ሰማያዊ ወግ (The tradition of heaven)
前往频道在 Telegram
ንጉስ ዳዊት፣ ለልጁ ሰሎሞን "በርታ ሰውም ሁን!!" እንዳለው፤ ጳውሎስም "...በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት ሙሉ ሰውም ወደመሆን" እንዳለው፣ ሰው ለመሆን ሰማያዊ ወጎችን እናወጋለን።
显示更多477
订阅者
无数据24 小时
+57 天
+230 天
帖子存档
እግዚአብሔር በአላት።
የእስራኤል ህዝብ ከግብፅ ባርነት እንደወጣ በየመንገዱ በአል ያደርግ ነበር፣ ድንኳን የመትከል በአል፣ ድንኳን የማንሳት በአል፣ የሞሎት የኮከቦች በአል፣ የወርቅ ጥጃ በአል፣ የሞአብና ምድያም መስዋእት በአል፣ የመናፍስት መጠየቅ በአል፣ ለአማልክት መስዋእት ማቅረብ በአል፣ የልጆች መስዋእት ለሞሎክ በአል... እጅግ ብዙ በአላትን ከአህዛብ ተቀብለው ሲያከብሩ ይውሉ ነበር።
እግዚአብሔር ለእርስቱ የመረጠው ህዝብ ያገኘውን ሁሉ የሚያከብር ሆነ፣ የሌሎች አማልክትን በአል ያክበራሉ።
በኛ ዘመን ብዙ የአህዛብ በአል ሳይታወቀን እየወረሰን ነው፣ ገና ትምህርት ለሚጀምሩ ህፃናት በየቤቱ በአል ይደረጋል፣ በተባበሩት መንግስታት አማካይነት ብዙ የስላቅ በአላት አለ። የውሸት ቀን፣ የትራስ ቀን፣ የሰነፍ ቀን፣ የፒዛ ቀን፣ የቸኮሎት ቀን... እኚህን የመሰሉ አስቂኝ ቀኖች ይከበራሉ፣ አላማቸውም ገብያ ነው፣ እኛም እናከብራቸዋለን። ሰማይ ሳይሆን ገብያ የሚመራውን በአል እናከብራለን።
ክርስቲያን እግዚአብሔርን ያህል አፍቃሪ፣ ክርስቶስን ያህል ባለፀጋ መንፈስ ቅዱስን ያህል አፅናኝ እያለው፣ ቀኖችን በአህዛብ አምላክ አይዋጅም።
ለእግዚአብሔር የምስጋና ቀን ማወጅ ትልቅ በረከት ነው፣ አህዛብ እንደሚያደርጉ በየወቅቱ ለመብላትና ለመጨፈር መነሳት እግዚአብሄራዊ አይደለም።
ኢሳያስ፣ መባቻችሁንና በዓላቶቻችሁን ነፍሴ ጠልታለች፤ ሸክም ሆነውብኛል፥ ልታገሣቸውም ደክሜያለሁ። ይላል እግዚአብሔር ብሎ ተናግሯል። ኢሳ 1:14
ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ መልካም ነው፣ ለእግዚአብሔር የምስጋና ቀን ማወጅ ድንቅ ነው፣ በእግዚአብሔር በራሱ ደስ መሰኘት መባረክ ነው፣ ነገር ግን እግዚአብሔር የሌለበት፣ ክርስቶስ የሌለበት በአል ብክነት ነው።
ዛሬ የስላሴን በአል ያከበራችሁ፣ ክብር አይጉደልባችሁ።
የኔ ምስክርነት። ፪
(እግዚአብሔር አይቷል።)
የሥነ ልቦና ጉዳት እውነት መሆኑን የምመሰክር ነኝ፣ ሁሉ ቢችል በተግባር ባይችል በዘዴ የስነ ልቦና ጥቃት አድራሽ ነው። ያለፈው ህይወቴ ልክ እንዳሁኑ ሁኖ ይሰማኛል።
ጌታ እንዲህ ያደረገ ይመስለኛል። ሁል ጊዜ ፊቴ የተገተረውን ትልቅ ቋጥኝ "ግፋው" የሚለኝ ልክ እንዳለኝ ያን ቋጥኝ ስገፋ ብውልም ቋጥኙ ንቅንቅ የማይል።
ጌታ ያደረገው ፊቴ የተገተረውን ቋጥኝ ማንሳት አይደለም፣ እሱ ያደረገው፣ እኔን ማጠንከር ነው፣ አሁን እኔ ጠንካራ ነኝ፣ ፊቴ በተነጠፉት ብዙ ችግሮች መሃል ጌታ ብርቱ አድርጎኛል፣ በዘመኔ የሚገዳደሩኝን ሁሉ ክርስቶስ አይቷልና ብርቱ ያደርገኛል።
ሰዎች ድሮ ባሳለፍኩት ችግር ዛሬም እንደ ድሮ እንደሚያዩኝ አስተውያለሁ፣ ጌታ ሰውን እንደሚለውጥ እረስተዋል። ያ የድሬ ህፃንነቴን ዛሬም በእኔ ላይ ያዩታል። በድሮ ስህተቴ ዛሬም እነሱ ልክ እንደሆኑ ያስባሉ። ሁሉ መለወጡን አውቃለሁ፣ ኢየሱስ ለውጦኛል።
ክፉ መናፍስት እንዳሉ የምመሰክር ነኝ፣ ክፉ መናፍስት ሰዎችን በተለያዩ ክፉ ልማድ እንደሚጠምዱ አውቃለሁ፣ ክፉ መናፍስት ጩኾ የሚወጣው ብቻ እንዳይመስላችሁ፣ መፅሀፍ ቅዱስ ቤታችሁ እያለ ካላነበባችሁ፣ የቅዱሳን ህብረትን ከናቃችሁ፣ ሰዎች ለእግዚአብሔር ሲዘምሩ ምንም ካልተሰማችሁ የጌታን ስም ስትሰሙ ችላ ካላችሁ ክፉ መናፍስትን ጠርጥርሩ። ሰዎች ሁሉ ከዚህ እንዲጠበቁ እመሰክራለሁ። ለእየሱስ ስሜት አትጡ።
ሐዘንና ጥፋት እውነት መሆናቸውን እመሰክራለሁ፣ ነገር ግን ከዚህ ሁሉ የሚበልጥ ኃያሉ ኢየሱስ እንዳለም እመሰክራለሁ፣ "ይሄ ሀዘን" ካልኩበት በርትቻለሁ። "የጥፋት መጨረሻ" ካልኩበት ተስፋን ተሞልቼ አይቻለሁ። ፈገግታዬን የቀማ "በዛው ቀርቷል" ስል ጌታዬ አፌን በሳቅ ሞልቶች አይቻለሁ። ይሄን ያደረገ እግዚአብሔር እንደሆነ የምመሰክር ነኝ።...
