችውን እጅግ ጥንታዊቷን ቸር ተከል ማርያምን ቆረቆሯት፡፡ ጻድቁ የሚታወቁበት ትልቁ ገድላቸውም ሳይንት ውስጥ በቸር ተከል ማርያም ገዳም ውስጥ ለ21 ዓመታት ሳያርፉ ሳይቀመጡ በመቆም ጸሎት ያደረጉ ታላቅ አባት መሆናቸው ናቸው፡፡ አቡነ አርከሌድስ እጃቸውን ሲያጨበጭቡ 500 ርግቦች በአንድ ጊዜ ይሰበሰቡላቸው ነበር፡፡ እነርሱንም ወደፈለጉት ቅዱሳን መልእክት ይልኳቸው ነበር፡፡ በዚህ አስደናቂ ሥራቸውም በቅዱሳን ዘንድ ትልቅ ክብር ነበራቸው፡፡ለቅዱሳን የተለያየ ታሪክ አላቸው፣ ለአንዱ አንበሳ፣ ለአንዱ ጅብና አጋዘን፣ ለአንዱ ንብ፣ ለአንዱ ነብር፣ ለአንዱ አጋንንት ይታዘዙላቸው ነበር፡፡ ጻዲቁ በመጨረሻ ወደ ምረድ ግብፅ ተመልሰው ከሰማዕታት ጋር ተሰይፈው በሰማዕትነት ያረፉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢትና #ከገድላት_አንደበት)

ያን ጊዜ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ በመብረቅ ላይ ተጭኖ በረረ እነዚያ አጋንንት ወደአሉበትም ወረደ። ደመናትም ከበቡአቸው መላእክትም በእሳት ሰይፍ መተሩአቸው በመብረቅም አጨዱ አቸው አመድም ሆነው በነፋስ በተኑአቸው። የእነዚያም አጋንንት ቁጥራቸው ሰባት መቶ ሺህ እልፍ ከአንዱ ሺህ ነበር። ከዚህም በኃላ ጌታ ክርስቶስን የካዱ ወዳሉበት ወደ ምእራብ ሀገር ወሰደው። ነገስታቱና መሳፍንቱ መኳንንቱም በሚወጡበትና በሚገቡበት ጉዳና ላይ አቆመው ጌታችንም በዚች ጉዳና ብዙ መከራ ያገኝሀል ግን በርታ ታገስ ብሎት በዚያ ተወው። በዚያን ጊዜም የአርብ ንጉስ ጣዖታቱን አስይዞ መኳንንቱን ሰራዊቱን አስከትሎ በዚያች ጎዳና መጣ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስን በጎዳና ውስጥ በተገናኙት ጊዜ ጣኦታቱ ወድቀው ተሰባበሩ። ንጉሱም አባታችንን በአየው ጊዜ አንተ ጠጉር ለባሽ ምንድነህ ሰው ነህን አለው።አባታችንም አዎን ክብር ያለው የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያው የሆንኩ ሰው ነኝ ብሎ ለከሀዲው ንጉስ መለሰለት። ንጉሱም ዳግመኛ አባታችንን በዚያ አይሁድ በሰቀሉት ታምናለህን አለው አባታችንም በሰው ፊት አምንበታለሁ።ስለ እኔ በተሰቀለው አላፍርበትም ስለ እኔ ብቻ የተሰቀለ አይደለም ስለ አንተና ከአንተ ጋራ ስለ አሉትም ነው እንጂ ንጉስ ሆይ የዘላለም ህይወትን ታገኛላችሁ እመኑበት አለው። ንጉሱም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ተቆጣ ሰራዊቱንም ጠርቶ በፍጥረት እሳትን አንድዱ ለተሰቀለው ለናዝሬቱ ሰው ባሪያው ነኝ የሚለውን ጠጉር ለባሽ ወስዳችሁ ጨምሩት አላቸው። የእሳቱም ነበልባል በረጅም ዛፍ መጠን ከፍ ከፍ እስከሚል አነደዱ። አባታችን ግን ንጉሱና ሰራዊቱ ሁሉ እያዩት አልፎ በፈቃዱ ወደ እሳቱ ገባ። እሳቱም እንደወንዝ ውኃ ሆነ ሰረዊቱም እጅግ አደነቁ እኩሌቶቹም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ንጉሱም ሲያደንቁ በአየ ጊዜ ፈፅሞ ተቆጣ ከሰባ ሰባት አርበኞቹ ጋራ በቁጣ ተነስቶ ያደነቁትንና ያመኑትን አንገታቸውን ቆረጠ ። በዚያችም ቀን የተቆረጡ አርባ መቶ ሺህ ሆነው ተቆጠሩ።ንጉሱም የአባታችንን አንገት ሊቆርጥ ሰይፉን መዞ ተወርውሮ ሄደ። ያን ጊዜም ከመብረቅና ከነጎድጓድ ጋራ ታላቅ ንውፅውፅታ ሆነ ንጉሱንም ከሰራዊቱ ጋራ አጠፋው ከከሀዲው ንጉስ ጋራ የሞቱት ቁጥራቸው አራት ሺህ እልፍ ሆነ። ጌታችንም አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስን ጠላቶችህንና የኔንም ጠላቶች አጠፋሁልህ አለው።አባተችን ግን በመብረቅ የሞቱትን ሬሳቸውን ነፍሳቸውንም መላእክተ ፅልመት ወደ ስቃይ ሲወስዱአቸው በአየ ጊዜ መድኃኒታችንን እሊህን ስሁታን ማርልኝ ሰው ስሁትና ከዳተኛ ነውና አቤቱ አንተ ግን መሀሪ ይቅር ባይ ታጋሽም ነህ አለው።አባታችንም ይህን ሲናገር ጌታችን ተሰወረ። አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም ከዚያ ሄደ ታላቅ ገደልም አገኘ እግሮቹንም በገመድ አስሮ በገደሉ ውስጥ ተዘቅዝቆ ተሰቀለ።ሰይጣንም መጥቶ ያቺን ገመድ ቆረጣት ወደ ታችም ተወርውሮ ወረደ።ቅዱስ ሚካኤልም ቀድሞ አባታችንን ያዘው በእግርህ ላቁምህ ወይም በራስህ አለው በራሴ እቆም ዘንድ ተወኝ አለው ትቶት ሄደ። በዚያም በራሱ ቁሞ በጥርሶቹም ደንጊያ ነክሶ እስከ ሰላሳ አመት ኖረ አንጀቱና ናላው ሁሉ እየፈሰሰ አልቆ መላ አካሉ እንደእንጨት ቅርፊት ሆነ። ከሰላሳ አመትም በኃላ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አባታችንን ገብረ መንፈስ ቅዱስ እያለ ሶስት ጊዜ ጠራው። እርሱም እነሆኝ ጌታዬ አለ ጌታችንም እነዚያን ከሀዱዎች ምሬልሀለሁ ከዚህ ተነሳ አለው።ያን ጊዜ የነከሰውን ደንጊያ ትቶ ተነሳ።ጥርሱም ተነቅሎ በድንጊያ ተተክሎ ቀረ። ክንፎችም ተሰጥተውት እየበረረ ከእግዚአብሔር ፊት ደረሰ ጌታውንም ከማርክልኝ ከስጋቸው ጋራ ተነስተው በመጠመቅ ክርስቲያኖች ይሁኑ ብሎ ለመነው። መድኃኒታችንም በሽተኞችን ልትፈውስ ሙታንን ልታስነሳ ስልጣን ሰጥቼሀለሁ አሁንም ወደተገደሉት ሄደህ በመስቀል ምልክት በላያቸው አማትብ ህይወት መድኃኒት በሆነ ስሜም አስነሳቸው አለው።