fa
Feedback
Troubled Thoughts Dept.

Troubled Thoughts Dept.

رفتن به کانال در Telegram

Contact me through: https://t.me/Novalis07

نمایش بیشتر
1 223
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
اطلاعاتی وجود ندارد7 روز
اطلاعاتی وجود ندارد30 روز
آرشیو پست ها
photo content

photo content

photo content

photo content

ትልቅነትህን ፣ ሊያዋርደው ሲሻ ጋን አ’ርጎ አኖረህ ፣ በጠጠር ትከሻ ———————

photo content

«… አምስት፣ ስድስት፣ ሰባት …» አንድ ወቅት ላይ ለተወሰኑ ቀናት … ወደኾነ የሀገራችን ክፍል የመሄድ ዕድል አገኘኹ። ከመሄዴ በፊት …ስለቦታው አንድ ኹለት ያኽል ደስ የሚሉ ዘፈኖች ሰምቼ ነበርና …ቦታውን ለማየት በጣም ጓጓኹ። እንዲኽ የተዘፈነለት፣ ግጥምና ዜማ የተሠራለት ቦታ እንዴት ያለ ቢኾን ነው የሚልን ሀሳብ እያሰብኹ፣ ወደ መንገድ ዳር ወጥቼ ባጃጅ ተሳፈርኩ። «እስቲ እንትን የሚባለው ቦታ አድርሰኝ» «እሺ ግባ» የተወሰኑ ደቂቃዎች እንደነዳ የመንገዱን ጥግ ይዞ ቆመ። «ምነው?» «ደረስንኮ» «እንትን የሚባለው ቦታ ይኼ ነው እንዴ?» ማመን አልቻልኹም… «አዎ» ወርጄ ሳይ ወዲያና ወዲኽ ተራርቀው አምስት ቤቶች፣ ስድስት ዛፎችና፣ ሰባት ሰዎች ብቻ ይታዪኛል። … የቀረው ቁጥቋጦ የወረረው በረሃና የተራቆተ ተራራ ነው። ክው ነው ያልኹት። በጉጉት የተሞላው ልቤ በኩርፊያ ኩምሽሽ አለ። «በቃ ይቺው ናት?» አልኹት ባለማመን «ምን ፈልገኽ ነበር?» አለኝ እየሳቀ … … አንዳንድ ደስታዎች እንዲኽ አይደሉም ወይ? አብዛኛው መሻትና ፍላጎታችን ጉም እንደመጨበጥ አይደለም ወይ? አንዳንድ ነገሮች በጥበብ ስም፣ በዕውቀት ስም፣ በፋሽን ስም፣ በሥልጣኔ ስም፣ በወጣትነት ስም፣ በሀገር ስም የተጋነኑ ናቸው። እዚኽ ካልደረስክ «ፋራ» የሚያስብሉ … ስንደርስ ግን ኹሉም በጋራ መስማማት እውነት የተደረጉ ውሸቶች መኾናቸውን እንረዳለን። ሀቀኞች ሮጠው ወደመጡበት ይመለሳሉ። ፈሪዎች ግን ራሳቸውን እየዋሹ መኖር ይቀጥላሉ። አንዳንድ ሰዎች ሲታዪ ረዥም ይመስሉና ደርሳችኹ አጠገባቸው ስትቆሙ አያጥሩባችኹም? ስብዕናቸውም እንደዚያው የኾኑ አሉ። ስታውቋቸው ወርደው ተዋርደው ቅልል የሚሉ እንደገለባ … ምነው ባላውቃቸው ኖሮ የሚያስብሉ አሉ። አንዳንዴ የኾነን ነገር ደርሶ ከማየት በጉጉት መኖር የተሻለ ነው። አስቡት ዕድሜ ልካችኹን አንድን ነገር ስታሳድዱት ከርማችኹ የደረሳችኹበት ቀን ምንም ሲኾን? … አምስት ምንም፣ ስድስት ከንቱ፣ ሰባት ባዶ … ሲኾን እና ጥቂት የጥርጣሬ ሥፍራ መተው አሪፍ ነው መሰለኝ። ————— 𝙰𝚙𝚘𝚝𝚑𝚎𝚘𝚜𝚒𝚜 𝙷𝙴𝚗𝚘𝚌𝚔 𝙱. 𝙻𝚎𝚖𝚖𝚊