በርጤሜዎስ እና የሰፈራችን ለማኝ።
እንዲህ ያለ ነገር በየሰፈራችሁ ሰምታችሁ ይሆናል፣ እኛ ከመወለዳችን በፊት በልመና የሚተዳደሩ፣ አስፋልት ዳር የላስኪት ቤት ሰርተው ይኖራሉ፣ እዛው ይለምናሉ፣ እዛው ይኖራሉ።
ልጆች ሆነን ወደ ትምህርት ቤት ስንሄድ እናያቸዋለን፣ እኚህን የኔ ብጤ ሰላም እንላቸዋለን እሳቸውም "ልጆቼ" ይሉናል። አንድ ቀን ግን የሆነ ነገር ተከሰተ።
በጠዋት ወደ ትምህርት ቤት ስንሄድ ፖሊስና ህዝቡ የአባባን የላስቲክ ቤት ከቦ ቆሟል፣ ስንጠጋ ለካ አባባ ሞተው ተገኝተው ነው። ማታ ሞተው አደሩ።
እሬሳቸውን አምፑላንስ መጥቶ ወሰደው። በኋላ አስገራሚ ነገር አየን፣ የአባባን ቤት የሞላው ቡትቶ ወጥቶ ወጥቶ ወጥቶ አላልቅ አለ። የሚያስገርመው ከዛች ደሳሳ ጎጆ ዘመናቸውን ሙሉ የለመኑት ሳንቲም ከብዛቱ የተነሳ በማዳበሪያ ታፈሰ።
ለቁጥር የሚያታክት አሮጌ ብሮች ታፍሶ ወጣ፣ በኋላ እንደሰማነው ብሩ ሲቆጠር ብዙ ሺ ሁኖ ነበር፣ አባባ ህይወታቸውን የሚቀይር ብር የነበራቸው ቢሆንም ከቡትቶዋቸው ጋር ኖረው ሞቱ።
በርጤሜዎስ እንደዚህ ያለ ሰው ነበር፣ በርጤሜዎስ ጌታን ባያገኝ ኖሮ፣ ከኮተቱ አይገላገልም ነበር። እሱ ግን እንደፈራችን ለማኝ አልነበረም፣ ጌታን እንዳየ "እባክህ እራራልኝ" ብሎ ጮኸ፣ ጌታም ራራለት።
የእየሱስ ኮቴ ሲሰማ አብዝቶ ተጣራ፣ እስከ ዛሬ የሰበሰብኩትን ሳይል ኮተቱን ጥሎ ወደ ጌታ ገሰገሰ፣ አይኑ በራለት፣ ጌታን ተከተለ።
በዚህ ዘመን የሚያዋጣን ላይጠቅመን የሰበሰብነውን ቡትቶ መጣል ነው። የማይጠቅም ነገር ተሸክሞ የሚጠቅመንን ኢየሱስን መጣል አይበጀነም።
ጌታን መከተል የማይጠቅም ቡትቶ ያስጥላል፣ እርሱን ለመከተል ስንነሳ የተቀመጥንበት ብዙ ኮተት ይራገፋል።
ከጌታ ጋር ስንሆን ነው ያለንን በደስታ ልንጠቀም የምንችለው። ጌታ ከሌለ የማንጠቀምበት ቡትቶ ውስጥ ነን።
የኔ ምስክርነት።
እግዚአብሔር አይቷል።
ኪሳራዎች ተከታትለው ቢመጡ፣ የምንወዳቸው ሰዎች ሁል ጊዜ ከጎኔ ይሆናሉ ያልኳቸው ባይታመኑ፣ ያመኑትን ማጣት ከራስ አካል የተቆረጠ ያህል ስሜት ሲሰማኝ እግዚአብሔር አይቷል።
ሀዘን በሃዘን ላይ፣ ስቃይ በስቃይ ላይ ቢደራረብ፣ መንፈሳዊ አካላዊና አእምሮአዊ ጦርነት ውስጥ እራሴን ሳገኝ እግዚአብሔር አይቷል።
እግዚአብሔር ማንንም ለዘላለም አይተውም፣ እያንዳንዷን ግፍ አይቷል። እርሱ በእኔ ላይ የተፈጸመውን እያንዳንዱን ግፍ አይቷል። እያንዳንዱን ቁስል አይቷል። እያንዳንዷ እንባ አይቷል። "ብቻዬን ነኝ!" ብዬ የተሰማኝን እያንዳንዷን ቅጽበት አይቷል። እግዚአብሔር አይቷል።
እግዚአብሔር የተሸከመኝ ሰው ነኝ። የተረፍሁት ጠንካራ ስለነበርሁ አይደለም፤ እግዚአብሔር ስለተሸከመኝ ነው።
ጠላት መቃብር ሊያደርግልኝ ያሰበውን ስፍራ እግዚአብሔር የምስክርነት መድረክ ያደርገዋል።
ጠላት በኀፍረት ሲያራቁተኝ እግዚአብሔር ግን የክብር ልብስ አድርጎልኛል። እሱ በሃጥያት እርቃን ቢያስቀረኝም፣ እግዚአብሔር የቆዳ ልብስ አልብሶኛል፣ ያውም ውብ የፀጋ ልብስ አልብሶኛል።
እግዚአብሔር አይቷልና በግድ የተጫነብኝን ዝምታ አስወግዶ፣ በኃይል የሚናገር ድምፅ ሰጠኝ፣ ተመስገን የማለት ድምፅ ሰጠኝ። እግዚአብሔር በእሳቱ ውስጥ አብሮኝ እንደተጓዘ አውቃለው፣ ስለዚህ እሳት ውስጥ ሁኜ እመሰክርለታለሁ። እግዚአብሔር እያየ ነው እላለሁ።
የእኔ ምስክርነት "ፈጽሞ ወድቄ አላውቅም!" የሚል አይደለም፤ በወደቅሁ ቁጥር ሁሉ እግዚአብሔር እንዳነሳኝ እናገራለሁ።
የእኔ ምስክርነት "ፈጽሞ አላጣሁም" አይደለም፤ ጠላት ሊሰርቀኝ የሞከረውን እግዚአብሔር አብዝቶ እንደመለሰልኝ እናገራለሁ።
እኔ ሁል ጊዜ ከሞት የተረፍሁ ሰው ነኝ፤ እኔ ይሄን የምመሰክር ህያው የእግዚአብሔር ምስክር ነኝ። .... እቀጥላለሁ
አንተ ይህን ለእኔ አደረግህ።
በአሜሪካ የአሪዞና ግዛት፣ የሚገኝ ውብ ቦታ አለ። ድንጋዮችና በዛፎች መካከል ወደ ተራራው የሚወጣ መንገድ አለ፣ ጌታ ኢየሱስ ወደ መስቀል እየሄደ ካለፈባቸው መንገዶች አሥራ ሁለቱን ደረጃዎች የሚያሳዩ ቅርጻ ቅርጾች ተቀምጠዋል።
ይህን ቦታ ከማየቴ ከሁለት ዓመት በፊት ስለቦታው ሕልም አይቼ ነበር። በኋላ በእውነት ሳየው ወዲያውኑ አወቅሁት፣ ያሳየኝ መንፈስ ቅዱስ ነበር። ከዚያ ቦታ ጥቂት ርቀት ላይ ቤት አገኘሁ፣ ከዚያ በኋላ ወደዛ ስፍራ መሄዴን አላቋረጥኩም።
ቦታው ጥገና ያስፈልገው ነበር። እየሱስ የተጓዘባቸው መታሰሚያዎች አጥሩ በመውደቅ ላይ ነበር። በዛ ያገኘሁት አረጋዊው የወደቁትን በመጠገን እንድረዳው ጠየቀኝ። አጥሮቹ ከባድ የባቡር ሃዲድ እንጨቶች ሲሆኑ በተለያየ ርዝመት ተቆርጠው የተሰሩ ነበሩ።
ለመርዳት ተስማማሁ፤ ጠንካራ ወንድ ጓደኞቼ ያግዙኛል ብዬ በማሰብ። ነገር ግን ማንም አልመጣም።
