የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
رفتن به کانال در Telegram
2 641
مشترکین
+324 ساعت
+177 روز
+5630 روز
آرشیو پست ها
የሐዘን መግለጫ
የእህታችን ዮርዳኖስና ሰላማዊት ገ/ሚካኤል እህት ባል ከዚህ ዓለም ድካም ያረፉ ሲሆን ሥርዓተ ቀብራቸውም ነገ ረቡዕ ሐምሌ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከ8:00-9:00 በሽሮ ሜዳ ቅድስት ሥላሴ ቤ/ክ የሚፈጸም ይሆናል። ነፍሱን እግዚአብሔር በቅዱሳኑ እቅፍ ያሳርፍልን።
በአንዲትም ዕለት ቅዱስ በጥላን በከተማው አደባባዮች ሲያልፍ እባብ የነደፈውን አንድ ሰው ሲጨነቅ አየው እባቡም በርሱ ዘንድ ቆሞ ነበር በልቡም የመምህሬን ቃል ልፈትን ክብር ይግባውና በክርስቶስ ከአመንክ በስሙ ታምራት ታደርጋለህ ብሎኛልና አለ። እባብ ወደ ነከሰውም ሰው ቀርቦ ኃይሉን ይገልጽለት ዘንድ እባቡንም ይገድለው ዘንድ ሰውዬውን ያድነው ዘንድ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ረጅም ጸሎትን ጸለየ ያን ጊዜም ሰውዬው ያለ ምንም ጉዳት ድኖ በጤና ተነሣ ከይሲውም ወደቀ ወዲያውም ሞተ። የበጥላንም ሃይማኖቱ ተጨመረለት።
ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ ሁልጊዜም ወደ ቄሱ እየመጣ ይማር ነበር። በአንዲት ቀንም ያድነው ዘንድ አንድ ዕውር መጣ። የቅዱስ በጥላን አባትም ባየው ጊዜ ዕውሩን ከውጭ መልሶ ሰደደው በጥላንም አባቱን ማነው የፈለገኝ ብሎ ጠየቀው አባቱም ልታድነው የማትችል አንድ ዕውር ነው አለው።
እርሱም አባቱን የእግዚአብሔርን ክብር ታይ ዘንድ አለህ አለው ይህንንም ብሎ ዕውሩን ጠራውና ዐይኖችህ ቢገለጡ ያዳነህን ታመልከዋለህን አለው ዕውሩም አዎን አምናለሁ አለ ቅዱስ በጥላን በዕውሩ ላይ ረጅም ጸሎትን ጸለየ እጆቹንም በዕውሩ ዐይኖች ላይ አኑሮ እንድታይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እመን አለው ወዲያውኑም ዐይኖቹ ተገለጡ።
አባቱም ይህን ድንቅ ሥራ በአየ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታ በኢየሱስ ከዕውሩ ጋር አመነ ቅዱስ በጥላንም ወደ ቄሱ ወሰዳቸውና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ከዚህም በኋላ ባሮቻቸውን ነፃ አወጡ ገንዘባቸውንም ለድኆችና ለችግረኞች አከፋፈሉ።
ቅዱስ በጥላንም ጥበብን ያደርግ ነበር። ያለ ዋጋም ሰዎችን ያድናቸው ነበር። ነገር ግን ክብር ይግባውና በክርስቶስ እንዲያምኑ ይሻ ነበር። ስለዚህም ጥበበኞች ሰዎች በእርሱ ላይ ተነሡ ወደ ንጉሥም ሒደው ከቄሱ ጋራና ከአዳነውም ዕውር ጋራ በጌታችንም ከአመኑ ከብዙዎች ጋራ ከሰሱት። ወደ ንጉሡም በቀረቡ ጊዜ ንጉሡ ተቆጥቶ ለአማልክት ሠዉ አላቸው ባልታዘዙለትም ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጠ። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ በጥላንን የጸና ሥቃይን አሠቃየው። ከእርሱም ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ በእጁም ብዙ ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን አመኑ። በሰማዕትነትም ሞቱ። ንጉሡም አይቶ በበጥላን ላይ ተቆጣ። ለአንበሳም አስጣለው አንበሳውም እግሩን ላሰው እንጂ ክፉ አላደረገበትም። ሁለተኛም ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚህም ምስክርነቱን ፈጽሞ በመንግሥተ ሰማያት አክሊልን ተቀበለ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን👇
https://youtube.com/@finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_19
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሕፃኑ #ቅዱስ_ቂርቆስ እና #እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ፣ #ቅዱሳን_ሱርስ_ኀርማን_ያኑፋና_ስንጣንያ የሚባሉ የእስና ሀገር ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ፣ ብልህ የሆነ #ቅዱስ_በጥላን በሰማዕትነት ሞተ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ
ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ። ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች በዚያም የሸሸችውን መኰንን አገኘችው።
ሰዎችም ነገር ሠሩባት ወደርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት እርሷም መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው።
ሕፃኑም ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው። ሕፃኑም መልሶ አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ።
መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው እናቱንም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሠቃያት እግዚአብሔርም ያለምንም ጉዳት ያነሣቸው ነበር። ብዙዎች አሕዛብም ይህን አይተው አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ።
በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት። ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳናቸው።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ ያን ጊዜም ፍርሀትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።
ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች ከዚህም በኋላ ጸናች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው ልጅዋንም ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው።
ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት አለች ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጐትቷቸው አዘዘ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ አዳናቸው መኰንኑም በታላቅ ሥቃይ ያሠቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወህኒ ቤት ዘጋባቸው።
ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው አረጋጋውም። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱሳን_ሱርስ_ኀርማን_ያኑፋ_እና_ስንጣንያ
በዚህች ቀን ስማቸው ሱርስ፣ ኀርማን፣ ያኑፋ፣ ስንጣንያ የሚባሉ የእስና ሀገር ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ። የሰማዕትነታቸው ምክንያትም እንዲህ ነው መኰንኑ አርያኖስ ወደ እስና ከተማ ሦስት ጊዜ ደረሰ። በመጀመሪያ የተባረከች መስተጋድልት የሆነች ዳላዢን ገደላት። ስማቸውን አስቀድመን የጠራናቸው አራቱን ልጆቿንም ገደላቸው። የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ ግንቦት ሰባት ቀን ሆነ።
በሁለተኛም ጊዜ ስማቸው አውሳፍዮስ፣ ታማን፣ ኀርማን፣ ባኮስ የሚባል አራቱን መኳንንት ገደላቸው። የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ ሰኔ ሰባት ቀን ሆነ። በሦስተኛም ጊዜ በቤቷ ውስጥ በዐልጋዋ ላይ ተኝታ የነበረችውን አሮጊት የአርያኖስ ወታደሮች ስለ እነዚህ ቅዱሳን ከጠየቋት በኋላ ገደሏት።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከክርስቲያን ወገን ያገኙትን ሁሉ እንዲገድሉ የተክል ማጠጫ በተባለች በከተማዋ ምዕራብም መግደልን እንዳያቋርጡ አዘዘ ወደ ከበረ አባት ወደ ባሕታዊ ይስሐቅም እስኪደርሱ ድረስ በመንገድ ብዙ ሕዝብን አገኙ።
ያን ጊዜም ጠባቂያቸው እንዲህ እያለ ያጽናናቸውና ያረጋጋቸው ነበር። ወደ ሰማያዊት መንግሥት እንድትገቡ ጸንታችሁ ታገሡ። እንዲህም ሲወስዷቸው መኰንኑ ደረሰ በአዩትም ጊዜ ሁሉም በአንድ ቃል እኛ ክርስቲያን ነን እያሉ በግልጽ ጮኹ መኰንኑም ሁሉንም እንደበግ ያርዷቸው ዘንድ አዘዘ።
ጭፍሮች ግን በላያቸው በሰይፎች አጋና ተጫወቱ። በዚችም በሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን የእስናን ከተማ ሰዎች ከታናሾቻቸው እስከ ታላቆቻቸው ሴቶችንና ወንዶችን ጨረሷቸው። የመላእክት ሠራዊትም ነፍሶቻቸውን ይቀበሉ የብርሃን አክሊሎችንም ያቀዳጁአቸው ነበር።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከዚያ ወደ እስዋን ከተማ ሔደ ሁለተኛም ወደ እስና ከተማ ተመልሶ ሦስት ገበሬዎችን የእርሻ ዕቃቸውን ተሸክመው አገኘ። መኰንኑንም በአዩት ጊዜ እኛ ክርስቲያን ነን ብለው በግልጥ ጮኹ መኰንኑም ሰምቶ ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ በእርሻ መሣሪያቸውም ገደሏቸው የእነዚህም ስማቸው ሱሩፋስ፣ አንጣኪዮስ፣ ስሐድራ ይባላል የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ መስከረም ዐሥራ አንድ ቀን ነው።
ይህንንም ቅዱስ አባት ኤጲስቆጶስ ይስሐቅን መኰንኑ አሥሮ ለጣዖት እንዲሠዋ አስገደደው። እምቢ ባለውም ጊዜ ወደ እሳት እንዲወረውሩት አዘዘ የሰማዕትነቱም ፍጻሜ ታኅሣሥ ዐሥራ አራት ቀን ነው ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ገንዘው ቀበሩት። የስደቱ ወራትም ከአለፈ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው በስሙ አከበሩዋት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_በጥላን_ጠቢብ_ሰማዕት
በዚህችም ቀን ትዕማዳን ከምትባል ከተማ ብልህ የሆነ ቅዱስ በጥላን በሰማዕትነት ሞተ። አባቱም አረማዊ ነበረ ስሙም አውሱጢኪዮስ ነበር እናቱ ግን አማኝ ነበረች ስሟም ኤልያና ነበር። በአደገ ጊዜም አባቱ ጥበብን ሁሉ አስተማረው እጅግም አዋቂ ሆነ።
በበጥላን ቤት አቅራቢያም አንድ ቄስ ይኖር ነበር። በጥላንም በፊቱ ሲያልፍ መልኩንና ዕውቀቱን ብልህነቱንና አሰተዋይነቱንም ይመለከት ነበር ከሀዲ ስለመሆኑም ስለርሱ ያዝን ነበር። ቄሱም በጥላንን መንገድ መርቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ያስገባው ዘንድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው።
ስለ በጥላንም ልመናውን በአዘወተረ ጊዜ በጥላን በእርሱ እጅ ያምን ዘንድ እንዳለው ጌታችን በራእይ ገለጠለት ቄሱም ደስ አለው ሁልጊዜም በፊቱ ሲያልፍ በጥላንን ያነጋግረውና ሰላምታ የሚሰጠው ነበር። ስለዚህም በመካከላቸው ፍቅር ጸና።
ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ቤት ይገባና ስለ ሃይማኖት ይነጋገር ነበር። ቄሱም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ምን ያህል ክብር እንዳላት ለሚያምኑበትም ሁሉ ዕውቀትና ማስተዋል እንደሚሰጣቸው ድንቆችና ታላላቅ ተአምራቶች እንደሚደረግላቸው ታላቅ ፈውስም እንደሚያደርጉ ገለጠለት።
