ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Ir al canal en Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Mostrar más637
Suscriptores
Sin datos24 horas
-37 días
-1230 días
Archivo de publicaciones
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ለልበ_አምላክ_ለእሴይ_ልጅ ለእስራኤል ንጉሥ ለነቢዩ #ለቅዱስ_ዳዊት_ለዕረፍት መታሰቢያ በዓል፣ ለከበረ ተጋዳይ አባት ለገዳማዊ #ለአባ_ጢሞቴዎስ_ዕረፍት በዓል፣ ለቅዱሳን #ለአባ_ሳሙኤል_ለአባ ስምዖን_ለአባ ገብርኤል ለዕረፍታቸው መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱሳን_ከይስሐቅ_ከአባ_አሞን፣ #ከአባ_አቦሊ_ከመቃርስ_ከአይተለአትካ_ከፊልጦስ_ከመርቆሬዎስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ልበ_አምላክ_ነቢዩ_ንጉሥ_ቅዱስ_ዳዊት፦ ይህም ንጉሥ ዳዊት በእግዚአብሔር ፊት መልካም ጒዞን የተጓዘ ከእራኤልም ነገሥታት ሁሉ እውነተኛ ፍርድን ያደረገ ነው እርሱም አገሩ ቤተልሔም የሆነች ከይሁዳ ነገድ ነው ሳኦልም የእግዚአብሔር ትእዛዝ በተላለፈ ጊዜ ለእስራኤል ንጉሥ ይሆን ዘንድ መረጠው ነቢይ ሳሙኤልንም ቅብዐ መንግሥትን የእሴይን ልጅ ይቀባ ዘንድ ላከው። ሳሙኤልም ታላቁን ኤልያብን ተመለከተ መልኩ ያማረ አካሉም የጸና ነበርና እግዚአብሔር ግን አልመረጠውም። "የኤልያብ ፊቱን አትይ የመልኩንም ማማር አትመልከት እግዚአብሔር ሰው እንደሚያይ የሚያይ አይደለምና" አለው እንጂ "ሰው መልክ ያያል እግዚአብሔር ግን ልብን" ያያል።
❤ ከእሴይ ከሰባቱ ልጆች በኋላ ነቢይ ሳሙኤል ዳዊትን በእስራኤል ልጆች ላይ ይነግሥ ዘንድ ቀባው እግዚአብሔርም በሥራው ሁሉ ከእርሱ ጋር ሆነ። ከልቡናው ንጽሕና ከየዋህነቱም ብዛት የተነሣ ጠላቱን ሳኦልን ብዙ ጊዜ ሲያገኘው በላዩ ምንም ምን ክፉ ነገር አላደረገበትም። በአንዲትም ዕለት ሳኦል ከእስራኤል ሁሉ የተመረጡ ሦስት ሺህ ሰዎችን ይዞ ዳዊትን ከሰዎቹ ጋር ይፈልገው ዘንድ ዋሊያዎች ወደሚታደኑበት ሔዶ በጐዳና አጠገብ ያሉ ዘላኖችም ወደሚሠማሩበት ደረሰ በዚያም ዋሻ ነበር ሳኦልም ይናፈስ ዘንድ ወደዚያች ዋሻ ውስጥ ተቀምጠው ነበር። ዳዊትም ተነሥቶ ቀስ ብሎ ከልብሱ ጫፍ ቆረጠ። በሁለተኛም ጊዜ በድንክ አልጋ ላይ ተኝቶ ወዳለበት ከአቢሳ ጋር ገብቶ ከራስጌው ጦሩንና ውኃ ያለበትን ረዋቱን ይዞ ተመልሶ ሔደ ክፉ ነገርንም አላደረገበትም ሰዎቹም ጠላትህ ሳኦልን ግደለው በአሉት ጊዜ እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጄን ልዘረጋ አይገባኝም ብሎ መለሰላቸው።
❤ ስለ ሳኦልም መገደል አንድ ሰው በነገረው ጊዜ ዳዊትም "ያንን ሰው ማን ገደለው" አለው ሰውዬውም "እኔ ገደልሁት" አለው ዳዊትም እጅግ አዘነ ልብሱንም ቀደደ ያንንም ሳኦልን እኔ ገደልሁት ያለውን ሰው ገደለው። እግዚአብሔር በዚህ በጻድቅ ዳዊት ልብ ብዙ ትሩፋትን፣ ትሕትናን፣ የዋህነትን፣ ቅንነትን፣ ትዕግሥትን ፍቅርን አከማቸ ክብር ያለው ንጉሥ ሲሆን ራሱን ውሻ ትል እንስሳም አድርጎ ይጠራል ስለዚህም ከምድር ነገሥታት ሁሉ ከፍ ከፍ አደረገው እንዲህም ብሎ አመሰገነው "የእሴይን ልጅ ዳዊትን እንደ ልቤ ሆኖ አገኘሁት ፈቃዴን ሁሉ የሚያደርግ ታማኝ ሰው ነው"።
❤ እግዚአብሔርም የእስራኤልን ልጆች ኢየሩሳሌምንም ስለ ዳዊት ደግነት ብዙ ጊዜ ጠበቃቸው እርሱ ካለፈ በኋላም በነቢያቶቹ አንደበት አከበረው ነገሥታትንም ከእርሱ ዘር አደረገ። እርሱም በሁሉ ዓለም የታወቀ የመዝሙሩን መጽሐፍ ደረሰ ይኸውም በሰይጣናት ላይ ጋሻና ጦር የሆነ መልካም ቃልንም የተመላ በሰማይና በምድርም ያሉ በእርሱ እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት ነው።
❤ ቅዱስ ዳዊትም ፊቱ እንደ ሮማን ቀይ ነው ቁመቱም መካከለኛ የሆነ አካሉም የጸና ብርቱ ነበር ታናሽ ብላቴናም ሁኖ ሳለ እርሱ የአባቱን በጎች ሲጠብቅ አንበሳ ወይም ተኵላ መጥቶ ከመንጋው ውስጥ በግ ነጥቆ በሚወስድ ጊዜ ተከትሎ ገድሎ ከአፉ ያስጥለው ነበር ሊጣላውም ቢነሣበት ጒረሮውን ይዞ ይሠነጥቅዋል። ከፍልስጥዔማውያንም ጋራ ሰልፍ በሆነ ጊዜ ብርቱ ሰው ስሙ ጎልያድ የሚባል ከጌት ሰዎች የተወለደ ቁመቱ ስድስት ክንድ ከስንዝር የሆነ ከኢሎፍላውያን ሰፈር ወጣ። በራሱ ላይ የነሐስ በርቦርቴ ደፍቷል የነሐስ ጽሩርም ለብሷል በርሱ ላይ ያለ የብረቱና የነሐሱ ሁሉ ሚዛኑ አምስት ሽህ ወቄት ነበር። በእግሮቹ ባቶችም ላይ የነሐስ ሰናፊል ታጥቆ ነበር በጫንቃውም መካከል የነሐስ እባቦች ነበሩ። የጦሩም ዛቢያ እንደ ሸማኔ መጠቅለያ ሁኖ በላዩ ሽቦ ነበረበት የጦሩም ብረት መጠን ስድስት መቶ ወቄት ነበር ጋሻ ጃግሬውም በፊቱ ይሔድ ነበር።
❤ ቁሞም ወደ እስራኤል ሰፈር ይጮህ ነበር "ከእኛ ጋር ትዋጉ ለምን ወጣችሁ እኔ የኤሎፍላውያን ወገን ነኝ ከእናንተ የሳኦል ባሮች አይደላችሁምን ከእናንተ አንድ ሰው መርጣችሁ ወእኔ ይውረድ ከእኔ ጋር መዋጋት ችሎ ቢገድለኝ ባሮች እንሆናችኋለን እኔ ከርሱ ጋራ ችዬ ብገድለው እናንተ ባሮች ሁናችሁ ትገዙልናላችሁ" አላቸው። ያም ኢሎፍላዊ ለወገኖቹ "ዛሬ በዚች ቀን አንድ ሰው ስጡኝና ሁለታችን ለብቻችን እንደዋጋ ብሎ የእስራኤልን አርበኞች እነሆ ተገዳደርኳቸው" አላቸው። እስራኤል ሁሉና ሳኦልም ይህን የኢሎፍላዊውን ቃል በሰሙ ጊዜ ደነገጡ እጅግም ፈሩ የእራኤልንም ወገኖች እንዲህ እየተገዳደራቸውና እየተመካባቸው አርባ ቀኖች ያህል ኖረ ከእስራኤልም ወገን ወደርሱ ይወጣ ዘንድ የደፈረ የለም።
❤ በዚያም ወራት ቅዱስ ዳዊት ወንድሞቹን ሊጐበኝ ወጣ ያንንም የኢሎፍሊ ወገን የሆነ ሰው የእግዚአብሔር ወገኖችን ሲገዳደራቸው በአየው ጊዜ አምላካዊ ቅናትን ቀና ሳኦልንም እንዲህ አለው "እኔ ሔጄ ይህን ያልተገረዘ ቈላፍ ገድዬ ዛሬ ከእስራኤል ሽሙጥን አርቃለሁ። ሕያው የሚሆን የእግዚአብሔርን አርበኞች ይገዳደር ዘንድ ይህ ቈላፍ ቁም ነገር ነው ከድብ አፍና ከአንበሳ አፍ ያዳነኝ እርሱ እግዚአብሔር ከዚህ ካልተገረዘ ኢሎፍላዊ እጅ ያድነኛል"። ሳኦል "ሒድ እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር ይሁን" አለው። ዳዊትም ወንጭፋን በእጁ ያዘ ከወንዝ መካከልም ሦስት ደንጊያዎችን መረጠና ወደዚያ ኢሎፍላዊ ሔደ። ጎልያድም ዳዊትን በአየው ጊዜ ናቀው እንዲህም አለው "ደንጊያና በትር ይዘህ ወደኔ ትመጣ ዘንድ እኔ ውሻ ነኝን" ዳዊትም "ከውሻ የምትሻል አይደለህም ከውሻ ትብሳለህ እንጂ" ቈላፍ ጎልያድም ዳዊትን በጣዖቶቹ ስም ረገመው።
❤ ያም ኢሎፍላዊ ዳዊትን "ወደ እኔ ና ሥጋህን ለሰማይ ወፎችና ለዱር አራዊት እሰጣሁ" አለው ዳዊትም ያንኑ ኢሎፍላዊ "አንተ ጦር ሰይፍና ጋሻ ይዘህ ወደኔ ትመጣለህ እኔ ግን አሸናፊ በሚሆን በእግዚአብሔር ስም ወዳንተ እመጣለሁ። ዛሬ የእስራኤልን አርበኞች የተገዳደርክ አንተን ዛሬ እግዚአብሔር በእጄ ይጥልሃል እገድልህምአለሁ ራስህንም እቆርጣለሁ የኢሎፍላውያን ሠራዊት ሬሳና ያንተን ሬሳ ዛሬ ለዱር አራዊትና ለሰማይ ወፎች እሰጣለሁ ሰዎችም ሁሉ እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር እንዳለ ያውቃሉ ሠራዊትም ሁሉ እግዚአብሔር በጦርና በሰይፍ የሚያድን እንዳይደለ ያውቃሉ ድል የእግዚአብሔር ገንዘብ ነውና"።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፳፪ (22) ቀን።