ያን ጊዜም በድኖቻቸው ወዳሉበት ሂዶ አስነሳቸው አጥምቆም ክርስቲያኖች አደረጋቸው ከእርሳቸውም ሄደ። ከዚህ ዓለም የሚለይበት በቀረበ ጊዜ እነሆ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እነሆ ተገለጠለት። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ እስከ አስራ አምስት ትውልድ የምህረት ቃል ኪዳን ሰጠው።የእድሜውም ዘመናት አምስት መቶ ስልሳ ሁለት ሲሆን በሰላም በፍቅር አረፈ። ጌታችንም ነፍሱን ተቀበለ አቅፎም ሳማት በመላእክትና በቅዱሳን ሁሉ ምስጋና አሳረጋት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)

🔴 ስንክሳር #መጋቢት_5 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት አምስት በዚችም ቀን ተአምራቱና ትሩፋቱ የበዛ ቅዱስ አባት #አባ_ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ የእረፍቱ ቀን መታሰቢያ ሆነ፣ ክቡር ቅዱስ መናኝና ገድለኛ አባት #ቅዱስ_አባ_ሰረባሞን አረፈ፣ የከበረች #ቅድስት_አውዶክሲያ በሰማእትነት አረፈች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ መጋቢት አምስት በዚችም ቀን ተአምራቱና ትሩፋቱ እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነ ቅዱስ አባት ተጋዳይ አባ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የእረፍቱ ቀን መታሰቢያ ሆነ፡፡ ይህም ቅዱስ አባት በተወለደባት ቀን ድንቅ የሆነ ስራን ሰራ ተነስቶ ከእናቱ እቅፍ ወርዶ ከጨለማ ወደ ብርሀን ላወጣኸኝ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን እያለ ለስላሴ ሰግዷልና ምስጋናም አቅርቧልና። ህፃኑም ሶስት አመት በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር መልክተኛ ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ህፃኑን ከእናቱ እቅፍ አንስቶ ብዙ ባህታውያን ወዳሉበት ገዳም ወስዶ በደጅ አኖረው ወደ አበምኔቱ ወደ አባ ዘመደ ብርሀንም ገብቶ ስለ ህፃኑ እግዚአብሔር ያዘዘውን ሁሉ ነገረው። በዚያን ጊዜም ነገሩ እውነት እንደሆነ ይረዳ ዘንድ አባ ዘመደ ብርሀን ተነስቶ ወደ ደጅ ወጣ። መልአኩም እንደ ነገረው ህፃኑ ከበር ተቀምጦ ፈገግታን ተሞልቶ አገኘው። እጅግም ደስ ብሎት ለእግዚአብሄር ሰገደ ህፃኑንም አንስቶ ሳመው ታቅፎም ወደ በአቱ አስገባው። በፍቅር በስነስርአት አሳደገው። የዳዊትን መዝሙርና ቤተ ክርስቲያን የምትቀበላቸውን መፃህፍት ሁሉ ብሉይንና ሀዲስን አስተማረው። ከዚያም በኃላም ክህነት ይሰጠው ዘንድ ስሙ አብርሀም ወደሚባል ጳጳስ ወሰደው ጳጳሱም በአየው ጊዜ ደስ አለው። የዲቁና ማእረግንም ሾመው እንደ ቀዳሜ ሰማእት እስጢፋኖስም ፀጋንና ሞገስን የተመላ ሆነ። ከጥቂት ቀኖች በኃላም በጌታችን ትእዛዝ ቅስና ተቀበለ። በፆም በፀሎት በስግደት በብዙ ትጋትም እየተጋደለ በበረሀ ውስጥ ብቻውን ኖረ። በበረሀም ብዙ ዘመናትን ሲኖር ነፍሱን "ነፍሴ ሆይ እወቂ በእግዚአብሔር ፊት ራቁትሽን ትቆሚ ዘንድ እንዳለሽ እንግዲህስ ፅኚ በርቺ ታገሺ!" ይለት ነበር። ቆዳው ከዐጥንቱ እስቲጣበቅ ያለ መብልና ያለ መጠጥ በእንዲህ ያለ ግብር በገድል ተጠምዶ ኖረ።ከእፅዋት ፍሬዎች ወይም ከእንጨት ስሮች አልተመገበምና ለስጋውም የሚጠቅም ምንም ምን ምክንያት አልፈለገም። ለገብረ መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር እንዲህ አለው ከእንግዲህ በአለም ካሉ ሰዎች ከካህናት ከመነኮሳት ወይም ከምእመናን ህዝባውያን እንዳያውቁህ አደርግልሀለሁ። እንዳንተ ካሉ በቀር አንተ ራስህ ብትፈቅድ እንጂ መላእክትም ይጎበኙሀል። የብርሀን ሰረገላም ይሁንልህ መድረስ ወደምትሻበት ሁሉ ብረር እኔንም ማየትና በፈለግህ ጊዜ ከአባቴና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በሶስትነቴ ታየኛለህ። አሁንም ወደ ኢትዮጵያ ምድር ሂድ በዚያም ከደይን የምታወጥቸው ነፍሳት አሉህ አለው። ከዚህም በኃላ ስልሳ አንበሶች ስልሳ ነብሮች በፊት በኃላ አጅበውት ወደ ኢትዮጵያ ምድር ተጓዙ። የእግዚአብሔር መልእክተኛ ቅዱስ ገብርኤልም ከአንበሶችና ከነብሮች ጋር በነፋስ ሰረገላ አሳፍሮ ይመራው ነበር። ወደ ምደረ ከብድም አደረሰው ከዚያም ወደ ልዩ ተራራ ወደ ደብረ ዝቋላ ወሰደው። አባታችንም በባህሩ ቁሞ ምስራቁን ምዕራቡን ሰሜኑን ደቡቡን አራቱን ማእዘን ተመለከተ።