ታኦዳኮስ
رفتن به کانال در Telegram
ታኦዶኮስ (ወላዲተ እግዚአብሔር) ታኦዶኮስ ይሏታል ትርጓሜውም "የአምላክ እናት" ማለት ነው ለዛም ነው ቅድስት ኤልሳቤጥ ☞ በሉቃ 1፥43 ላይ ''የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?'' ያለችው ስለዚህ ብቸኛዋ የአምላክ እናት ስለሆነች "አንዲት" እያልን እንጠራታለን ።
نمایش بیشتر1 187
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-17 روز
-530 روز
آرشیو پست ها
1 187
እንኳን ለአዲሱ ለዘመነ ሉቃስ በሰላም በጤና አደረሰን!!
ይኩን ለኵልነ ወለኵሉ ዓለም ዘመነ ሉቃስ ዘመነ ሰላም፣
የሉቃስ ዘመን በኹላችን በዓለምም ኹሉ የሰላም ዘመን ይኹንልን።
አዲሱ ዓመት ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር የተሰጠን ሌላ አዲስ ዕድል ነው። አማኑኤል ከእኛ ጋር ለመሆን የእኛን ሥጋ ተዋሕዷል። አምላክነቱ ሳያሳስበው የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አድርጉዋል። በደሃ ቤት አድሯል፣ በበረት ተወልዷል፣ ከብርድ መከለያ ጨርቅን ፈልጓል፣ ፍጥረትን የሚመግብ እርሱ ከእናቱ የድንግልናዋን ወተት ለምኖ አልቅሷል፣ እንደ ሕፃናት በጉልበቱ ድኋል፣ ለእናቱ እየታዘዛት ጥቂት በጥቂት አድጓል። ከአደገም በኋላ ራሱን የሚሰውርበት ጎጆ ሳይኖረው በተራራ ተንከራቷል፣ ተርቧል፣ ከኃጢአተኞች በደረሰበት ተቃውሞ ተሰድቧል፣ ተገፍቷል። ከብቻዋ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ሆኗል።
ከእኛ ጋር ለመሆን ብቻ ሳይሆን በእኛ ውስጥ ለመኖር ደግሞ በዕለተ አርብ በመስቀል ተሰቅሎ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ተሰጥቶናል። እኛስ ወደ እርሱ ሊያቀርበን ይህን ሁሉ ከሆነልን አምላክ ጋር ለመኖር ምን አደረግን? ለእርሱ ብለን ክፋትን አወገዝን? የተሸከምነውን ኃጢአት በንስሐ አራገፍን? ሥጋ ወደሙን ተቀበልን?
ከእግዲህስ በኃጢአት ያረጀ ማንነታችንን እንተው። አዲሱን ዓመት "ማለዳ ማለዳ አዲስ" ከሆነው ፈጣሪያችን ጋር ለመኖር ለራሳችን ብሩህ ተስፋ እንሰንቅ። እስኪ አምና ወድቀን ከተሰበርንበት የዘር፣ የጥላቻ ጉድጓድ ወጥተን ዘንድሮን ተዋድደን፣ ተፋቅረን በሰላም እንኑር። እስኪ ደግሞ ወደ ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርበን ይህችን ዓመት በሰላም ጀምረን እንፈጽማት።
መልካም አዲስ ዓመት!!!
1 187
፰ (የመጨረሻ)
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ዳግመኛም አንድ ሰው በመጸለዩ ምክንያት እግዚአብሔርን አስቈጥቷል፡፡ ምክንያቱም ጸሎቱ ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ አልነበረም፤ ርሱም ፈሪሳዊው ነው /ሉቃ.18/፡፡ ፊንሐስ ግድያን ስለ ፈጸመ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት አገኘ፤ ፈሪሳዊው ደግሞ በአንጻሩ ስለ ጸለየ እግዚአብሔርን አስቈጣ፡፡ ስለዚኽ ማናቸውም የምናደርገው ነገር ምንም መንፈሳዊ ቢኾንም ለእግዚአብሔር ክብር እስካልተደረገ ድረስ ትርፉ ጉዳት ነው፡፡ ሥጋዊ ሥራም ብንሠራ ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ሰውን ከመግደል በላይ እጅግ ክፉና ዘግናኝ ነገር ምን አለ? ነገር ግን ይኽ ለእግዚአብሔር ክብር የሚደረግ ከኾነ ከዚኹ ግድያ እንኳን ጽድቅን ማግኘት ይቻላል፡፡
እንግዲኽ ከነፍሰ ገዳይ እንኳን እንዲኽ ዓይነት ጽድቅ ከተገኘ እያንዳንዱ ግብራችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ አይቻለንም እንደምን ማለት ይቻለናል? የልቡና ፈቃደኝነት ካለን ግን ኹሉንም ነገር ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ብንገዛም ብንሸጥም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ከአግባብ በላይ ዋጋን በመጨመር ሸማቹን ማኅበረ ሰብ ባለ ማስቸገር ንግዳችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ አንድን ዕቃ በመደበቅ (አኹን ባለው የአገራችን ተጨባጭ ኹኔታ ዘይትንና ስኳርን ማለት እንችላለን) አለአግባብ ለመክበር ብለን የምንደብቀው ከኾነ “እኽልን የሚያስቀር ሰው በሕዝቡ ዘንድ የተረገመ ነው” እንደተባለ /ምሳ.11፥26/ ንግዳችን እግዚአብሔር የከበረበት ንግድ አይደለም፡፡
ከእናንተ መካከል፡- “አባታችን! አንድ ምሳሌ መስለኽ ልታስተምረን ስትችል ወደዚኽ ኹሉ ዝርዝር መግባት ለምን አስፈለገኽ?” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ አንድ የሕንፃ ተቋራጭ አንድን ሕንፃ ለመገንባት የሚዠምረው መሠረት በመጣል ነው፡፡ ከዚያም ደረጃ በደረጃ የተቀረውን የሕንፃን ክፍል ይገነባል፡፡ በመጨረሻም ሕንፃው እጅግ የሚያምር እንዲኾን የቅብ (finishing) ሥራን ይሠራል፡፡ እኛም ይኽን ኹሉ በዝርዝር ማየታችን በክፍል 2 ትምህርታችን፡- ወዳጄ ሆይ! ቤቱ ቆሽሾ ሳለ ውጫዊ በሩን ብቻ ለማሽቀርቀር ለምን ትጨነቃለኽ? ነፍስህ በኀጢአት ተዳድፋ ሳለ ሥጋኽን ብቻ ለማስደሰት ለምን ትሮጣለኽ? አስቀድመኽ ቤቱን (ነፍስኽን) ለማስዋብ አትሽቀዳደምምን? አስቀድመኽ ለነፍስኽ የምታስብ ከኾነ ከሰው እጅ ሳይኾን ከክርስቶስ እጅ ሹመት ሽልማት ትቀበላለኽ፡፡ ኹል ጊዜ “የማደርገው ነገር እግዚአብሔር ይከብርበታልን?” ብለኽ አስብ እንጂ እንዲኹ ከአኹን (ከአዲሱ ዓመት) በኋላ በዘልማድ የምትመላለስ አትኹን ብዬ እመክርኻለኁ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመክረን፡- “እንግዲኽ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትኾኑ ወይም ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ኹሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ያለንም ስለዚኹ ነውና በአዲሱ ዓመት በድርጊቶቻችን ኹሉ እግዚአብሔርን ለማክበር እንዘጋጅ /1ኛ ቆሮ.10፡31/፤” የሚለውን መሠረት ይዘን ነው፡፡
ከእንግዲኽ ወዲኽ ብንጸልይም፣ ብንጦምም፣ ብንገሥፅም፣ ይቅር ብንልም፣ ብናመሰግንም፣ ብንወቅስም፣ ብንገባም፣ ብንወጣም፣ ብንሸጥም፣ ብንገዛም፣ ብንናገርም፣ ዝም ብንልም፣ ማናቸውን ነገር ብናደርግ ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርጋቸው ይገባናል፡፡ ይኽን ያልዠመርን ካለንም አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ እንዠምረው፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር የማናደርገው ከኾነ ግን አንሥራው፤ በማኅበር መካከል እንድንናገር ብንገፋፋም አንናገር፡፡ የትም ብንሔድ ይኽቺውን የሐዋርያው ቃል በልቡናችን ጽላት ጽፈን ይዘናት እንሒድ፡፡ ርሷም (ኃይለ ቃልዋ) የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር እንድናደርገው ታሳስበናለች፡፡ የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር የምናደርገው ከኾነም “ያከበሩኝን አከብራለኹ” ብሏልና /1ኛ ሳሙ. 2፥30/ ከሰው እጅ ሳይኾን ከራሱ ከክብር ባለቤት ከልዑል እግዚአብሔር ዘንድ በዚኽም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም ክብርን እንጐናጸፋለን፡፡
እንኪያስ ከእንግዲኽ ወዲኽ ክብር የክብር ክብር፣ አምልኮና ውዳሴ ለአምላካችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ይገባዋልና በቃል ብቻ ሳይኾን በገቢር ጽድቅ በምግባር በትሩፋት ዘወትር እናክብረው፡፡ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ አሜን!!!