❤ እንኳን #እመቤታችንን_ቅድስት_ድንግል_ማርያምን የከበረ_ሊቀ መላእክት_ቅዱስ_ገብርኤል በአበሠራት መሠረት #ቅዱስ_ደቅስዮስ_በዓል_ላከበረት_ለብሥራት ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና የእመቤታችንን ተአምረ ማርያም መጽሐፍ ለጻፈው #ለቅዱስ_ደቅስዮስ_ለዕረፍት መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰ። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከከበረ መልአክ ከመላእክት አለቃ #ከቅዱስ_ገብርኤል ከበዓሉ መታሰቢያ ዳህና በሚባል አገርም ቤተ ክርስቲያኑ ከተሠራችበትና ከከበረችበት ተአምራትም ካሳየበትና ከአገር ኤጲስቆስ #አባ_አርኬላዎስ ምስክር ከሆነበት፣ ከእስክድርያ አገር ሠላሳ ስድስተኛ ጳጳስ ከከበረ ከአባት #ከአባ_አንስጣስዮስ ዕረፍት ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ደቅስዮስ_በዓለ_ብሥራትን_ማክበሩ፦ በዓልን የማክበሩ ምክንያትም እንዲህ ሆነ ይህ ኤጲስቆጶስ ደቅስዮስ ከፍቅሩ ጽናት የተነሣ አስቦ በመትጋት የተአምራቷን መጽሐፍ ሰብስቦ አዘጋጀላት። የምእመናን ክብር የሆነች አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ማርያምም ተገለጸችለትና መጽሐፋን በእጅዋ አንሥታ ይዛ "ወዳጄ ደቅስዮስ ሆይ ይህን መጽሐፍ ስለ ጻፍክልኝ ባንተ ደስ አለኝ አመሰገንኩህም" አለችው ከዚህም በኋላ ከእርሱ ተሠወረች። ቅዱስ ደቀስዮስም ይህን ነገር በራይ ባየ ጊዜ ክብርት ድንግል እመቤታችን ማርያምን ከመውደዱ የተነሣ ፈጽሞ ደስ አለው እርሷንም ስለ ወደደ ፍቅርዋ እንደ እሳት አቃጠለው የሷን ክብር አብዝቶ ይጨምር ዘንድ ምን እንደሚያደርግ የሚሠራውን ያስብ ጀመር።
❤ ከዚህም በኋላ በዚያን ጊዜ ጾም ስለነበር ሰዎች አስቀድመው ሊአከብሩት ያልተቻላቸውን የመላእክት አለቃ የከበረ ቅዱስ ገብርኤል ባበሠራት ቀን በዓሏን አከበረ። እርሱም የከበረ የሚሆን የልደትን በዓል ከማክበር አስቀድሞ በስምንት ቀን አደረገ ይኸውም ታኅሣሥ በባተ በሃያ ሁለት ቀን ነው በጵጵስናውም ዘመን ተሠርታ እስከዚች ቀን ጸንታ ትኖራለች። ሰዎችም በዓሉን በአከበሩት ጊዜ ፈጽሞ ደስ አላቸው።
❤ ደግነትን ምሕረትን ቸርነትን የምትወድ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ማርያም በእጅዋ የከበረ ልብስ ይዛ ዳግመኛ ተገለጸችለትና "አገልጋዬ የሆንክ ወዳጄ ደቅስዮስ ሆይ በእውነት አመሰገንኩህ በአንተም ደስ አለኝ ሥራህንም ወደድሁ። በእኔም ደስ እንዳለህና የከበረ መልአክ ገብርኤል እኔን በአበሠረበት ቀን በዓሌን ስለአከበርክ ሰውንም ሁሉ ስለ እኔ ደስ ስለአሰኘህ እኔም ዋጋህን ልሰጥህ አንተ በዚህ ዓለም እንዳከበርከኝም በሰው ሁሉ ፊት አከብርህ ዘንድ እወዳለሁ" አለችው። እሷም "ትለብስ ዘንድ ይችን ልብስ እነሆ አመጣሁልህ በላዩም ትቀመጥ ዘንድ ይህን ወንበር አመጣሁልህ ከሰው ወገን አንድ ስንኳ ይህችን ልብስ ሊለብሳት በዚህም ወንበር ላይ ሊቀመጥ የሚቻለው የለም። ይህን ነገሬን የሚተላለፍ ቢኖር እኔ እበቀለዋለሁ" አለችው ይህንንም ተናግራ ከእርሱ ተሠወረች።
❤ ከዚህም በኋላ ታኅሣሥ22 ቀን በዐረፈ ጊዜ ሌላ ኤጲስቆጶስ ተሾመ ያቺንም ልብስ ለበሳት በወንበሩም ላይ ተቀመጠ ወዲያውኑ ከወንበሩ ላይ ወድቆ ሞተ ይህንንም ያዩ ከእመቤታችን ማርያም ተአምር የተነሣ አደነቁ እጅግም ፈርተው እመቤታችንን አከበሩዋት ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ለእርሱም ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ቀን የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ #የቅዱስ_ገብርኤል_የበዓሉ_መታሰቢያ ዳህና በሚባል አገርም ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራችበት ተአምራትም ያሳየበትና በዚች ቀን ቤተ ክርስቲያኒቱ የከበረችበት ነው የዚያች አገር ኤጲስቆጶስ አርኬላዎስ ምስክር የሆነበት ነው።
❤ ይህም መልአክ ስለ ወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ምሥጢር የታመነ ሆኖ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተላከ "የደስታ መገኛ ደስ ይበልሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው አንቺም ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ" አላት።
❤ ስለ መጥምቁ ዮሐንስ መወለድም ካህኑን ዘካርያስን ያበሠረው እርሱ ነው ይህ መልአክ እጅግ የከበረ የተመረጠ ገናና የሆነ ነውና ስለ እኛ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ዘንድ ልባችንን አንጽተን ወደዚህ የከበረ መልአክ እየለመንን መታሰቢያውን ልናደርግ ይገባል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በከበረ መልአክ በቅዱስ ገብርኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱ ረድኤቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ22 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_እብል_ለደስቅዮስ_ባሕርያ። ኤጺስቆጶስ ዘሀገረ ጥልጥልያ። በእንተ ዘጸሐፈ ላቲ ትምእምርተ ዜናሃ ወጸጋ ዕበያ። እንተ ወሀበቶ ወላዲተ አምላክ ማርያ። ልብሰ ሰማያዊት እስከ ዮም ነያ"። አርከ ሥሉስ (አርኬ) የታኅሣሥ22።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ማኅሌቱ_ምስባክ፦ "በቅድመ መላእክቲከ እዜምር ለከ። ወእሰግድ ውስተ ጽርሐ መቅደስከ። ወእገኒ ለስመከ። መዝ 137፥1-2። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ1፥26-39።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ። ወትሠይም(ሚ)ዮሙ መላእክተ በኵሉ ምድር። ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ"። መዝ 44፥16-17። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ጢሞ 1፥8-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 4፥9-18 እና የሐዋ ሥራ 12፥7-12። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥39-57። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች የማርያም ቅዳሴ ነው፡፡ መልካም የብሥራት ቅዱስ ገብርኤል በዓል፣ የቅዱስ ደስቅዮስ የዕረፍት በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፳፩ (21) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለአንዱ የስሙ ትርጓሜ የመረጋጋት ልጅ ለሆነ #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_በርናባስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱና #ለእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም ለወራዊ መታሰቢያ በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በዚች ቀን በተጨማሪ ከሚታሰቡ፦ ከአባ ይስሐቅ ከዕረፍቱ መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ቀን #የእመቤታችን_አምላክን_የወለደች_የቅድስት_ድንግል_ማርያም የበዓልዋ መታሰቢያ ነው። እርሷ የባህርያች መመኪያ ናትና በእርሷ በእናቱ አማላጅነት ጌታችን ይጠብቀንና ያድነን ዘንድ መታሰቢያዋን እያደረግን ወደርሷ እንለምን ዘንድ ይገባል። እርሷን ሕይወትን መድኃኒትን አድርጎ ለሰጠን እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_በርባስ፦ ይህም ቅዱስ ሐዋርያ ከሊዊ ነገድ የሆነ አገሩ ቆጵሮስ ነው የቀድሞ ስሙ ዮሴፍ ነው ክብር ይግባውና ጌታችን ከመከራው በፊት ይሰብኩ ዘንድ ከላካቸው ከሰባ ሁለት አርድእት ጋር መረጠው ስሙንም በርናባስ ብሎ ጠራው። ከጌታ ዕርገትም በኋላ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ እርሱም ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ተቀብሎ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተማረ። የእርሻ ቦታ ነበረውና ሽጦ ዋጋውን አምጥቶ ከሐዋርያት እግር በታች አኖረው።