ቃሌን ማፍረስ ስላልፈለግሁ፣ ራሴ ልሠራው ጀመርሁ። መጀመሪያ አጫጭር እንጨቶቹን ወደ ተራራው ወጥቼ አንድ በአንድ አውርጄ ወደ ታች አመጣኋቸው። ከዚያ ግን ረጅጅሞቹና እጅግ ከባዶቹ ቀሩ።
ከእነርሱ አንዱን በትከሻዬ ተሸክሜ ተራራውን መውረድ ጀመርሁ። እንጨቱ ከኋላዬ ባለው ደረጃ ተጣብቆ መሬት ላይ ጣለኝ፤ አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን ደጋግሞ ጣለኝ።
ያኔም፣ “እንዴት ያለችው ሞኟ ነኝ እንዴት ልሰራው ተስማማሁ?” አልኩ። ጀርባዬ ይታመም ነበር፣ በጣምም ህመም ውስጥ ነበርሁ።
በዚያን ጊዜ ግን እየጸለየ የሚያሳየው የጌታ ኢየሱስ ሐውልት ዓይኔን ሳበው። በዚያ ቅጽበት እንዲህ ብዬ አሰብሁ፦ “አንተ ይህን ሁሉ ለእኔ አድርገሃል። አንተ ይሄን ተራራ ወደ ላይ ወጣኸው፣ እኔ ወደታች መጎተት አቃተኝ።" ያን ጊዜ በልባዊ አመስጋኝነት ሥራዬን ቀጠልሁ።
ይሄ ረቤካ እውነተኛ ምስክርነት ነው።
አለማዊ ድግስ ፪
ለሁሉ የሚሆን የምስራች
ወቅቱ የአለም ዋንጫ የሚካሄድበት ነው፣ በቤታችን የተለያየ ቡድን እንደግፋለን። አንዱ ሲደሰት አንዱ ያዝናል። አንዱ የምደግፈው ቡድን ስለማይጫወት "አላይም" ብሎ ይተኛል።
የሚደግፈው ቡድን ያሸነፈለት በደስታ ይቦርቃል፣ የተሸነፈበት ይበሳጫል የተኙትን ይረብሻል። ጉዳዩ እግር ኳስ ነውና አንቀያየምም።
ሀገራቸው የተሸነፈባቸው ስቅስቅ ብለው ሲያለቅሱ በቴሌቭዥን መስኮት አይተናል፣ አሸናፊ ሀገሮችም በደስታ ሲቃ ያነባሉ አይተናል፣ እግር ኳስ ነውና አንዱ ሊያዝን አንዱ ይደሰታል።
አሸናፊዎች ከደስታቸው መለስ ሲሉ በሃዘን ልባቸው የተሰበረውን ያፅናናሉ። እግር ኳስ ነው፣ አቻነት የለም፣ ወይ መሸነፍ ወይ ማሸነፍ ብቻ ነው። ለሁሉ ደስታን የማይሰጥ ስፖርት ነው።
በዚህ የአለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳተፉት ሀገራት 48 ቢሆኑም ይሄን ውድድር አሸንፎ የሚደሰተው አንድ ቡድን ብቻ ነው። ቀሪዎቹ 47 ቡድንኖች በየተራ እያዘኑ ይሰናበታሉ።
በዚህ ምድር ለሁሉ የምስራች የሆነ ዜና የለም። የአንዱ ደስታ የአንዱ ሀዘን ነው። የአንዱ የምስራች የአንዱ መርዶ ነው። ለአንዱ ድል ለአንዱ ሽንፈት ነው።
በዚህ ምድር ለሁሉ የምስራች የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው።
ከሰማይ የመጣ የምስራች፣ ለእረኞች የተነገረ ታላቅ የምስራች የመልአኩ ቃል "ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁ" ያለለት ኢየሱስ ነው። ሉቃ 2:10
በዚህ ምድር ለሁሉ የሚሆን የምስራች አንድ ብቻ ነው፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሁሉ እድሜ፣ ለሁሉ እውቀት ሁሉን ደስ የሚያሰኝ የምስራች ነው።
ለአንድ ቦታ ብቻ ለዚህ ስፍራ የማይባል፣ ለሁሉ ድንቅ የምስራች ኢየሱስ ነው። ስለ ኢየሱስ መስማት ለሁሉ ታላቅ የምስራች ነው። ከቶም ሀዘን የለበትም። የሁሉ ፈገግታ ኢየሱስ።....
ኢየሱስን የት አቆማችሁት??
ደጋግሞ ቢያንኳኳም ወደ በሩ የመጣ የለም። ከውስጥ የአምልኮ ድምፅ ይሰማል፣ ፀሎቱና ዝማሬው ልዩ ነው፣ ከበር ቆሞ የሚያንኳኳውን ግን የሚሰማው የለም። እራሱ ከፍቶ እንዳይገባ ከውጭ በኩል መክፈቻ የለውም። ተስፋ ቆርጦ ወደ ኋላ አፈገፈገ።
አይኖቹ የሚያበሩ፣ የልብሶቹ ንጣት በቃላት የማይገለፅ፣ ፈገግታው አካባቢውን ሁሉ ወገግ የሚያደርግ ሰው ከበሩ ጥግ ቆሟል።
"ምን እያደረክ ነው ልጄ?" አለኝ፣
"ወደ ውስጥ ገብቼ አብሬያቸው መሆን ፈልጌ ነበር፣ ግን አልከፈቱልኝም" አልኩት።
"እኔም ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ ከበር ቆሜ እያንኳኳሁ ነው፣ ማንም አልከፈተልኝም" አለኝ። ማን እንደሆነ በንግግሩ ለየሁት።
"ጌታ ሆይ ወደዚህ ቤት መግባት የፈለኩት አንተን ፈልጌ ነው፣ አንተም በደጅ ቆመሃል" አልኩት። ተንደርድሬ በእቅፉ ውስጥ ገባሁ፣ የምፈልገው ይሄን ነበር።
በዘመናችን ያለ ክርስትና ጌታን በደጅ የተወ ይመስላል፣ ሁላችን በውስጥ ነን፣ ጌታ ግን በደጅ።
ብዙ ስርአቶች እንፈፅማለን እርሱ ሳይኖር ያገኘነው ይመስለናል፣ እንስታለን።
ጌታ እየሱስ እነማን ቤት እያኳኳ ይሆን?? እኛ ሁላችንም የራሳችንን አማልክት በየቤታችን ሰርተናል። እስራኤል በበረሃ እንደሳተ፣ እኛም እምነታችንን አቅልጠን ጥጃችንን ሰርተናል፣ "አምላካችን ይሄ ነው" እያልን በየቤታችን በዐል አድርገናል።
በክርስቶስ ላይ ዘግቶ ክርስቶስን መፈለግ ሞኝነት ነው!! ለክርስቶስ የተዘጋ ልብ ክፍት አይደለም። የክርስቶስን ድምፅ የማያውቅ እንዴት መጣራት ቻለ?
