የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
رفتن به کانال در Telegram
2 640
مشترکین
-224 ساعت
+87 روز
+5630 روز
آرشیو پست ها
Watch "MK TV || ሰ/ት/ቤት ወግቢ ጉባኤያት || የበዓለ ገና ሥጦታ በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ" on YouTube
https://youtu.be/Pbz-cbeGQQ8
የተከበራችሁ የሰንበት ት /ቤታችን አባላት ለጥምቀት አገልግሎት እንድታገለግሉ የተመረጣችሁ አባላት የአገልግሎት ልብስ (ዩኒፎርም) የሚሰጥበት ቀን
- ለባለትዳር
ከ23 ጀምሮ እስከ 05/05/2015 ድረስ
- ወጣት
ከ29 ጀምሮ እስከ 03/05/2015 ድረስ
- ማዕከላዊያን
ከ03 ጀምሮ እስከ 05/05/2015 ድረስ ይሆናል ከራሳችሁ ውጪ ለሌላ አባላት እንደማይሰጥ ከወዲሁ እናሳስባለን የሚመለስበት ቀን ከ15-21 ይሆናል ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችንም ጋር ይሁን።
ሕማማት ላይይውላልና በዚህ ወቅት ደግሞ ፍጹም ሐዘን ልቅሶ ጾም ጸሎት ይያዛል እንጂ ደስታ ፌሽታ እልልታ ጭብጨባ የለም፡፡ ዓቢይ ጾም ፍጹም የሐዘን ወራት ነው፡፡ ታቦት አውጥቶ በዓል ማክበር ስህተት ነው፤ የአባቶችንም ሥርዓት ማፍረስ ነው፡፡ ምስጋና ይድርሳቸውና ቅዱሳን አባቶቻችን ሁሉንም ነገር በሥርዓት በሥርዓቱ አድርገው ሰፍረው ቆጥረው አስቀምጠውልናል፡፡ ከዓቢይ ጾም በኋላ ያሉትን 50 ቀናት ረቡዕና ዓርብንም ጭምር ሥጋ እንኳን እንድንበላ ነው ሥርዓት የሠሩልን፡፡ አባቶቻችን የሠሯት ሕግ ፍጽምት ናት፡፡ በዚህም መሠረት አባቶቻችን ሥርዓትን ሠሩልንና የመጋቢት 27 የጌታችንን የስቅለቱን በዓል ወደ ጥቅምት 27 ቀን አምጥተው እንዲሁም የመጋቢት 5 የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስን የዕረፍት በዓል ወደ ጥቅምት 5 ቀን አዙረው እንዲከበር አድርገዋል፡፡ የመጋቢት 29 የብሥራቱን በዓል ደግሞ ወደ ታኅሣሥ 22 ቀን አዙረውት በዚህ ዕለት እንዲከበር አድርገውታል፡፡ አንድም ነገረ ልደቱን ከማክበር አስቀድሞ ነገረ ፅንሰቱን ማዘከር ማክበር ተገቢና መሆንም ያለበት ነውና ነው፡፡ ይህንንም ያደረገው ታላቁ አባት ቅዱስ ደቅስዮስ ነው፡፡ በእመቤታችን ፍቅር ልቡ የነደደው ይህ ታላቅ አባት የእመቤታችንን ተአምራቶቿን የጻፈላትም እርሱ ነው፡፡ እርሱም ከፍቅሩ ጽናት የተነሣ የእመቤታችንን የተአምራቷን መጽሐፍ ሰብስቦ አዘጋጀ፡፡
አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናቸ ክብርት እመቤታችንም ተገለጸችለትና መጽሐፉን በእጇ አንሥታ ይዛ ‹‹ወዳጄ ደውስዮስ ሆይ! ይህን መጽሐፍ ስለጻፍክልኝ ባንተ ደስ አለኝ፣ አመሰገንኩህ፣ እንዳከበርከኝ እኔም አከብርሃለው›› አለችው፡፡ ከዚህም በኋላ ከእርሱ ተሠወረች፡፡ ደቅስዮስም እመቤታችንን ከመውዱ የተነሣ ፈጽሞ ደስ አለው፡፡ ፍቅሯም እንደ እሳት አቃጠለው፡፡ የእርሷን ክብር አብዝቶ ይጨምር ዘንድ ምን እንደሚያደርግ የሚሠራውን ያስብ ጀመር፡፡
ከዚህም በኋላ በዚያን ጊዜ ጾም ስለነበር ሰዎች አስቀድመው ሊያከብሩት ያልተቻላቸውን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ባበሠራት ቀን በዓሏን አከበረ፡፡ እርሱም የከበረ የሚሆን የልደትን በዓል ከማክበር አስቀድሞ በ8 ቀን አደረገ፡፡ ይኸውም ታኅሣሥ በባተ በ22ኛው ቀን ነው፡፡ ይኽችውም ሥርዓቱ እስካሁን ጸንታ ኖራለች፡፡ ሰዎቹም በዓሉን ባከበሩ ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናቸ ክብርት እመቤታችን በእጇ የከበረ ልብስ ይዛ ዳግመኛ ለቅዱስ ደቅሲዮስ ተገለጸቸለትና ‹‹አገልጋዬ የሆንክ ወዳጄ ደቅስዮስ ሆይ! በዕውነት አመሰገንኩህ፣ በአንተ ደስ አለኝ፣ ሥራህንም ወደድኩ፡፡ በእኔም ደስ እንዳለህና የከበረ መልአክ ገብርኤል እኔን በአበሠረበት ቀን በዓሌን ስላከበርክ ሰውንም ሁሉ ስለእኔ ደስ ስላሰኘህ እኔም ዋጋህን ልሰጥህ መጥቻለሁ፤ አንተ በዚህ ዓለም እንዳከበርከኝ እኔም በሰው ሁሉ ፊት አከብርህ ዘንድ እወዳለሁ›› አለችው፡፡ ይህንንም ካለችው በኋላ ‹‹እርሷን ትለብስ ዘንድ ይህችን ልብስ እነሆ አመጣሁልህ፤ በላዩም ትቀመጥ ዘንድ ይህን ወንበር አመጣሁልህ ፡፡ ከሰው ወገን አንድ ስንኳ ይህችን ልብስ ሊለብሳት በዚህችም ወንበር ላይ ሊቀመጥ የሚቻለው የለም፡፡ ይህንን ነገሬን የሚተላለፍ ቢኖር እኔ እበቀለዋለሁ›› አለችውና ሰማያዊ ልብስና ሰማያዊ ወንበር ሰጠችው፡፡ እመቤታችንም ይህንን ተናግራ ከባረከችው በኋላ ከእርሱ ተሠወረች፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ደቅስዮስ በዚሁ በዓለ ብሥራትን ባከበረበት ዕለት ታኅሣሥ 22 ቀን ካረፈ በኋላ አንድ ሌላ ኤጲስቆጶስ በተሾመ ጊዜ እመቤታችን ለቅዱስ ደቅስዮስ የሰጠችውን ልብስ ለበሰ፣ በወንበሩም ላይ ተቀመጠ፡፡ ሰዎችም ይህን አይተው ‹‹እባክህ ይቅርብህ እመቤታችን እንዲህ ብላ ተናግራለችና›› ቢሉት በመታጀር ‹‹እርሱም (ደቅስዮስም) ሰው እኔም ሰው፣ እርሱም ኤጲስቆጶስ እኔም ኤጲስቆጶስ›› ብሎ በትዕቢት ተናገረ፡፡ በወንበሩም ላይ እንደተቀመጠ ወድቆ ሞተ፡፡ ይህንንም ያዩ ሁሉ ከእመቤታችን ተአምር የተነሣ አደነቁ፡፡ እጅግም ፈርተው እመቤታችንን አከበሯት፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ ለቅዱስ ደቅስዮስ የተለመነች ክብርን የተመላች ድንግል ወላዲተ አምላክ ለእኛም ትለመነን! አምላካችን ልጇ በምልጃዋ ይማረን!https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_22
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
#ቅዱስ_ገብርኤል_እመቤታችንን ያበሰረበት መታሰቢያ ነው፣ የመላእክት አለቃ #የቅዱስ_ገብርኤል ዳህና በሚባል አገር ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራችበት ነው፣ #የብርሃን_እናቱ_ድንግል_ወላዲተ_አምላክ ለወዳጇ #ለቅዱስ_ደቅስዮስ ሰማያዊ ወንበርና ልብስ የሰጠችበት እና የዕረፍቱ ዕለት ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ብሥራተ_ቅዱስ_ገብርኤል
ታኅሣሥ ሃያ ሁለት በዚህች ዕለት ብርሃናዊው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን አምላክን እንደምትወልድ ያበሰረበት መታሰቢያ ነው፡፡ ይኸውም ‹‹ልዑል እግዚአብሔር ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤልን ‹ሂድና ለጽዮን ልጅ ለድንግል የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ወደአንቺ መጥቶ ኃይለ ልዑል ወልድ ሥጋሽን ለብሶ ሰው ይሆናል፤ ይኸውም ካንቺ የሚወለደው ጽኑዕ ነው ብለህ ንገራት› አለው፡፡ ‹ደንቆሮዎች የሚሰሙበት፣ ድዳዎቸ የሚናገሩበት፣ ዕውራንም የሚያዩበት፣ ሙታን የሚነሡበት፣ ለምጻሞች የሚነጹበት፣ ሐንካሳዎች የሚሄዱበት፣ በጨለማ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ብርሃን የሚያዩበት ጊዜ እነሆ ደረሰ ብለህ ንገራት› አለው፡፡