photo content

« ወዲያ ገጠር ፣ ወዲህ ከተማ•••» | ሀሳብ ቢጤ ለእኔ … ብዙውን ጊዜ የገጠር ሕይወት ፍጥነትና ድሎት፣ የከተማው ደግሞ ስክነትና አስተውሎት ይጎድላቸዋል —ለእኔ ። ገጠር ውስጥ ሰዓቱ የሚቆጥር አይመስልም። ቀስስ ብሎ ይነጋል፣ ተዝናንቶ ይመሻል። አንድ ወሬ ከሩቅ ቦታ ለመድረስ ብዙ ይፈጅበታል። እያንዳንዷ ነገር በትኩረት የምትከወን ናት። ቦታ አለ— ሰፊ ባዶ ቦታ አለ። ጸጥታ አለ —ደስ የሚል ጸጥታ አለ። ግን ግን … ይሰለቻል። «በላገሩ … ገጠሩ» ምናምን ብለው የዘፈኑ ኹሉ ያሉት አሜሪካ ወይ አውስትራሊያ ነው። ደረቱን የገለበጠ ግዙፍ ተራራ፣ ዝም ብሎ የሚፈስስ ወንዝ፣ የሚዘናፈል የአዝዕርት ቁንዳላ፣ ሳር የለበሰ መረሬ አፈር፣ በሬዎች፣ ላሞች፣ በግና ፍየሎች፣ ከል የለበሱ ሕፃናት አሉ። ደስ ደስ ይልና፣ አስምጦ ሊያስቀር ይፈልግና …ከዚያ ይሰለቻል። ጥፋ ጥፋ ያሰኛል። እዚያ ያሉ ሰዎች አብዛኞቹ ደስስ ይላሉ። እርስ በራሳቸው እንጃ እንጂ ለእንግዳ ምቹ ናቸው —አልጋ። ብዙም ጭንቀት የላቸውም። የሚያስፈልጋቸው ምንም ወይም ጥቂት ነው። በብዛት ቆዳቸው ሸካራ ልብሳቸው አዳፋ ስለኾነ ብዙም አይታዘቡኽም። ጸጉርኽን ባትስተካከል፣ ጢምህ ቅርጽ ባይወጣለት፣ እጆችህ ቢቆሽሹ፣ ጥርሶችኽ በልማም ቢሸፈኑ ማንም ግድ አይሰጠውም። እዚኽ ተቀምጠህ እዚያ ከተማ ዓለም እያለፈኽ ይመስላል። ከተማው ይናፍቃል። ጠቆር ያለ ማኪያቶ ይናፍቃል። ቲያትር ማየት ይናፍቃል። ትንሽ ፈጠን ያለ ሕይወት ይናፍቃል። ጥቁር አስፓልት ይናፍቃል። ከተሜነት ልቡ ላለ ሰው …ዝምታ ጩኸቱ ያስፈራል። ዝምታ ይጠይቅኻል? «አንተ ማነኽ? ከወዴት መጣኽ? ወደየትስ ትሄዳለኽ?» ይልኻል —መልሱን ማሰብ ያስደነግጥኻል። ራስኽን ማሞኘት አለብኽ። በሌት ወጥተኽ የመጀመሪያዋን ሀገር አቋራጭ ትሳፈራለኽ። … ሮጠኽ ትመጣለህ። ወደ ዘመናይ ጓደኞች፣ ወደ ፈጣን ጎዳናዎች። «አራዳ ስሙ ሲነሣ አንረን ፒያሳ ፒያሳ . ቦሌ ነኽ ወይ ሳሪስ ቄራ ልምጣ ባየር እንዳሞራ … አሃ አሃ አሃ አሃ» [ዓለም ከበደ —አራዳ] . ከተማ ቀኑ ከሸማኔ መወርወሪያ ይልቅ ይፈጥናል። ሰኞ ብለኽ ሰኞ ነው። መቼ ነው በውል ሰማዩን ቀና ብለኽ ያየኸው? — አታስታውስም። ስትወጣ በሩን ቆለፍክ? መብራቱን አጠፋኽ? —ግማሽ መንገድ ደርሰኽ ግራ ይገባኻል። እንዳትመለስ ጊዜ፣ ትተኸው እንዳትሄድ ዋስትና የለኽም። ኹሉ ነገር ይጮኽብኻል። ጠዋት የምትነሳሣው በአእዋፍ ዜማ ሳይኾን በሚደብት የአላርም ጩኸት ተገፍትረኽ ነው። ጎዳናው እሪሪሪ ይላል። አፍንጫህ ጠረን ሳይመርጥ ይምጋል —ከቆንጆ ሽቶ እስከ ትቦው ምናምን ድረስ ይሸትኻል። … ዓይንህ ብዙ ነገር ያያል —መንገድ ላይ ከነልጆቿ ከተኛች እናት እስከ እኔ ነኝ ባይ ቆነጃጅት ድረስ። እያየኽ ብዙ መቆየት አትችልም። እያንዳንዱ ነገር ለተረኛው ቦታውን መልቀቅ አለበት። እኔን ብቻ ካላየኽ የሚል ተራራ የለም እዚኽ —ፍጥነት አለ እዚኽ —በፍጥነት መቀያየር አለ እዚኽ። በአጭሩ ገጠር ፎቶግራፍ እንደማየት ያለ ሲኾን ከተማ ፊልም እንደማየት ነው። በአብዛኛው ሥራህ ስሙን ያሳመረ ባርነት ነው —የእንትን እንትን አፊሰር ወይ የእንትን እንትን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር …። ሥራህን አትወደው ይኾናል ግን መብላት አለብኽ —መውጣት መግባት አለብኽ። ስልክ መደወል፣ ኢሜይል መመለስ፣ መተረማመስ፣ እዚያም እዚኽም መድረስ አለብኽ። እንቅስቃሴ ውስጥ፣ ፍጥነት ውስጥ፣ ፉርጎው ላይ መገኘት አለብኽ። «ስልኬ ሳይለንት ነበር» ብለኽ መዋሸት አለብኽ። የከተማ ሕይወት ለጽድቅ አይመችም የምልኽ ለዚኹ ነው። እዚኽ በመኖርኽ ብቻ ኃጢአተኛ ነኽ። ይኽን ልጓም አጥብቀን «ያየ አመነዘረ» ድረስ ከጎተትነው አብዛኞቻችን ጠፊ ነን። እዚኽ ንጹሕ መልበስ አለብህ። ባዕድ ትበላለኽ አቧራ ትተነፍሳለኽ። በሲኒ የሰፈፈ የቡና ፎቶ ፖስት ታደርጋለኽ —የቡናው አማሃይ ገብስ ወይ አሻሮ መኾኑን ግን ልብኽ ያውቀዋል። መማር፣ መሥራት፣ ከዚያ ደግሞ ከዚኽ ሀገር መውጣት ትፈልጋለኽ። አንዴ ልውጣ እንጂ ወደዚኽ ዞሬ አልሸናም ብለኽ ትዝታለኽ። ስለብዙ ነገር መረጃው አለኽ፣ empirical ዕውቀቱ ግን የለኽም። እንደ ምሳሌ እኔን ተመልከት። አዲሳባ ተወልጄ አድጌ ላረጅ ያለኹት ሰው ፈረንሳይ ፣ ሽሮሜዳ፣ ጨርቆስ የሚባሉ ታዋቂ ሰፈሮችን ረግጬ አላውቅም። ቀጨኔን ቅርብ ቀን ነው ያየኹት። መሐል መርካቶ ወስደው ቢጥሉኝ ስዋትት ማምሸቴ ነው … ምክንያት ስለሌለኽ የብዙ ሰዎችን ስም አትጠይቅም ። ግንኙነትህ የላይ በላይ ነው ። ታክሲ ውስጥ ያገኘኸውን ሰው ደግመህ የማየት ዕድልህ እጅግ የመነመነ ነው። እንደ ገጠር «የአያ እገሌ ልጅ ነው» የሚልኽ የለም —መጠነኛ መፋነን ይፈቀዳል። አርባ ዓመት ኖረኽ ዛሬም እንግዳ ነኽ። ባለፈው ቡና ልጠጣ በተቀመጥኹበት ያስተናገደችኝን ልጅ እግር ወጣት «አንች ልጅ ስምሽን ማን ይሉታል?» አልኋት … «አስምራ» አለችኝ። «ቆንጆ ስም ነው» አልኋት። «አመሰግናለኹ» አለችኝ። በአልኋትና አለችኝ በየሄድኹበት ረባም አልረባም እንዲኽ ባይተዋርነቴን ለመቀነስ እሞክራለኹ። ጥዱፍ ሕይወት ውስጥ ትንሽ ዕረፍት ለማግኘት ያኽል። « አማን አይደለም ወይ ባላገሩ ናፈቀኝ ደጉ ሰው ገራገሩ… እንደው ሂጂ ሂጂ ጩሂ፣ ብረሪ፣ ጥፊ …ይለኛል በይ በይ! በይ በይ» [አቦነሽ አድነው —ባላገሩ] በልብኽ የገጠርና የከተማ አማኻይ ቦታ ትሻለህ ፣ ያንን ማድረግ የምትችለው ከመኖር የሚዘልል ገንዘብ ሲኖርኽ ነው። ገንዘብ ካለኽ ገጠር ውስጥ ከተማ ፣ ከተማ ውስጥ ገጠር መሥራት ትችላለኽ። አሊያ ካፒታሊስት ነኽ ካፒታሊዝም ግን አያገለግልኽም። ኮሚኒስት ነኝ ትላለኽ ግን ኮሚኒዝም እንደ ልጅነት ነው —ተመልሶ አይመጣም። ከጎርባቾቭ ጋር አፈር ከድሜ በልቷል። የሚገመት አይደለም መኖር … ምናልባት ሕይወት በልምድ እንጂ በፍልስፍና የማትመራው ለዚኹ ይኾናል …በ’ንደዚህ ዓይነት ተቃርኖ ተሞልታለች። ——— 𝚃𝚑𝚎 𝚌𝚊𝚍𝚎𝚗𝚌𝚎 𝚘𝚏 𝙳𝚞𝚊𝚕𝚒𝚝𝚢 𝙷𝙴𝚗𝚘𝚌𝚔 𝙱. 𝙻𝚎𝚖𝚖𝚊