የኢትዮጵያ ሰዎች የሚሰሩትን ኃጢአታቸውን በአይኖቹ ፊት የተገለጠ ሆኖ አየ። በራሱም ተዘቅዝቆ ተወርውሮ ወደ ባህሩ ውስጥ ገባ እሊህን የእጅህ ፍጥረቶች የሆኑትን ካልማርካቸው ከእዚህ ባህር እንዳልወጣ በእግሮቼም እንዳልቆም በህያው ስምህ እምላለሁ እያለ ማለ እንዲሁም ሆኖ አርባ ቀን አርባ ሌሊት ኖረ። ስምህን የጠራውን መታሰቢያህን ያደረገውን እምርልሀለሁ የሚል ቃል በመልአክ አማካይነት ወደ አባታችን መጣ። አባታችንም መልአኩን መላውን የኢትዮጵያን ሰው ካልማረልኝ ከዚህ ባህር አልወጣም አለው መልአኩም ከአጠገቡ ሄደ። አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም በዚያ ባህር ውስጥ መቶ ዓመት ኖረ ስጋው ሁሉ አለቀ ደሙም በባህሩ ውስጥ ፈሰሰ አጥንቶቹም እንደበረዶ ነጭ ሆነው ታዩ። አጋንንትም ከአራቱ ማእዘን በየቀኑ ሰባት መቶ ሽህ ሶስት መቶ ሽህ እየሆኑ በመምጣት በቀስታቸው ይነድፉታል እስከ መቶ አመትም አጥንቶቹን በሻፎ ድንጋይ ይፍቁታል ይህን ሁሉ መከራ በትእግስት ሲቀበል ኖረ። ከዚህም በኃላ ጌታችን ወደርሱ መጥቶ ከባህሩ ዳር ቆመ። አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስንም መላውን የኢትዮጵያ ሰው ምሬልሀለሁና ተነስተህ ውጣ አለው ያንጊዜም ወጣ አጥንቶቹም እንደ ወንፊት ቀዳደሰ የተበሳሱ ሆነው ተገኙ ጌታም ዳሰሰውና ጤነኛ አደረገው ወደ ምድር ከብድም ሰደደው። ከዚያም ወደ ላይ ወጥቶ ከፀሀ ከሰማይ በታች እስከ ሰባት አመት ኖረ። ዳግመኛም ወደ ምድረ ከብድ ተልኮ እንደ አምድም የተተከለ ሆኖ ሰባተረ አመት ቆሞ ኖረ። ወደ ሰማይም ሲመለከት ቅንድቦቹን አልከደነም ራሱንም ወደ መሬት ዝቅ አላደረገም ነበር እጆቹም ወደ ሰማይ ተዘርግተዋል። እነሆ ሰይጣንም በቁራ ተመስሎ መጣ አይኖቹንም ወደ ሰማይ ያንጋጠጡ ሁለቱን አይኖቹን አንቁሮ አሳወረው። እርሱ ግን ምንም ሳያጓድል እስከ ሁለት ሳምንት ድረስ እንደ ቀድሞው በመትጋት ሲፀልይ ኖረ። ከዚህም በኃላ ሚካኤልና ገብርኤል መጥተው በፊቱ ቆሙ በሁለቱ አይኖቹ ላይም እፍ አሉበት ብርሀንም ተሰጥቷቸው እንደ ቀድሞው አዩ። ከሰማይ ታላቅ ኃይል ተሰጥቶሀልና ጠላቶችህን ትበቀላቸው ዘንድ ወደ ዝቋላ ሂድ አሉት ከዚያም መላእክት ከአጠገቡ ሄዱ። እርሱም ተነስቶ ወደ ዝቋላ ተጓዘ በጎዳናም ሲጓዝ ሶስት ሽማግሌዎች ከእንጨት ጥላ በታች ተቀምጠው አየ አባታችንም በአያቸው ጊዜ ልሰውራቸው ብሎ በልቡ አሰበ። እንርሱም ፈጥነው በእግዚአብሔር ዙፋን ተማጥነናልና ሶስታችንንም በጀርባህ እያዘልክ አንዳንድ ምእራፍ ሸኘን እንጂ አትተውን ብለው ተጣሩ። በመጣም ጊዜ ሁለመናቸውን ሽበት የከበባቸው የደከሙ ሽማግሎች ሁነው አገኛቸው አንደኛውንም አንስቶ በጀርባው አዘለው ወደ አንድ ምእራፍም አደረሰው ሽማግሌውም ከዚህ አሳርፈኝ አንተ ደክመሀል የማትበላ የማትጠጣ ስለሆንክ አለው አባታችንም ሽማግሌ ሆይ በምን አወቅከኝ አለ። ሽማግሌውም ሂደህ ባልንጀሮቼን አምጣልኝ አለው ተመልሶ ሁለቱ ወደአሉበትም ደርሶ ሁለተኛውን ሽማግሌ በጀርባው አዝሎ ወደ ቀደመው ሽማግሌ አድርሶ አብሮ አስቀመጠው ሶስተኛም ተመልሶ ሶስተኛውን ሽማግሌ አዝሎ ሁለቱ ወዳሉበት አድርሶ በአንድነት አኖረው፡፡ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስም እነዚያን አረጋውያን እናነተ ከወዴትናችሁ መአዛችሁ ልብ ይመስጣል እጅግም ደስ ያሰኛል አላቸው።እነርሱ ግን ተነስተው ቆሙ አንድ ሲሆኑ ሶስት ሶስት ሲሆኑ አንድ መሆናቸውን ገለጡለት የአባቶች አለቃ አብርሀም እንደ አየ። ያንጊዜም የእግዚአብሔርን የጌትነቱን ክብር አየ የእሊያ አረጋውያንም ፊታቸው ተንቦገቦገ ከፀሀይና ከመብረቅ ብልጭታም ሰባት እጅ በራ አባታችንም በምስጢራት ጎርፍ የተዋጠ ሆኖ ፈራ ተንቀጠቀጠ በምድር ላይም ወደቀ። ህልምን የሚአልምም መሰለው ከዚያም ጌታችን አባታችንን አነቃውና መቶ አመት ያህል ስጋህን ሲነዱፉህ አጥንቶችህን ሲፍቁህ የኖሩ አጋንንትን ታጠፋቸው ዘንድ ወደ ዝቋላ ተራራ ውጣ አለው። እኔ እንደ ወሰድኩህ ባለማወቃቸው በባህር ውስጥ አለ በማለት በትእቢት ላይ ናቸው ሰባቱ ሊቃነ መላእክትም ይረዱሀል መባርቅትም በፊት በኃላ ሆነው ይከተሉሀል አለው።

..................ምኵራብ................. ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ምኵራብ› ይባላል፡፡ ምኵራብ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲፈጸምበት፣ ሕገ ኦሪት ሲነበብበት የነበረ በአይሁድ
..................ምኵራብ................. ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ምኵራብ› ይባላል፡፡ ምኵራብ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲፈጸምበት፣ ሕገ ኦሪት ሲነበብበት የነበረ በአይሁድ የሚሠራ መካነ ጸሎት ነው፡፡ ዘወትር ቅዳሜ ብዙ ሕዝብ ይሰበሰብበት ስለ ነበር ጌታችን ለማስተማር ብዙ ጊዜ በምኵራብ ተገኝቶአል፡፡ ስያሜው የተወሰደው በዮሐንስ ፪፥፲፬ ‹‹ወረከበ በምኵራብ እለ ይሠይጡ አልህምተ ወአባግዐ ወአርጋበ …፤ በመቅደስም በሬዎችን፣ ላሞችን፣ በጎችን፣ ርግቦችን፣ የሚሸጡትን አገኘ …›› ተብሎ ከተገለጸው ኃይለ ቃል ላይ ሲኾን፣ ‹ምኵራብ› የሚለው ቃልም በአማርኛ ‹መቅደስ› ተብሎ ተተርጕሟል፡፡ ምኵራብ የሚባለው ሳምንት ጌታችን ወደ ምኵራብ ገብቶ ማስተማሩ የሚነገርበት፤ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን የሌቦች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ በምኵራብ ይሸጡ፣ ይለውጡ የነበሩትን የገሠፀበት፤ ቤተ መቅደስን የከብት መንጃ የወርቅና የብር መነገጃ ያደረጉ ሰዎችን ከነሸቀጣቸው ከቤተ መቅደስ ያስወጣበት፤ ቤተ መቅደስ የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ የስሙ መጠሪያ፣ የጸሎት ሥፍራ መኾኗን ያስረዳበትና ያወጀበት፤ በቤተ መቅደስ የንግድ ሥራ ማከናወን እንደማይገባ ያረጋገጠበት ዕለት ነው፡፡

