fa
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

رفتن به کانال در Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

نمایش بیشتر
2 639
مشترکین
-224 ساعت
+37 روز
+5630 روز
آرشیو پست ها
ቀዳም ስዑር የተሻረ ሰንበት ማለት ነው፡፡ የተሻረ የተባለውም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ደቀ መዛሙርቱ ‹‹የጌታችንን ትንሣኤ ሳናይ እህል አንቀምስም›› ብለው በአክፍሎት ስለጾሙበት ነው፡፡ በዚህ ዕለት ነፍሳት ከሲኦል ወጡ፤ አንቀጸ ገነት፣ ርስት ገነት ተከፈተልን፡፡ አባታችን አዳም ከፈጣሪ ታረቀልን በማለት በመስቀሉ ሰላምን አደልን እያልን የተድላና የደስታ ምልክት ወይም መግለጫ ቄጠማ ይዘን የምሥራች እንባባላለን፡፡ (ግብረ ሕማማት) በቀዳሚ ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል (ቃለ ዓውዲ) እየመቱ ‹‹ገብረ ሰላመ በመስቀሉ አገሀደ ትንሣኤሁ፤ በመስቀሉ ሰላምን አደረገ፤ በትንሣኤውም ገለጠልን›› የሚለውን ያሬዳዊ ዜማን በመዘመር፣ ጌታችን በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር ቄጤማውን ለምእመን ይሰጣሉ፡፡ ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቁ ምእመናን ብሥራት ይሆናሉ፡፡ ምእመናኑም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቀጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ (ጾመ ድጓ፤ ቀዳም ስዑር ዜማhttps://t.me/finotebirhan12

ከዚህም በኋላ ጌታችን እንዳዘዛት የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ እራስ እንደንስር በአየር ላይ እየበረረች የምታስተምር ሆነች፡፡ በምሥራቅ በኩል ሄዳ በዐረብ አገር ውስጥ በሰማይ ላይ ስታስተምር በዚህች ዕለት ጥቅምት 30 ቀን በግልጽ ታየች፡፡ ነጋዴዎች ድምጹዋን ሰምተውና አይተዋት እጅግ ተደስተው ገንዘባቸው ሁሉ ጥለው የቅዱስ ዮሐንስን እራስ ለመያዝ ሰውነታቸውን ብዙ አደከሙ፡፡ ነገር ግን ለመያዝ አልተቻላቸውም፡፡ ከዚህም በኋላ ከሰማይ ‹‹የምትያዝበት ጊዜ ስላልደረሰ ሰውነታችሁን አታድክሙ›› የሚል ድምጽ ከሰማይ መጣላቸው፡፡ መፈለጋቸውንም ተው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስም እራስ 15 ዓመት ስታስተምር ኖራ ሚያዝያ 15 ቀን በዐረብ ሀገር ዐረፈች፡፡ የታዘዙ ቅዱሳን መላእክትም መጥተው ከቅዱስ ዮሐንስ እራስ ከተባረኩ በኋላ በታላቅ ዝማሬ እያመሰገኑ የቅዱስ ዮሐንስን አንገት ወስደው በነቢዩ ኤልሳዕ መቃብር ውስጥ አብረው ቀበሯት፡፡ ቅድስትን ነፍሱንም እያመሰገኑ ወደ ሰማይ አሳረጓት፡፡ በዚያም በሥሉስ ቅዱስ ዙፋን ፊት ወድቃ ከሰገደች በኋላ አባቷ ዘካርያስንና እናቷ ኤልሳቤጥን እጅ ነሳቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ በ3ኛው ሰማይ ውስጥ ተቀመጠች፡፡ ጌታችን ሦስቱን ሰማየ ሰማያት ርስት ጉልት አድርጎ ሰጥቶታልና፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ መላ ዘመኑ 45 ዓመት ከ8 ወር ነው፡፡ 2 ዓመት በእናት በአባቱ ቤት ተቀመጠ፣ 28 ዓመት በበረሃ ብቻውን ኖረ፣ 8 ወር ርጉም ሄሮድስ አንገቱን ከማስቆረጡ በፊት ሲያስተምር ቆየ፣ 15 ዓመት አንገቱ ከተቆረጠች በኋላ በዓለም ዞሮ ሲያስተምር ኖረ፡፡ ይህች እጅግ የከበረች የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ እራስ እኛው ሀገር ኢትዮጵያውያ ውስጥ ነው የምትገኘው፡፡ ይህንንም መጽሐፈ ጤፉት በደንብ ይገልጸዋል፡፡ ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይግውና የቅዱሳን አምላክ ልዑል እግዚአብሔር ቅዱስ መስቀሉን በተአምራት አባቶቻችን ወደ ሀገራችን እንዲያመጡት ሲያደርግ የብዙ ቅዱሳንን ዐፅንም አብሮ ሰጥቶናል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ የከበረች እራሱ አንዷ ናት፡፡ እርሷም በግሸን ደብረ ከርቤ በእግዚአብሔር አብ ቤተ መቅደስ ውስጥ በክብር ተቀምጣ ትገኛለች፡፡ የአመጣጧም ነገር እንዲህ ነው፡- የቅዱስ ዮሐንስ እራስ 15 ዓመት ስታስተምር ኖራ ሚያዝያ 15 ቀን በዐረብ ሀገር ካረፈች በኋላ የታዘዙ ቅዱሳን መላእክት ወስደው በነቢዩ ኤልሳዕ መቃብር ውስጥ አብረው ቀበሯት፡፡ ከብዙ ዘመን በኋላ በገንዘብ ድኆች በሃይማኖት ግን ባለጸጎች የሆኑ ሁለት ደጋግ ክርስቲያኖች ለአርባ ጾም ስግደት ወደ ኢየሩሳሌም መጥተው ሳለ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ለአንደኛው በራእይ ተገለጠለትና የከበረች ራሱ ያለችበትን ቦታ ነገረው፡፡ እርሱም ወዳመለከተው ቦታ ቢሄድ የቅዱስ ዮሐንስን ራስ በሸክላ ዕቃ ውስጥ አገኛት፡፡ መዓዛዋም እጅግ የሚመስጥ ነው፡፡ ሰውየውም ከእርሷ ከተባረከ በኋላ ከእርሱ ጋራ ወደቤቱ ወስዶ በፊቷ መብራት እያበራ ዕጣን እያጠነ በታላቅ ክብር አኖራት፡፡ እርሱም በሞት ባረፈ ጊዜ ለእኅቱ ምሥጢሩን ነግሯት እርሷም በክብር ስትብቃት ኖረች፡፡ የቅዱስ ዮሐንስም ራስ በአንድ አርዮሳዊ ሰው እጅ እስከገባች ድረስ ከአንዱ ሰው ወደ አንዱ ሰው የምትፋለስ ሆነች፡፡ አርዮሳዊውም ሰው ከሞተ በኋላ በኢየሩሳሌም፣ አባ አንያኖስ በሀገረ ኀምዳ ኤጲስቆጶስነት ተሹመው ሳለ ቅዱስ ዮሐንስ ለአባ አንያኖስ ተገለጠለትና የከበረች ራሱ ያለችበትን ነገረው፡፡ አባ አንያኖስም ሄዶ እንደዛሬው ባለ ዕለት ግንቦት 30 ቀን ከዚያ አወጣት፡፡ ይህም የካቲት 30 ቀን ከአገኟት በኋላ ዳግመኛ ያገኙበት ነው፡፡ የመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስንም ራስ በነቢዩ ኤልሳዕ መቃብር ውስጥ አብረው ካኖሯት ከብዙ ዘመን በኋላ የነቢዩ ኤልሳዕና የመጥምቁ ዮሐንስ ዐፅም ሰኔ 2 ቀን ፍልሰተ ዐፅማቸው ሆነና በፈቃደ እግዚአብሔር በተአምር ወደ እስክንድርያ ሄደ፡፡ የቅዱሳኑም ዐፅም እስክንድርያ እንደደረሰ ቅዱስ አትናቴዎስ ሕዝቡን ይዞ ወጥቶ በታላቅ ክብር ተቀበላቸው፡፡ በዓላቸውንም በደስታ አከበረላቸው፡፡ በስማቸውም ቤተ ክርስቲያን አነጸላቸውና ዐፅማቸውን በክብር አስቀመጠው፡፡ የቅዱሳኑም ዐፅም በእስክንድርያ እጅግ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን እያደረጉ ብዙ ዘመን ኖሩ፡፡ ከዓባይ ወንዝ ውጭ ሕይወት የሌላቸው ግብጾች አምጸው በሀገሪቱ ያሉትን ክርስቲያኖች ያሠቃዩአቸው ጀመር፡፡ ሊቀ ጳጳሳቱን አባ ሚካኤልንም አሠሯቸው፡፡ ይህንንም ሲሰሙ ዐፄ ዳዊት ሱዳን ድረስ ዘምተው የዓባይን ወንዝ አቅጣጫውን በማስቀየር ግብጻውያንን በረሀብ ሊፈጇቸው ሲሉ እስላሞቹ የግብጽ መሪዎች ሊቀ ጰጳሳቱን ከእስር ፈቷቸውና አከበሯቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም የግብጹን ሊቀ ጳጳሳት ከእስላሞች የግዞት እስራት ካስፈቷቸው በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱና ክርስያኖቹ ተመካክረው ብዙ ወርቅ እጅ መንሻ አድርገው ቢሰጧቸው ንጉሣችን ግን ‹‹የዳነው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው እንጂ በሰው ነውን? እኔስ ወርቅና ብር አልሻም የጌታዬን ቅዱስ መስቀሉን ስጡኝ እንጂ›› ብለው መልእክት ጽፈው እጅ መንሻቸውን መልሰው ላኩላቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም የዓባይን ወንዝ አለቀቀላቸውም ነበርና ገዥዎቹ እስላሞች እጅግ ተጨንቀው ሊቀ ጳጳሳቱንና ኤጲስቆጶሳቱን ካህናቱንም ሁሉ ሰብስበው የኢትዮጵያዊውን ንጉሥ ፈቃዱን እንዲፈጽሙለት ነገሯቸው፡፡ የግብጹ ሊቀ ጳጳሳትና ክርስያኖቹም በጉዳዩ ከተመካከሩ በኋላ ‹‹እርሱስ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ደገኛ ንጉሥ ነውና ቅዱስ መስቀሉን ከሌሎች ቅዱሳን ዐፅም ጋር እንስደድለትና ደስ እናሰኘው›› ብለው ተማሩ፡፡ በመጨረሻም በፈቃደ እግዚአብሔር በግብጽ ያሉ የከበሩ ቅዱሳት ንዋያትንና የብዙ ቅዱሳንን ዐፅም ከቅዱስ መስቀሉ ጋር ለዐፄ ካሌብ ላኩለት፡፡ ከእነዚህም ቅዱሳን ዐፅም ውስጥ እጅግ የከበረች የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ እራስ አንዷ ናት፡፡ ጥንቁቅ የሆኑ አባቶቻችን የጌታችንን ቅዱስ መስቀል በዕንጨት፣ በብረት፣ በነሐስና በወርቅ ሣጥን ደራርበው በክብር ሲያስቀምጡ የመጥምቁ ዮሐንስን ዐፅም ከሌሎቹ ቅዱሳን ዐፅም ጋር አብረው በግሸን እግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን በታላቅ ክብር አስቀምጠውታል፡፡ ይህንንም መጽሐፈ ጤፉት በዝርዝር ይገልጸዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_15 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት #የመጥምቁ_የቅዱስ_ዮሐንስ ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየዞረች ዐሥራ አምስት ዓመት ካስተማረች በኋላ ተለይታ የወጣችበት ሆነ፣ የከሃዲው ንጉሥ የዱድያኖስ ሚስት #ቅድስት_እለእስክንድሪያ በሰማዕትነት ዐረፈች፣ ከሰባ ሁለቱ አርድእት የአንዱ ሐዋርያ #ቅዱስ_አጋቦስ መታሰቢያው ነው፣ የአገረ ሜራ ኤጲስቆጶስ በሆነ #በቅዱስ_ኒቆላዎስ ስም ለያዕቆባውያን ወገን በግብጽ አገር ያለች ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት መታሰቢያ ሆነ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #መጥምቁ_ዮሐንስ ሚያዝያ ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት የመጥምቁ የቅዱስ ዮሐንስ ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየዞረች ዐሥራ አምስት ዓመት ካስተማረች በኋላ ተለይታ የወጣችበት ሆነ፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ቅድስት ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየበረረች 15 ዓመት ስታስተምር ከኖረች በኋላ ጥቅምት 30 ቀን በዐረቢያ ምድር በግልጽ ታይታለች፡፡ ይኸውም የሆነው እንዲህ ነው፡- ሄሮድያዳ ልጅ ርጉም የሆነ ንጉሥ ሄሮድስን በዘፈኗ በጣም አድርጋ አስደሰተችው እርሱም በተራው ሊያስደስታት ፈለገና እስከ መንግሥቱ እኩሌታ ድረስም ቢሆን የለመነችውን ይሰጣት ዘንድ በሕዝቦቹና በመኳንንቱ ሁሉ ፊት እንዳይከዳት በፅኑ ቃልኪዳን ማለላት፡፡ እርሱም አስቀድሞ ‹‹የፈለግሽውን ጠይቂኝ፣ የመንግሥቴንም እኩሌታ ቢሆን እሰጥሻለሁ ምን ላድርግልሽ?›› እያለ በመሐላ ባላት ጊዜ በእናቷ ምክር የዮሐንስን አንገት ቆርጦ ይሰጣት ዘንድ ለመነችው፡፡ እርሱም ስለማሐላው የዮሐንስን አንገት እንድትቆረጥ አደረገ፡፡ በመጀመሪያም የሄሮድስ ወታደሮች ሠይፍ ይዘው የዮሐንስን አንገት ይቆርጡ ዘንድ ወደ መኅኒ ቤት ሲሄዱ ቅዱስ ዮሐንስም የሄሮድስ ጭፍሮች ሊገድሉት እንደመጡ በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ስላወቀ ከጨለማው ቤት ውስጥ አንገቱን በመስኮት አውጥቶ እንደሚመቻቸው አድርጎ ጠበቃቸው፡፡ የንጉሡም ጭፍሮች የመጥምቁን ራስ በወጪት አድርገው ለንጉሣቸው ሄሮድስ ሰጡት፡፡ ሄሮድስም ለሄሮድያዳ ልጅ ሰጣት፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ግን በወጪት ላይ ሆና ሕዝቦቹና የመንግሥቱ ታላላቅ ሰዎች እየሰሟት በየመኳንንቱ ፊት ንጉሥ ሄሮድስን ‹‹የወንድምህን የፊሊጶስን ሚስት ማግባት አይገባህም›› እያለች መጀመሪያ ትዘልፈው እንደነበረው ሁሉ አሁንም ዘለፈችው፡፡ መዓዛዋም እጅግ ደስ የሚያሰኝ ነበር፣ ዐይኖቹም እንደፀሐይ ያበሩ ነበር፡፡ የሄሮድያዳም ልጅ የመጥምቁን ራስ ወስዳ ለእናቷ ልትሰጣት ስትል ዐይኖቹ እንደፀሐይ ሲያበሩ ብታየው ‹‹ንጉሡን አትፈራውምን?›› በማለት ተቆጣች፡፡ በመቀጠልም ‹‹እነዚህን ዐይኖቹን በወስፌ እያወጣሁ እጥላቸዋለሁ፣ ምላሱንም ደግመኛ እንዳይገሥጽ ቆርጨ እጥላቸዋለሁ›› በማለት ፊቱን በጥፊ ለመምታት እጇን ስታነሣ ያንጊዜ የዮሐንስ ራስ ክንፍ አውጥታ በረረች፡፡ በአየር ላይ ሳለችም ዳግመኛ ‹‹የተረገምሽ ሄሮድያዳ የባልሽን ወንድም ሄሮድስን ማግባት አይገባሽም፣ ቀድሞ የምዘልፍሽ አሁንም የምዘልፍሽ እኔ ነኝ›› እያለች የዮሐንስ ራስ የቤቱን ጣሪያ ሰንጥቃ እንደንሥር በአየር በራ ሄደች፡፡ ከዚህም በኋላ ለጥፊ የዘረጋቻቸው የሄሮድያዳ እጆቿ ከትከሻዋ እየተቆረጡ መሬት ላይ ወደቁ፤ እውነቷንም መሬት አፏን ከፍታ ዋጠቻት፡፡ ዘፋኟ ልጇም አብዳ የቤተ መንግሥቱን ዕቃ ሁሉ መሰባበር ጀመረች፡፡ የንጉሡ አንዱ ጭፍራም የሄሮድያዳን በእሳት እንደተለበለበ የግንድ እሳት የመሰለና የተቆረጠ እጇን አምጥቶ ለሄድሮስ ሰጠውና የሆነውን ነገረው፡፡ ንጉሡም ነገሩ እውነት መሆኑን ሄዶ ባየ ጊዜ በሀፍረት እጅግ ተሸማቀቀ፡፡ ዘፍና በማስደሰት የዮሐንስን ራስ እንዲያስቆርጠው ያደረገችው የሄሮድያዳ ሴት ልጅም አብዳ በቤተ መንግሥቱ ስትለፈልፍ አገኛት፡፡ ሄሮድስም መኳንንቶቹን ‹‹በቤተ መንግሥቴ የተደረገውን ይህን ነገር ለማንም አትንገሩ›› ብሎ አማላቸው ነገር ግን ያበደችው የሄሮድያዳ ሴት ልጅ ራሷ ሄዳ ሄሮድስን ‹‹የወንድምህን የፊሊጶስን ሚስት ማግባት ፈጽሞ አይገባህም›› እያለች በመኳንንቶቹ ፊት ገሠጸችው፡፡ ንጉሥ ሄሮድስም ይህን ቃል ከእርሷ በሰማ ጊዜ እጅግ ተናደደና ‹‹ቀደሞ ያልሆነ ሥራ ታሠራ በኋላ ደግሞ ምሥጢር ታወጣ ንሣ በሰይፍ ቁረጣት›› ብሎ አንገቷን በሰይፍ አስቆረጣት፡፡ ሥጋዋንም ዓሣ አንበሪ ተቀብሎ ዋጣት፡፡ ሄሮድም የወንደሙን ሚስት ሲያገባ አስቀድሞ አግብቷት የነበረችውን ሚስቱን በግፍ አባሯት ነበር፡፡ እርሷም ይህንን ሄሮድስ ያደረሰባትን ግፍ ለአባቷ አርጣ ብትነግረው አባቷ ብዙ ጦር ሰብስቦ መጥቶ ምድረ ገሊላን በኃይል አፈራረሳት፡፡ የበላዩ ንጉሥ ቄሳርም የገሊላን መፍረስና መውድም ሲሰማ ምክንያቱን ቢጠይቅ ሄሮደስ ባደረገው ግፍ ምክንያት መሆኑን ነገሩት፡፡ ቄሳርም ሄሮድስን ከሥልጣኑ ሽሮ አጋዘውና በወህኒ ጣለው፡፡ ሄሮድስም በወህኒ ቤት ሳለ አብዶ ራሱን ስቶ የገዛ አካሉን እየነጨ እየበላ ቷ ብሎ ፈንድቶ ተልቶ ሸቶ እጅግ ክፉ አሟሟት ሞተ፡፡ የኃጢአት መጨረሻው ይህ ነው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስን ራስ ካስቆረጡ በኋላ ሦስቱም የደረሰባቸውን ተመልከቱ፡፡ በሥጋም በነፍስም ጽኑ ቅጣት አገኛቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በምድርም በመንግሥተ ሰማያትም ለዘለዓለም ከብሮ ይኖራል፡፡ የተቀደሰች ራሱም በሰማይ ላይ እየበረረች ወደ ደብረ ዘይት ሄደች፡፡ ጌታችንም በደብረ ዘይት እያስተማረ ሳለ ወደ እርሱ ሄደችና ከእግሩ በታች ወድቃ ሰገደች፡፡ ጌታችንም የዮሐንስን ራሱ በእጆቹ አቅፎ ይዙ በመለኮት አፉ አክብሮ ሰማት፡፡ እመቤታችንም የዮሐንስን ራስ በጌታን እጅ ላይ ሆና ባየቻት ጊዜ በሀዘን እጅግ አምርራ አለቀሰች፡፡ ጌታችንም ቅድስት እናቱን ካረጋጋት በኋላ ‹‹ክብርት እናቴ ሆይ! አታልቅሺ እነሆ ዮሐንስ ሙቶ እንዳየሽው እኔም ደግሞ እሞታለሁኝ እገደላለሁኝ፡፡ ነገር ግን የእኔ ሞት እንደ ዮሐንስ አንገቴን በሰይፍ ተቆርጨ አይደለም እጅና እግሬን በብረት ተቸንክሬ በመስቀል ላይ ተሰቅዬ ነው፣ ቀኝ ጎኔንም በጦር እወጋለሁ ደምና ውኃም ከጎኔ ይፈሳል›› አላት፡፡ ሌላም ብዙ ምሥጢርን ነገራትና አጽናንቶ አረጋጋት፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ራስ መለስ ብሎ እንዲህ በማለት ሥልጣን ሰጣት፡- ‹‹እነሆ መንፈስሽን በራስሽ ውስጥ አድርጌልሻለሁ በሰማይም የምትበሪበት እንደ ንሥር ክንፍ ሰጥቼሻለሁና እንደንስር በሰማይ እየበረርሽ በዓለም ሁሉ እየዞርሽ የሄሮድስንና የሄሮድያዳን ኃጢአት ግለጭባቸው፤ እስከ 15 ዓመት ድረስ ገቢረ ተአምራት የምታደርጊበት ኃይሌን መንፈሴን በእራስሽ ውስጥ አድርጌልሻለሁ›› አላት፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ዮሐንስን ‹‹እኔም ከ3 ዓመት በኋላ ለአዳም የሰጠሁትን ተስፋ ፈጽሜ በሞቴ ወደ ሲኦል ወርጄ ነፍሳትን ከዲያብሎስ እጅ ማርኬ በ3ኛው ቀን ከሙታን ተለይቼ ተነሥቼ ወደ ባሕርይ ክብሬ ተመልሼ ወደ ሰማይ አርጌ ባባቴ ቀኝ በተቀመጥኩኝ ጊዜ ከ15 ዓመት በኋላ ርጉም ሄሮድስ ካስፈጃቸው ከትንንሾቹ ሕፃናት ጋራ ትሆን ዘንድ በአባቴ ፈቃድ እራስህን ተሸክመው ወደ አባትህ ወደ ዘካርያስ ያመጧት ዘንድ እኔ መላእክትን አዛቸዋለሁ፡፡ ዛሬ ግን ነፍስህን በእኔ ቀኝ ባባትህ በዘካርያስ አጠገብ አኑሬያታለሁ መንፈስህንም እስከ 15 ዓመት በእራስህ ውስጥ እንድትኖር አዝዣታለሁ፣ ሥጋህም ከነቢዩ ከኤልሳዕ ጋር እንዲቀመጥ አድርጌያለሁ›› አለው፡፡

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_14 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #አባ_መክሲሞስ_ሊቀ_ጳጳሳት ሚያዝያ አሥራ አራት በዚች ቀን በእስክንድርያ ለተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት ዐሥራ አምስተኛ የሆነ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መክሲሞስ አረፈ ። ይህም አባት መንፈሳዊና በሥራው ሁሉ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው። እርሱም ከእስክንድርያ ሰዎች ወገን ነው ወላጆቹም ሃይማኖታቸው የቀና ነበረ የዮናናውያንንም ጽሕፈትና መጽሐፋቸውን ጥበባቸውንም ሁሉ ተምሮ ፍጹም አዋቂና አስተዋይ ሆነ በዮናኒ ቋንቋ። ከዚህም በኋላ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ልዑል እግዚአብሔር የሠራውን ሕግና ሥርዓት ተማረ። አባት ያሮክላም ዲቁና በእስክንድርያ ሾመው ከዚያም በኋላ ዲዮናስዮስ ቅስና ሾመው በተሾመባት ሁሉ ላይ ተጠምዶ የሚአገለግልና የሚጋደል ሆነ ። አባ ዲዮናስዮስም በአረፈ ጊዜ አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳትና ካህናት ማኅበሩም ሁሉ መረጡት በእግዚአብሔርም ፈቃድ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ላይ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ሾሙት ። ዲዮናስዮስም ስለ ጳውሎስ ሳምሳጢ በአንጾኪያ ከተማ የተጀመረው የኤጲስቆጶሳት ማኅበር ጉባኤ ተጀመሮ ሳይፈጸም አረፈ። ይህም አባት መክሲሞስ በተሾመበት ወንበር በተቀመጠ ጊዜ በማኅበሩ ጉባኤ ስለ ተወሰነውና ከሀዲው ጳውሎስ ሳምሳጢን እንደአወገዙት ከጉባኤው ሹማምንት መልእክቶች ወደርሱ ደረሱ። በትምርቱ ያመኑትንም መልእክቶቹንም ካህናቱ በአንድነት በተሰበሰቡበት አነበበው። ከዚያም በኋላ ዳግመኛ ከራሱ መልአክቶችን ጽፎ የጳውሎስ ሳምሳጢን ስሕተት ያርቅ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልዩና እንዲማልዱ እያዘዘ ወደ ግብጽ አገሮች ሁሉ ወደ ኢትዮጵያና ወደ ኖባ አገር ላካቸው ። የክብር ባለቤት ጌታችን ልመናቸውን ተቀበለ ይህም ከሀዲ ከጥቂት ቀኖች በቀር አልኖረም በፍጥነት አጠፋው እንጂ የረከሰች ሃይማኖትንም ከዓለም አስወገደ አራቀ። በዚህም አባት ዘመን ከምሥራቅ አገር ማኒ የሚባል ራሱን የዕውነት መንፈስ ጰራቅሊጦስን ያደረገና ክፉ ስሕተትን የሳተ ሰው ተገለጠ። ወደ ሶርያ ምድርም ደረሰ አርኬላዎስ የሚባል ኤጲስቆጶስም ከእርሱ ጋራ ተከራከረ ስሕተቱንም ገላልጦበት አሳፍሮ ከአገሩ አሳደደው ። ከዚያም ተመልሶ ወደ ፋርስ ሔደ ራሱንም ነቢይ አደረገ የፋርስ ንጉሥ ብህራምም ይዞ ከሁለት ሠነጠቀው። ተከታዮቹ የሆኑ ሁለት መቶ ሰዎችን ዘቅዝቆ እስከ ወገባቸው በምድር ውስጥ ተከላቸው እነሆ ከሰው አትክልትን ተከልሁ አለ። ይህም አባት መንጋውን በመጠበቅ ሲጋደልና በቀናች ሃይማኖትም ሲያጸናቸው ኖረ ከመናፍቃንና ከከሀድያን ችግር እስከ አረፈባት ቀን ድረስ በድርሳናትና በተግሣጻት ጠብቆ አዳናቸው። በማርቆስም ወንበር ዐሥራ ስድስት ዓመት ኑሮ በሰላም አረፈ። በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። https://t.me/finotebirhan12

#ጉልባን ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚባላ ንፍሮ ነው፡፡ የጉልባን ትውፊት እስራኤላውያን ከግብፅ ተሰደው በሚወጡበት ጊዜ በችኮላ ስለነበር፤ አቡክተው ጋግረው መብላት ያለመቻላቸውን ሁኔታ ያመለክታል፡፡ ያን ጊዜ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መብላት፤ ንፍሮም ቀቅለው ስንቅ መያዝ ተግባራቸው ነበርና ይህን ለማሰብ በሰሙነ ሕማማት ቂጣና ጉልባን በማዘጋጀት በዓሉ ይታሰባል፡፡ በጸሎተ ሐሙስ ይህንን መሠረት በማድረግ የሚዘጋጀው ጉልባን አንዲህም ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ጨው ውኃ የሚያስጠማ በመሆኑ የጌታን መጠማት ያስታውሳል፡፡ ይህ ትውፊታዊ ሥርዓት ከእስራኤላውያን የመጣ ሲሆን በኢትዮጵያም አብዛኛዎቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ሥርዓቱ ዛሬም ይከበራል፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_13 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #የቅዱስ_አባ_ሜልዮስ_አርድእት_አባ_ኢያሱና_አባ_ዮሴፍ ሚያዝያ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን ሁለት የከበሩ መነኰሳት የአባ ሜልዮስ አርድእት አባ ኢያሱና አባ ዮሴፍ በሰማዕትነት አረፉ እርሱም አባ ሜልዮስ በኮራሳን ተራራ በሰማዕትነት የአረፈ ነው። እነሆ መላው ምስክርነታቸው ከመንፈሳዊ አባታቸው አባ ሜልዮስ ጋራ በዚሁ ወር በሃያ ስምንት ቀን እንዲህ ተጽፎ ይገኛል። ቅዱስ ሜልዮስ ሰማዕት ኮራሳት በምትባል አገር በተራራ ባሉ ዋሻዎች ከሁለት አርድእት ጋር ይኖር ነበር፡፡ እርሱም በተጋድሎ ሕይወቱ እጅግ የተመሰገነ ነው፡፡ እግዚአብሔርም በአባ ሜልዮስ እጅ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን በመንገድ ሲሄድ የሞተ ሰው አገኘ፡፡ የአገሪቱ ሰዎችም አንዱን መነኮስ ‹‹የገደልከው አንተ ነህ›› ብለው ይዘው አስጨነቁት፡፡ የከበረ አባ ሜልዮስም ወደ ጌታችን ከጸለየ በኋላ ሬሳውን ‹‹በውኑ የገደለህ ይኽ መነኩሴ ነውንመንፈስ?›› አለው፡፡ የሞተውም ሰው አፈፍ ብሎ ተነሥቶ ‹‹እርሱስ አልገደለኝም ነገር ግን ብዙ ገንዘቤን ከአንድ ቄስ ዘንድ አደራ አስጠበቅሁ፣ ስለዚህም ገደለኝ፣ ከዚህም ጣለኝ›› ብሎ መሰከረ፡፡ ዳግመኛም አባ ሜልዮስን ‹‹ወደዚያ ቄስ ዘንድ ሄደህ ገንዘቤን ተቀብለህ ለልጆቼ ስጥልኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ አባ ሜልዮስም ‹‹እስከትንሣኤ ቀን በሰላም አርፈህ ተኛ›› ብሎት ተመልሶ ዐረፈ፡፡ የኮራት አገር ንጉሥ ሁለቱ ልጆች ሠራዊቶቻቸውን ይዘው ለአደን ወደ ተራራው ቢወጡ የከበረ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ማቅ ለብሶ ጠጉሩም የረዘመ ሆኖ አገኙት፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ባዩት ጊዜ ፈርተውት ‹‹ሰው ነህን ወይስ መንፈስ?›› ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹በዚህ ተራራ ውስጥ የምኖር ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሰው ነኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይህን ሲናገር ሰምተው ‹‹ከእሳትና ከፀሐይ በቀር አምላክ የለም፣ እንዳንገድልህ ሠዋላቸው›› አሉት፡፡ አባ ሜልዮስም የሰው ፍጥረት ሁሉ እሳትንና ፀሐይን ለፈጠረ አምላክ ብቻ መገዛት እንዳለት ነገራቸው፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ከሁለቱ አርድእቱ ከአባ ኢያሱና ከአባ ዮሴፍ ጋር ይዘው ጽኑ ሥቃይ አሠቃዩአቸው፡፡ ከብዙ አሠቃቂ ሥቃይም በኃላ በዚህ ወር በ13ኛው ቀን የሁለቱን አርድእት አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸውና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡ አረጋዊ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ግን ለ15 ቀናት ሲያሠቃዩት ኖሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ከመካከላቸው አቁመው አንዱ በፊት አንዱ በኋላ ሆነው በፍላጻ እየነደፉ በእጅጉ ያሠቃዩት ጀመር፡፡ አረጋዊ አባ ሜልዮስም ‹‹እኔን በፍላጻዎቻችሁ ለመግደል እንዳሠቃያችሁኝ እናንተም ደግሞ በገዛ ፍላጻዎቻችሁ ትሞቱ ዘንድ አላችሁ›› በማለት ትንቢት ተናገረባቸው፡፡ እነርሱም ቃሉን በመናቅ ነፍሱን እስከሚያሳልፍና ምስክር ሆኖ የሰማዕትነት አክሊልን እስከሚቀበል ድረስ በፍላጻዎች ነደፉት፡፡ እርሱም ሰማዕትትነቱን በዚህ ፈጽሞ የክብር አክሊልን ተቀዳጀ፡፡ አባ ሜልዮስን በግፍ የገደሉት ጭፍሮቹም በማግሥቱ እንደልማዳቸው ለአደን በወጡ ጊዜ የዱር አህያ አገኙ፡፡ ተከታትለውም ቀስታቸውን አስፈነጠሩ፡፡ እግዚአብሔርም ፍላጻቸውን ወደራሳቸው መልሶ ቅዱስ አባ ሜልዮስ እንደተናገረ በራሳቸው ፍላጻ ሞቱ፡፡ የሰማዕታቱ የአረጋዊ አባ ሜልዮስ፣ የአባ ኢያሱና የአባ ዮሴፍ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክስር ሚያዝያ_12 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ዐሥራ ሁለት በዚህችም ዕለት የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤልን እግዚአብሔር ወደ #ነብዩ_ኤርምያስ ላከው፣ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #አባ_እለእስክንድሮስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኤርምያስ_ነቢይ ሚያዝያ ዐሥራ ሁለት በዚህችም ዕለት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን እግዚአብሔር ወደ ነብዩ ኤርምያስ ላከው፡፡ ጠባቡና ረግረግ ከሆነ እሥር ቤት ሴዴቅያስ ንጉሥ በአሠረው ጊዜ የንጉሡ ባለሟልና የጭፍራ አለቃ የሆነው አቤሜሌክ አወጣው። ያንጊዜም የኢየሩሳሌምን ጥፋት እንዲያይ መራራ ምርኮንም እንዳይቀምስ ኤርምያስ ነብይ መረቀው እንዲሁም ሆነ። ስሳ ስድስት ዓመትም ተኝቶ ኖረ ከእርሱ ጋራ ወይንና በለስ ነበረ አልተለወጠም የእስራኤል ልጆች ከምርኮ እስቲመለሱ በለሱንም ከደብዳቤ ጋራ ወደ ኤርምያስ ባቢሎን አገር ላከው። ስለዚህም የዚህን የከበረ መልአክ ሚካኤልን በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን መታሰቢያውን እንድናደርግ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ_ዘኢየሩሳሌም በዚህች ቀን የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አባ እለእስክንድሮስ አረፈ። ይህ ቅዱስም አስቀድሞ በቀጰዶቅያ አገር ኤጲስቆጶስነት ተሹሞ ነበር። እርሱም የከበሩ ቦታዎችን ተሳልሞ በረከት ተቀብሎ ወደ አገሩ ሊመለስ አስቦ ኢየሩሳሌም መጣ። በኢየሩሳሌምም ስሙ በርኪሶስ የሚባል መቶ ዐሥር ዓመት የሆነው ጻድቅ ሰው ነበረ ሹመቱንም ሊተው ይወድ ነበረ ወገኖቹ ግን አልለቀቁትም። ቅዱስ እለእስክንድሮስም ሥራውን ፈጽሞ ወደ አገሩ ቀጰዶቅያ ሊመለስ በፈለገ ጊዜ እግዚአብሔር እንዲህ የሚል ቃል እነሆ ከሰማይ አሰማ። ወደ እገሌ በርውጡ አስቀድሞ የሚገባውንም ይዛችሁ በላያችሁ ኤጲስቆጶስነት ሹሙት። ያን ጊዜም ሲወጡ አባ እለእስክንድሮስን አገኙትና ያዙት። እርሱም እኔ የቀጰዶቅያ ኤጲስቆጶስ ነኝ የክብር ባለቤት ክርስቶስ በእነርሱ ላይ የሾመኝን መንጋዎቼን ልተው አይቻለኝም አላቸው። እነርሱም ከሰማይ ስለሰሙት ስለዚያ ቃል ስለርሱም እንደአመለከታቸው ነገሩት። ይህ ነገር ከእግዚአብሔር እንደሆነ በተረዳ ጊዜ ለበዓሉም የተሰበሰቡ አባቶች መከሩት ቃላቸውንም ተቀበለ ወደ ሀገሩ ቀጰዶቅያም እንዲህ ብሎ መልእክት ጽፎ ላካት። ይቅርታ አድርጉልኝ በእኔ ላይ አትዘኑ በእናንተ ላይም ኤጲስቆጶስ በእኔ ፈንታ ሹሙ እናንተም የተፈታችሁ ናችሁ ያቺን መልእክትም ከእርሱ ጋራ አብረው ከመጡ ከቀጰዶቅያ ሰዎች ጋራ ላከ። ከዚህም በኃላ እየተራዳው አምስት ዓመት ያህል ከአባ በርኪሶስ ጋራ ኖረ። ከዚህም በኃላ ሽማግሌው አባ በርኪሶስ አረፈ። አባ እለእስክንድሮስም መንጋውን ተረክቦ እንደ ሐዋርያት በመልካም አጠባበቅ ጠበቃቸው። ከሀዲ መክስምያኖስም በነገሠ ጊዜ ይህን አባት ይዞ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ አሠቃየው። ከዚያም በላዩ የሚያደርግበትን እስከሚያስብ ድረስ አሠረው፡፡ ጌታችንም ይህን ከሀዲ ፈጥኖ አጠፋው፣ ወገኖቹም ይህን አባት እለእስክንድሮስን ከእሥር ቤት አወጡት። ገርድያኖስም በነገሠ ጊዜ ጸጥታና ሰላም ሆነ ከክርስቲያን ወገኖች ላይም ጥቂት ወራት መከራው ጸጥ አለ። ገርድያኖስም በሞተ ጊዜ በርሱ ፈንታ አማኒ የሆነ ፊልጶስ ነገሠ። እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ስለሚአምን በክብር ባለቤት በጌታ ክርስቶስ ሰም የታሠሩትን ምእመናንን ፈታቸው እጅግም አከበራቸው ይህም አባት በጸጥታ ኖረ። ከዚህም በኃላ ከሀዲ ዳኬዎስ ተነሣ ፊልጶስንም ገድሎ መንግሥቱን ወሰደ ክርስቲያኖችንም እጅግ አሠቃያቸው ይህንንም አባት ያዘው ብዙዎችንም የቤተ ክርስተያን ሊቃውንት ጽኑ ሥቃይም አሠቃያቸው። ይልቁንም ይህን አባት አብዝቶ አሠቃየው ጽኑ ግርፋትንም ገርፎ ስለት በአላቸው በትሮች የጐኑ ዐጥንቶች ተሰብረው ወደሆዱ እስቲገቡ አስመታው። ከዚህም በኃላ እስከ እሥር ቤት ጐትተው በዚያ እንዲጥሉት አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት።እግዚአብሔር ለመረጣቸው ያዘጋጀውን መንግሥተ ሰማይ እስከ ወረሰ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠ ድረስ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እየታመነ በዚያ ወድቆ ኖረ በጸሎቱ የምትገኝ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_11 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ቅድስት_ታኦድራ_ገዳማዊት ሚያዝያ ዐሥራ አንድ በዚች ዕለት የከበረችና የነጻች እመሜኔት ታዖድራ አረፈች። ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ከታላላቆች ባለጸጎች ወገን ናት። ወላጆቿም ክርስቲያኖች ናቸው። እነርሱም ዋጋው ብዙ በሆነ በወርቅና በብር ያጌጡ የከበሩ ልብሶችን አሠሩለት ከእርስዋ በቀር ልጅ ስለሌላቸው ሊአጋቡአት እነርሱ ያስባሉና። እርሷ ግን የምንኲስና ልብስ ለብሳ በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ልትጋደል ትወዳለች መከራ መስቀሉንም ልትሸከም ትወድ ነበር የዚህን የኃላፊውን ሠርግ አልፈለገችም። ከዚህም በኃላ የወላጆቿን ዕቃ ገንዘብ ወስዳ ለሚሸጥላት ሰጠችው ለድኆችና ለምስኪኖች መጸወተች በቀረውም ከእስክንድርያ ውጭ በስተምዕራብ አብያተ ክርስቲያናትን አነፀች። ወደ እስክንድያው ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ አትናቴዎስም ሔዳ ራሷን ተላጭታ ከእርሱ ዘንድ መነኰሰች። ከደናግል ገዳማትም ወደ አንዱ ገብታ በገድልም ተጸምዳ ጽነዕ ገድልን ተጋደለች አምላካዊ ራእይንም ታይ ዘንድ ተገባት መላእክትን ታያለችና የሰይጣናትንም ሥራቸውን ለይታ ታውቃለችና ለሠሩ የታሰቡትን የምታውቅበትና የምትፈትንበት እውቀት ተሰጣት። ቅዱስ አትናቴዎስም በእርሷ ፈጽሞ ደስ ይለው ነበር ወደርሱም ይጠራታል እርሱም ሊጎበኛት ወደርሷ ይሔዳል ኀሳቧንም ትገልጥለታለች እርሱም የጠላት ደያብሎስን ወጥመዱንና ምትሐቱን ያስገነዝባታል። ከመንበረ ሢመቱ ከእስክንድርያ በአሳደዱትም ጊዜ ብዙዎች ድርሳናትን ጽፎ ላከላት። ይቺም ቅድስት እጅግ እስከአረጀች ድረስ ኖረች በመንፈሳዊ ተጋድሎም የጸናች ናት እርስዋ ከአምስቱ ሊቃነ ጳጳሳት ተምራለችና። እሊህም እለ እስክንድሮስ አትናቴዎስ ጴጥሮስ ጢሞቴዎስና ተዎፍሎስ ናቸው። እንዲህም ብለው ጠየቋት ሰው ተርታ ነገር ቢናገር ዝም በል ሊሉት ወይም እንዳይሰሙት ጆሮአቸውን መክደን ይገባልን እንዲህም ብላ መለሰች ምንም ምን ሊሉት አይገባም ነገሩ ደስ እንዳላቸው ሆነው ዝም ይበሉ እንጂ ሰው ማዕዱን በፊትህ ቢያኖር በላይዋም በጎ የሆነና ብላሽ የሆነ ምግብ ቢያኖር ይህን ብላሹን ከእኔ ዘንድ አርቀው አልሻውም ልትለው አይቻልህም መጥፎውን ትተህ ከምትፈቅደው ትበላለህ እንጂ ያለ ትሕትና ያለ ጾምና ጸሎት ሰይጣንን ድል የሚነሣው የለም። መላ ዕድሜዋም መቶ ዓመት ሆኖዋት በሰላም። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_10 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ዐሥር በዚች ቀን ታላቁ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ #አቡነ_ሳሙኤል_ዘቆየጻ ልደታቸው ነው፣ የታላቁ አባት የአባ ዕብሎ ረድእ #ቅዱስ_ይስሐቅ አረፈ፣ ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ገብርኤል አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ሳሙኤል_ዘቆየጻ ሚያዝያ ዐሥር በዚህች ቀን ታላቁ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ አቡነ ሳሙኤል ዘቆየጻ ልደታቸው ነው፡፡ ሀገራቸው ትግራይ ቆየጻ ከተባለው ቦታ ነው፡፡ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ካመነኮሷቸው ከሰባቱ ከዋክብት ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ ይህ ጻድቅ በተለየ ሁኔታ በሊቅነታቸው ይታወቃሉ፡፡ ከ5 ሺህ በላይ ተከታይ መነኮሳት ነበሯቸው፡፡ 120 የሐረግ ሥዕላት ያሉት ትርጓሜ ወንጌል በ4 ዓምድ አድርገው በብራና ላይ ጽፈው እንደ አይሁድ 70ው ሊቃውንት እሳቸውም 70 እውቅ የሀገራችንን ሊቃውንት ሰብስበው እጅግ ትልቁን ትርጓሜ ወንጌል በጉባኤ አስወስነዋል፡፡ በጉባኤውም ካስወሰኑ በኋላ ወስደው ከሙታን መቃብር ላይ ቢጥሉት 211 ሙታን ተነሥተው ነአምን በአምላከ ጻድቃን ወሰማዕታት በጸሎተ ሳሙኤል ተንሣዕነ ብለው መስክረዋል። ወንጌላቸውንም በሊቃውንት ሲያጽፉ ቀለሙን ቅዱሳን መላእክት ያመጡላቸው ነበር፡፡ ጻድቁ ባረፉ ጊዜ 5 ነብሮች መጥተው መቃብራቸውን ቆፍረው ቀብረዋቸዋል፡፡ ትልቁ ገዳማቸው በትግራይ ክፍለ ሀገር እንዳ ሥላሴ ቆሪሮ ወረዳ ውስጥ ይገኛል፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን! ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ይስሐቅ ዳግመኛም በዚህች ቀን የታላቅ አባት የአባ ዕብሎ ረድእ ቅዱስ ይስሐቅ አረፈ። ይህም ቅዱስ ይህን ዓለም ተድላ ደስታውን ምቾቱን ጣዕሙን ትቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጥቶ መነኰሰ ። ለአባ ዕብሎም ረድእ ሁኖ ሃያ አምስት ዓመት ሲያገለግለው ኖረ። ሥጋውም እሰኪደርቅ ድረስ ጹኑዕ ተጋድሎን ተጋደለ ። ከሰውነቱም ሥጋዊ ፍላጎትን ሁሉ አጠፋ ባሕርዩ ቀንቶለት ኖረ በጸሎትና በቅዳሴም ጊዜ ጸጥታን አጸና ። የቍርባን ቅዳሴ ጸሎትም እስኪፈጸም ሁለት እጆቹ የኋሊት ታሥረው ራሱን አዘንብሎ እያለቀሰ ይቆማል። ከቅዳሴም በሚወጣ ጊዜ በዚያች ዕለት ከሰው ወገን ከማንም ጋራ አይገናኝም በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜ ከአንተ ጋራ መነጋገር ከሚፈልግ ሰው ጋራ ለምን አትነጋገርም ብለው በጠየቁት ጊዜ እንደሚገባ ለሁሉ ጊዜ አለው ብሎ መለሰ ። ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ በረከት ከርሱ ሊቀበሉና በጸሎቱም ሊማጻኑ መነኰሳት ወደርሱ ተሰበሰቡ። ከሰው ለምን ትሸሻለህ ብለው ጠየቁት እርሱም ከሰይጣን እንጂ ከሰው የምሸሽ አይደለም አንድ ሰው መብራት እያበራ በነፋስ ውስጥ ቢቆም መብራቱ የሚጠፋ አይደለምን? እንዲሁ እኛም በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜ ልባችን ብሩህ ሁኖ ሳለ ከሰው ጋራ ተገናኝተን እርስበርሳችን በተነጋገርን ጊዜ ልባችን ይጨልማል ብሎ መለሰ። ይህም አባት መልካም ገድሉን ፈጽሞ በገድሉም እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው ጊዜ ጌታችንም ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ድካም ሊአሳርፈው ወደደ። ጥቂትም ታሞ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ገብርኤል በዚችም ዕለት ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ገብርኤል አረፈ። ይህም ቅዱስ የምስር አገር አለቆች ከሆኑት ከልጆቻቸው ውስጥ ነው። በግብጽ ባለች በቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያንም ዲቁና ተሾመ ዐዋቂና ጥበበኛም ስለሆነ ጸሐፊ ሁኖ ብዙዎችን መጽሕፍቶች ጻፈ የሚበዙትንም በዐረብና በቅብጥ ቋንቋ ተረጐመ። ከመሆኑ በፊት ሁሉን አይቶ በመንፈስ ቅዱስ የሚናገር የእግዚአብሔር ጸጋ በላዩ ያደረች ሶርያዊ አባ ዮሴፍ የሚባል አንድ አረጋዊ ሰው ነበረ። አረጋውያን መነኰሳትና ኤጲስቆጶሳት ወደርሱ ተሰብስበው ለዚች ለከበረች የሊቀ ጵጵስና ሹመት ማን እንደሚሻል ይገልጥላቸውና ይነግራቸው ዘንድ ለመኑት። እርሱም የታሮይክ ልጅ አንድ ሰው አለ ብሎ መለሰላቸው ምልክቱንም አመለከታቸው መነኰሳቱና ኤጲስቆጶሳቱም በዚህ ወደው ተስማሙ ከዓመተ ሰማዕታትም በስምንት መቶ ዓመት የካቲት ሃያ አንድ ቀን ይዘው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት። ወደ አስቄጥስ ገዳምም በሔደ ጊዜ መታመንን ጨመረ ይቺም በባስልዮስ ቅዳሴ ፍጻሜ ከመለኮቱ ጋር አንድ ሆነ የምትል ናት። መለኮቱ ከትስብእቱ ተጨመረ ብሎ እንዲህ እንዳያስብ መነኰሳቱ ስለፈሩ እኛስ ልማዳችን እንዲህ አይደለም አሉት። ከብዙ ምርምርም በኋላ ይች ቃል ከሚከተላት ያለ መለያየት ያለ መጨመርና ያለ መደባለቅ ከሚለው ጋራ ተሰራች በበጎ አቀባበልም ተቀብለዋት እስከዚች ቀን ጻንታ ኖረች። በሹመቱ ወራትም ብዙዎች በጎ ሥራዎች ተሠሩ ሙታንን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳይቀብሩዋቸው በውግዘት ከለከለ ሁለተኛም ዕቁባቶችን በእነርሱ ዘንድ ያኖሩትን አውጥተው እንዲሰዱ አወገዘ ። ይህም አባት ስለሙታን ርስትና ስለሌሎች ሥራዎች የሕግና የሥርዓት መጽሐፍን ደረሰ፡፡ ከቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትም ብዙዎችን ተረጐመ፡፡ በዘመኑም ኃምሳ ሦስት ኤጲስቆጶሳትንና ብዙ ካህናትን ሾመ፤ ነገረ ግን ከእርሳቸው አንድ አላድ እንኳ አልተቀበለም። የግብጽ ንጉሥም በግፍ ከእርሱ ገንዘብ ሽቶ አሠቃየው እንዲጠባበቁትም ሰላዮችን በላዮ አኖረ። ጸሐፊዎችና ሹሞች ከሕዝቡም ታላላቆች ከሕዝቡም ሆነ ከአብያተ ክርስቲያናት ወይም ከገባሬዎች ምንም ምን እንዳልወሰደ በአወቁ ጊዜ ስለዚህ ሦስት መቶ የወርቅ ዲናር ሰብስበው ስለርሱ ለንጉሡ ሰጡት ። የዕረፍቱም ጊዜ ሲቀርብ እግዚአብሔርም ትሩፋቱንና ጽድቁን ለሰው ሊገልጽ ወደደ ጥቂትም ታመመ ብዙ ካህናትና መነኰሳትም ወደ ርሱ እንደ መጡ በሌሊት ራእይ አየ። እነርሱም ወንጌሎችን መስቀሎችንና ማዕጠንቶችን በእጆቻቸው ይዘዋል። እንዲህም አሉት እኛ ልንጐበኝህ መጣን ከዓመትም ፍጻሜ በኋላ ወደአንተ ተመልሰን መጥተን ከእኛ ጋራ እንወስድሃለን ። በነቃም ጊዜ ከእርሱ ዘንድ ላሉ መነኰሳትና ኤጲስቆጶሳት ለካህናትም እንዴት እንዳየ ነገራቸው ከደዌውም ዳነ። ከዓመት ፍጻሜም በኋላ ጥቂት ታመመ አስቀድመው ወደርሱ መጥተው የነበሩትን ካህናትና መነኰሳት ደግሞ አያቸው፤ ሰላምታም ሰጡት ። ከእንርሱም ጋራ ደስ አለው በዚያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጥቶ በሰላም አረፈ፡፡ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ዓሥራ አራት ዓመት ከኖረ በኋላ ነው። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ከዚህም በኃላ እየአንዳንዱ ወደ በረሀ ይበተናሉ አንዱም አንዱ ባልንጀራውን ያየ እንደሆነ እንዳያየው ወደ ሌላ ቦታ ይሄዳል። ቅዱስ ዘሲማስም በየአመቱ ከሳቸው ጋራ ወጥቶ በበረሀው ውስጥ ይዘዋወራል የሚፅናናበትንም ይገልጥለት ዘንድ እግዚአብሄርን ይለምነው ነበር፡፡ ሲዘዋወርም በበረሀ የምትኖር ግብፃዊት ማርያምን አገኘ ከእርሷም በልጅነቷ ወራት በእርሷ ላይ እንዴት እንደሆነና በበረሀም የሆነውን ኑሮዋን ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተረዳ። ከዚህ በኃላም በሁለተኛው አመት ስጋውንና ደሙን ያመጣላት ዘንድ ፈለገች እንዳለችውም አደረገላት። ለዚህም ፃድቅ ብሄረ ብፁአን ይገባ ዘንድ ተገባው እርሱም ገድላቸውን ፃፈ ስራቸውንና ፅድቃቸውን ገለጠ። ዘጠና ሶስት የሚሆን መላ እድሜው በተፈፀመለት ጊዜ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ስንትዩ በዚህችም ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ስንትዩ እጅ ታላቅ ምልክት ታየ። ይኸውም የከበረች የጌታን ፆም ከመነኰሳት ጋራ ይፆም ዘንድ ወደ አስቄጥስ ወደ አባ መቃርስ ገዳም ወጣ። ሰሙነ ህማማትም በሆነ ጊዜ ገዳማቱንና አድባራቱን ሊዘርፉና ሊማርኩ የአረብ እስላሞች ተሰበሰቡ። በቤተ ክርስቲያኒቱ በስተምስራቅ ሰዎችንም ይገድሉ ዘንድ ሰይፎቻቸውን መዝዘው በእጆቻቸውም ይዘው በአለት ላይ ቆሙ። ኤጲስቆጶሳትና መነኰሳትም ወደ አባ ስንትዩ ተሰብስበው ከአረብ እስላሞች እንዴት እንደሆነ ነግረው ከዚያ ገለል እንዲል ለመኑት። የከበረ አባ ስንትዩም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግራቸውን አጥቦ አዲስ ስርአት የሰራበት የፋሲካ ፍስህ በአል ሳይፈፀም እኔ ከዚህ አልለይም አላቸው። እነዚህ እስላሞችም እየደነፉ ጩኸታቸው ተጨመረ። አባ ስንትዩም የወገኖቹን ድንጋፄ በአየ ጊዜ በላዩ የመስቀል ምልክት ያለበት በትሩን ይዞ ከእግዚአብሄር ወገኖች ጋራ ብሞት ይሻለኛል እያለ ወደ እነርሱ ሊወጣ ተነሣ። ኤጲስቆጶሳቱም እንዳይወጣ ያዙት። እርሱ ግን ልባቸውን በማፅናናት አረጋጋቸውና ወደ አረብ እስላሞች ወጣ። እስላሞችም መስቀል ያለበትን በትር በእጁ ይዞ በአዩት ጊዜ ብዙ ሰራዊት እንዳሳደዳቸው ሆነው ወደ ኃላቸው ተመልሰው ሸሹ። ከዚያችም እለት ወዲህ ወደ ቅዱሳት መካናት እስላሞች አልተመለሱም። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዚያ 9 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ እረፍታቸው ነው፣ የከበረ #ቀሲስ_ዘሲማስ አረፈ፣ በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #በአባ_ስንትዩ እጅ ታላቅ ምልክት ታየ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ ሚያዝያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ እረፍታቸው ነው። አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ እናቱ ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለት ተነሥተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመስግነዋል፡፡ የስማቸው ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡ በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባሕሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመታት ያህል በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኮሳት ምግብ የሚሆናቸው ዓሣ ከባህር ውስጥ በማውጣት አገልግለዋል፡፡ አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመሥዋዕት ወይኑን ለቍርባን በተአምራት አድርሰዋል፡፡ አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡ ጌታንም በቅዱሳኑ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን ‹‹ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው›› ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡ አባታችን ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትን ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡ ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያሥነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ›› በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡ ጻድቁ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ስትል ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁንም ቀጥ ብለሽ ቁሚ›› ብለው ገዝተው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አሰጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ ‹‹አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ›› ስትላቸው ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡ በአምላክ ልቡና የሚገኝ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሚገኝ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ መድኃኔዓለም ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡ ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡ ጻድቁ ታኅሣሥ 8 ቀን ተወልው ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዘሲማስ_ገዳማዊ በዚህች ቀን የከበረ ቀሲስ ዘሲማስ አረፈ። ይህም ፃድቅ ከፍልስጥኤም ሰዎች ወገን ነው። ወላጆቹም ደጋጎች ክርስቲያኖች ናቸው ይህንን ፃድቅ በወለዱት ጊዜ አምስት አመት አሳደጉት። ከዚያም የቤተክርስቲያን ትምህርትን የሀይማኖትንም ምስጢር ህግና ስርአትንም እያስተማረ እንዲያሳድገው ለአንድ ሽማግሌ መምህር ሰጡት። ያ ሽማግሌም ተቀበሎ ልጁ አደረገው ትምህርቱንም ሁሉ አምላካዊ ጥበብ ሀይማኖትንም አስተምሮ አመነኰሰው ዲቁናም አሾመው በበጎ ስራም አደገ ትሩፋት መስራትንም አበዛ እግዚአብሄርንም ሁልጊዜ ያመሰግነዋል በቀንና በሌሊትም መፃህፍትን ያነባል። ስራ ሲሰራ ሲበላም ቢሆን ሁል ጊዜ ከአፉ ምስጋናዎችን አያቋርጥም።