በጥላንም ክብር ይግባውና በክርስቶስ የሚያምኑ ተአምራትን እንደሚያደርጉ ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት በዚያ ቄስ ትምህርት በጌታ አመነ ቄሱም ሁልጊዜ የሃይማኖትን ትምህርት ያስተምረው ጀመር።
አክሊል
ተቀዳጁ፡፡
ቅዱስ ኤስድሮስንም ቸንክረው ሰቀሉት፡፡ ሕጻኑም ተሰቅሎ ሳለ በእናቱና በእኅቱ የሆነውን ነገር ይመለከት ነበር፡፡ ሆዱን ሰንጥቀው በመቅደድ አንጀቱን አውጥተው ወስደው በተራራ ላይ ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከሞት አሥተነስቶት እንደ ቀድሞው ሕያውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ቅዱስ ኤስድሮስም ተመልሶ ሄዶ ከከሃዲው ንጉሥ ፊት ቆመ፡፡ አሁንም በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከሥር እሳት አነደዱበት፡፡ ሁለተኛም በብረት ላይ አስተኝተው ፈጩት፡፡ ነገር ግን ጌታችን አሁንም ከሞት አስነሣው፡፡ በዚህም ብዙዎች ‹‹በኤስድሮስ አምላክ አምነናል›› እያሉ በምስክርነት ዐረፉ፡፡ ዳግመኛም በእርሱ አምላክ ካመኑት ከሰምንት መቶ ነፍሳት ጋር ሰቀሉት፡፡ አሁን ጌታችን አድኖ አሥነሳው፡፡ በሥቃይም ብዛት አልሞት ቢላቸው አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት ነገር ግን አሁንም ጌታችን ለሦስተኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ኤስድሮስን ትልቅ ድንጋይ በአንገቱ ላይ አስረው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከባሕሩ ውስጥ አውጥቶ በንጉሡ ፊት አቆመው፡፡ ዳግመኛም ወደ ከተማ ወስዶ ሰቅሎ ገደለው፣ ጌታችንም ለ4ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡ ለተራቡ አንበሶች ሲሰጡት እነርሱም ምንም ሳይነኩት ቀሩ ይልቁንም አክብረው ሲሰግዱለት ቢመለከቱ በንዴት ሰውነቱን ቆራርጠው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከቅዱስ ሚካኤልና ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ተገልጦለት ለ5ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡ ንጉሡም እጅግ አፈረና የሚያደርገው ቢያጣ በግዞት ወደ ሰሎንቅያ ሀገር ላከው፡፡ በዚያም ብዙ ካሠቃዩት በኋላ ወደ ንጉሡ መለሱት፡፡ ንጉሡም በእሥር ቤት አሥሮ በርሃብ እንዲሠቃይ አደረገው፡፡ በመጨረሻም ቅዱስ ኤስድሮስ ግንቦት 19 ቀን የሰማዕትነት ፍጻሜው ሆነና ተሰቅሎ ዐረፈ፡፡ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀዳጀ፡፡ ቅዱስ ኤስድሮስ የኖረበት ዘመን 12 ዓመት ነው፡፡ በቅዱስ ኤስድሮስ ምክንያት በጌታችን አምነው ከኤስድሮስ ጋር አብረው በሰማዕትነት የሞቱት ሰዎች ብዛት 8 መቶ 5 ሺህ ሰባት ሰዎች ናቸው፡፡ ጌታችንም ለሕፃኑ ሰማዕት ለቅዱስ ኤስድሮስ አስደናቂ ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን👇
https://youtube.com/@finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_18
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ስምንት የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ፣ #ቅዱስ_አትናቴዎስ በከሀዲው በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተ፣ ሰማዕት የሆኑ #የቅዱስ_ኤስድሮስ_ማኅበርተኞች መታሰቢያቸው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ያዕቆብ
ሐምሌ ዐሥራ ስምንት የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የጌታችን ወንድም የሚባለው ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት ሞተ።
ይህም ቅዱስ የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ነው። እርሱም ከልጆቹ ሁሉ የሚያንስ ነበር። እርሱም ንጹሕ ድንግል ነበር ከጌታችንም ጋራ አደገ ስለዚህም ክብር ይግባውና የጌታችን ወንድም ተባለ። ከጌታችን ዕርገትም በኋላ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ላይ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተምሮ ብዙዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።
እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ። በአንዲት ዕለትም በጐዳና ሲጓዝ አንድ ሽማግሌ አገኘ። ቅዱስ ያዕቆብም ሽማግሌ ሆይ በቤትህ ታሳድረኛለህን አለው። አረጋዊውም እሺ እንዳልክ ይሁን አለ በአንድነትም ሲጓዙ ጋኔን ያደረበት ሰው አገኘው በአየውም ጊዜ የክርስቶስ ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ልታጠፋኝ መጣህን ብሎ ጮኸ ሐዋርያውም በናዝሬቱ ኢየሱስ ስም ተጠጋ ከሰውዬውም ውጣ አለው። ወዲያውም ያ ጋኔን ከሰውዬው ላይ ወጣ።
ያ ሽማግሌም ይህን ድንቅ ተአምር አይቶ ደነገጠ ከሐዋርያው እግር በታችም ወድቆ እንዲህ አለው። ወደ ቤቴ ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን እድን ዘንድ ቤተሰቦቼም ሁሉ ይድኑ ዘንድ ምን ላድርግ አለ ያን ጊዜም ሐዋርያው አቤቱ ጌታዬ ሆይ መንገዴን አሳምረህልኛልና አመሰግንሃለሁ ብሎ ጌታችንን አመሰገነው። ወደ ሽማግሌውም ተመልሶ የድኅነትን ነገር ነገረው ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ሰው መሆን ስለ መከራው ስለ ሞቱና ስለ መነሣቱ አስተማረው።
ከዚህም በኋላ ያ ሽማግሌ ሐዋርያውን ወደ ቤቱ አስገባው ቤተሰቦቹም ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ ቅዱስ ያዕቆብም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው።
የከተማው ሰዎችም በሰሙ ጊዜ በሽተኞችን ሁሉ ወደርሱ አመጡ ሁሉንም አዳናቸው ለእነርሱም ሃይማኖትን አስተምሮ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው። ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመላቸው ያንን ሽማግሌም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመው ክብር ይግባውና የጌታችንንም ወንጌል ሰጣቸው ከዚህም በኋላ ያስተምር ዘንድ ወደ ሌሎች አገሮች ወጥቶ ሔደ።
አንዲት መካን ሴት ነበረች እግዚአብሔር ልጅን ይሰጣት ዘንድ ስለርሷ እንዲጸልይላት ቅዱስ ያዕቆብን ለመነችው። እርሱም ጸለየላትና ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ያዕቆብ ብላ ጠራችው ልጅዋንም ተሸክማ ወደ ሐዋርያው መጥታ ሰላምታ አቀረበችለት ከልጅዋም ጋር ከእርሱ ተባረከች ።
ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ብዙዎች አይሁድ ወደርሱ ተሰበሰቡ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስም የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጠየቁት እነርሱ እርሱ ጌታን የዮሴፍ ልጅ እንደሆነ እርሱም ወንድሙ እንደሆነ እንደሚነግራቸው አስበው ነበርና።
ቅዱስ ያዕቆብም በሦስተኛ ደርብ ላይ ወጥቶ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ከአብ ጋራም ትክክል እንደሆነ ይገልጽላቸው ጀመረ።
ይህንንም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቄጡ ከደርቡ ላይ አውርደው የጸና ግርፋትን ገረፉት ከእነርሱም ውስጥ የልብስ ማጠቢያ የዕንጨት ገበታ የያዘ አንድ ሰው መጣ በዚያ ዕንጨትም ቅዱስ ያዕቆብን ራሱ ላይ መታው ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
ስለ እርሱም ወይን እንዳልጠጣ፣ ደም ካለው ወገን እንዳልበላ፣ በራሱም ላይ ምላጭ እንዳልወጣ፣ በውሽባ ቤት እንዳልታጠበ፣ ሁለት ልብስንም እንዳልለበሰ፣ ሁልጊዜም እንደሚቆምና እንደሚሰግድ ተጽፎአል። ከመቆም ብዛት የተነሣም እግሮቹ አብጠው ነበር ከዚህም በኋላ አረፈና በቤተ መቅደሱ ጐን ቀበሩት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አትናቴዎስ
በዚህችም ቀን ከቍልዝም ከተማ ቅዱስ አትናቴዎስ በከሀዲው በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ ከነገሥታት ወገን ነበረ በሃይማኖቱም የጸና ነበረ። እኒህ ከሐዲያን ነገሥታት ዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ የጣዖታትን አምልኮ በዓወጁ ጊዜ ይህን አትናቴዎስን ለግብጽ አገር ገዥ አድርገው ሾሙት አብያተ ክርስቲያናትንም እንዲአፈርስ አዘዙት።
እርሱ ግን ወደ ግብጽ በደረሰ ጊዜ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ሒዶ በረከትን ተቀበለ እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ነገረው በእርሱም ደስ አለው። ንጉሡም በሰማ ጊዜ ይዞ ይመረምረው ዘንድ ሌላ መኰንን ላከ።
መኰንኑም በደረሰ ጊዜ ተገናኘውና የአማልክትን ፍቅር ለምን ተውክ አለው። አትናቴዎስም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ ከታናሽነቴ ጀምሬ ክብር ይግባውና የክርስቶስ ነኝ የቀናች ሃይማኖቴንም አልተውም።
መኰንኑም የንጉሥን ትዕዛዝ የሚለውጥ ሁሉ ቅጣት እንዲአገኘውና በጽኑ ሥቃይ እንዲሠቃይ አታውቅምን አለው። ቅዱስ አትናቴዎስም እንዲህ አለው አንተ ሰነፍ በአንተ ላይና በንጉሥህ ላይ ቸር ሕይወት ሰጭ እግዚአብሔርን በሚጠላ በአባትህ ሠይጣን ላይ የሚመጣው የዘላለም ሥቃይን እስከምታይ ጥቂት ታገሥ አለው።
መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ራሱንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ቅዱስ አትናቴዎስም ነፍሱን ከቅዱሳኑ ጋራ እንዲያሳርፍ ከቤተ ክርስቲያንም መከራን እንዲያርቅ የሮምንና የአኲስምን የክርስቲያን መንግሥት እንዲአጸና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ጸሎቱም በፈጸመ ጊዜ በርከክ ብሎ ሰገደ ጭፍሮችም ራሱን በሰይፍ ቆረጡ። ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ቀበሩት። ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ተአምራት ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#የቅዱስ_ኤስድሮስ_ማኅበር
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የቅዱስ ኤስድሮስ ማኅበርተኞች የሆኑ ዘጠኝ ሺህ ሰማዕታት በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው ይውላሉ፡፡ ይኸውም ሰማዕት ኤስድሮስ ጌታችን 5 ጊዜ ከሞት እያስነሣውና ስለ ስሙ ምስክር የሆነለት የ12 ዓመት ሕጻን ነው፡፡ ከእርሱም ጋር ማኅበርተኞቹ የሆኑ 8 መቶ 5 ሺህ ሰባት ሰዎች በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ በዚህች ዕለትም ማኅበርተኞች የሆኑ ዘጠኝ ሺህ ሰማዕታት በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው ይውላሉ፡፡