ቅዱስ ገብርኤልም ይህን ሰምቶ በግንባሩ ተደፍቶ ልዑል እግዚአብሔርን ‹ጌታ ሆይ! የምትነግረኝ ይደረግ ዘንድ እንደምን ይሆናል?› አለው፡፡ ጌታም ‹የጀመርኩትን ቸርነት ፈጸምኩ፣ የወይን ግንድ ይቆረጣል (ወልደ እግዚአብሔር ይሞታል)፣ ወይራም ከበለስ ጋር ይተከላል (መስቀል ይተከላል)፣ ቅጽሮችም ይቀጸራሉ (ምግባር ከሃይማኖት ጋር ይሠራል)፣ የኤልፍና የሌሚ ወገን ይነሣል፡፡ ገብርኤል ሆይ! ሄደህ ለዳዊት ልጅ ‹እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ነውና ደስ ይበልሽ› ብለህ አብሥራት› አለው፡፡ ‹ለዘለዓለም ነግሦ የሚኖረውን እነሆ ትፀንሳለሽ በላት› አለው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ይህን ሰምቶ ሰገደ፡፡ ልብሱንም በላዩ ይዞ በመስቀል ቀኝ ይወርድ ዘንድ ወደደ፡፡ ጌታም ‹መግባትህና መውጣትህ በፍቅር አንድነት ይሁን› አለው፡፡ ‹ዘካርያስን ረግመህ አንደበቱን እንዳሰርህ እርሷን እንዳታሳዝናት ይልቁንም አብዝተህ ደስ አሰኛት አንጂ› አለው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ይህን ሰምቶ ፈጽሞ ደስ እያለው ሊባኖስ ከሚባል ተራራ እስኪሰማ ድረስ ክንፉን እያማታ ወረደ፡፡ በዚህም ጊዜ በዙሪያው ያሉ ሁሉ ‹ይህ የምንሰማው ምንድነው?› ይሉ ነበር፡፡ የተደረገበትንም ቦታ አላወቁትም ነበር፡፡››
እመቤታችንን በ3 ዓመቷ እናትና አባቷ ብፅዓት አድርገው ለእግዚአብሔር ሰጥተዋታልና ካህናትም በቤተ መቅደስ ከመካነ ደናግል አስገብተዋት በመልአኩ በቅዱስ ፋኑኤል አማካኝነት ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ሰማያዊ እየመጣላት ያንን እየተመገበች ቅዱሳን መላእክት እየጎበኟት 12 ዓመት ኖራለች፡፡ በ15 ዓመቷ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን ጌታችንን እንደምትወልድ በዚህች ዕለት አብሥሯታል፡፡ በመጀመሪያ እመቤታችን ውኃ ቀድታ ስትመለስ የጠተማ ውሻ እያለከለከ ሲመጣ ብታየው ለፍጥረት ሁሉ የምትራራ ናትና በወርቅ ጫማዋ ለዛ ለተጠማው ውሻ ውኃ ስታጠጣ አብሯት የነበሩ ሴቶች ‹‹ማድጋሽን አጎደልሺው፣ ቀድቼ እሞለዋለሁ እንዳትይ ጉድጓዱ ጥልቅ ነው መቅጃም የለሽም›› አሏት፡፡ ክብርት እመቤታችንም ‹‹ውሃ የሚገኘው ከወደላይ ነው እንጂ ከወደታች ነውን? ፍጥረቱን ያጠጣ ጌታ ይሞላልኛል›› አለቻቸው፡፡ ማድጋዋም በተአምራት ሞልቶ ተገኘ፡፡ ሴቶቹም ዳግመኛ ‹‹በዚህ ዘመን አምላክ ከድንግል ይወለዳል ይላሉ ካንቺ ይሆን?›› እያሉ ሲዘብቱባት ወዲያው ከወደኋላዋ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ‹‹እነሆ ትጸንሻለሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም ዞር ብትል የተናገራትን አጣችው፡፡ በዚህም ጊዜ ‹‹አባቴን አዳምን እናቴን ሔዋንን ያሳተ ጠላት ይሆናል›› ብላ ሄደች፡፡
ዳግመኛም እመቤታችን ከቤት ደርሳ ማድጋዋን ስታስቀምጥ መልአኩ አሁንም በድምፅ ‹‹እነሆ ትጸንሻለሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም ይህን ጊዜ ‹‹ምነው ይህስ ነገር ደጋገመኝ እንዲህ ያለውን ነገር ቤተ መቅደስ ሄደው ሊረዱት ይገባል›› ብላ ወደ ቤተ መቅደስ ሄዳ ወርቅና ሐር እያስማማች ስትፈት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እሁድ ቀን በ3 ሰዓት በገሃድ ተገለጸላትና እጅ እየነሳ እየሰገደ አበሠራት፡፡ ‹‹የዕውነተኛ ንጉሥ እናቱ እመቤታችን ላንቺ ፍቅር አንድነት ይባል›› አላት፡፡ ዳግመኛም ‹‹አንቺ ከሴቶች ይልቅ ተለይተሸ ንዕድ ክብርት ነሽ›› አላት፡፡ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናቸ ክብርት እመቤታችንም የብርሃናዊውን መአልክ የቅዱስ ገብርኤልን ቃል በሰማች ጊዜ ‹‹እንዲህ ያለውን ሰላምታ እንደምን ይቀበሏል! እንዴትስ መቀበል ይቻላል? እንጃ›› አለችው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ‹‹ማርያም ሆይ! መንፈስ ቅዱስ ያድርብሻል፣ ኃይለ ልዑል ወልድም ሥጋሽን ይለብሳልና አይዞሽ አትፍሪ›› አላት፡፡ ዳግመኛም ‹‹ይህ ካንቺ የሚወለደው ጽኑ ከሃሊ ነው፡፡ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ፣ እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፣ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፣ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለላም ይነግሣል፣ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም›› አላት፡፡ እመቤታችንም መልአኩን ‹‹ምድር ያለ ዘር ፍሬን አትሰጥምና እኔ ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል?›› አለችው፡፡ መልአኩም መልሶ ‹‹መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፣ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል። እነሆም ዘመድሽ ኤልሳቤጥ እርሷ ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ፀንሳለች፡፡ ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው፣ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና›› አላት፡፡ ክብርት እመቤታችንም ይህን ጊዜ ‹‹እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ›› አለችው፡፡ መልአኩም ከእርሷ ዘንድ ሄዶ ተሠወረ፡፡ አካላዊ ቃልም በማኅፀኗ አደረ፡፡ በዚያችም ቅጽበት የእመቤታችን የፊቷ መልክ ተለወጠ፣ እንደፀሐይም አሸበረቀ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ገብርኤል
በዚች ቀን የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ገብርኤል የበዓሉ መታሰቢያ ዳህና በሚባል አገርም ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራችበት ተአምራትም ያሳየበትና በዚች ቀን ቤተ ክርስቲያኒቱ የከበረችበት ነው የዚያች አገር ኤጲስቆጶስ አርኬላዎስ ምስክር የሆነበት ነው።
ይህም መልአክ ስለ ወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ምሥጢር የታመነ ሆኖ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተላከ "የደስታ መገኛ ደስ ይበልሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው አንቺም ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ" አላት።