photo content

«… ኩኒስ ኒደርባ — ይኽም ያልፋል…» አንድ ሰው በአንድ ወቅት አንዲት ድኽነት ባደቀቃት፣ አዱኛ በራቃት መንደር እያለፈ ነበር። እያለፈ በድንገት ያየው ነገር ክፉኛ ያሳዝነዋል። ያየው ይኽን ነበር — አንድ ጎልማሳ ሰው ከአንድ በሬ ጋር እንደ ተጣማጅ በሬ በሞፈር ተጠምዶ ሌላኛው ሰው እርፉን ይዞ ያርሳል። መንገደኛውም ጠጋ ብሎ ሰውየውን እንዲኽ ይለዋል። «አንተ ሰው ይኽን መከራ እንዴት ቻልከው?» ሰውየውም ቀንበሩ በላዩ እንዳለ በላብ የተጠመቀ ፊቱን ቀና አድርጎ እንዲኽ ብሎ መለሰለት… «…ኩኒስ ኒደርባ…» ቃሉ የአፋን ኦሮሞ ሲኾን ትርጉሙም «ይኽም ያልፋል» የሚል ነው። ——— ብዙ ዘመናት አልፈው ያ መንገደኛ ድጋሚ ወደ መንደሯ ይመጣል። የዚያን ሰውዬ ነገር ለምን አልጠይቅም ይልና አፈላልጎ ሲያጣራ … ያ እንደበሬ ተጠምዶ ያርስ የነበረው ደሀ ሰውዬ እንዳለውም አልፎለት አኹን ንጉሥ እንደኾነ ይሰማል። መንገደኛው በመደነቅ ይኽን ሰው ማግኘት አለብኝ ብሎ ወደ ቤተ-መንግሥት ይኼዳል። «ያስገቡኝ ይኾንን …?» በሚል ስጋት ውስጥ ኾኖ በቦታው ሲደርስም ሰዎች እንዳሉት ያ መከረኛ ሰው በጋሻ ጃግሬዎች ተጠብቆ ፣ ወዙ ተመልሶ በወርቅና አልማዝ በተንቆጠቆጠ ዙፋን ላይ ተቀምጦ ያገኘዋል። ሰላምታ ከተለዋወጡ በኋላም መንገደኛው ጠጋ ብሎ … «በሕይወቴ እንዲኽ የሚያምር ቤተ-መንግሥት ዓይቼ አላውቅም» ይለዋል። . ሰውየውም ፈገግ ብሎ ትከሻውን መታ መታ እያደረገ … «ኩኒስ ኒደርባ» ብሎ መለሰለት። ——— በውስጡ ስንኾን ማገናዘብ የምንችለውና ዓለምን የምንረዳበትን ብቸኛ አማራጭ የሚሰጠን ያለንበትን ከባቢ ነው። ስለዚኽም መከራውም ደስታውም የሚያልፍ አይመስለንም። ከመከራው በላይ የመከራው ሐሳብ እንዳንነሣ አድርጎ ይጥለናል። ከተድላው በላይ የተድላውን አማራጮች መቋቋም ያቅተናል። ——— ምንም ተራ አባባል ቢመስል ግን «ይኽም ያልፋል» እያሉ መኖርን ያኽል ብልሕነት የለም። ዘመን እንደ ጥላ ያልፋል። ክፉ ቀን እንደ ደመና ይገፈፋል። ውበትም ቢኾን ይረግፋል። አቅምም ቢኾን ይደክማል። ሥልጣንም ቢኾን ይወሰዳል። ኀዘንም በሳቅ ይቀየራል። ስንከፋ ብቻ «ይኽም ያልፋል …» አንበል፣ ሲሳካልንም ያሰብነው ሲሞላም እንደሚያልፍ እንወቅ። ጊዜ ባቀናልን፣ ጥረትና ዕድል ባደላደለልን ነገር ሰውን አንበድል። የደከመን ቀን በሚወዱን ሰዎች ተጠልለን እንለፍ። በፈጣሪ የምታምኑ አንዳንዴ ሞኝነት ቢመስላችኹ እንኳ የያዛችኹትን አትልቀቁት። ለሰው በዚያ መኾን መልካም ነው። አዎ! «ኩኒስ ኒደርባ» …አዎ! «ይኽም ያልፋል» …. ያለፈ ቀን እንዳናጣችኹ በመጨረሻዋም ተስፋ ቢኾን ተንጠልጥላችኹ ትረፉ … ያለፈ ቀን ተሰላችተው ከቀሩት እንዳትኾኑ ክረሙ። . አንድ ቀን ከማዕበሉ ማዶ እንገናኛለን። —————— 𝙲𝚘𝚞𝚛𝚝𝚎𝚜𝚢 𝚘𝚏 𝚃𝚑𝚎 𝚜𝚢𝚖𝚙𝚊𝚝𝚑𝚎𝚝𝚒𝚌𝚜 𝙷𝙴𝚗𝚘𝚌𝚔 𝙱. 𝙻𝚎𝚖𝚖𝚊