(የዕረፍታቸውን ዕለት ግንቦት 19ን ይመለከቷል፡፡)
ሕጻኑ ሰማዕት ቅዱስ ኤስድሮስ ሀገሩ እስክንድርያ ሲሆን አባቱ በድላዖን እናቱ ሶፍያ ከቤተ መንግሥት ወገኖች ናቸው፡፡ አባቱ የዲዮቅልጥያኖስ መኰንን ነበር፡፡ ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ በክርስቲያኖች ላይ እጅግ አሠቃቂ መከራ ባደረሰ ጊዜ አባቱ በድላዖን ምስፍናውን ትቶ ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ ገዳም ገባ፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም ጭፍሮቹን ልኮ አስመጣውና እምነቱን እንዲክድ ጠየቀው፡፡ በድላዖንም ‹‹ክርስቶስን በተውከው ሰዓት እኔም አንተን ተውኩህ›› አለው፡፡ ወዲያም አንገቱን በሰይፍ አስቆረጠው፡፡ ቅዱስ ኤስድሮስም ገና የ12 ዓመት ሕፃን ልጅ ነበርና ይመለስ ይሆናል በሚል በእሥር ቤት እንዲቆይ ተደረገ፡፡ በማግሥቱም ‹‹ክርስትናህን ትተህ የንጉሡን ሃይማኖት ተቀበል›› ብለው ሲያባብሉት እምቢ አላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ በንጉሡ ፊት አቅርበው ደሙ እንደ ውኃ እስኪወርድ ድረስ አሠቃቂ ግርፋትን ገረፉት፡፡ እናቱ ሶፍያም የሕፃኑን ልጇን ደም በዲዮቅልጥያኖስ ፊት ላይ እረጭታ እረገመችው፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም በንዴት ከሴት ልጇ ጋር ከወገባቸው ላይ ከሁለት አስቆረጣቸውና ሰማዕትነታቸውን ፈጽመው የክብር
ዮናስም ከዓሣ አንበሪ ሆድ ያለ ምንም ጥፋት እንደመጣ እንዲሁ መደኃኒታችን ያለመለወጥ ተነሥቷልና።
እንዲህም ሆነ ከእግዚአብሔር ፊት ዮናስ ሸሽቶ ወደ ተርሴስ አገር ሊሔድ ተነሣ ወደ ኢዮጴ አገርም ወርዶ ወደ ተርሴስ አገር የሚሔድ መርከብን አግኝቶ በገንዘቡ መርከቡን ተከራየ።
ከእግዚአብሔር ፊት ኰብልሏልና ከእነርሱ ጋር ወደ ተርሴስ ይሔድ ዘንድ ወደ መርከቡ ወጣ እግዚአብሔርም ታላቁን ነፋስ ወደ ባሕር አመጣ የባሕሩም ማዕበል ከፍ ከፍ አለ መርከባቸውም ሊሰበር ቀረበ። ቀዛፊዎችም ፈርተው ወደ ጣዖቶቻቸው ጮኹ መርከባቸውም ይቀልላቸው ዘንድ ገንዘባቸውን፣ ዕቃቸውን አውጥተው ወደ ባሕር ጣሉ። ዮናስ ግን በዚያን ጊዜ ወደ ከርሠ ሐመሩ ወርዶ ተኝቶ ያንኰራፋ ነበር።
መርከቡንም የሚቀዝፍ ቀዛፊ ወደ ርሱ ወርዶ ምን ያስተኛሃል እንዳንሞት እግዚአብሔር ያድነን ዘንድ ተነሥተህ የፈጣሪህን ስም ጥራ አለው። ይህች መከራ ያገኘችን ስለማናችን ኃጢአት እንደ ሆነ እናውቅ ዘንድ እርስ በርሳቸው ኑ ዕጣ እንጣጣል ተባባሉ በተጣጣሉም ጊዜ ዕጣ በዮናስ ወጣበት። እነርሱም ይህች መከራ ያገኘችን በማናችን ኃጢአት እንደሆነ ንገረን አንተስ የምታመልከው ምንድንነው ከወዴትስ መጣህ አገርህስ የት ነው ወዴትስ ትሔዳለህ ወገንህስ ማንነው አሉት።
ዮናስም እኔስ የእግዚአብሔር ባርያው ዕብራዊ ነኝ ፈጣሪዬም ምድርንና ሰማይን ባሕሩንና የብሱን የፈጠረ እግዚአብሔር ነው አላቸው። እነዚያም ሰዎች ታላቅ ፍርሀትን ፈርተው ምን አድርገሀል አሉት እሱ ነግሮአቸዋልና ከእግዚአብሔር ፊት ኰብልሎ እንደሔደ እነርሱም አወቁት።
ባሕሩ ይታወክ ነበርና ታላቅ ማዕበልም ተነሥቶ ነበርና ባሕሩ ይተወን ዘንድ እንግዲህ ምን እናድርግህ አሉት። ዮናስም አንሥታችሁ ወደ ባሕር ጣሉኝ ባሕሩም ይተዋችኋል ይህ ታላቅ የማዕበል ሞገድ የመጣባችሁ በእኔ ምክንያት እንደ ሆነ አውቃለሁ አላችው።
ባሕሪቱ ትታወካለችና ማዕበሊቱም በእነሣቸው ትነሣለችና እነዚያ ሰዎች ወደ ምድር ሊመለሱ ወደዱ ነገር ግን ተሳናቸው። ሁሉም አንድ ሁነው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ አቤቱ ስለዚህ ሰው በእውነት ልታጠፋን አይገባህም አቤቱ እንደ ወደድክ አድርገሃልና የጻድቅ ሰው ደም አታድርግብን አሉ። ከዚህም በኋላ ዮናስን አንሥተው ወደ ባሕር ጣሉት ባሕርም ድርጎዋን ተቀብላ ጸጥ አለች። እነዚያም ሰዎች እግዚአብሔርን ፈሩት ለእርሱም መሥዋዕትን ሠዉ ስእለትንም ተሳሉ።
እግዚአብሔርም ታላቅ ዓሣ አንባሪን ዮናስን ይውጠው ዘንድ አዘዘው ዮናስም በዓሣ አንባሪ ሆድ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት ኖረ። ዮናስም በአንበሪ ሆድ ውስጥ ሳለ ጸሎትን ጸለየ ከዚህም በኋላ በነነዌ አገር በኩል ያ ዓሣ አንበሪ ዮናስን ወደ የብስ ምድር ተፋው።
የእግዚአብሔርም ቃሉ ዳግመኛ ወደ ዮናስ መጣ ቀድሞ አስተምር ብዬ እንደ ነገርኩህ ወደ ታላቂቱ የነነዌ አገር ተነሥተህ ሒደህ አስተምራቸው አለው።
ዮናስም እግዚአብሔር አስተምር ብሎ እንደ ነገረው ተነሥቶ ወደ ነነዌ ሔደ። ነነዌ ግን ለእግዚአብሔር ታላቅ አገር ናት በዙሪያዋ ያለ ቅጽርዋም ከበር እስከ በር ድረስ በእግር የሦስት ቀን ጐዳና ነው። ወደ ከተማም ሊገባ ደርሶ ያንድ ቀን መንገድ ሲቀረው ነነዌ እስከ ሦስት ቀን ትጠፋለች ብሎ አስተማረ።
የነነዌም ሰዎች በእግዚአብሔር ቃል አመኑ ጾምን እንጹም ብለው አዋጅ ነገሩ የክት ልብሳቸውንም ትተው ማቅ ምንጣፍ ትልቁም ትንሹም ለበሱ። የነነዌ ንጉሥም ይህን ሰምቶ ከዙፋኑ ተነሣ ልብሰ መንግሥቱንም ትቶ ማቅ ለበሰ በአመድ በትቢያ ላይም ተቀመጠ።
ሰዎችም ቢሆኑ ከብቶችም ምንም ምን አይብሉ ትልልቆችም ትንንሾችም አይጠጡ እንስሶችም ወደ ሣር አይሠማሩ ውኃም አይጠጡ ብሎ አዋጅ ነገረ። እግዚአብሔርም ከክፉ ሥራቸው እንደ ተመለሱ አይቶ በእነርሱ ላይ ያደርገው ዘንድ ከተናገረው ክፉ ነገር ተመለሰ በእነርሱ ላይም ክፉ ጥፋትን አላደረገም።
ዮናስም ጽኑ ኀዘንን አዘነ ወደ ፈጣሪው እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ለመነ ጥንቱን በአገሬ ሳለሁ እንዲህ ብዬ የተናገርሁ አይደለሁምን አንተ ይቅር ባይ ርኅሩኅም ከመዓት የራቅህ ቸርነትህ የበዛ እውነተኛ የሆንክ ክፉ ነገርን ከማምጣት እንደምትመለስ አውቃለሁ ስለዚህ ከአንተ ኮብልዬ ወደ ተርሴስ ሔድሁ።
ነቢየ ሐሰት እየተባልኩ ከመኖር ሞት ይሻለኛልና አቤቱ አሁን ነፍሴን ከሥጋዬ ለያት አለ። እግዚአብሔርም ዮናስን በዚህ ነገር አንተ እጅግ ታዝናለህን አለው እርሱም አዎን አዝናለሁ አለ። ከዚህም በኋላ ዮናስ ከከተማ ወጥቶ ከከተማው ውጭ ተቀመጠ ጎጆም ለራሱ ሠራ በአገር ላይ የሚደረገውን ነገር እስኪያይ ድረስ ከጥላዋ ሥር ተቀመጠ።
ይበቅል ዘንድ በዮናስ ራስ ላይ ይሸፍነው ዘንድ እግዚአብሔር ቅልን አዘዘ ቅሉም በዚያን ጊዜ በቅሎ የዮናስን ራስ የፀሐይ ትኩሳት እንዳያሳምመው በዮናስ ራስ ላይ ሸፈነው ዮናስም በቅሊቱ መብቀል ታላቅ ደስታ አደረገ።
እግዚአብሔርም በማግሥቱ ትሉን ይምጣ ቅሉንም ይምታ ብሎ አዘዘ ቅሊቱንም ቆረጣት እርሷም ደረቀች እግዚአብሔርም ፀሐይ በወጣ ጊዜ የሚያቃጥል ሐሩር ያለበት ነፋስ ይምጣ ብሎ ዳግመኛ አዘዘ። ነፋሱም መጥቶ የዮናስን ራስ አሳመመው እርሱም አእምሮውን እስከማጣት ደርሶ በልቡናውም ተበሳጭቶ ከመኖር ሞት ይሻለኛል አለ።
እግዚአብሔርም ዮናስን በቅሊቱ መድረቅ እጅግ አዘንክን አለው እርሱም አዎን ልሙት እስከ ማለት ደርሼ አዘንኩ አለ። እግዚአብሔርም አንተስ በአንድ ሌሊት በቅላ በአንድ ሌሊት ለደረቀች ውኃ ላላጠጣሃት ላልደከምክባት ቅል ታዝናለህ። ቀኝና ግራቸውን ላልለዩ ከዐሥራ ሁለት እልፍ የሚበዙ ሰዎች እንዲሁም ብዙ እንስሶች ላሉባት ታላቅ አገር ለሆነች ነነዌ እኔ አላዝንላትምን ከበደሉ ተመልሶ ንስሐ ለሚገባ እኔ መሐሪና ይቅር ባይ ነኝና አለው።
ከዚህም በኋላ ዮናስ ተነሥቶ ወደ አገሩ ተመልሶ በሰላም አረፈ መላው ዕድሜውም መቶ ሰባ ነው። የነቢዩ የዕረፍት በዓል መስከረም 25 እንደሚከበር ስንክሳሩ ያስረዳናል።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን👇
https://youtube.com/@finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_17
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን #ቅድስት_አውፎምያ በሰማዕትነት ሞተች። #የቅዱስ_ዮስጦስ የከበረች ዐፅሙ በክብር ተገኘች፣ #ታላቁ_ነቢይ_ዮናስ ከዓሣ አንበሪ ሆድ ለወጣበት መታሰቢያው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_አውፎምያ
ሐምሌ ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን ቅድስት አውፎምያ በሰማዕትነት ሞተች። ይቺንም ቅድስት በርሴፎስ የሚባል ከዲዮቅልጥያኖስ መኳንንቶች አንዱ አሠቃያት። የታሠሩ ሰማዕታት በሚያልፉ ጊዜ በአንገታቸው የሚከብዱ ሰንሰለቶች ነበሩ። እንደ ውሾችም ይጐትቷቸው ነበር። ግፋቸውንም ባየች ጊዜ ይቺ ቅድስት አለቀሰች ልቡናዋም ክብር ይግባውና በክርስቶስ ፍቅር ተቃጠለ ዲዮቅልጥያኖስንና የረከሱ አማልክቶቹንም ረገመች። ያንንም መኰንን እንዲህ ብላ ዘለፈችው ርኅራኄ የሌለህ ልብህ እንደ ደንጊያ የሆነ ለእኒህ ቅዱሳን ሰዎች አትራራምን ፈጣሪያቸውስ እንዳያጠፋህ አትፈራምን።
መኰንኑም ሰምቶ ወደርሱ ያቀርቡአት ዘንድ አዘዘ። ስለ ሃይማኖቷም ጠየቃት እርሷም ክርስቲያን እንደሆነች በፊቱ አመነች። በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ በግርፋትና በስቅላት ታላቅ ሥቃይን አሠቃያት።
ከዚህ በኋላ በእሳት ምድጃ ውስጥ ጨመሩዋት ነገር ግን ከሥቃዩ የተነሣ ምንም ጉዳት አልደረሰባትም። በዚያን ጊዜም በእሳቱ መካከል ቆማ ጸለየች ፊቷንና መላ ሥጋዋንም በመስቀል ምልክት አማትባ ነፍሷን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዮስጦስ
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የቅዱስ ዮስጦስ የከበረች ዐፅሙ በክብር ተገኘች፡፡ በሰማዕትነት ያረፈው የአንጾኪያው ንጉሥ የኑማርያኖስ ልጅ ነው፡፡ ታላቁ የአንጾኪያ ንጉሥ ኑማርያኖስ በጦርነት ውስጥ በሞተ ጊዜ ልጁ ቅዱስ ዮስጦስም በሌላ ቦታ በጦርነት ውስጥ ስለነበር መንግሥትም ያለ ንጉሥ ቀረች፡፡
የቴዎድሮስ በናድልዮስ አባት ሲድራኮስና ቅዱስ ፋሲለደስ ዲዮቅልጥያኖስ ነግሦ ሃይማኖቱን እስከካደ ድረስ የመንግሥቱን አስተዳደር ይመሩ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ታላቁ የአንጾኪያ ንጉሥ ኑማርያኖስ የፋርስና የቁዝ ሰዎች በጦር በርትተው በመጡበት ጊዜ ቅዱስ ፋሲለደስንና ህርማኖስን ጠርቶ ‹‹እነሆ እኔና የተረፉት ሠራዊት ሄደን የቁዝን ሰዎች እንዋጋለን እናንተ ቤተ መንግሥቱን ጠብቁ፣ ልጆቼን ለእናንተ አደራ ሰጥቻለሁ›› አላቸው፡፡ ንጉሡም የመንግሥቱን ልብስ አውልቆ ዘውዱን ጥሎ ተራ ልብስ ለብሶ ሲዋጋ በጦር ተወግቶ ሞተ ነገር ግን የቁዝ ሰዎች አላወቁትም ነበር፡፡
ጦርነቱም ባለቀ ጊዜ የሮም መንግሥት ያለንጉሥ ብቻዋን ቀርታ አንድ ዓመት ሙሉ ቅዱስ ፋሲለደስና ህርማኖስ የመንግሥት ሕጓንና ሥርዓቷን እየጠበቁ ቆዩ፡፡ የቁዝ ሰዎችም የሮም መንግሥት ያለ ንጉሥ መሆኗን ሲያውቁ ዳግመኛ ሊያጠፏቸው በጦር በርትተው መጡ፡፡ የሮም ሰዎችም ተሰብስበው ቅዱስ ፋሲለደስን ‹‹በስራችን ወዳሉ ግዛቶች ወደ ግብጽም ተዋጊ አርበኞችን ይልኩልን ዘንድ እንጠይቃቸው›› አሉት፡፡ መኳንንቱም ወደ ግብጽ ወርደው በጦር ኃይለኛ የሆኑ ሰዎችን ይዘው ተመለሱ፡፡ ከግብጽ ካመጧቸው ኃይለኛ ሰዎች ውስጥ ከላይዕላይ ግብጽ ስሙ ከርቢጣ የሚባል ፍየል የሚጠብቅ አንድ ኃይለኛ ሰውን ወደ አንጾኪያ አመጡ፡፡