በዚህ ዘመን ክርስቶስ በልባችን ደጅ ቆሞ ሲያንኳኳ አየዋለሁ፣ በምንኖርበት ቤት ከበራፋችን ቆሞ ይታየኛል፣ ልናመልከው በቆምንበትም ቤተ መቅደስ ከደጅ ቆሞ ሲያንኳኳ በምናቤ አየዋለሁ፣ እርሱ ላይ ዘግተን እርሱን እንፈልጋለን፣ ማስተዋል ይሁንልን።....
የሰሊጥ አገልግሎት
(የበደሉንን ይቅር እንደምንል)
በወንድማማችነት ይኖሩ የነበሩት ህዝቦች በብሄር ተከፋፍለው ተገዳደሉ፣ በአንድ ቤተ ክርስቲያን ያመልኩ የነበሩ ተገዳደሉ በህይወት ያሉትም ለመገዳደል ይፈላለጋሉ።
ከዝች ከተማ ስልክ ተደወለልኝ "በጣም አዝነንባችኋል፣ በደጉ ዘመን ብዙ የነበራችሁት አገልጋዮች ዛሬ የላችሁም። ሰሊጥ በነበረን ጊዜ ህዝባችን ታገለግሉ የነበራችሁ፣ ዛሬ ሰሊጣችንን በጦርነት ስናጣ ቀራችሁ፣ እኛን ሳይሆን ሰሊጡን ነበር የምትፈልጉት" አለኝ፣ "ይኸው ብዙ አመት ሆነን አገልጋይ አጥተን" አለኝ። በደጉ ዘመን ህዝቡ ለአገልጋይ የፍቅር ስጦታ እያለ ብዙ የሚሰጥ ህዝብ ነበር። ዛሬ ሰው የሚሆናቸው አጡ።
በደዋዩ ሰው መልእክት ልቤ ተነካ "እውነትህን ነው፣ በቃ እንመጣለን ጠብቁን" አልኩት ቦታው ምናልባት አደገኛ ሊሆን ይችላል፣ ቢሆንም ከጓደኛዬ ጋር ለመሄድ ቆረጥን።
ህዝቡ ቤተ ክርስቲያኗን ሞልቶ ጠበቀን። ፕሮግራሙ ሲጀመር ህዝቡ ፊት ተንበረከክን "ይቅርታ አድርጉልን፣ እኛ የሰበክነው የሰላም ወንጌል ፍሬ ስላላፈራ፣ እኛ የሰበክነው ወንጌል መጋደልን ስላላቆመ። በችግራችሁ ጊዜ ምን ሆናችሁ? ብለን ስላልመጣን ይቅር በሉ" ብለን አለቀስን፣ ምእመኑም አብሮን አለቀሰ። ይቅርታ አደረጉልን።
አንዲት ሴት እያለቀሰች፣ ወደ አንድ ሰው ጠቆመችኝ "እሱ ነው አባቴን የገደለው፣ ግን ይቅር እለዋለሁ" ብላ ወደ ስውዬው አቀናች "በዚህ ምድር አባቴን ነጥቀኸኛል፣ አሁን ደሞ እየሱስን እንድትነጥቀኝ አልፈልግም" ብላ ይቅር አለችው። በይቅርታ አለቀስን።
ወደ ገዳዩ ቀርበን ፀለይን ስንፀልይ አጋንንት ከሰውዬው ላይ አጓርቶ ወጣ። ለካ ገዳዩ ሰው አይደለም።
የዚህ ታሪክ መስካሪ የወንጌል አገልጋዩ ሁሴን መሃመድ ነው። በዚህ ዘመን ሰው ከአውሬ በላይ እየፈራን ነው። ሰው መንፈስ ቅዱስ ሲርቀው አውሬ ይሆናል።
አለማዊ ድግስ!!!
ጊዜው የአለም ዋንጫ ወቅት ነው፣ ቢሆንም ስቴድየም ገብቶ ለመመልከት እጅግ ውድ ሁኗል።
በዚህ ጊዜ ድሃ ሃገራት ኳስን ማትና መጫወት የማይችሉበት ዘመን ላይ ደርሰናል። እንደ ጥንቱ ዘመን እግር ኳስ በነፃ የሚከናወን ስፖርት መሆኑ ቀርቷል።
ዘማች በንኪ የሚባል tik tok ላይ አጫጭር ግሩም መልእክት የሚያስተላልፍ ሰው እንዲህ አለ። "እኔ የምኖረው በአሜሪካ ነው፣ የአለም ዋንጫ እየተከናወነ ቢሆንም እያየሁ አይደለም፣ እኔ እዚህ የምሰራው ኳስ የሚያዩትን ዜጎችና እንግዶች ከኤርፖርት ወደ ሆቴል፣ ከሆቴል ወደ ስታዲየም በሹፍርና ማመላለስ ነው። እዚህ ያለ ዲዬስፖራ ሁሉ ስራው ይሄ ነው፣ በሹፍርና ተመልካቾችን እናመላልሳለን እንጂ ኳሱን አንመለከትም" ይላል።
"እዚህ መኖራችን ከትኩረታችን ዞር አያደርገንም፣ ሁላችንም የምናስበው አንድ ቀን ጥሪት ይዘን ወደ ሀገራችን መግባት ነው፣ አለም በምታዘጋጀው ድግስ ሁሉ ትኬት የምቆርጥ ከሆነ ሀገራችን መግቢያ ቤሳቤስቲን አይኖረንም። ውድ የሆነውን የአለም ዋንጫ መግቢያ ከፍለን የምገባ ከሆነ መቼም ቢሆን ሃገራችን አንገባም" በማለት መልእክቱን ያስተላልፋል።
ክርስቲያን እንደዚህ ነው። ሀገር አለን የሚጠብቃት፣ የምንናፍቃት፣ እዚህ ባለው ነገር ላይ ጉልበትም ሃብትም አናባክንም። በዚህ ምድር ስንኖር አሜሪካ እንዳሉት ሹፌሮች ሰዎችን ወደሚፈልጉት እናደርሳለን።
በዚህ በምፃተኝነት በምንኖርበት ምድር ሰዎች ወደ ገቡበት ሁሉ አንገባም፣ ሰዎች ወደ ገቡበት ሁሉ ብንገባ ከሀገራችን እንቀራለን። እዚህ ሰዎችን ወድደ ፣ ጌታ ወደ ዘላለማዊ ህይወት እየመራን እናደርሳለን።
ምድር በምታዘጋጀው ወጥመድ እንዳንታለል ሃሳቧን አንስተውም። ማስተዋል ይሁንልን።
ሰማያዊ መንግሥት
፫
ኢየሱስ መንግስቱ ከዚህ ምድር አይደለምና ተራበ፣ ተጠማ፣ ታረዘ፣ ተጎሳቆለ። ሰማይ ምድር የእርሱ ቢሆንም ምንም እንደሌለው ብቸኛ ሆነ። እልፍ አእላፍ መላእክት የሚሰግዱለት ቢሆንም ምንም እንደሌለው የህማም ሰው ሆነ።
መንግስቱ ከዚህ ምድር አይደለችምና ምድርን በመዳፉ የያዘ ጌታ እጁ ሲጎተት ዝም አለ። ሁሉ በእርሱ ተጋጥሞ ሳለ ሁሉ ፊቱን ሲያዞርበት ዝም አለ።
መንግስቱ ከዚህ አይደለምና የሚወዳቸው ከአጠገቡ ሲወሰዱ ዝም አለ፣ መጥምቁ ዮሃንስ እንገቱ ሲቀላ ዝም ብሎ አየ፣ እሱን የሚከተሉት አሳዳጅ ሲበዛባቸው ዝም አለ።
መንግስቱ ከዚህ ምድር አይደለችምና የመረጣቸው ሃዋርያት በአደባባይ ሲሰቀሉ፣ በድንጋይ ሲወገሩ፣ ከቤተ መቅደስ ጫፍ ተወርውረው ሲፈጠፈጡ፣ በዘይት ሲቀቀሉ፣ በመጋዝ ሲሰነጠቁ ዝም አለ።