❤ ቅዱስ ጳውሎስም በጌታችን አምኖ ወደ ሐዋርያት በመጣ ጊዜ ክብር ይግባውና ለክርስቶስ እርሱ ደቀ መዝሙሩ እንደሆነ ሐዋርያት አላመኑትም ነበር። ይህ በርናባስ ጌታችን በመንገድ እንደ ተገለጸለትና እንደአነጋገረው እርሱም በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በደማስቆ እንደ አስተማረ ነገራቸው። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔርን ሥራ ሲሠሩ ሲጾሙ ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ "ሳውልና በርናባስን እኔ እነርሱን ለመረጥኩት ሥራ ለዩልኝ" አላቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ጹመው ጸልየው እጆቻቸውን በራሳቸው ላይ ጭነው ሾሟቸው። ከመንፈስ ቅዱስም ተሹመው ወደ ሴሌውቅያ ወረዱ ከዚያም ወደ ቆጵሮስ ሔዱ የእግዚአብሔርንም ቃል በአገሩ ሁሉ አስተማሩ። ልስጥራን በተባለ አገርም ልምሾ የነበረውን ሰው በአዳኑት ጊዜ የልስጥራን ሰዎች መሥዋዕትን ሊሠዉላቸው ወደዱ። ሐዋርያት ቅዱስ ጳውሎስና በርናባስም በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀድው ወደ ሕዝቡ ሔዱ ድምፃቸውንም ከፍ አድርገው እንዲህ አሏቸው "እናንት ሰዎች ይህ ነገር ምንድን ነው እኛማ እንደናንተ የምንሞት ሰዎች አይደለንምን ይህን ከንቱ ነገር ትታችሁ ሰማይና ምድርን ባሕርንም በውስጧቸው ያለውን ሁሉ ወደ ፈጠረ ወሕያው እግዚአብሔር ትመለሱ ዘንድ እናስተምራችኋለን" አሏቸው እንዲህም ብለው መሠዋትን በጭንቅ አስተዋቸው።
❤ ከዚያም ብዙ አገሮችን ከአስተማሩ በኋላ ቅዱስ በርናባስ ከቅዱስ ጳውሎስ ተለይቶ ቅዱስ ማርቆስን ይዞ ወደ ቆጵሮስ ሔደ በዚያም አስተማረ ብዙዎችን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን መለሳቸውና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።
❤ በቆጵሮስ አገር የሚኖሩ አይሁድም ቀኑበት በመኳንንትም ዘንድ ወነጀሉት በእግር ብረትም አሥረው ጽኑ ግርፋትን ገረፉት ከዚህም በኋላ በደንጊያ ወገሩት ዳግመኛም ወስደው ከእሳት ጨመሩት ምስክርነቱንም ፈጸመ። ቅዱስ ማርቆስም ከርሱ ጋር አለ ግን እግዚአብሔር ጠብቆ አተረፈው። እርሱም ቅዱስ በርናባስን ከእሳት ውስጥ አወጣው ሥጋውንም እሳት ከቶ አልነካውም በአማሩ ልብሶችም ገንዘውና ተሸክሞ ወስዶ ከቆጵሮስ ከተማ ውጭ በዋሻ ውስጥ አኖረው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያ ቅዱስ በርናባስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 21 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለበርናባስ በማእሠረ ጌጋይ ዘኢትእኅዘ። #ከመ_መንፈስ_ቅዱስ_አዘዘ። ሥርዓተ ፈጺሞ ወመልእክተ ቃለ አዚዘ። በዋዕየ እሳት ሶበ እምዓለም ግዕዘ። ለወንጌላዊ ማርቆስ በእዱ ተገንዘ"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ) የታኅሣሥ 21።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ማኅሌት_ምስባክ፦ "ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ። ወውስተ ፀሐይ ሤመ ጽላሎቶ"። መዝ 18፥4-5። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወትቀውም ንግሥት በየማንከ። በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኊብርት። ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአጽምዒ ዕዝነኪ"። መዝ 44፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 2፥1-14፣ ቈላ 4፥1-ፍ.ም ወይም ይሁ 1፥17-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 11፥23-ፍ.ም የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥17-34። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ በርናባስ የዕረፍት በዓልና የነቢያት የገና (ጾም) ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለክብር_ባለቤት_ለጌታችን_ለአምላካች_ለመድኃኒታችን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ ለንዑስ በዓል ለአንዱ #ለብርሃን እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፮ "አቅዲሙ ነገረ በኦሪት አቅዲሙ ነገረ በኦሪት ከመ #ይመጽእ_ወልድ_በስብሐት ዘይዜንዋ ለጽዮን ቃለ ትፍሥሕት ወካዕበ ይቤ #በአፈ_ዳዊት ቡሩክ ዘይመጽእ #በስመ_እግዚአብሔር_ብርሃን_ዘመጽአ_ውስተ_ዓለም_ዘያበርህ_ላዕለ_ጻድቃን መርዓዊሃ #ለቤተ_ክርስቲያን ይርዳእ ዘተኃጒለ ያስተጋብእ ዝርዋነ ኃቤነ"። ትርጉም፦ ዳግመኛ #በዳዊት_አፍ እንደነገረ #በእግዚአብሔር_ስም_የሚመጣ_እርሱ_ምስጉን ነው፣ ለጽዮን የደስታን ቃል የሚነግራት ወልድ በክብር እንደሚመጣ አስቀድሞ በኦሪት ተናገረ፣ #ወደ_ዓለም_የመጣ_ብርሃን_በጻድቃን ላይ የሚያበራ #የቤተ_ክርስቲያን_ሙሽራ የጠፋውን ሊፈልግ የተበተነውን ሊሰበስብ ወደ እኛ መጣ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ "ዕለተ ብርሃን" ፦ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስንና የቅዱስ ያሬድን አስተምሕሮ መሠረት አድርጋ ታኅሣሥ 14 ቀን "ዕለተ ብርሃን" ትለዋለች። ሳምንቱን (ከታኅሣሥ 14-20 ነው)። በእነዚህ ዕለታት እሑድ በዋለበትን ቀን ማኅሌት ተቁሞ ብርሃን ተብሎ ይከበራል። ደግሞ "ሰሙነ ብርሃን" ስትል ታስባለች::
❤ "ብርሃን" በቁሙ የእግዚአብሔር ስሙ፤ አንድም የባሕርይ ገንዘቡ ነው። "እግዚአብሔር ብርሃን ነውና:: ጨለማም በእርሱ ዘንድ የለችምና።" (ዮሐ 1፥4)
❤ በዚህ ዕለት "ብርሃን" በሚል መነሻ ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ታስተምሠራለች:-
1.እግዚአብሔር ብርሃን መሆኑን። (ዮሐ 1፥5)
2.አምላካችን በመጀመሪያው የፍጥረት ቀን (በዕለተ እሑድ) ዲያብሎስ ቅዱሳን መላእክትን ሲረብሽ "ለይኩን ብርሃን" ብሎ ብርሃንን መፍጠሩን። (ዘፍ. 1፥2 አክሲማሮስ)
3.ነቢያት አበው በጨለማው ዓለም ሆነው መከራ ሲበዛባቸው "ፈኑ ብርሃነከ - ብርሃንህን ላክልን" እያሉ መጮሃቸውን። (መዝ 42፥3)
4.ጩኸታቸውን የሰማ ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ (እውነተኛው ብርሃን) ወደዚህ ዓለም መምጣቱን። (ሉቃ 1፥26)
5."እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ" ሲል የባሕርይ ብርሃንነቱን እንደ ነገረን። (ዮሐ 8፥12)
6.ብርሃነ መለኮቱን በገሃድ መግለጡን። (ማቴ 17፥1)
7.ብርሃን የሆነችውን ሕግ፤ ወንጌልን እንደ ሠራልን:: (1ዮሐ 2፥9)
8.ድንግል እመቤታችን ብርሃን፤ የብርሃንም እናቱ መሆኗን። (ሉቃ 1፥26፣ ራዕ 12፥1)
9.ቅዱሳኑ ብርህን መባላቸውን። (ማቴ. 5፥14)
10.እኛ በሰው ፊት ሁሉ እንድናበራ መታዘዛችን። (ማቴ 5፥16) ሁሉ ይታሰባል።
❤ እርሱ ፈጣሪያችን ክርስቶስ ጨለማውን በምሕረቱ አርቆልናልና ዳግመኛ ወደ ጨለማ እንዳንሄድ እየለመንን እናመስግነው።
❤ "ክርስቶስ ብርሃን ዘአሰሰልከ ጽልመተ።
ላዕለ ኪሩቤል ነቢረከ ዘትሬኢ ቀላያተ።
ስቡሕኒ ወልዑል አንተ"። (መልክአ ኢየሱስ) ምንጭ፦ ከዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ ፔጅ የተወሰደ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ፈኑ ብርሃንከ ወጽድቀከ። እማንቱ ይምርሓኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ"። መዝ 42፥3። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 13፥11-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 1፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 26፥12-19። የሚነበው ወንጌል ዮሐ1፥1-19። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ አትናቴዎስ ወይም ቅዳሴ እግዚእነ ቅዳሴ ነው። መልካም የብርሃን በዓል፣ ዕለተ ሰንበትና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፱ (19) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያውያኑ_ጻድቅ ለታላቁ አባት #እግዚአብሔር_አምላክ ብዙ ቃል ኪዳን ለገባላቸው #ለአቡነ_አባለ_ክርስቶስ ለዕረፍት በዓል፣ ተንቤን ውስጥ የሚገኘውን አስደናቂውን የውቅን #ቅዱስ_ገብርኤል ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ ለሠሩት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ዳንኤል_ዘተንቤንና መልአከ ሞት ከበራቸው ላይ ለሦስት ወር ላቆሙ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ስነ_ኢየሱስ ለዕረፍታቸው በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_አባለ_ክርስቶስ፦ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ አቡነ አባለ ክርስቶስ ዘደብረ መድኃኒት ጻድቁ አቡነ አባለ ክርስቶስ ከአባታቸው ቅዱስ አቃርዮስ እና ከእናታቸው ቅድስት ታውክልያ በ8ኛው ክፍለ ዘመን በየካቲት 19 810 ዓ.ም በአክሱም ከተማ የተወለዱ ጻድቅ ሲሆኑ ከሰውነታቸው ማሀል ዲካባ፣ ማርትያስ፣ ክስብኤል የሚሉ ኅቡአን የሥላሴ አስማት ተጽፎውላቸው የተወለዱ ጻድቅ ናቸው።