ቅዱስ ፋሲለደስና ህርማኖስም ይህ ሰው የሚያስፈራ በሥራውም ኃይለኛ ጉልበቱ የጸና ጨካኝ መሆኑን አይተው በንጉሡ ፈረስ ላይ ባልደራስ ወይም ሹም አድርገው ሾሙት፡፡ ከጥቂት ወራትም በኋላ ታላቂቱ የንጉሡ ልጅ ከቤተ መንግሥት ሆና በመስኮት በኩል ሆና ሲወጣ ባቱን ሲገባ ደረቱን አይታ በሀፀ ዝሙት ተነድፋ እጅግ ወደደችው፡፡ እርሱንም ሰይጣን ከልጅነቱ ጀምሮ ይከተለው ነበር፡፡ የንጉሡም ሴት ልጅ ወስዳ አገባችውና ስሙን ዲዮቅልጥያኖስ ብላ አነገሠችው፡፡ ይኽም ዲዮቅልጥያኖስ ከካደ በኃላ ሰይጣን ማደሪያው አድርጎት ከ470,000 (አራት መቶ ሰባ ሺህ) በላይ የሚሆኑ ክርስቲያኖችን በግፍ በሰማዕትነት የገደለ ነው፡፡
የንጉሡ ልጅ ቅዱስ ዮስጦስ ጦርነቱን አሸንፎ በድል ወደ ቤተ መንግሥት በተመለሰ ጊዜ ዲዮቅልጥያኖስ ጌታችንን ክዶ ጣዖታትን ሲያመልክ ቢያገኘው እጅግ አዝኖ ሰማዕት ይሆን ዘንድ ተመኘ፡፡ የሀገሩም ሰዎች ወደ ዮስጦስ ዘንድ ቀርበው ‹‹እኛ ዲዮቅልጥያኖስን እንገድለዋለን አንተ በአባትህ ዙፋን ተቀመጥ›› አሉት፡፡ እርሱ ግን ከምድራዊው መንግሥት ይልቅ ሰማያዊውን መንግሥት መርጧልና እሺ አላላቸውም፡፡ በጌታችንም ስም ሰማዕት ይሆን ዘንድ መረጠ፡፡ በንጉሡ ዲዮቅልጥያኖስም ዘንድ ቀርቦ ስለ ጌታችን ክብር መሰከረ፡፡
ንጉሡም ገና ሲያየው እጅግ ፈርቶና ደንግጦ ‹‹ጌታዬ ዮስጦስ ሆይ! ይህን ታደርግ ዘንድ ያስገደደህ ማነው?›› አለው፡፡ ቅዱስ ዮስጦስም ከሃዲውን ንጉሥ ‹‹በምስክርነቴ ደሜን እንዳፈስ ካልጻፍክ ሕዝቡን በአንተ ላይ አስነስቼ ከመንግሥትህ እንደማስወጣህ በጌታዬ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እምልልሃለሁ›› አለው፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም እየፈራ የዮስጦስን ፈቃድ ይፈጽምለት ዘንድ ከሚስቱ ከታውክልያና ከልጁ ከአቦሊ ጋር ወደ ግብፅ እንዲወስዷቸው አዘዘ፡፡ እንዲያባብለውም ለእስክንድርያው መኮንን ጻፈለት፡፡
የእስክንድርያውም ገዥ እጅግ ፈርቶ ዮስጦስን ‹‹ጌታዬ ዮስጦስ ሆይ! እንዲህ አታድርግ ለአንተ ክብርህ ይሻልሃል…›› እያለ ሊያግባባው ሲሞክር ቅዱስ ዮስጦስ ግን ‹‹የመንግሥትህን ክብር እንዳታጣ ሰማዕትነቴን ፈጸምልኝ›› አለው፡፡ እርሱም ፈርቶ ወደ ላይኛው ግብፅ ወደ እንዴናው ገዥ ላከው፡፡ ከአገልጋዮች ጋራ ሚስቱን ቅድስት ታውክልያን ፃ ወደምትባል አገር ሲልካት ልጁን አቦሊን ደግም ወደ ሀገረ ብስጣ ላከው፡፡ ከአገልጋዮቹም ውስጥ እንዲያገለግሏቸው በማለት አንድ አንድ ሰጣቸው፡፡ ሚስቱ ቅድስት ታውክልያም ሰማዕትነቷን በድል ፈጽማ የክብርን አክሊል ተቀዳጀች፡፡
ቅዱስ ዮስጦስንም የእንዴና ከተማ ጣዖት አምላኪዎች ብዙ ካሠቃዩት በኋላ የካቲት 10 ቀን በሰይፍ ራሱን ቆርጡትና የተመኘውን ሰማዕትነቱን በድል ፈጸመ፡፡ ከሥጋውም ብዙ ድንቅ የሆኑ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡ ለሕሙማንም ታላቅ ፈውስ ሆነ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ነቢዩ_ዮናስ
በዚህች ቀን ታላቁ ነቢይ ዮናስ ከዓሣ አንበሪ ሆድ ለወጣበት መታሰቢያው ነው። ይህም እውነተኛ ነቢይ ዮናስ የሲዶና ክፍል በምትሆን ስራጵታ በምትባል አገር ለምትኖር መበለት ልጅዋ የሆነ ነቢይ ኤልያስም ከሙታን ለይቶ ያሥነሣው ኤልያስንም ያገለገለውና የትንቢት ጸጋ የተሰጠው ነው።
ከዚህም በኋላ ስሙ ከፍ ከፍ ያለና የተመሰገነ እግዚአብሔር ወደ ነነዌ አገር ሒደህ ሀገራቸሁ እስከ ሦስት ቀን ድረስ ትጠፋለች ብለህ አስተምር ብሎ አዘዘው።
እግዚአብሔርም ይህን በአለው ጊዜ ዮናስ በልቡ እንዲህ ብሎ አሰበ እግዚአብሔር ሊአጠፋቸው ቢወድ ኖሮ ሒደህ አስተምር ብሎ ባላዘዘኝ ነበር እግዚአብሔር መሐሪ ነውና ሲምራቸው እኔ በእነርሱ ዘንድ ሐሰተኛ ነቢይ እንዳልባል እፈራለሁ ከቶ ትምህርቴን አይቀበሉኝም ወይም ይገድሉኛል ወደዚያች አገርም ሒጄ እንዳላስተምር ከእግዚአብሔር ፊት ብኰበልልና ብታጣ ይሻለኛል።
ወንድሞች ሆይ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ፊት ለፍጡር ማምለጥ ይቻለዋልን። ይህስ ዮናስ የእስራኤልን ልጆች ከሚያስተምሩ ነቢያት ውስጥ ሲሆን ይህን አያውቅምን ነገር ግን አግዚአብሔር በረቀቀ ጥበቡ ይህን አደረገ እንጂ የዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት አድሮ መውጣት መድኃኒታችን በመቃብር ሆድ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት አድሮ ከዚህ በኋላ ከሙታን ተለይቶ ለመነሣቱ ምልክት ይሆን ዘንድ ነው።
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_16
#ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌሉ_ዘወርቅ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ስድስት በዚች ቀን ቅዱስ አባት ወንጌሉ ዘወርቅ የተባለ ዮሐንስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከሮሜ አገር ነበር አባቱም አጥራብዮስ የሚባል ባለጠጋ ነው። የእናቱም ስም ብዱራ ይባላል። እንዲማርም ለመምህር ሰጡት ቅዱሳት መጻሕፍትንም ተማረ።
ከዚህም በኋላ ገበታው የወርቅ የሆነ ወንጌልን ያሠራለት ዘንድ አባቱን ለመነው አባቱም እንደፈለገው አሠራለት ሁል ጊዜም ያነበው ነበር። በሚያነብ ጊዜም አባቱና እናቱ ደስ ይላቸው ነበር።
በዚያም ወራት ወደ ኢየሩሳሌም የሚጓዝ መነኵሴ ወደ እነርሱ መጣ በእነርሱም ዘንድ አደረ ከቅዱስ ዮሐንስም ጋራ ተነጋግሮ የምኵስናን ሥራ አመሰገነለት ይህን ዓለም እስከ ናቀና እንደ እርሱ መነኰስ ይሆን ዘንድ እስከ ወደደ ድረስ ልቡን ማረከው።
ያን ጊዜም ያ መነኰስ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ ሁለተኛም ተመልሶ እንደ ልማዱ በእነርሱ ዘንድ አደረ። ቅዱስ ዮሐንስም መነኵሴው ወደ ገዳሙ ይወስደው ዘንድ ፈለገ መነኲሴውም አባትህን እፈራዋለሁ ልወስድህ አይቻለኝም አለው። ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሱ ጋራ እንዲወስደውና ነፍሱን እንዲያድን አማለው።
ከዚህም በኋላ በስውር ወሰደው በመርከብም ተጭነው ያ መነኰስ ወደሚኖርበት ገዳም ደረሱ የገዳሙም አበ ምኔት የወጣቱን ዮሐንስን መልኩን አይቶ አደነቀ። ቅዱስ ዮሐንስም የምንኵስናን ልብስ ያለብሰው ዘንድ አበ ምኔቱን ለመነው አበ ምኔቱም ልጄ ሆይ የምንኵስና ሕግ እጅግ ጭንቅ ናት እኮ አለው። አብዝቶም በለመነውና ግድ ባለው ጊዜ ራሱን ላጭቶ አመነኰሰው።
ከዚህም በኋላ ከጾም ከትጋትና ከኀዘን የተነሣ ሥጋው ደርቆ አጥንቶቹ እስከሚታዩ ድረስ በብዙ ተጋድሎ ተጸመደ። አበ ምኔቱም ልጄ ሆይ ለሰውነትህ እዘን ድካምህንም ቀንስ መነኰሳቱም ሁሉ እንደሚሠሩት ሥራ እያለ ያጽናናውና ይመክረው ነበር።
በዚህ ተጋድሎም ሰባት ዓመት በሆነው ጊዜ ከእነርሱ በረከትን ትቀበል ዘንድ ከመሞትህ በፊት ወደ አባትህና እናትህ ሒድ የሚል ራእይ አየ። ይህንንም ራእይ በሦስት ሌሊቶች ውስጥ አየ ለአበ ምኔቱም እንዴት እንዳየ ነገረው አበ ምኔቱም ይህ ራእይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለ ሆነ ልትሔድ ይገባሃል አለው። ከገዳሙም በወጣ ጊዜ አንድ ምስኪን ሰው ጨርቅ ለብሶ አገኘ። የእርሱንም ልብስ ሰጥቶት ጨርቁን ወሰደ።
ወደ አባቱ ቤትም በደረሰ ጊዜ በትንሽ ጎጆ ውስጥ በአባቱ ደጅ በጾም በጸሎትና በስግደት እየተጋደለ ባሮች ከአባቱ ማዕድ የሚጥሉለትን ፍርፋሪ እየተመገበ ሰባት ዓመት ኖረ። እናቱም በአንጻሩ ስታልፍ የሚከረፋ ሽታው ያስጨንቃት ነበር። ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰባት ቀን በኋላ ከዚህ ዓለም ትወጣለህ ብሎ ነገረው።
ያን ጊዜም ወደ እናቱ ልኮ ልመናውን ልትሰማ ወደ እርሱ መጣች ልጅዋም እንደሆነ ፈጥኖ አልነገራትም ነገር ግን በዚያች በታናሽ ማደሪያ ውስጥ በላዩ ባለ ጨርቅ እንድትቀብረው የለበሰውንም ጨርቅ እንዳትለውጥ አማላት። ከዚህም በኋላ ያንን የወርቅ ወንጌል ሰጣት። እንዲህም አላት ይህን መጽሐፍ አንብቡ እኔንም አስቡኝ።
አባቱም በመጣ ጊዜ ያንን የወርቅ ወንጌል አሳየችው እርሱም ለልጁ ያሠራለት ወንጌል እንደሆነ አወቀ። አባቱና እናቱም ወደ እርሱ ሔደው ስለ ልጃቸው ጠየቁት እርሱም ከዚህ ጨርቅና ከዚህ ትንሽ ማደሪያዬ ውስጥ በቀር በሌላ እንዳትቀብሩኝ ማሉልኝ አላቸው።
በአማላቸውም ጊዜ እርሱ ልጃቸው እንደሆነ ነገራቸው ያን ጊዜም ጮኹ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ የሮሜ ከተማ ሽማግሌዎችና ሕዝቡ ሁሉ ተሰበሰቡ ሰባቱ ቀንም ሲፈጸም ቅዱስ ዮሐንስ አረፈ። እናቱም መሐላዋን ረስታ አስቀድማ ለሠርጉ ያዘጋጀቻቸውን ያማሩ ልብሶች አውጥታ ገነዘችው። በዚያችም ጊዜ ታመመች አባቱ ግን መሐላውን አስታውሶ እነዚያን ያማሩ ልብሶች አስወገደ በጨርቆቹም ገነዙት በዚያ በትንሹ ማድሪያም ውስጥ ቀበሩት ከሥጋውም በሽተኞች የሚፈወሱበት ታላቅ ድኅነት ተገኘ።
ከዚህም በኋላ በስሙ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ሥጋውን በውስጧ አኖሩ። ከእርሱም ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
https://youtube.com/@finotebirhan12
ውድ የተከበራችሁ የሰንበት ት/ቤታችን አባላት ይህ ሥርዓተ አምልኮ ዘፍልሰታ የሚለው መጽሐፍ በሰ/ት/ቤታችን የልማት ሱቅ እየተሸጠ ይገኛል። እርስዎም መጽሐፉን በመግዛት እንዲያነቡ ጋብዘንዎታል።
የፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት ልማት ሱቅ
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
ማስታወቂያ
ዛሬ 15/11/15 ዓ.ም በቦታ እጥረት ምክንያት የቅዳሜ መደበኛ ትምህርት የማይኖር መሆኑን እናሳውቃለን። ሳምንት 22/11/15 ዓ.ም ጀምሮ በመደበኛው ሰዓት ትምህርቱ የሚቀጥል ይሆናል።
ሐዋርያትም የምድራዊ ንጉሥ ጭፍራ መሆንን እንዲተዉ ፈረሶቹንና የጦር መሣሪያውንም እንዲመልሱለት ክብር ይግባውና በክርስቶስ በግልጥ እንዲአምኑ አዘዟቸው። እነዚያ ጭፍሮቹም ወደ ንጉሣቸው ጰራግሞስ ሔደው በፊቱ ቆሙ ታመጧቸው ዘንድ የላክኋችሁ እነዚያ ሁለት ባለ ሥራዮት ወዴት አሉ አላቸው። የልጅህን ዐይኗን በማዳን በጎ በሠሩልህ ፈንታ ለምን በክፋት ትፈልጋቸዋለህ አሉት። ከዚህም ጥሩራቸውንና ትጥቃቸውን ፈትተው ገንዘብህን ውሰድ እኛ ግን ከአንተ የተሻለ ንጉሥ አግኝተናል ይኸውም የጴጥሮስና የጳውሎስ አምላክ ነው ብለው ከፊቱ ጣሉለት። በሰማ ጊዜም ደነገጠ ተቆጥቶም እስከሚገድላቸው ድረስ በወህኒ ቤት ይጨምሯቸው ዘንደ አዘዘ።
ከዚህ በኋላም ራሱ ይይዛቸው ዘንድ ተዘጋጀ የጦር መሣሪያውንም አዘጋጀ ወደ ፊልጶስ አገር ሔደው እስከ መሠረቷ ያጠፏት ዘንድ ሃያ ሺህ አራት መቶ እግረኞች ጭፍሮችን አዘዛቸው። ቅድስ ጴጥሮስም በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ቅዱስ ጳውሎስን እንዲህ አለው። ወንድሜ ሆይ አገርን እንዳያጠፋ ሳይወጣ ወደ ጰራግሞስ ተነሥ እንሒድ አለው ከዚህም በኋላ ጸሎትን ጸለዩ ወጥተውም በደመና ተጫኑ በቤተ መንግሥት መካከልም አወረዳቸውና በጰራግሞስ ፊት ቆሙ እንዲህም አሉት እነሆ እኛ በፊትህ ነን ስለ እኛ አገርን አታጥፋ። ያን ጊዜም ጭፍሮች እንዲመለሱ አዘዘ።
ሐዋርያትንም እንዲህ አላቸው አገሩን ሁሉ በሥራይ የምታጠፉ ሥራየኞች አናንተ ናችሁን እነርሱም ይህ ሥራ ለእኛ አይገባም አሉት። ሁለተኛም ኃጢአታችሁ ነው ወደዚህ ያመጣችሁ አላቸው።