ዛሬም በዘመኔ እንዲሁ ነው፣ ግፉአን ድሆችን ሲጠሉ፣ ከሚኖሩበት ስፍራ ሲያፈናቅሉ፣ ቤተ መቅደስ እፍርሰው ቤተ መንግስት ሲሰሩ ኢየሱስ ዝም ይላል፣ ሃይሉ ብዙ ቢሆንም ስለ ፍቅሩ ይታገሳል።
በመንግስቱ እስኪመጣ ድረስ መንግስታትን ይታገሳል። ቅዱሳንን ሲያስጨንቁ ይታገሳል።
እግዚአብሔር ሰውን እጅግ ይወዳል። ሰው ሲወድቅ ሰውን ለማዳን ሰው ሁኖ መጣ፣ ዛሬ የእግዚአብሔር ማደሪያ ቅዱስ ቤተ መቅደስ ሰው ነው። ሰውን መጉዳት የእግዚአብሔርን መጉዳት ነው።
ሰውን መግደል መቅደስ ማፍረስ ነው። ኢየሱስ የሞተለት ሰው ሲነካ፣ ገበሬ መንገድ ሲያጣ፣ አዛውንቶች ማረፊያ ሲያጡ፣ ሴቶች በፍርሃት ሲዋጡ ፣ ወንዶች መራመጃ ሲያጡ ኢየሱስ ክርስቶስ ዝም የሚለው መንግስቱ ከዚህ ስላልሆነ ነው።
የነገስታት ንጉስ በቅርቡ ሃይሉን ያሳያል የዛን ጊዜ የምድር ሃያላን ዋይ ዋይ ይላሉ። የዛኔ ክፉ ጉልበተኞች ተራሮችን ደብቁን ይላሉ፣ ተራሮችን ግን ይቀልጡባቸዋል። ኢየሱስ በቅርቡ ያመኑትን ሊያስጥል ይመጣል።
ሰማያዊ መንግሥት
፪
የዚህ ምድር ገዢዎች ግዛታቸውና መንግስታቸው እዚህ ብቻ ነው፣ ታላላቅ ቤተ መንግስት እና ጠባቂዎችን ያደርጋሉ የዚህ ምድር ናቸውና አያስገርምም።
የፅድቅ መልአክ እስኪመስሉ ድረስ ቢያወሩም ተግባራቸው ግን ሌላ ነው። ቅድሚያ የሚሰጡት ለራሳቸው ብቻ ነው። ለስልጣናቸው አምላክንም ቢሆን መስዋእት ያደርጋሉ። ምድራዊ ናቸው በቃኝ አይሉም።
የእስራኤል ህዝብ መሪ እግዚአብሔር ነበር፣ እነሱ ግን እንደ አህዛብ በአይን የሚታይ ፈለጉ። "ሰው ይሾምልን" አሉ። ሰውን አስቀደሙ።
እግዚአብሔርም የሚሆንባቸውን ነገራቸው፣ ወንዶች ልጆቻችሁን ወታደር፣ ሴቶች ልጆቻችሁን ሽቶ ቀማሚ ያደርግባችኋል፣ ግብር እያለ ምርጥ ነገራችሁን ይወስድባችኋል አላቸው፣ እነሱም ባለማስተዋል ይሁን ሰው ይምራን አሉ። በቃ ከዛ ጊዜ ጀምሮ ሰው ጤና አላገኘም።
እኛ ሁላችን እንዲህ ሁነናል፣ የሚመራን ሰው ይመስለናል፣ በሁሉ ቦታ የሚኖረውን እግዚአብሔር ትተን በአይን የሚታይ ውሱን ነገር እንፈልጋለን። አይናችን እግዚአብሔርን ማየት ስላልቻለ የሌለ ይመስለናል።
በልባችን የሞላውን እግዚአብሔርን አናስተውለውም። እኛም እንደ አባቶቻችን ጣኦት ሰርተናል።
እግዚአብሔር የታል አሳዩን እንላለን፣ እነሱም እንደ አሮን ጣኦት ቀርፀው ይኸው ይሉናል፣ ሞኝ ሆነናል።
ቤተ ክርስቲያንም ሃዋርያዊት ናት፣ ሁሉንም በዚህ ምድር ለማከማቸት የምትኖር አይደለችም። ተጓዝ ጓዝ አያበዛም፣ ቤተ ክርስቲያን ጌታ በመጣ ጊዜ የምትነጠቅ ናት፣ በዚህ ምድር ያላት በክርስቶስ ላይ ያላት እምነቷ ብቻ ነው። መንግስቷ ከዚህ ምድር አይደለምና መንፈሳዊ ሃይል እንጂ ምድራዊ ሃይል የላትም።
ሁላችንም ሰማያዊ ሃብት እንጂ ምድራዊ ሃብት የለንም፣ ሰማያዊ ቤት እንጂ ምድራዊ ቤት የለንም። በምድር እንኖራለን እንጂ የሰማዩን መንግስት የምንጠባበቅ ነን።
...
ሰማያዊ መንግስት።
እግዚአብሔር ማዳንን ለሰው ልጆች አልሰጠም፣ ማዳን የሰው እጅ ስራ አይደለም። ማዳንን ለሰው እጅ ያልሰጠ እግዚአብሔር ይመስገን።
ምድራዊ መንግስት ለሁሉ ያስከፍላል፣ ኢየሱስ ግን መንግስቱ ከዚህ አለም ስላልሆነ ማዳኑን በነፃ ሰጠን። ምድራዊ መንግስት ጉልበት ባገኘ ቁጥር ጭንቅ ነው፣ እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ያዘጋጀውን እየወረሱ ይሸጣል።
በምድራዊ መንግስት ሁሉ በሽያጭ የሚገኝ ነው። አየርን እንኳን የሚቆጣጠር ቢሆን ግዙኝ ይለን ነበር።
እግዚአብሔር ውሃን ሲፈጥት ምድራዊ መንግስት ውሃን ተቆጣጥሮ በገንዘብ ይሸጣል፣ እግዚአብሔር ተራሮችን ፈጠረ መንግስት ተራሮችን አጥሮ ህፃናት እንደልብ እንዳይቦርቁ ከፍለው እንዲገቡ ያደርጋሉ።
እግዚአብሔር ምድርና መኖሪያን ፈጠረ፣ ሃያላን ግን ምድርን ተቆጣጥረው ለመኖሪያ እጅግ ውድ ገንዘብ ያስከፍላሉ፣ መክፈል ያልቻለ ጎዳና ይጣላል።
በምድር በነፃ የሚገኝ ነገር የለም፣
ዛሬ የሰፈር ሜዳዎች ታጥረዋል፣ ህፃናት ገብተው ለመጫወት ይከፍላሉ። በየሰፈራችን ያሉ ክፍት ቦታዎች በመንግስታት ቁጥጥር ስር ናቸው፣ ሰዎች በፈለጉ ጊዜ ሊጠቀሙባቸው አይችሉም።
ያደግንባቸው ቤተ እምነቶች እንኳን ኳስ ሜዳዎችን እያጠሩ በኪራይ ያስከፍላሉ። የሰማይ መንግስት ወኪል የሆኑት ቤተ እምነቶች እንደ ምድራዊ መንግስት አዳራሾችን ያከራያሉ።
ምድራዊ መንግስት በፍፁም አገልጋይ አይደለም፣ ምድራዊ መንግስት በፍፁም ለሰው ብሎ አይሰራል። ምድራዊ መንግስት ለራሱ ዙፋን ብቻ ይሰራል። ከምድራዊ መንግስት ደግነት ፈፅሞ የለውም።
ጌታ ኢየሱስ በጲላጦስ ፊት ቆሞ በነበረ ጊዜ፣ "ልፈታህ ወይም ልፈርድብህ እንደምችል አታውቅምን" ብሎት ነበር። ጌታ ኢየሱስ ድንቅ መልስ ነበረው "መንግስቴ ከዚህ አለም አይደለችም" አለ።
ይቀጥላል...