#መጋቢት_3 #አባ_ቆዝሞስ መጋቢት ሦስት በዚች ቀን በእስክንድርያ ለተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሣ ስምንተኛ የሆነው የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ወቅዱስ አባ ቆዝሞስ አረፈ። ይህም አባት እውነተኛና ንጹሕ የዋህ ርኅራኄው የበዛ የቤተ ክርስቲያንንም መጻሕፍትና ትርጓሜያቸውን የሚያውቅ ነበር። እግዚአብሔርም በወንጌላዊው ማርቆስ መንበር ላይ ለሊቀ ጵጵስና ሹመት መረጠው የግብጽ ንጉሥ መቅትር በነገሠ በአሥራ ስምንት ዓመት ሊቀጳጳሳት ሆኖ ተሾመ። በተሾመም ጊዜ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መንጋዎች በፈሪሀ እግዚአብሔርና በጥበብ ጠበቃቸው። ለእርሱ ከሚገባው ከግብሩ ገንዘብ የሚተርፈውን ለጦም አዳሪዎች ይሰጣቸው ነበር ደግሞም ቤተክርስቲያን ሕንፃ ማሠሪያ ያወጣ ነበር። መልካም ተጋድሎውንም በአየ ጊዜ ሰይጣን ያለ ኀዘን አልተወውም ነገር ግን የሚያዝንበትን ምክንያት በላዩ አመጣ። ይህም እንዲህ ነው ጴጥሮስ የሚባል ጳጳስ ለኢትዮጵያ አገር ሹሞ ነበር። አባ ጴጥሮስም ወደ ኢትዮጵያ በደረሰ ጊዜ ጥቂት ዘመን በሰላም ኖረ። ከዚህም በኋላ የኢትዮጵያ ንጉሥ ታመመ አባ ጴጥሮስንም ጠርቶ ሁለቱን ልጆቹን አቀረበ ዘውዱንም ከራሱ ላይ አንሥቶ ለአባ ጴጥሮስ ሰጠው እነሆ እኔ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እሔዳለሁ እነሆም ሁለቱ ልጆቼ በፊትህ ናቸው አንተም ለመንግሥት የሚሻለውን አውቀህ ከሁለቱ አንዱን ከእኔ በኋላ አንግሥ አለው። ንጉሡም ካረፈ በኋላ ጳጳሱ መኳንንቱና የጦር ሠራዊቱ አለቆችና የመንግሥት ሠራዊት አለቆች ተማከሩ እርስ በርሳቸውም ለመንግሥት የሚሻል የሚያንሰው ነው ተባባሉ። ጳጳሱ አባ ጴጥሮስም ታናሹን የንጉሥ ልጅ ቀብቶ አነገሠው በኢትዮጵያ መንግሥት ዙፋን ላይም አስቀመጠው ጥቂት ዘመንም በሰላም ኖረ። በዚያም ወራት ከሶሪያ አገር በሆኑ በሁለት መነኰሳት ልብ ሰይጣን አደረ ከአባ እንጦንስ ገዳም እስከ ሚደርሱ ከቦታ ወደቦታ ይዞሩ ነበር። በዚያም በአባ እንጦንስ ገዳም ጥቂት ቀኖች ተቀመጡ ስለ ሥራቸውም ክፋት አባረሩአቸው። ከዚህም በኋላ አንዱ ጳጳስ ሁለተኛውም ረዳት ሊሆን እርስ በርሳቸው ተስማሙ። ተነሥተውም ወደ ኢትዮጵያ ደረሱ። የሐሰት ጽሑፍንም ጻፉ ያ ጽሑፋቸውም እነርሱ ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ከአባ ቆዝሞስ ዘንድ ተሹመው እንደ መጡ የሚገልጥ ነበር። በዚያ ጽሑፍም እኛ ያልሾምነውና ወደ እናንተ ያልላክነው ራሱን ጳጳስ ያደረገ ስሙ ጴጥሮስ የተባለ ሰው ወደ እናንተ እንደመጣ ሰምተናል እርሱ ሐሰተኛ ነው እንጂ እውነተኛ አይደለም። ይህን ጽሑፍ ይዞ የሚመጣው ግን ስሙ ሚናስ የሚባል ጳጳስ በእውነት እኛ የሾምነውና ወደ እናንተ የላክነው እውነተኛ ነው አሉ። ሁለተኛም እንዲህ ብለው ጻፉ ጳጳሱ ጴጥርስ ታላቁን ትቶ ታናሹን የንጉሥ ልጅ አነገሠው ይህም የማይገባ ነው ዐመፅ ነውና። እሊህም ክፉዎችና ሐሰተኞች ሁለቱ መነኰሳት ሚናስና ፊቅጦር የሐሰት ጽሑፋቸውን ሳይጽፉ ወደ ጳጳሱ ጴጥሮስ ደርሰው ወርቅ ይስጣቸው ዘንድ ፈለጉ እርሱም ምንም አልሰጣቸውም። ይህንንም የከፋና የረከሰ ሥራ ሰይጣን አስተማራቸው ። የሐሰት ደብዳቤም ጽፈው ወደ ታላቁ የንጉሥ ልጅ ወሰዱ እርሱም ከጥቂት ሰዎች ጋር ለብቻው ይኖር ነበር እነዚያንም የሐሰት ደብዳቤዎች አነበቡለት እጅግም ደስ አለው። ከዚህም በኋላ ብዙ ሠራዊት ሰብስቦ እሊያን የሐሰት ደብዳቤዎች በፊታቸው አነበበላቸው ከንጉሡ ወንድሙ ጋራም ጦርነት ገጥሞ ድል አደረገው ወንድሙንም አሠረው የመንግሥቱንም ሥልጣን ያዘ እንዲሁም ጳጳሱን ጴጥሮስን አሠረው በሩቅ አገርም አጋዘው ያንንም ሐሰተኛ ሚናስን በጳጳሱ በጴጥሮስ ፈንታ አስቀመጠው። ከጥቂት ቀንም በኋላ ሐሰተኞች ፊቅጦርና ሚናስ እርስ በርሳቸው ተጣሉ ፊቅጦርም በመንበረ ጵጵስና ያለውን ገንዘብ ሁሉ ሰርቆ ወደ ግብጽ ሀገር ሸሽቶ ሔደ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ካደው። ከመንበረ ጵጵስናው የሰረቀውንም ገንዘብ ሁሉ እግዚአብሔር የማይወደውን ሥራ በመሥራት አጠፋው። ሊቀ ጳጳሳት ቆዝሞስም ሐሰተኛ ሚናስ ያደረገውን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ደብዳቤም በመጻፍ አውግዞ ለየው። የኢትዮጵያ ንጉሥም ሰምቶ እጅግ አዘነ ሐሰተኛው ሚናስንም ይዞ ገደለው። ጳጳሱ ጴጥሮስንም ከተሰደደበት ይመልሱት ዘንድ መልእክተኞችን