ችንካር ያላቸው ሁለት የራስ ቁሮችን ከብረት እንዲሠሩ አቃቂርንም እንዲመሉአቸው በእሳትም አግለው በሐዋርያት ራስ ላይ እንዲደፉአቸው አዘዘ እንዲሁም አደረጉባቸው። ያን ጊዜም ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ ጸለየ አቤቱ ፈጣሪዬ ሆይ የጌትነትህን ኃይል በጰራግሞስ ላይ ግለጽ። ያን ጊዜም ጰራግሞስ ከወገኖቹ ሁሉ ጋር በነፋስ ውስጥ ተዘቅዝቆ ተሰቀለ። በዚያን ጊዜም ጌቶቼ ሆይ ይቅር በሉኝ ከዚህ ፆዕርም አድኑኝ እያለ ጮኸ የእንዶር ንጉሥ አስቶኛልና የተረገመ ይሁን በእናንተም ላይ ክፉ የሚናገር ሁሉ የተረገመ ይሁን አለ። ቅዱስ ጴጥሮስም የታሠሩትን ጭፍሮች ይፈቷቸው ዘንድ እስከምታዝ ከዚህ ስቅላት አትወርድም አለው እርሱም ወደ ልጁ ወደ ሎይ ተጣርቶ ትፈታቸው ዘንድ አዘዛት እርሷም አንዳዘዛት ፈታቻችው።
ቅዱስ ጴጥሮስም ዳግምኛ አለው አሁንም ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም በምድር ላይም እንደእኔ ያለ ርኩስ የለም ብለህ ካልጻፍህ አትወርድም ይህችንም በከተማው መካከል ያነቧት ዘንድ ታዝዛለህ። ንጉሡም ወረቀትንና ቀለምን ታቀብለው ዘንድ ወደ ልጁ ተጣራ እርሷ ብቻዋን ከስቅላት ቀርታ ነበርና ባመጣችለትም ጊዜ ቊልቊል ተሰቅሎ እያለ ጻፈ በከተማውም መካከል ያነቧት ዘንድ ላካት።
ያን ገዜም ጰራግሞስንና ወገኖቹን አወረዷቸው ወደ ሐዋርያትም መጥተው ከእግራቸው በታች ሰገዱላቸው ንጉሡም ጌቶቼ ይቅር በሉኝ እኔ በአምላካችሁ አምናለሁ አለ ሕዝቡም ሁሉ ሕያው በሆነ አምላካችሁ እናምናለን እያሉ ከሐዋርያት እግር በታች ወድቀዉ ሰገዱ።
እነርሱም ሃይማኖትን አስተምረው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው ጭፍሮችንም አጠመቋቸው። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን አንድ ሆኑ። ቤተ ክርስቲያንንም ሠሩላቸው ከአዋቂዎቻቸውም ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾሙላቸው። ነገረ ምሥጢርንም እያስገነዘቡአቸው በእነርሱ ዘንድ ኖሩ። ሃይማኖታቸውንም ይጸና ዘንድ ቅዱሳት መጻሕፍትን ሰጧቸው። እንዲህም አሏቸው በሃይማኖታችሁ ጽኑ እኛ ካስተማርናችሁ ትምህርት አትናወጹ ወደ እናንተም እንመለሳለን። ከዚህም በኋላ ሰላምታ ሰጥተዋቸው ወደ ፊልጶስ ሀገር ሔዱ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ተስፋ_ሐዋርያት_ዘዋልድባ
ዳግመኛም በዚህች እለት የዋልድባው አቡነ ተስፋ ሐዋርያት የተሰወሩበት ዕለት ነው፡፡ አባታቸው ተክለ ሐዋርያት ሲባሉ እናታቸው ወለተ ሐዋርያት ይባላሉ፡፡ የአባታቸው የትውልድ ቦታ ሰሜን ጎንደር ሲሆን የእናታቸው ደግሞ ሽሬ ነው፡፡
በዋልድባ ከሳሙኤል ዘዋልድባ ቀጥለው በገዳሙ የተሾሙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ይኸውም የሆነው በአቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ትእዛዝ መሠረት ነው፡፡
አቡነ ተስፋ ሐዋርያት በአቡነ ሳሙኤል መቃብር ላይ የፈለቀውን ፀበል ለአትክልት አንድ ጊዜ ብቻ በማጠጣት ለብዙ ጊዜ ዳግመኛ አያጠጡትም ነበር፡፡ ዛሬም ድረስ በዋልድባ አካባቢ ያለው የለምነት ምሥጢር ይኸው ነው፡፡
አቡነ ተስፋ ሐዋርያት ልዩ ስሙ አባ ነፅዓ በተባለው ቦታ ገዳማቸውን ከመሠረቱ በኋላ በዋልድባ ያለውን የአንድነት ማኅበሩን በከፍተኛ ሁኔታ አጠናክረውታል፡፡ በጣም ብዙ መነኮሳትንም አፍርተዋል፡፡ ጻድቁ በታላቅ ተጋድሎአቸው በእጅጉ ይታወቃሉ፡፡
በመጨረሻም ሞትን ሳይቀምሱ በዚህች ዕለት ተሰውረዋል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_15
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን የሶርያ ሰው #ቅዱስ_አባት_ኤፍሬም አረፈ፣ #ቅዱሳን_ሐዋርያት_ጴጥሮስና_ጳውሎስ በንጉሥ ጰራግሞስ ላይ ተአምራትን አደረጉ፣ የዋልድባው #አቡነ_ተስፋ_ሐዋርያት የተሰወሩበት ዕለት ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ኤፍሬም_ሶርያዊ (አፈ በረከት)
ሐምሌ ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን የሶርያ ሰው ቅዱስ አባት ኤፍሬም አረፈ። ይህም ቅዱስ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች ሀገር ነው አባቱም ክብር ይግባውና የክርስቶስን አምልኮት የሚጠላ የጣዖት ካህን ነበር።
በዚያን ጊዜም የእግዚአብሔር ቸርነት ቀሰቀሰችውና አነሳሥታ የንጽቢን ጳጳስ ወደሆነው ወደ አባ ያዕቆብ ወሰደችው እርሱም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው በእርሱም ዘንድ በጾምና በጸሎት ያለማቋረጥ እየተጋደለ ለብዙ ዘመናት ኖረ።
የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት አሕዛብን ተከራክሮ ይረታቸው ነበር። ኒቅያ በሚባል ከተማ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ በተደረገ ጊዜ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከአባ ያዕቆብ ጋራ ወደ ቅዱሳን ጉባኤው ሔደ።
ከሀዲው አርዮስንም አውግዘው ከለዩት በኋላ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም በዚያች ሌሊት ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ አየ ከዚህ ራእይም የተነሣ አደነቀ ይገልጽለትም ዘንድ ወደ ጌታ ጸለየ ይህ የቂሣርያ ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ባስልዮስ ነው የሚል ቃል ከሰማይ ወደርሱ መጣ።
ቅዱስ ኤፍሬምም ያየው ዘንድ ወድዶ ወደ ቂሣርያ ሀገር ተጓዘ በደረሰም ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በማእዘኑ በኩል ቆመ ቅዱስ ባስልዮስንም ወንጌልን ሊያነብ በወጣ ጊዜ ዋጋው ብዙ የሆነ ከወርቅ የተሠራ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አየው። ሦስት ምልክቶችንም እሰኪያይ ድረስ ተጠራጠረ ምልክቶችም እኒህ ናቸው ነጭ ርግብ መጥታ በራሱ ላይ አረፈች ሁለተኛም በልብሱ ላይ የሚያርፉ ተዋሐስያን ይቃጠሉና ይረግፉ ነበር። ሦስተኛም ከአፉ የእሳት ነበልባል ወጥቶ በምእመናን ላይ ያድር ነበር።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ባስልዮስ ቅዱስ ኤፍሬምን በስሙ ጠራውና እርስ በርሳቸው ሰላምታ ተለዋወጡ። በአስተርጓሚ ይነጋገሩ ጀመሩ። የየራሳቸውንም ቋንቋ ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልይ ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመነው። በጸለየ ጊዜም ተገልጾላቸው ያለ አስተርጓሚ ተነጋገሩ።
ከዚህ በኋላም ቅዱስ ኤፍሬምን ዲቁና ሾመው ከጥቂት ወራትም በኋላ ቅስና ሾመው ከእርሱም ብዙ ትሩፋቶች ተገለጡ በመንፈሳዊ ተጋድሎ ሁሉ ተጋደለ። አንዲት በወገን የከበረች ባለ ጸጋ ሴት ነበረች ራስዋንም ለካህን ለማስመርመር ታፍር ነበር ከታናሽነቷ ጀምራ የሠራችውን ኃጢአቷን ሁሉ ጽፋ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አመጣች። አባቴ ሆይ በዚህ ክርታስ ውስጥ ያሉት ኃጢአቶቼ ይደመሰሱ ዘንድ ተናገር ብላ ለመነችው እርሱም እንዳልሺው ይሁንልሽ አላት።
እርሷም ክርታሱን በገለጠች ጊዜ ከአንዲት ኃጢአትዋ በቀር ኃጢአቷ ሁሉ ተደምስሶ አገኘች ያችም ኃጢአት አስጨናቂና ታላቅ ኃጢአት ነበረች።
ባገኘቻትም ጊዜ ያቺን የቀረች ኃጢአቷን ያጠፋላት ዘንድ አልቅሳ ለመነችው እርሱም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሒጂ እርሱ ይህችን የቀረች ኃጢአትሽን ያስተሠርይልሻል አላት። ወዲያውም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሔዳ ከርሷ የሆነውን ሁሉ ነገረችው። እርሱም እንዲህ አላት ፈጥነሽ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ሒጂ ግን ሙቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱት ታገኝዋለሽ ሳትጠራጠሪም ይህችን ክርታስ በላዩ ጣይ ይደመሰስልሻል።
ያቺም ሴት ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ተመለሰች ሙቶ ተሸክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱትም አገኘችው። ያንንም ክርታስ በአስክሬኑ ላይ ጣለችው ወዲያውኑም ተደመሰሰላት። ይህም ቅዱስ ኤፍሬም ብዙ ተአምራቶችን አድርጓል በዘመኑም ዲዳን የሚባል አንድ ከሀዲ ተነሣ ይህም አባት ኤፍሬም ተከራክሮ ረታው።
እጅግም ብዙ የሆኑ ዐሥራ አራት ሽህ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋ ነው። አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል። መልካም የሆነ ገድሉንም በፈጸመ ጊዜ ወደ ወደደው ወደ እግዚአብሔር ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱሳን_ሐዋርያት_ጴጥሮስና_ጳውሎስ
በዚህችም ቀን ለአባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስ በንጉሥ ጰራግሞስ ላይ ተአምራትን አደረጉ። አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍልሰት በኋላ ደመና ነጥቆ ወሰዳቸውና በቤተ መንግሥት መካከል አወረዳቸው ንጉሥ ጰራግሞስም በአያቸው ጊዜ ደንግጦ እናንተ ምንድን ናችሁ አላቸው። እነርሱም መንግሥታትን ሁሉ የሚያጠፋ የሚሰሙትንም ማዳን የሚችል የሕያው እግዚአብሔር ልጅ የክርስቶስ ባሮች ነን አሉት።
ንጉሡም ነገራችሁ ትክክለኛ መሆኑን እንዴት ማወቅ እችላለሁ አላቸው። ከዚህ በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ያደረጋቸውን ድንቆችንና ተአምራቶቹን ነገሩት።
የቀኝ ዐይኗን ወፍ ያወጣው አንዲት ልጅ አለችኝ እርሷን ካዳናችኋት በአምላካችሁ አምናለሁ አላቸው ልጅህን ወደ እኛ አምጣ አሉትና ልጁን ወደ እነርሱ አመጣት። ሐዋርያትም ወደ እግዚአብሔር ጸልየው እጆቻቸውን በዐይኗ ላይ አኖሩ። ያን ጊዜም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ዳነች። ንጉሡና ሕዝቡ ሁሉ አይተው ከሐዋርያት እግር በታች ሰገዱ ክብር ይግባውና በጌታችንም አመኑ።
ከዚህም በኋላ ሐዋርያት ክብር ይግባውና ጌታችን እንዳዘዛቸው ወደ ሀገረ ፊልጶስ ሔዱ። ሰይጣንም በእንዶር ንጉሥ ተመስሎ አጋንንትን በጭፍራ አምሳል አስከትሎ ወደ ንጉሥ ጰራግሞስ መጣ በሥራያቸው አገርን ሳያጠፉ እኒህን ሁለቱን ሥራየኞች ፈጥነህ የማታጠፋቸው ለምንድነው አለው።
የንጉሥ ጰራግሞስም ልብ ወደ ክህደት ተመለሰ። ሐዋርያትንም ያመጧቸው ዘንድ ዐሥር ሺህ ጭፋሮችንና ሁለት መቶ ፈረሰኞችን ላከ ጭፍሮችም ሔደው ከተማዋን ከበቧት የከተማዋ ሰዎችም ደንግጠው ለሐዋርያት ነገሩዋቸው። ሐዋርያትም ከከተማው፤ ወጥተው በጭፍሮቹ ፊት ቁመው ርዳታን ይልክላቸው ዘንድ ወደ ጌታችን ጸለዩ።
ያንጊዜም የጭፍሮቹ ፈረሶች ወደ ሐዋርያት ተመለሱ እግሮቻቸውንም አስተካክለው ተንበርክከው ሰገዱ እንደሚያለቅስም በቃጪን ድምጽ ጮኩ። ከፈረሶችም አንዱ ድምፁን ከፍ ከፍ አድርጎ እንዲህ ብሎ እንደ ሰው ተናገረ እናንት ሰነፎች የጰራግሞስ ጭፍሮች ክብር ይግባውና የክርስቶስን ጭፍሮች ጴጥሮስንና ጳውሎስን ለምን ትፈልጓቸዋላቸሁ ሥራየኞችስ ለምን ትሏቸዋላችሁ እነርሱ ግን ሥራይንና የሰይጣንን ሥራ ሁሉ ሊያጠፉ መጥተዋል። ክብር ይግባውና ከንጉሣቸው ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በነጫጭ ፈረሶች ተቀምጠው አታዩአቸውምን ለክብር ንጉሥ ለክርስቶስ ጭፍሮቹ ትሆኑ ዘንድ ስሞቻችሁም በሕይወት መጽሐፍ ይጻፍ ዘንድ ስለ እናንተ ይለምናሉ። እኛ እንኳ እንስሳ ስንሆን ለአምላካችው እንሰግዳለን ፈረሱም ይህንን ተናግሮ ዝም አለ።