ሰማያዊ ወግ
የነፍስ ጩኸት
ጌታ ሆይ ቢርበኝ እበላለሁ፣ ቢጠማኝም እጠጣለሁ፣ ቢበርደኝም እደርባለሁ፣ ይሄን ሁሉ ማድረግ እያቅተኝም።
አይኔም ማረፊያ አያጣም፣ የምድር ውበት፣ መስኩን አያለሁ፣ በመቅደስ ያለውን አበባ አያለሁ፣ ዱርና ሸንተረሩ ለአይኔ ምግብ ነው። አይኔ ማረፊያ አያጣም፣ በዚህ ምድር ብዙ ውበት አለ አይኔን በዛ አሳርፋለሁ፣ ልቤ ግን ካለ አንተ ማረፊያ የለውም።
የልቤ ማረፊያ አንተ ብቻ ነህ። በዚህ ምድር ማረፊያ የሌላት ልቤ ብቻ ናት። ልቤ ባንተ ካልሆነ ማረፊያ የላትም፣ ልቤን ጠብቅልኝ።
ሲደክመኝ በመኝታዬ እርፍ እላለሁ፣ ልቤ ግን ከታወከች እንቅልፍን አጣለሁና ልቤን አደራ። ልቤን አደራ የምለው ሌላ የሚታመን የለምና አምላኬ ሆይ ልቤን አደራ።
ልቤን ብቻ ለአንተ አደራ እሰጣለሁ። ይሰብረኛልና ልቤን ለሰው አደራ አልሰጥም፣ ብሰጥም ልቤን ማሳረፍ የሚችል ሰው የለም። ሰውን ተስፋ ባደርግ ልቤን ያሳዝነዋልና፣ ኢየሱሴ ልቤን ጠብቅልኝ። የልቤ ስፍራ አንተ ነህና ልቤን አሳርፍልኝ።
"ልብህን ጠብቅ!! የህይወት መውጫ ከዚያ ነውና" ብለኸኛል። እኔ ግን ልቤን ለመጠበቅ የማልችል ምስኪን ነኝና ልቤን አንተው ጠብቅልኝ።
በልቤ ሰውን ስወድ በጥላቻ ይሞሉኛል፣ በልቤ ሳፈቅር ማፍቀሬን ይጎዱታል፣ በልቤ ሰውን ሳምን እምነቴን ይሰብሩታል፣ በልቤ ሰውን ተስፋ ሳደርግ ተስፋ ቢስ ያደርጉኛል። የልቤ ታማኝ ማረፊያ አንተ ብቻ ነህና ልቤን ጠብቅልኝ።
በሞት መንገድ....
በጥንቱ ቤተ ክርስቲያን አንዳንድ መነኮሳት በሬሳ ሳጥን ውስጥ ይተኙ ነበር። አንዳንዶቹ ደግሞ በመኝታ ክፍላቸው የሬሳ ሳጥን ያስቀምጡ ነበር። ይሄ በመላው ገዳማት የተለመደ ባይሆንም አንዳንዶች ያደርጉት የነበረ እውነት ነው።
አላማው ግልፅ ነው። መነኮሳቱ ህይወት አጭር መሆኗን እና ሁል ጊዜ ሞት አጠገባቸው እንደሆነ በማስታወስ ስራቸውን እንዲፈፅሙ የሚያስታውሳቸው ነበር። መነኮሳቱ “ፍጻሜህን አስብ፤ ከቶም ኃጢአት አትሠራም።” የሚለውን ቃል ያስታውሱበታል።(ሲራክ 7፥36)
እንደ ዛሬው ለመኖር ብቻ ሳይሆን ለሞት የተዘጋጁ ነበሩ።
በቤተ ክርስቲያን የስደት ዘመን ካህናቱና አማኙ በዋሻ ውስጥ ተደብቀው እግዚአብሔር ያመልኩ ነበር፣ በዋሻ ውስጥ እያሉ አንዳንዶች ይሞታሉ፣ ወደ ውጭ አውጥተው መቅበር ስለማይችሉ በሞቱት ካህናት አስከሬን ላይ መሰውያ በመስራት ቅዳሴ ያደርጉ ነበር። ክርስትና ይሄ ሁሉ የታለፈበት የድል መንገድ ነው።
ይሄን አስታውሱ!! ህይወት አጭር ናት፣ ሰማይ ግን ዘላለም ነው። በዚህ ምድር ስንኖር ተጓዥ መሆናችንን መርሳት የለብንም። በዚህ ምድር ስንጓዝ ስንቅ እንይዛለን፣ ወደ ሰማይ ስንሄድ ግን አንዳች አንይዝም። መያዝ የሚፈቀድልን በዚህ ምድር ያመነውን ኢየሱስን ብቻ ነው። በመጨረሻ ሰማይ የሚያውቀን ኢየሱስ ክርስቶስን ስንመስል ነው።
ጳውሎስ እንዲህ ይላል "የዚያንም የመሬታዊውን መልክ እንደ ለበስን የሰማያዊውን መልክ ደግሞ እንለብሳለን።" 1ቆሮ 15:49
እንደ ጥንት አባቶች ሞታችንን እያሰብን ባንኖር እንኳን ህይወትን በማሰብ እንኑር።
እንዲሁ.....
