2 485
Suscriptores
Sin datos24 horas
-157 días
-5230 días
Archivo de publicaciones
2 485
የጉራጌ ዞን የደቡብ ክልል ምክር ቤት ተወካይ፤ ለሁለተኛ ጊዜ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋሉ
የደቡብ ክልል ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ታረቀኝ ደግፌ ትላንት ቅዳሜ ሰኔ 24፤ 2015 ምሽት በፌደራል ፖሊስ አባላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ጠበቃቸው እና ባለቤታቸው ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። አቶ ታረቀኝ በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ ወደ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ መወሰዳቸውን ባለቤታቸው ገልጸዋል።
የፌደራል ፖሊስ የደንብ ልብስ የለበሱ እና በ“ፒክ አፕ” መኪና የተጫኑ የጸጥታ አባላት በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራኒዮ አካባቢ ወደሚገኘው የአቶ ታረቀኝ መኖሪያ ቤት የደረሱት፤ ትላንት ከምሽቱ 2፡30 ገደማ እንደነበር ባለቤታቸው ወይዘሮ አዜብ መርሻ ተናግረዋል። የጸጥታ አባላቱ “ከፌደራል ፖሊስ ነው የመጣነው” ሲሉ መስማታቸውን የጠቀሱት አዜብ፤ “ለጥያቄ እንፈልግሃለን” ብለው አቶ ታረቀኝን አብረዋቸው እንዲሄዱ ጥያቄ ማቅረባቸውን አክለዋል።
ባለቤታቸው “እኔ ያለመከሰስ መብት አለኝ፤ የህዝብ ተወካይ ነኝ” ቢሉም፤ ፖሊሶቹ “እሱን እዚያ ታወራለህ፤ ተነስ ዝም ብለህ” የሚል ትዕዝዝ መስጠታቸውን አዜብ ገልጸዋል። የተሻሻለው የደቡብ ክልል ህገ መንግስት፤ የክልሉ ምክር ቤት አባል “ከባድ ወንጀል ሲፈጽም እጅ ከፍንጅ ካልተያዘ በስተቀር ያለ ምክር ቤቱ ፈቃድ አይያዝም፤ በወንጀል አይከሰስም” ሲል ይደነግጋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11341/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ቪዲዮ፦ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት ዛሬ ቅዳሜ ሰኔ 24፤ 2015 በአዲስ አበባ ከተማ አክብሯል፡፡ የኦነግ የቀድሞ አመራሮች እና ለፓርቲው አላማ “መስዋትዕነት” የከፈሉ ግለሰቦች በታወሱበት በዚህ የወርቅ ኢዩቤልዩ በዓል ላይ የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ተገኝተዋል፡፡
የኦነግን 50ኛ ዓመት አስመልክቶ በኦሮምኛ ቋንቋ ዘለግ ያለ ንግግር ያደረጉት የፓርቲውን ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ፤ በኦሮሚያ ክልል የሽግግር መንግስት የመመስረትን ጉዳይ አንስተዋል፡፡ ኦነግ ከሌሎች 17 ገደማ ፓርቲዎች ጋር በህብረት እየሰራ መሆኑንም ሊቀመንበሩ በንግግራቸው ጠቅሰዋል፡፡
“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የዛሬውን ክብረ በዓል እና ኦነግ እያነሳ ስላለው የሽግግር መንግስት ጉዳይ በተመለከተ የፓርቲው የፖለቲካ ኦፊሰር የሆኑትን ኮሎኔል ገመቹ አያናን አነጋግራለች፡፡ ኮሎኔል ገመቹ የሰጡትን ምላሽ እና የዛሬውን አከባበር ድባብ ሙሉውን ለመመልከት ይህን ይጫኑ፦ https://www.facebook.com/watch/?v=3540130406257026
@EthiopiaInsiderNews
2 485
የፌዴሬሽን ምክር ቤት የ“ደቡብ ኢትዮጵያ” ክልልን ለመመስረት የተካሄደውን ህዝበ ውሳኔ ውጤት ሊያጸድቅ ነው
የፌደሬሽን ምክር ቤት በመጪው ሳምንት ማክሰኞ እና ረቡዕ በሚያደርገው መደበኛ ስብሰባው፤ “ደቡብ ኢትዮጵያ” የሚል ስያሜ የተሰጠውን ክልል ለመመስረት የተካሄደውን ህዝበ ውሳኔ ውጤት እንደሚያጸድቅ የምክር ቤቱ ምንጮች ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፤ የህዝበ ውሳኔውን አጠቃላይ ሪፖርት ከነገ በስቲያ ሰኞ ሰኔ 26፤ 2015 ለፌደሬሽን ምክር ቤት በጹሁፍ ያቀርባል ተብሏል።
የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት፤ ከማንነት እና ራስን በራስ ከማስተዳደር ጋር በተያያዙ የሚነሱ ጥያቄዎችን የመመልከት ስልጣን የሰጠው ለፌደሬሽን ምክር ቤት ነው። የፌዴሬሽን ምክር ቤትን ስልጣን እና ተግባር ለመዘርዘር የወጣው አዋጅ፤ ምክር ቤቱ የህዝብ ፍላጎትን በህዝበ ውሳኔ እንዲረጋገጥ የማድረግ ኃላፊነትንም ሰጥቶታል።
