Dr. Tesfaye Robele
رفتن به کانال در Telegram
ተስፋዬ ሮበሌ (ዶ/ር) ሥነ መለኮት እና ፍልስፍና ያጠና ባለ ጥልቅ እውቀት አቅብተ እምነት ነው። ሥነ መለኮትን እና ፍልስፍናን ለመማር ከፈለጉ ይቀላቀሉን። ይህ ቻናል የራሱ (የዶክተር ተስፋዬ) አይደለም፤ ነገር ግን እኛ መውደዳችንን ለመግለፅና ሰው ሁሉ የእርሱን ጽሑፍ ወይም ቪድዮ በቀላሉ ማግኘት እንዲችል ካለን ፍላጎት የተከፈተ ነው። Ethiopia No: +251923439161 @chereGC
نمایش بیشتر6 732
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
+177 روز
+11330 روز
آرشیو پست ها
6 732
አፊዎተ እግዚአብሔርና ቀኖናውያት መጻሕፍት
ክፍል አንድ
ከተስፋዬ ሮበሌ
ሀ. ትልም
የዚህ ተከታይ ጽሑፍ ቀዳማይ ዐላማ:—
(1) በዕቅበተ እምነት ውስጥ የቅዱሳት መጻሕፍት ያላቸውን ጒልህና ትክክለኛ ቦታ ማሳየት፣
(2) በሃይማኖት ገበያ ውስጥ የቅዱሳት መጻሕፍትን ሥልጣናዊ ቃልነት ለሚቃወሙ ሁለት አግድም ዐደግ ዐሳቦች፣ አጸፋ መዘንዘር ነው፡፡
ለ. መግቢያ
የክርስትና ሃይማኖት፣ “አምላክ ፍጥረቱ ለሆኑ ለሰው ልጆች ሁሉ፣ ራሱን በተለያየ መንገድ ገልጾአል” ብሎ ያምናል፤ ያሳምናል፤ ያጠምቃል[1]፡፡ በነገረ መለኮት ትምህርት፣ አምላክ በሥነ ፍጥረት ወይም በታሪክ ሂደት ውስጥ ራሱን የገለጠበት መንገድ፣ “አጠቃላይ መገለጥ”[2] (ጥቅልል አስተርዮት[3]) ተብሎ የሚጠራ ሲሆን፣ አምላክ ራሱን በስፋት የተነተነበት መንገድ ደግሞ፣ “ልዩ መገለጥ”[4] (ልዩ አስተርዮት) ተብሎ ይታወቃል፡፡ ጥቅልል አስተርዮት ስለ ሀልዎተ እግዚአብሔር[5] የተወሰነ ጥቈማ ቢኖረውም፣ የአምላክን ባሕርይና ዕቅድ በዝርዝር አይናገርም፡፡ ልዩ አስተርዮት ግን የአምላክን ማንነት፣ ለፍጥረቱ ያለውን ዘላለማዊ ዕቅድና ምግባራዊ አኗኗር እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ጒዳዮችን በዝርዝር ይተነትናል፡፡
ከብዙ አንጻር ሲታይ፣ መጽሐፍ ቅዱስ እጅግ የተለየ መጽሐፍ ነው፡፡ በብዙ መጻሕፍት ውስጥ በእማኝነት የተጠቀሰ፣ እጅግ ብዙ በሆኑ የዓለማችን ቋንቋዎች የተተረጐመ፣ እጅግ ጥንታዊ የሆነ፣ በብዙ ሚሊዮን ሳይሆን በብዙ ቢሊዮን ቅጆች ታትሞ የተሠራጨ፣ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ እጅግ ትልቅ አዎታዊ ተጋቦት (ተጽእኖ) የፈጠረ…እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ያለ አንዳችም መጽሐፍ የለም ቢባል፣ እንኳን እብለት ነቊጥ ታህል ግነት የለበትም፤ በጭራሽ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ለዓለም ሥልጣኔ፣ ፍልስፍናና ሳይንስ ፈር ቀዳጅ ፋና ወጊ መሆኑን ማን ይክዳል? ይህና ይህን መሰል ጒዳዮች፣ መጽሐፍ ቅዱስ በሰው ልጆች ሕይወትና ታሪክ ውስጥ ትንግርታዊ ክሥተት፣ ተኣምራዊ ሁነት አድርገውታል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልዩ አስተርዮት ነው በሚለው አስተምህሮ ውስጥ አራት መሠረታውያን ጒዳዮች አሉ፡፡ ይኸውም:— (1) ግልጠተ እግዚአብሔር (አስተርዮተ እግዚአብሔር)[6]፣ (2) አፊዎተ እግዚአብሔር (እስትንፋሰ እግዚአብሔር)፣ (3) አብርሆተ እግዚአብሔርና (4) ተግባራዊ ክርስቲያናዊ ሕይወት ናቸው፡፡