ላከ ግን ሙቶ አገኙት። ይህም ነገር በሊቀ ጳጳሳት በቆዝሞስ ዘንድ ተሰማ ሁለተኛም ጳጳስ አልሾመላቸውም ከእርሱም በኋላ የነበሩ ሊቃነ ጳጳሳት አባ መቃርስ አባ ታውፋንዮስ አባ ሚናስ አባ አብርሃም በእነዚህ ዘመን ከዘጠኝ መቶ አሥራ አንድ ዓመተ ምሕረት እስከ ዘጠኝ መቶ ዘጠና አምስት ዓመተ ምሕረት ድረስ ለሰማንያ አራት ዓመታት ያህል ለኢትዮጵያ ሰዎች ጳጳስ ተሹሞ አልተላከላቸውም። የኢትዮጵያ ንጉሥ ግን የጳጳሱ የጴጥሮስ ረዳት የነበረውን ወስዶ በመምህርህ ፈንታ ጳጳስ ሁነህ ተቀመጥ አለው። እርሱም እኔ ጳጳስ ልሆን አይገባኝም የሐዋርያትንም ሥርዓት ተላልፌ ይህን ልሠራ አይቻለኝም ግን ልቀቀኝና ወደ ግብጽ ልሒድ ጳጳስ እንዲሾምላችሁም ሊቀ ጳጳሱን እለምነዋለሁ ከዚያም በኋላ ወደ እናንተ እመለሳለሁ እያለ ንጉሡን ማለደው። ንጉሡም ወደ ግብጽ እንዲሔድ አላሰናበተውም ያለ ውዴታው ወስዶ የጵጵስናውን ልብስ አለበሰው እንጂ። የጵጵስናውንም ሥራ እንዲሠራ አደረገው። አባ ቆዝሞስም እጅግ ሸመገለ የሹመቱም ዘመን ድኀንነትንና ሰላምን የተመላ ነበር በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም አሥራ ሁለት ዓመት ኖረ በሰላምም አረፈ፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት)

🛑 ለበዓለ ጥምቀት እንዲሁም በደብራችን ለተከበሩ በዓላት ዩኒፎርም ወስዳችሁ ያልመለሳችሁ የወጣት ክፍል አባላት እስከ እሁድ ለንብረት ክፍል ገቢ እንድታደርጉ እናሳስባለን
🛑 ለበዓለ ጥምቀት እንዲሁም በደብራችን ለተከበሩ በዓላት ዩኒፎርም ወስዳችሁ ያልመለሳችሁ የወጣት ክፍል አባላት እስከ እሁድ ለንብረት ክፍል ገቢ እንድታደርጉ እናሳስባለን

🔴 ስንክሳር #መጋቢት_2 መጋቢት ሁለት በዚች ቀን የኒቅዮስ ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_አባ_መከራዊ በሰማዕትነት ሞተ። የሮሀ አገር የሆነ የተሠወረውን የሚያይ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_መከራዊ_ዘሃገረ_ኒቅዮስ መጋቢት ሁለት በዚች ቀን የኒቅዮስ ኤጲስቆጶስ አባ መከራዊ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም አባት በግብጽ ደቡብ ከምትገኝ ከእስሙናይን ከታላላቆቿ ወገን ነው። ለኒቅዮስ ከተማም ኤጲስቆጶስነት ተሾመ። የስደትና የመከራ ወራት በሆነ ጊዜም ስሙ ዮፋንስ የሚባል መኰንን ወደዚያች አገር ከንጉሥ ተልኮ መጣ። የክርስቲያን ወገኖችንም ያሠቃይ ዘንድ ጀመረ። የዚህንም የቅዱስ ኤጲስቆጶስ አባ መከራዊን ዜና ሰምቶ ወደርሱ ያመጡት ዘንድ ወታደሮቹን ላከ እርሱም ወደ መኰንኑ ከመሔዱ በፊት ወደ ቅዱስ መሠዊያው ገባ እጆቹንም ዘርግቶ ጸለየ። ንዋየ ቅዱሳቱንና የመቀደሻውን ልብሶች በመቅደሱ ውስጥ አኖረ። ከዚያም በኋላ ቤተ ክርስቲያኑን ይጠብቅ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ ማለደ። በላያችሁ የፀሐይ ብርሃን ይወጣ ዘንድ ያልተዋችሁ የጽዮን ልጅ ደጆች ሆይ ለእግዚአብሔር ቤት ማገልገያ የሆነ ነዋየ ቅዱሳቱን ጠብቁ እያለ ታላቅ ልቅሶ በማልቀስ ጮኸ። ከዚህም በኋላ ከንጉሥ መልክተኞች ጋራ ወጥቶ ሔደ ወደ መኰንኑም ቀረበ። ስለ ስሙና ስለ አገሩ ስም ስለ ሥራውም ጠየቀው። የኒቅዮስ ከተማ ኤጲስቆጶስ እንደሆነም ባወቀ ጊዜ እንዲገርፉትና እንዲያጐሳቁሉት ብርና እርሳስም አቅልጠው በአፉ እንዲጨምሩ አዘዘ። እግዚአብሔርም የሚያጸናውና የሚያስታግሠው ሆነ። ያለ ጉዳትም በጤንነት መልሶ ያነሣው ነበር። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ገዥ ወደ ኄርሜኔዎስ ሰደደው። እርሱም ቅዱስ አባ መከራዊን እንዲአሥሩት አዘዘ። እግዚአብሔርም በእጆቹ ብዙዎች ድንቆች ተአምራትን አደረገ ከተአምራቱም አንዱ ለአቅፋስ ከተማ ሹም ለሆነ ለዮልዮስ ስሙ አውካሪስጦስ የሚባል እጆቹና እግሮቹ ሽባ የሆነ ልጅ ነበረው አባ መከራዊም በላዩ ጸለየ። ከደዌውም አዳነው። ከዚህ በኋላ በዮልዮስ ቤት ቀድሶ ለአማንያን ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ስለ ሥጋውም እንዲአስብና ገድሉንም እንዲጽፍለት ከዮልዮስ ጋራ ስምምነት አደረገ። መኰንኑ ኄርሜኔዎስም አባ መከራዊ ስለ አደረጋቸው አስደናቂ ተአምራት በሰማ ጊዜ በተለያየ ሥቃይ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ። ሕዋሳቶቹ እስቲቆራረጡ በመንኰራኵሮች ውስጥ አስገብተው አሠቃዩት። ለነጣቂዎች አንበሶችም ጣሉት በባሕርም አሠጠሙት በእሳት ምድጃ ውሰጥም ጨመሩት። ቅዱስ አባ መከራዊ በሥቃዩ ሁሉ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የሚታገሥና የሚጸና ሆነ። ጌታም ያለ ጉዳት መልሶ በጤንነት ያስነሣው ነበር። የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ቤተ ክርስቲያን የምታገለግል አንዲት ድንግል እኅትም ነበረችው። ሁለት ወንድሞችም ነበሩት የአንደኛው ስም ዮሐንስ የሁለተኛውም ይስሐቅ ይባላል በእሥር ቤትም ሳለ ወደርሱ መጡ አንተ ስለ አባታችን ፈንታ አባት ሆነኽን ነበር እነሆ የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ ትተኸን ትሔዳለህ እያሉ በፊቱ አለቀሱ። እርሱም አጽናንቶ ወደ ቤቶቻቸው አሰናበታቸው። ዮልዮስም የዚህን ሽማግሌ ሞት በጽሑፍ እዘዝ ከእርሱም ታርፋለህ ብሎ መኰንኑን መከረው። ቃሉንም ተቀብሎ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ ።በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀዳጀ። ዮልዮስም የቅዱስ አባ መከራዊን ሥጋ ወስዶ በከበሩ በወርቅ ልብሶች ገነዘው በደረቱም ላይ የወርቅ መስቀል አደረገ ወደ ሀገሩ ወደ ኒቅዮስም ከአገልጋዮቹ ጋራ ሰደደው። መልካም ነፋስም ሆኖላቸው መርከቢቱ ፈጥና ሔደች በከተማውም በር አንጻር ደርሳ ቆመች። ቀዛፊዎችም ሊያንቀሳቅሱዋት ፈልገው ነበር ግን አልተቻላቸውም አብዝተው በደከሙም ጊዜ ሥጋዬ በውስጡ እንዲኖር እግዚአብሔር የፈቀደው ቦታ ይህ ነው የሚል ቃል ከበድኑ ወጣ። ይህንንም ለሀገር ሰዎች ነገሩአቸው የሰሌን ዝንጣፊም እየያዙ ወደርሱ መጡ በሀገራቸውም ውስጥ እርሱ በመረጣት ቦታ እስከ አኖሩት ድረስ በታላቅ ክብር ተሸክመው ወሰዱት። መላው የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ ሠላሳ አንድ ሆነ። መጻሕፍትን እስከተማረ ድረስ ስምንት ዓመት በዲቁና ሹመት ሃያ አራት ዓመት ከዚያም ቅስና ተሹሞ በቅስና አገልገሎት ሠላሳ ዓመት ኖረ ከዚያም በኋላ ኤጲስቆጶስ ሁኖ ተሾመ። በዚህም ስልሳ ዘጠኝ ዓመት ኑሮ መልካም ተጋድሎውን ፈጸመ። የሕይወት አክሊልንም ከክብር ባለቤት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)

"ልጆቼ ሆይ! ከብርሃን ጨለማን ከደግነት ክፋትን ከጽድቅ ይልቅ ኃጢአትን . . . ምነው መምረጣችሁ? እኔ ስለ እናንተ በየቀኑ እየለመንሁ እነሆ አለሁ:: ወደ ጨለማ ገሃነም እንዳትወርዱ እባካችሁ ንስሐ ግቡ!" ቅድስት ድንግል ማርያም ይህንን ለቅዱሱ ሰው ነግራው ቅዱስ ዳዊትን አስከትላ በግሩማን መላእክት ታጅባ ወደ ውሳጤ መንጦላዕት (የእሳት መጋረጃዎች ወደ ተተከሉበት ድንኳን) ገባች:: በዚያም ተመሰገነች:: ለዛም አይደል ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ:- "ይዌድስዋ መላእክት ለማርያም በውስተ ውሳጤ መንጦላዕት : ወይብልዋ : በሐኪ ማርያም ሐዳስዩ ጣዕዋ::" ሲል ያመሰገናት:: ቅዱስ ጐርጐርዮስም ከሰማይ ቆይታ መልስ ያየውን ሁሉ ጽፎ ለአበው ሰጥቷል:: ስለዚህም ረዓዬ ኅቡዓት (ምሥጢራትን ያየ) ይሰኛል:: ቅዱሱ ተረፈ ዘመኑን በተጋድሎ ፈጽሞ በዚህች ቀን አርፏል:: ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)

🔴 ስንክሳር #መጋቢት_2 መጋቢት ሁለት በዚች ቀን የኒቅዮስ ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_አባ_መከራዊ በሰማዕትነት ሞተ። የሮሀ አገር የሆነ የተሠወረውን የሚያይ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_መከራዊ_ዘሃገረ_ኒቅዮስ መጋቢት ሁለት በዚች ቀን የኒቅዮስ ኤጲስቆጶስ አባ መከራዊ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም አባት በግብጽ ደቡብ ከምትገኝ ከእስሙናይን ከታላላቆቿ ወገን ነው። ለኒቅዮስ ከተማም ኤጲስቆጶስነት ተሾመ። የስደትና የመከራ ወራት በሆነ ጊዜም ስሙ ዮፋንስ የሚባል መኰንን ወደዚያች አገር ከንጉሥ ተልኮ መጣ። የክርስቲያን ወገኖችንም ያሠቃይ ዘንድ ጀመረ። የዚህንም የቅዱስ ኤጲስቆጶስ አባ መከራዊን ዜና ሰምቶ ወደርሱ ያመጡት ዘንድ ወታደሮቹን ላከ እርሱም ወደ መኰንኑ ከመሔዱ በፊት ወደ ቅዱስ መሠዊያው ገባ እጆቹንም ዘርግቶ ጸለየ። ንዋየ ቅዱሳቱንና የመቀደሻውን ልብሶች በመቅደሱ ውስጥ አኖረ። ከዚያም በኋላ ቤተ ክርስቲያኑን ይጠብቅ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ ማለደ። በላያችሁ የፀሐይ ብርሃን ይወጣ ዘንድ ያልተዋችሁ የጽዮን ልጅ ደጆች ሆይ ለእግዚአብሔር ቤት ማገልገያ የሆነ ነዋየ ቅዱሳቱን ጠብቁ እያለ ታላቅ ልቅሶ በማልቀስ ጮኸ። ከዚህም በኋላ ከንጉሥ መልክተኞች ጋራ ወጥቶ ሔደ ወደ መኰንኑም ቀረበ። ስለ ስሙና ስለ አገሩ ስም ስለ ሥራውም ጠየቀው። የኒቅዮስ ከተማ ኤጲስቆጶስ እንደሆነም ባወቀ ጊዜ እንዲገርፉትና እንዲያጐሳቁሉት ብርና እርሳስም አቅልጠው በአፉ እንዲጨምሩ አዘዘ። እግዚአብሔርም የሚያጸናውና የሚያስታግሠው ሆነ። ያለ ጉዳትም በጤንነት መልሶ ያነሣው ነበር። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ገዥ ወደ ኄርሜኔዎስ ሰደደው። እርሱም ቅዱስ አባ መከራዊን እንዲአሥሩት አዘዘ። እግዚአብሔርም በእጆቹ ብዙዎች ድንቆች ተአምራትን አደረገ ከተአምራቱም አንዱ ለአቅፋስ ከተማ ሹም ለሆነ ለዮልዮስ ስሙ አውካሪስጦስ የሚባል እጆቹና እግሮቹ ሽባ የሆነ ልጅ ነበረው አባ መከራዊም በላዩ ጸለየ። ከደዌውም አዳነው። ከዚህ በኋላ በዮልዮስ ቤት ቀድሶ ለአማንያን ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ስለ ሥጋውም እንዲአስብና ገድሉንም እንዲጽፍለት ከዮልዮስ ጋራ ስምምነት አደረገ። መኰንኑ ኄርሜኔዎስም አባ መከራዊ ስለ አደረጋቸው አስደናቂ ተአምራት በሰማ ጊዜ በተለያየ ሥቃይ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ። ሕዋሳቶቹ እስቲቆራረጡ በመንኰራኵሮች ውስጥ አስገብተው አሠቃዩት። ለነጣቂዎች አንበሶችም ጣሉት በባሕርም አሠጠሙት በእሳት ምድጃ ውሰጥም ጨመሩት። ቅዱስ አባ መከራዊ በሥቃዩ ሁሉ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የሚታገሥና የሚጸና ሆነ። ጌታም ያለ ጉዳት መልሶ በጤንነት ያስነሣው ነበር። የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ቤተ ክርስቲያን የምታገለግል አንዲት ድንግል እኅትም ነበረችው። ሁለት ወንድሞችም ነበሩት የአንደኛው ስም ዮሐንስ የሁለተኛውም ይስሐቅ ይባላል በእሥር ቤትም ሳለ ወደርሱ መጡ አንተ ስለ አባታችን ፈንታ አባት ሆነኽን ነበር እነሆ የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ ትተኸን ትሔዳለህ እያሉ በፊቱ አለቀሱ። እርሱም አጽናንቶ ወደ ቤቶቻቸው አሰናበታቸው። ዮልዮስም የዚህን ሽማግሌ ሞት በጽሑፍ እዘዝ ከእርሱም ታርፋለህ ብሎ መኰንኑን መከረው። ቃሉንም ተቀብሎ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ ።በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀዳጀ። ዮልዮስም የቅዱስ አባ መከራዊን ሥጋ ወስዶ በከበሩ በወርቅ ልብሶች ገነዘው በደረቱም ላይ የወርቅ መስቀል አደረገ ወደ ሀገሩ ወደ ኒቅዮስም ከአገልጋዮቹ ጋራ ሰደደው። መልካም ነፋስም ሆኖላቸው መርከቢቱ ፈጥና ሔደች በከተማውም በር አንጻር ደርሳ ቆመች። ቀዛፊዎችም ሊያንቀሳቅሱዋት ፈልገው ነበር ግን አልተቻላቸውም አብዝተው በደከሙም ጊዜ ሥጋዬ በውስጡ እንዲኖር እግዚአብሔር የፈቀደው ቦታ ይህ ነው የሚል ቃል ከበድኑ ወጣ። ይህንንም ለሀገር ሰዎች ነገሩአቸው የሰሌን ዝንጣፊም እየያዙ ወደርሱ መጡ በሀገራቸውም ውስጥ እርሱ በመረጣት ቦታ እስከ አኖሩት ድረስ በታላቅ ክብር ተሸክመው ወሰዱት። መላው የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ ሠላሳ አንድ ሆነ። መጻሕፍትን እስከተማረ ድረስ ስምንት ዓመት በዲቁና ሹመት ሃያ አራት ዓመት ከዚያም ቅስና ተሹሞ በቅስና አገልገሎት ሠላሳ ዓመት ኖረ ከዚያም በኋላ ኤጲስቆጶስ ሁኖ ተሾመ። በዚህም ስልሳ ዘጠኝ ዓመት ኑሮ መልካም ተጋድሎውን ፈጸመ። የሕይወት አክሊልንም ከክብር ባለቤት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ተቀበለ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ጐርጐርዮስ_ረዓዬ_ኅቡዓት ዳግመኛም በዚች ቀን የሮሀ አገር የሆነ የተሠወረውን የሚያይ ቅዱስ ጎርጎርዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ሰው አስቀድሞ አመፀኛና ኃጥእ ነበረ ከዚህም በኋላ ከዐመፁ ወደ እግዚአብሔር በንስሓ ተመልሶ መነኰሰ። የጻድቃንን ማደሪያና ብዙ ዋጋቸውን የኃጥአንንም ኵነኔና እየራሱ የሆነ ሥቃያቸውን እግዚአብሔር እስከ አሳየው ድረስ ብዙ ተጋደለ። ቅዱስ ጐርጐርዮስ ሃገሩ ሮሃ (ሶርያ አካባቢ) ሲሆን ረዓዬ ኅቡዓት (ምሥጢራትን የተመለከተ) ይባላል:: ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- ቅዱሱ ተወልዶ ባደገባት ሃገር ይህ ቀረው የማይባል ኃጢአተኛ ሰው ነበር:: ታዲያ ምንም ኃጢአተኛ ሰው ቢሆን እመቤታችን ድንግል ማርያምን በፍፁም ልቡ ይወዳት ነበርና በመዳን ቀን ጥሪ ለንስሐ አበቃችው:: ከዚያች ዕለት ጀምሮም ቅዱስ የእግዚአብሔር ሰው ንጹሕ የቤተ ክርስቲያን መስዋዕት ጽኑዕ የበርሃ ምሰሶ ሆነ:: ድንግል እመቤታችንም ከነሥጋው ወደ ሰማያት ወስዳ ገነትና ሲዖልን አሳይታ ከአዳም፣ ኖኅ፣ አብርሃም፣ ሙሴ፣ ዳዊትን ከመሰሉ ቅዱሳን ጋር አስተዋውቃ ከዚህም በላይ የሆነና በሰብአዊ አንደበት የማይነገር ብዙ ምሥጢር አሳይታ ወደ ምድር መልሳዋለች:: ቅዱስ ጐርጐርዮስ በሰማይ (በገነት) በነበረው ቆይታ ክብረ ቅዱሳንን ተመልክቶ አድንቋል:: በተለይ በፍጹምነት ድንግልናቸውን የጠበቁ ቅዱሳንና ቅዱሳት ደናግል አኗኗራቸው ከአምላክ እናት ከሰማይ ንግሥት ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም ጋር መሆኑን አይቷል:: "የለበሱት ልብስም በፍጡር አንደበት ተከናውኖ ሊነገር የሚቻል አይደለም" ይላል:: የደናግል ፊታቸው ከፀሐይ 7 እጅ ያበራልና ግርማቸው ያስፈራል:: ቅዱሱ ሰው በዚያው በሰማይ ሳለ ደግሞ ይህንን ተመለከተ:: አንድ አረጋዊ ጽሕሙ ተንዠርግጐ የብርሃን ካባ ላንቃ ለብሶ ይመጣል:: ቅዱሳን መላእክት በፊት በኋላ በቀኝ በግራ ከበውት ሳለ እግዚአብሔርን ሊያመሰግን ጀመረ:: "እግዚኦ እግዚእነ ጥቀ ተሰብሐ ስምከ በዲበ ምድር (አቤቱ ጌታችን በምድር ሁሉ ስምህ የተመሰገነ ሆነ)" ሲል . . . መላእክቱ በዝማሬ አጀቡት:: በዚህ ጊዜም ታላቅ መናወጥ ሆነ:: ደናግሉም የቅዱሱን ሽማግሌ በረከቱን ተሳተፉ:: ይህ አመስጋኝ ሽማግሌ ልበ-አምላክ ጻድቅ የዋህና የእሥራኤል ንጉሥ የሆነው ዳዊት ነበር:: በምን ታወቀ ቢሉ:- በበገናው:: አንድም እመቤታችን "አባቴ ዳዊት!" ብላ ስትጠራው ጐርጐርዮስ ሰምቷልና:: በመጨረሻም እመቤታችንን በፍጹም ክብርና ግርማ ተመልክቷት ሐሴትን አድርጓል:: እመብርሃንም "ተወዳጅና ንጹሕ ሰው ነህ" ስትል ቅዱስ ጐርጐርዮስን አመስግናዋለች:: ስለዚህ ዓለምም እንዲህ የሚል መልእክትን ልካለች::