በምርጫ ቦርድ የተከናወነውን ህዝበ ውሳኔ ውጤት የማጽደቅ ኃላፊነት በአዋጅ የተሰጠውም ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው። በመጪው ማክሰኞ ሰኔ 27፤ 2015 ከሰዓት በኋላ ተጀምሮ በማግስቱ በሚቀጥለው የምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ፤ ምርጫ ቦርድ የ“ደቡብ ኢትዮጵያ ክልል” ህዝበ ውሳኔን ሪፖርት በንባብ እንዲያቀርብ ቀጠሮ መያዙን የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ምንጮች ገልጸዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11334/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ግብይት ለመጀመር ዝግጅት ማጠናቀቋ ተገለጸ
ኢትዮጵያ በቀጣዩ የ2016 በጀት ዓመት በአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና፤ በአህጉሪቱ ካሉ ሀገራት ጋር ግብይት እንድትጀምር እቅድ መያዙን እና ዝግጅቶችም እየተጠናቀቁ መሆኑን የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ካሳሁን ጎፌ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። ኢትዮጵያ በአህጉራዊው ነጻ የንግድ ቀጣና የምትገበያያቸውን የምርቶች እና አገልግሎቶች አይነት፤ በቀጣዩ ሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ በሚካሄድ የአፍሪካ የንግድ ሚኒስትሮች ጉባኤ ላይ እንደምታቀርብም ገልጸዋል።
የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነት፤ በአህጉሩ ስር ባሉ ሀገራት መካከል የሚደረጉ የንግድ ግንኙነቶች ያሉባቸውን ተግዳሮች በመቅረፍ የሀገራቱን የንግድ ልውውጥ ለማሳለጥ ያለመ የአፍሪካ ህብረት ፕሮጀክት ነው። ኢትዮጵያን ጨምሮ 54 የአፍሪካ ሀገራት የፈረሙት ይህ ስምምነት፤ ሀገራቱ እርስ በእርስ በሚገበያዩት ወቅት የሚጣለውን ቀረጥ የማስወገድ እቅድ አለው።
በነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነቱ መሰረት፤ የአፍሪካ ሀገራት እርስ በእርስ የሚገበያዩዋቸውን 90 በመቶ ምርቶች እና አገልግሎቶች በአስር ዓመት ውስጥ ከቀረጥ ነጻ ያደርጋሉ። በ13 ዓመት ውስጥ ደግሞ ተጨማሪ ሰባት በመቶ ምርቶች እንዲሁ ከቀረጥ ነጻ አድርገው ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት እንዲያስገቡ ይጠበቃል። ሀገራቱ ቀረጥ መጣል የሚችሉት በመረጧቸው ሶስት በመቶ የሚሆኑ ምርቶች ላይ ብቻ ነው።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11317/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
የኢትዮጵያ የ11 ወራት የወጪ ንግድ አፈጻጸም የ12 በመቶ ገደማ ቅናሽ አስመዘገበ
የኢትዮጵያ የወጪ ንግድ (export) ባለፈው 11 ወራት የነበረው አፈጻጸም፤ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ11.8 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ። በዚህ ጊዜ ውስጥ ከወጪ ንግድ ለማስገባት ታቅዶ ከነበረው የገንዘብ መጠን ውስጥ፤ 1.5 ቢሊዮን ዶላር ያህሉን ማግኘት እንዳልተቻለም መስሪያ ቤቱ ገልጿል።
ባለፈው ጥር ወር ላይ 6.9 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱ ተገልጾ የነበረው የሀገሪቱ የወጪ ንግድ አፈጻጸም ጉድለት፤ ይበልጥኑ ከፍ እያለ መምጣቱ የተነገረው ዛሬ አርብ ሰኔ 23፤ 2015 በፓርላማ በተካሄደ የቋሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ነው። በተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የዛሬውን ስብሰባ የጠራው፤ የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴርን የ11 ወራት የእቅድ አፈጻጸም ለመገመገም ነበር።
የሚኒስቴሩን የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ለፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ ያቀረቡት፤ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የስትራቴጂክ ጉዳዮች ስራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ ኡርጌሳ ባይሳ ናቸው። በ11 ወራት ውስጥ ከወጪ ንግድ ለማግኘት ታቅዶ ከነበረው 4.74 ቢሊዮን ዶላር ውስጥ፤ 3.24 ቢሊየን ዶላር ያህል ማግኘት መቻሉን ስራ አስፈጻሚው ተናግረዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11312/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
#SafaricomEthiopia
በተሰናባቹ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ስራ አስፈጻሚ ምትክ አዲስ ኃላፊ ተሾመ
ሳፋሪኮም በኢትዮጵያ ለሚገኘው ኩባንያው ቤልጅየማዊውን ዊም ቫንሔለፑትን አዲስ ዋና ስራ አስፈጻሚ አድርጎ ሾመ። ላለፉት ሁለት ዓመታት ሳፋሪኮም ኢትዮጵያን የመሩት አንዋር ሶሳን የሚተኩት አዲሱ ስራ አስፈጻሚ፤ ከነሐሴ 26፤ 2015 ጀምሮ መሾማቸውን መቀመጫውን በናይሮቢ ያደረገው ሳፋሪኮም አስታውቋል።
አዲሱ የሳፋሪኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ ሀገራት የቴሌኮም ገበያ ከ25 ዓመታት በላይ የስራ ልምድ እንዳላቸው ኩባንያው ዛሬ ሹመታቸውን ይፋ ሲያደርግ ገልጿል። ዊም ቫንሔለፑት ሳፋሪኮም ኢትዮጵያን የተቀላቀሉት ሌላኛውን ግዙፍ የቴሌኮም ኩባንያ ኤምቲኤን ግሩፕን በመልቀቅ ነው።
ዊም ቫንሔለፑት በኤምቲኤን ውስጥ የገበያዎች ኦፕሬሽን ስራ አስፈጻሚ የነበሩት ቫንሔለፑት፤ በምዕራብ እና መካከለኛው አፍሪካ የሚገኙ አራት ኩባንያዎችን የስራ አፈጻጸም እና አስተዳደር የመምራት ኃላፊነት ሲወጡ ቆይተዋል ተብሏል። አዲሱ ተሿሚ በኡጋንዳ እና በኮትዲቯር የኤምቲኤን ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆነው የሰሩ ሲሆን በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሴኔጋል፣ ቻድ እና ጋቦን የሚገኙ የቴሌኮም ኩባንያዎችን ደግሞ በተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች መምራታቸውን ሳፋሪኮም በዛሬው ዕለት ያወጣው መግለጫ ይጠቁማል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ለመንግስት ተመላሽ መደረግ ከነበረበት 7 ቢሊዮን ብር ገደማ ውስጥ የተሰበሰበው ከ1 በመቶ በታች መሆኑን የፌደራል ዋና ኦዲተር አስታወቀ
በ2013 በጀት ዓመት እና ከዚያ በፊት በተደረገ ኦዲት ተመላሽ እንዲደረግ አስተያየት ከተሰጠበት 6.88 ቢሊዮን ብር ውስጥ ተመላሽ የተደረገው 0.65 በመቶው መሆኑን የፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት አስታወቀ። ይህ የገንዘብ መጠን ባለፈው ዓመት ተመላሽ ከተደረገው ጋር ሲነጻጸርም “በጣም ዝቅተኛ” መሆኑን መስሪያ ቤቱ ገልጿል።
የፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ይህንን ያስታወቀው የፌደራል መንግስት መስሪያ ቤቶችን የ2014 በጀት ዓመት የፋይናንስ ህጋዊነት እና ክዋኔ ኦዲት ሪፖርትን ዛሬ ማክሰኞ ሰኔ 20፤ 2015 ለተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበበት መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው። የመስሪያ ቤቱን ሪፖርት ለፓርላማ አባላት ያቀረቡት ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሰረት ዳምጤ፤ ተቋማቸው በ2013 በጀት ዓመት እና ከዚያ በፊት ባከናወናቸው የኦዲት ሪፖርቶች ላይ የታዩ ጉድለቶች ላይ እርምጃ የተወሰደ መሆኑን ለማረጋገጥ ማጣራት ማካሄዱን ተናግረዋል።
እንደ ዋና ኦዲተሯ ገለጻ መስሪያ ቤቱ በ2013 በጀት ዓመት፤ 86 የመንግስት መስሪያ ቤቶች 6.88 ቢሊዮን ብር “ተመላሽ” እንዲያደርጉ አስተያየት ተሰጥቷቸዋል። በዚህ አስተያየት መሰረት የተወሰደውን ማስተካከያ ያጣራው የፌደራል ዋና ኦዲተር፤ መስሪያ ቤቶቹ ያስመለሱት የገንዘብ መጠን 44.99 ሚሊዮን ብር ሆኖ ማግኘቱን ወ/ሮ መሰረት ለምክር ቤቱ አስታውቀዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11298/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ቪዲዮ፦ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ “አስተባባሪነት” የሚሰሩ ሜጋ ፕሮጀክቶችን አስመልክቶ “በግልጽ ጥያቄ” የሚቀርብ ከሆነ ኦዲት ለማድረግ “ዝግጁ” መሆኑን የፌደራል ዋና ኦዲተር አስታወቀ፡፡ የፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ይህንን ያለው ዛሬ ማክሰኞ ሰኔ 20፤ 2015 በተካሄደው ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው፡፡