ሐ. አስተርዮተ እግዚአብሔር
እነዚህን አራት መሠረታውያን የነገረ መለኮት ጭብጦች፣ በቅኝት መልክ እንመልከት፡፡ በመጀመሪያ ግልጠተ (አስተርዮተ) እግዚአብሔርን እንመልከት፡፡ የዐማርኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጒሞች፣ “መገለጥ”[7] ብለው የተረጐሙትን ቃል፣ የዐዲስ ኪዳን ግሪክ መጻሕፍት፣ “አፖካሊፕሲስ” (ἀποκάλυψις)[8] እና “ፋኔሮ” (φανερόω)[9] የሚሉትን ሁለት ቃላት፣ ቀያይረው ተጠቅመዋል፡፡ የግሪክ መዛግብተ ቃላት[10]፣ ሁለቱም ቃላት መሠረታዊ ትርጒም አንድ መሆኑ፣ በዐማርኛው አንድ ቃል ወክሏቸው መገኘቱ፣ አንዳችም የትርጒም ተፈልሶ እንዳይኖር አድርጓል፡፡ የሁለቱም ቃላት መሠረታዊ ትርጒም አንድ ነውና፡፡ ይኸውም:— ተሸፍኖ የነበረን ነገር ሽፋኑን በማንሣት ምንነቱን ወይም ማንነትን ማሳየት፡፡ በድቅድቅ ጨላማ ውስጥ ያለን ነገር፣ በበርሃን ወጋገን ግልጥልጥ አድርግጎ መመልከት፣ ስውሩንና ድብቁን ነገር ገሓድ ማውጣት፣ ለቀትር ፀሓይ ማጋለጥ፣ ርቃኑን ማስቀረት ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍት፣ በክርስትና ሕይወት እንዲሁም በዕቅበተ እምነት አገልግሎት ውስጥ ትልቅ ቦታ እንዳለው አመልካች ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች፣ ራሱንና ዐላማውን በዝርዝር ተንትኖአልና[11]፡፡
አምላክ ራሱን ለቅዱሳት መጻሕፍት ጸሓፊዎች የገለጠው እጅግ ብዙ በሆነ መንገድ ነው፡፡ በራእይ፣ በህልም፣ በድምፅ፣ ተኣምራዊ በሆነ መንገድ ወዘተ፡፡ (የሚከተሉትን ክፍሎች ይመለከቷል ዘፍ. 12፤ 32፤ ዘፀ. 3÷10፤ 33÷20፤ 13÷20-22፤ 24÷9-11፤ ዘዳ. 31÷14-15፤ ኢያ. 5÷13-15፤ ዳን. 3፤ ዕብ. 1÷1-2፤ ማቴ. 3፤ 5÷17፤ 3÷13-17፤ ዮሐ. 16÷8-11፤ ዮሐ. 1÷1-14፤ ሐሥ. 2÷3-4)፡፡
መጽሐፍ ቅዱስን ከሌሎች መጻሕፍት ፍጹም ልዩ የሚያደርገው፣ አምላክ ልዩ በሆነ መንገድ ለፀሓፍያኑ ራሱን መግለጡ ብቻ ሳይሆን፣ ከአምላክ የተገለጠው ሐቅ፣ በአምላክ ሉዓላዊ ጥበቃ በትክክል ተጽፎ መቅረቡ ነው፡፡ ግልጠተ (አስተርዮተ) እግዚአብሔር አምላክ ለፀሓያኑ ራሱን የገለጠበት መንገድ ሲሆን፣ አፊዎተ እግዚአብሔር ደግሞ፣ ፀሓያኑ ጒዳዩን በጽሑፍ ያስቀመጡበት ሂደት ነው፡፡
መ. አፊዎተ እግዚአብሔር