🔴 ስንክሳር #መጋቢት_1 መጋቢት አንድ በዚህች ቀን የኢየሩሳሌም አገር ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_በርኪሶስ አረፈ፣ የሰማዕቱ #የቅዱስ_እለእስክንድሮስ መታሰቢያው ነው፣ የሄኖክ ልጅ #ቅዱስ_ማቱሳላህ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_በርኪሶስ መጋቢት አንድ በዚህች ቀን የኢየሩሳሌም አገር ኤጲስቆጶስ ቅዱስ በርኪሶስ አረፈ። ይህም አባት ክርስቲያኖችን በሚወዳቸው በቄሣር እለእስክንድሮስ ዘመነ መንግሥት ተሹሞ ሳለ ሐዋርያት ሲጠብቋቸው እንደነበረ በበጎ አጠባበቅ ሕዝቡን ጠበቃቸው። ከጥቂት ጊዜ በኋላ እለእስክንድሮስ ሞተ ከእርሱም በኋላ ቄሣር መክስሚያኖስ ነገሠ፡፡ ክርስቲያኖችንም በጽኑዕ መከራ አሠቃያቸው ከእርሳቸውም ብዙዎችን ገደላቸው። ሀገሮቻቸውን ትተው የተሰደዱም አሉ። ይህም አባት ሽሽቶ ወደ ገዳም ገባ ሕዝቡም ፈልገው አጡት። ከዚህም በኋላ ስሙ ዲዮስ የተባለ ሌላ ኤጲስቆጶስ በላያቸው ሾሙ። እርሱም በጥቂት ቀን አረፈ። ከዚህ በኋላ ስሙ አግርንዲኖስ የሚባል ሌላ ኤጲስቆጶስ ሾሙ። የስደቱም ወራት በአለፈ ጊዜ ይህ አባት በርኪሶስ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ተመለሰ። አግርንዲኖስ የሚባል ሌላ ኤጲስቆጶስ ሹመው አገኛቸው። ወደርሳቸውም በደረሰ ጊዜ ሕዝቡ በመምጣቱ ደስ አላቸው አግርንዲኖስም ተመልሶ በመንበረ ጵጵስናው ላይ እንዲቀመጥ ለመነው በታላቅ ድካምም በወንበሩ ላይ አስቀመጡት። ከአግርንዲኖስም ጋራ አንዲት ዓመት ኖረ አግርንዲኖስም አረፈ። አባ በርኪሶስም እጅግ እስኪያረጅና እስኪደክም ድረስ ኖረ ወገኖቹንም ሌላ ኤጲስቆጶስ በላያቸው እንዲሾሙ ለመናቸው እነርሱም አይሆንም አሉ። በዚያም ወራት የቀጰዶቅያ ኤጲስቆጶስ ስሙ እለእስክንድሮስ የሚባል አንድ ሰው ነበር። እርሱም በውስጥዋ ሊጸልይና ወዳገሩ ሊመለስ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ። ሥራውንም በጨረሰ ጊዜ የበዓሉም ቀኖች በተፈጸሙ ጊዜ ወዳገሩ ሊመለስ ወደደ። በመድኃኒታችን ትንሣኤ በዓል በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ መግቢያ ወደ ዕገሌ ደጃፍ ውጡ ወደ ደጃፉ መጀመሪያ የሚገባውን ያዙት በጵጵስና ሥራም ይረዳው ዘንድ ከበርኪሶስ ጋራ አድርጉት የሚል ቃል እነሆ ተሰማ። ወጥተውም ወደ ደጃፉ በደረሱ ጊዜ እለእስክንድሮስን አገኙት ይረዳውም ዘንድ ያለ ፈቃዱ ከአባት በርኪሶስ ጋራ አደረጉት። እስከሚአርፍበትም ጊዜ አብሮት ኖረ። መላ የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ አሥራ ሰባት ዓመት ሆነ ኤጲስቆጶስነት ሳይሾም ሰማንያ አንድ ዓመት ኖረ በሹመቱም ላይ ሠላሳ ስድስት ዓመታትን ኖረ። እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ በዚህችም ዕለት የሰማዕቱ የቅዱስ እለእስክንድሮስ መታሰቢያው ነው። ይህም ቅዱስ ሰማዕት የሮም ሀገር ሰው ነው ለእርሱ ባለመታዘዙና ለረከሱ ጣዖቶቹ ባለመሠዋቱ ከሀዲው መክስሚያኖስ ጽኑዕ ስቃይን አሠቃየው። እጅግ ከባድና ታላቅ የሆነ ደንጊያ በእጆቹና በእግሮቹ ላይ አሥሮ ሰቀለው። ብዙ ግርፋትንም ገረፈው ጐኖቹንም ቀደደ በፊቱም ላይ የእሳት መብራት ጨመሩ። ሥቃዩንም ባልፈራ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕታትን አክሊል ተቀዳጀ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ማቱሳላ ዳግመኛም በዚህች ዕለት የሄኖክ ልጅ የማቱሳላህ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እርሱም 969 ዓመት የኖረ ሲሆን የአዳም 7ኛ ትውልድ የሆነው የሄኖክ ልጅ ነው፡፡ አዳም ሴትን ወለደ፣ ሴት ሄኖስን፣ ሄኖስ ቃይናን፣ ቃይናን መላልኤልን፣ መላልኤል ያሬድን፣ ያሬድ ሄኖክንመ ሄኖክ ማቱሳላህን ወለደ፡፡ ማቱሳላህም ላሜሕን ወለደ፣ ላሜህም ኖኅን ወለደ፡፡ ማቱሳላህም 969 ዓመት ከኖረ በኋላ ዐረፈ፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን ልዩ የሆነች በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት እና #ከገድላት_አንደበት)

የወጣት ምድብ አገልግሎት ተጀመረ ከላይ የተዘረዘረውን ስም በማየት ከታች ያስቀመጥነውን የቴሌግራም ሊንክ በየምድባችሁ እየተጫናችሁ ስለምድቡ መወያየት ትችላላችሁ