ከዚህም በኋላ እንዲህ የሚል ቃል ተሰማ ሐዋርያቶቼ ሆይ ሐዲሶች አትክልቶችን ቸለል አትበሏቸው። ያን ጊዜም ሕዝቡ ሁሉ ዐይኖቻቸውን ቀና አድርገው በታላቅ ክብር ወደ ሰማይ ሲዐርግ ጌታችንን አዩት እነዚያም ዐሥር ሺህ ሁለት መቶ ጭፍሮች ክብር ይግባውና በጌታችን በእየሱስ ክርስቶስ አመኑ ለሐዋርያትም ተገዙላቸው።
ተስፋ መቁረጥን በልባቸው አሳደሩባቸው፡፡ በአጋንንት ምክንያት ይህም እንደሚመጣባቸው አባ እንጦንስ አስቀድመው ነግረዋቸው ነበር፡፡ ወደ አባ እንጦንም በመሄድ በአጋንንቱ የደረሰባቸውን ፈተናና ጾር ነገሯቸው። አባ እንጦንስም አመንኩሰው እንዲጸኑ በመምከር ወደ በዓታቸው ሸኟቸው፡፡ አንድ እርኩስ መንፈስ ያደረበት ባሕታዊ አግኝቶ ትንሣኤ ሙታንን አላምንም ቢላቸው ሙት አስነሥትው አሳይተው አሳምነውታል፡፡ ሙቱንም አጥምቀው አምነኩሰውት 7 ዓመት በተጋድሎ ኖሮ በሰላም ዐረፈ፡፡
አባ መቃርስ በበረሃ ውስጥ ራቁታቸውን ጌታችን ከብርዱም ሆነ ከሙቀቱ እየጠበቃቸው 40 ዘመን የኖሩ ጻድቃንን አገኟቸውና ‹‹እንደ እናንተ እንድሆን ምን ላድርግ?›› ቢሏቸው ‹‹ወደ በዓትህ ተመልሰህ ስለ ኃጢአትህ አልቅስ አንተም እንደ እኛ ትሆናልህ›› አሏቸው፡፡ አባ መቃርስም የጻድቃኑን በረከታቸውን ተቀብለው ወደ በዓታቸው ተመልሰው ማልቀስ ጀመሩ፡፡ ጻዲቁ በመጨረሻ ነፍሳቸውን መላእክት ሲያሳርጓት ይፈትኗቸው የነበሩ አጋንንት ‹‹መቃርስ ሆይ አመለጥከን አሸነፍከን…›› እያሉ ሲጮኩ አባ መቃርስም ‹‹እስከ ዛሬ ገና ነኝ፣ በጌታዬ በቀኙ ልቁም በግራው አላወኩምና›› ብለው በትሕትና መለሱላቸው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አሞንዮስ
ዳግመኛም በዚሀች ዕለት የሰማዕቱ የአሞንዮስ መታሰቢያቸው ሆነ፡፡ ጨካኙ አርያኖስ የክርስቲያን ደም እንደውኃ እያፈሰሰ ወደ እስና አገር በደረሰ ጊዜ ብዙ ሰዎች ተሰብስበው በአባ አሞንዮስ ሥር ተቀምጠው ሃይማኖትን ሲማሩ አገኛቸውና ሁሉንም ይዞ ገደላቸው፡፡ አባ አሞንዮስን ግን አሥሮ ወስዶ ለጣዖታቱ እንዲሰግዱና እንዲሠው አዘዛቸው፡፡ አባ አሞንዮስ ግን ‹‹ከንቱ የሆነ የእንቆቅልሽ ጨዋታህን ብላሽ የሆነ ነገርህንም መስማት አልወድም፣ የረከሱ ጣዖቶችህንም ማየት አልፈልግም›› ብለው ለመኮንኑ ለአርያኖስ መለሱለት፡፡ አርያኖስም በዚህ ጊዜ እጅግ በቁጣ ተመልቶ አባታችንን በሕይወት ሳሉ እሳት ውስጥ እንዲጣሉ አዘዘ፡፡
አባታችንም ወደ እሳቱ ውስጥ ከመጣላቸው በፊት እጅና እግራቸውን እንደታሰሩ ስለ አርያኖስ ጸለዩለት፡፡ ጸሎታቸውንም ከፈጸሙ በኋላ አርያኖስም ተመልሶ እርሱም ራሱ ሰማዕት እንደሚሆን በእርሱ ላይ ትንቢት ተናገሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ አባ አሞንዮስ ወደ እሳቱ ተወርውረው ያማረ ሰማዕትነታቸውን በድል ፈጸሙ፡፡ የድል አክሊልንም ተቀዳጁ፡፡
ሥጋቸውንም እሳቱ ከነደደበት ቦታ ባወጡ ጊዜ የእሳቱ ነበልባል ምንም አልነካቸውም ነበር፡፡ ከሥጋቸውም ብዙ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡
በአባ አሞንዮስም ትንቢት መሠረት ጨካኙ መኮንን አርያኖስም በመጨረሻ ዘመኑ በጌታችን አምኖ ሰማዕት ሆኖ በክብር አርፎ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀብሏል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
https://t.me/finotebirhan12
የዩቲዩብ ቻናላችን
https://youtube.com/@finotebirhan12
ሐምሌ_14
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ አራት በዚች ቀን የጌታ ክርስቶስ ጭፍራ #ቅዱስ_አብሮኮሮንዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የታላቁ #አባ_መቃርስ እና #የሰማዕቱ_አሞንዮስ መታሰቢያቸው ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አብሮኮሮንዮስ
ሐምሌ ዐሥራ አራት በዚች ቀን የጌታ ክርስቶስ ጭፍራ ቅዱስ አብሮኮሮንዮስ በሰማዕትነት አረፈ። የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ከኢየሩሳሌም ነው የአባቱ ስም ክርስቶፎሮስ ነው ትርጓሜውም ክርስቶሰን የለበሰ ማለት ነው። ክርስቲያንም ነበረ የእናቱም ስም ቴዎዶስያ ነው እርሷ ግን ጣዖታትን ታመልክ ነበረች።
አባቱም በአረፈ ጊዜ እናቱ ወሰደችው ከእርሱም ጋራ ብዙ ገንዘብ ይዛ ወደ አንጾኪያ ከተማ ሔደች ልጅዋንም በእስክንድርያ ከተማ ገዥ አድርጎ ይሾመው ዘንድ ለዲዮቅልጥያኖስ እጅ መንሻ ሰጠችው እርሱም ሾመው የሹመት ደብዳቤውንም ጽፎ ክርስቲያኖችን እንዲአሠቃይ አዘዘው።
ከአንጾኪያም ከተማ ወጥቶ ጥቂት እንደተጓዘ ወደእርሱ የሚያስፈራ ቃል ከሰማይ መጣ በስሙም ጠርቶ እንዲህ አለው ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ እንዳዘዘህ ብታደርግ አንተ በክፉ አሟሟት ትሞታለህ።
እርሱም ራስህን ትገልጥልኝ ዘንድ ጌታዬ ሆይ እለምንሃለሁ አለው ወዲያውኑም የብርሃን መስቀል ታየው ዳግመኛም በኢየሩሳሌም የተሰቀልኩ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ነኝ የሚለውን ቃል ሰማ።
ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ ተመልሶም ከአንጥረኛ ዘንድ የወርቅ መስቀል አሠራ ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ከተማ ተጓዘ በጉዞውም ውስጥ ሊገድሉት ዐመፀኞች አረማውያን ተነሡበት እርሱም በእነርሱ ላይ በርትቶ ክብር ይግባውና በጌታ ክርስቶስ መስቀል ድል አደረጋቸው።
እናቱም በጦርነት ላይ ለረዱህና ላዳኑህ አማልክት መሥዋዕትን ሠዋ አለችው እርሱም እንዲህ አላት እኔስ አዳኝ በሆነ በመስቀሉ ኃይል ላዳነኝ ክብር ይግባውና ለእግዚአብሔር እሠዋለሁ።
ይህንንም በሰማች ጊዜ ልጅዋ አብሮኮሮንዮስ ክርስቲያን እንደሆነ ወደ ዐመፀኛው ዲዮቅልጥያኖስ ልካ ነገረችው። ዲዮቅልጥያኖስም ጭፍራ ልኮ ወደ ቂሣርያ ከተማ አስወሰደው የቂሣርያውንም ገዥ ስለ ርሱ እንዲመረምርና እንዲአሠቃየው አዘዘው።
ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ በአቀረቡት ጊዜ በፊቱ ቁሞ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ለመሞት እስቲደርስም ጽኑዕ ግርፋትን ገረፈው ከዚህም በኋላ አሠረው። በዚያችም ሌሊት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ብርሃን ውስጥ ታየው ከእርሱም ጋራ ብርሃናውያን መላእክት ነበሩ ከማሠሪያውም ፈታውና በመለኮታዊ እጁ ዳሰሰው ከቍስሎቹም ሁሉ አዳነው።
በማግሥቱም መኰንኑ ስለ ቅዱሱ ዜና ሙቶ እንደሆነ ወይም አልሞተ እንደሆነ ጠየቀ ለእርሱ የሞተ መስሎት ነበረና። ቅዱሱም በመጣ ጊዜ ጤነኛ ሁኖ አየውና መኰንኑ አደነቀ በዚያ የነበሩ ሕዝቡም አይተው እጅግ አደነቁ እንዲህም እያሉ ጮኹ እኛ በግልጥ ክርስቲያን ነን በቅዱስ አብሮኮሮንዮስ አምላክ እናምናለን። ከእነርሱም ጋራ ሁለት መኳንንትና ዐሥራ ሁለት ሴቶች እናቱ ቴዎዶስያም ነበሩ መኰንኑም ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ። እነርሱም ቆረጡአቸው። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ሐምሌ ስድስት ቀን ተቀበሉ።
ቅዱስ አብሮኮሮንዩስን ግን ምን እንደሚያደርግበት እስቲአስብ ድረስ ሦስት ቀን አሠረው ከዚህም በኋላ አውጥቶ እንዲህ አለው ልብህ እንዲመለስ ነፍስህንም እንድታድን ለአማልክትም እንድትሠዋ እነሆ በአንተ ላይ ሦስት ቀናት ታገሥኩ። ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት መኰንን ሆይ የለም ልቤ ወደ ስሕተት አይመለስም ክብር ይግባውና ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ እንደሌለ አውቄ ተረድቼአለሁ ጣዖታቱም ሁሉ ከዕንጨትና ከደንጊያ በሰው እጅ የተሠሩ ፍጡራን ናቸው እንጂ አማልክት አይደሉም አይጐዱም አይጠቅሙም።
መኰንኑም ሰምቶ እጅግ ተቆጣ ጐኖቹንም በሰይፍ እንዲሰነጣጥቁ አዘዘ አርኬላዎስ የሚባል ባለ ሰይፍም የቅዱሱን ጐኖቹን ሊሠነጥቅ እጁን ዘረጋ ያን ጊዜም እጁ ደረቀች ወድቆም ሞተ። መኰንኑም ተቆጥቶ በምድር ጥለው ይገርፉት ዘንድ አዘዘ እንደ አዘዘም ገረፉት በሰይፍም ጐኖቹን ሠንጥቀው በቍስሉ ውስጥ መጻጻ ጨመሩ እስከ ወህኒ ቤትም ድረስ በእግሩ ጐተቱት በዚያም ሁለት ቀኖች ኖረ ከዚህም በኋላ አውጥቶ እሳትን በተመላች ጕድጓድ ውስጥ ጣለው ክብር ይግባውና ጌታችንም አዳነው ምንም ምን አልነካውም።
ብዙ ከማሠቃየቱም የተነሣ መኰንኑ በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ታላቁ_ቅዱስ_መቃርስ
ዳግመኛም በዚሀች ዕለት የታላቁ አባ መቃርስ መታሰቢው ሆነ፡፡ መቃርስ (መቃርዮስ) ማለት "ቅዱሱ ለእግዚአብሔር" ማለት ነው፡፡ ከደቡባዊ ግብፅ ከተወደዱ ደጋግ ክርስቲኖች የተገኘ ታላቅ አባት ነው፡፡ አባታቸው አብርሃም እናታቸው ሣራ ይባላሉ፡፡ እነርሱም መጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዳሉት እንደ አብርሃምና ሣራ እጅግ ደጎች ነበሩ፡፡ ልጅ ግን አልነበራቸውምና በስለት መቃርስን ወለዱ፡፡ ሲያድጉም በግድ ያለፈቃዳቸው ሚስት አጋቧቸው፡፡ አባ መቃርስ ግን ወደ ሙሽራይቱ በገቡ ጊዜ ዐውቀው እንደታመሙ ሆነው ተኙ፡፡ ‹‹ከበሽታዬ ለጥቂት ጊዜ ጤና ባገኝ ወደ ገዳም ልሂድ›› ብለው ወደ አስቄጥስ በረሃ ሄዱ፡፡ መልአክም ተገልጦ ‹‹ይህች አስቄጥስ የአንተና የልጆችህ ርስት ናት›› አላቸው፡፡ ወደ ቤተሰባቸውም በተመለሱ ጊዜ ሙሽራ እጮኛቸው በድንግልና እንዳለች ሞታ ደረሱ፡፡ ከጥቂት ቀንም በኋላ እናትና አባታቸውም ዐረፉ፡፡ እርሳቸውም ንብረታቸውን ሁሉ ለድሆች መጽውተው ገዳም ገቡ፡፡ ሕዝቡም ደግነታቸውንና እውነተኛነታቸውን አይተው ትንሽ ማረፊያ ሠርተው ሌሎች እንዲያገለግሏቸው አደረጉ፡፡
ከዕለታትም በአንድ ቀን አንዲት ሴት ልጅ ከጎረምሳ አርግዛ ሳለ ጎረምሳው ‹‹አባትሽ ሲጠይቅሽ ከአባ መቃርስ አረገዝኩ በይ›› ብሎ መከራትና ለአባቷ እንደተባለችው ተናገረች፡፡ ‹‹አባ መቃርስ በግድ ደፍረውኝ አረገዝኩ›› አለች፡፡ የከተማው ሰውም አባ መቃርስን ከበዓታቸው አውጥተው ለሞት እስኪደርሱ ድረስ ደበደቧቸው፡፡ መላእክትም በሰው አምሳል ተገልጠው ዋስ ሆነው ለልጅቷም ምግቧን ሊሰጡ ተስማምተው ወደ በዓታቸው መለሷቸው፡፡ አባ መቃርስም ለራሳቸው ‹‹መቃርስ ሆይ እንግዲህ ባለ ሚስትና ባለ ልጅ ሆነሃልና ሌሊትና ቀን መሥራት ይገባሃል›› እያሉ ቅርጫቶችን እየሠፉ ለሚያገለግላቸው ልጅ እየሰጡት እርሱ ሸጦ እያመጣ ብዙውን ለዚያች በዝሙት ጸንሳ በሳቸው ላሳበበች ሴት ይሰጡ ጀመር፡፡ መውለጃዋም በደረሰ ጊዜ እስከ 4 ቀን ድረስ በጽኑ ሥቃይ ቆየች፡፡ እውነቱንም ተናግራ ንስሓ በገባች ጊዜ ወደ አባ መቃርስ ዘንድ አደረሷት፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ‹‹አባታችን ይቅር በሉን›› ብለው ከእግራቸው ላይ ሲወድቁ ይቅር ብለዋቸው ቀድሰው አቆረቧቸው፡፡
ከዚህ በኋላ መልአኩ ወስዶ አስቄጥስ ገዳም አደረሳቸው፡፡ የቅዱሳኑ የመክሲሞስና የዱማቴዎስ በዓት ወደ ሆነች ቦታም አስገብቶ በዚያ በልጆቻቸው ቦታ ላይ በዓታቸውን እንዲያጸኑ ነገራቸው፡፡ አባ መቃርስ ወደ አባ እንጦንስ ዘንድም በመሄድ በረከታቸውንና ምክራቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡ ሰይጣናትም በእርሳቸው ላይ የሚያደርሱትን ክፉ ነገር ሲመካከሩ ይሰሟቸው ነበር፡፡ በእሳት እያቃጠሉ ፈተኗቸው፣ የዝሙት መንፈስ እያመጡም ፈተኗቸው፣ በዚህም ትዕግስትን ቢያደርጉ በሌላም ዓለማዊ ክብርን መውድን፣ ትዕቢትን፣ መመካትን፣ ታካችነትን፣ ስድብን፣ ሃይማኖት ማጣትን፣