አሁን ደግሞ፣ “አፊዎተ[12] እግዚአብሔር” የሚባለው ፅንሰ ዐሳብ ምን እንደ ሆነ፣ ዐጭር ቅኝት እናድርግ፡፡ በግሪክ፣ “ቴዎፊኒስቶስ” (θεόπνευστος) የሚለው ቃል፣ በዐዲስ ኪዳን በኲረ ጽሑፋት ላይ አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሲሆን (2ጢሞ. 3÷16)[13]፣ ነባሩ እንዲሁም ዐዲሱ መደበኛ ትርጒም፣ “የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው” መጻሕፍት ብለውታል፡፡ የእንግሊዝኛ መጻሕፍት፣ “inspiration” የሚል አቻ ቃል ቀምረውለታል፡፡ የቃሉን ጭብጥ በትክክል ለማረዳት የእግዚአብሔርን ሉዓላዊነት እንዲሁም ዘላለማዊነት ታሳቢ አድርጎ መነሣት የግድ ይላል፡፡ ምክንያቱም በዚህ መጠን ጥልል ጥንፍፍ ያለ ሥራ ማከናወን የሚለው፣ አምላክ ብቻ ነው፡፡ አምላክ “እንዴት?” አይባልምና፡፡
□ “የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ፣ ልብንም ለማቅናት፣ በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል”፡፡
እነዚህ መጻሕፍት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን (2ጢሞ. 2÷15) እንዲሁም በወቅቱ እየተነበቡ የነበሩትን፣ የዐዲስ ኪዳን መጻሕፍት (2ጴጥ. 3÷16) ሊያመለክት ይችላል፡፡ አብ ኢየሱስን በላከበት ሥልጣን (ዮሐ. 20÷21)፣ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን መላኩ፣ ደቀ መዛሙርት የቤተ ክርስቲያን መሠረት እንዲሆኑ አድርጓል (ኤፌ. 2÷19-22)፡፡ ይህ ባሕርይ በዐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ላይ መታየቱ፣ ቃሉ ለብሉያት ብቻ ሳይሆን፣ ለዐዲስ ኪዳን መጻሕፍትም እንዲገለግል ምክንያት ሆኗል፡፡
በዐማርኛ የተዘጋጁ የነገረ መለኮት መጻሕፍት፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ይዘት፣ “አፊዎተ እግዚአብሔር”፣ “አምላካውያት መጻሕፍት”፣ “እስትንፋሰ አምላካውያት” ወይም “ቀኖናውያት መጻሕፍት” ብለውታል፡፡ አንዳንድ ጸሓፍያን ደግሞ፣ “አሥራው መጻሕፍት” ይሉታል፡፡ “አሥራው” የሚለው ቃል፣ “ሥረ መሠረት”፣ “መሠረቶች” የሚለውን ቃል የሚያመለክት ቅመራው፣ “የመጻሕፍት ሁሉ ሥረ መሠረት” ለማለት ተፈልጎ ነው[14]፡፡ አንዳንድ ኦርቶዶክሳውን፣ “መጻሕፍት አምላካውያት” ያሏቸው ሲሆን፣ “አምላክ ያጻፈቸው፣ በአምላክ ፈቃድ የተጻፉ፣ የአምላክን ነገር የሚናገሩ” ለማለት ነው[15]፡፡
6 732
Repost from Dr. Tesfaye Robele
እግዚአብሔርን በተመለከተ ልጆች የሚጠይቁአቸው 101 ጥያቄዎችና መጽሐፍ ቅዱሳዊ መልሶቻቸው
ከ19 ዓመታት በፊት በተስፋዬ ሮበሌ የተተረጐመ
6 732
ቅዱሳት መጻሕፍት ብቻ!
ይህ መጽሐፍ "ቅዱሳት መጻሕፍት ብቻ" የሚለውን የወንጌላውያን አስተምህሮ:-
(1) እርስ በርስ የተምታታ (ራሱን መልሶ የሚቃረን)
(2) የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ውግድ ያለ እንዲሁም
(3) መጽሐፍ ቅዱስን ለግላዊ ትንታኔ የሚዳርግ ነው ይላል!
በተከታታይ ጽሑፍ ከትካች አጸፋ እንዲሁም ተቃራኒ አጸፋ አቀርባለው! የትችቱን ምክንዮአዊ ጥንካሬና መጽሐፍ ቅዱስ መሠረት እገመግማለሁ!