ስለ መጥምቁ ዮሐንስ መወለድም ካህኑን ዘካርያስን ያበሠረው እርሱ ነው ይህ መልአክ እጅግ የከበረ የተመረጠ ገናና የሆነ ነውና ስለ እኛ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ዘንድ ልባችንን አንጽተን ወደዚህ የከበረ መልአክ እየለመንን መታሰቢያውን ልናደርግ ይገባል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ደቅስዮስ
በዚህችም ዕለት ዳግመኛ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናቸ ክብርት እመቤታችንን የከበረ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ባበሠራት መሠረት ቅዱስ ደቅስዮስ በዓልን ያደረገበት እና ቅዱስ ደቅስዮስ ያረፈበት ዕለት ነው፡፡ በዓልን የማክበሩ ምክንያትም እንዲህ ሆነ፡- መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ያበሠራትና የጌታችንም ፅንሰት የተከናወነው በመጋቢት ወር በ29ኛው ቀን በዕለተ እሁድ በ3 ሰዓት ነው፡፡ ታዲያ ምነው በታኅሣሥ 22 ብሥራቱና ፅንሰቱ ተከበረ? ቢሉ መጋቢት 29 ቀን ሰሙነ
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_21
ታኅሣሥ ሃያ አንድ ይህችን ዕለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን #ኖላዊ_ሔር ብላ ታከብራለች፣ #የሐዋርያው_ቅዱስ_በርናባስ ዕረፍቱ ነው::
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ኖላዊ_ሔር
ታኅሣሥ ሃያ አንድ ይህችን ዕለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን "ኖላዊ ሔር" ብላ ታከብራለች:: ይሕንንም ለሳምንት ያህል ታዘክራለች:: መሠረታዊ መነሻዋም (ዮሐ. 10፥1) ነው:: "ኖላዊ" ማለት በቁሙ "እረኛ" ማለት ሲሆን "ሔር" ደግሞ "ቸር፣ርሕሩሕ፣አዛኝ" እንደ ማለት ነው:: ገጥመን ብንተረጉመው ደግሞ "ቸር እረኛ" የሚል ትርጉምን ይሰጠናል:: ከአባታችን አዳም ስህተት በኋላ ተፈጥረው ከነበሩ ችግሮች አንዱ ቸር እረኛ ማጣት ነው። እግዚአብሔር አዳምን ፈጥሮ: ቸር እረኛ ሆኖ በገነት አሰማርቶት ነበር።
ኤዶም ገነት የለመለመች: ፈሳሾች የሞሉባት መልካም መስክ ናትና:: አባታችን ቅዱስ አዳም ደግሞ እንደ አቅሙ የጸጋ እረኝነት ተሰጥቶት ነበር:: ድቀት ካገኘው በሁዋላ ግን ከነፍስ እረኛው ጋር ተጣልቶ ከመልካሟ መስክ ገነት ወጣ:: እርሷንና የነፍሱን እረኛ ሲሻም አለቀሰ:: ተስፋ ድኅነት ሲሰጠውም ለልጆቹ ነገራቸው:: ከዚያም በመንጋው ላይ በአዳም ሴት ተተካ:: ከሴት ኄኖስ፣ ከኄኖስ: ቃይናን . . . እያለ ከኖኅ ደረሰ።
ከኖኅም በሴም ከአብርሃም: ከአብርሃምም በይስሐቅና በያዕቆብ ወርዶ ከሙሴ ደረሰ:: ከሙሴም በኢያሱ አልፎ ከነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ደረሰ:: እነዚህ ሁሉ እረኞች ምንም እንኩዋ ለእግዚአብሔር ሕዝብ በትጋት ቢሠሩም ሕዝቡን ከሲዖል ማዳን አልቻሉም:: ከሲዖል የሚያድን የነፍስ እረኛ ነውና ያን ጊዜ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት የራሱን: የአባቶቹንና የልጆቹን ጩኸት ባንድ አድርጐ ጮኸላቸው:: "ኖላዊሆሙ ለእሥራኤል አጽምዕ - የእሥራኤል እረኛ ሆይ ስማን!" አለ:: (መዝ. 79:1)
ጩኸቱም ቅድመ እግዚአብሔር ደረሰ:: ይህንን የሰማ ጌታም በጊዜው ከድንግል ማርያም ተወለደ:: በየጥቂቱ አድጐ ቸር እረኝነቱን ገለጠ:: መድኃኒታችን እንዳስተማረን እርሱ ቸር እረኛ ነው:: ከእርሱ በፊት የተነሱት ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ (ሐዋ. 5:36, ዮሐ. 10:8) ሐሰተኛ እረኞች ነበሩ:: እርሱ ግን እውነተኛው የበጐች በር ነውና (ዮሐ. 10:7) በእርሱ የሚገቡ ሁሉ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛሉ:: እርሱ እውነተኛ እረኛ ነውና (ዮሐ. 10:11) ለመንጋው ራሱን አሳልፎ ይሰጣል:: በእሥራኤል ባሕል እረኞች ከፊት: መንጋው (በጐቹ) ከሁዋላ ሆነው ይሔዳሉና ገዳይ ቢመጣ መጀመሪያ የሚገድለው እረኛውን ነው::
መድኃኒታችን ክርስቶስ በሞቱ ሕይወትን: በመራቆቱ የጸጋ ልብስን: በውርደቱ ክብርን: በድካሙ ኃይልን ይሰጠን ዘንድ ስለ እኛ ራሱን አሳልፎ ሰጠ:: የማይሞት ንጉሥ ስለ መንጋው ሞተ:: ሰማይን ከነግሡ ምድርንም ከነልብሱ የፈጠረ ጌታ (ዘፍ. 1:1, ዮሐ. 1:2) ስለ በጐቹ ይህንን ሁሉ ታግሦ ከሲዖል አዳነን:: በሚያርግ ጊዜም በእርሱ ፈንታ ባለ ሙሉ ስልጣን እረኞችን: ሐዋርያትን (ዮሐ. 21:15) ሊቃነ ዻዻሳትን (ሐዋ. 20:28) ካህናትን (ማቴ. 18:18) ሾመልን:: እነርሱን እረኞች አሰኝቶ እርሱ "ሊቀ ኖሎት-የእረኞች አለቃ" ተባለ:: እነርሱም እስከ ዓለም ፍጻም የክርስቶስን መንጋ ሊጠብቁ ስልጣኑም ኃላፊነቱም አለባቸው:: (ማቴ. 28:19)
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_በርባስ
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ሐዋርያው ቅዱስ በርናባስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ሐዋርያ ከሊዊ ነገድ የሆነ አገሩ ቆጵሮስ ነው የቀድሞ ስሙ ዮሴፍ ነው ክብር ይግባውና ጌታችን ከመከራው በፊት ይሰብኩ ዘንድ ከላካቸው ከሰባ ሁለት አርድእት ጋር መረጠው ስሙንም በርናባስ ብሎ ጠራው። ከጌታ ዕርገትም በኋላ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ እርሱም ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ተቀብሎ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተማረ። የእርሻ ቦታ ነበረውና ሽጦ ዋጋውን አምጥቶ ከሐዋርያት እግር በታች አኖረው።
ቅዱስ ጳውሎስም በጌታችን አምኖ ወደ ሐዋርያት በመጣ ጊዜ ክብር ይግባውና ለክርስቶስ እርሱ ደቀ መዝሙሩ እንደሆነ ሐዋርያት አላመኑትም ነበር። ይህ በርናባስ ጌታችን በመንገድ እንደ ተገለጸለትና እንደአነጋገረው እርሱም በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በደማስቆ እንደ አስተማረ ነገራቸው። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔርን ሥራ ሲሠሩ ሲጾሙ ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ "ሳውልና በርናባስን እኔ እነርሱን ለመረጥኩት ሥራ ለዩልኝ" አላቸው።
ከዚህም በኋላ ጹመው ጸልየው እጆቻቸውን በራሳቸው ላይ ጭነው ሾሟቸው። ከመንፈስ ቅዱስም ተሹመው ወደ ሴሌውቅያ ወረዱ ከዚያም ወደ ቆጵሮስ ሔዱ የእግዚአብሔርንም ቃል በአገሩ ሁሉ አስተማሩ። ልስጥራን በተባለ አገርም ልምሾ የነበረውን ሰው በአዳኑት ጊዜ የልስጥራን ሰዎች መሥዋዕትን ሊሠዉላቸው ወደዱ። ሐዋርያት ቅዱስ ጳውሎስና በርናባስም በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀድው ወደ ሕዝቡ ሔዱ ድምፃቸውንም ከፍ አድርገው እንዲህ አሏቸው "እናንት ሰዎች ይህ ነገር ምንድን ነው እኛማ እንደናንተ የምንሞት ሰዎች አይደለንምን ይህን ከንቱ ነገር ትታችሁ ሰማይና ምድርን ባሕርንም በውስጣቸው ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወደሕያው እግዚአብሔር ትመለሱ ዘንድ እናስተምራችኋለን" አሏቸው እንዲህም ብለው መሠዋትን በጭንቅ አስተዋቸው።