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_13
ሐምሌ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን የሀገረ ቅፍጥ ኤጲስቆጶስ #አባ_ብስንድዮስ አረፈ፣ #ቅዱስ_አሞን ምስክር ሁኖ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ብስንድዮስ_ሊቅ_ወጻድቅ
ሐምሌ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን የሀገረ ቅፍጥ ኤጲስቆጶስ አባ ብስንድዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ሰው መንኩሶ በታላቅ ገድል ተጠመደ ቅዱሳት መጻሕፍትንም አጠና ከቅዱሳት መጻሕፍትም ውስጥ የዳዊትን መዝሙርና የነቢያትን መጻሕፍት አጥንቶ ነበር። ከነቢያት ትንቢትም አንዳንዱን መጽሐፍ ያነብ ነበረ። ትንቢቱ የሚነበብለት ነቢያም ወደርሱ መጥቶ ንባቡን እስቲፈጽም ይቆይ ነበር።
ስለርሱም እንዲህ ተባለ እርሱ እጆቹን አንሥቶ በሚጸልይ ጊዜ ጣቶቹ እንደ ፋና ይበሩ ነበር እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ።
እርሱም በዕድሜው ዘመን ሁሉ የሴት ፊት አላየም።ራሱን ወደ ምድር ያዘነብል ነበር እንጂ። በሆድዋ ውስጥ ታላቅ ደዌ የነበረባትም አንዲት ሴት ነበረች ከበዓቱ ደጅ ጠበቀችውና በድንገት አገኘችው። እርሱም ሮጠ እርስዋም ተከትላው ሮጠች። ወደርሱ መድረስም በተሳናት ጊዜ እግሩ የረገጠቻትን አንዲት እፍኝ አፈር ዘግና በእምነት በላች ከደዌዋም ፈጥና ተፈወሰች።
በአንዲት ዕለትም የሚያበሩ ሦስት ሰዎችን አየ እነርሱም አንተ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትመግባት ዘንድ አለህ እያሉ መክፈቻ ቁልፍን ሰጡት። ከዚህ በኃላ ቅፍጥ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ተሾመ። የቁርባን ቅዳሴ በሚቀድስ ጊዜም ጌታችንን እጆቹ በመሠዊያው ላይ ሁነው ይመለከተው ነበር መላእክቶቹንም በዙሪያው ቁመው ያያቸው ነበር።
በአንዲት ዕለትም አንድ ቄስ ሊቀድስ ገባ በቅዳሴ እኩሌታ ላይም በመሠዊያው ፊት እያለ ምራቁን ተፋ። ቅዳሴውም በተፈጸመ ጊዜ ይህ አባት ገሠጸው እንዲህም አለው በሚያስፈራ መሠዊያው ፊት በምትቆም ጊዜ ከእግዚአብሔር ጌትነት የተነሣ አትፈራምን የተፋኸውስ ምራቅ በመሠዊያው ዙሪያ በቆመ ኪሩብ ክንፎች ላይ እንደደረሰ አታውቅምን ።ያን ጊዜም ያንን ቄስ መንቀጥቀጥ ያዘው ተሸክመውም ወደ ቤቱ ወሰዱትና ታሞ ሞተ።
ይህም ቅዱስ አባት አንደበቱ ጣዕም ያለው ነበር በሚያነብ ጊዜ በሚያስተምርም በሚመክርም ጊዜ አይጠገብም ነበር። የዕረፍቱም ቀን በቀረበ ጊዜ አውቆ ሕዝቡን ጠራቸውና አስተማራቸው መከራቸውም በቀናች ሃይማኖትም ይጸኑ ዘንድ አዘዛቸው። ከዚህም በኃላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ።ከሥጋውም ብዙ ተአምር ተገለጠ ደቀ መዝሙሩ ከመግነዙ ጥቂት ቁራጭ ወስዶ በእምነት በሽተኞችን ሁሉ ይፈውስ ነበር።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አሞን_ሰማዕት
ዳግመኛም በዚች ቀን ከግብጽ ደቡብ ከቡና አውራጃ ጡሕ ከሚባል አገር ቅዱስ አሞን ምስክር ሁኖ አረፈ። ለዚህም ቅዱስ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ተገለጸለት ከእርሱ የሚሆነውንም ሁሉ ነገረው።
ከዚህ በኃላ ወደ እንዴናው ከተማ ሒዶ አውግስጦስ በሚባል መኮንን ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኮንኑም በመንኩራኩር ውስጥ በእሳት ላይ በመጣል በእሳት በአጋሉት በብረት ዐልጋ ላይ በማጋደም ከላም ቆዳ በተሠራ ጅራፍ በውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥ በመጨመር ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃዩት።
የራሱንም ቆዳ ገፈው በራሱ ላይ የእሳት ፍም አኖሩ እግዚአብሔርም ያጸናው ነበር ያለ ምንም ጉዳት ጤነኛ አድርጎ ያስነሣው ነበር። ከዚህም በኃላ ክብር ይግባውና እግዚአብሔር ክርስቶስ በጎልማሳ አምሳል በብርሃን ሠረገላ ላይ ሁኖ ተገለጠለትና አጽናናው እንዲህም አለው ወዳጄ አሞን እኔ ከአንተ ጋራ እኖራለሁ ስምህን የሚጠራውን መታሰቢያህን የሚደርግውን ሁሉ ወይም ገድልህን የሚጽፈውን ሁሉ እኔ በመንግሥቴ ውስጥ አስበዋለሁ እጠብቃለሁ ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጥቶት ከእርሱ ዘንድ ዐረገ።
ይህም ቅዱስ በሥጋው ሳለ ታላላቅ ተአምራቶችንና ድንቆችን አደረገ ወዲያውኑም በሰይፍ ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ። ቅዱስ ዮልዮስም በዚያ ነበረ ሥጋውን ወስዶ በመልካም ልብስ ገነዘው ከሁለት አገልጋዮቹም ጋራ ወደ አገሩ ላከው በላይኛው ግብጽም ታላላቅ የሆኑ ድንቆችንና ተአምራቶችን እያሳየ እስከ ዛሬ አለ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_12
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የከበረ መልአክ #የመላእክት_አለቃ_ቅዱስ_ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ #አባ_ሖር በሰማዕትነት ሞተ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#የመላእክት_አለቃ_ቅዱስ_ሚካኤል
ሐምሌ ዐሥራ ሁለት በዚህች ቀን የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ የሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚች ቀን የፋርስ ንጉሥ ወደ ሆነ ወደ ሰናክሬም ሠራዊት እግዚአብሔር ላከው ከሰናክሬም ሠራዊትም መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ አርበኞች ወንዶችን ገ*ደለ።
ይህም እንዲህ ነው ሰናክሬም ኢየሩሳሌምን በከበባት ጊዜ ሕዝቅያስንና ፈጣሪው እግዚአብሔርን እየዘለፈ ወደ ሕዝቅያስ መልእክተኞችን ላከ እንዲህም አለ እግዚአብሔር ያድናችኋል እያለ ሕዝቅያስ አያስታችሁ ከእጄ የሚያድናችሁ ማን ነው።
የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስም እጅግ አዘነ ወገኖቹንና ሀገሩ ኢየሩሳሌምንም ያድን ዘንድ ማቅ ለብሶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። እግዚአብሔርም ልመናውን ተቀብሎ ወደ ፋርስ ንጉሥ ወደ ሰናክሬም ሠራዊት የመላእክት አለቃ ሚካኤልን ላከለት። ድንቅ ሥራንም ሠርቶ ኢየሩሳሌምንና የይሁዳን ሰዎች ሁሉ አዳናቸው።
ስለዚህም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ የሚካኤልን በዓል መታሰቢያ በዚች ቀን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ሖር
በዚህችም ቀን ስርያቆስ ከሚባል አገር አባ ሖር በሰማዕትነት ሞተ፡፡ አባቱም አንጠረኛ ነበር አንዲት እኅትም ነበረችው። ጐልማሳም በሆነ ጊዜ ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደ ሀገረ ፈርማ ሔደ በመኰንኑም ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑ ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው ከሥቃዩም ድኖ ተነሣ።
መኰንኑም በእጁ ላይ ጌታችን ያደረገውን ይህን ተአምር አይቶ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋራ አመነ። በሌላ መኰንን እጅም ከሚስቱና ከልጆቹ ጋራ በሰማዕትነት ሞተ።
ቅዱስ አባ ሖርን ግን ወደ እንዴናው ላከው በዚያም በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ አሠቃዩት በመንኰራኵሮችም አበራዩት ዘቅዝቀውም ሰቅለው በእሳት በአጋሉት የብረት በትር ደበደቡት።
መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘ የሰማዕትነትን አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
በዚያም ወራት ሉቀ ጳጳሳቱ አባ ቄርሎስ አረፈ። የወንጌላዊው የማርቆስ መንበርም ያለሊቀ ጳጳሳት ነበር። ስለዚህም ኤጲስቆጶሳት፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ሕዝቡ ሁሉ ተሰብስበው ይሾሙት ዘንድ በአንድ ምክር ተስማሙ ሰይጣን ግን ክፉዎች ሰዎችን አነሣሥቶ ተቃወሙት። ሹመቱንም አልፈቀዱም። ነገር ግን መንፈሳዊ አባት የነበረውን የከሊል ልጅ አባ አትናቴዎስን ሾሙት። እርሱም መንጋውን በበጎ አጠባበቅ ጠበቀ።
እርሱም በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆሳትና የሕዝብ አለቆች ዳግመኛ ተሰበሰቡና በእጃቸው ጽፈው አባ ገብርኤል እንዲሾም ፈቀዱ ሁለተኛም በሕዝቡ መካከል ሁከት ተነሣ ከሌሎችም ጋራ ዕጣ ያጣጥሉት ዘንድ ተስማሙ ስሞቻቸውንም ጽፈው በመንበሩ ላይ አኖሩ በላዩም እየጸለዩና እየቀደሱ ሦስት ቀኖች ሰነበቱ። ከዚህም በኋላ ታናሽ ብላቴና አምጥተው በውስጡ የአባ ዮሐንስ ስም ያለበትን ክርታስ አወጣላቸው። ያም አባ ዮሐንስ ተሾመ። ይህን አባ ገብረኤልን ግን ለማዕልቃ ቤተ ክርስቲያን ተከራካሪ አድርገው ሾሙት።
በዚያ ወራትም በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ላይ ችግር ሁኖ ነበር። ይህ አባ ገብርኤልም ወደ አባ እንጦንስ ገዳም ሒዶ በጾምና በጸሎት በስግደትም በቀንና በሌሊት ሲጋደል ኖረ። ከቅዱሳን መነኰሳትም ብዙዎች መልካም ራእይን አዩለት ከእርሳቸው በእስክንድርያ ከተማ የሊቀ ጳጳሳት ልብስን እንደሚአለብሱት ብዙዎች ከአሕዛብ የተመለሱ ክርስቲያኖችም እንደሚያጅቡት ያየ አለ። ደግሞም ይሾምባት ዘንድ ወደ አስቄጥስ ወደ አባ መቃርስ ገዳም ሲሔድ ያየለት አለ። ቁጥር የሌላቸውንም መክፈቻዎችን ሲቀበል ያዩ አሉ።
ከገዳሙም ሊወርድ ብዙ ጊዜ ይሻ ነበር ነገር ግን አልተቻለውም። ከዚህ በኋላ አባ እንጦንስ በራእይ ተገልጦ እንዲህ አለው ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ ከዚህ ገዳም ትወርድ ዘንድ እኔ አልፈቅድም ጊዜው ሳይደርስ አትውረድ አለው።
ከሦስት ዓመት በኋላም አንዱ አረጋዊ የከበረ መልአክ እንግዲህስ አባ ገብርኤልን ወስደው በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና ይሾሙታል እያለ እንደሚያነጋግረው ራእይ አየ። በዚያችም ቀን የሀገረ እንጣፊ መኰንን መጣ ከእርሱም ጋር ብዙዎች መሳፍንቶች ነበሩ። አባ ገብርኤልን አምጥተው በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና ይሾሙት ዘንድ የሚያዝዝ የንጉሥ ደብዳቤም ከእርሱ ጋር ነበረ።
ከዚህም በኋላ ያለ ፈቃዱ ወስደው በወንጌላዊው በማርቆስ ወንበር ላይ ሊቀ ጵጵስናን ሾሙት። በዚያችም ቀን እርሱ ለኢየሩሳሌም አንድ ጳጳስና ሌሎችንም ኤጲስቆጶሳት ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመ። ከዚህም በኋላ ሦስት ጊዜ ሜሮን አከበረ ባረከ እንደዚህም አድርጎ አንድ ዓመት ከአንድ ወር ኖረ።
በዚያን ጊዜም አባ እንጦንስ ተገልጦ እንዲህ አለው እነሆ ዕረፍትህ ቀርቦአል ከዐሥራ ስምንት ወሮች በኋላ ወደ እግዚአብሔር ትሔዳለህ የዘላለም ሕይወትንም ትወርሳለህ።