በዚያ ገዳም አርባ አምስት አመት በተፈፀመለት ጊዜ ቅስና ተሾመ ተጋድሎውንም ጨመረ። ከዚህ በኃላም እየተጋደለና አገልግሎት በመጨመር በቅስና ሹመት አስራ ሶስት አመት ሲሆነው በዘመኑ ካሉ ተጋዳዮች ሁሉ እርሱ በገድሉ ከፍ ከፍ እንዳለ ተቃራኒ ጠላት ዲያብሎስ በልቡ ክፉ ሀሳብ አሳደረበት በልቡም ከበጎ ስራ እኔ ያልሰራሁት የቀረኝ አለን ይል ጀመር። ነገር ግን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አልተወውም መልአኩን ልኮ በዮርዳኖስ ወንዝ አቅራቢያ ወደ አለ ገዳም ይሄድ ዘንድ እንጂ። ያን ጊዜም ተነስቶ ሄዶ ወደዚያ ገዳም ደረሰ በገድላቸው ፍፁማን የሆኑ እውነተኞች አገራውያንን አገኘ እርሱ ከእርሳቸው እንደሚያንስ አወቀ እርሱ በአለም ውስጥ ነው የኖረውና ስለዚህ ከእርሱ ይሻላሉ። በዚያ ገዳም ከሳቸው ጋር ኖረ ብዙ ዘመናትም አብሮአቸው ሲጋደል ኖረ። ለዚያ ገዳም መነኰሳትም ልማድ አላቸው ታላቁ ፆም በደረሰ ጊዜ የመጀመሪያውን አንድ ሱባኤ በአንድነት ይፆማሉ በቅድስት እሑድ ስጋውንና ደሙን ይቀበላሉ በማግስቱም ሰኞ ጥዋት ሀያ ስድስተኛ መዝሙር እግዚአብሄር ብርሀነ ረድኤቱን ሰጥቶ ያድነኛል የሚያስፈራኝ ምንድነው የሚለውን እሰከ መጨረሻው እየዘመሩ ይወጣሉ በሚወጡም ጊዜ ወደ በሩ ተሰብስበው በአንድነት ፀልየው እርስ በርሳቸው ሰላምታ ይሰጣጣሉ የገደሙ አበ ምኔትም ይባርካቸዋል።

🔴#ስንክሳርሚያዝያ_8 ሚያዝያ ስምንት በዚህች ዕለት የከበሩ ሦስት ሴቶች #ቅዱሳት_አጋሊስ_ኤራኒና_ሱስንያ በሰማዕትነት አረፉ፣ መቶ ሃምሳ ሰዎች በፋርስ ንጉሥ እጅ በአንዲት ቀን በሰማዕትነት አረፉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳት_አጋሊስ_ኤራኒና_ሱስንያ ሚያዝያ ስምንት በዚህች ዕለት የከበሩ ሦስት ሴቶች በሰማዕትነት አረፉ። የእሊህም ስማቸው አጋሊስ ኤራኒና ሱስንያ ነው። ከተሰሎንቄ ሀገርም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመልኩ ናቸው። ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ነበሩ። እሊህም ደናግል በድንግልና በንጽሕና መኖርን ወደው በአንድ ምክር ተስማሙ ጽኑዕ በሆነ ገድልም ተጠመዱ ይልቁንም ያለማቋረጥ ተግተው ይጸልዩና ይጾሙ ነበር። ወደ ገዳሙም ተመልሰው ከመነኰሳቱ ጋራ ያገለግላሉ። ከሀዲ መክስምያኖስም በነገሠ ጊዜ የጣዖታትን አምልኮ አቁሞ የንጹሆችን ደም አፈሰሰ። እሊህም ደናግል በአዩ ጊዜ ፈርተው ወደ ተራራ ሸሹ በዚያም በዋሻ ውስጥ ተሸሸጉ በጾምና በጸሎት በመጸመድ ሳይወጡ በዋሻው ውስጥ ኖሩ። አንዲት የክርስቲያን ወገን አሮጊት በየሰባት ቀን ትጐበኛቸውም ነበር የሚአሻቸውንም ትሰጣቸዋለች የእጅ ሥራቸውን ትሸጥላቸውና ከእነርሱ የሚተርፈውን ትመጸውታለች። አንድ ሰውም ከከተማ ወጥታ ወደ ተራራ ሁልጊዜ ስትሔድ አያት ሳታየውም ተሠውሮ በሩቅ ተከተላት ወደ ዋሻውም እስከምትገባ ተመለከተ ከዚያ እስከምትወጣም ተሠውሮ ቆየ በዚያ ቦታ ብዙ ገንዘብ ያላት መስሎታልና። ያቺ አሮጊትም ከዋሻው በራቀች ጊዜ ያ ሰው ገባ ለክብር ባለቤት ሙሽሮቹ የሆኑ የከበሩ አዕናቍ ደናግልን ቁመው ሲጸልዩ አገኛቸው ተሰሎንቄ ከተማ እስኪያደርሳቸውም አሥሮ ጐተታቸው። መኰንኑም ሃይማኖታቸውን በጠየቃቸው ጊዜ ስለ እሳቸው የተሰቀለ የክብር ባለቤት ክርስቶስን የሚያመልኩ ክርስቲያኖች እንደሆኑ በፊቱ አመኑ። መኰንኑም ተቆጥቶ ይገርፉአቸው ዘንድ አዘዘ የሚአሠቃይ ጽኑ ግርፋትም ገረፉአቸው ባልተሰዘዙና ወደ ክህደቱ ባልገቡ ጊዜ ወደ እሳት እንዲጨምሩአቸው አዘዘ። በእሳትም ውስጥ በጣሉአቸው ጊዜ ነፍሳቸውን አሳለፉ በመንግሥተ ሰማያትም የሕይወትን አክሊል ተቀዳጁ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #የፋርስ_ሰማእታት በዚህችም ቀን መቶ ሃምሳ ሰዎች በፋርስ ንጉሥ እጅ በአንዲት ቀን በሰማዕትነት አረፉ። እርሱም ለሀገሩ ቅርብ የሆነ የክርስቲያንን አገር ከበበና ብዙ የሰው ምርኮ ማርኮ ወደ አገሩ ወሰዳቸው ፀሐይን ጨረቃንና ከዋክብትንም ያመልኩ ዘንድ አስገደዳቸው አይሆንም ባሉትም ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጡአቸው ዘንድ አዘዘ። ራሶቻቸውንም ቆረጡአቸው በመንግሥተ ሰማያትም የሕይወትን አክሊል ተቀበሉ፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡ https://t.me/finotebirhan12

ክብርት እመቤታችን በተፀነሰች ጊዜ ብዙ ተአምራት ተደርጓል፡፡ የሃናን ማሕፀን እየዳሰሱ፡- ብዙ እውራን አይተዋል፣ ድውያን ተፈውሰዋል፣ ምውታን ተነሥተዋል፡፡ ይህንን የተመለከቱ አይሁድ ቅዱስ ኢያቄምን እና ቅድስት ሐናን በድንጋይ ወግረው በእሳት አቃጥለው ሊገድሏቸው በጠላትነት ሲነሡ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሊባኖስ ወደ ሚባል ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሳሉ በግንቦት 1 ቀን ከፀሐይ 7 እጅ የምታበራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀልይ በም.4፥8 ላይ እንደተናገረ “ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ነይ…. ከአንበሶች ጉድጓድ ከነብሮችም ተራራ ተመልከች፡፡” እንዳለ ይህ ትንቢት ተፈጸመ በተወለደች በ8ኛው ቀን ስሟን “ማርያም” ብለው አወጡላት ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእናቷ ማኅፀን እያለች አያሌ ተአምራትን በማድረጓ፥ ለቅዱስ ኢያቄምና ለቅድስት ሐና ከባድ ፈተና ሆኖባቸው ነበር።የበጎ ነገር ሁሉ ጠላት ሰይጣን አይሁድን በምቀኝነት አስነ ሣባቸው። የምቀኝነት ምንጩ ደግሞ ክፉ ልቡና ነው፤ ማር፡፯፥፳፪። የሰው ልጅ መንፈሳዊነቱን ትቶ ፍጹም ሥጋዊ ሲሆን ምቀኝነት ይሰለጥንበታል። ገላ፡፭፥፳፩። ፈቃደ ሥጋው ገዝቶት በክፋትና ነት የሚኖር ሰው ደግሞ ለማንም ፍቅር ሊኖረው አይችልም። ገላ፡፫፥፫። ሰይጣን አዳምን እና ሔዋንን ያሳሳተው በምቀኝነት ነው። ዘፍ፡፫፥፩። ቃየል አቤልን የገደለው በምቀኝነት ነው። ዘፍ ፬፥፰። ዔሳው ወንድሙን ያዕቆብን ለመግደል የዛተው በምቀኝነት ነው። ዘፍ፡፳ ፯፥፵፩። የያዕቆብ ልጆች ወንድማቸውን ዮሴፍን፡- “እንግደለውና በአንድ ጉድጓድ ውስጥ እንጣለው፤” ያሉት፥ በኋላም በሮቤል በጎ ምክር አሳባቸውን ለውጠው ለእስማኤላውያን ነጋዴዎች የሸጡት በምቀኝነት ነው። ዘፍ፡፴፯፥፳፣፳፰። ሄሮድስ፡- ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ያሳደደው፥ በዚህም ምክንያት አሥራ አራት እልፍ ሕፃናትን ያሳረደው በምቀኝነት ነው። ማቴ፡፪፥፲፮። አይሁድ ኢየሱስ ክርስቶስን እጆቹን እና እግሮቹን በቅንዋተ መስቀል ቸንክረው የገደሉት በምቀኝነት ነው። ማር፡፲፭፥፳፬። ምቀኝነት የባህርያቸው እስከሚያስመስልባቸው የደረሱ አይሁድ፥ በማኅፀነ ሐና ባለች ፅንስ ምክንያት የሚደረጉት ልዩ ልዩ ተአምራት አላስደሰታቸውም። ተሰብስበውም፡- “ስለዚህ ነገር ምን እንላለን? ሐና ፀንሳ ሳለች በማኅፀንዋ ታድናለችና፥ የእስራኤልን መንግሥት አጥፍታ በእኛ ላይ ልትነግሥ አይደለምን?” ተባባሉ። ይኸውም፡- “ከአሁን ቀደም ከእነዚህ ወገን የሆኑት ዳዊት ሰሎሞን፥ አርባ፣ አርባ ዓመት ገዝተውን ነበር፥ ከእነዚህ የሚወለደው ደግሞ ምን ያደርገን ይሆን?” ብለው ነው። ሀገር ያወቀውን፥ ፀሐይ የሞቀውን ምቀኝነታቸውን በሃይማኖት ለመሸፈን፡- “በሙሴ ሕግ መሠረት በድንጋይ ቀጥቅጠን እንግደላቸው፤” ብለው በሌሉበት ሞት ፈረዱባቸው። ይህ የሙሴ ሕግ የሚጠቀሰው ለአመንዝሮች እንጂ፥ ትዳራቸውን አክብረው፥ ሕገ እግዚአብሔርን ጠብቀው፥ በጾም በጸሎት ተወስነው በቅድስና ለሚኖሩ፥ ለቅዱስ ኢያቄምና ለቅድስት ሐና አልነበረም። ዘሌ፡፳፥፲፣ዘዳ፡፳፪፥፳፬። መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜ፥ የመፀነሷን ነገር አስቀድሞ በሕልም ነግሮአቸው የነበረ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል፥ እያዩት ከሰማይ ወርዶ፥ “በዘመድ የከበራችሁ ኢያቄምና ሐና ሆይ፥ ተነሡ፤” አላቸውና ወደ ሊባኖስ ተራራ ወሰዳቸው። ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ኢያቄምን እና ቅድስት ሐናን ወደ ሊባኖስ ተራራ የወሰዳቸው ያለ ምክንያት አይደለም። “ወዳጄ ሆይ፥ ሁለንተናሽ ውብ ነው፤ (ጥንተ አብሶ የተባለ የአዳም ኃጢአት ያላረፈብሽ ንጽሕተ ንጹሐን ነሽ፤) ነውር የለብሽም። (የአዳም ኃጢአት የለብሽም)። እኅቴ ሙሽራ ሆይ፥ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነዪ፤” ተብሎ ስለ እመቤታችን ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተነገረው ቃለ ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው። መኃ፡፬፥፯። ሊባኖስ፡- ከገሊላ በስተ ሰሜን እና ከፊንቄ በስተ ምሥራቅ የሚገኝ ተራራማ ሀገር ነው። ዘዳ፡፩፥፯። በዝግባ ዛፍ የተሞላ ተራራ ነው፥ ንጉሡ ሰሎሞን ለቤተ መቅደሱ ሥራ ያስፈለገውን የዝግባ እንጨት ያስመጣው ከዚያ ነበር። ፩ኛ፡ነገ፡፬፥፴፫፤ ፭፥፮። ምሳሌነቱ ጥሩ ነው፥ ከሊባኖስ የተገኘ ዝግባ ለአግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆነ ሁሉ፥ በሊባኖስ የተወለደች ድንግል ማርያምም ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ሆና ተገኝታለች። አንድም የሊባኖስ ዝግባ ለቅዱሳን ምሳሌ ነው፤ የዚያ ፍሬው እንዲበዛለት፥ እነርሱ ደግሞ ጸጋና ክብር ይበዛላቸዋል። መዝ፡፺፩፥፲፪። ቅድስት ሐና የፅንስዋ ወራት በተፈጸመ ጊዜ፥ ግንቦት አንድ ቀን፥ ከፀሐይ ይልቅ የምታበራ ሴት ልጅ ወለደች። ቅዱስ ኢያቄምም እመቤታችንን ስለሰጠው እግዚአብሔርን ካመሰገነ በኃላ በልቡናው ደስ ብሎት መሥዋዕት አቅርቧል፡፡ እመቤታችንንም ጡት ካስጣሏት በኃላ ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐና ተሸክመው ወደ ቤተ መቅደስ ወስደው አስገቧት፡፡ ጻድቁ ኢያቄምም ጥቂት ዘመን ኑሮ በዚኽች ዕለት በሰላም ዐረፎ ወደሚወደው እግዚአብሔር ሔደ፡፡ የአባታችን የቅዱስ ኢያቄም ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_7 