ከዚያም ብዙ አገሮችን ከአስተማሩ በኋላ ቅዱስ በርናባስ ከቅዱስ ጳውሎስ ተለይቶ ቅዱስ ማርቆስን ይዞ ወደ ቆጵሮስ ሔደ በዚያም አስተማረ ብዙዎችን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን መለሳቸውና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።
በቆጵሮስ አገር የሚኖሩ አይሁድም ቀኑበት በመኳንንትም ዘንድ ወነጀሉት በእግር ብረትም አሥረው ጽኑ ግርፋትን ገረፉት ከዚህም በኋላ በደንጊያ ወገሩት ዳግመኛም ወስደው ከእሳት ጨመሩት ምስክርነቱንም ፈጸመ። ቅዱስ ማርቆስም ከርሱ ጋር አለ ግን እግዚአብሔር ጠብቆ አተረፈው። እርሱም ቅዱስ በርናባስን ከእሳት ውስጥ አወጣው ሥጋውንም እሳት ከቶ አልነካውም በአማሩ ልብሶችም ገንዘውና ተሸክሞ ወስዶ ከቆጵሮስ ከተማ ውጭ በዋሻ ውስጥ አኖረው።
የመድኃኔዓለም ቸርነቱ የድንግል እናቱ ምልጃዋ ከእኛ ጋር ይሁን፤ በሐዋርያ ቅዱስ በርናባስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12
የሐዘን መግለጫ
የሰንበት ት/ቤት አባላችን የሆነችው ለተእግዚ አረፋዓይኔ አክስት ስላረፉ ቀብር ዛሬ ታሕሳስ 20/2014 ዓ.ም ከቀኑ 8 ሰዓት ላይ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤ/ክ ቀብር ሥርዓታቸው ስለሚፈፀም ሁላችንም በተጠቀሰው ቦታ ላይ እንድንገኝ ስንል እናሳስባለን፡፡
ነፍሳቸውን በቅዱሳኑ ጎን ያሳርፍልን
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_20
#ቅዱስ_ሐጌ_ነቢዩ
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ታኅሣሥ ሃያ በዚህች ዕለት ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ፣ ከሌዊ ነገድ ከአሮን ትውልድ የሆነው ቅዱስ ሐጌ ዐረፈ። እርሱም ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ነው። ናቡከደነጾርም የኢየሩሳሌምን ሕዝብ በማረከ ጊዜ የዚህ ጻድቅ ነቢይ ወላጆች ከእስራኤል ልጆች ጋር ወደ ባቢሎን አገር ተማርከው ሔዱ ዳርዮስ የተባለውም ኵርዝ በነገሠ ጊዜ በሁለተኛው ዘመነ መንግሥቱ ይህ ነቢይ ትንቢት ተናገረ።
የእስራኤልን ልጆች ወደ አገራቸው ይገቡ ዘንድ ኵርዝ ዳርዮስ በአሰናበታቸው ጊዜ እነርሱም ከገቡ በኋላ ቤተ መቅደስን ከመሥራት ቸለል በአሉ ጊዜ እነርሱ ግን በአማሩና በተሸለመ ቤቶች ውስጥ ይኖሩ ነበርና እንዲህ አላቸው። "ሁሉን የሚገዛ እግዚአብሔር እንዲህ አለ የኔ ቤት ፈርሷል እናንተ ግን ሁላችሁም ቤታችሁን ታጸናላችሁ" አላቸው። "ስለዚህ ከምድር በላይ ያለች ሰማይ ዝናም ለዘር ትነሣለች ምድርም ፍሬዋን አትሰጥም" አላቸው።
ከሕዝቡም ደናጎቻቸው ሰምተው እጅግ ፈሩ የእግዚአብሔርንም መመስገኛ ቤት እንደሚገባ መሥራት ጀመሩ። ይህም ጻድቅ ነቢይ ሰባ ዓመት ያህል ኖረ የትንቢቱም ወራት ክብር ይግባውና ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት በአራት መቶ ሠላሳ ዓመት ነው። ከዚህ በኋላም በሰላም በፍቅር ታኅሣሥ 20 ቀን ዐረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ ቅዱስ ሐጌ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የሐዘን መግለጫ
የሰንበት ት/ቤታችን አባል የሆነው የወንድማችን ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አያት ስላረፉ ነገ በ20/04/15 በ9:00 ቀጨኔ መድሐኔዓለም ቀብር ስለሆነ ቀብር እና ማጽናናት ላይ እንድንገኝ እናሳስባለን።
አቡነ ስነ ኢየሱስ የትውልድ ሀገራቸው ሰሜን ሸዋ ደብረ ብርሃን ልዩ ቦታው ልብሆ ይባላል። ከሽዋ ምድር ተነሥተው ወደ ታች አርማጭሆ በመሄድ በበረሃ ውስጥ በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡ በቅዱስ ገብርኤል መሪነት በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ ሰሜን ጎንደር አርማጭሆ በመሄድ የወርቅ ለብሆ ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ የተባለው ገዳም እንደገና አቅንተው በጽኑዕ ተጋድሎ ለብዙ ጊዜ ኖረዋል። ገዳማቸው ታች አርማጭሆ ከሳንጃ ከተማ የ3 ሰዓት መንገድ ይወስዳል።
መልአከ ሞትን ገዝተው ያቆሙት ጻድቁ ለ300 ዓመት በአንዲት ዐለት ላይ ቆመው ጸልየዋል። አቡነ ስነ ኢየሱስ ብዙ መናንያን አርድእትን ያፈሩ ታላቅ አባት ሲሆኑ በደመና እየተጫኑ ከመጓዝ ጀምሮ በርካታ አስገራሚ ተአምራትን በማድረግም ይታወቃሉ፡፡ ጻድቁ "የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብር አይሆንም" ብለው መልአከ ሞትን ለ3 ወራት ከበራቸው ላይ ካቆሙትና በዓሉን ካከበሩ በኃላ ታኅሣሥ 19 ቀን በሰላም ዐርፈዋል፡፡
በእርሳቸውም ግዝት መሠረት መልአከ ሞት ከቆመበት ሳይነቃነቅ ከመስከረም 1 ቀን እስከ ታኅሣሥ 19 ቀን ቆመ። ጻድቁም የቅዱስ ገብርኤልን ዝክር ዘክረው እንደፈጸሙ ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታኅሣሥ 19 ቀን ድንግል እናቱን ቅድስተ ቅዱሳን ንጽሕይት ድንግል ማርያምን፣ እልፍ አእላፍ መላእክትን፣ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን፣ የከበሩ መነኮሳትን አስከትሎ በመምጣት እንዲህ የሚል ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፦ "ቦታህን ሊሳለም የመጣውን ወደ ኢየሩሳሌም እንደሄደ እቆጥርለታለሁ፤ በቦታህ ከወደቀው ፍርፋሪ እንኳን በስምህ የወደቀውን ምግብ ቢመገብ አማናዊውን ሥጋዬን ደሜን እንዲቀበል አደርገዋለሁ፤ የእጀ ሰብዕ ሥራይ የተደረገበት ሰው ከመቃብርህ አፈር አዋሕዶ በውኃ ቢረጨው ሥራዩን እፈታለታለሁ:: በሬም ላምም ቢሆን ቢታመምበት በስምህ ጻድቁ ስነ ኢየሱስ ብሎ ቢማጸን በደልና ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ።" ጻድቁ በዚኽች ዕለት ዐርፈዋል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ዮሐንስ_ዘቡርልስ
ዳግመኛም በዚኽች ዕለት በሚቀድስበት ጊዜ ፊቱ እሳት ሆኖ ይታይ የነበረውና በጸሎቱ እሳት ከሰማይ አውርዶ መናፍቃንን ያቃጥል የነበረው አቡነ ዮሐንስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ይኸውም ቅዱስ ቡርልስ በምትባል አገር ኤጲስቆጶስ የነበረው ነው፡፡ በሕፃንነቱ ወላጆቹ እጅግ የከበሩ ስለነበሩ እነርሱ በሞቱ ጊዜ የወላጆቹን የተትረፈረፈ ንብረት ወስዶ ቤተ ክርስቲያን ሠራበት፡፡ የእንግዳ ማረፊያ ሕመምተኞች የሚያርፉበት ቤትም ሠራበትና በውስጡ ብዙ ነዳያንን አስቀምጦ ይንከባከባቸው ነበር፡፡ ገንዘቡንም ሁሉ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥቶ አባ ዳንኤል ለአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት በነበረበት ወቅት ወደ አስቄጥስ ገዳም ገብቶ በአንድ ዋሻ ውስጥ እየተጋደለ መኖር ጀመረ፡፡ አባ ዳንኤልም አመነኮሱት፡፡ ሰይጣናትም በተጋድሎው ቀንተውበት በብዙ መከራና ሕመማም ፈተኑት፤ ጌታችንም ፈወሰው፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ዮሐንስ ቡርልስ በምትባ አገር ኤጲስቆጶስ ሆኖ ተሾመ፡፡