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፯
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ትዳራችን እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ መኝታችን (በትዳር ውስጥ የሚደረገው ሩካቤ) ንጹሕ ማድረግ፣ ትዳርን ለብር ወይም ሌላ ምድራዊ ነገርን ለማግኘት ሳይኾን ነፍሳችንን ለማዳን፣ እግዚአብሔርን ለማግኘት የሚደረግ ከኾነ ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ የትዳር አጋራችንን ከዘለዓለማዊ ሕይወት አንጻር እንጂ ከውበት፣ ከሃብት፣ ወይም ከሌላ ጊዜአዊ ጥቅም አንጻር የማንመለከት ከኾነ ትዳራችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ በአዲሱ ዓመት ይኽን ልንለማመድ ይገባናል፡፡ እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የሚምትወዱት ልጆቼ! ይኽን ኹሉ በዝርዝር የምነግራችኁ ለምን ይመስላችኋል? ይኽን ኹሉ በዝርዝር መናገሬ በዘዴ ኹላችንም የምናደርገውን ማናቸውም እንቅስቃሴያችን ለእግዚአብሔር ክብር እናደርገው ዘንድ ስለምሻ ነው፡፡ በባሕር የሚነግዱ ነጋዴዎች ንብረታቸውን ወደ ከተማ ዳር መልሕቅ ካመጡ በኋላ መዠመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር በቀጥታ ወደ ገበያ ሥፍራ መሔድ አይደለም፡፡ ወደ ገበያ ሥፍራ ከመሔዳቸው በፊት ስለ ትርፋቸው ያስባሉ እንጂ፡፡ እኛም በምናደርገው ኹሉ ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘውን ጥቅም ማሰብ አለብን፡፡
ከእናንተ መካከል፡- “ኹሉንም ነገር ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ማድረግ ግን የሚቻል አይደለም” የሚል ፈጽሞ አይገኝ፡፡ ጫማችንን ብንጫማ፣ ፀጕራችንን ብናስተካክል፣ ልብሳችንን ብንለብስ፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ብንጓጓዝ፣ የቁመናችን አኳኋን፣ ንግግራችን፣ ስብስባችን፣ መግባታችን፣ መውጣታችን፣ መገሠፃችን፣ ማመስገናችን፣ መውቀሳችን፣ አለ መውቀሳችን፣ ሰውን ወዳጅ ወይም ጠላት ማድረጋችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ የሚቻለን ከኾነ እኛ ከፈቀድን ለእግዚአብሔር ክብር ተብሎ የማይደረግ ምን ይቀራል? የወኅኒ አለቃ ከመኾን ምን የከፋ አለ? የወኅኒ ጠባቂ ሕይወት እጅግ የምትከብድ አትመስልምን? ነገር ግን የልቡና ፈቃደኝነት ካለን የወኅኒ አለቃም ተኩኖ ኹሉንም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻላል፡፡ እስረኞችን ማዳን ይቻላል፡፡ ያለ አግባብ የታሰሩትን መንከባከብ ይቻላል፡፡ ንጹሐን ሰዎችን አለ አግባብ ከሚያሰቃዩ ክፉዎች ጋር አለመተባበር ይቻላል፡፡ እስረኞችን እንደ አለቃ ሳይኾን እንደ ወንድምና እኅት ማገልገል ይቻላል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ሃይማኖት የመለሰውን የወኅኒ ጠባቂ ስንመለከት እንደዚኽ ዓይነት ሰው ነበር /ሐዋ.16፡25-40/፡፡ ስለዚኽ በአዲሱ ዓመት ኹሉንም ነገር ለእግዚአብሔር ክብር እናድርገው ብንል ይቻለናል ማለት ነው፡፡
እስኪ ንገሩኝ! ከነፍሰ ግድያ በላይ ምን የከፋ ነገር አለ? ነገር ግን በዚኽ የነፍስ ግድያ እንኳን የጽድቅን ሥራ መሥራት ይቻላል፡፡ አትደንግጡ! ግድያ እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ተብሎ ሊደረግ ይችላል፡፡ ከእናንተ መካከል “ነፍሰ ገዳይ ሰው እንዴት አድርጐ ነው በነፍሰ ገዳይነቱ ጽድቅ ሠራ ተብሎ ሊነገርለት የሚችለው?” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ የተመዘገበውን አንድ ታሪክ አንሥቼ ልነግራችኁ እወዳለኹ፡፡ አንድ ጊዜ ምድያማውያን ከእስራኤል ጋር ጦርነት ይገጥሙ ዘንድ እግዚአብሔርን ለቁጣ ቀስቅሰዉት ነበር፡፡ በጦርነቱም ልዕልናቸውን በማሳየት፥ የእግዚአብሔርን መልካም ፈቃድ ለማስቀረት አስበው ሴቶቻቸውን በማሳመር በድንኳኑ ፊት ቆመው ነበር፡፡ በዚኽም እስራኤላውያንን በዝሙት እስከ መሳብና ለጣዖት እንዲሰግዱ እስከ ማታለል ደርሰው ነበር፡፡ ይኽም ብቻ ሳይኾን እስራኤላውያን ሃይማኖት የለሽ እንዲኾኑ ፈልገው ነበር፡፡ ፊንሐስ ግን ይኽን ባየ ጊዜ በእጁ ሰይፍ ይዞ ኹለት ሲያመነዝሩ የተገኙትን ሰዎች ሆዳቸውን በሰይፍ ወግቶ ገድሏቸዋል፡፡ በዚኽም የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደኾነ አረጋግጧል፡፡ ፊንሐስ ያደረገው ነገር ሰውን መግደል ነው፡፡ የዚኹ ግድያ ዓላማ ግን እስራኤልን በጠቅላላ ማዳን ነበር፡፡ በመኾኑም ከግድያ እንኳን ጽድቅን ማፍራት ይቻላል ማለት ነው /ዘኅ.25/፡፡
ፊንሐስ በፈጸመው ግድያ እጁ አልረከሰም፡፡ ይልቁንም ያ “ነፍሰ ገዳዩ” ፊንሐስ እስራኤላውያንን ከዝሙት ጠንቅ ጠብቆ ንጹሐን አደረጋቸው እንጂ፡፡ ፊንሐስ እነዚያ ኹለቱንም የገደላቸው ጠልቷቸው አልነበረም፤ የተቀሩትን የእስራኤል ሰዎች ለማዳን እንጂ፡፡ ኹለቱንም ብቻ በመግደል እልፍ እስራኤልን በነፍስ በሥጋ ከመሞት ለመታደግ እንጂ፡፡ ይኸውም ሐኪሞች እንደሚያደርጉት ነው፡፡ ሐኪሞች አንድ በቁስል መበስበስ (በጋንግሪን) የተጠቃን የሰውነት ክፍል ቈርጠው ቢያስወግዱት የተቀረውን ሰውነት ለማዳን ነው፡፡ ፊንሐስም ያደረገው እንደዚኹ ነው፡፡ መዝሙረኛው ክቡር ዳዊት ይኽንን በተመለከተ ሲናገር፡- “ፊንሐስም ተነሥቶ ፈረደባቸው፤ ቸነፈሩም ተወ፡፡ ያም እስከ ዘለዓለም ለልጅ ልጅ ጽድቅ ኾኖ ተቈጠረለት” ብሏል /መዝ.106፡30-31/፡፡ ፊንሐስ ያደረገው ነገር ትክክል ነው ተብሎ እስከ ዘለዓለም ሲነገርለት ይኖራል፡፡ (በነገራችን ላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አልመለስ ያሉትን መናፍቃን ከቤተ ክርስቲያን አውግዛ የምትለያቸው ቀሪውን ምእመን እንዳይበክሉ እንጂ ጠልታቸው አይደለም፡፡ በቅርብ ጊዜ የተወገዙት የተሐድሶ አራማጆች የተወገዙትም ከዚኹ አንጻር ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ ውግዘቱ ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው፡፡)
ይቀጥላል.....
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፮
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ማመስገንና መገሠፅ፣ ወይም ከቤት ውስጥ መኾንና አለመኾን ወይም መናገርና አርምሞ ብቻ አይደለም፤ ኀዘናችንም ደስታችንም ስለ እግዚአብሔር ክብር ሊኾን ይገባል፡፡ አንድ ወንድማችን ኀጢአት እየሠራ ብናየው ወይም እኛው ራሳችን በበደል ስንወድቅ ብናለቅስና ብናዝን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የኾነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፣ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና” /2ኛ ቆሮ.7፥10/ ኀዘናችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ አንድ ወንድማችን መልካም ነገርን ስላገኘ ልክ ለእኛ እንደተደረገ አድርገን እግዚአብሔርን ብናመሰግንም ደስታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ ከዚኽ ደስታም እጅግ ብዙ ጥቅምን እናገኝበታለን፤ እንኪያስ ይኽን በአዲሱ ዓመት እንለማመደዋ!!!