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ቅዱስ_ኢያቄም ሚያዝያ ሰባት በዚች ቀን የእመቤታችን አምላክን የወለደች የቅድስት ድንግል ማርያም አባትዋ ጽድቅ ኢያቄም አረፈ። ይህም ጻድቅ በሦስት ስሞች ይጠራል እንርሱም ኢያቄም ዮናኪር ሳዶቅ ናቸው እርሱም ከይሁዳ ነገድ ከዳዊት ዘር ነው። ይህም የአልዓዛር የኤልዩድ ልጅ ኢያቄም በትውልድ ሐረግ እስከ ሰሎሞንና እስከ ንጉሥ ዳዊት የሚደርስ ነው ። ይኸውም በዙፋኑ የሚቀመጥና ለዘላለሙ በእስራኤል ዘሥጋ በእስራኤል ዘነፍስ ነግሦ የሚኖር ከዘሩ ሊሰጠው ጌታ የማለለት ነው። ሚስቱ ሐናም መካን ሆነች ሁለቱም ወደ እግዚአብሔር አዘ ውትረው ይጸልዩና ይማልዱ ነበር። እግዚአብሔርም ልመናውቸውን ተቀበሎ ይችን ጣፋጭ የሆነች መልካም ፍሬን ዓለሙን ሁሉ ከረኃበ ነፍስ ያዳነች ሰጣቸው። መሪር የሆነ ተገዢነትንም ከሁሉ በእርስዋ አስወገደ። ለዚህም ጻድቅ ኢያቄም ለክብር ባለቤት ክርስቶስ አያት መሆን ተገባው ድንቅ ስለ ሆነ ሥጋዊው ከልጁ ስለመወለዱ ነው። እግዚአብሔርም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ደስ በአሰኘው ጊዜ በልቡናው ደስ ብሎት መስዋዕቱን አቀረበ። ከላዩም ከወገኖቹም ልጆች ኀፍረትን አስወገደ። አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ጡት ከአስተዋት በኋላ ለእግዚአብሔር እንደተሳሉ ተሸክመው ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወስደው አስገቡአት። ጻድቅ ኢያቄም ጥቂት ዘመን ኑሮ በሰላም አረፈ። (ስንክሳር ዘወርኀ ሚያዝያ) ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ አባታችን ቅዱስ ኢያቄም (ከገድላት አንደበት-የተወሰደ) ጴጥርቃ እና ቴክታ የሚባሉ ደጋግ ሰዎች በኢየሩሳሌም በአንድነት ተጋብተው ይኖሩ ነበር፡፡ እነዚህም በእግዚአብሔር የሚያምኑ የተወደዱ ጻድቃን ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚህም ሰዎች በእግዚአብሄርም በሰውም ዘንድ የተመሰከረለላቸው ባለጸጎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን መካን ስለነበሩ የሚወርሳቸው ልጅ አልነበራቸውም፡፡ አንድ ቀን ጴጥርቃ ቴክታን እንዲህ አላት፡- ‹‹እኅቴ ሆይ! ይህን ሁሉ የሰበሰብነውን ገንዘባችንን ምን እናደርገዋለን? ልጅ የለን የሚወርሰን አንቺም መካን ነሽ፣ እኔም ካንቺ በቀር ሌላ ሴት አላውቅም›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹ወንድሜ ሆይ! አምላከ እስራኤል ለእኔ ልጅ ቢነሳኝ አንተም እንደኔው ሆነህ ትቀራለህን? ከሌላ ደርሰህ ውለድ እንጂ›› ብላ ብታሰናብተው ‹‹እንደዚህ ያለ ነገር እንኳንስ ላደርገው በልቦናዬም እንዳላስበው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን የሚያውቅ የለም፣ ትላንትና ማታ በህልሜ ነጭ ጥጃ ከማኅፀኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ሌላ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንዲሁ እስከ 7ት ትውልድ ሲዋለድ ሰባተኛይቱ ጨረቃን ስትወልድ፣ ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ አየሁ›› አለችው፡፡ እርሱም በጠዋት ከህልም ፈቺ ዘንድ ሄዶ የነገረችውን ሁሉ ነገረው፡፡ ያም ህልም ፈቺ ‹‹እግዚአብሔር በምሕረቱ አይቷችኋል በሳህሉ መግቧአችኋል፣ 7 አንስት ጥጆች መውለዳችሁ 7 ሴቶች ልጆችና የልጅ ልጆች ትወልዳላችሁ፣ ከቤታችሁ ሰባተኛይቱ ጨረቃ መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክትም የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ፤ የፀሐይ ነገር ግን አልታወቀኝም›› አለው፡፡ እርሱም የነገረውን ሁሉ ሄዶ ለሚስቱ ነገራት፡፡ እርሷም ‹‹እንጃ አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን ማን ያውቃል!›› ብላ ዝም አለች፡፡ ከዚያም ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ስሟንም ሔሜን ብለው አወጡላት፤ ሔሜንም አድጋ ለአካለ መጠን ስትደርስ ባል አጋብተዋት ሴት ልጅ ወለደች፣ በስምንተኛ ቀኗም ዴርዲ ብለው ስም አወጡላት፡፡ ዴርዲም አድጋ እንዲሁ ሴት ወለደችና ቶና አለቻት፣ ቶናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሲካር አለቻት፣ ሲካርም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሴትና አለቻት፣ ሴትናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሔርሜላ አለቻት፣ ሔርሜላም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ንጽህት ቅድስት ክብርት የምትሆን እመቤታችንን የወለደቻትን ቅድስት ሐናን ወለደች፡፡ ይኽችም ቅድስት ሐና በሥርዓት አድጋ ለአእምሮ ስትበቃና አካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ መንግስት ወገን ከነቅዱስ ዳዊት ወገን ከሆነው ከቅዱስ ኢያቄም ጋር አጋቧት፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ፡፡ እነርሱም እጅግ ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንድ ልጅ እንኳ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ወደ ቤተ መቅደስ እየሄዱ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ አጥብቀው ይለምኑት ነበር፡፡ መብዓ ይዘው ለሊቀ ካህኑ ሲሰጡት ሊቀ ካህኑም እንኳ ሳይቀር ‹‹እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ያለውን ሕግ በእናንተ ላይ እንዳይፈጸም አድርጎ ልጅ የከለከላችሁ ኃጢአተኛ ብትሆኑ ነውና መብዓችሁን አልቀበልም›› ብሎ በእጅጉ አሳዝኗቸዋል። በሊቀ ካህኑ እያዘኑና እየተከዙ ሲመለሱ ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠው ሳለ እርግቦች ጫጩቶቻቸውን ሲያጫውቱ ተመልክተው ‹‹ለእነዚህ ወፎች እንኳ ልጆችን የሰጠህ አምላክ ለእኛስ መች ይሆን ልጅ የምትሰጠን?›› ብለው እጅግ አምርረው አለቀሱ፡፡ ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐና ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ከዘካርያስ ከሊቀ ካህናቱ ሄደው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ውኃ ቀድታ መሶብ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን›› ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ዘካርያስም ‹‹እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ የልቦናችሁን ሀሳብ ይፈጽምላችሁ›› ብሎ አሳረገላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት ሐናና ቅዱስ ኢያቄም ዕለቱን ራእይ አይተው ነገር አግኝተው አደሩ፡፡ ራእዩስ እንዴት ነው ቢሉ ኢያቄም ‹‹ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› አላት፡፡ ‹‹ወፍ›› የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባህሪው ነው፤ ‹‹ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› ማለቱ የኢያቄምን (የሰውን) ባህርይ ባህርይ እንዳደረገው ዕወቅ ሲል ነው፡፡ ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ልዩ ባሕርይው ምልአቱ ስፍሃቱ ርቀቱ ልእልናው ናቸው፡፡ ቅድስት ሐናም ‹‹እኔም ደግሞ አየሁ እንጂ›› አለችው፡፡ ‹‹ምን አየሽ?›› ቢላት ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ›› አለችው፡፡ ‹‹ርግብ›› የተባለች እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት፣ ነጭነቱ ንጽህናዋ ቅድስናዋ ድንግልናዋ ነው፡፡ ‹‹ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ›› ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችንን መፀነሷን ነው፡፡ ይህንኑም ራእይ ያዩት ሐምሌ 30 ዕለት ነው፡፡ እነርሱም እንዲህ ያለ ራእይ ካየን ነገር ካገኘን ብለው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም ይልቁንም ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ብለው አዳምንና ሔዋንን ‹‹‹ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት› ብሎ ያበሰረ አምላክ ለእኛስ ይልክልን የለምን!›› ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ ሰባት ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን ‹‹ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁና ዛሬ በሩካቤ ሥጋ ተገናኙ ብሎሏችኋል ጌታ›› ብሎ መልአኩ ለሐና ነገራት፡፡ በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም ተፀነሰች፡፡

ቅዱስ ዳዊት ታላቅና ገናና የከበረ ንጉሥ ከመሆኑ የተነሣ መንግሥቱ የመሢሕ መንግሥት ምሳሌ ሆኗል፤ መሢሑም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዳዊት ስም ብዙ ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅሶ ይገኛል። (ኢሳ 9፡7፣ ኤር 23፡5-6፣ ኤር 33፡14-17፣ ሕዝ 34፡23፣ ሆሴዕ 3፡5) በሐዲስ ኪዳንም ወንጌላዊያኑ ጌታችንን ‹‹የዳዊት ልጅ›› በማለት ነው መጀመሪያ ነገረ ልደቱን ማውሳት የጀመሩት፡፡ ማቴ 1፡1፡፡ ራሱ ጌታችንም ‹‹እኔ የእሴይ ሥርና የዳዊት ዘር ነኝ›› ብሏል፡፡ ራእ 22፡16፡፡ ቅዱስ ዳዊት 7 ሀብታት የተሰጡት ጻድቅ አባት ነው፡፡ እነዚህም የተሰጡት ሀብታት፡- ሀብተ ክህነት፣ ሀብተ መንግሥት፣ ሀብተ መዊዕ (የማሸነፍ ሀብት)፣ ሀብተ ትንቢት፣ ሀብተ ኃይል፣ ሀብተ በገና (ዝማሬ) እና ሀብተ ፈውስ ናቸው። ቅዱስ ዳዊት 24 ሰዓት ሙሉ የእግዚአብሔር ምስጋና እንዳይቋረጥ መዘምራንን መድቦ እንዲያገለግሉ ያደርግ ነበር፡፡ ራሱም 10 አውታር ባለው በገና ሌት ተቀን በፍጹም ተመስጦ ያመሰግን ነበር፡፡ በመዝሙሩም አጋንንትን ያቃጥል ነበር፡፡ መዝሙረ ዳዊት በውስጡ የያዘው ሚሥጢር እጅግ ጥልቅ ነው፡፡ አባቶቻችን ዛሬም በዱር በጫካ ሆነው መዝሙረ ዳዊትን አብዝተው ይደግማሉ፡፡ እንኳንስ የሰው ልጅ ይቅርና ‹‹መዝሙረ ዳዊትን›› ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክትም እግዚአብሔርን ለማመስገኛነት ተጠቅመውበታል፡፡ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እድሜ ዘመኑን እግዚአብሔርን በማገልገልና በመፍራት ኖሮ በታኅሣሥ 23 ቀን በሰላም ዐርፎ በኢየሩሳሌም ተቀብሯል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ https://t.me/finotebirhan12