በዘመኑም በሀገሮች ውስጥ ኑፋቄ የያዙ ሐሰተኞች የበዙ ነበሩ፡፡ ከላይኛው ግብፅ የተነሣ አንድ ሰው ‹‹ቅዱስ ሚካኤል ምሥጢር ይገልጥልኛል›› በማለት ብዙዎችን አሳታቸው፡፡ አባ ዮሐንስም ይህን አሳች ሰው ይዘው እንዲገርፉት አዘዘ፡፡ በተገረፈም ጊዜ ስህተቱን አምኖ ከሀገር አሳደዱት፡፡ ‹‹ነቢይ ዕንባቆም ይታየኛል ብዙ ምሥጢርም ይገልጥልኛል›› የሚል ሌላ ሰውም ተነሥቶ ነበር፡፡ በሐሰት ትምህርቱም ብዙ ተከታዮችን አፈራ፡፡ አባ ዮሐንስ ይህንንም አሳች ገርፈው እንዲያባርሩት አደረገ:: መጻሕፍቶቹንም አቃጠላቸው፡፡ የሳቱትንም በትምህርቱ መለሳቸው፡፡
አባ ዮሐንስ በሚቀድስበት ጊዜ ፊቱ እሳት ይሆናል፡፡ ሥጋውም ከእሳት ምድጃ ውስጥ እንደወጣ ይሆናል፡፡ የመላእክትን ሠራዊት በመሠዊያው ዙሪያ በግልጽ ያያቸዋልና ዕንባውንም እንደ ዝናብ ያዘንባል፡፡ ኅብስቱን በሚፈትት ጊዜ ጽዋውን ሲባርከው እንደፍሕም የጋለ ሆኖ ጽዋውን ያገኘዋል፡፡ በቀን በልተው የሚቆርቡ ክፉ ሰዎች ተነሥተው ሳለ አስተምሮ ሊመልሳቸው ቢሞክር ፈጽመው እምቢ አሉት፡፡ ባልተመለሱም ጊዜ አወገዛቸው፡፡ በዚህም ጊዜ አቡነ ዮሐንስ ወደ ጌታችን ቢጸልይ እሳት ከሰማይ ወርዳ አቃጠለቻቸውና ለብዙዎች መቀጣጫ ሆኑ፡፡ የአባ ዮሐንስ ጊዜ ዕረፍታቸው ሲደርስ እንጦንስንና መቃርስን ጌታችን ልኳቸው መጥተው የቅዱስ ዮሐንስን ዕረፍቱን ነገሩት፡፡ ሕዝቡንም ሰብስቦ በቀናች ሃይማኖት እንዲኖሩ ካስጠነቀቃቸው በኋላ ታኅሣሥ 19 በሰላም ዐረፈ፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን መላእክት፣ በጻድቃን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_19
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ታኅሣሥ ዐስራ ዘጠኝ ቀን በዚህች ዕለት #ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ገብርኤል ሠለስቱ ደቂቅን ከእቶን እሳት ውስጥ ያዳነበት ዕለት ነው፣ መልአከ ሞትን ለሦስት ወራት ከበራቸው ላይ ያቆሙት #አቡነ_ስነ_ኢየሱስ ዕረፍታቸው ነው፣#አቡነ_ዮሐንስ_ዘቡርልስ ዕረፍታቸው ነው፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ገብርኤል
ታኅሣሥ ዐስራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ሠለስቱ ደቂቅን ያዳነበት ነው፡፡ ንጉሥ ናቡከደነፆር ከአባታቸው ከይሁዳው ንጉሥ ከኢዮአቄም ጋር የማረካቸው አናንያ፣ ሚሳኤልና አዛርያ እግዚአብሔር በዚህች ዕለት መልአኩን ልኮ ታላቅ ተአምር አድርጎላቸዋል፡፡ ንጉሥ ናቡከደነፆር እነዚህን ወጣቶች በቤተ መንግሥቱ ውስጥ ጥበብን እያስተማረ ካሳደጋቸው በኋላ በባቢሎን ሀገሮች ሁሉ ውስጥ ሾማቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ንጉሡ የወርቅ ምስል በሠራ ጊዜ መኳንንቱንና በግዛቱ ውስጥ ያሉ ሁሉ ለዚያ ምስል እንዲሰግዱ አዘዘ፡፡ በዚህም ጊዜ ለጣዖቱ ባለመስገድ እግዚአብሔርን ብቻ በማምለክ የጸኑት እነዚህ ሦስት ወጣቶች ብቻ ነበሩ፡፡ ስለ እነርሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዲህ ተብሎ ነው የተጻፈው፡-
‹‹ንጉሡ ናቡከደነፆር ቁመቱ ስድሳ ክንድ ወርዱም ስድስት ክንድ የሆነውን የወርቁን ምስል አሠራ፤ በባቢሎንም አውራጃ በዱራ ሜዳ አቆመው፡፡ ንጉሡም ናቡከደነፆር መኳንንትንና ሹማምቶችን፥ አዛዦችንና አዛውንቶችን፥ በጅሮንዶችንና አማካሪዎችን፣ መጋቢዎችንም፣ አውራጃ ገዦችንም ሁሉ ይሰበስቡ ዘንድ፣ ንጉሡም ናቡከደነፆር ላቆመው ምስል ምረቃ ይመጡ ዘንድ ላከ፡፡ በዚያን ጊዜም መኳንንቱና ሹማምቶቹ፣ አዛዦቹና አዛውንቶቹ፣ በጅሮንዶቹና አማካሪዎቹ፣ መጋቢዎቹና አውራጃ ገዦቹ ሁሉ ንጉሡ ናቡከደነፆር ላቆመው ምስል ምረቃ ተሰበሰቡ፤ ናቡከደነፆርም ባቆመው ምስል ፊት ቆሙ፡፡ አዋጅ ነጋሪውም እየጮኸ እንዲህ አለ፡- ‹ወገኖችና አሕዛብ በልዩ ልዩ ቋንቋም የምትናገሩ ሆይ! የመለከትንና የእንቢልታን፣ የመሰንቆንና የክራርን፣ የበገናንና የዋሽንትን፣ የዘፈንንም ሁሉ ድምፅ በሰማችሁ ጊዜ፣ ተደፍታችሁ ንጉሡ ናቡከደነፆር ላቆመው ለወርቁ ምስል እንድትሰግዱ ታዝዛችኋል፡፡ ተደፍቶም የማይሰግድ በዚያን ጊዜ በሚነድድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣላል፡፡› ስለዚህ በዚያን ጊዜ አሕዛብ ሁሉ የመለከቱንና የእንቢልታውን፣ የመሰንቆውንና የክራሩን፣ የበገናውንና የዘፈኑንም ሁሉ ድምፅ በሰሙ ጊዜ፣ ወገኖችና አሕዛብ በልዩ ልዩ ቋንቋም የተናገሩ ሁሉ ተደፉ፤ ንጉሡም ናቡከደነፆር ላቆመው ለወርቅ ምስል ሰገዱ፡፡
በዚያን ጊዜም ከለዳውያን ቀርበው አይሁድን ከሰሱ፡፡ ለንጉሡም ለናቡከደነፆር ተናገሩ እንዲህም አሉ ‹ንጉሥ ሆይ! ሺህ ዓመት ንገሥ፡፡ አንተ ንጉሥ ሆይ የመለከትንና የእንቢልታን፣ የመሰንቆንና የክራርን፣ የበገናንና የዋሽንትን፣ የዘፈንንም ሁሉ ድምፅ የሚሰማ ሰው ሁሉ ተደፍቶ ለወርቁ ምስል ይስገድ፤ ተደፍቶም የማይሰግድ በሚነድድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣላል ብለህ አዘዝህ፡፡ በባቢሎን አውራጃ ሥራ ላይ የሾምሃቸው ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም የሚባሉ አይሁድ አሉ፤ ንጉሥ ሆይ! እነዚህ ሰዎች ትእዛዝህን እንቢ ብለዋል፤ አማልክትህን አያመልኩም፥ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል አይሰግዱም፡፡› ናቡከደነፆርም በብስጭትና በቍጣ ሲድራቅንና ሚሳቅን አብደናጎንም ያመጡ ዘንድ አዘዘ፤ እነዚህንም ሰዎች ወደ ንጉሡ ፊት አመጡአቸው፡፡ ናቡከደነፆርም ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም ሆይ! አምላኬን አለማምለካችሁ ላቆምሁትም ለወርቁ ምስል አለመስገዳችሁ እውነት ነውን? አሁንም የመለከቱንና የእንቢልታውን የመሰንቆውንና የክራሩን የበገናውንና የዋሽንቱን የዘፈኑንም ሁሉ ድምፅ በሰማችሁ ጊዜ ተደፍታችሁ ላሠራሁት ምስል ብትሰግዱ መልካም ነው፤ ባትሰግዱ ግን በዚያ ጊዜ በሚነድድ እሳት እቶን ውስጥ ትጣላላችሁ፤ ከእጄስ የሚያድናችሁ አምላክ ማን ነው?›› ብሎ ተናገራቸው፡፡ ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም መለሱ ንጉሡን ‹ናቡከደነፆር ሆይ! በዚህ ነገር እንመልስልህ ዘንድ አስፈላጊያችን አይደለም፡፡ የምናመልከው አምላካችን ከሚነድደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፡፡ ነገር ግን ንጉሥ ሆይ! እርሱ ባያድነን አማልክትህን እንዳናመልክ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድለት እወቅ› አሉት፡፡