በወንድሙ ደስታ መደሰት ሲገባው ወንድሙ ስለ ተጠቀመ ብቻ በቅናት ከሚቃጠል ሰው በላይ አሳዛኝ ሰው ማን አለ? እስኪ ንገሩኝ! በወንድሙ ደስታ በማዘኑ የእግዚአብሔርን ፍርድ በራሱ ላይ በመጨመር በነፍስ በሥጋ ከሚጐዳ ቅናተኛ ሰው በላይ የሚያሳዝን ፍጥረት ማን አለ? ወንድማችን ስለ ተጠቀመ ብናመሰግን ወይም ብንደሰት፣ ወንድማችን ስለ ተጐዳም ብናዝን እና ብናለቅስ ይኽንንም ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ብናደርገው አንጠቀምምን?
ፀጉርን ከማሳጠር በላይ ምን ትንሽ ነገር አለ? ነገር ግን ይኽም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ሴቶች በፀጉራቸው ምክንያት ወንዶች የሚሰነካከሉ ከኾነና ይኽንን ዐውቀው ባይቈርጡትም ወንዶቹ በማይሰናከሉበት መንገድ ቢሸላለሙት፣ ደካማ ወንድሞቻቸው በማይሰናከሉበት መንገድ ራሳቸውን ቢያጌጡ ይኽን ለእግዚአብሔር ክብር አድርገዉታልና ሹመት ሽልማታቸው የበዛ ነው፡፡ የክፉ ምኞት ፍላጻን ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል አስቀርተዉታልና ዋጋቸው በሰማያት ዘንድ ታላቅ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ አንዲት ኩባያ ውኃን የሰጠ ሰው ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያገኝ ከኾነ፥ የምናደረግው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን የምናከናውነው ከኾነማ ሹመት ሽልማታችን እንደምን አይበዛ?
ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ መሔድም አለመሔድም አለ፡፡ ምን ማለት ነው? ወደ ክፋት የማንሔድ ከኾነ፣ የቆነጃጅትን ውበት በማድነቅ ስም ልቡናችን በምኞት መንፈስ የማንጠመድ ከኾነ፣ አንዲት ቆንጆ ልጅ በፊታችን ብናይና እንደምታሰናክለን ተረድተን ዓይናችንን ከርሷ ዞር የምናደርግ ከኾነ ውበትን ለእግዚአብሔር ክብር አዋልነው ይባላል፡፡
አለባበሳችንም ቢኾን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ባንለብስ፣ ሰውነታችንን እጂግ ሳናራቁት፣ በአጭሩ ሰውን የማያሰናክል አለባበስን ብንከተል አለባበሳችን ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል (በነገራችን ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአጸደ ሥጋ በዚኽ ዘመን ቢኖርና ከቅርብ ጊዜ ወዲኽ የምናየውን የእኅቶቻችንን አለባበስ ቢያይ ምን ብሎ ሊገሥፅ እንደሚችል አስቡት፡፡ ምክንያቱም እኅቶቻችን በስመ ዘመናዊነት የሚለብሱት እጅግ በጣም አጭር ቀሚስ ወይም ሱሪ የብዙ ደካማ ወንዶችን ልብ በዝሙት ይፈታተናልና)፡፡
የምጫማው ጫማ እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለሚያደርጉት ጫማ ከዓቅም በላይ ሲጨናነቁ አያለኹ፡፡ ፊታቸውን በተለያየ መንገድ ለማሸብረቅ የሚወዱትን ያኽል ስለ ጫማቸው ውበት እጂግ የሚጨነቁ ሰዎችን አያለኹ፡፡ ምንም እንኳን ይኽ እንደ ትንሽ ነገር አድርገን ብናስበውም ዘወትር በወንዶችም በሴቶችም የምናየው ነገር ነው፡፡ ስለዚኽ ጫማችን እንኳን ሳይቀር ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል ማለት ነው፡፡ በአካሔዳችንም፣ በአለባበሳችንም፣ እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት እንደሚቻል ሲናገር ጠቢቡ ምን እንደሚለን እስኪ እናድምጠው፡- “ከአለባበሱና ከአካሔዱ ከአሳሳቁም የተነሣ የሰው ጠባዩ ይታወቃል” /ሲራክ 19፡27/፡፡ ስለዚኽ በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር የምናደርገው ከኾነ አሕዛቡም፣ መናፍቁም፣ ፈላስፋውም አስቦበት ሳይኾን እንዲኹ በእኛ ይደነቃል፡፡
ይቀጥላል....
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፭
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን መውቀስም አለ፡፡ ከእናንተ መካከል፡- “እንዴት ብሎ? ርግጥ ነው ብዙውን ጊዜ ሠራተኞቻችንን እንወቅሳለን፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ መውቀስስ እንደምን ያለ ነው?” አዎ! የሚሰክር ወይም የሚሰርቅ ሠራተኛ ወይም ጓደኛ ብናይ ወይም ከዘመዳችን አንዱ ወደ ተውኔት ቤት፣ ወይም ለነፍሱ ምንም ረብሕ ወደማያገኝበት ሥፍራ ሲሮጥ፣ በከንቱ ሲምል፣ የሐሰት ምስክርነትን ሲሰጥ፣ ወይም ሲዋሽ፣ ወይም ሲቈጣ ብናየው ዠርባችንን ብንሰጠውና ብንገሥፀው ወቀሳችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡
ዳግመኛም አንድ ሰው ቢበድለን፣ ርሱ ራሱ የሠራውንም ጥፋት በእኛ ቢያመካኝ ስለ እግዚአብሔር ብለን ይቅር ልንለው ይገባል፡፡ ብዙዎቻችን ግን ለጓደኞቻችን፣ ለሠራተኞቻችን የዚኽ ተቃራኒውን ነው የምናደርገው፡፡ ጓደኞቻችን ወይም ሠራተኞቻችን ቢበድሉን እናንባርቃለን፤ ይቅርታ የሌለው ፍርድም እንፈርድባቸዋለን፡፡ እኛው ራሳችን እግዚአብሔርን በገቢር ስንሰድብ አንድም ስናሰድብ ወይም ነፍሳችንን ስንጐዳ ግን እንደበደልን አይሰማንም፡፡ ይኽ ግን በአዲሱ ዓመት ልናስተካክለው የሚገባ ነገር ነው፡፡ ዕለት ዕለትም ልንለማመደው ይገባል፡፡ የበደሉንን ሰዎችስ ወዳጅ ማድረግ ይገባልን? አዎ! ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል የበደሉንን ሰዎች ወዳጅ ማድረግ ይገባናል፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ሰውን ጠላት ማድረግስ? አዎ! ይቻላል፡፡ ለመኾኑ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ወዳጅና ጠላት ማድረግ ሲባል ምን ማለት ነው?ሰውን ወዳጅ ማድረግ ሲባል ያንን ሰው ከገንዘባችን፣ ከማዕዳችን እንዲካፈል በእኛም እንዲደገፍ ማድረግ ማለት አይደለም፡፡ አንድን ሰው እውነተኛ ወዳጅ ኾንነው አንድም አደረግነው የሚባለው ነፍሱን እንዳይጐዳ ብንገሥፀውና ብንመክረው፣ ቢበድል (በበደሉ የሚጐዳው ርሱ ራሱ ነውና) እንደ ጠላት ሳይኾን እንደ ወዳጅ ቀረብ ብለን የሚረባውን ብንነግረው፣ ከወደቀበት የኀጢአት አረንቋ እንዲነሣ ብናደርግ ለዚኽም ዘወትር በጸሎት ብንረዳውና ወደ እግዚአብሔር እንዲቀርብ ብናደርግ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ጠላት ማድረግም ይፈቀዳል፡፡ ይኽን ከዚኽ በፊት ያላከናወንነው ከኾነም ከአኹኑ አዲሱ ዓመት መዠመር እንችላለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ሰውን ጠላት ማድረግ፡፡ ለምሳሌ አንድ ጋጠ ወጥ፣ ክፋትን የተመላ፣ ንግግሩ (ትምህርቱ) ኹሉ በምንፍቅና መርዝ የተለወሰ፣ ዘወትር ነፍሳችንን የሚያውካትና የሚጐዳት ሰው ካለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ቀኝ ዓይንኅም ብታሰናክልኽ አውጥተኽ ከአንተ ጣላት” እንዳለ /ማቴ.5፡29/ እነዚኽን ሰዎች መራቅ ጠላትም ማድረግ ይፈቀዳል፡፡ እነዚኽ ሰዎች ቀኝ ዓይን ተብለው መጠቀሳቸውም ምንም እንኳን እንደ ዓይናችን የምናያቸው ወዳጆቻችን ቢኾኑም ነፍሳችንን የሚጐዷት ከኾነ ከእኛ ዘንድ ልናርቃቸው ይገባል፡፡
ንግግራችንም ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ብሎ መናገር ሲባል ምን ማለት ነው? ለምሳሌ ከአንድ ጓደኛችን ጋር ቁጭ ብለን ስንጨዋወት “ማን ሥልጣን ላይ ወጣ፣ ማን ወረደ፣ ማን አለፈ፣ ማን ምን ክብር አገኘ” እያልን ከምንጨዋወት ይልቅ ስለ ነገረ ሃይማኖት፣ ስለ ገሃነመ እሳት፣ ስለ መንግሥተ ሰማያት ብንጨዋወት መናገሩ ጥቅምን ይሰጣል፡፡ ነፍሳችንን በማይጠቅማት ነገር አላስጨነቅናትምና፡፡ ይኽን ዓይነት ኅብረት ባንተወዉም አንጐዳንም፡፡ በኋለኛው ቀን ላይ ይኽ ኹሉ ማድረጋችን አንዳች ጥቅም ይሰጠናልና፡፡ ስለዚኽ ለነፍሳችን አንዳች የሚጠቅም ነገር በሌለው ስብስብ መካከል መቀመጡና ማውራቱ ለእኛ ጉዳት እንጂ ረብሕ የለውም፡፡ የዚኽ ስብስብ መንፈስ ለውጦ ስለ ነገረ እግዚአብሔር ማውራቱም ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን ይገቧል፡፡ ምንም ሳንበድለው ክፉ ለሚያደርግብን ሰው፣ ሳንወቅሰውና ሳናንጐራጉርበት በትዕግሥት ዝም ብንል ዝምታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡
ይቀጥላል.....