ለአባታችን አዳምም ዘጠኝ መቶ ሠላሳ ዓመት ሲሆን መላልኤልም መቶ ሠላሳ አምስት ዓመት ሲሆነው በተፈጠረባት ዐርብ በዘጠኝ ሰዓት አረፈ ያረፈባትም ሰዓት ከገነት የወጣባት ናት በዚያን ጊዜም የመላእክት ሠራዊት ከልጆቹ ጋራ ተሰበሰቡ። መልካም አገናነዝም ገነዙት በብዙ ሽቱዎችም መዓዛውን አጣፈጡ። ይህም በገነትና በደብር ቅዱስ ያለ ነው ስጋውንም በፀሐይ መውጫ በኲል በዋሻ ውስጥ አኖሩ የሚያበራ መብራትም አኖሩ ከእርሱም ጋራ ወርቁን ከርቤውንና ዕጣኑን አስቀመጡ ዋሻውንም በአዳምና በሔዋን በሴት ቁልፍ ቆልፈው አተሙት። የጥፋት ውኃም እስከ መጣ ድረስ ሴትና ልጆቹ ለአባታችን አዳም ሥጋ ሲያገለግሉ ኖሩ። ከዚህ በኃላም ኖኅ በአምላክ ትእዛዝ ደብረ አራራት እስከሚአደርሰው ከእርሱ ጋራ የአባታችን የአዳምን ሥጋ በመርከብ ወሰደው። ከዚያም ሴምና መልከ ፀዴቅ የእግዚአብሔር መልአክ እየመራቸው ይዘውት ሔዱ ከቀራንዮ ቦታ ደርሰው በዚያ ቀበሩት መልከ ጼዴቅም በዕጣንና በቁርባን ሲያገለግል ኖረ። የእግዚአብሔርም ልጅ መጥቶ ከድንግል ልጁ በተወለደ ጊዜ መድኃኒት በሆነች ሞቱ አድኖ ወደ ቀደመው ርስቱ መለሰው እርሱ ለከበሩ ደጋጎች ነቢያት ለተጋዳዮችም ሰማዕታትና ጻድቃን አባት ነውና ስለ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ ወደ ዓለም መጥቶ ሰው ሁኗልና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባታችን_ቅዱስ_ኖኅ (ልደቱ) ዳግመኛም በዚህች ቀን ከአባታችን አዳም ጀምሮ አሥረኛ ትውልድ የሆነ ጻድቁ ኖኅ ልደቱ ነው፡፡ እርሱም ከታናሽነቱ ጀምሮ ኃጢአት እንደሚበዛና ደጋጎች እንደሚያንሱ ሥጋ የለበሰ ሁሉ በጥፋት ውኃ እንደሚደመሰስ አምላካዊ ምሥጢርን የሚያይ ሆነ፡፡ ስለዚህም ፊቱ የተቋጠረ ሆኖ ፈጽሞ ያለቅስ ነበር፡፡ ጻድቁ ኖኅ ኖኅም የአቡዚር ልጅ የሆነች ሐይከል የምትባል ሴት አግብቶ ወደ እርሷ ሦስት ጊዜ ቢገባ ሦስት ልጆችን ሴም ካም ያፌትን ወለዳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ለኖኅ ከደብር ቅዱስ ዕንጨት ቆርጦ መርከብን እንዲያሠራ ካዘዘው በኋላ አሠራሯን በዝርዝርና በጥልቀት አስረዳው፡፡ የቃየል ልጆችም ኖኅን መርከብ ሲሠራ አይተው ዘበቱበት፡፡ የአዳምንም ሥጋ ወስዶ በውስጡ አኖረ፡፡ ሴም ወርቁን፣ ካም ከርቤውን፣ ያፌት ዕጣኑን ወስደው ወደ መርከብ አስገቡ፡፡ ኖኅም ከልጆቹና 500 ዓመት ድንግልናውን ጠብቆ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ለአባታችን አዳም ሥጋ ሲያገለግል ኖረ፡፡ ከዚህም በኋላ ሚስት እንዲያገባ እግዚአብሔር አዘዘው፡፡ ሥጋ የለበሰ ሁሉ እንደሚደመሰስ ከእርሱ ዘር በቀር የሚተርፍ እንደሌለ ነገረው፡፡ ጻድቁ ከሚስቶቻቸው ጋራ ወደ መርከቡ ገባ፡፡ ንጹሐን የሆኑት እንስሳትና አእዋፋት ሴትና ወንድ ሰባት ሰባት፣ ንጹሐን ካልሆኑት ደግሞ ሁለት ሁለት ሴትና ወንድ አስገባ፡፡ ከዚያም ሰማይ ተከፍቶ የምድርም ምንጮች ሁሉ ተነድለው ራጃጅም ተራራዎችም እስኪሸፈኑ ድረስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ዘነመ፡፡ ውኃውም በላያቸው 15 ክንድ ከፍ አለና ሥጋ የለበሰ ሁሉ ሞተ፡፡ ከ150 ቀንም በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን አስቦ ነፋስን በምድር ላይ አመጣና ውኃውን አጎደለ፡፡ ምንጮች ተደፍነው የሰማይ መስኮት ተዘጋ፡፡ መርከቢቱም በ7ኛው በ12ው ቀን አራራት ተራራ ላይ አረፈች፡፡ ከጊዜም በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን ከነቤተሰቡ አንድ ላይ ከመርከቡ እንዲወርዱ አዘዘው፡፡ ኖኅም መሠዊያን ሠርቶ ንጹሕ ከሆኑት ሁሉ ወስዶ መሥዋዕት ባቀረበ ጊዜ እግዚአብሔር መልካም መዓዛን አሸተተ፡፡ ዳግመኛም ምድርን በንፍር ውኃ እንዳያጠፋ ቃልኪዳን ገባለት፡፡ ምድር ፀንታ በምትኖርበት ዘመን ሁሉ ዘር መከር፣ ቅዝቃዜና ሙቀት፣ በጋና ክረምት፣ መዓልትና ሌሊት እንደማይቋረጥ ቃልኪዳን ገባለት፡፡ እግዚአብሔርም ኖኅንና ልጆቹን ባረካቸው፡፡ ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉዋት ግዟት አላቸው፡፡ ኖኅም ምድርን ያርሳት ይቆፍርራትም ጀመር፡፡ ወይንም ተክሎ ከእርሶ ፍሬውን አድርሶ ወይን ጠጥቶ በሰከረና ራሱን በሳተ ጊዜ የከነዓን አባት ካም የኖኅን ራቁትነት አይቶ ሳቀ፣ ሄዶም ለሁለቱ ወንድሞቹ ነገራቸው፡፡ ያፌትና ሴምም ልብስ ወስደው የአባታቸውን ርቃን ሸፈኑ፡፡ ኖኅም ከስካሩ በነቃ ጊዜ ሁሉም ያደረጉትን ዐወቀ፡፡ ‹ከነዓን የተረገመ ይሁን፣ ለወንድሞቹም ተገዥ አገልጋይ ይሁን› ብሎ ከረገመው በኋላ ‹‹የሴም ፈጣሪ እግዚአብሔር ይመስገን፣ እግዚአብሔርም የያፌትን አገር ያስፋ፣ በሴም ቤትም ይደር›› ብሎ መረቃቸው፡፡ አባታችን ኖኅ ‹‹እግዚአብሔር በሴም ቤት ይደር›› ማለቱ የጌታችንን ሰው መሆን በትንቢት መናገሩ ነው፡፡ እርሱም ከጥፋት ውኃ በኋላ 350 ኖረ፡፡ በአጠቃይ ዕድሜው 950 ዓመት በሆነ ጊዜ በሰላም ዐረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ልበ_አምላክ_ቅዱስ_ዳዊት (ልደቱ) በዚህችም ቀን የሰሎሞን አባት ንጉሡ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ልደቱ ነው፡፡ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ነሐሴ 13 ቀን ተጸነሰ፣ በሚያዝያ 6 ቀን በይሁዳ በቤተልሔም ሀገር ተወልደ። 1ኛ ሳሙ 16፡10-11፡፡ ዳዊት ማለት ‹‹ኅሩይ›› ማለት ነው። አንድም ‹‹ልበ አምላክ›› ማለት ነው። ሐዋ 13፡22፡፡ ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ ነው። አባቱ እሴይ እናቱ ሁብሊ ይባላሉ። ሁብሊ መልከ መልካም ሴት ነበረች። ከጎረቤታቸው ያለ ጎልማሳ መልኳን እያየ በሐጸ ዝሙት ተነደፈ። እሴይ የእሷም ፈቃድ እንደሆነ አውቆ መንገድ እሄዳለሁ ብሎ ስንቁን ይዞ ወጣ። የሄደ መስሎ ከዚያው ውሎ ሲመሽ በልብሱ ተሸፋፍኖ ድምጹን ለውጦ ያንን ሰው መስሎ ገብቶ ከእርሷ ጋር አድሮ ጎህ ሳይቀድ ወጥቶ ሄደ። ዳዊት በዚህ ዕለት ተጸንሷል። በዓመፃ ተፀነስሁ፥ እናቴም በኃጢአት ወለደችኝ” (መዝ 50፡5) ማለቱ ስለዚህ ነው። ቅዱሱም ተወልዶ ጉልበቱ ከጸና በኋላ የአባቱን በጎች ሲጠብቅ አድጓል። እረኛና ብላቴና የነበረ ቢሆንም የፍልስጤማውያኑን ኃያል ሰው ጎልያድን በ12 ዓመቱ 5 ጠጠርን ከወንዝ ለቅሞ በወንጭፍ ወርውሮ ገድሏል፡፡ 1ኛ ሳሙ 12፡45-51፡፡ ንጉሥ ሳዖል በጌልቦአ ተራራ በራሱ እጅ ከሞተ በኋላ አስቀድሞ በይሁዳ 7 ዓመት በመላው እስራኤል 33 ዓመት ነግሡዋል፡፡ 2ኛ ሳሙ 2፡4፤ 5፡1-5፡፡‹‹እግዚአብሔር እንደ ልቡ የሆነ ሰው መርጦአል” (1ኛ ሳሙ 13፡14) ተብሎ በእግዚአብሔር የተመረጠና ነገረ ሥጋዌን፣ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን፣ ዳግም ምጽዓትን፣ ነገረ ማርያምን፣ ክብረ ቅዱሳንን፣ በስፋትና በጥልቀት የተናገረ የብሉይ ኪዳን ‹‹ወንጌላዊ›› የተባለ ቅዱስ ነቢይ ነው። “ብዙ ውሾች ከብበውኛልና የክፋተኞች ጉባኤም ያዘኝ እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ። አጥንቶቼ ሁሉ ተቈጠሩ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም። ልብሶቼን ለራሳቸው ተከፋፈሉ፥ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ…” እያለ የጌታችንን መከራ መስቀል በትንቢት ተናግሯል፡፡ መዝ 21 (22)፡ 16-18፡፡ “አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።”፣ “ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል። አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም እሳት በፊት ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ…” እያለ የጌታችንን ዕርገቱንና ዳግመኛ ለፍርድ የሚመጣ መሆኑን በግልጽ ተናግሯል፡፡ መዝ 46(47)፡4-5፣ መዝ 49(50)፡ 1-5፡፡ “የንጉሦች ሴት ልጆች ለክብርህ ናቸው በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እያለ የእመቤታችንን ክብር አይቶ በትንቢት ተናግሯል፡፡ መዝ 44(45)፡9፡፡

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_6 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ስድስት በዚህችም ቀን #የአባታችን_አዳምንና #የእናታችን_ሔዋን መታሰቢያቸውን ነው፣ ከአባታችን አዳም ጀምሮ አሥረኛ ትውልድ የሆነ #ጻድቁ_ኖኅ ልደቱ ነው፣ ንጉሡ ልበ አምላክ #ቅዱስ_ዳዊት ልደቱ ነው፣ በበረሀ የምትኖር #ግብፃዊት_ማርያም አረፈች፣ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሣኤው ሳምንት #ለሐዋርያው_ቶማስ ተገለጠለት፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_አዳምና_ሔዋን ሚያዝያ ስድስት በዚህችም ቀን የአባታችን አዳምን የእናታችን ሔዋንን መታሰቢያቸውን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙን። ይህን አባታችን አዳምን ሳይፈጥረው አስቀድሞ በሰማይና በምድር ያለውን አዘጋጀለት። ሐዋርያው ጳውሎስ እንደተናገረ መላእክትንም ስለርሱ ፈጠረ። ከዚህም በኃላ በኤዶም ተክልን አዘጋጀለት እርሱም የፍሬው ጣዕም በየራሱ ልዩ ነው የሚአሻውን ሁሉ አከናውኖ እነሆ ከምድር መካከል ይኸውም ጎልጎታ ነው አፈር አንሥቶ በሦስት ሰዓት እርሱን ፈጠረው። ከአራት በሕርያት ይኸውም ውኃ እሳት ነፋስና መሬት ነው በአርአያውና በምሳሌው ራሱን አስመስሎ ፈጠረው በፊቱም እፍ ብሎ የሕይወት መንፈስን አሳድሮ የሚናገርና የሚያስተውል የሚያውቅ አደረገው የብርሃንንም ልብስ አልብሶ ንጉሥ ነብይ ካህን አስተዳደሪ አድርጎ በፈጠረው ሁሉ ላይ ሾመው። ከዚህም በኃላ አይቶ ስማቸውን ይሰይም ዘንድ አራዊትን እንስሳትን የሰማይ ወፎችን ሁሉ ወደርሱ አመጣ። አዳምም መንፈስ ቅዱስ እንዳናገረው ለሁሉም ስም አወጣላቸው። ከዚህም በኃላ በአዳም ላይ እንቅልፍን አመጣበትና አንቀላፋ ከጐኑም አንድ ዐጥንትን ነሣ ቦታዋንም በሥጋ መላው እግዚአብሔርም ሴት አድርጎ አሰምሮ ሠራት በአዳምም በፊቱ አኖራት። አዳምም ነቅቶ ይቺ ከዐጥንቴ ዐጥንት ከሥጋዬ ሥጋ ናት ሚስት ትሁነኝ ብሎ ተናገረ ስሟንም ሔዋን አላት። አዳምም በጎልጎታ ቁሞ የፈጣሪውን ቃል እየሰማ ሳለ እነሆ ከሚስቱ ከሔዋን ጋራ በፊት በኃላ ሁነው በየነገዳቸው አዳምን ስለ አከበረው መላእክት እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ደመና ተሸክማ ወሰደቻቸው በኤዶም ገነትም አኖራቸው። እግዚአብሔርም አዳምንና ሔዋንን በገነት ካለው ተክል ሁሉ ብሉ ግን ከገነት መካከል ዕፀ በለስን አትቡሉ ከእርሱ በበላችው ቀን ሞትን ትሞታላችሁ አላቸው። አዳምም ገነትን እያረሰና እየቆፈረ ከፍሬዋም እየተመገበ ከመላእክት ጋራ ሲያመሰግን ኖረ። የበጎ ሥራ ጠላት ሰይጣን ግን ከማዕርጉ በወደቀ ጊዜ በአዳም ጌትነትና ክብር ቀንቶ በእባብ አድሮ ወደሔዋን ሔደ። ያንን ዕፀ በለስንም ትበላ ዘንድ አታለላት አምላክ የመሆንንም ተስፋ አሳደረባትና አሳታት። ያንን ዕፀ በለስንም በአየችው ጊዜ አማራት በልታ ለባልዋም አበላችው ያን ጊዜ የብርሃን ልብሳቸው ከላያቸው ተገፈፈ። እነርሱም ራቁታቸውን እንደሆኑ አውቀው በበለስ ቅጠል ኀፍረተ ሥጋቸውን ሸፈኑ። እግዚአብሔርም ስሕተታቸውን አውቆ አስቀድሞ እባብን