በዚህ የፓርላማ ውሎ ላይ የፌደራል ዋና ኦዲተር የፌደራል መንግስት መስሪያ ቤቶችን የ2014 በጀት ዓመት የፋይናንስ ህጋዊነት እና ክዋኔ ኦዲት ሪፖርትን አቅርቧል፡፡ 59 ገጾች ያሉትን የመስሪያ ቤቱን ሪፖርት በንባብ ያቀረቡት ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሰረት ዳምጤ፤ ከመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እና ከምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ዋና ኦዲተሯ ከምክር ቤት አባላት ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ “አስተባባሪነት” የሚሰሩ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ኦዲት ከማድረግ ጋር የተያያዘው ይገኝበታል። የፌደራል ዋና ኦዲተሯ ወ/ሮ መሰረት ዳምጤ ለዚህ ጥያቄ የሰጡትን ምላሽ ከተያያዘው ቪዲዮ ይመልከቱ። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
2 485
የፌደራል መንግስት የበጀት ቅነሳ፤ የ12ተኛ ክፍል የፈተና አሰጣጥ ሂደት ላይ “ጉድለት ያመጣል” ተባለ
የትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት ለ2016 በጀት ዓመት ከጠየቀው ገንዘብ ውስጥ 476 ሚሊዮን ብር ገደማ ተቀንሶ መያዙ፤ በዘንድሮ የ12ተኛ ክፍል ፈተና ላይ ጉድለት እንደሚያስከትልበት አስታወቀ። ለ12ተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና የተጠየቀውን ገንዘብ በተመለከተ፤ “ከመንግስት ውሳኔ መተላለፍ” እንዳለበት የገንዘብ ሚኒስቴር ምላሽ ሰጥቷል።
የትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት ይህንን ጥያቄ ያነሳው፤ የ2016 ረቂቅ በጀትን አስመልክቶ ዛሬ ሰኞ ሰኔ 19፤ 2015 ዓ.ም በተካሄደ የህዝብ ይፋዊ ውይይት ላይ ነው። የተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባዘጋጀው በዚህ ውይይት ላይ፤ የተቋማት ተወካዮች፣ የፓርላማ አባላት እና ሌሎች ተሳታፊዎች በጀቱን የተመለከቱ ጥያቄዎችን አቅርበዋል።
ከእነዚህ ተቋማት ውስጥ አንዱ በሆነው በትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት በኩል የተነሳው ጥያቄ፤ የ12ተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተናን ለማከናወን ከሚያስፈልገው በጀት ጋር የተያያዘ ነበር። የዘንድሮውን የ12ተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና 870 ሺህ ገደማ ተማሪዎች እንደሚወስዱ ዛሬ በተካሄደው የበጀት ውይይት ላይ የጠቀሱት የትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት የስትራቴጂክ ጉዳዮች ዋና ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ግርማ መኮንን፤ ለእነዚህ ተማሪዎች ለሚቀርብ ቀለብ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚስፈልግ አስረድተዋል። ለእነዚህ ተፈታኞች ቀለብ ለማቅረብ፤ በመደበኛው የዩኒቨርስቲዎች አሰራር ለአንድ ተማሪ በቀን የሚመደበው 22 ብር በቂ አለመሆኑንም ጠቁመዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11281/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
#Budget #Parliament
በመጪው በጀት ዓመት ለበርካታ መንገዶች የተመደበው በጀት “አነስተኛ መሆኑ” በፓርላማ ቅሬታ አስነሳ
በ2016 የበጀት ሰነድ ላይ በርካታ የመንገድ ፕሮጀክቶች የተመደበላቸው ገንዘብ ከአስር ሚሊዮን ብር በታች መሆኑ፤ በፓርላማ ውይይት “አነስተኛ ነው” የሚል ቅሬታ አስነሳ። የፌደራል መንግስትን በጀት ያዘጋጀው የገንዘብ ሚኒስቴር፤ የእነዚህ የመንገድ ፕሮጀክቶች ጉዳይ “በበጀት አስተዳደር” ሊታይ እንደሚችል አስታውቋል።
የገንዘብ ሚኒስቴር በተያዘው ሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ ለፓርላማ ያቀረበው የ2016 በጀት አጠቃላይ መጠን 801.6 ቢሊዮን ብር ነው። ከዚህ በጀት ውስጥ ለመንገድ ፕሮጀክቶች የተመደበው ገንዘብ 68.4 ቢሊዮን ብር ሲሆን፤ ይህም ከፌደራል መንግስት የመደበኛ እና የካፒታል ወጪ ውስጥ 11.93 በመቶውን የሚሸፍን ነው።
በሚቀጥለው ሳምንት መጨረሻ በሚጀምረው የ2016 በጀት ዓመት፤ ለ300 ገደማ የመንገድ ፕሮጀክቶች የካፒታል በጀት እንደተያዘላቸው ለፓርላማ በቀረበው የበጀት ረቂቅ ሰነድ ላይ ሰፍሯል። ለእነዚህ መሰል የመንገድ ፕሮጀክቶች የተመደበው የገንዘብ መጠን “አነስተኛ መሆን”፤ ዛሬ ሰኞ ሰኔ 19፤ 2015 በፓርላማ በተካሄደ የህዝብ ይፋዊ ውይይት ላይ አነጋግሯል። በውይይቱ ላይ የተገኙ ተሳታፊዎች፤ ተወክለው በመጡበት አካባቢ የሚገኙ የመንገድ ፕሮጀክቶች የተያዘላቸውን የገንዘብ መጠን በመጥቀስ ቅሬታቸውን አሰምተዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11273/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ብርቱካን ሚደቅሳ የስራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን አስታወቁ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአፈ ጉባኤ ጽህፈት ቤት የስራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን አስታወቁ። ለአራት ዓመታት ከስድት ወራት ምርጫ ቦርድን የመሩት ብርቱካን ከመጪው ነሐሴ 1፤ 2015 ጀምሮ ስራ ለመልቀቅ መወሰናቸውን መወሰናቸውን የገለጹት በተረጋገጠ የፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ነው።