የዚያን ጊዜም ናቡከደነፆር በሲድራቅና በሚሳቅ በአብደናጎም ላይ ቍጣ ሞላበት፡፡ የፊቱም መልክ ተለወጠባቸው፡፡ እርሱም ተናገረ የእቶንም እሳት ይነድድ ከነበረው ይልቅ ሰባት እጥፍ አድርገው እንዲያነድዱት አዘዘ፡፡ ሲድራቅንና ሚሳቅንም አብደናጎንም ያስሩ ዘንድ ወደሚነድድም ወደ እቶን እሳት ይጥሉአቸው ዘንድ በሠራዊቱ ውስጥ ከነበሩት ኃያላን አዘዘ፡፡ የዚያን ጊዜም እነዚህ ሰዎች ከሰናፊላቸውና ከቀሚሳቸው ከመጐናጸፊያቸውም ከቀረውም ልብሳቸው ጋር ታስረው በሚነድድ በእቶን እሳት ውስጥ ተጣሉ፡፡ የንጉሡም ትእዛዝ አስቸኳይ ስለሆነ የእቶኑም እሳት እጅግ ስለሚነድድ፣ ሲድራቅንና ሚሳቅን አብደናጎንም የጣሉአቸውን ሰዎች የእሳቱ ወላፈን ገደላቸው፡፡ እነዚህም ሦስቱ ሰዎች ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም ታስረው በሚነድደው በእቶኑ እሳት ውስጥ ወደቁ፡፡ የዚያን ጊዜም ንጉሡ ናቡከደነፆር ተደነቀ ፈጥኖም ተነሣ፤ አማካሪዎቹንም ‹ሦስት ሰዎች አስረን በእሳት ውስጥ ጥለን አልነበረምን?› ብሎ ተናገራቸው፡፡ እነርሱም ‹ንጉሥ ሆይ! እውነት ነው› ብለው ለንጉሡ መለሱለት፡፡ እርሱም ‹እነሆ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎች አያለሁ፤ ምንም አላቈሰላቸውም፤ የአራተኛውም መልክ የአማልክትን ልጅ ይመስላል› ብሎ መለሰ፡፡ የዚያን ጊዜም ናቡከደነፆር ወደሚነድደው ወደ እሳቱ እቶን በር ቀርቦ ‹እናንተ የልዑል አምላክ ባሪያዎች ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም! ኑ ውጡ› ብሎ ተናገራቸው፡፡ ሲድራቅና ሚሳቅም አብደናጎም ከእሳቱ መካከል ወጡ፡፡
መሳፍንቱና ሹማምቶቹም አዛዦቹና የንጉሡ አማካሪዎች ተሰብስበው እሳቱ በእነዚያ ሰዎች አካል ላይ ኃይል እንዳልነበረው፣ የራሳቸውም ጠጕር እንዳልተቃጠለች ሰናፊላቸውም እንዳልተለወጠ፣ የእሳቱም ሽታ እንዳልደረሰባቸው አዩ፡፡ ናቡከደነፆርም መልሶ ‹መልአኩን የላከ ከአምላካቸውም በቀር ማንም አምላክ እንዳያመልኩ ለእርሱም እንዳይሰግዱ ሰውነታቸውን አሳልፈው የሰጡትን የንጉሡንም ቃል የተላለፉትን በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ፣ የሲድራቅና የሚሳቅ የአብደናጎም አምላክ ይባረክ፡፡ እኔም እንደዚህ የሚያድን ሌላ አምላክ የለምና በሲድራቅና በሚሳቅ በአብደናጎም አምላክ ላይ የስድብን ነገር የሚናገር ወገንና ሕዝብ በልዩ ልዩም ቋንቋ የሚናገሩ ይቈረጣሉ፣ ቤቶቻቸውም የጕድፍ መጣያ ይደረጋሉ ብዬ አዝዣለሁ› አለ፡፡ የዚያን ጊዜም ንጉሡ ሲድራቅንና ሚሳቅን አብደናጎንም በባቢሎን አውራጃ ውስጥ ከፍ ከፍ አደረጋቸው፡፡›› ትንቢተ ዳንኤል 3፡1-30፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_አቡነ_ስነ_ኢየሱስ
በዚኽች ዕለትም መልአከ ሞት መስከረም 19 ቀን መጥቶ "ጊዜ ዕረፍትህ ደርሷል" ቢላቸው "የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብር አይሆንም" ብለው መልአከ ሞትን ለ3 ወራት ከበራቸው ላይ ገዝተው ያቆሙት ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ስነ ኢየሱስ ዕረፍታቸው ነው።
የሐዘን መግለጫ
የሰንበት ት/ቤታችን አባል የሆነው ናትናኤል ቴዎድሮስ አያት ስላረፉ ጎላ ሰፈር በተለምዶ ዬፎ የተባለው ሰፈር በመገኘት ማጽናናት ላይ እንድንገኝ እናሳስባለን !!!
የሐዘን መግለጫ
የአባላችን ናትናኤል ቴዮድሮስ አያት ሰላረፋ ጎላ በተለምዶ ዬፎ የተባለው ሰፈር በመገኘት ማጽናናት ላይ እንድንገኝ እናሳስባለን !!!
ዛሬም ድረስ ሕንድ ውስጥ በመንበሩ ላይ የቅዱስ ቶማስ ቀኝ እጁ በሕይወት እንዳለች ሆና ትታያለች፡፡ መለኮትን (የጌታችንን የተወጋ ጎኑን) የዳሰሰች ቅድስት እጅ ናትና ዛሬም ድረስ ሕያው ናት፡፡ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ፓትርያርክ ሲሾሙም የቅዱስ ቶማስን ቀኝ እጅ በሚሾመው ፓትርያርክ ላይ ጭነው ነው፡፡ አንድ ወቅት አንድ ሰው ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ገብቶ የቅዱስ ቶማስ ቀኝ እጅ እጨብጣለሁ ብሎ እጁን ቢዘረጋ የቶማስ እጅ ተሰወረችባቸው፡፡ እንደገና ብዙ እግዚኦታና ኪሪያላይሶን ካደረሱ በኋላ የቅዱስ ቶማስ እጅ በቦታዋ ተመልሳላቸዋለች፡፡
ይህች ዕለት የሥጋው ፍልሰት መታሰቢያ እንድትሆን አባቶች ሥርዓት ሠሩልን፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ቲቶ
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የሐዋርያው የቅዱስ ቲቶ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ቀርጤስ ከሚባል አገር ሲሆን ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጇ ነው፡፡ ሐዋርያው ከታናሽነቱ ጀምሮ የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ፡፡ በጠባዩም ቅን፣ ሥራው ያማረ፣ ለድኆችና ጦም አዳሪዎች መራራት የሚወድ ነው፡፡
ከዕለታትም በአንዲቱ ዕለት ‹‹ቲቶ ሆይ ስለነፍስህ ድኅነት ተጋደል፣ ይህ ዓለም አይጠቅምምና›› የሚለውን በራእይ ተመለከተ፡፡ ምን እንደሚሠራም አላወቀምና ከእንቅልፉ በነቃ ጊዜ ደነገጠ፡፡ ከዚህም በኋላ የጌታችንን ተአምራት እያነሡ ሰዎች ሲነጋገሩ የአክራጥስ መኮንን ሰማ፡፡ መኮንኑም የሰማውቸው የጌታችን ተአምራቶች እውነት መሆናቸውን ወይም የሥራይ ሥራ እንደሆነ ያረጋግጥ ዘንድ የሚልከውን ብልህና አዋቂ ሰው ፈለገ፡፡ ከእርሱ የሚሻል አዋቂ የለምና መኮንኑ የእኅቱን ልጅ ቲቶን መርጦ ስለ ጌታችን ተአምራቶች ጥልቅ ምርምር ያደርግለት ዘንድ አዘዘው፡፡ ቅዱስ ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ድንቅ ድንቅ ተአምራት በዐይኑ ተመለከተ፡፡ ትምህቶቹንም ሰማና የጌታንን ትምህርቶች ከዮናናውያን ትምህርትና ፍልስፍና ጋር አነጻጸረ፡፡ የዮናናውያንም ትምህርት የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ቲቶ በጌታችን አመነ፣ ደቀ መዝሙሩም ሆኖ ተከተከለው፡፡
ቅዱስ ቲቶ ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥው መልአክትና ላከና ጌታችን የሚያደርጋቸው ተአምራቶችና የሚያስተምራቸው ትምህርቶች እውነት እንደሆኑ ነገረው፡፡ ጌታችንም ቅዱስ ቲቶን ቁጥሩን ከ72ቱ አርድእት ወገን አደረገው፡፡ ቅዱስ ቲቶም ከጌታችን ዕርገት በኋላ ከከበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ በሀገሮች ሁሉ ዞሮ የከበረች ወንጌልን አስተማረ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በጌታችን ተጠርቶ ወንጌልን መስበክ ሲጀምር ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን ተከትሎት በብዙ አገሮች ወንጌልን ሰበከ፡፡ የከበረ ቅዱስ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ሰማዕት ከሆነ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ፡፡ በዚያም ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው፡፡ በዙሪያቸው ባሉ ሀገሮችም እንዲሁ አደረገ፡፡ በመጨረሻም ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ሄደ፡፡