❤ በዚሁ መሰረት ከጻድቁ አቡነ ጰንጠሌዎን በሠላሳ ሁለት ዓመታቸው ሙንኲስናን ከተቀብሉ በኋላ ጽላትን ለ24 ዓመታት ያህል እያጠኑ ከቆዩ እንደ ሌሎቹ ቅዱሳን ዛሬ ገደማቸው በሚገኝበት እና አፅማቸው ካረፈበት ገዳማቸው ተጋድሎን በመፈጸም ከፈጣሪያቸው በታሕሳስ 19 ቀን ቃልኪዳን ተቀብለው በ332 ዕድሜያቸው ያረፉ ኢትዮጵያዊው ጻድቅ ናቸው።
❤ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጣቸው ቃል ኪዳን "ዝክርህን የዘከረ ስምህን የጠራ እስከ 24 ትውልድ ምሬልሀለሁ" አላቸው። "ስምህን በመጥራት የተራቡ ያበላ የተጠሙ ያጠጣ የታረዙትን ያለበሰ ለቤተ ክርስቲያንህ የተለያዩ ምፅዋት የሰጠ እስከ 28 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው። ማየ ጸሎትህም፣ ፀበልህ፣ የተጠመቁ፣ የታጠቡ እስከ 27 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው። ገዳምህን ለመሳለም፣ ለመሳም፣ አስበው ያልተሳካላቸው 26 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው። ቤተ ክርስተያንህን የሰራ በመንግስተ ሰማያት እስከ 33 ትውልድ የብርሃን ማደርያ እሰራለታለሁ አላቸው። ዝክርህን፣ መታሰብያህን፣ ሊያደርግ ብሎ ያሰበ ነገር ግን በተለያየ ምክንያት ሳይሳካለት የቀረ እሰከ 25 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው።
❤ "በገዳምህ በየዓመቱ እና በየወሩ ቅዱስ ቊረባን የተቀበለ እስከ 35 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው:: መፅሓፍህን የፃፈ፣ ያነበበ፣ የተረጎመ፣ የሰማ እስከ 28 ትውልድ አድነዋለሁ" አላቸው። "ይህች የምታርፍባት የነበርክ ድንጋይ የመካናት ማህፀን ፈትታ ልጅነት ትሰጣለች" አላቸው። ሰውነታቸው በተለያዩ ሕመሞች፣ በሽታዎች የተያዙ አለቱን ቤተክርስቲያኑን በምትፈለፍልባት የነበርክ በትርህ ታሽቶው ይደናሉ" በማለት በማይሻር ቃሉ ይሀንን ቃል ኪዳንገበቶላቸው በክብር ወደ ሰማያት አረገ።
❤ ገዳሙ የምገኘው ከአክሱም ወደ ማሕበረ ጻድቃን ዴጔ 17 ኪሎሜትር ተጉዘው ማሕበረ ጻድቃን ዴጔ ከተማ ላይ እንደደረሱ ወደ ግራ በመንገጠል 25 ኪ.ሜ እንደተጓዙ ጠላዕ በምትባል ትንሽ ከተማ ቀበሌ ሲደርሱገዳሙ አስደናቂ በሆነ አቀማመጥ ከሚያስደንቅ ሸለቆ ከአለት ተፈልፍሎ የተሰራ ጥንታዊ እና ታሪካዊ ባለ ቃል ኪዳንገዳሙ ያገኙታል። በገዳሙ በየዓመቱ ታሕሳስ 19 ቀን የጻድቁ በዓለ ዕረፍት ፥ የካቲት 19 ቀን የጻድቁ በዓለ ልደታቸው ዓበይት በዓላት ብዙ ምእመናን በተሰበሰቡበት በታላቅ ድምቀት ይከበራል። ጻድቁ ገድለኛ እና ታአምረኛ በመሆናቸው በእሳቸው እጅ ከአለት ተፈልፍሎ የተሠራ ቤተ መቅደስ፣ቅኔ ማህሌት፣ ምቋም ሰዓታት እና ቤተ አንድነት በገዳሙ ውስጥ ይገኛል። ያርፉባት የነበረች ድንጋይ እብነ ሕይወት ተብላ እንድትጠራ እና የመካናት ማህፀን ፈትታ ልጅ እንድ ትሰጥ ቃል ኪዳንየተሰጣት ድንጋይ እና ቤተ መቅደሱን የሚፈለፍሉባት የነበረች በትረ ትእምርት ለምስክር ያህል እስከ አሁን ብዙ ህሙማን እና መካናት እየተፈወሱ በገዳሙ ውስጥ ይገኛሉ።
❤ በገዳሙ ካሉ ቅርሳቅርሶች ከ1000 ዓመት በላይ ዕድሜ ያላቸው መዛግብተ እክል፣ ጎተራዎች፣ ሰፍየዶች፣ ከሸክላ የተሰሩ ፅዋዎች እና ጋኖች በአስገራሚ ሁኔታ እስከ አሁን በገዳሙ ውስጥ ተጠብቀው ይገኛሉ። እንዲሁም በገዳሙ ውስጥ የሚገኙሁለት ዓይነት ጠበል ማለትም መጀመርያ ወደ ገዳሙ ሲገቡ በመስቀላቸው ባርከው ከዐለት ያፈለቁት ማየ ጸሎት እና በዕረፍታቸው ቀን ከመቃብራቸው ከቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚመነጭ ማየ ጸሎት ብዙ ህሙማን እየተፈወሱበት የሚገኝ ታሪካዊ ገዳም ነው። ከአባታችን ከአቡነ አባለ ክርስቶስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ Tmihrt Fikre Debre Birhan።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ዳንኤል_ዘተንቤን፦ አገራቸው ትግራይ ዘተንቤን ነው። ዳንኤል ሐዲስ በሚል ስያሜም ይታወቃሉ። በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመን የነበሩ ሲሆን ለዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ከሰማይ የወረደላቸውን መስቀል ይይዙት ስለነበር ዛሬ ያንን መስቀል። ትግራይ ወስደውት ውቄን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ውስጥ በክብር አስቀምጠውታል። የዐፄ ዘርዐ ያዕቆብንም መጽሐፈ ነገሥት ተርጓሚ ነበሩ። ጻድቁ እህል ሳይበሉ ውኃም ሳይጠጡ 40ቀንና 40ሌሊት ይጾሙ የነበሩ መናኝ ባሕታዊ ናቸው። እንደ ነቢዩ ኤልሳዕም ሁለት ሙት አስነሥተዋል። ከአባታችን አቡነ ዳንኤል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን።
✝ ✝ ✝
❤ #ጻድቅ_አቡነ_ስነ_ኢየሱስ፦ መልአከ ሞት መስከረም 19 ቀን መጥቶ "ጊዜ ዕረፍትህ ደርሷል" ቢላቸው "የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብር አይሆንም" ብለው መልአከ ሞትን ለ3 ወራት ከበራቸው ላይ ያቆሙት አቡነ ስነ ኢየሱስ በደመና ተጭነው በመዘዋወር በሀገራችን ወንጌልን ሰብከዋል፡፡ ገዳማቸው ታች አርማጭሆ ከሳንጃ ከተማ በእግር የ3 ሰዓት መንገድ ርቀት ላይ ይገኛል፡፡
❤ ጻድቁ ከሽዋ ምድር ተነሥተው ወደ ታች አርማጭሆ በመሄድ በበረሃ ውስጥ በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡ በዚያም የሰማዕቱ የቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድን ገዳም ገድመዋል፡፡ አቡነ ስነ ኢየሱስ ብዙ መናንያን አርድእትን ያፈሩ ታላቅ አባት ሲሆኑ አስገራሚ ተአምራትን በማድረግም ይታወቃሉ፡፡ የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብር አይሆንም ብለው መልአከ ሞትን ለ3 ወራት ከበራቸው ላይ ካቆሙትና በዓሉን ካከበሩ በኃላ በዚኽች ዕለት ታሕሳስ 19 ቀን በሰላም ዐርፈዋል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ስነ ኢየሱስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፱ (19) ቀን።
❤ እንኳን #ለመጋቤ_ሐዲስ_ለሊቀ_መላእክት #ለቅዱስ_ገብርኤል_አናንያን_አዛርያን_ሚሳኤልን (ሠለስቱ ደቂቅን) ከነደደ እሳት ለዳናቸው ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከካህናት ወገን ከሆነ #ከሀገረ_ቡርልስ_ኤጲስቆጶስ ከቅዱስ አባት #ከአባ_ዮሐንስ_ዕረፍት ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ቀን #የመላእክት_አለቃ_የመልአኩ_ቅዱስ_ገብርኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው በዚች ቀን በዚህ ወር እግዚአብሔር ወደባቢሎን አገር ላከው የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ሦስቱን ልጆች አናንያን አዛርያንና ሚሳኤልን ከእሳት ማንደጃ ውስጥ በጣላቸው ጊዜ አራተኛ ገጽ ሁኖ ታየ። የእሳቱም ነበልባል አርባ ዘጠኝ ክንድ ያህል ወላይ ከፍ ከፍ አለ የጨመሩአቸውን ሰዎችና እሳት የሚያንዱትን አቃጠላቸው ይህም የከበረ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል የእሳቱን ነበልባል በበትሩ መትቶ ከሠለስቱ ደቂቅ ላይ አጥፍቶ አዳናቸው ምንም አልነካቸውም እንደ ቀዘቀዘ እንደ ጧት ጤዛ አድርጎታልና።