ብርቱካን ከዋና ሰብሳቢነታቸው የሚለቅቁት ጤናቸውን “በሚገባ ለመጠበቅ የረጅም ጊዜ እረፍት” ስለሚያስፈልጋቸው እንደሆነ በዚሁ የፌስ ቡክ መልዕክታቸው ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አቅራቢነት ብሔራዊ የምርጫ ቦርድን እንዲመሩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ህዳር 13፤ 2011 የተሾሙት ብርቱካን፤ መልቀቂያቸውን ለፓርላማ አፈ ጉባኤ ጽህፈት ቤት ያስገቡት ሰኔ 5፤ 2015 መሆኑን በመልዕክታቸው ጠቅሰዋል።
ዋና ሰብሳቢዋ ስራ ሲጀምሩ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን “ተዓማኒ እና ራሱን ችሎ ምርጫን ማከናወን የሚችል ተቋም” የማድረግ ህልም እንደነበራቸው ስንብታቸውን ይፋ ባደረጉበት አጭር ጽሁፍ ገልጸዋል። ብርቱካን የምርጫ ቦርድን ዋና ሰብሳቢነት ከተረከቡ በኋላ፤ ተቋሙ ስድስተኛውን አጠቃላይ አገራዊ ምርጫ እና በደቡብ ክልል ሶስት ህዝበ ውሳኔዎችን አካሂዷል። ብርቱካን በስንብት ጹሁፋቸው ምርጫ ቦርድን “ተዓማኒነት በማሻሻል ረገድ፣ በተቻለ አቅምም የፓለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴዎች ለማገዝ ባደረግነው ጥረት ስኬታማ ነን ብዬ አምናለሁ” ሲሉ ጽፈዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ኢትዮ ቴሌኮም ባለፉት አምስት ዓመታት ከ31 ቢሊየን ብር በላይ የውጭ ምንዛሪ ኪሳራ እንደገጠመው አስታወቀ
ኢትዮ ቴሌኮም ባለፉት አምስት ዓመታት ከ31 ቢሊየን ብር በላይ የውጭ ምንዛሪ ኪሳራ እንደገጠመው የተቋሙ ዋና የፋይናንስ ስራ አስፈጻሚ አቶ አሰግድ አየለ ተናገሩ። የኩባንያው ትርፍ ባለፉት አምስት ዓመታት ከ12 በመቶ ወደ 22 በመቶ ቢደርስም፤ የዋጋ ንረት እና የውጭ ምንዛሪ ኪሳራ እንደሚፈታተኑት አቶ አሰግድ ገልጸዋል።
የተቋሙ ዋና የፋይናንስ ስራ አስፈጻሚ ይህን ያሉት፤ የኢትዮ ቴሌኮም ከፍተኛ አመራሮች የኩባንያውን የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ዛሬ አርብ ሰኔ 16፤ 2015 ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለመንግስት የልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረቡበት ወቅት ነው። በዛሬው የፓርላማ ቋሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩን ጨምሮ የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
ዋና አስራ አስፈጻሚዋ የሚመሩት ተቋም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ዘጠኝ ወራት 52.7 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱን እና 103 ሚሊዮን ዶላር ማስገባቱን ለቋሚ ኮሚቴ አባላቱ ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ከሁለት ዓመታት ገደማ በፊት ስራ ያስጀመረው “ቴሌ ብር” የተሰኘው የተሰኘውን የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ደንበኞች ቁጥር ከ30.5 ሚሊዮን በላይ መድረሱንም አስታውቀዋል። በዚህ አገልግሎት ባለፈው ዘጠኝ ወራት ብቻ 394.7 ቢሊዮን ብር ዝውውር መፈጸሙንም ተናግረዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11265/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ጋር በትላንትናው ዕለት ባደረገው ቃለ ምልልስ ከተነሱ ጥያቄዎች መካከል፤ የከተማይቱ አስተዳደር “የኑሮ ውድነት ጫና ባለበት የቤት ግብር ማሻሻያ ማድረጉ ትክክለኛ ጊዜው ነው ወይ?” የሚለው ይገኝበታል። ከንቲባ አዳነች ለዚህ ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ የግብር ተመን ማሻሻያው በራሱ የኑሮ ውድነትን ያባብሳል ብሎ ለማመን እንደሚያስቸግራቸው ገልጸዋል።