photo content

photo content

photo content

"𝚃𝚑𝚎𝚊𝚝𝚛𝚎 𝚘𝚏 𝚝𝚑𝚎 𝙰𝚋𝚜𝚞𝚛𝚍" ይኽ ቦታ «የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት» ይባላል። ስሙ እንደሚገልጸው ሕዝብን የወከሉ ሰዎች የተሰበሰቡበት ቦታ ነው። እነዚኽ ሰዎች ሕዝብ የተባለው ባለ እልፍ ቅጽ መጽሐፍ አጠሬራ ናቸው። በደንብ አድርገው መልካችንን ይናገራሉ። ተወካዮቻችን የሕዝቡን ኹኔታ ወክለው ለምክክር ይቀመጣሉ። ምክራቸው ግን የአኪጦፌል ነው። እንደ ሕዝብ አንዳችን ሳንቀር እንዴት እንዳበድን፣ ድንቁርና በመካከላችን እንዴት እንደገነገነ፣ ሆድ አደርነት እንዴት የሚያኮራ ሙያ እንደኾነ፣ ፒ.ኤች.ዲ ሠርቶ ተራ ሎጂክ መረዳት እስካለመቻል መደንዘዝ እንደሚቻል ያስረዱናል። በየሰፈሩ ያለውን ቀን የሚጠብቅ የአምባገነን መዓት ስናያቸው ይገለጥልናል። ሱፍ ለብሶ እንዴት አውሬ መሆን እንደሚቻል፣ አብረን እየዋልን እንዴት እንደማንተዋወቅ፣ አጽዳቂ እንጂ አርቃቂ እንዳልሆንን፣ በሚያስለቅሰው የመሳቅ በሽታ ( PBA, pseudobulbar affect ) እንደተለከፍን ያስገነዝቡናል። ዕውቀት እንዴት እንደሚያሰቃይ፣ መፍትሔ ከማምጣት እንደ በግ መነዳት እንዴት እንደሚቀልል እኛ እንዲገባን የሕዝቡን ኹሉ ባሕርይ ይዘው በዚያ ተሰብስበዋል። በመኻላችን ያሉ ጤነኞችን እንዴት እንደምናሳቅቅ፣ በጋራ እብደታችን መሃል ለማሰብና ለመጠየቅ የመረጡትን እንዴት እንደምናሰቃይ ያሳዩናል። የሕዝብ ተወካዮች ሆይ ባክቴሪያዊ፣ ፈንገሳዊ ጠባያችን የሚጠናበት “culture media” ሆናችኹ ስለከረማችኹ እናመሰግናለን። ምክር ቤታችኹ የበሽታችን ማሳያ “petri dish” ሆኖ ስላገለገለ እናመሰግናለን። ይኽ እናንተን ለመውቀስ አይደለም። ገጸ-ባሕርይ ሆናችሁ ይህንን ትራጆኮሜዲ በዓለም የቲያትር መድረክ ስለተወናችሁን አመሰግናለኹ። እንዲኹ ሳያችኹ ምንም ተስፋ አይሰማኝም። 𝘛𝘩𝘪𝘴 𝘪𝘴 𝘵𝘩𝘦 𝘵𝘩𝘦𝘢𝘵𝘳𝘦 𝘰𝘧 𝘵𝘩𝘦 𝘢𝘣𝘴𝘶𝘳𝘥… 𝘸𝘩𝘦𝘳𝘦 𝘭𝘪𝘧𝘦 𝘩𝘢𝘴 𝘯𝘰 𝘱𝘶𝘳𝘱𝘰𝘴𝘦, 𝘨𝘰𝘢𝘭 𝘰𝘳 𝘖𝘣𝘫𝘦𝘤𝘵𝘪𝘷𝘦.