❤ በዚያንም ጊዜ የአባቶቻችን ፈጣሪ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እያሉ ስድስት ቃላትን ተናገሩ በዚህም ከስድስት መቶ ዓመት በኋላ ክርስቶስ እንደሚወለድ ትንቢት ተናገሩ። ከዚህም በኋላ የጌታ እግዚአብሔር ሥራዎቹ ሁሉ ያመሰግኑታል እርሱ ለዘላለሙ ምስጉን ልዑልም ነው እያሉ ሠላሳ ሦስት ጊዜ አመሰገኑት በዚህም በምድር ላይ ሠላሳ ሦስት ዓመት ክርስቶስ እንደሚኖር አመለከቱ።
❤ ስለዚህም አባቶቻችን የቤተ ክርስቲያን መምህራን የመላእክት አለቃ የሆነ የቅዱስ ገብርኤልን የበዓሉን መታሰቢያ እንድናደርግ ሥዓትን ሠሩ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ገብርኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 12 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የአገረ_ቡርልስ_ኤጲስቆጶስ_አባ_ዮሐንስ፦ የዚህም ቅዱስ ወላጅቹ የከበሩ ናቸው እነርሱም ከገንዘባቸው ለድኆችና ለችግረኞች ይሰጡ ነበር ወላጆቹም በአረፉ ጊዜ የተዉለትን ገንዘብ ወስዶ ቤተ ክርስቲያን ሠራ ዳግመኛም የእግዳ ቤት ሠራ በውስጡም መጻተኞችንና በሽተኞችን ሰብስቦ የሚያገለግላቸው ሆነ የሚሹትንም ሁሉ ያቀርብላቸዋል።
✝ በዚያም ወራት ወደርሱ አንድ መነኵሴ መጣ የምንኵስናንም ሥራ አመሰገነለት ክብሩንም ገለጠለት ያ መነኵሴም ከሔደ በኋላ ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ሰጥቶ አባ ዳንኤል ለአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ በነበረበት ወራት ወደ አስቄጥስ ሒዶ በአባ ዳንኤል ዘንድ መነኰሰ በዋሻ ውስጥም ብቻውን ሁኖ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ። ስለ መልካም ተጋድሎውም ሰይጣናት ቀኑበት ብዙ ዘመንም ታሞ ከኖረ በኋላ በደዌ መቅሠፍት ቀሠፉት።
❤ ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈወሰውና ኃለኛ ጽኑዕ አደረገው በእግዚአብሔርም ፈቃድ ቡርልስ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶሰነት ተሾመ በዘመኑም በአገሮች ውስጥ ብዙ ኑፋቄ ነበር እርሱም እንክርዳዱን ከሥንዴ መካከል ይነቅል ዘንድ ብዙ ድካምን ደከመ ከላይኛው ግብጽ የሆነ አንድ ሰው ነበረ ብዙ ነገርንም ይቀርባጥር ነበር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ምሥጢር ይገልጥልኛል በማለት እርሱ ብዙ ሰዎችን አሳታቸው ይህንንም በአወቀ ጊዜ ይዘው ይገርፋት ዘንድ አዘዘ ስሕተቱንም አመነ ከአገርም አሳደዱት።
❤ ነቢይ ዕንባቆም ይታየኛል ብዙ ምሥጢራትንም ይገልጥልኛ የሚል ሌላ ሰው ነበር ብዙዎችም ተከተሉት እርሱንም አሳደደው ትምህርቱንም አጠፋ መጻሕፍቱንም ቀደደ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው። ይህ አባ ዮሐንስ መሥዋዕት ለማሳረግ በሚቀድስ ጊዜ ፊቱ እሳት ይሆናል ሥጋውም ከእሳት ማንደጃ ውስጥ እንደወጣ ይሆናል ዕንባውም እንደ ዝናብ ይዘንባል የመላእክትን ሠራዊት በመሠዊያው ዙሪያ በመሠዊያው ዙሪያ በግልጥ ያያቸዋልና። ኅብስቱ በሚፈተት ጊዜ ሦስቱን የመፈተቻ ምስጋናዎች አንብቦ ጽዋውን ሲባርከው እንደ ፍም የጋለ ሁኖ ጽዋውን ያገኘዋል።
❤ በኋላ በዘመኑ በቀን ከበሉ በኋላ በአንድ ቀን ሁቸተኛ የሚቆርቡ ክፉዎች ሰዎች ተነሡ አስተምራቸው ገሠጻቸው ባልተመለሱም ዳግመኛ አወገዛቸው ባልተመለሱም ጊዜ ስለርሳቸው ጌታን ለመነው እሳትም ከሰማይ ወርዶ አለቃቸውን አቃጠለው የቀሩትም ይህን አይተው እጅግ ፈሩ ተጸጽተውም ወደ ቀናች ሃይማኖት ተመለሱ።
❤ ከዚህም በኋላ ከዚህ ከኃላፊው ዓለም እግዚአብሔር ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ ቅዱሳን አባ እንጦስና አባ መቃርስን ወደርሱ ላካቸው እነርሱም ዕረፍቱ እንደ ደረሰ አስረዱት ሕዝቡንም ሰብስቦ ሕግና ሥርዓትን እንዲጠብቁ እርስ በርሳቸውም ይፋቀሩ ዘንድ በቀናች ሃይማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው ከዚህም በኋላ በመኝታው ላይ ጋደም ብሎ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት በአባ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 19 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ማኅሌት_ምስባክ፦ "ባርክዎ ለእግዚአብሔር ኵሎሙ መላእክቲሁ። ጽኑዓን ወኃያላን እለ ትገብሩ ቃሎ። ወእለ ትሰምዑ ቃለ ነገሩ። መዝ 102፥20-21 ወይም መዝ 137፥1-2። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 12፥29-34 ወይም ሉቃ 1፥11-21። መልካም የቅዱስ ገብርኤል በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፰ (18) ቀን።
❤ እንኳን #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ቶማስ ለሥጋው ፍልሰት በዓልና ለሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ_ደቀ_መዝሙር_ለቅዱስ_ቲቶ ሥጋው ከአቅራጥስ ከሚባል አገር ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ ለፈለሰበት ለመታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከኢርቅና በሰማዕትነት ከሞተ በብሕትውና ከሚኖር #ከቀሲስ_ፊልሞና ከዕረፍታቸው መታሰቢያ፣ #የፍርክዮን_ከኢልኮዮስ_ከበሳንቅስ፣_ከዮናስ፣ ከባልጀሮቻቸው ሰማዕታትም ከመታሰቢያቸው፣ #ከአርሲስ_ከዳስያና_ከዲሞንም ከሥጋቸው ፍልሰት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ቀን #የሐዋርያ_ቅዱስ_ቶማስ_የሥጋው ፍልሰት መታሰቢያ ሆነ ከሥጋውም አስደናቂዎች የሆኑ ብዙ ተአምራት በተገለጡ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት ሥጋውንም በውስጧ አኖሩ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በጸሎቱ ይማረን በከቱም ከእኛ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 18 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የቅዱስ_ቲቶ_የሥጋ_ፍልሰት ወደ #ቊስጥንጥንያ_ከተማ፦ ይህም እንዲህ ነው ታላቁ ጻድቅ ቈስጠንጢኖስ በእግዚአብሔር ፈቃድ በነገሠ ጊዜ ስለ አብያተ ክርስቲያናት ሥራ አስቦ በሚገዛቸው አገሮቹ ሁሉ ሠርቶ በመልካም ጌጥ አስጌጣቸው በዕንቊዎችና በከበሩ ደንጊያዎችም ይልቁንም በቊስጥንጥንያ ከተማ እርሷ መናገሻ ከተማው ናትና። የሐዋርያትንም ሥጋቸውን ከሁሉ ቦታ ከከበሩ ሰማዕታትም ብዙውን ሰበሰበ ስለ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ሥጋ አቅራጥስ በሚባል አገር እንዳለ በሰማ ጊዜ የካህናትን አለቆች ከብዙ ገንዘብ ጋር ላካቸው እነርሱም የቅዱስ ቲቶን ሥጋ በታላቅ ክብር ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ አደረሱት ንጉሡም ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠራለት ሥጋውንም ከከበረ ደንጊያ በተሠራ ሣጥን ውስጥ አኖረ።