ከዚህም በኋላ በክርስቲያን ወገኖች ላይ ታላቅ መከራ ሆነ። ይህም አባት ወገኖቹን ያድን ዘንድ ወደ ጌታችን ለመነ ክብር ይግባውና ጌታችንም ልመናውን ተቀብሎ ሕዝቡን ይቅር አለ።
ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ ከመንበረ ሢመቱ ወጥቶ በምስር አገር ዓመት ሙሉ ተሠወረ። ከአንድ ምእመን በቀር ማንም አላወቀበትም በቀንና በሌሊት በገድል ከመቀጥቀጡ የተነሣም መልኩ ተለወጠ ሥጋውም ደረቀ።
ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር እርሱን ለሚፈራው ለአንድ ምእመን ሥራውን ገለጠ። እርሱም ከዚያ ቦታ አውጥቶ በሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን አስቀመጠው በጸሎትና በቅዳሴ እያገለገለ ኖረ። ድኆችንም ይጐበኛቸው ነበር። የሚሹትንም ይሰጣቸው ነበር። ወደ ርሱ የሚመጡትንም ሕዝቦች ያስተምራቸውና ያጽናናቸው ነበር።
በአንዲት ዕለትም ሊቀ ጳጳሳት አባ አትናቴዎስ በግልጽ ታየው እንዲህም አለው ስለዚህ ፈጽሞ አትዘን ከዚህ ብዙ ድካምና መከራ እግዚአብሔር ያሳርፍሃልና አነሆ ምድራዊ ኑሮህን የሚፈጽም ደዌ በአንተ ላይ ይመጣል ነገር ግን ደስ ይበልህ ታላቅ የሆነ የእግዚአብሔርን ጸጋ ተቀብለሃልና። የዘላለም ሕይወትንና የማያልቅ ተድላ ደስታንም ትወርሳለህና አለው።
በዚያን ጊዜም በሚያስጨንቅ ደዌ ታሞ እየተጨነቀ ኖረ። ስለ ነፍሱም መውጣትና በእግዚአብሔር ፊት ስለ መቆሙ ይፈራና ይደነግጥ ነበር የእመቤታችን ማርያም ሥዕልም በዚያ ነበረ። ወደርሷም አዘውትሮ ይማልድ ነበረ በዚያን ጊዜም ክብር ይግባውና ራሱ እግዚአብሔር በብሩህ ገጽ ተገለጠለት መንግሥተ ሰማያትን አግኝተሃልና ደስ ይበልህ እንጂ አትፍራ እስከ ሦስት ቀንም ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ትወጣለህ በማለት አረጋጋው። ይህንንም ብሎ ከእርሱ ተሠወረ በሦስተኛውም ቀን በሰላም አረፈ። በቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያንም በታላቅ ክብር ተቀበረ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_11
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን #ቅዱሳን_ዮሐንስና_ስምዖን በሰማዕትነት ሞቱ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ገብርኤል አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_ዮሐንስ
ሐምሌ ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን መርባስ የሚባል አገር ሰዎች የሆኑ ቅዱሳን ዮሐንስና የአባቱ ወንድም ልጅ ስምዖን በሰማዕትነት ሞቱ። የዚህ ቅዱስ ዮሐንስ እናቱ መካን ነበረች አባቱም ልጅን ይሰጠው ዘንድ ክብር ይግባውና እግዚአብሔርን ይለምነው ነበር ከዚህም በኋላ ልጁን በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ለእግዚአብሔር አገልጋይ ሊአደርገው ተሳለ።
መጥምቁ ዮሐንስም እግዚአብሔር ልጅን እንደሚሰጠው በራእይ ተገልጦ ነገረው። ይህን ቅዱስም በወለደው ጊዜ ዮሐንስ ብሎ ጠራው በመጥምቁ ዮሐንስም ስም ቤተ ክርስቲያን ሠራ። ከዚህ በኋላ አድጎ ዐሥራ ሁለት ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ የበጎች እረኛ አደረገው ምሳውንም ለእረኞችና ለመንገደኞች ሁል ጊዜ ይሰጥ ነበር እርሱ ግን እስከ ምሽት ይጾም ነበር።
አባቱም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ስለዚህ ሊአረጋግጥ ወደ ርሱ ሔደ አባቱንም በአየው ጊዜ ዮሐንስ ፈርቶ ሊሸሽ ወደደ። አባቱም የዛሬ ምሳህን አሳየኝ አለው ብላቴናውም ታይ ዘንድ ግባ አለው ወደ መጠለያውም በገባ ጊዜ አገልግሉን ትኩስ እንጀራን ተመልቶ አገኘው እጅግም አደነቀ ከልጃቸው የሆነውንም ለሚስቱ ነገራት።
ከዚያችም ቀን ጀምሮ የእግዚአብሔር ጸጋ እንደ አደረችበት አወቁ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዲማር አደረጉት እንጂ በጎችን የሚጠብቅ እረኛ እንዲሆን አልተዉትም።
ከዚህም በኋላ አባቱ ሊአጋባው ወደደ። እርሱ ግን ይህን አልወደደም። ዐሥራ ስምንት ዓመት በሆነውም ጊዜ ቅስና ተሾመ የአባቱ የወንድም ልጅ የሆነ ስምዖንም በጎቹን ትቶ መጥቶ የእርሱ ደቀ መዝሙር ሆነ። እርሱም ስለ ተአምራቱ የተናገረ ነው። እግዚአብሔር በእጆቹ ላይ ድንቆችንና ተአምራቶችን ገልጧልና። ደዌ ያለባቸውንም ሁሉ ያመጡአቸው ነበር እርሱም በዘይቱ ላይ ይጸልይና ይቀባቸው ነበር ወዲያውኑም ከደዌያቸው ይድኑ ነበር። እርሱም ወደርሱ የሚመጡትን ከኃጢአት ይርቁ ዘንድ ያስተምራቸው ነበር። ይመክራቸውና ይገሥጻቸውም ነበር። ተአምራቱም የማይቈጠር ብዙ ነው። ከተአምራቱም አንዱ ይህ ነው። በአንዲት ዕለት አንድ የንጉሥ ጭፍራ አንዲት መበለት የተሸከመችውን ገብስ ቀምቶ ለፈረሱ አበላት ያችም መበለት በዚህ ቅዱስ ዘንድ ከሰሰችው ቅዱስ ዮሐንስም ረገመው ያን ጊዜም ፈረሱ ሞተች።
ዳግመኛም የንጉሥ የጭፍራ አለቃ ግብር ሊሰበስብ መጣ አንድ ዐይኑ የታወረች አንድ አገልጋይም ነበረው። ከእርሱም ተባርኮ ወዲያውኑም የታወረች ዐይኑ ተገለጠች በእርስዋም ደኅና አድርጎ አየ። ይህም ቅዱስ የሰዎችን ሥራቸውን በግልጽ ያይ ነበር ስለ ኃጢአታቸውም ንስሓ ይገቡ ዘንድ ይገሥጻቸው ነበር።
ዜናውም በንጉሥ ማርያኖስ ዘንድ ተሰማ ለእርሱም አንዲት ሴት ልጅ ብቻ ነበረችው ወደ ሆድዋም ከይሲ ገብቶ ለሞት ተቃረበች ከዚህም በኋላ ያድኗት ዘንድ ገንዘቡን ለባለ መድኃኒቶች ሰጠ ነገር ግን አልተቻላቸውም። ከዚህም በኋላ የጭፍራ አለቃው የባሪያውን ዐይን እንደ አዳነ የቅዱስ ዮሐንስን ዜና ነገረው ንጉሡም ጭፍራ ልኮ ወደርሱ ሊአስመጣው ወደደ ቅዱስ ዮሐንስም በመንፈስ ዐወቀ እርሱ ግን የመንገዱን ድካምና ባሕሩን ይፈራ ነበር ያን ጊዜም ደመና መጥታ ነጠቀችው ሰርመላስ ከሚባል አገርም ወደ አንጾኪያ ከተማ አደረሰችው። በንጉሡም ዐልጋ ላይ አቆመችው ንጉሡም ደነገጠ ቅዱስ ዮሐንስም ወደዚህ ወዳንተ ልታስመጣኝ የተመኘኸው ምስኪን ሰው እኔ ነኝ ብሎ ነገረው። አሁንም ልጅህን አምጣት አለው ልጁንም አመጣ። በላይዋም በጸለየ ጊዜ ከይሲው ሳያሳምማት ከሆድዋ ወጣ። ንጉሡም ከቤተ መንግሥቱ ሰዎች ሁሉ ጋር ከእርሱ ተባረከ። እጅግም አደነቁ ለሚፈሩት ይህን ጸጋ የሚሰጥ የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
እጅ መንሻውንም ብዙ ገንዘብ አቀረበለት እርሱ ግን ምንም አልወሰደም። ንጉሡም በእርሱ ዘንድ ሊአኖረው ወደደ ቅዱሱ ግን አልወደደም ንጉሡም እንዳይሔድበት ቀሚሱን ያዘ ያንጊዜም ንጉሡ ቀሚሱን እንደያዘ ደመና ነጥቆ ወሰደው ቀሚሱም ተቆርጦ በንጉሥ እጅ ላይ ቀረ ቅዱስ ዮሐንስም በዚያች ሰዓት ወደ ሀገሩ ደረሰ።
ንጉሡም ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ የቀሚሱን ቁራጭ በውስጧ አኖረ ቤተ ክርስቲያኒቱም እስከ ዛሬ ድረስ የፊቃር ቤተ ክርስቲያን ተባለች። የቊርባን ቅዳሴ በሚቀደስ ጊዜም ሥጋውንና ደሙን መቀበል የሚገባቸውንና የማይገባቸውን ጻድቃንና ኃጥአንን ያያቸዋል።
ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ የጣዖትን አምልኮ በአቆመ ጊዜ ለአባቱ ወንድም ልጅ ለስምዖንም ይህን አስረድቶት ወደ እስክንድርያ ከተማ ሔዱ በመኰንኑ ፊትም ቁመው ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ጽኑዕ የሆነ ሥቃይም አሠቃያቸው። ከዚህም በኋላ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቈረጣቸው የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ ከሥጋቸውም ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ ለበሽተኞችም ታላቅ ፈውስ ተገኘ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ገብርኤል_ሊቀ_ዻዻሳት
ዳግመኛም በዚህች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ ስምንተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ገብርኤል አረፈ። የዚህ ቅዱስ ወላጆች በእግዚአብሔር ሕግ የጸኑ ደጋጎች ፈቃዱንና ትእዛዙንም የሚፈጽሙ ነበሩ።
ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ በፈሪሀ እግዚአብሔር አሳደጉት። በአንዲት ዕለትም ቅዱሳን መነኰሳት ወደርሱ መጡ ከውስጣቸውም መልካም ገድል ያለው አንድ አረጋዊ ነበረ። እርሱም ብዙዎች ኤጲስቆጶሳት ሕፃኑን ከበው እጃቸውን እንደሚጭኑበት እንደሚባርኩትና ይሁን ይሁን ይገባዋል እንደሚሉ ራእይን አየ።
ሽማግሌውም ይህን ራእይ በአየ ጊዜ ሕፃኑ ታላቅ እንደሚሆን አሰበ ለአባቱም ይህን ሕፃን አስተምረው ለብዙዎች ሕዝቦች አለቃ ይሆን ዘንድ አለውና አለው። አባቱም ሰምቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው ከዚህ ሕፃን ምን ይደረግ ይሆን አለ።
ሕፃኑ ሁለት ዓመት በሆነው ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ፈቃድ አባቱ አረፈ ብህና በሚባል አገርም ገድሉ የተደነቀ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ብሉያትንና ሐዲሳትንም የሚያውቅ የእናቱ ወንድም ስሙ ጴጥሮስ የሚባል ኤጲስቆጶስ ነበረ ሕፃኑንም ወስዶ አስተማረው ከተሰጠውም ጸጋና ከዕውቀቱ የተነሣ ያዩት ሁሉ ያደንቁ ነበር ዲቁናም ተሾመ።
ዐሥራ ሁለት ዓመትም በሆነው ጊዜ የምንኵስናን ልብስ ሊለብስ ወደደ ይህንም ኃላፊውን ዓለም ናቀ ኤጲስቆጶሱ አባ ጴጥሮስም በገድል ተጸምዶ ለሚኖር ለቀሲስ አባ ጴጥሮስ ሰጠው እርሱም በጥቂት ቀኖች የምንኵስናን ገድል አስተማረው ከእርሱም ብዙ ትሩፋቶች ታዩ።
ከዚህም በኋላ መምህሩ ቀሲስ አባ ጴጥሮስ በአረፈ ጊዜ ከዚያ ተነሥቶ ወደ አባ እንጦንስ ገዳም ሔደ በዚያም በጾምና በጸሎት በስግደት በመትጋት እየተጋደለ ያለ ማቋረጥ ብዙ ዘመናት ኖረ።
ከዚህም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወደ አባ መቃርስ ደብር ሔደ። በደብረ ማርስ ባለች በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን አበምኔት አደረጉት ሕንፃዋንም አደሰ።
ከዚህም በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሒዶ ከቅዱሳት መካናት ተባረከ በዚያም በቅድስት ትንሣኤ በተሰየመች ቤተ ክርስቲያን በጳጳሱ በአባ ሚካኤል እጅ ቅስና ተሾመ። ከዚያም ወደ ምስር አገር ተመልሶ በማዕልቃ ባለች በእመቤታችን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት መጻሕፍትን እየጻፈ ተቀመጠ።
ይህም ቅዱስ በወንጌላዊው በማርቆስ መንበር ዐሥራ አራት ዓመት መንጋውን እየጠበቀ ከኖረ በኋላ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ታላቁ_አባ_ብስንዳ_ጻድቅ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባት ብስንዳ አረፈ። ይህም ቅዱስ ጥልቅ በሆነ የውኃ ጉድጓድ ውስጥ ቆሞ ሲጋደል ኖረ መላእክትም ይጐበኙትና ዘጠኝ ክንድ ያህል በሠረገላ ከፍ ከፍ ያደርጉት ነበር። ከዚህም በኃላ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
اکنون در دسترس! پژوهش تلگرام ۲۰۲۵ — مهمترین بینشهای سال 