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፬
#አዲሱ_ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ከላይ እንደነገርኳችኁ “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ለሚላችኁ ሰው እንዲኽ በሉት፡- “ወዳጄ! ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ነው የምትለኝ ስለምንድነው? እጂግ ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ (በዚኹ በ21ኛው መ/ክ/ዘ. የግል አውሮፕላን ወይም ሃመር መኪና ልንለው እንችላለን!) ስላለው ወይም ብዙ ሠራተኞችን (ብዙ ኩባንያዎችን ልንለው እንችላለን!) ስለሚያስተዳድር፣ እጂግ ውድ ውድ የኾኑ ፋሽን ልብሶችን ስለሚለብስ፣ በየዕለቱም የተለያዩ የመጠጥ ዓይነቶችን ስለሚጠጣና ቅንጡ የኾነ ሕይወትን ስለሚመራ ነውን? እውነት እውነት እልኻለኁ! ለዚኽ ሰውዬስ የዕድሜ ዘመን ዕንባ ያስፈልገዋል ብዬ እነግርኻለኁ፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው አፍአዊ ነገሩን ብቻ በማየት ነው፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው ግሩምና ድንቅ የኾነችውን ሠረገላው፣ ወይም ወርቃማው መጋለቢያውን፣ ወይም ልብሱን ዐይተኽ ነው፡፡ ይኽ ግን ለእኔ ምንም ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ከዚኽ ሰው በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? ሠለገላው፣ መጋለቢያው፣ ልብሱ፣ እና ሌላው ሃብቱ እየተደነቀለት ሳለ ርሱ ግን ምንም ሳይመሰገን ቢሞት ከርሱ የባሰ ጐስቋላ ሰው ማን አለ ትለኛለኽ? ከዚኽ ዓለም ወደዚያኛው ዓለም ይዞት የሚሔድ ብዕል (ሃብት) ከሌለው ከዚኽ ሰው በላይ ድኻ ማን አለ? ከአፍአ ሲታይ እጂግ የሚያምርበት ከውስጡ ግን የተለሰነ መቃብር ከኾነው ከዚኽ ሰውዬ በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? የእኛ የክርስቲያኖች ትክክለኛ ሃብት ጌጣ ጌጥ፣ ወይም ሠራተኞቻችን ወይም ልብሳችን ወይም ሠረገላዎቻችን አይደሉም፡፡ የእኛ ትክክለኛ ሃብት ምግባር ትሩፋታችን ነው፡፡ የእኛ ሃብት በእግዚአብሔር ማመናችንና መታመናችን ነው፡፡”
ዳግመኛም እጅግ ድኻ፣ በጓደኞቹ ዘንድ ዕድሜውን በሙሉ እንደ ፋራና ያልዘመነ ሰው የሚቈጠር፥ ግን ደግሞ በምግባር በትሩፋት ያጌጠ ሰውን ብታዩ ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ሰው ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ምንም በዚኽ ምድር ላይ ያፈራውና ያጠራቀመው ሃብት ባይኖሮውም በሰማያት ዘንድ ድልብ ሃብት አለውና ይኽ ሰው በእውነት ንዑድ ክቡር ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡
ይኽን አመለካከት ስለያዛችኁ ብቻ ጓደኞቻችኁ፡- “ኧረ በሥሉስ ቅዱስ! ይኽ ሰውማ እጅግ የተረገመ ሰው ነው!” ቢልዋችኁ፥ “እንደዉም እንደዚኽ ሰው ንዑድ ክቡር የለም፡፡ ወዳጅነቱ ከኃላፊውና ጠፊው ሃብትና ንብረት ሳይኾን ከእግዚአብሔር ጋር ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ ዕድሜውን በሙሉ ሲያከማች የነበረው እንደ እኛ አፍአዊውን ሳይኾን ብልና ዝገት የማያገኘውን ብዕል ነበርና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ የዚኹ ሰው ሀብቱ በትዕቢት፣ በቁጣ፣ በዘፈን፣ በስካርና በገቢረ ኀጢአት ያልቆሸሸ ንጽሐ ልቡናው ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ይኽ ሰው ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ፣ በወርቅ የተሽቆጠቆጠ መጋለቢያ፣ ውድ ውድ የኾኑ አልባሳት ስለሌለው የተጐዳ ይመስልኻልን? ርስት መንግሥተ ሰማያትን ከማግኘት በላይ ሌላ ምን ሃብት አለ ብለኽ ልትነግረኝ ትችላለኽ?” ብላችኁ መልሱላቸው፡፡
እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የምትወዱት ሆይ! በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ዘወትር እንዲኽ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ የምንገሥፅ፣ ወይም የምናመሰግን ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ ነው፡፡
ልጆቼ! ይኽን ኹሉ የምነግራችኁ እንዲኹ ስሜታችኁን ለማርካት አይደለም፡፡ ይልቁንም በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ አስተሳሰባችንን እንዲኽ የምናስተካልለው ከኾነና እኛም እንደዚኹ በምግባር በትሩፋት ለማጌጥ የምንሽቀዳደም ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ የብዙም ብዙ መኾኑን ለማስረዳት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት ስለዚኹ ጕዳይ ምን እንደሚል እስኪ አብረን እናድምጠው፡- “በአንደበቱ የማይሸነግል፣ በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ፣ ሰርቆ ቀምቶ እናት አባቱን የማያሰድብ፣ እኩይ ምግባር በፊቱ የተናቀለት፣ እግዚአብሔርንም የሚፈሩትን የሚያከብር፣ ለባልንጀራው ምሎ የማይከዳ፣ ገንዘቡን በአራጣ የማያበድር፣ ከድኻው መማለጃን የማይቀበል፣ እንዲኽ የሚያደርግ ሰው በመከራ ሥጋ መከራ ነፍስ ለዘለዓለም አይታወክም” /መዝ.15፡3-5/፡፡ ይኽም ማለት ክፋትን በመጸየፍ በጐውንም በማመስገን እግዚአብሔርን የሚያከብር ሰው ነፍሱ ለዘለዓለም አትታወክም ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም ይኼ ክቡር ዳዊት በሌላ ሥፍራ እንዲኽ አለ፡- “አቤቱ ባለሟሎችኅ በእኔ ዘንድ እንደምን እጅግ ንዑዳን ክቡራን ናቸው! አስቀድመው ከነበሩት ባለሟሎችኅ ይልቅም እኒኽ ፈጽመው ጸኑ!” /መዝ.139፡17/፡፡
እግዚአብሔር ያከበረውን ግን አትገሥፁ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በጽድቅ በቅድስና ሕያዋን የኾኑትን ያከብራልና፡፡ በሰው ዓይን እዚኽ ግቡ የማይባሉ ድኾች ቢኾኑም በእግዚአብሔር ዘንድ ንዑዳን ክቡራን ናቸውን እነዚኽን አትገሥፁ፡፡ እግዚአብሔር ያላከበረውን ግን ገሥፁት፡፡ ምንም ያኽል በወርቅ ላይ ቆሞ በወርቅ ላይ ቢተኛም ምግባር ትሩፋትን ሳይይዝ በገቢረ ኀጢአት የፀናውን፣ በሚቀጥለው ዓመትም ይኽን ለማድረግ የሚያቅደውን ሰው ገሥፁት፡፡ በአጭር ቃል ስታመሰግኑም ስትገሥፁም ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት፡፡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት እንደዚኽ በኹለንተናችን አዲስ ሰው ኾኖ በመዘጋጀት ነውና፡፡ .....ይቀጥላል...