የእግዚአብሔር ፍቅር ከራሱ ከማንነቱ ይመነጫልና የኛ ማንነት ሳይገደው ይወደናል።
ደካሞች ስንሆን አምላካችንን እንከተለዋለን፣ የደካሞች ተስፋ እግዚአብሔር ብቻ ነው። እርሱ ደካሞችን ገፍቶ አያውቅም፣ ሃጥያት በከበደንም ጊዜ ወደ ፊቱ እንገሰግሳለን እርሱ ሃጥያተኞችን አይከስም።
የምንበድለው እግዚአብሔርን ነው፣ የሚከሱን ሌሎች ናቸው። እግዚአብሔር ግን እራሱ ይከላከልልናል።
ከሰው ፍቅር ስናጣ ወደ እርሱ የምንገሰግሰው ለዚህ ነው። ስንራቆት እንጠራዋለን የፀጋ ልብስ ያለብሰናል። እኛ ጥቂት ደቂቃ የሚቆይ ቅጠል እንለብሳለን እርሱ ግን ለዘላለም የሚከልለንን የልጁን ፀጋ ያለብሰናል።
ተስፋ ቢስነት ሲሰማን ከእርሱ አንርቅም ተስፋ ቢስን ከእግዚአብሔር በቀር ማን ይቀበለዋል?።
ምናልባት ሰዎች በድክመታችን ይፈርዱብናል። የምንወዳቸው ጠላት ይሆኑብናል፣ መኖራችን በእግራቸው ስር እንዲሆን ሲፈልጉ፣ እግዚአብሔር ስለኛ ይቆጣል፣ ከእርሱ ጋር ነንና ለእኛ ምህረቱ ለጠላት ቁጣው ይነዳል።
እስከ ድካማችን አምላካችንን የምንታመነው፣ ድንጋይ ከሚወረውሩብን፣ ከሚፈርዱብንና ከሚያዋርዱን ለመትረፍ ነው። ዳዊት እንዳለ እንዳንዴ ሁሉም ሰው ሊቀበለን ፈቃደኛ አይደለም፣ እናትና አባታችን እንኳን ሊተውን ይችላሉ እግዚአብሔር ግን ይቀበለናል። ዳዊት እንዲህ ብሎ ነበር "እናትና አባቴ ትተውኛል እግዚአብሔር ግን ተቀበለኝ"
ሰዎች በሁኔታዎች ይለዋወጣሉ፣ በደስታም በሃዘናችን ያለው እግዚአብሔር ብቻ ነው። ያሉ የመሰሉን ሁሉ የሉም፣ እግዚአብሔር ግን የሌለ በመሰለ ጊዜ ሁሉ አለ።
ከኛ ምንም ፈልጎ አልወደደንምና ምንም ስለሌለን አይጠላንም፣ እየባስን ስንሄድም ይወደናል፣ የሚወደን በጎ ነገር ስለተገኘብን ሳይሆን እርሱ መልካም ስለሆነልን ነው።
የአበባ ሀይል
ከታች የምታዩት ፎቶ አንድ አሜሪካዊ ወጣት አሜሪካ ከቬትናም ጋር ታደርግ የነበረውን ጦርነት የተቃወመበት መንገድ ነው።
የአሜሪካ ወታደራዊ ፖሊስ ሰልፍ ለማሳየት መሳሪያቸውን ይዘው አደባባይ ተገኙ፣ ጦርነትን በሰላም ለመቃወም አንድ ወጣት አበባ ይዞ መሳሪያ ወደያዙት ወታደሮች በማቅናት እሳት በሚተፋው አፍ ውስጥ አበባ አስቀመጠ።
ይሄ ፎቶ ከተነሳ ወደ 57 አመት ሆነው። መሳሪያው ግን ዛሬም አበባ ሳይሆን እሳት ይተፋል።
ጦር ይዞ ሰው ለመግደል መዝመት ፀያፍ ነው። ሀገራት ሀብታቸውን መሳሪያ ለመግዛት ያወጣሉ፣ ይሄ ለማመን የሚከብድ ሃቅ ነው። ምግብ ለቸገረው ህዝባቸው ሞት ይገዙለታል።
ለህመምተኞች መድሃኒት ሳይሆን ለጤነኞች መሳሪያ የሚሸጥባት ሃገር ሆነናል።
ህፃናትን ለመመገብ የእርሻ መሳሪያ ለመግዛት የሚፈራ መሪ፣ ስልጣኑን ለመጠበቅ ከአውሮጳ አጥፊ መሳሪያ ይገዛል። ተው የሚል የለም፣ መንግስት ከእግዚአብሔር በላይ የሚፈራበት ዘመን ደረስን።
ነብዩ ኤርሚያስ እንደዚህ ያሉትን አብዝቶ ይቃወም ስለነበር በዘመኑ አልቃሻው ነብይ ይሉት ነበር። ብዙ ነብያቶች "እጅግ ሰላም ነው!!" እያሉ ሲዋሹ፣ ኤርሚያስ ግን እያለቀሰ፣ "ሰላም ሳይሆን ሰላም ነው ይላሉ፣ ነገ በዚህ አመት ትወርሳላችሁ ይላሉ፣ እግዚአብሔር ይሄን አላለም" እያለ ሲያለቅስ፣ በዘመኑ የነበሩ መሪዎች ማጥ በሞላው እስር ቤት ጥለውት ነበር። ማጡ ግን ኤርሚያስን ሳይሆን የከተቱትን ዋጠ።
ነብዩ ኤርሚያስ በዘመኑ የእግዚአብሔር አፍ ነበር፣ በዘመኑ የነበረውን ዋሾ አገልጋዮች፣ ጨቋኝ መሪዎች ሲያይ "ሰቆቃወ ኤርሚያስ" በሚል አምስቱን ሀዘናቱን ፃፈ። "ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምህረት የተነሳ ነው" አለ። እኔም ይኸው ነው መልእክቴ ክፉዎች በከፉበት ጊዜ የእግዚአብሔር ምህረት ያኖረናል። ...
ስለ እኔ
እምነቴ ጥቂት ነው ከሰናፍጭ ዘር እንኳን ታንሳለች፣ መስራት የምችለው ነገር የለም ጉልበቴ ደካማ፣ ፀባዬም ቢሆን አይመችም። እኔን የሚገልፀው "እኔ ምንም ነኝ!" የሚለው ነው።
የመናገር ችሎታ፣ የመደመጥ ሞገስ የለኝም፣ አንዲት ጥበብ አላውቅም፣ "ይኸው" ብዬ የማሳየው ከኔ የሆነ የለም። በጣም ደካማ ነኝ፣ ለጤና የበላሁት ምግብ የማይስማማኝ፣ ጥቂቷ እንቅፍት አደናቅፋ የምትጥለኝ ምስኪን ሰው ነኝ።
ከብዙ ወንድሞች መሃል የምረሳ ነኝ ግን የማንም ጥፋት አይደለም ከእኔ ብዙ ድክመት የተነሳ ነው።
በቀን ከሰባት ጊዜ በላይ እወድቃለሁ፣ ከአንዱ ስህተቴ ተምሬ ማሻሻል የማልችል፣ መውደቅ ብቻ፣ መሳሳት ብቻ..።
እኔ እንደዚህ ነኝ፣ ግን አንድ ትምክህት አለኝ። እምነት ባይኖረኝ ስለኔ የታመነ አለ፣ ስደክም ሀይሌን የሚያድስ አለ፣ ኢየሱስ አለ።
የጥበብ ሁሉ ራስ መታያዬ ኢየሱስ አለ። ሰማያዊ ዜግነት የሰጠኝ ኢየሱስ ስለኔ አለ፣ ከኔ ሳይሆን ከእየሱስ የተነሳ እንዲሁ ተገባኝ።
ከተረሳሁበት የሚያስታውሰኝ፣ ከወደኩበት የሚያነሳኝ በድግሱ ከፊት የሚያስቀምጠኝ፣ ፅዋዬን ያትረፈረፈልኝ ኢየሱስ አለልኝ።
ሰባቴ ብወድቅም ሰባቴ የሚያነሳኝ፣ ስህተቴን እየቆጠረ የማያሳቀኝ ትምክህት አለኝ።
ስወድቅ እነሳለው፣ ስደክም እበረታለሁ፣ ክፉ ሲፈልገኝ በኢየሱስ ተሰውሬያለሁ።
ጌታ ኢየሱስ ሆይ!! እኔ ደካማ ነኝና እንኳን አንተ ስለኔ ታየህልኝ። እኔ እርግማን የሞላኝ ነኝና እንኳን ፅድቄ ሆንክልኝ። እኔ የምታይ አይደለሁምና እንኳንም አንተ ስለኔ ታየህልኝ። እግዚአብሔር እኔን ሲያይ እንዳይቆጣ በልጁ በኢየሱስ ባረከኝ።
አሁን እኔ የምኖረው በክርስቶስ ያለውን ህይወት ነው። በኢየሱስ ተስፋ ሞላኝ፣ በኢየሱስ በላሁ፣ በኢየሱስ ፈገግ ብዬ ቆምኩኝ፣ ከእኔ የተነሳ ሁሉ ጨለማ ነበር፣ ከክርስቶስ የተነሳ ብርሃን ሆነልኝ። ..