ረገመ በእርሷና በሴቲቱ ዘር መካከል ጠላትነትን አጸና። በሔዋንም ላይ በፃር በገዐር ውለጂ ወልደሽም መመለሻሽ ወደባልሽ ይሁን እርሱም ይግዛሽ ብሎ ፈረደባት። አዳምንም እንዲህ አለው ስለ አንተ ምድር የተረገመች ትሁን ጥረህ ግረህ እንጀራህን ብላ አንተ አፈር ነህና ወደ አፈርነት ትመለሳለህ። እግዚአብሔርም የቁርበትን ልብስ አዘጋጅቶ አለበሳቸው ሰባት ዓመት በተድላ ከኖሩ በኃላ በምሽት ጊዜ ከኤዶም ገነት ወጡ። አዳምም በማለዳ ፀሐይ ሲወጣ ነጭ ዕጣን ቀንዓት ሰሊሖት የሚባል ሽቱ ከሎሚ ውኃ ጋር አጠነ። አዳምም በኤዶም ገነት እንደተማረ ምድሪቱን እያረሰና እየቆፈረ ኤልዳ በሚባል ምድር ኖረ። አዳምም ሔዋንን በግብር አወቃት ቃየልን ከእኅቱ ጋር ወለደችለት ከእርሱም በኃላ አቤልን ከእኅቱ ጋራ ወለደችው ቃየልና አቤልም አድገው አካለ መጠን አደረሱ። ወደ እግዚአብሔርም መሥዋዕት በአቀረቡ ጊዜ ጌታ የአቤልን መሥዋዕት ተቀበለ ስለዚህም ቃየል ተቆጣ በአቤልም ቀንቶ ገደለው። አዳምም በልጁ በአቤል ሞት እያዘነና እያለቀሰ አራት የዘመን ሱባዔ ኖረ። ከዚህም በኃላ ሴት ተወለደለት በእርሱም መታሰቢያው ጸና ከእርሱም በኃላ ብዙዎች ወንዶችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ። እግዚአብሔርም ንስሓውንና ልቅሶውን አይቶ የድኅነት ተስፋ ሰጠው። አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ወደ ዓለም መጥቼ ከልጅ ልጅህ እወለዳለሁ ሕፃንም ሆኜ በሜዳህ ውስጥ እድሀለሁ በመስቀሌና በሞቴም አድንሃለሁ አለው። አዳምም ከገነት በወጣ ጊዜ የወሰደውን ወርቅ ከርቤና ዕጣን ለልጁ ለሴት ሰጠው እንዲህም አለው በኃላ ዘመን የእግዚአብሔር ልጅ መጥቶ ከድንግል ይወለዳል ያን ጊዜ የጥበቡ ሰዎች ይህን ወርቁን ከርቤውንና ዕጣኑን እጅ መንሻውን ያመጡለታል እርሱም መዝግቦ በዕቃ ቤት አኖረው። ወደ ኖኅም እስኪደርስ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ ኖረ ከኖኅም የምሥራቅ ሰዎች ወደ ሆኑ የጥበብ ሰዎች እስኪ ደርስ ተላለፈ። እነርሱም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ በተወለደ ጊዜ አምጥተው ለእግዚአብሔር ልጅ እጅ መንሻ አድረገው አቀረቡለት እመቤታችንም ከእጃቸው ተቀበላ በኃላ ለቅዱስ ጴጥሮስ ሰጠችው ቅዱስ ጴጥሮስም ለቀሌምንጦስ ሰጠው። አዳምም የሚያርፍበትን ሰዓት በአወቀ ጊዜ ልጁ ሴትን ጠርቶ ከመሞቴ በፊት ልጆችህንና የልጅ ልጆችህን ወደእኔ አቅርባቸው አለው። የአባቱን ቃል ሰምቶ ዕንባው በጉንጩ ላይ እየፈሰሰ ወጣ ወደ አዳምም አቀረባቸው። አዳምም በአያቸው ጊዜ ከእሳቸው ስለ መለየቱ አለቀሰ። እነርሱም ሲያለቅስ በአዩት ጊዜ ሁሉም በአንድነት ወደ እግዚአብሔር በግምባራቸው ተደፍተው አለቀሱ ምድር እንዴት ትሸፈንሃለች ከዐይኖቻችንስ እንዴት ትሠወራለህ አሉ። ከዚህም በኃላ አባታችን አዳም ሁሉን ልጆቹን ባረካቸው መረቃቸው። ልጁን ሴትን እንዲህ አለው ይቺ ዓለም ድካምና ችግርን የተመላች ናትና በእግዚአብሔር እየታመንክ ዕውነትን ንጽሕናን ጠብቅ ሰይጣን ወደ ሚያሳይህ ምትሐቱና ወደ ነገሩ አታዘንብል። በሞትኩ ጊዜም ሥጋዬን ወስዳችሁ ሰሊክ ሚዓ በሚባል ሽቱ ገንዛችሁ በግምጃ ቤት አኑሩኝ የጥፋት ውኃ ይመጣ ዘንድ አለውና ፍጥረት ሁሉ ይሰጥማል ከስምንት ነፍስ በቀር የሚቀር የለም። ልጄ ሆይ ለወገኖችህ ቋሚ ሁነህ እግዚአብሔርን በመፍራት ጠብቃቸው የዕውነት መንገድንም ምራቸው ለስይጣንም እንዳይ ታዘዙና እንዳያጠፋቸው አደራ አስጠብቃቸው። ልጆችህንና የልጅ ልጆችህን ከቃየል ልጆች ለያቸው አንድ ይሆኑ ዘንድ ከቶ አትተዋቸው ወደ ሥራቸውና ወደ ጨዋታቸውም አይቅረቡ። ከዚህም በኃላ ወደ ልጁ ወደ ሴትና ወደ ሔዋን መለስ ብሎ ያንን ወርቅ ከርቤና ዕጣን ከእርሳቸው ጋራ አኑረው ይጠብቁት ዘንድ አደራ አላቸው። እንዲህም አላቸው የጥፋት ውኃ በመጣ ጊዜ ሥጋዬን ከወርቁ ከከርቤውና ከዕጣኑ ጋራ ወደ መርከብ ያስገቡ ከዚያም በኃላ በምድር መካከል ያኑሩት። ከብዙ ዘመናት በኃላም ያቺን አገር ይወርዋታል እሊህንም ወርቅ ከርቤና ዕጣን ከብዙ ምርኮ ጋር ይወስዱትና አካላዊ ቃል መጥቶ ሰው እስከሚሆን ድረስ በዚያ ይጠበቃል። ነገሥታትም ይዘው መጥተው ይገብሩለታል ወርቁ ስለ መንግሥቱ ዕጣኑ ስለ ክህነቱ ከርቤውም ማሕየዊት ስለሆነች ሞቱ ነው።

ቅዱስ ያሬድ ካህንም የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ወዳለችበት ጽዮን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ሁለት እጆቹን በታቦተ ጽዮን ላይ አኑሮ "ቅድስት ወብፅዕት፣ ስብሕት ወቡርክት፣ክብር ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዓርገ ሕይወት" ብሎ በደረሰው አንቀጸ ብርሃን ጸሎት እመቤታችንን አመሰገ። በዚህ ጊዜ እጁ በታቦተ ጽዮን ላይ ረቦ በመንፈስ ቅዱስ እየተቃኘ ስለነበር ከመሬት አንድ ክንድ ከፍ ከፍ ብሎ ይታይ ነበር። እስከመጨረሻው በከፍተኛ ቃል በዕዝል ዜማ እየዘመረ እግዚአብሔር እና እመቤታችንን ከአመሰገነ በኋላ እመቤታችንበጸሎት መንገድ እንድትመራውና እስከ ፍጻሜ ገድሉ ትረዳው ዘንድ በጸሎት ለመናት። እመቤታችንም መልሳ "ሰማያዊት ጽዮን ያደረግኻት መቅደሴን፣ በመዝሙር በማሕሌት ምስጋና የኪሩቤልና የሱራፌል ወገን ሰማያውያን ያደረግኻቸው ልጆቼ ካህናትን እንዴትድረስ ትተህ ትሔዳለህ" ብላ ቃል በቃል አነጋገረችው። የመንገዱን ስንብት እስክትፈቅድለት በለቅሶና በእንባ ዳግመኛ ለመናት እርሷም እንዲሔድ ፈቀደችለት። የቅዱስ ያሬድ ምናኔ፦ ወደ ገዳም ሊሆድ ተዘጋጀ በዚህ ጊዜ የሚወዱት ካህናት፣ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ተከትለውት እስከ ተከዜ ወንዝ ድረስ ሸኙት። ከእርሱ በሚለዩበትም ጊዜ "ሰላመ ነሳእነ ወሰላም ኃደግነ ለክሙ ወሰላመ እግዚአብሔር የሀሉ ምስለ ኩልክሙ፤ ሰላምን ከእናንተ ተቀበልን ለእናንተም ሰላምን ተውንላችሁ የእግዚአብሔር ሰላምም ከሁላችሁ ጋራ ይኹን" ብሎ በዜማ ተሰናበታቸው። ዳግመኛ "ወሰላም እግዚአብሔር እንተ ኵሉ ባቲ ተሀሉ ወትረ ምስለ ኵልክሙ፤ ፍቅርና ስምምነት ሁሉ ያለበት የእግዚአብሔር ሰላምታ ሁል ጊዜ ከሁላችሁ ጋራ ትኑር" ብሎ በጣዕ ዜማው መረቃቸው። ካህናቱም ይህን ሰምተው አለቀሱ። እርሱም ከእርሱ ጋራ አለቀሰ። በዚሁ ጣዕመ ዜማው የመጨረሻ ቡራኬውን ሰጣቸውና እርስ በእርሳቸው ተሳስመው ተነሰነባብተው ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑና እየተከዙ ወደ አገራቸው አኵሱም ተመለሱ። እርሱ ግን የተከዜን ወንዝ ተሻገረ። የወንዙ ፏፏቴና ጎርፍ እንሚጮህ አንበሳ ሲጮህ በሰማ ጊዜ "አኅለፍኮሙ በእግር እንተ የብስ ማእከለ ባሕር ተከዜ...፤ በተከዜ ባሕር መካከል በእግር እንደሚሻገር በደረቅ አሻገርካቸው..." እያለ በረቀቀ ምስጢር እግዚአብሔርን በማመስገን እየዘመረ ሲሒድ አንዲት ሴት ውሃ ቀድታ ወደ ቤቶ ስትመለስ ድምፁን ሰምታ ወይ ቃል! ወይ ቃል! እንዴት አንጀት ይበላል! ምንኛስ ያሳዝናል! ብላ ደጋግማ በማድነቅ ስለ ተናገረች ቅዱስ ያሬድ ቆሞ የዘመረባት ቦታ "ወይ ቃል" ተብላ ተጠራች። ዛሬ ይህች ቦታ ጎንደር ክፍለ አገር ደባርቅ አካባቢ "ወይ ቃል" ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ተብላ ትጠራለች። ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ሔዶ ጸለምት ወጥቶ ብርድ በጸናበት በረዶ በተከማቸበት ሳኔር ተብሎ በሚጠራ በሐዊ ዐምባ ጽመና ይዞ ተቀመጠ። በዚያም በብዙ ትጋት በጾምና በጸሎት ይልቁንም በስብሐት እግዚአብሔር ብቻ ተወስኖ ጉባኤ ዘርግቶ፣ ትምህርት አስፍቶ ከሱራፌል መላእክት እንደተማረው አድርጎ ከጸለምት፣ ከስሜን፣ ከአገውና ከሌላ አገር ወደ እርሱ የሚመጡትን ሰዎች ሁሉ ማሕሌተ እግዚአብሔር እያስተማረ ኖረ። ቅዱስ ያሬድ ከትውልድ አገሩ አኵሱም መንኖ ከወጣ በኋላ ትዕግሥቱን እያዘወተረ ወደ እርሱ የመጡትን ሁሉ በማስተማር በገዳመ ስሜን ኖረ። ቅዱስ ቍርባን ለመቀበልና ቅዱሳት ገዳማትን ለመሳለም በፈለገ ጊዜ በሠረገላ ብርሃን ተጭኖ አኵሱም ደርሶ ቅዱስ ቍርባን ተቀብሎ ሌሎች ገዳማትንም ይሳለም ነበር። በመጨረሻ ቅዱስ ያሬድ ካህን ዘመኑን ሁሉ በመላእክት ማኅሌት እግዚአብሔርን በማገልገልና ይህን ማኅሌት ለሚከተሉት ደቀ መዛሙርት በማስተማር ዘመኑን ፈጽሞ ለሃያ ሁለት ዓመታት በላይ በምናኔ ታግሦ በገድሉና በጣዕመ ዜማው ፀላኤ ሠናያትን ድል አድርጎ ከዚህ ዓለም ድካምና መከራ የሚያርፍበት፣ የሚሰወርበት ቀንና ሰዓት መድረሱን በጸጋ በዐወቀ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን ሰብስቦ "ይቤ ጳውሎስ ኃላፊ ንብረቱ ለዝንቱ ዓለም አኃውየ አስተፋጥኑ ገቢረ ሠናየ አነሰ በድረየኒ ፈጸምኩ ወሃይማኖትየኒ ሠለጥኩ እንከሰ ጽኑሕ ሊተ አክሊል ዘየዓሥየኒ መኰንነ ጽድቅ" 2ጢሞ4፥7-8 እያለ በሚያራራ ቃል ምክሩን ሰጥቶ ተሰናበታቸው። እነርሱም ምክሩን ተቀብለው "አባ አቡነ፣ አባ መምህርነ አይቴ ተሐውር ወለመኑ ተኀድገነ፤ አባታችን መምህራችን ወደ የት ትሔዳለኽ? ለማንስ ትተወናለኽ? እያሉ ሲያዝኑ ሲያለቅሱ በአንድ ዋሻ ውስጥ ገብቶ ግንቦት11 ቀን በ571ዓ.ም ተሰወረ። (ምንጭ፦ የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ቅዱስ ያሬድና የቅዱስ ያሬድ ታሪክ ከሚሉት መጻሕፍት።) ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሕዝቅኤል_ነቢይ ዳግመኛም በዚህች ቀን የካህኑ የቡዝ ልጅ ታላቅ ነቢይ ሕዝቅኤል አረፈ። ይህም ካህንም ነቢይም ሆኖ ናቡከደነጾር የእስራኤልን ልጆች በማረካቸው ጊዜ ወደ ባቢሎን ተማርኮ ሔደ። በባቢሎን አገርም ሳለ የትንቢት መንፈስ በላዩ አደረ በትንቢቱ ውስጥ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያም ስለ መወለዱና ከወለደችውም በኃላ በድንግልና ጸንታ ስለ መኖርዋ ተናገረ። እንዲህም ብሎ ትንቢት ተናገረ እኔ ወደ ምሥራቅ ስመለከት የተዘጋች ደጅ አየሁ። ይህች በር ተዘግታ ትኖራለች አትከፈትም የሚገባባትም የለም። የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር እንደተዘጋች ይገባባታልና ከእርሱ በቀር የሚገባም የሚወጣም የለም አለኝ። ሁለተኛም ስለ ክርስትና ጥምቀት በንጹሕ ውኃ እረጫችኃለሁ ከኃጢአታችሁም ትነጻላችሁ ከርኲሰታችሁም ሁሉ። አዲስ ልብን እሰጣችኃላሁ አዲስ ዕውቀትንም አሳድርባችኃለሁ ድንቊርና ያለበትንም ልብ ከሰውነታችሁ አርቄ ዕውቀት ያለውን ልብ እሰጣችኃለሁ መንፈስ ቅዱስንም ተቀብለው የእግዚአብሔር ልጆች እንደሚሆኑ ተናገረ። ሕዝቡንም ማስተማር ስለ መተዋቸው ካህናትን ሲገሠጽ ካላስተማራችኃቸውና ካላነቃችኃቸው የሰዎችን ነፍስ እግዚአብሔር ከእናንተ ይፈልጋል አላቸው። ደግሞ ስለ ሥጋ መነሣት በሕይወት ለመኖርም ቢሆን ወይም በሥቃይ አስቀድሞ እንደነበሩት በድኖች ተነሥተው ከነፍሶቻቸው ጋራ አንድ ሊሆኑ አላቸው ብሎ ተናገረ። ለሚያነባቸው የሚጠቅሙ ብዙዎች ትምቢቶችን ተናገረ። እግዚአብሔርም በእጆቹ ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶችን ገለጠ። የእስራኤል ልጆች በባቢሎን ሳሉ ጣዖት ባመለኩ ጊዜ ገሠጻቸው። ስለዚህም አለቆቻቸው በጠላትነት በላዩ ተነሥተው ገደሉት ይህም ሁሉ ትንቢቱ የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ሰው ከመሆኑ በፊት ነው። የትንቢቱም ዘመን ሃያ ዓመት ነው። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12