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፫
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመት ሲመጣ መደሰት፣ ብዙ መብልና መጠጥ ማዘጋጀት፣ አዲስ ልብስም መልበስ ጥቅም የለውም፡፡ ነፍሳችን በኀጢአት እየተጨነቀች፣ ነፍሳችን ተርባና ተጠምታ ሳለ፣ የተዳደፈ የኀጢአት ልብስም ተጆቡና ሳለ አዲስ ዓመት ማክበር ለእኛ ምን ጥቅም ይሰጠናል? እንዲህ ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት ለእኔ እንደ ልጆች የዕቃ ዕቃ ጨዋታ ነው፡፡
ክርስቶስ ከዚሁ ሥራ አውጥቶናል፡፡ ከሕፃንነት አዕምሮ ወደ ማወቅ አሸጋግሮናል፡፡ ከምድራውያን ለይቶ ከሰማያውያን ጋር ደባልቆናል፡፡ ስለዚህ “መልካሙን ሥራችሁን ዐይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ” እንደ ተባለ አፍአዊ ሳይኾን መንፈሳዊውን ብርሃን ልናበራ ይገባናል (ማቴ.5፡16)፤ በአዲሱ ዓመት፡፡ ይህም ብርሃን ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን የሚያስገኝ ነው፡፡
ወዳጄ ሆይ! ቤቱ ቆሽሾ ሳለ ውጫዊ በሩን ብቻ ለማሽቀርቀር ለምን ትጨነቃለህ? ነፍስህ በኀጢአት ተዳድፋ ሳለ ሥጋህን ብቻ ለማስደሰት ለምን ትሮጣለህ? አስቀድመህ ቤቱን (ነፍስህን) ለማስዋብ አትሽቀዳደምምን? አስቀድመህ ለነፍስህ የምታስብ ከኾነ ከሰው እጅ ሳይኾን ከክርስቶስ እጅ ሹመት ሽልማት ትቀበላለህ፡፡ ኹል ጊዜ “የማደርገው ነገር እግዚአብሔር ይከብርበታልን?” ብለህ አስብ እንጂ እንዲሁ በዘልማድ የምትመላለስ አትኹን ብዬ እመክርኻለሁ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመክረን፡- “እንግዲህ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትኾኑ ወይም ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ኹሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ያለንም ስለዚሁ ነውና በአዲሱ ዓመት በድርጊቶቻችን ኹሉ እግዚአብሔርን ለማክበር እንዘጋጅ (1ኛ ቆሮ.10፡31)፤ አዲስ ዓመት ማክበር ማለት ይኼ ነውና፡፡
ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል መብላት ወይም መጠጣት ማለት ምንድነው? ድኻውን ወደ ቤታችን ስንጠራው፤ በማዕዳችን ክርስቶስ አብሮ ሲኖር ለእግዚአብሔር ክብር በላን ወይም ጠጣን ይባላል፡፡
ሐዋርያው የመከረን ግን በመብላችን ወይም በመጠጣችን ብቻ አይደለም፤ ጨምሮም፦ "ማናቸውንም ነገር ብታደርጉ ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት " አለን እንጂ፡፡ ስለዚህ ወደ ሸንጎም ብንሔድ ፤ ወደ ቤተክርስቲያንም ብንሔድ ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡
እነዚህን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ የምንችለውስ እንዴት አድርገን ነው ?
ወደ ቤተክርስቲያን ፣ ወደ ሥርዓተ ቅዳሴው ፣ ወደ ጉባኤው ፣ ወደ ሌላው መንፈሳዊ አገልግሎት ስንሔድ አካሔዳችን እግዚአብሔር የሚከብርበት መኾን አለበት፡፡ እግዚአብሔር የማይከብርባቸው ብዙ ምልልሶች አሉና በአዲሱ ዓመት ወደ ቤተክርስቲያን መመላለሳችን ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡
እቤት ስንቀመጥ መቀመጣችን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ " ምን ማለት ነው ? " ትለኝ ይኾናል፡፡ ከቤት ወጥተን ክፋት ወደ መላበት ሥፍራ ፣ ክርክርና ክስ ወደሰፈነበት ሸንጎ ፣ ዘፈን ስካርና ሌላውም ገቢረ ኃጢአት ወደሚደገስበት ፣ ነፍስንም ወደሚያውክ ስፍራ ከመሄድ ተቆጥበን ከቤት ቁጭ ብንል ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል ብዬ እነግርሃለሁ፡፡
ስለዚህ ከቤት ውስጥ ቁጭ ማለትም ወደ ቤተ እግዚአብሔር መሄድም በዚህ መንገድ ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል ማለት ነው፡፡"
በአዲሱ ዓመት ብናመሰግንም ብንገሥፅም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡ “ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ማመስገንና መገሠፅ ሲባልስ ምን ማለት ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እንበልና በመሥሪያ ቤታችን ቁጭ ብለናል፡፡ እጂግ ክፋትን የተመሉ ሰዎችም በፊታችን ይመላለሳሉ፡፡ እነዚኽ ሰዎች በውስጣቸው በትዕቢት፣ በቁጣ፣ እንዲኹም ይኽን በመሳሰሉ ጥገኛ ተሐዋስያን የተመሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ለብሰዋል፡፡ አከባቢውን የሚለውጡ ውድ የኾኑ ሽቶዎችን ተቀብተዋል፡፡ ይኽን እያየን ሳለ አንድ ሰው መጥቶ፡- “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ሊለን ይችላል፡፡ እንዲኽ የሚላችኁን ሰው ገሥፁት፤ ምክሩት፤ ወይም ዝም በሉት፡፡ ቢቻላችኁ እዘኑለት (አልቁስለት)፡፡ ተግሣፅን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ማለትም ይኼ ነው፡፡
ተግሣፅ ሲባል ሰዎች ከነበሩበት የተሳሳተ አመለካከት ወጥተው ወደ ቀና አስተሳሰብ እንዲመጡ ማድረግ ነው፡፡ ከእንግዲኽ ወዲኽ ክፋትን ሳይኾን ምግባር ትሩፋትን እንዲያደንቁና እነርሱም ራሳቸው ለዚያ የተዘጋጁ እንዲኾኑ ማድረግ ነው፤ ተግሣፅ፡፡
ይቀጥላል.....
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፪
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
እግዚአብሔር የሚወዳችሁ እናንተም የምትወዱት ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የእውነት አዲስ ዓመት እንዲኾንላችሁ ካሻችሁ ነፍሳችሁን ከኀጢአት ቀንበር አላቋት እንጂ ድጋሜ በኀጢአት ሸክም አትጫኗት፡፡ አሮጌው ዓመት እንዳለቀ ስታዩ እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ወደሌላ ዘመን አሸጋግሯችኋልና እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ልቡናችሁንም ውቀሱት፡፡ በዕሜአችሁ ስንት ጊዜ እያለፈ እንደ ኾነ እያሰባችሁም ራሳችሁን እንዲህ ብላችሁ ጠይቁት፡- “ቀናት እየሮጡ ነው፡፡ ዓመታቱም እየነጐዱ ነው፡፡ የዕድሜዬ መንገድም እየተጋመሰ ነው፡፡ ታዲያ ምን በጐ ምግባር ያዝኩ? ከዚህ ምድር የማልፍበት ቀን እየቀረበ ነው፡፡ ታዲያ ምን የጽድቅ ሥራ ሠራሁ? በዚህ ዕድሜዬ መሥራት የነበረብኝ ምግባር ትሩፋት ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ አልችልም፡፡ ታዲያ ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ የማልችላቸውም የጽድቅ ሥራዎች (ፆም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ አገልግሎት፣… ዕድሜ ሲገፋ ይከብዳሉና) እንዳቅሜ እያደረግኩ ነውን?”