“እንዴት ነው የአዲስ አበባን ህዝብ እቺን ግብር በማሻሻል የኑሮ ውድነትን ጫና የምናመጣበት? ዝቅተኛ ገቢ ያለው ላይ አይደለም ይሄ ሁኔታ እየታየ ያለው። የተሻለ ገቢ ያለው ነው፤ የግብር አከፋፈሉን እየተቃወመው ያለው። ሚዲያም የመክፈል አቅም ያለው እርሱ ነው። ዝቅተኛው ማህበረሰብ አይደለም” ሲሉ ሲሉ “በርካታ የማህበረሰብ ክፍል” የግብር ተመኑ ላይ ተቃውሞ እንደሌለው ተናግረዋል።
ይህን ሊንክ ተጭነው ዝርዝሩን ያንብቡ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11260/
2 485
የራያ አካባቢዎች በጀት ለትግራይ ክልል እንዳይተላለፍ የሚጠይቅ የ145ሺህ ሰዎች ፊርማ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀረበ
የፌደራል መንግስት ለሚቀጥለው በጀት ዓመት “በራያ እና አካባቢው ለሚገኙ መዋቅሮች የሚመድበው ድጎማ”፤ ወደ ትግራይ ክልል እንዳይተላለፍ የቀረበን ጥያቄ የደገፉ የ145 ሺህ ሰዎች ገደማ ፊርማ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀረበ። በአካባቢው የሚገኙ ሶስት ወረዳዎች እና አንድ የከተማ አስተዳደርን የተመለከተው ጥያቄ የቀረበለት የፌዴሬሽን ምክር ቤት፤ ጉዳዩን ለመመልከት ቃል ገብቷል ተብሏል።
ይህንን ጥያቄ የሚደግፉ ሰዎችን ፊርማ አሰባስቦ ከትላንት በስቲያ ሰኞ ሰኔ 12፤ 2015 ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ያስረከበው፤ የወሎ ራያ አማራ ማንነትና ወሰን አስመላሽ ኮሚቴ ነው። ለፌዴሬሽን ምክር ቤት በደብዳቤ የቀረበው ይህ ጥያቄ፤ የሰሜኑ ጦርነት ከመቀስቀሱ በፊት በትግራይ ክልል ደቡባዊ ዞን ስር የነበሩ አራት መዋቅሮችን የተመለከተ ነው።
እነዚህ መዋቅሮች በትግራይ ክልል ስር በነበሩበት ወቅት “የማንነት ጥያቄ ይነሳባቸው” እንደነበር የጠቀሰው ደብዳቤው፤ ሆኖም የሰሜን ኢትዮጵያውን ጦርነት ተከትሎ የአካባቢው ህዝብ “ራሱን በራሱ ለማስተዳደር” መቻሉን አትቷል። ጥያቄውን ያቀረቡት አመልካቾች፤ የአካባቢው ህዝብ “ከፌደራል መንግስቱ ሊያገኝ ይገባ የነበረው በጀት” የሚላከው “በትግራይ ክልል በኩል ነው” በመባሉ ምክንያት እስካሁን የገንዘብ ድጎማ አለማግኘታቸውን ያስረዳል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11252/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
በ2016 የአዳዲስ ሰራተኛ ቅጥር የማይደረገው፤ የሀገሪቱን ሲቪል ሰርቪስ ለማሻሻል ታስቦ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር አስታወቀ
በፌደራል መንግስት በኩል 2016 በጀት ዓመት የአዳዲስ ሰራተኛ ቅጥር እንዳይኖር የተደረገው፤ የሀገሪቱን ሲቪል ሰርቪስ ለማሻሻል በመታሰቡ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር ዲኤታው ዶ/ር እዮብ ተካልኝ ተናገሩ። መንግስት በጀት ሲያዘጋጅ፤ “የግሉን ዘርፍ በማነቃቃት” እና “ስራ ፈጠራን ማዕከል ባደረገ” መልኩ መሆኑንም ሚኒስትር ዲኤታው ገልጸዋል።
ከሁለት ሳምንት በፊት ሰኔ 1፤ 2015 በፓርላማ በተካሄደ መደበኛ ስብሰባ፤ የ2016 በጀት ዝግጅት የተደረገው የአዳዲስ ሰራተኛ ቅጥር እንደማይኖር ታሳቢ ተደርጎ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ተናግረው ነበር። ከዚህ የሚኒስትሩ ንግግር በኋላ አነጋጋሪ ሆኖ የሰነበተው የአዳዲስ ሰራተኞች ቅጥር ጉዳይ፤ ዛሬ ረቡዕ ሰኔ 14፤ 2015 በፓርላማ በተካሄደ የአስረጂ መድረክ ስብሰባ ላይም በድጋሚ ተነስቷል።
የፌዴራል መንግስት የ2016 የበጀት ረቂቅ አዋጅን በተመለከተ የገንዘብ ሚኒስቴር ኃላፊዎችን ወደ ፓርላማ በመጋበዝ የዛሬውን የአስረጂ መድረክ ያዘጋጀው፤ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ነው። አቶ ወንድወሰን አድማሴ የተባሉ የዚሁ ቋሚ ኮሚቴ አባል፤ “እንደ ሀገር በርካታ ስራ አጥ ባለበት እና አሁን ያለውን ስራ አጥ መሸከም የሚችል የግል ዘርፍ ባልተፈጠረበት በአዋጅ አዲስ ቅጥር አይኖርም ብሎ ማወጁና ዝግ ማድረጉ ተገቢ ነው ወይ?” ሲሉ ጠይቀዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11248/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
የብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት መስሪያ ቤት፣ የፌደራል ፖሊስ እና የአየር ኃይልን የተመለከቱ ዘጋቢ እና ፊቸር ፊልሞች፤ በቅርብ ጊዜያት በተካሄዱ ተከታታይ መርሃ ግብሮች ተመርቀው ለዕይታ መብቃታቸው የአንድ ሰሞን መነጋገሪያ ሆኖ ነበር። ከፍተኛ የመንግስት እና የጸጥታ ባለስልጣናት እንዲሁም ወታደራዊ እና የፖሊስ መኮንኖች በተገኙባቸው ስነ ስርዓቶች የተመረቁት እነዚህ ፊልሞች፤ በብሔራዊው፣ በክልል እና ለመንግስት ቅርበት ባላቸው የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ለሚሊዮኖች እንዲሰራጩ ተደርጓል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በትላንትናው ዕለት በተከፈተው ሀገር አቀፍ የጤና አውደ ርዕይ ማስመጀመሪያ ስነ ስርዓት ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ እነዚህን ፊልሞች በተመለከተ ጥቂት ነጥቦችን አንስተዋል። የደህንነት እና የጸጥታ ተቋማትን የተመለከቱ ፊልሞች ዝግጅት “ዝም ብሎ ድንገት የሆነ ጉዳይ አይደለም” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ የተደረገው ተቋሞቹን ለወጣቶች እና ለተማሪዎች “expose ለማድረግ” መሆኑን ገልጸዋል።
“ [ተቋሞቹ] ጋር የሚፈለግ ቴክኖሎጂ፤ እነርሱ ሳያውቁት በአንድ ሃይ ስኩል ወይም ኮሌጅ ሊኖር ይችላል። ለማገናኘት የምንችለው፤ አጥር አጥረን አትድረሱብን በማለት ሳይሆን ራሳቸውን expose እያደረጉ ሲሄዱ [ነው]። ተማሪዎች ‘ለካ እንደዚህ አይነት ነገር መከላከያ ይፈልጋል፤ ደህንነት ይፈልጋል። ለሀገር ደህንነት የሚያስፈልግ gadaget እኔ ልሰራው እችላለሁ’ እያሉ እንዲመራመሩ ስለሚያስችል ነው፤ በፊልም ትናንሽ ነገር ብልጭ ማድረግ የተጀመረው” ሲሉ አብይ የትላንቱን የመክፈቻ ስነ ስርዓት ለታደሙ የመንግስት ባለስልጣናት እና ሌሎች ተጋባዦች ተናግረዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
@EthiopiaInsiderNews
2 485
በፌዴሬሽን ምክር ቤት በጸደቀ ቀመር መሰረት በጀት ለወረዳዎች የሚያሰራጩት ሶስት ክልሎች መሆናቸው ተገለጸ
የፌደራል መንግስት ለክልሎች ከሚሰጠው የበጀት ድጋፍ ውስጥ፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤት የጸደቀውን የማከፋፈያ ቀመር ተከትለው ለወረዳዎች የድጎማ ገንዘብ የሚያሰራጩት 3 ክልሎች መሆናቸውን የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ አቶ አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ። አፈ ጉባኤው የድጎማ በጀት ለወረዳዎች “በትክክል ያሰራጫሉ” ያሏቸው ክልሎች፤ ደቡብ፣ ደቡብ ምዕራብ እና ሲዳማ ክልሎች ናቸው።
የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት፤ የፌደራል መንግስት ለክልሎች ድጎማ የሚሰጥበትን ቀመር የመወሰን ስልጣን የሰጠው ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው። አሁን በስራ ላይ ያለውን የድጎማ በጀት ማከፋፈያ ቀመር፤ የክልሎችን የህዝብ ብዛት፣ የዕድገት ደረጃ፣ የድህነት ሁኔታ፣ ገቢ የመሰብሰብ አቅም እና የወጪ ፍላጎትን ታሳቢ በማድረግ የተሰላ ነው።
የፌደራል መንግስት በ2016 በጀት ዓመት ለክልሎች የመደበው የበጀት ድጋፍ 214 ቢሊዮን ብር መሆኑን ከሰሞኑ ይፋ ተደርጓል። ለዘላቂ ልማት ግቦች ማስፈጸሚያ በመጪው የበጀት ዓመት ለክልሎች እንዲከፋፈል የተመደበው የገንዘብ መጠን 14 ቢሊዮን ብር መሆኑም ተገልጿል።
ከፌደራል መንግስት እና ከዓለም አቀፍ አካላት ለክልሎች የሚተላለፉ በጀቶች “ውስን ዓላማ ያላቸው” መሆኑ ትላንት ሰኞ ሰኔ 12 በተካሄደ የፌደሬሽን ምክር ቤት እና የክልሎች የጋራ የምክክር መድረክ ላይ ተነስቷል። በዚህ አይነት መልኩ ለክልሎች የሚከፋፈሉት በጀቶች ለትምህርት፣ ለጤና፣ ለውሃ እና ለመሳሰሉት አገልግሎቶች ሊውል እንደሚገባው በስብሰባው ላይ የጠቆሙት አፈ ጉባኤ አገኘሁ፤ እነዚህ በጀቶች “በስርዓቱ መሰረት፤ ለተባለለት ዓላማ ነው ወይ የሚሰራጩት?” ሲሉ ጠይቀዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11241/
2 485
#Wolaita #Referendum
በወላይታ ዞን በተካሄደው ህዝበ ውሳኔ፤ “በርካታ” መራጮች ስድስት ወራት ያልሞላው መታወቂያ ይዘው መገኘታቸውን ምርጫ ቦርድ አስታወቀ
በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን በዛሬው ዕለት በድጋሚ ሲካሄድ በዋለው ህዝበ ውሳኔ፤ “በርከት ያሉት” መራጮች የያዙት መታወቂያ ከተሰጠ ስድስት ወር ያልሞላው ሆኖ መገኘቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ። እነዚህ መራጮች በዞኑ ነዋሪ መሆናቸውን የሚያረጋግጡ ሌሎች አማራጮችን ተግባራዊ ማድረጉን ቦርዱ ገልጿል።