photo content

[ጭንቀቴን ለማን ላዋየው? አንተም እንደ ሰው ችላ ካልኸው] . የትላንት መንገዶች የሉኝም፣ የነገ ተስፋዎች አላበጀኹም —ምንም። ያለኸኝ አንተ ብቻ ነኽ —አንተ ብቻ። አንተ ከማየት የማታንቀላፋ ዓይን፣ ከመስማትም የማትሰለች ጆሮ ነኽ። አንተ ከመደገፍ የማትደክም ክንድ፣ ከመናገርም የማትበድል አንደበት ነኽ። ታዲያ እኔን ለምን ዝም ትለኛለኽ? ማን ያዋራት ብለኽ ፊትኽን ትመልሳለኽ? ለሰው ታካችነት ለምን አሳልፈኽ ትሰጠኛለኽ? እናት እንኳ የወለደችውን ልጅ በምትረሳበት ዓለም፣ ፍቅር እንደጠዋት ጤዛ ሳይውል በሚተንንበት ምድር ውስጥ እስከመቼ ታልፈኛለኽ? የዳዊት ልጅ እባክኽ አትለፈኝ፣ ለእኔም እዘንልኝ — አንገትኽን አዘንብልልኝ። . [ፍጥረት አሸልቦት እንቅልፍም ተጭኖት እኔ ግን ዓይኖቼ ገና አልተከደኑም የምኀረቱን ደጃፍ እሻለኹ አኹንም] . የልጅነቴ አምላክ የለኽም ወይስ ግድ የለኽም? በእጅኽ አልተሠራኹም? የድንገቴ ፈጠራ ውጤት ነኝ? እንደ ዓይን ብሌንህ አትሳሳልኝም? ፍጻሜዬ ምንም ነው? ከእንስሳት ብልጫ የለኝም? በኀዘን ወደ መቃብሬ ልውረድ? ስጠፋ አይገድኽም? የማይነጠቅን ሰላም እንዳጣኹ እንዲኹ ነፍሴ ትውጣ? ታዲያ ለምን ዝም ትለኛለኽ? ኃጢአቴ አቃተችኽ? ስለ በደሌስ ብዛት እጅኽ ከማዳን አጠረች? የእውነት ትርጉም አንተ አይደለኽም? በሕይወት የመቆየትስ ምክንያት፣ የእስትንፋሴስ ባለቤት አንተ አይደለኽምን? ግራ የተጋባችን ነፍስ ለምን በዝምታኽ ወደ ጥልቅ ትገፋታለኽ? በአጥንቴ ውስጥ አንተን መፈለግ የለም? ይኽን ግራ የተጋባ ትውልድ ሊያድን የሚወድድ የሚችልስ ማን አለ? በለሊት ወደ አንተ ስለሚቃትቱ ጎበዛዝት፣ በጠፍር አልጋቸው ላይ ስምኽን ስለሚጠሩ አዛውንት፣ ዛሬም ፍርድን ስለማያጣምሙ ንጹሐን ስትል አትመልስምን? ማን ያዋራት ብለኽ ዝም ትለኛለኽ? . [መቼ ነው የምንተያየው ዓይንኽን በዓይኔ የማየው? ቶሎ ና ዓለቴ ባሰብኝ ናፍቆቴ] . መንገዱ በትርጉም ማጣት ተመትቷል። ሕፃናት ጦርነትን አውቀው፣ ቂምንም ተምረው ያድጋሉ። ድኾች ይበደላሉ። ጉልበተኞች እንዳሻቸው ይኾናሉ። ማልቀስ ብቻ አቅም ሲኾን ሕይወት እጅግ ይታክታል። ዝም ስላልኽ ረስተንሃል። ትተንሃልና ተውኸን? እንደ ሰው ? አናሳዝንህም። አለኹ አትለኝም? በቃኹኽ? ታከትኹኽ? የት ነኽ? የት ታሰማራለኽ? በሌሊትስ የት ትመስጋለኽ? ከዚኽ በላይ በድንግዝግዝ መኖር አልችልምና የት ብዬ ልምጣ? አንተ የሴተኛ አዳሪ ወዳጅ አይደለኽምን? የወንበዴውስ አፍቃሪ አይደለኽምን? እና ለምን ዝም ትለኛለኽ? ማን ያዋራኝ? ማን ያጽናናኝ? ማን መንገድ ያሳየኝ? ማንስ ከሞት ጎዳና ይመልሰኝ? . [ጌታ ሆይ ጨርቅኽን ይዤ እማጸናለኹ ከአንተ ወዴት ከቶ እሄደለኹ ደጃፍኽ ብኖር ተጥዬ ክብሬ ነኽ ለኔ ደስታዬ] —————- N.B :— ግጥሞቹ የተወሰዱት ከዶ/ር ደረጀ ከበደ የመዝሙር ስንኞች ነው።