ተወዳጆች ሆይ! አዲስ ዓመት ሲመጣ እነዚህን ነገሮች በጥንቃቄ ልናስብባቸው ይገባናል፡፡ ይህን እያደረግንም ስለ ቀጣዩ ዓመት እናስብ፡፡ ይህን የምናደርግ ከኾነ “ቀኖቻቸውም በከንቱ አለቁ፤ ዓመቶቻቸውም በችኰላ” አይባልብንም (መዝ.78፡3)፡፡ ዕለት ዕለት በዓልን እናድርግ ብዬ የገለጥኩላችሁም ይኸው ነው፡፡ የእኛ በዓል ዘወትር መኾን ይገባዋል፡፡ የክርስቲያኖች በዓል በዓመታትና በቀናት ብቻ መወሰን የለበትም፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በሳምንት፣ በወር፣ በዓመት የሚከበሩ በዓላት እንዲኖሩ ማድረጓ ዘወትር ከዚሁ ልንርቅ እንደማይገባ ማሳሰቧ እንጂ ሌላ አይደለምና፡፡ ይህን በዓል በየዕለቱ ማድረግም ለኹሉም ይቻላል፤ ለድኻውም ለባለጸጋውም ይቻላል፡፡ በዓልን ለማድረግ (የጽድቅ ሥራን ሠርቶ ሐሴት ለማድረግ) የሚያስፈልገው ቅን ልቡና እንጂ ገንዘብ አይደለምና፡፡
ወዳጄ ሆይ! ገንዘብ የለህምን? ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ አድርግ፡፡ ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ የምታደርግ ከኾነ ገንዘብ ካላቸው በላይ ባለጠጋ ነህ፡፡ “እንዴት?” ትለኝ ይኾናል፡፡ እኔም እንዲህ ብዬ እመልስልሃለሁ፡- የእነዚያ (የባለጠጐቹ) ገንዘብ ያልቃል፡፡ ያንተ ግን ብል አይበላውም፡፡ ጊዜ አይለውጠዉም፡፡ አያልቅም፡፡ ወደ ሰማያት፣ ወደ ሰማየ ሰማያት፣ ወደ ምድር፣ ወደ አየራት፣ ወደ እንስሳቱ ዓይነት፣ ብዙ የብዙ ብዙ ወደሚኾኑት ዕፅዋት፣ ወደ ደቂቀ አዳም በጠቅላላው፣ ወደ መላዕክት፣ ወደ መላዕክት አለቆች፣ ወደ ኀይላት ተመልከት፡፡ እነዚህ ኹሉ የአምላክህ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ የእነዚህን አምላክና መጋቢ ባሪያ መኾን ድኻ መኾን አይደለምና ድኻ አይደለህም ብዬ እነግርሃለሁ፡፡
ተወዳጆች ሆይ! ቀናትን ቆጥሮ በዓል ማድረግ የክርስቲያን ግብር አይደለም፤ የአሕዛብ ግብር እንጂ፡፡ እንዴት? የክርስቲያኖች ተፈጥሮ በቀንና በወር የተገደበ አይደለምና፡፡ አገራችን ሰማይ ነው፡፡ ግብራችን ሰማያዊ ነው፡፡ ኅብረታችንም ከሰማያውያን መላዕክት ጋር ነው፡፡ በዚያ መዓልት ለሌሊት ስፍራውን አይለቅም፡፡ ሌሊትም በተራው ለመዓልት አይለቅም፡፡ እዚያ ኹሌ መዓልት ነው፡፡ እዚያ ኹል ጊዜ ብርሃን ነው፡፡ ስለዚህ “ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ” እንደተባልን ኹል ጊዜ ማሰብ ያለብን ይህንን ነው (ቈላስ.3፡1)፡፡ ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችን ከዚህ ምድራዊ አቈጣጠር በላይ ነው፡፡ በንጽህና በቅድስና እየኖርን ዘወትር በዓልን የምናከብር ከኾነም የዚሁ ዓለም ሌሊት ለእኛ ሌሊት አይደለም፤ መዓልት ነው እንጂ፡፡ ዘመናችንን በሙሉ በገቢረ ኀጢአት፣ በስካር፣ በዘፈን የምናሳልፈው ከኾነ ግን መዓልቱ ለእኛ መዓልት አይደለም፤ ሌሊት ነው እንጂ፡፡ ፀሐይዋ ብትወጣም ልቡናችን ገና በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ይኖራልና ቀን እንደወጣ አይቈጠርም፡፡
ይቀጥላል....
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
፩
አዲሱ ዓመት
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው)
ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የደስታ የሰላምና የጤና እንዲኾንላችሁ ትሻላችሁን? እንኪያስ ገና ከጅመሩ በስካር፣ በዘፈን፣ በገቢረ ኀጢአት ለማሳለፍ አታቅዱ፡፡ የአዲሱ ዓመት የመጀመሪያውን ዕለት ብቻ ሳይኾን እያንዳንዱን ቀን በገቢረ ኀጢአት አትጀምሩት፡፡ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሥራ፣ ምግባር ትሩፋት በመሥራት አሐዱ በሉ እንጂ፡፡ ዕለታት ክፉዎች ወይም ጥሩዎች የሚኾኑት በተፈጥሮአቸው እንደዚያ ኾነው አይደለም፡፡ ዕለቱን ክፉ ወይም ደግ እንዲኾን የምናደርገው እኛው ነን፡፡ የአምናው ማክሰኞ ከዘንድሮ ማክሰኞ የተለየ አይደለም፡፡ የተለየ የሚያደርገው የእኛ ብርታት ወይም ስንፍና ብቻ ነው፡፡
የጽድቅን ሥራ የምንሠራበት ከኾነ አዲሱ ቀን ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመት ለእኛ መልካም ነው፡፡ ኀጢአት የምንሠራበት ከኾነ ግን ቀኑ ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመትም ክፉና መከራ የመላበት ይኾንብናል፡፡ አዲሱን ዓመት በበጐ ሥራ የምንጀምረው ከኾነ በዓመቱ በምናደርገው ማንኛውም ክንውን ላይ በጐ ተጽዕኖ ያሳድርብናል፡፡ በትግሃ ሌሊት፣ በቀዊም፣ በጾም በጸሎት እንድንበረታ ስንቅ ይኾነናል፡፡ በስካር፣ በዘፈን፣ በኀዘን የምንጀምረው ከኾነ ግን ዓመቱ ሙሉ እንዲህ የተጐሳቈለ ዓመትን እናሳልፋለን፡፡ ሕይወታችንን በከንቱ እንገፋለን፡፡ ዲያብሎስም ይህን ጥንቅቅ አድረጐ ስለሚያውቅ ዓመቱን በገቢረ ኀጢአት እንድንጀምረው እየቀሰቀሰ ነው፡፡ ፈቃዳችንን አጥፍቶ፣ ዓይነ ልቡናችንን አሳውሮ በዘፈን፣ በስካር፣ በዋይታ እንድንጀምረው በተለያየ መንገድ እየለፈፈ ነው፡፡
ሰነፍ ሰው “ቀኑ ክፉ ወይም መልካም የሚኾነው በእኔ ምክንያት አይደለም” ብሎ ያምናል፡፡ እንዲህ በማመኑም ክፉ ነው ብሎ በሚያስበው ቀን ገቢረ ጽድቅ መሥራት እንደሚቻል አያስብም። ቢያደርግም ትርጕም እንደሌለው አድርጐ ይቈጥሯል፡፡ የጽድቅ ሥራ ለመሥራት በተመቻቸለት ቀንም ልል ዘሊል ከመኾኑ የተነሣ ምግባር ትሩፋት ለመሥራት አይሽቀዳደምም፡፡ ስንፍናው ምን ዓይነት ጉዳት እንደሚያመጣበት አይረዳም፡፡ ድኅነቱን ሳይፈጽም ዕድሜውን ኹሉ በከንቱ ይገፋል፡፡ እንዲህ ያለ የሥጋም የነፍስም ጕዳት እንደሚያገኘው ዲያብሎስ ዓይነ ልቡናውን ስለሚያሳውርበት ከአጋንንት ወጥመድ ለመሸሽ ዓቅምን ያጣል፡፡
ዲያብሎስም ዕለት ዕለት ይህን እንዳንገነዘብ በተለያየ ማጥመጃ መንገዶች እኛን ለመጣል ይሯሯጣል፡፡ አንዱ መንገድም ስለ ክርስትና ሕይወታችን ግድ እንዳይኖረን ማድረግ ነው፡፡ በዚህም ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችንን ያሳጣናል፡፡ የእግዚአብሔርን ሥራ በገቢር እንድንሰድብ ያደርገናል፡፡ ነፍሳችንን በቆሸሸ ስፍራ ተወሽቃ እንድትቀር ያደርጋታል፡፡
የምወዳችሁ ልጆቼ! እኛ ግን ይህን ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዓለም ላይ ከኀጢአት በቀር ክፉ ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ ከምግባር ከትሩፋት በቀርም መልካም ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዚህም ዘወትር እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን ልንኖር እንዲገባን ማወቅ መረዳት ይገባናል፡፡
መጠጥ ደስታን አያመጣም፤ ደስታን የሚያመጣው ጸሎት ነው፡፡ ደስታን የምናገነኘው ቃለ እግዚአብሔርን ከመስማት እንጂ ከስካር አይደለም፡፡ ስካር የነፍስ መታወክን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ተመስጦን ያመጣል፡፡ ስካር ሁካታን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ሁካታን ያርቃል፡፡ ስካር ዓይነ ልቡና እንዲጨልም ያደርጋል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን የጨለመው ዓይነ ልቡናችን ብሩህ እንዲኾን ያደርጋል፡፡ ስካር የኀጢአት ጓዝ ይዞ ይመጣል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን አዲስ የሚመጡትን ብቻ ሳይኾን የነበሩትንም ያስወግዳል፡፡