ጻድቁ ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ከ470,000 በላይ ክርስቲያኖችን በግፍ የገደለውን የሃዲውን ንጉሥ የዲዮቅልጥያኖስን መንግሥት ካጠፋ በኋላ የታሰሩትን ቅዱሳን አስፈትቶ በሚገዛቸው አገሮች ሁሉ አብያተ ክርስቲያናትን አሳነጸ፡፡ ይልቁንም ቁስጥንጥንያ መናገሻ ከተማው ናትና ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን ካሳነጸባት በኋላ የቅዱሳን ሐዋርያን እና የቅዱሳን ሰማዕታትን ሥጋቸውን ከየቦታው እየሰበሰበ በክብር በማምጣት በውስጣቸው አኖረ፡፡ የሐዋርያውም የቅዱስ ቲቶ ሥጋ አቅራጥስ በሚባል አገር መኖሩን ሲሰማ የካህናት አለቆችን ከብዙ ገንዘብና ሠራዊት ጋር ልኮ ወደ ቁስጥንጥንያ በክብር አስመጣው፡፡
ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ የቅዱስ ቲቶ ሥጋ አቅራጥስ በሚባል አገር አፍልሶ ወደ ቁስጥንጥንያ ከተማ በክብር ካስመጣው በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶለት የቅዱስ ቲቶን ሥጋ በውስጧ በክብር አኖረ፡፡ ከሥጋውም ብዙ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡ ይኸውም የሆነው ታኅሣሥ 18 ቀን ነው፡፡ የቅዱሱን ሥጋ ከከበረ እምነበረድ በተሠራው ሣጥን ውስጥ አድርገው ተሸክመው ሲወስዱ ከሰው ግፊያ የተነሣ ሣጥኑ ወድቆ የአንዱን ሰው እግር ሰበረው፡፡ እርሱም የቅዱስ ቲቶ ሥዕል ካለበት የመብራት ቅባት ላይ ወስዶ የተሰበረ እግሩን ቀባውና ሲያመው እየጮኸ አሰረው፡፡ ወደ ቤቱም መሄድ ባልቻለ ጊዜ የቅዱስ ቲቶ ሥጋ ሣጥን ባለበት በዚያው አደረ፡፡ በማግሥቱም አይቶ መድኃኒት ሊያደርግ ተሰብሮ የታሰረ እግሩን በፈታው ጊዜ ከቶ ምንም ምን ሕማም እንዳላገኘው ደህና ሆነ፡፡ ለምልክት ይሆን ዘንድ ግን ደም ነበረበት፡፡ ሰውየውም ተነሥቶ እየሮጠ በመሄድ የተደረገለትን ተአምር ለሰው ሁሉ ተናገረ፡፡ ያዩትም ሁሉ የቅዱስ ቲቶን አምላክ ልዑል እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_18
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ታኅሣሥ ዐስራ ስምንት በዚህች ቀን #አቡነ_ሰላማ_ከሣቴ_ብርሃን ጵጵስና የተሾሙበት ዕለት ነው፣ #የሐዋርያው_ቅዱስ_ቶማስ እና የቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙር የሆነው #የቅዱስ_ቲቶ የሥጋቸው ፍልሰት ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ሰላማ_ከሣቴ_ብርሃን
ታኅሣሥ ዐስራ ስምንት በዚህቸ ቀን #አቡነ_ሰላማ_ከሣቴ_ብርሃን ጵጵስና የተሾሙበት ዕለት ነው፡፡ ቅዱስ አባታችን አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በኋላ በ245 ዓ.ም በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ህዳር 26 ቀን ሲወለዱ ታላቅ ብርሃን ከሰማይ ወርዶ ለ7 ቀናት አብርቷል፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ወደ ምድር ወርደው በመወለዳቸው ታላቅ ደስታን አድርገዋል፡፡ በተወለዱም ጊዜ ‹‹ለአብ ስግደት ለወልድ ስግደት ለመንፈስ ቅዱስ ስግደት ይገባል፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጡኝ ቅድመ ዓለም ለነበሩ ዛሬም ላሉ ዓለምን አሳልፈው ለሚኖሩ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል ብለው ዳግመኛም አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ብለው ፈጣሪያቸውን በአንድነት በሦስትነት አመስግነዋል፡፡
ቅዱስ አባታችን በሌላኛው ስማቸው ፍሬምናጦስ እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ በ40 ቀናቸው ጌታ በተጠመቀበት በዮርዳኖስ ያጠመቋቸውና ስመ ክርስትና የሰጧቸው ሊቀ ጳጳስ ‹‹ይህ ሕፃን ለኢትዮጵያውን ሁሉ ብርሃን ይሆንላቸዋል›› በማለት ትንቢት ተናግረዋል፡፡ በሊቀ ጳጳሱ በቅዱስ አትናቴዎስ በሚገባ ተምረው ካደጉ በኋላ በ257 ዓ.ም ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ ስሙ ሜርጵዮስ ከሚባል ከአንድ ነጋዴ ጋር መጡ፡፡ ከእነሱም ጋር አድስዮስ የሚባል ልጅ ነበር፡፡ ወደ ሀገራችንም ሊመጡ የቻሉት እንዴት ነው? ቢሉ መጀመሪያ ለሰባት ወር በአንድ ሌላ አገር ኖረው ወደ ኢየሩሳሌም ሊመለሱ ሲሉ የበረሃ ሽፍቶች ሜርጵዮስንና ሌሎች መንገደኞችን ገደሏቸውና ሁለቱን ልጆች ማርከው ወስደው ስሙ አልአሜዳ ለሚባል ለአክሱም ንጉሥ ሰጡት፡፡ እርሱም አድስዮስን የቤተክርስቲያን የአልባሳትና የዕቃ ቤት ጠባቂ አድርጎ ሲሾመው ፍሬምናጦስን ደግሞ የቤተክርስቲያንና የሕግ ጠባቂ አደረገው የቤተክርስቲያንን ሥርዓቷንና አገልግሎቷን ጠንቅቆ ያውቅ ነበርና፡፡
በአክሱምም በተጋድሎና በትጋት ኖረ፡፡ ቅዳሜና እሁድ የዛፍ ቅጠሎችን ከመመገብ በቀር ሌላ ምግብ አይቀምስም ነበር፡፡ በየቀኑም አምስት ሺህ ስግደትን ይሰግድ ነበር፡፡ በእርሱም የተጋድሎ ዘመን ደጋግ የሆኑ ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ ነገሡ፡፡ እነርሱም ሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍሬምናጦስን በጣም ይወዱት ነበር፡፡ አንድ ቀን ፍሬምናጦስ የአክሱሙን ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ሚናስን ‹‹ግዝረትና እምነት በእናንተ ዘንድ አለ ነገር ግን ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ መቀበል በእናንተ ዘንድ የለም›› አለው፡፡ ቅዱስ ሚናስም ‹‹ግዝረትንስ አባቶቻችን ሌዋውያን አመጡ፣ በክርስቶስ ማመንን ሕንኬ የተባለች የኢትዮጵያ ንግሥት ጃንደረባ አመጣልን፡፡ ስለ ጥምቀትና ሥጋ ወደሙ ሐዋርያ ወደ እኛ አልተላከም ነገር ግን ያልከውን ሁሉ የሚያደርግልን የሚባርከንና የሚቀድሰን ጳጳስን ታመጣልን ዘንድ ሊቀ ጳጳሱ ወዳለበት ወደ እስክንድሪያ አገር አንተ ሂድ›› አለው፡፡ ጥምቀትስ በጃንደረባው በኩል አገራችን ገብቶ ነበር ነገር ግን ገና ስላልተጠናከና ብዙ ሕዝብም አልተጠመቀም ነበርና አባታችን ፍሬምናጦስ አጠናክሮ ያልተጠመቀውን ሁሉ አጥምቆአል፡፡