ምርጫ ቦርድ ይህንን ያለው የ“ደቡብ ኢትዮጵያ” ክልልን ለመመስረት በወላይታ ዞን እየተደረገ ያለውን ህዝበ ውሳኔ አስመልክቶ ዛሬ ሰኞ ሰኔ 12፤ 2015 ባወጣው መግለጫ ነው። ምርጫ ቦርድ በዚሁ መግለጫው፤ በህዝበ ውሳኔው ከተሳተፉ ድምጽ ሰጪዎች ውስጥ “በርከት ያሉት” ቦርዱ መራጮችን ለመመዝገብ ያስቀመጠውን መስፈርት የማያሟሉ ናቸው ብሏል።
በ2012 ዓ.ም የወጣው የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነምግባር አዋጅ፤ “ማንኛውም ሰው በምርጫ ክልሉ ቢያንስ ስድስት ወር የኖረ ከሆነ በመራጭነት ሊመዘገብ ይችላል” ሲል ደንግጓል። በዛሬው ህዝበ ውሳኔ ላይ ድምጻቸውን ለመስጠት የወጡ “በርካታ” የዞኑ ነዋሪዎች የያዙት መታወቂያ፤ “ከተሰጣቸው ስድስት ወር ያልሞላው” ሆኖ መገኘቱን ምርጫ ቦርድ በመግለጫው አመልክቷል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11229/
@EthiopiaInsiderNews
2 485
ኢትዮ ቴሌኮም የ994 የጥሪ ማዕከል አገልግሎቱን ለውስን ደንበኞች ብቻ ክፍት እንዲሆን አደረገ
ኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞቹ ከጥሪ ማዕከል ሰራተኞች ጋር የሚገናኙበትን አገልግሎት፤ በከፊል የሚያስቀር አሰራር ተግባራዊ ማድረግ ጀመረ። በአዲሱ አሰራር መሰረት ከድርጅቱ የጥሪ ማዕከል ሰራተኞች ጋር የሚገናኙ ተገልጋዮች፤ “የፕሪሚየም እና የተለዩ አገልግሎቶችን የሚፈልጉ” ተብለው የተለዩ ደንበኞች ብቻ እንደሚሆኑ ኢትዮ ቴሌኮም አስታውቋል።
መንግስታዊው የቴሌኮሚዩኒኬሽን አቅራቢ ድርጅት ከደንበኞቹ ለሚነሱ ጥያቄዎች ምላሽ ከሚሰጥባቸው አማራጮች ውስጥ አንዱ፤ ወደ ተቋሙ የጥሪ ማዕከል በ994 አጭር ቁጥር መወደል ነው። በዚህ ቁጥር ላይ የሚደውል ደንበኛ፤ በስልኩ ላይ በድምጽ የሚቀርብለትን አማራጮች በመከተል የሚፈልገውን የአገልግሎት አይነት እንዲያገኝ ይደረጋል። ደንበኞቹ ከተቋሙ አገልግሎቶች ጋር በተያያዘ ለሚያነሷቸው ጥያቄዎችም፤ በመስመር ላይ የሚጠብቁ የጥሪ ማዕከሉ ሰራተኞች ምላሽ ይሰጣሉ።
የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች ለጥሪ ማዕከሉ ከሚያቀርቧቸው ጥያቄዎች ውስጥ አብዛኛዎቹ “የፒን ቁጥርን ከመርሳት፣ የጥሪ ዝርዝርን ከመጠየቅ እንዲሁም ስልክ ቁጥር ከማስከፈት እና ከማዘጋት” ጋር የተያያዙ መሆናቸውን የተቋሙ ቺፍ ኮሚዩኒኬሽን ኦፊሰር አቶ መሳይ ውብሸት ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል። እነዚህ ጥያቄዎች እንዲመለሱላቸው የሚፈልጉ ደንበኞች መስመሩን ለረጅም ጊዜ ይዘው የሚቆዩ መሆናቸው እና ቁጥራቸውም በርካታ መሆኑ፤ ሌሎች “መሰረታዊ ጥያቄዎች የሚጠይቁ ሰዎች” ከጥሪ ማዕከሉ ሰራተኞች ጋር እንዳይገናኙ ማድረጉን አስረድተዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11224/
@EthiopiainsiderNews
2 485
#Tigray
በትግራይ ክልል 75 በመቶ ገደማ ተማሪዎች እስካሁንም ወደ ትምህርት ገበታ አለመመለሳቸው ተነገረ
በትግራይ ክልል በትምህርት ገበታቸው ይገኛሉ ተብሎ ከሚጠበቁ ተማሪዎች ውስጥ፤ እስካሁን ወደ ትምህርት ቤት የተመለሱት 23.3 በመቶው ብቻ መሆናቸውን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ካሉ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ግማሽ ገደማ የሚሆኑት፤ “በአማራ ታጣቂዎች እና በኤርትራ ሰራዊት” በተያዙ አካባቢዎች የሚገኙ በመሆናቸው እና ተፈናቃዮችን በማስጠለላቸው እስካሁን ትምህርት አለመጀመራቸውን ቢሮው ገልጿል።
የኮሮና ወረርሽኝ መከሰቱን ተከትሎ በ2012 ዓ.ም ስራ ያቋረጡት በትግራይ ክልል የሚገኙ ትምህርት ቤቶች፤ በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት መነሳት ሳቢያ በተሟላ ሁኔታ ትምህርት ሳይጀምሩ ለሶስት ዓመታት ገደማ እንደተዘጉ ቀጥለዋል። የትግራይ ክልል ትምህርት ቢሮ እነዚህ ትምህርት ቤቶች በድጋሚ ተከፍተው መደበኛ ትምህርት እንዲጀምሩ ያደረገው ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ ነበር።
በትግራይ ክልል ከተጀመረ 50 ገደማ ቀናት ባሳለፈው የመማር ማስተማር ሂደት፤ ትምህርት ቤቶቹ ከመደበኛው የትምህርት አሰጣጥ በተለየ መልኩ የተፋጠነ የትምህርት ስርዓትን (accelerated learning program) እንዲከተሉ መደረጉን የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ኪሮስ ጉዕሽ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል። ይህ አሰራር ተማሪዎች በአንድ ዓመት ሁለት የክፍል ደረጃዎችን እንዲያጠናቅቁ የሚያደርግ መሆኑንም አስረድተዋል።
ለዝርዝሩ፦ https://ethiopiainsider.com/2023/11212/
@EthiopiaInsiderNews