ልጆቼ! የዚህን ዓለም ደስታ ንቆ ሰማያዊ ደስታን እንደ መሻት ያለ ጥበብ ምንም የለም ብዬ እነግራችኋለሁ፡፡ ይህን ገንዘብ የምናደርግ ከኾነ፣ ለሰማያዊ ሕይታችን ቅድሚያን የምንሰጥ ከኾነ የዚህ ዓለም ዝባዝንኬ ቢቀርም አይከፋንም፡፡ አንድ ሰው ባለጸጋ ስለኾነ ቅናት አይይዘንም፡፡ ምንም ምድራዊ ሀብት ባይኖረንም ድኾች እንደኾንን አናስብም፡፡ ባለ ጸጋውን ክርስቶስ የያዘ ሰውስ እንዴት ድኻ ይባላል? በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ በዓል ማድረግ ማለትም ይኸው ነው፡፡
እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! አንድ ክርስቲያን በዓልን ሲያከብር ሳምንትን ወይም ወርን ወይም ዓመትን ጠብቆ መኾን የለበትም፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር እንደሚስማማ አድርጐ ዕለት ዕለት በዓል ሊያደርግ ይገቧል እንጂ፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር የሚስማማ በዓል ማለትስ ምን ማለት ነው? ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ምን እንደሚለን አብረን እናድምጠው፡- “በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም” (1ኛ ቆሮ.5፡8)፡፡ ንጽሐ ልቡናን ገንዘብ ያደረገ ሰው ዕለት ዕለት በዓልን ያከብራል፡፡ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት የተጠበቀለት ነው፡፡ ከሰማያዊው ማዕድና መጠጥ ተካፍሎ ሐሴት ያደርጋል፡፡ በዚህ ምድር ላይ የሚደረጉ ጊዜያዊ ክንውኖች ስለቀረበት የኾነ ነገር እንደቀረበት አያስብም፤ እርሱ ያገኘው ከዚህ በእጅጉ የሚልቅ ነውና፡፡ ነፍሱን ከሚያቆሽሹ ገቢረ ኀጢአቶች ራሱን ይጠብቃል፡፡
በገቢረ ኀጢአት ተሰማርተን ሳለ ሺሕ ጊዜ በዓላትን ብናከብር ግን እንዳከበርን ልንቈጥረው አይገባንም፡፡ ያከበርነው የበዓል ቀን (በዓል ማለት ደስታ ማለት ነው) ሳይኾን የኀዘን ቀን ነውና፡፡ ነፍሴ በኀጢአት ቀንበር ተይዛ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ሳለች የደስታን ቀን ባከብር ለእኔ ምን ጥቅም ያመጣልኛል?.....ይቀጥላል
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ- ሰማዕትነት አያምለጣችሁ እና ሌሎች ገጽ 13-36)
1 187
ዛሬም አለሽ በልቤ
ዛሬም አለሽ በልቤ/3/
ድንግል ሆይ ወለታሽ አይጠፋም ከሀሰቤ
አዝእንደ ሀጥያቴ ብዛት እንዴ በደሌማ የጥልቁ ሰንሰለት ሲይንሰኝ ነው ጨለማ ግን ያንች ሆንኩኝና ሁሉንም አለፈኩኝ ያንን የሞት ባህር በምልጃሽ ቀዝፈኩኝ
አዝአርፏል ልቤ በአንቺ በአዛኝቷ ማርያም ውስጤ እያፈሰሰ ፍቅርና ሠለም ህመሜም ቢያስረሳኝ የወዳሴሽ ቃና እመቤቴ እላለሁ ዛሬም እንደገና
አዝእናታችን ፅዮን ሰው ሁሉ ይልሻል ዳዊት በበገና ያመሰግንሻል የአሴቦን ነግሥታት ለክብርሽ ዘማሩ የማትፈርሽ መቅደስ የእግዚአብሔር ሀገሩ
አዝእጅግ ብዙ ነገር አድርገሽልኛል ይቅር ባይ ልጅሽ በፍቅር አይቶኛል እኔስ እኖራሉሁ ድንግል በአንች ጥላ ጨለማን አላይም ከእንግድህ በኃላ ዘማሪ ልዑልሰገድ ጌታቸው
1 187
እንደተመለከቱ ደስታውን እንደተካፈሉ ቅዱስ ሉቃስ ጽፎልናል፡፡ በትንሣኤው ነጭ ልብስ ለብሰው የታዩ መላእክት የደስታ ዘመን ነው ሲሉ በእርገቱም ነጭ ልብስ ለብሰው የዕርገቱን የምሥራች ለሐዋርያት አብስረዋል፡፡
/ምንጭ፤ የቃል ትምህርትና በመምህር ምሥጢረ ሥሳሴ ማናየ/
የአምላካችን ቸርነቱ ረድኤቱ አይለየን፡፡፠ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ፠
1 187
ዕርገተ እግዚእ
እንኳን ለጌታችን በዓለ ዕርገት አደረሳችሁ፥ አደረሰን፤ በዓሉን የሚመለከት ጽሑፍና ሥርዐተ ማኅሌቱን እንደተለመደው አቅርበንላችኋል፡፡ መልካም ንባብ፤ መልካም የምሥጋና ማኅሌት፡፡
‹‹አልቦ ዘዓርገ ውስተ ሰማይ ዘእንበለ ዘወረደ እምሰማይ ወልደ ዕጓለመሕያው፤ ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡›› ዮሐ.3፥13
ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡ እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው፡፡ ይህ ኃይለ ቃል ክብር ምስጋና ይግባውና ስለጌታችን፣ አምላካችን፣ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት መውረድ ከድንግል ማርያም መወለድ እና የሰውነቱን ሥራ ጨርሶ በክብር ወደ ሰማይ ማረጉን የሚገልጽ ነው፡፡ እንደሚታወቀው አምላካችን ስለሁለት ዐቢይ ጉዳዮች ሰው ሆኗል፡፡
1. *ለቤዛነት /ዓለምን ለማዳን/
2. *ለአርአያነት /ምሳሌነት/
የሰውን ልጅ በመውደዱ ልዑል ባሕርዩን ዝቅ አድርጎ ከሰማይ ወረደ ሥጋ ለበሰ በምድር ላይ ተመላለሰ፤ ምድርን በኪደተ እግሩ ቀደሰ፤ ድውያንን ፈወሰ፤ ፍጹም ሰው እንደ መሆኑ ተራበ ፍጹም አምላክ መሆኑንም ያስረዳ ዘንድ አምስት ገበያ ሕዝብ በአምስት እንጀራ በሁለት ዓሣ አጠገበ ማቴ.14፥19 ለእኛ አርአያና ምሳሌ ለመሆን ዝቅ ብሎ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ ዮሐ.13፥14 እኛም ፍለጋውን እንከተል ዘንድ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ ለቢጽክሙ እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ ብሎ አዘዘ፡፡ መምሕረ ትሕትና ነውና በዚህ ዓይነት መልኩ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር በዚህ ዓለም ኖረ ለሐዋርያት ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን አስተማራቸው ትምህርት በሚገባ ከተረዳለት በኋላ ለድኅነተ ዓለም በማዕከለ ምድር በቀራንዮ ተሰቀለ፡፡
#ወገብረ_መድኀኒተ_በማዕከለ_ምድር_እንዲል_በምድር_መካከል_መድኀኒትን_አደረገ_መዝ.73፥12
‹‹እስመ ኢይደልዎ ለነቢይ መዊት በአፍአ ዘእንበለ በኢየሩሳሌም፤ ነቢይ በኢየሩሳሌም ነው እንጂ በውጭ ሊሞት አይገባውም፡፡›› ብሎ እንደተናገረ፡፡ ሉቃ.13፥33 በሞቱ ዓለምን አድኖ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር አድሮ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ብርሃነ መለኮቱን ገልጾ ተነሣ፡፡ ነቢያት እንደተናገሩ ‹‹እግዚአብሔር ይነሣል ጠላቶቹም ይበተናሉ››� መዝ.67፥1 ‹‹እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁ እግዚአብሔርም አስነሥቶኛልና ተነሣሁ፡፡›› መዝ.3፥5 ‹‹እግዚአብሔር አሁን እነሣለሁ ይላል መድኀኒትንም አደርጋለሁ በዕለቱም እገለጣለሁ››� መዝ.11፥5፡፡
‹‹ሥጋየ ደግሞ በተስፋ /በትንሣኤ/ ታድራለች ነፍሴን በሲዖል /በመቃብር/ አትተዋትምና/ እነሣለሁ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተወውም፡፡›› መዝ.15፥9 ‹‹አቤቱ ንቃ ለምንስ ትተኛለህ ተነሥ ለዘወትርም አትጣለን›› መዝ.43፥23 ‹‹እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ›› መዝ.77፥65 ተብሎ የተተነበየውን ትንቢት ፈጽሞ ተነሣ፡፡ በሞቱ ሞታችንን ሻረልን፤ በመቀበሩም ሙስና መቃብርን አጠፋልን፡፡ ‹‹በሞቱ ሞትን አጠፋው›› እንዲል መጽሐፈ ኪዳን፡፡ ሕንፃ መነኮሳት ‹እርሱ በሁሉ ምሉዕ ሲሆን በመቃብር ለመቀበር ዮሴፍ ኒቆዲሞስ ገንዘውት ታየ፡፡ ከመሬት ውስጥ በመቀበሩም ሙስና መቃብርን አጠፋ፤ ከሥሩም ነቀለው ከተነሣ በኋላ ትንሣኤውን መጀመሪያ ለማርያም መግደላዊት ገለጸ ማር.16፥9፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ስለ ትንሣኤው ሲመሰክር ‹‹ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ፤ ተቀበረም፤ መጽሐፍ እንደሚል፤ በሦስተኛው ቀን ተነሣ፡፡ ለኬፋም ታየ በኋላም ለአሥራ ሁለቱ ከዚያም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታየ፡፡ ከዚያም በኋላ ለያዕቆብ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ ታየ›› 1ቆሮ.15፥3-8 ብሎ ክርስቶስ ትንሣኤውን ለተከታዮቹ በሙሉ የገለጠ መሆኑን መስክሯል፡፡ የሚያምኑ ፈሪሳውያንም ‹‹ትንሣኤው ምትሐት ነው›› እንዳይሉ እየታየ እያስተማረ እስከ 40 ቀን ድረስ መቆየቱን ይገልጽልና፡፡ በዚህም የአርባ ቀን ከትንሣኤ በኋላ ቆይታው ሦስት ቀን ጉባኤ አድርጎ ደቀ መዛሙርቱን እንዳስተማረ ቅዱስ ወንጌል ይነግረናል፡፡ ኢየሱስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ሲገለጥላቸው ይህ ሦስተኛ ጊዜ ነበረ እንዲል ዮሐ.21፥14 ይህንም ሊቃውንት አባቶቻችን፡-