ከታክሲው ጋቢና ጀርባ ተቀምጧል —ሞተሩ ላይ። ረዳቱ ይጣራል . . . «ቦሌ …ቦሌ…»። አንድ አዛውንት አስተዛዝነው ሞተሩ ላይ የተቀመጠውን ወጣት ይለምኑታል። ልመናው ቀስ በቀስ ወደ መብት ጥያቄ እየተሸጋገረ ነው። . « … ኧረ ልጄ ስጠኝ እንጂ … ቢቸግረን እንጂ መች በዚህ ፀሐይ እንዞር ነበር ብለህ ነው። እንደው ያለህን … » . ልጁ ዝም እንዳለ ነው። መስጠት ካለመፈለጉ በላይ እጁን ወደ ኪሱ መክተት የደከመው ይመስላል። ሰውየው ግን ተስፋ አልቆረጡም። . « ልጄ … እ … እ» . ታክሲው ሞልቶ መንቀሳቀስ ሊጀምር ሲል አዛውንቱ እንዲህ አሉ… «ድሮም ሲያዩህ መናጢ ድሀ ነው የምትመስለው። አመዳም» . እንዴ አዲስ አበባ 😑

𝚂𝚘 𝚕𝚘𝚗𝚐, 𝚖𝚢 𝚏𝚛𝚒𝚎𝚗𝚍.
𝚂𝚘 𝚕𝚘𝚗𝚐, 𝚖𝚢 𝚏𝚛𝚒𝚎𝚗𝚍.

«ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ ለቅድስና አትመችም።» የኾነ ቦታ ለኾነ ጉዳይ ሄጄ ነበር። እና የሚፈርመው ኃላፊ የለም። ፕሪንተሩ አይሠራም። በጣም የተከመረ የፋይል ወረፋ አለ። ፋይል መፈለግ ራሱ ሳምንት ይፈጃል። መብራት ይቆራረጣል። ፋይናንሷ ራሷን አሟት ከቤት አልመጣችም። ሰው ሃብቱ ስብሰባ ገብቷል። ሰው ኹሉ ተስፋ እየቆረጠ ይመላለሳል። ከዚኽ በፊት ከአንድም ኹለቴ ስለመጣኹ የቤቱ አመል አልጠፋኝም። አንድ ሾካካ ሰውዬ አለ ( ይቅርታ ለቃሉ ግን ሾካካ ነገር ነው) … እርሱ ባለጉዳይ ስለሚበዛበት ሰው ቶሎ ቶሎ ይረሳል። እኔ ደግሞ “የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳም” ነውና ፊቱን ከብዙ ዓለማት ርቀት አልስተውም። . ሰው አለመኖሩን ጠብቄ ሰላምታ ሰጥቼ የተወሰኑ መቶ ብሮች እጁ ላይ ሳስቀምጥለት አንዳች ተአምር ተከሰተ። ፕሪንተሩ ሠራ። ወረፋው ገለል አለ። የሚፈርመው ኃላፊ እየሮጠ ቢሮው ገባ። ፋይናንሷ ደረሰኟን ይዛ ከተፍ አለች። መብራት ባይኖር ምን ችግር ፣ ጄኔሬተሩ ተረክ አለ። ሰው ሃብቱ ስብሰባውን ረግጦ ወጣ። ዐየኽ! የተፈረመ መብትኽን በተሸረፈ ገንዘብ የምትገዛበት ሀገር ነው። “ቅድስት” ሀገር ኢትዮጵያ ለቅድስና አትመችም። ስወጣ «ወጣቶችኮ በቃ አራዳ ናችኹ … » አለኝ። «ልክ ነሽ ብራዘር» ብዬው ወጣኹ። … ሾካካ ፈጣሪውን ከማይፈራ ሰውን ከማያፍር ቢሮክራት መብትን መጠበቅ ወይስ መብትን መግዛት … የቱ ነው እርድና? ———