❤ እግዚአብሔርም ታላላቅ አስደናቂዎች ተአምራትን ከሥጋው ገለጠ ከዕብነ በረድ የተሠራ ሥጋው ያለበትን ሣጥን በተሸከሙ ጊዜ ከአንድ ሰው ላይ ወድቆ እግሩን ቀጥቅጦ ሰበረው እርሱም ከቅዱስ ቲቶ ሥዕል ፊት ካለው የመብራት ቅባት የተሰበረ እግሩን ቀብቶ ሲያመው እየጮኸ አሠረው። ወደ ቤቱም መሔድ ባልቻለው ጊዜ የቅዱስ ቲቶ ሥጋ ሣጥን በአለበት በዚያ አደረ። በማግሥቱም አይቶ በውስጡ መድኃኒት ሊያደርግ እግሩን በፈታው ጊዜ ከቶ ምንም ምን ሕማም እንዳላገኘው እንደሁለተኛው ደኅና ሁኖ አገኘው ግን የደም ፍለጋ ምልክት አለ ይህን ድንቅ ሥራ ያዩ እጅግ አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት እርሱም የዳነው ፈጽሞ እያመሰገነ ወደ ቤቱ ገባ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_እብል_ለፍልሰተ_ሥጋሁ_በዘምሮ። #ለረድአ_ጳውሎስ_ቲቶ_እግዚአብሔር_እንተ አፍቀሮ። ሣፁነ ሥጋሁ ዘዕብን አመ ለብእሲ ሰበሮ። ረከበ ፈውስ ወጥዒና ከመ መንፈስ ቅዱስ አምከሮ። እምቅብዐ ማኅቶት ዘገጸ ሥዕሉ ሶበ ቀብዐ እግሮ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የታኅሣሥ_18።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አፅናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 7፥13-ፍ.ም፣ 1ኛ ይሁ 1፥17-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 5፥12-17። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 11፥9-17። የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን የሲመት በዓልና የሐዋራዊው ቅዱስ ቶማስና የቅዱስ ቲቶ የሥጋ ፍልሰት በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፭ (15) ቀን።
❤ እንኳን #ለአርማንያ_ሊቀ_ጳጳስ ያለ ደም መፍሰስ ሰማዕት ለሆነ #ለቅዱስ_ጎርጎርዮስ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱስ_ሉቃስ_ዘአምድና_ከአባ_ይምላህ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #የአርማን_አገር_ኤጲስቆጶስ_አባ_ጎርጎርዮስ፦ ይህንንም ቅዱስ የንጉሡን ትእዛዝ ስመተላለፋና ለአማልክት አልሠዋም ስላለ የአርማንያ ንጉሥ ድርጣድስ አሠቃይቶ ጥልቅ ወደ ሆነ ደረቅ ጒድጓድ ውስጥ ጨመረው በዚያ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ። እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ነበር አንዲቷን አሮጊትም ሁል ጊዜ ምግቡን እነሰድታመጣለት አደረጋት ሕያው እንደሆነም የሚያውቅ የለም።
❤ ንጉሥ ድርጣድስም ቅድስት አርሴማን ለማግባት ሽቶ ነበርና በእርሷ ምክንያት ደናግሎችን ገደላቸው። የእሊህ ደናግልም ሥጋቸው በተራራ ላይ እንደ ወደቀ ነበር ንጉሡም ስለ ገደላቸው ደናግል ይልቁንም ውበቷንና ደም ግባቷን እያሰበ ስለ ቅድስት አርሴማ አብዝቶ የሚያዝንና የሚጸጸት ሆነ።
❤ ከዚህም በኋላ ወገኖቹ ለመኑት እንዲህም አሉት አውሬ ታድን ዘንድ በፈረስ ተቀመጥና ወደ ዱር እንውጣ የልብህም ኀዘን ይወገድልሃል። በዚያንም ጊዜ አውሬ ለማደን በፈረሱ ተቀምጦ ወደ ዱር ወጣ። የሚነክስ ሆነ ወገኖቹንም ነከሳቸው እግዚአብሔርም መልኩን ለውጦ እንደ እሪያ አደረገው ያገኘውን ሁሉ የሚነክሰ ሆነ። እንዲሁም ከቤተ መንግሥት ሰዎች በብዙዎቹ ላይ ሰይጣን አደረባቸው ታላቅ ድንጋጤም ሆነ ይህም ሁሉ የሆነ ስለ ቅዱሳት ደናግልና ስለ ቅድስት አርሴማ ነው።
❤ የንጉሡ እኅት ግን "ጎርጎርዮስን ከጒድጓድ ካላስወጣችሁት ድኅነት የላችሁም" የሚላት ሰው በራእይ አየች ይህንንም ለወገኖቿ ነገረች እርሱ አስቀድሞ በጒድጓድ ውስጥ የሞተ ስለ መሳላቸው ደነገጡ። በዚያንም ጊዜ ወደ ጒድጓድ ሔዱ በሕይወት እንዳለም ያወቁ ዘንድ ወደ ጒድጓዱ ውስጥ ገመዶችን አወረዱና ገመዶቹን እንዲይዝ ወደርሱ ጮኹ እርሱም ገመዶችን ያዘ ስበው አወጡት አጥበውም ንጹሕ ልብስን አለበሱት በበቅሎም አስቀምጠው ወደ ቤተ መንግሥት አደረሱት። በዚያንም ጊዜ በሰማዕትነት ስለሞቱ ደናግል ሥጋ ጠየቀ እነርሱም የደናግሉ ሥጋቸው ወዳለበት መርተው አደረሱት የዱር አራዊትና አዕዋፍ ሳይበሏቸው በደኅና አገኛቸው ያማሩ ቦታዎችን አዘጋጅተው በውስጣቸው ያኖሩዋቸው ዘንድ አዘዘ እንዳዘዛቸውም አደረጉ።
❤ ከዚህም በኋላ ንጉሡን ያድነው ዘንድ ሕዝቡ ለመኑት ንጉሡም ወዳለበት ዱር አደረሱት እርሱም "ከክፉ ሥራህ ትመለሳለህን? ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታምናለህን?" አለው። እሪያ የሆነውም ንጉሥ አዎን እንደሚል ራሱን ዘንበል አድርጎ አመለከተ በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ጸለየ ከንጉሡም ላይ በእሪያ አምሳል ሰይጣንን አስወጣው። የንጉሡም አእምሮውና መልኩ እንደ ቀድሞው ተመለሰለት ነገር ግን ዳግመኛ እንዳይታበይ ከእግሩ ላይ የእሪያ ጥፍር አስቀረ ፈጣሪውም ተገዢ ይሆን ዘንድ ዳግመኛም የቤተ መንግሥት ሰዎችን ሁሉንም አዳናቸው ከላያቸውም አጋንትን አስወጥቶ ሰደዳቸው።
❤ ከዚህም በኋላ የአርማንያን ሰዎች ሁሉንም ሰበሰባቸውና ሥርዓትን ሠራላቸው ስምንት ቀንም እንዲጾሙ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ የእግዚአብሔርንም ሕግ እያስተማራቸው ኖረ። ዳግመኛም ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆኑን አስተማራቸው ታላቆችም ታናናሾችም ትምህርቱን ተቀበሉት ለአርማንያ ሰዎች ሃይማኖትን የመቀበላቸው ምክንያት ይህ ነው።
❤ ከዚህም በኋላ የክርስትና ጥምቀትን ያጠምቃቸው ዘንድ ቅዱስ ጎርጎርዮስን ለመኑት እርሱም "እኔ ካህን ስለአልሆንኩ አይገባኝም ነገር ግን የሚያጠምቃችሁን ካህን ይልክላችሁ ዘንድ ወደሮሜ ሊቀ ጳጳሳት መልክተኞችን ላኩ" አላቸው። በዚያንም ጊዜ ከርሱ ጋር ወደ ንጉሥ አኖሬዎስና ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ መልክተኞችን ልከው የአርማንያ ሰዎች ወደ እግዚአብሔር እንደተመለሱ አስረዱአቸው ንጉሡም ሊቀ ጳጳሳቱም ሰምተው ደስ አላቸው ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ ለአርማንያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ይሆን ዘንድ ቅዱስ ጎርጎርዮስን ሾመው ወደ አርማንያን ንጉሥ ወደ ድርጣድስም በክብር ላከው።
❤ ቅዱስ ጎርጎርዮስም ተሹሞ ወደ አርማንያ አገር በደረሰ ጊዜ በመምጣቱ ደስ ተሰኙበት እርሱም የአርማንያን ሰዎች ሁሉንም አጠመቃቸው በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያምም ስም ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው ሃይማኖንትም ከአጸናቸውና መልካም ጉዞንም ከፈጸመ በኋላ ታኅሣሥ15 ቀን በሰላም በፍቅር ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ጎርጎርዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ15 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለሉቃስ_ዘፃመወ_ፃማ። በልብሰ ኀፂን ይትጋደል ወይትቃተል ምስለ መስቴማ። መዋዕለ ጾሙ ስዱስ እስከ ይትፌጸማ። ለዕርቅት ከርሡ እንዘ ይሠርዕ ዓቅማ። በዕለተ ሰንበት ይሴሰይ አሐደ ጳኵሲማ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የታኅሣሥ_15።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ቀብፁኒ እምልብ ከመ ዘሞተ። ወኮንኩ ከመ ንዋይ ዘተኀጒለ። እስመ ሰማዕኩ ድምፀ ብዙኃን እለ ዐገቱኒ ዐውድየ"። መዝ 30፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት ፊሊ 2፥5-12፣ ያዕ 1፥19-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 20፥28-31 ወይም 8፥18-26። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 15፥11-25። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ቆራይ የዕረፍታቸ በዓል፣ የአቡነ ኤዎስጣቴዎስ የመታሰቢያቸው በዓልና የነቢያት (የገና) ጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፭ (15) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያውያኑ_ጻድቃን ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ኤዎስጣቴዎስ_ከፋሌ_ባሕር አጽፋቸውን እንደጀልባ ተጠቅመው #የኢያሪኮን_ባሕር_ለተሻገሩት መታሰቢያ በዓል፣ እጅና እግር የሌላቸውና የእኔ ቢጤ ለነበሩት ጽድቃቸውን ማንም ሳያውቅባቸው ለኖሩት ለታላቁ ጻድቅ #ለአባ_ቆራይ_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ኤዎስጣቴዎስ_የኢያሪኮን_ባሕር #በዓጽፍቸው_ስለመሻገራቸው፦ ወደ አርማንያ ሔደ ወደኢያሪኮ ባሕርም ሲደርስ በመርከባቸው ያሳፍሩት ዘንድ መርከበኞችን ለመናቸው በከለከሉትም ጊዜ ዓጽፉን በባሕሩ ላይ ዘረጋ በቅድስት ሥላሴ ስም በላዩ ባረከ ራሱንም በመስቀል ምልክት አማተበ እንደ መርከብም ሁኖለት በላዩ ተጫነ ሁለት መላእክትም ቀዛፊዎች ጌታችንም እንደ ሊቀ ሐመር ሆኑለት። ከባሕሩም ግርማ የተነሣ እንዳይፈሩ ልጆቹን አጽናናቸው። ግን እንዲህ አላቸው "ልጆቼ በልባችሁ ቂምንና ሽንገላን እንዳታኖሩ ተጠበቁ ለኔ ግን ከእናንተ አንዱ እንደ ሚጠፋ ይመስለኛል" ይህን ሲናገረሰ ልቡ የቂም የበቀል ማከማቻ ስለሆነ ወዲያውኑ አንዱ ከእነርሱ መካከል ሠጠመ። በእግዚአብሔርም ፍቃድ ባሕሩን ተሻግሮ ወደ አርማንያ ከተማ ደርሶ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር ተገናኘ ሰገደለትም ከእርሱም ቡራኬን ተቀበለ ሊቀ ጳጳሱም በአየ ጊዜ ታላቅ ደስታ ደስ አለው በፍቅርም ተቀበለው። አባታችን ኤዎስጣቴዎስም ሁሉም በትምህርቱ አንድ እስከሆኑ ድረስ የአርማንያን ሰዎች ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው የሠሩትን ሥርዓት እያስተማራቸው ኖረ። ከአባታችን ከአቡነ ኤዎስጣቴዎስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ የመስከረም18 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የእኔ_ቢጤው_አባ_ቆራይ፡- እጅና እግር የሌላቸውና የእኔ ቢጤ የነበሩት ጽድቃቸውን ማንም ሳያውቅባቸው የኖሩት አባ ቆራይ ጻድቅ መሆናቸው ካረፉ በኋላ ነው የታወቀው፡፡ ገዳማቸው ትግራይ ተንቤን ውስጥ ይገኛል፡፡ ቅዱሱ በዐፄ ልብነ ድንግል ዘመነ መንግሥት በትግራይ ተንቤን አውራጃ አዲ ራእሶት-የራሶች (የታላላቅ ሰዎች አገር) በሚባለው ቦታ የእግርና የእጅ ጣቶች የሌሏቸው አባ ቆራይ ወንበር በምትመስል ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ተገለጡ፡፡
❤ አንድ የአካባቢው ሰው በመንገድ ሲያልፍ አባ ቆራይ ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ጸሎት ሲያደርጉ አያቸውና በሁኔታው ተገርሞ ወደ እርሳቸው ጠጋ ብሎ ስማቸውንና የመጡበትን አገር ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም "ስሜ አባ ቆራይ ይባላል፣ አገር ግን የለኝም" አሉት፡፡ እርሱም "እባክዎን ወደ መንደር እንሂድና የጸሎትና ቤት ሠርተንልዎት በዚያ ይቀመጡ" አላቸው፡፡ አባ ቆራይ ግን "ማረፊያዬ ይህቺ ናት፣ ከዚህች ሥፍራ አልነሣም" አሉት፡፡ አባ ቆራይም በዚያው እንደተቀመጡ ዝናቸው በሁሉ ዘንድ ተሰማና ሰዎች መጥተው በተቀመጡበት ድንጋይ ዙሪያ ጎጆ ቀለሱላቸው፡፡
❤ ከዚህም በኋላ መንደርተኞቹ በየተራ በምግብ ሊረዷቸው ዕጣ ተጣጥለው ወደየቤታቸወ ሄዱ፡፡ በመጀመሪያ ተራ የደረሰው ሰው ከአንድ ሰዓት በኋላ ምግብ ይዞ ቢመለስ የአባ ቆራይ ጎጆ በብርሃን ተሞልታ አገኘ፡፡ ወደ ጎጆዋም ሲጠጋ ነበልባሉ እየፈጀው አላስቀርበው አለ፡፡ እርሱም በድንጋጤ ወደ መንደሩ ተመልሶ ለአካባቢው ሰው ነግሮ ሁሉም ተሰብስበው መጡ፡፡ መንደርተኛውም ካህናትን ይዘው ብዙ የምሕላ ጸሎትና እግዚኦታ ካደረሱ በኋላ እግዚአብሔር ወደ ጎጆዋ እንዲገቡ ፈቀደላቸውና ገቡ፡፡ ነገር ግን አባ ቆራይን በሕይወት አላገኟቸውም፡፡ አስክሬናቸውን ብርሃን ከቦት አገኙት፡፡ ከአስክሬናቸው አጠገብ "የአባ ቆራይን አስክሬን ከዚህች ጎጆ ውስጥ እንድትቀብሩት፤ ወደ ሌላ ቦታ ወይም ቤተ ክርስቲያን ወስደን እንቀብራለን ብላችሁ እንዳታስቡ፡፡ ነገሩን በድፍረት ብትፈጽሙት በሀገሩ ላይ እግዚአብሔርን ቁጣ ታመጣላችሁ" የሚል ትእዛዝ በብራና ተጽፎ ተገኘ፡፡ በዚሁ ትእዛዝ መሠረት የአሀሩ ሕዝብ ተሰብስቦ አባ ቆራይን ታኅሣሥ 15 ቀን እዚያው ቀበሯቸው፡፡
❤ ከጥቂት ዘመናት በኋላ ባልና ሚስት የሆኑ ሰዎች መቆመም ሆነ መራመድ የማይችል ድውይ ልጃቸውን ይዘው ወደ ጸበል ሲሄዱ መሸባቸውና በአካባቢው ማደሪያ ሲፈልጉ የአባ ቆራይ ጎጆ ክፍት ሆኖ ታያቸውና ልጃቸውን ይዘው ሄደው ገቡ፡፡ ድውይ ልጃቸውን በአባ ቆራይ መቃብር ላይ ቢያስተኙት የኤልሳዕን አጥንት እንደነካውና ፈጥኖ እንደተነሣው ሙት ይህ ድውይ ልጅም በአባ ቆራይ መቃብር ላይ እንዳረፈ ወዲያው አፈፍ ብሎ በመነሣት እንደ እንቦሳ ጥጃ መዝለል ጀመረ፡፡ ወላጆቹም እልልታቸውን አቀለጡት፡፡ ወላጆቹም በነጋ ጊዜ ወደ መንደርተኛው ሄደው የተደረገላቸውን ተአምር ተናገሩ፡፡ ከዚያም ጊዜ ጀምሮ የአባ ቆራይ በዓል በአካባቢውና አጎራባች ቦታዎች ሁሉ ዘንድ መከበር ጀመረ፡፡ የዕረፍታቸውም በዓል ታኅሣሥ 15 ቀን ሆነ፡፡
❤ አባ ቆራይ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ለይተው እንደ ቅዱስ አልዓዛር (ሉቃ 16፡19-35) ለዚህ ዓለም ውዳቂ መስለው ለታላቅ ክብር የበቁ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡ ዛሬም ልብሳቸውንና አካላቸውን ብቻ እያየን የምንንቃቸው ሰዎች እንደ አባ ቆራይ ያሉ ቅዱሳን ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ከልዑል እግዚአብሔር በቀር ማንም ማንንም የሚያውቅ የለም። ከባታችን አባ ቆራይ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤት በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባና በጨለማ ቦታ ቆመ ከዚያ ያሉ መነኰሳትም እስከ አደነቁ ድረስ የዳዊትን መዝሙር ሲያነብ ድምፁን እንደ መላእክት ድምፅ ሁኖ ሰማሁት በነጋም ጊዜ በእግሮቹ ላይ ተቀመጠ ምንም ምን ማንበብ አልሻም። እኛ ግን ይጸልይልን ዘንድ ልንለምነው ቀረብን እርሱም "አባቴቼ ሆይ በበደሌ ብዛት ፊቴን ያጨለምኩ ስሆን ስለ እናንተ እንዴት እጸልያለሁ" አለን። ቊርባንንም በምናሳርግ ጊዜ በእግሩ ቁሞ የቅዱስ ጳውሎስን መልእክት፣ የሐዋርያትንም መልእክትና የሐዋርያትን ሥራ ማንበብ ጀምረ በአራተኛም ጊዜ በመሠዊያው ፊት ቁሞ የቅዱስ ዮሐንስን ወንጌል ማንበብ ጀመረ በፊቱም ላይ የተከናነበውን ልብስ አስወግደ ከፊቱም ብርሃን ገናናነት የተነሣ ሊያዩት አልተቻላቸውም። እኛ ቊርባንን ከተቀበልን በኋላ ቆረበ ከነገሥታት ልጆች ወገንም እንደሆነ ተጠራጠርን መብልንም በአቀረብንለት ጊዜ ከእኛ አልተቀበለም ነገር ግን ሰይጣን በእነርሱ ከሚያስትባቸው ሴቶችን ከማየት እንርቅ ዘንድ መከረን።
❤ ሮማዊ የሆነ አንድ ደግ ጻድቅ አረጋዊ መነኵስ ነበር እርሱም "አባቴ ያዕቆብ ሆይ ይቺ ከነገሥታት ልጆች ውስጥ የሆነች ሴት ናት ስለዚህም እንዳትታወቅ ፊቷን ከሰው ትሠውራለች" አለኝ። ከዚህም በኋላ ሥራዋን ከእኔ ሳትሠውር እንድትነግረኝ በክርስቶስ ስም አምላት ዘንድ ወደርሷ ሔድሁ። ግን አላገኘኋትም ከአምስት ወርም በኋላ ከንጉሥ አባቷ ዘንድ የተላኩ ብዙ ሰዎች እርሷን እየፈለጉ መጡ። እነርሱም ቤተሶቦቿ ከተኙ በኋኋ በሌሊት እንደወጣች እነርሱም እርሷን ሲፈልጉ ዐሥራ ሁለት ዓመት እንደሆናቸው ሥራዋን ነገሩን። ከዚህም በኋላ መጻተኞች ሰዎች በዚች ቀን እንዳረፈች ነገሩን። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ነሳሒት በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 14 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወሌሊትኒ ብሩህ ከመ መዓልት። በአምጣነ ጽልመታ ከማሁ ብርሃና። እስመ አንተ ፈጠርከ ኵልያትየ እግዚኦ"። መዝ 138፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 11፥1-17፣ 1ኛ ጴጥ 1፥13-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 8፥18-26። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፬ (14) ቀን።