የነፍስ ጩኸት
ምድር አንዳንድ ጊዜ ደም በቃኝ ትላለች፣ ሰው ግን ደም አፍስሶ አይበቃውም።የምንኖርባት ምድር እንባ ጠግባለች ሰው ግን የሰው እንባ አፍስሶ አይበቃውም።
የሰው ልጅ ክቡር ነው፣ እግዚአብሔር ልጁን ለሞት የሰጠለት ክቡር። የሰውን ጭካኔ ስናይ የእግዚአብሔር ምህረት እንዴት ትልቅ እንደሆነ እንረዳለን።
በዘመናችን ያለ ሰው በአስር ብር ለህፃን ዳቦ ከመግዛት፣ በአስር ሚሊየን ጥይት መግዛት የሚመርጥ ነው፣ በነፃ ሰውን ከማዳን ሚሊየን አውጥቶ መግደል የሚፈልግ ነውና ጌታ ሆይ ይቅር በለን።
ያልፈጠረን ሊገለን ይፈልጋል፣ ምድርን ያልሰራ ከምድር ሊያስወግደን ይፈልጋልና ይቅር በለን።
የአቤል ደም በሰማይ እንደጮኸ የምስኪኖች ደም ወደ ዙፋንህ ይጩህ፣ ጌታ ሆይ የጉልበተኛውን ክንድ እንድትሰብርልን እንጠራሃለን።
የዘመናችን ጭካኔ ልክ እያጣ ነው፣ ሮጠው ማምለጥ የማይችሉ ሽማግሌዎች፣ አባረው መያስ የማይችሉ ህፃናት ከእናታቸው ተነጥቀው ሲገደላሉና ይቅር በለን።
ለምስኪኑ ተሟጋች የለም፣ ዙሪያችን በሃጥያት ሲነድ ሙቀቱ አልተሰማንም ይቅር በለን፣ በአጠገባችን እሳት እየነደደ ወላፈኑ አልነካንም የምንል ውሸተኞች ነንና ይቅር በለን።
ጌታ ሆይ አንተ ሰውን ወደህ ነፍስህን ስለሰው ሰጠህ፣ እኛ ግን ይቺን ምድር ወደን አንተ በሞትክለት ሰው ላይ ካራ እንመዛለን። ያንተ የሆኑ ሰዎች ያንተ ያልሆኑ ይገሏቸዋልና ይቅር በለን።
በቤትህ ለአገልግሎት የተለዩ እንኳን መንግስትህን ሳይሆን መንግስታቸውን፣ ሰማይህን ሳይሆን ምድራቸውን ይሰብካሉ፣ ሰማይን ቀና ብለው ቢያዩት ይቀልባቸዋል፣ ክብርህን ሳይሆን ክብራችንን ብለናልና ይቅር በለን።
አላዛር በሞተ ጊዜ መላእክት በደስታ በእቅፋቸው አጅበው ወደ ሰማይ መወሰዱን እናውቃለን፣ ምድራውያን እድል ፋንታቸው ምድር ነው፣ ሰማይን የታመኑ በሰማይ ሃገር አላቸው፣ ተመስገን።
የምስጋና ድል።
ምስጋና የሚያውቁ ከአምላክ ጋር መነጋገር የሚችሉ ናቸው፣ መዘመርና አምልኮ የተሰጣቸው የተባረኩ ናቸው። ምስጋና የእግዚአብሔርን ዙፋን አሽትቶ የመድረስ ሀይል አለው። ከሰማይ ጋር ሙሉ ህብረት የሚደረገው በምስጋና ነው።
ሀና ፀሎቷ ሲመለስ.. ዳዊት ከሳኦልና ከሌሎች ጠላቶቹ ሲተርፍ.. የኢየሱስ እናት ቅድስት ማርያም መልአኩ ሲያበስራ "መንፈሴ በአምላኬ ሀሴት ታደርጋለች" ብላ በምስጋና መሞላቷ። ስምኦን አዳኙን ሲያቅፍ...
84 አመቷ ነብይት ሃና በትንቢት የተናገረችለት ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ባየችው ጊዜ ለሚጠብቁት ቤዛ የሆነ ብላ ስታመሰግን..።
ኢየሱስ ከፈወሳቸው 10 ለምፃሞች አንዱ፣ በታላቅ ድምፅ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን የምስጋናው ድምፅ ብዙዎች ሲሰማ..።
ምስጋና እግዚአብሔርን ማክበር ብቻ አይደለም፣ መክበር ነው። ምስጋና እግዚአብሔርን ማስደሰት ብቻ አይደለም ፣ በእግዚአብሔር ህልውና መደሰት ነው።
ምስጋና መድሃኒት ነው። እግዚአብሔር ፊት ሊያለቅስ የመጣ ስቆ የሚመለስበት፣ አዝኖ የመጣ ተደስቶ የሚመለሰው በምስጋና ነው።
ምስጋና እግዚአብሔርን ማክበር ብቻ ሳይሆን መክበርም ነው። እንደ ምስጋና ወደ እግዚአብሔር ፊት የሚያቀርብ የለም፣ ብዙ ነገር ከእግዚአብሔር የምንቀበለው ሲሆን ምስጋና የምንሰጠው ነው፣ እግዚአብሔር ታላቅ ቢሆንም የታናናሾችን ምስጋና አይንቅምና መአዛውን ያሸተዋል።
ጌታ ኢየሱስ በዲያቢሎስ ከተፈተነ ጊዜ 'ዲያብሎስ ከፍ ወዳለ ተራራ አወጣውና የአለምን ነገስታት ሁሉ ከነክብራቸው አሳየው፣ ብትሰግድልኝ ይሄን ሁሉ እሰጥሃለው' አለው።
ለዲያቢሎስ አንድ ስግደት የአለም ነገስታትንና ክብራቸውን ያህል ከሆነ፣ ሁሉን ማድረግ ለሚችለው ለእግዚአብሔር በምስጋና መቅረብ ዋጋው ምን ያህል ይሆን?
ወደ ሰማይ አምልኮ መግቢያ በሩ ምስጋና ነው። አንተ ምስጋናችን ነህ።