ፍሬምናጦስም ወደ እስክንድሪያ ለመሄድ አስቦ ሳለ እንደተኛ ድንግል ማርያም ተገልጣለት ‹‹ዲቁናና ቅስናን መቀበል ይገባሃል፣ ለጵጵስና ተዘጋጅ፣ እግዚአብሔር ይህችን ከፍ ያለችውን ማዕረግ ሰጥተሃልና የልጄ ወዳጅ ሆይ በጸሎትህና በልመናህ በስብከትህም የኢትዮጵያ ሰዎች ሁሉ ይድናሉ፣ በእጅህ ጥምቀትንና ሥጋ ወደሙን ይቀበላሉ›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ወደ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አትናቴዎስ ሄደህ ከፍ ያችውን ማዕረግ ተቀብለህ የኢትዮጵያን ሰዎች አጥምቅልኝ፣ ነቢዩ ዳዊት ስለ እነርሱ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ብሎ ተናግሯልና›› አለው፡፡ እርሱም ቅዱሳኑን ነገሥታት አብርሃንና አጽብሓን አግኝቶ ከእነርሱም ጋር ተማክሮ ወደ እስክንድሪያ ሄዶ በቅዱስ አትናቴዎስ እጅ በአገራችን ላይ የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ታኅሳስ 18 ቀን ተሾመ፡፡ ስሙንም ሰላማ ከሣቴ ብርሃን አለው፡፡ ሰላማ ማለት እግዚአብሔርንና ሰውን የሚያስታርቅ ማለት ነው፡፡ ከሣቴ ብርሃን ማለትም ሃይማኖትን ገልጦ የሚያስተምር ማለት ነው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስም ከሾመው በኋላ ታቦትና በጣም ብዙ ንዋያተ ቅድሳትንና መገልገያ ዕቃዎችን ሰጥቶ መርቆ በሰላም ወደ ኢትዮጵያ ላከው፡፡ ይህች ዕለት አባታቸን በ330 ዓ.ም በሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እጅ ጵጵስና የተሾሙባት ዕለት ናት፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ቶማስ
በዚህች ዕለት የሐዋርያው የቅዱስ ቶማስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፡፡ ቶማስ ማለት ፀሐይ ማለት ሲሆን ቀዳሚ ስሙ ‘ዲዲሞስ’ ነው ‘ዲዲሞስ’ ማለት ጨለማ ማለት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ከ12 ሐዋርያት አንዱ ነው ሲሆን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ያየው በ8ኛው ቀን እሁድ ነው ያየውም በጦር የተወጋ ጐኑን ዳስሶ ነው እንዲሁም የእመ አምላክን ዕርገቷን አስቀድሞ ያየውም እርሱ ነው፡፡
ሀገረ ስብከቱ ሕንደኬ ሲሆን ለምክንያት ይሁነኝ ብሎ በ30 ብር ተሽጦ ከመስፍነ ብሔሩ ክሉክዮስ ቤት እያገለገለ ይኖር ነበር ምን ምን መሥራት ትችላለህ ቢለው ሕንፃ ማነጽ ሐውልት መቅረጽ እችላለሁ አለው እንኪያስ ሠርተህ ቆየኝ ብሎ ብዙ ወርቅ እና ብር ሰጥቶት አሕዛብ ምኩሀን ናቸውና እንዲህ ያለ ጠቢብ አገኘሁ ለማለት ወደ ንጉሥ ሄደ፡፡ እሱም ሕንጻ ማነጽ ሐውልት መቅረጽ ከዚህ የበለጠ አለን ብሎ ለነዳያን መጸወተው ከዚያውም ዘንድ አስተምሮ አሳምኗቸዋል የሉክዮስም ሚስት አርሶንዋ ከነልጆቿ ከአገልጋዮቿ አምና ተጠምቃለች፡፡ ሉክዮስ ከሄደበት ሲመለስ ያነጽከው ሕንጻ የቀረጽከው ሐውልት ወዴት ነው? አለው በወርቅና በብርህ ያነጽኳቸው ሕንጻዎች እኒህ ናቸው ብሎ ያመኑትን አገልጋዮች አሳየው ይህ ክፉ ባሪያ ተጫወተብኝ ብሎ እጅ እግሩን አሥሮ ቆዳውን አስገፍፎ ስልቻ አስፍቶ በአሸዋ መልቶ አሸክሞ ገበያ ለገበያ ሲያዞረው ሚስቱ አርሶንዋ አይታ በድንጋጤ ወድቃ ሞተች ሚስቴ የሞተችው ባንተ ምክንያት አይደለምን ካዳንካት እኔም በአምላክህ አምናለሁ ቢለው ጌታ ቁስሉን እንደ ውኃ አቀዝቅዞለት ካለችበት ሄዶ ስልቻውን ቢያስነካት ተነሥታለች በዚህም ሉክዮስ አምኖ ተጠምቋል፡፡
ከዚህም በኋላ ስልቻውን ተሸክሞ ከቦታ ወደ ቦታ እየተዘዋወረ ሙት እያነሣ ድውይ እየፈወሰ አሕዛብን አሳምኖ አጠመቀ፡፡ ቀንጦፍያ ሲደርስ አንድ ሽማግሌ ሰባት ልጆቹን ገድለውበት ሲያዝን አግኝቶ ስልቻውን እያስነካ ሰባቱን አስነሥቶለታል፡፡ በኢናስም የቃሉን ትምህርት የእጁን ተአምራት አይተው ከንጉሱ ሚስት ከንግሥቲቱ ጀምሮ እስከ ተራ ገባር ድረስ ያሉት ሁሉ አምነው ተጠመቁ ኋላ ግን ካህናተ ጣኦት ጥቅም የሚቀርባቸው ቢሆን በተንኮል ከንጉሥና መኳንንቱ አጣልተው በዚህ ዕለት አንገቱን በሰይፍ አስመትተውታል፡፡
🔴#ስንክሳር ታኅሣሥ_17
#ቅዱስ_ሉቃስ_ዘዓምድ
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ታኅሣሥ ዐስራ ሰባት በዚች ቀን ጻድቁ አቡነ ሉቃስ ዘዓምድ ፍልሠተ ሥጋው ሆነ፡፡ እርሱም ከፋርስ አገር ነው በመጀመሪያ በመቶ ጭፍራ ላይ መኰንን ሁኖ ተሹሞ ነበር ከዚህም በኋላ ሹመቱን ትቶ የምንኵስና ልብስን ለበሰ። በምሥራቅ አገር ከአሉ ገዳማትም በአንዱ ገዳም እየተጋደለ ብዙ ወራት ኖረ የምንኵስናንም ሥራ ተጋድሎንና ትሩፋትንም በፈጸመ ጊዜ በዚያ ገዳም ውስጥ ቅስና ተሾመ። በተሾመም ጊዜ በዚያ በኖረበት መጠን የብረት ልብስ ለበሰ ከዚያቺም ወዲህ ስድስት ቀን የሚጾም ሆነ በክርስቲያን ሰንበት ቀንም ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ይቀበላል ከዚህም በኋላ ከጐመን ጋር አንድ የዳቦ ለከት ይመገባል።
ከዚህም በኋላ ከዓምድ ላይ ወጥቶ በላዩ ሦስት ዓመት ቆመ በስሙም ሲጠራውና ከዚያም ዓምድ ላይ እንዲወርድ ሲያዝዘው የመልአክን ቃል ሰማ የብርሃን መስቀል ተከተለው ከገዳማት ወደ አንዱ ገዳም እስከ አደረሰውም ድረስ መራው በዚያም የሚኖር ሆነ ሰዎችም ሁሉ ወደርሱ እየመጡ በትምህርቱ ይረጋጉ ነበር።
ከዚህም በኋላ የማይናገር ሆነ ከሰው ጋር ከቶ እንዳይናገር ከአፉ ውስጥ ደንጊያ ጐረሰ ዳግመኛም ወደ የቊስጥንጥንያ አገር ዳርቻ ይሔድ ዘንድ መልአክ አዘዘው ለእርሷም አቅራቢያ ወደ ሆነች ወደ አንዲት ቦታ ሔደ ከምሰሶ ላይም ወጥቶ ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ በላዩ አርባ አምስት ዓመት ኖረ እግዚአብሔርም የመፈወስን ሀብት ሰጠው አስደናቂዎች ተአምራትን በማድረግ ወደርሱ የሚመጡትን ከብዙዎች በሽተኞችን ፈወሳቸው።
እግዚአብሔርም ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው በፈቀደ ጊዜ በዚህ ወር በዐሥራ አምስተኛው ቀን ዐረፈ የሚያገለግለውም ረድ ለጳጳሳት አለቆችና ለካህናት አለቆች ስለ ዕረፍቱ ነገራቸው እነርሱም መስቀሎችን፣ ጽንሐዎችን፣ መብራቶችን፣ ከመያዝ ጋር በዚያን ጊዜ ተነሠሰተው ወደመኖሪያው ሔዱ በላዩም ጸልየው ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ ወሰዱት በዐረፈ በሦስተኛው ቀን ታኅሣሥ ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን አደረሱት ወደ ቤተ መቅደስም አስገብተው የከበረ ሥጋው በአለበት እንደሚገባ ጸሎትን ፈጸሙ። ከእርሱም ተባረኩ የተሰበሰቡትም ሁሉ ተባረኩ ከዚህም በኋላ ከርሱ አስቀድሞ የቅዱሳን ሥጋቸው ወዳለበት ሣጥን ውስጥ ጨመሩት እግዚአብሔርም እጅግ ጠቃመመ የሆኑ አስደናቂዎች ተአምራትን አብዝቶ ገለጠ አምነው በሚመጡ በብዙዎች በሽተኞች ላይ ታላቅ ፈውስ ሁኗልና።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የሐዘን መግለጫ
የዲ.ብሩክ አበበ ወንድም ስላረፈ ነገ በ17/04/15 በደብረ አሚን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተክርስቲያን በ9:00 ሰዓት ቀብር መሆኑን እና በተለምዶ 43 ቀበሌ ቆጪ ገባ ብሎ ስለሆነ ቀብር እና ማጽናናት ላይ እንድንገኝ እንሳስባለን!!!
اکنون در دسترس! پژوهش تلگرام ۲۰۲۵ — مهمترین بینشهای سال 