❤ እንኳን ለታላቁ ሰማዕት #ለቅዱሳን_መርምህናምና #ለእኅቱ_ቅድስት_ሣራ_ለአርባ_አገልጋዮቹም ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍት በዓላቸው፣#ለቅዱስ_መርምህናም_አባት_ለአቶር ንጉሥ ለሰናክሬም ሠራዊት #ለዐሥራ_ሰባት_እልፍ ሰማዕታት ለመታሰቢያቸው በዓላቸው፣ ከመ ከተማ በሰማዕትነት ለዐረፈ #ለቅዱስ_ስምዖን ለዕረፍት በዓል፣ #ለሀገረ_እስና_ኤጲስቆጶስ_ለአባ_አሞንዮስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል፣ ለእስክድርያ ስልሳ ስድስተኛ ሊቀ ጳጳስ #ለአባ_ገብረ_ክርስቶስ ለዕረፍት በዓልና የአውሲም ኤጲስቆጶስ #አባ_ያዕቆብ ስለርሷ እንደተናገረ ለሮሜ ንጉሥ ልጅ ስሟ #ቅድስት_ነሳሒት ለተባለች ለዕረፍቷ በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_መርምህናምና_እኅቱ_ሣራ_አርባ አገልጋዩቹ፦ የዚህም ቅዱስ አባት የአቶር ንጉሥ የተቀረጹ ስማቸው ቤል አጵሎን የሚባሉ ጣዖታትን የሚያመልክ ነው እናቱ ግን ክርስቲያን ናት። ይህም ቅዱስ መርምህናም ወደ ዱር ሒዶ አራዊትን ያድን ዘንድ እንዲፈቅድለት አባቱን ለመነው በፈቀደለትም ጊዜ ወደ እናቱ ሒዶ "አራዊትን ለማደን ወደ በረሀ እሔዳለሁ" አላት እናቱም "የሰማይና የምድር አምላክ እግዚአብሔር በላይህ በረከትን ያሳድር" አለችው።
❤ ከዚህም በኋላ ከአርባ ፈረሰኞች አገልጋዮቹ ጋር ወጥቶ ሔደ መቅሉብ ወደሚባል ተራራም ደርሶ በዚያ አደረ። በሌሊትም የእግዚአብሔር መልአክ ጠራው እንዲህም አለው "መርምህናም ሆይ ተነሥተህ ወደዚህ ተራራ ላይ ውጣ ስሙ ማቴዎስ የሚባል ቅዱስ ሰው ታገኛለህ እርሱም የሕይወትን ነገር ይነግርሃል" ሲነጋም ወደ ተራራው ወጣ እንደ በግ ጠጉር ለብሶ አባ ማቴዎስን አገኘው መርምህናም በአየው ጊዜ ፈራ ቅዱስ አባ ማቴዎስ "ልጄ ሆይ ወደ እኔ ቅረብ እኔም የእግዚአብሔር ፍጥረቱ የሆንኩ እንዳንተ ሰው ነኝ" አለው። መርምህናምም "ከአባቴ አማልክቶች በቀር አምላክ አለን?" አለው አባ ማቴዎስም የክርስትና ሃይማኖትን ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክርስቶስን ህልውና በተለየ አካሉ ሰው መሆኑንና መከራ ተቀብሎ መሞቱን መነሣቱን ወደ ሰማይ ማረጉንም የፍርድ ቀንም እንዳ ለጻድቃን በጎ ዋጋ ለኃጢአተኞች ቅጣት እንዳለ አስተማረው። መርምህናምም "ከራስዋ እስከ እግርዋ ለምጽ የያዛት እኅት አለችኝ የአምላክህን ስም ጠርተህ በጸሎትህ ብታድናት እኔ አምንበታለሁ" አለው አባ ማቴዎስም "እኔ አድናታለሁ ና በአንድነት እንውረድ" አለው ከተራራው በወረዱ ጊዜ አባ ማቴዎስን በመንገድ ትቶ ቅዱስ መርምህናም ወደ እናቱ ሒዶ ሁሉን ነገራት እኅቱንም በሥውር ወደ አባ ማቴዎስ ወሰዳት አባ ማቴዎስም ወደ እግዚአብሔር ጸለየና ምድሪቱን አመሳቅሎ መታት በዚያን ጊዜ ውኃ መንጭቶ እንደ ባሕር ሆነ ወደ ባሕሩም አውርዶ እጁን በራሳቸው ላይ አድርጎ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው አሽከሮቹን አርባ ሰዎችንም ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው ወዲያውኑ ሣራ ከለምጽዋ ነጻች።
❤ ከዚህም በኋላ አባ ማቴዎስ ስለ ከበረ ስሙ በላያቸው የሚመጣውን መከራ በሚቀበሉ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን እንዲጸኑ መከራቸው ከዚህም በኋላ በላያቸው ጸለየና በፍቅ አንድነት አሰናበታቸው። ቅዱስ መርምህናምም በመጣ ጊዜ ወደ እናቱ ቤት ገባ ወደ አባቱ ወይም ወደ አማልክቶቹ አልሔደም አባቱም ሰምቶ ተቆጣ ወደ አማልክቶቹ ቤትም እንዲጠሩት አዘዘ ቅዱስ መርምህናም ግን ከእኅቱና ከሠራዊቱ ጋር ስሟ ቅሳር ወደ ምትባል ተራራ ሒዶ ከላይ ወጥቶ በዚያ ተቀመጠ።
❤ አባቱም በሰማ ጊዜ ከልብሰ መንግሥትና ከዘውድ ጋር መኳንንቱን "የመንግሥቴን ሥልጣን ተረከብ ብሎሃል" እንዲሉት ላካቸው እርሱ ግን በቊጣ ተመለከታቸውና "እኔ ክብር ይግባውና የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ፈጽሞ የማይጠፋ መንግሥት እሻለሁ" አላቸው። የአቶር ንጉሥ አባቱም በዚያን ጊዜ ተቆጣ ልቡ ፈርቶ ይመለስ ዘንድ አገልጋዮቹን በፊቱ እንዲገድሏቸው ካልተመለሰ ግን እርሱንም እኅቱንም እንዲገድሉ አዘዘ። ቅዱስ መርምህናምም ሰምቶ የተመኘውን ይሰጠው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ "ጸሎትህን ሰማሁ ልብህ የወደደውንም ሰጠሁህ" የሚል ቃል ከሰማይ መጣ። ከዚህም በኋላ የቅዱሳኑን ራሳቸውን በሰይፍ ቆረጡና ከጒድጓድ ውስጥ ጣሏቸው ሥጋቸውንም ያቃጥሉ ዘንድ ብዙ ዕንጨቶችን ሰበሰቡ ግን አላገኙአቸውም እግዚአብሔር ሠውሮዋቸዋልና።
❤ ወዲያውኑ ንውጽውጽታ ሆነ ፀሐይም ጨለመ ወታደሮችም ፈርተው ሸሹ ሰይጣንም በአቶር ንጉሥ በሰናክሬም ላይ አድሮ አሳበደው እንደእሪያም ጮኸ የቅዱስ መርምህናምም እናት አይታ ወደ አባ ማቴዎስ ልካ አስመጣችውና የንጉሡን ነገር ነገረችው እርሱም በዘይት ላይ ጸልዮ ቀባው ሰይጣንም በእሪያ አምሳል ከርሱ ወጣ። በዚንም ጊዜ ንጉሥ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ ከቤተ ሰቦቹና በሚገዛው አገር ካሉ ሰዎች ሁሉ ጋር ተጠመቀ።
❤ ከዚህም በኋላ አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን እንዲሠሩ ገንዘብንም ለድኆችና ለችግረኞች እንዲበትኑ አዘዘ ሁሉንም እንዳዘዛቸው አደረጉ። የቅዱስ መርምህናምም እናት ከከበሩ ደንጊያዎች አርባ ሣጥኖችን አሠራች የልጅዋ ጭፍራ የነበሩ የእነዚያን አርባ ሰማዕታት አጥንቶቻቸውን አሰብስባ በየአንዳንዱ ሣጥን ጨመረቻቸው ለልጆቿም ብርሌ ከሚመስል ዕንቊ ሁለት ሣጥን አሠርታ በውስጣቸው አድርጋ በሠራችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖረቻቸው ከሥጋቸውም ታላላቅ የሆኑ ቊጥር የሌላቸው ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ስምዖን፦ እርሱም በእስላሞች ዘመን ከመሳፍንቶቻቸው ከአንዱ ጋር ተከራከረና ቅዱስ ስምዖን ረትቶ አሳፈረው ያም እስላም ወደ መሳፍንቱ አለቃ ሒዶ "ይህ ስምዖን የእስላሞች ሃይማኖት ያቃልላል" ብሎ ወነጀለው ስለዚህም ይዘው በጽነዕ ሥቃይ አሠቃዩት ከዚያም በኋላ ራሱን በሰይፍ ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ስምዖን በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የውሲም_ኤጲስቆጶስ_አባ_ያዕቆብ ስርሷ የተናገረላት #የሮሜ_ንጉሥ_ልጅ_ቅድስት_ነሳሒት፦ እንዲህም አለ በአንዲት ዕለት አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያለሁ የገዳሙን ደጅ ሰው ሲያንኳኳ ሰማሁ ተነሥቼም ወደ በሩ ሔድኩ ያረጀ ዓጽፍ የለበሰ ፊቱንም የተሸፋፈነ ሰው አየሁ "ከወዴት መጣህ? ወዴትስ ትሔዳለህ?" አልሁት። "ከአባ መቃርዮስ ገዳም መጣሁ በዚች ሌሊት ከዚህ ገዳም አድሬ ቊርባንን መቀበል እሻለሁ" አለኝ። ያን ጊዜ ቀዳሚት ሰንበት ነበረች እኔም "ፊትህን ካላሳየኸኝ አልከፋትልህም" አልሁት እርሱም "ፊቴን ማየት አትሻ ፊቴ በኃጢአቴ የጨለመ ነውና ፊቴንም ለሚያይ የከፋች ሥራዬ ትታየዋለች" አለኝ። በከለከልኩትም ጊዜ ወደ ዱር ሊመለስ ወደደ እኔም ተርቦ ወይም ተጠምቶ እንደሆነ ብዬ በልቤ አሰብኩ ስለዚህም ከፈትኩለትና ወደ ማደሪያዬ አስገባሁት መብልንም አመጣሁለት እርሱም "ከነገ ከቊርባን በኋላ በቀር እኔ አልበላም" በማለት እምቢ አለኝ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ ቆመ ላዕሌየ ሰማዕተ ዓመፃ። ወሐሰት ርእሰ ዓመፃ። እትአመን ከመ እርአይ ሠናይቶ በእግዚአብሔር በብሔረ ሕያዋን"። መዝ 26፥12-13 ወይም መዝ 86፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ተሰ 4፥15-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 1፥10-13 እና የሐዋ ሥራ 10፥9-17። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥26-34። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ወይም የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ሩፋኤል በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