በጎ ፈቃዳቸው ከሆነ ጸሓፊው ከትካች አጸፋዬን በመከትከት የሙግታቸውን ትክክለኝነት ማሳየት ይችላሉ! ጽሑፋቸውን ለመለጥፍ ፈቃደኛ ነኝ!
ይህን የዲያቆን ያረጋል አበጋዝ መጽሐፍ እስከ ገጽ 211 በማንበብ በውይይቱ ተሳተፉ!
ከእንከን የጸዳ አንዳችም ሰው ስለሌለ በጤናማ ውይይት ያስፈልጋል! ሰብአውያን መቅድመ ልባዌ ሰለባ እንዳይሆኑ ቃታ ጠባቂው ጤናማ ውይይት ነው!
በሩ ለምሁራዊ ውይይት ክፍት ነው!
በእኔ ቤት ስድብና ጥላቻ ቦታ የላቸውም! እንደምታውቁት ተሳዳቢን እስከ ወዳኛው “block” አደርጋለሁ ልጣፉን ጠራርጌ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ እከታለሁ! ነባር አካሄዴ ነው ተጠናክሮ ይቀጥላል!
ተስፋዬ ሮበሌ
6 732
በጠባብ ደረት በዐጭር ቁመት!
ብዙ ሰዎች የክርክር ምክንያት የሆነውን ቪዲዮ ለማግኘት ጠይቃችሁ ነበር! ቪዲዮው እነሆ!
የተናጋሪው መሠረታዊ ችግር በነገረ መለኮቱ ዓለም “The Economic Trinity” የሚባለውን ፅንሰ ዐሳብ ከ”The Immanent Trinity” ጋር ክፉኛ ማምታታቱ ነው!
“The Immanent Trinity” የአምላክ ኑባሬዊ ማንነት ሲሆን ይህ ጉዳይ በድነት ታሪክ ውስጥ (history of salvation) ለእኛ እንዴት እውን ሆነ ወይም ኢየሱስ ትስብእት ሲሆን የተነገረንን ጉዳይ ከአምላክ ማንነት አንጻር ማጣረሱ ነው!
ስለዚህ "አብ "በእርሱ" የሆነ አንዳችም ነገር የለም እንዲሁም ወልድ "ከእርሱ" የሆነ አንዳችም ነገር የለም" የሚለው የግለሰቡ ንግግር ከላይ ያለውን መሠረታዊ ልዩነት እርስ በርስ ያጠናበረ ነው!
1ቆሮንቶስ 8:6 መሠረት ተደርጎ አብ "ከእሱ" ብቻ ነው "በእርሱ" አይደለም እንዲሁም ወልድ "በእርሱ" ብቻ ነው "ከእርሱ አይደለም ከተባለ "ከ" እና "ለ" በጥምረት ለአንድ አካል ብቻ የዋሉባቸውን ምንባባት ምን እናድርጋቸው? (ለምሳሌ ሮሜ 11:36 "ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።"
እነዚህንም ክፍሎት ይመለከቷል:- ራእ. 5:12-14 ቆላ. 1:15-18 ዕብ. 2:10 ይሁዳ 1:25 ዕብ. 1:2-3 ኤፌ 4:5-6 ፊልጵ 2:9-11 ዮሐ 17:21-23 ማቴ 11:27
ይህ አንድ የሥላሴ አማኒ ነኝ የሚል ሰው ሊጠነቀቅበት የሚገባው ነጥብ ነው! ፍርጥም ብሎ መናገር ጥሩ ቢሆንም "ነገሩ እንዲህ ይሆንን?" ብሎ መጠየቅ ከወንጌል አገልጋይ ይጠበቃል!
Disclaimer: ከላይ ግልጋሎት ላይ የዋሉት ሙያዊ ቃላት ዛሬ ቃሉ በደርዛዌ ነገረ መለኮት ውስጥ ግጋግሎት ላይ የዋለበትን ዐሳብ ተንተርሶ የቀረበ እንጂ በጥንታውያኑ ሊቃውንት ዘንድ የነበረውን ቀደምት ክርክር በሚያሳይ መንገድ ጥቅም ላይ የዋለ አይደለም! ስለዚህ አንዳንድ ችኩል ተቺዎች "Etymological Fallacy" እንዳይፈጽሙ ለማሳሰብ ነው!
ቸር ሰንብቱልኝ!
ተስፋዬ ሮበሌ