1. *የትንሣኤ
2. *የአግብኦተ ግብር /ዳግም ትንሣኤ/
3. *የጥብርያዶስ ነው ብለው አስቀምጠውታል በዚህ 40 ቀን ቆይታ መጽሐፈ ኪዳንን ለደቀ መዛሙርቱ አስተምሯል፡፡
ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም ዕርገቱን ለመናገር ከሰማየ ሰማያት መውረዱን አስቀድሞ ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ማንም ወደ ሰማይ የወጣ የለም እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው ብሎ ከዕርገቱ በኋላ በየማነ አብ፤ በዘባነ ኪሩብ በአምላክነት ሥልጣን ለመኖር ወደሰማይ የወጣ ከእርሱ በቀር ሌላ እንደሌለ አስረግጦ ነገረን፡፡ ሲጀምር ከሰማይ መውረዱን ማስቀደሙ ወረደ ብሎ ዐረገ ለማለት ይመቻል፡፡ ተጸነሰ ተወለደ ለማለት ጥንቱ ከሰማያት ወረደ ማለት እንደሆነ ሁሉ፤ ‹‹ተሰቀለ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፤ ተነሣ'››ለማለት ‹‹ጥንቱ:- ተጸነሰ፤ ተወለደ፤ አደገ ተመላለሰ ሠላሳ ዓመት ኖረ›› የሚለው ነው፡፡ ስለሆነም ቅዱስ ዮሐንስ ጠርዝና ጠርዙን ይዞ ተናገረ፡፡ ‹‹ወረደ ዐረገ›› የሚሉት ሁለት ቃላት የዓለም ድኅነት መነሻና መድረሻ ናቸው፤ እነዚህን ሁለት ቃላት ስናይ በሁለቱ መካከል የተፈጸሙትን የአምላክ ሥራዎች ልብ ማለት ይገባል፡፡ ቤት በመሠረት ይጀመራል በጣሪያ ይፈጸማል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ይህን የቤዛነት ሥራ ሲያስረዳ በዮሐ.1፥14 ‹‹ቃል ሥጋ ኮነ፤� ቃል ሥጋ ሆነ›› ብሎ ጀምሯል ይህንም ቃል ‹‹ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም›› በማለት ሰው መሆኑን ብቻ ሳይሆን በአርያም የሚኖር መሆኑን አስተማረን፡፡ እንግዲህ ጌታችን ዕርገት እንዲሁ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አለመሆኑን ቀድሞ በነቢያት የተነገረ ኋላም በሐዋርያት የተመሰከረ መሆኑን ማወቅ ያስፈለጋል፡፡
#የክርስቶስ_ዕርገት_በትንቢተ_ነቢያት
‹‹ሰማዮችን ዝቅ ዝቅ አደረገ ወረደም ጨለማ /ዲያብሎስ/ ከእግሩ በታች ነበር በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ በረረ በነፍሳትም ክንፍ በረረ››� መዝ.17፥9 ‹‹አምላክ በእልልታ እግዚአብሔር በመለከት ድምጽ ዐረገ መዝ.46፥5 ወደላይ ዐረግህ፥ ምርኮን ማረክህ ፥ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ›› መዝ.67፥18፡፡
‹‹ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘዓርገ ውስተ ሰማይ ዘመንገለ ጽባሕ፤ በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ›› መዝ.67፥33፡፡
#የክርስቶስ_ዕርገት_በትምህርተ_ሐዋርያት
ጌታ ኢየሱስም ከእነርሱ ጋር ከተነጋገረ በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ፡፡ ማር.16፥19 ‹‹እስከ ቢታንያ አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ እነርሱም ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደኢየሩሳሌም ተመለሱ፤ ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ፡፡››� ሉቃ.24፥50 ‹‹ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ ደመናም ከዐይናቸው ሰውራ ተቀበለችው፤ እርሱም ሲሄድ ወደ ሰማይ ትኩር ብለው ሲመለከቱ ሳሉ እነሆ ነጫጭ ልብስ ለብሰው ሁለት ሰዎች /መላእክት/ በአጠገባቸው ቆሙ ደግሞም ‹‹የገሊላ ሰዎች ሆይ ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ስለምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት ዳግመኛ ይመጣል፡፡›› አሏቸው››� ሐዋ.1፥9-12 በማለት ሐዋርያት የክርስቶስን ዕርገት ከመላእክት ጋር ሆነው
1 187
#ሆሳዕና
በዕለተ ሆሳዕና እስራኤላውያን ለምን የዘንባባ ዝንጣፊ፤ የቴምር ዛፍ ዝንጣፊ እና የወይራ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ዘመሩ? (ማቴ. 21÷1-17፣ ማር. 11÷ 1-10፣ ሉቃ. 19÷29-38፣ ዮሐ. 12÷12-15)
#የዘንባባ_ዝንጣፊ፡-
☞ይስሃቅ በተወለደ ጊዜ አብርሃም ደስ ብሎት ዘንባባ ይዞ እግዚአብሄርን አመስግኖበታል የደስታ መግለጫ በመሆኑ አነተ ደሰታ የምታስገኝ ሃዘናችንንም የምታርቅ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡
☞ ዘንባባ ደርቆ እንደገና ህይወት ይዘራል የደረቀ ሕይወታችንን የምታለመልም አምላክ ነህ ሲሉ ነው
☞ ዘንባባ የሰላም ምልክት ነው የሰላም አምልክ ነህ ሲሉ ነው
☞ ዘንባባ እሾሃማ ነው አንተ ህያው አሸናፊ አምላክ ነህ ሲሉ ነው
☞ ዘንባባ እሳት አይበላውም ለብልቦ ይተወዋል እንጅ ጌታም አንተ ባህርይህ የማይመረመር ነው ሲሉ ነው
☞ ዘንባባ የነፃነት ምልክት ነው ከባርነት ነፃ የምታወጣን አንተነህ ሲሉ ነው አኛም ይህን በማሰብ ዘንባባ ይዘን ሆሳእና በአርያም እያልን እለቱን እናስባለን፡፡
#የቴምር_ዛፍ_ዝንጣፊ፡-
☞ የቴምር ዛፍ ፍሬ ጣፋጭ ነው፦ በሃጥያት የመረረውን ሂወታችን የምታጣፍጥልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው።
☞ የቴምር ፍሬ የሚገኘው ከዛፉ ከፍታ ላይ ነው አንተ አምላካችን ልዑለ ባህሪ ነህ ከፍ ከፍ ያልክ አምላክ ነህ ሲሉ ነው።
☞ የቴምር ዛፍ ፍሬ በውስጡ ያለው ፍሬ አንድ ነው አንድ አካል አንድ ባህሪ ነህ ሲሉ ነው።
☞ የቴምር ፍሬ በእሾህ የተከበበ ነው ይህም የአንት ባህሪ የማይመረመር በእሳት የተከበበ ነው ሲሉ ነው።
#የወይራ_ዛፍ_ዝንጣፊ፡-
☞ የወይራ ቅጠል የሰላም ማብሰሪያ ነው ሰላማችንን የምታበስርልን የምታስገኝልን አንተ ነህ ሲሉ ነው፡፡
☞ የወይራ ቅጠል ከእንጨት ሁሉ ጽኑ ነው አንተም ጽኑ ሃያል አምላክ ነህ ሲሉ ነው።
☞ ወይራ ለመብራት ያገለግላል ፍሬው ዘይት ያወጣል ከወይራ የሚገኝ ዘይት ጨለማን አሸንፎ ብርሃን እንደሚሰጥ ሁሉ አንተም ጨለማ ህይወታችንን የምታስወግድልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው።
☞ በኦሪት ግዜ የወይራ ዘይት ለመስዋአትነት ይቀርብ ነበር አንተም እንደ ዘይቱ ለመተላለፋችን መስዋዕት ሆነህ የምትቀርብ አምላክ ነህ ሲሉ ነው። በመስቀል ላይ መስዋዕት ሆኗልና።
በዓሉን በዓለ ክብር በዓለ ፍስሐ ያድርግልን፡፡
1 187
"ጌታ በአህያ ውርንጫ ላይ የተቀመጠው ትሕትናን ሊያስተምረን ነው። እርሱ ሰማያዊ ንጉሥ ሲሆን በምድራዊ ፈረስ ላይ አልተቀመጠም፤ ይልቁንም ትሕትናን ገንዘብ እንድናደርግ ዝቅ ብሎ ታየ። በሆሣዕና ዕለት ሕፃናት ዘንባባ ይዘው ሲዘምሩ፣ እርሱ ግን በልባቸው ውስጥ ያለውን እውነተኛ ፍቅር ይመለከት ነበር።"
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ
