ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
前往频道在 Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
显示更多636
订阅者
-124 小时
-37 天
-1330 天
帖子存档
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፲፫ (13) ቀን።
🌹 እንኳን #ለመነኰስ_ለአባ_ዘካርያስ ለዕረፍት በዓልና ለታላቁ አባት #ለቅዱስ_ዮሐንስ_አፈ_ወርቅ ለመታሰቢያው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቀሲስ_አብጥልማኮስና ከወንድሞቹ በሰማዕትነት ከዐረፋ፣ #ከአውስኖ_ከአውሲኪስ_ከታኦድራስ፣ #ከአብላስከ_ወንድሞቹ_ከናውላውስና_ከአቤላ ከመታሰቢያየው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #መነኰስ_አባ_ዘካርያስ፦ የዚህም መስተጋድል የአባቱ ስም አቃርዮስ ነው። ይህም አቃርዮስ የምንኲስና ልብስ ሊለብስ ሽቶ ለሚስቱ ነገራት እርሷም በነገራት ነገር ተስማማች። ወንድና ሴት ሁለት ልጆች አሉአቸው እነርሱንም ከእናታቸው ዘንድ ትቶ እርሱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዶ ከአንድ አረጋዊ አባት መነኰስ ዘንድ በዚያ መነኰሰ።
🌹 ከጥቂት ወራትም በኋላ በሀገር ውስጥ ረኃብ ሆነ ሚስቱም ልጆቿን ይዛ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወደባሏ አቃርዮስ መጣች በረኃብም ስለ ሆነው ችግር ነገረችው አቃርዮስም "እነሆ እግዚአብሔር በመካከላችን ፍርድን አድርጎ ልጆቻችንን አካፈለን እኔም ወንዱን ልጄን እወስዳለሁ አንቺም ሴት ልጅሽን ውሰጂ" አላት ይህንንም ብሎ ልጁን ወሰደ ይኸውም ዘካርያስ ነው እርሷም ሴቷን ልጅዋን ይዛ ተመለሰች።
🌹 ከዚህም በኋላ ልጁን ዘካርያስን ወደ ቅዱሳን አረጋውያን አቀረበው እነርሱም በላዩ ጸለዩ ባረኩትም እርሱ ፍጹም መነኲሴ እንደሚሆንም ትንቢት ተናገሩለት። ዘካርያስም ከበጎ ሥራ ጋር በገዳም ውስጥ አደገ መልኩም እጅግ ያማረ ነው ስለርሱም ጉርምርምታ ሆነ መነኰሳቱም እርስበርሳቸው "ይህ ወጣት ይህን ያህል እጅግ መልከ መልካም ሲሆን በገዳም ውስጥ በመነኰሳት መካከል እንዴት ይኖራል" ተባባሉ።
🌹 ዘካርያስም ስለርሱ መነኰሳት እንዳንጐራጐሩ በሰማ ጊዜ ናጥራን ወደሚባል ተራራ ስር ወደአለች ዐዘቅት ሔደ ልብሱንም አውልቆ በረግረግ ውስጥ ተኛ ሥጋውም ተነፋፍቶ ጠቆረ ተመላልጦም ቈሰለ ብዙ ዘመንም በደዌ እንደኖረ ሆነ፤ ከዚህም በኋላ ልብሱን ለብሶ ወደ ገዳም መጣ ያወቀውም የለም። ከብዙ ቀኖችም በኋላ አባቱ አስተውሎ ልጁ ዘካርያስ እንደ ሆነ አወቀውና "መልክህን የለወጠው ምንድን ነው?" ብሎ ጠየቀው አርሱም ያደረገውን ሁሉ ነገረው።
🌹 በእሑድ ቀንም ሥጋውንና ደሙን ሊቀበል ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ እግዚአብሔርም ያን ጊዜ ሥራውን ለአባ ኤስድሮስ ገለጸለት እርሱም ዘካርያስ የሠራውን ለወንድሞች መነኰሳት አስረዳቸው እነርሱም "አስቀድሞ እንደ ሰው ሁነህ መጣህ ዛሬ ግን እንደ እግዚአብሔር መልአክ ሁነህ መጣህ" አሉት።
🌹 ይህ አባት ዘካርያስም በብዙ ገድል ሲጋደል ኖረ ትሕትናን ቅንነትን ያማረ የትሩፋትን ሥራ ሁሉ ገንዘብ አደረገ አባቱም ስለርሱ "እኔ በገድል ብዙ ደክሜአለሁ ነገር ግን ከልጄ ሥርዓተ ገድል አልደረስኩም" ብሎ ተናገረ።
🌹 በዚህ ተጋድሎውም አርባ አምስት ዓመት ኑሮ እግዚአብሔርን ከአገለገለው በኋላ በፍቅር አንድነት ጥቅምት 13 ቀን ዐረፈ መላ ዘመኑም ሃምሳ ሁለት ነው። ከዚህም ሰባቱን ዓመት በወላጆቹ ቤት አርባ አምስቱን በገዳም ኖረ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ዘካርያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 13 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰላም_ለዘካርያስ_ቡሩክ። በውስተ ዓምዓም ሰኪቦ አባላቲሁ ዘአስሐከ። እለ ነጸሩ ትጋሖ ወተጋድሎቶ ውሱከ። ይቤልዎ ኮነ እንዘ ብእሲ መልአከ። እምሕገ ሥጋ ዓዲዎ ከሀከ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_13።
✝ ✝ ✝
🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ጻድቅሰ ከመ በቀልት ይፈሪ። ወይበዝኅ ከመ ዘግባ ዘሊባኖስ። ትኩላን እሙንቱ ውስተ ቤተ እግዚአብሔር"። መዝ 91፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 9፥1-10፣ ያዕ1፥9-17 እና የሐዋ ሥራ 20፥16-28። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 12፥26-32። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ዘካርያስ የዕረፍት በዓል፣ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ የመታሰቢያውና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
+6
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ ዓቢይ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጸሎት መከፈቱን ቤተክርስቲያኗ አሳውቃናለች።
+1
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰአሉ_ለነ_አርባዕቱ_ወንጌላውያን መምህራን ሥዩማን አዕማዲሃ ለቤተ ክርስቲያን ሰአሉ ለነ አስተምሕሩ ለነ"። ትርጉም፦ የቤተ ክርስቲያን ምሶሶዎች የምትኾኑ ሹማምንት መምህራን የምትኾኑ #አራቱ_ወንጌላውያን_ለምኑልን_ማልዱልን።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ዘብእሲ_ማቴዎስ እስመ ዜነወ ልደቶ ለመድኒነ #እምዘርዐ_ዳዊት_ንጉሥ በቤተልሔም ዘይሁዳ"። ትርጉም፦ በገጸ ብእሲ #ሰው_የተመሰለ_ማቴዎስ ነው የይሁዳ ክፍል በምኾን በቤተ ልሔም #ከንጉሥ_ዳዊት ዘር የመድኀኒታችንን ልደት ተናግሯልና። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በሰዓታቱ_ላይ።
🌹 ከዚህም በኋላ ካህናቱና ሕዝቡ እንዲህ ብለው ለመኑት "አባታችን ሆይ ይህን የሠራኸውን ሥራ ታስረዳን ዘንድ ከቅድስናህ እንሻለን" እርሱም "ይህን ሥራ የሠራሁት ከንቱ ውዳሴን ሽቼ አይደለም እናንተ እኔን አምታችሁ ስለእኔ እንዳትጐዱ እንድትድኑ ከዚች ሴት ጋር በመካከላችን ተሠውሮ ያለውን ሚሥጢር እገልጽላችሁ ዘንድ የእግዚአብሔር መልአክ ስለአዘዘኝ ነው እንጂ" አላቸው። "እርሷ የአባቴ የወንድሙ ልጅ ናት በሕፃንነቷም አባቷ ሞተ በአባቴም ቤት ከእኔ ጋር አደገች አካለ መጠንም በአደረሰን ጊዜ አባቴ እርሷን አጋባኝ ወደ ጫጉላ ቤትም በገባን ጊዜ "እኔ እኅትህ ስሆን ለአንተ እንዴት አጋቡኝ" አለችኝ። እኔም "የምትፈቅጂ ከሆነ ድንግልናችንን ጠብቀን በአንድነት እንኑር ይህንንም በመካከላችን ያለውን ምሥጢር የሚያውቅ አይኑር አልኋት" በዚህም ተስማምተን በአንድ ቤት ውስጥ በአንድ ዐልጋ እየተኛን አንድ መጐናጸፊያንም እየተጐናጸፍን አርባ ስምንት ዓመት ያህል ኖርን ይህን ሥራችንንም ያለ እግዚአብሔር የሚያውቅ የለም እኔም እርሷ ሴት እንደ ሆነች አላወቅኋትም እርሷም እኔን ወንድ እንደሆንኩ አታውቅም በየሌሊቱም ሁሉ በንስር አምሳል ወደ መኝታችን እየገባ ክንፎቹን አልብሶን ያድራል ሲነጋም ከእኛ ይሠወራል" አላቸው።
🌹 በዚያንም ጊዜ በደላቸውን ይቅር ይላቸው ዘንድ ከእግሩ ሥር ወድቀው ለመኑት እርሱም ይቅር አላቸው አጽናናቸውም። ይህንንም ድንቅ ሥራ ያዩ ሁሉ ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት።
🌹 በዚህ አባት ዘመንም ስማቸው ቀሌምንጦስ አርጌንስ የሚባሉ ሌሎችም መናፍቃን ስዎች ተነሥተው ታዩ ሌሎችም በአንድነት ሁነው ስለሃይማኖት የፈጠራ መጽሐፍን ጻፉ እርሱም አውግዞ ከምእመናን ለያቸው።
🌹 እርሱም ሁል ጊዜ ያለ ዕረፍት ከጥዋት እስከ ማታ ምእመናንን የሚያስተምራቸው ሆነ። ሸምግሎ በደከመም ጊዜ በዐልጋ ላይ አስቀምጠው ተሸክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ያደርሱታል እስከማታ ድረስም ያስተምራቸዋል ሰዎችም ሁሉ ትምህርቱን ይሰሙ ዘንድ ይጨናነቃሉ መላ የሕይወቱ ዘመንም መቶ ሰባት ነው ጥቅምት 12 ቀን በሰላም በፍቅር አንድነትም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ድሜጥሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱሜ ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 12 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰላም_ለድሜጥሮስ_ሐጋጌ_አጽዋም እምስቴ። ወሠራዔ መብልዕ በጰንጠቈስቴ። እመ ኢኮነ ላዕሌሁ መንፈስ ቅዱስ ከሣቴ። እፎ ይትከሠት ወይትረከብ በአይቴ። ሐሳበ ዘመን ዘስሙ ዓበቅቴ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_12።
✝ ✝ ✝
🌹 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወአልዐልኩ ኅሩይየ እምሕዝቡ። ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ። ወቀባዕክሙ ቅብዐ ቅዱስ"። መዝ 88፥19-20። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 19፥1-16።
✝ ✝ ✝
🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኀይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 5፥19-ፍ.ም፣ ይሁ 1፥9-14 እና የሐዋ ሥራ 13፥22-29። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 9፥9-32። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል የቅዱስ ሚካኤል ወራዊ በዓል፣ የሐዋርያው የቅዱስ ማቴዎስ፣ የአባ ድሜጥሮስ የዕረፍታቸው በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፲፪ (12) ቀን።
🌹 እንኳን #ለመላእክት_አለቃ_ለቅዱስ_ሚካኤል #ቅዱስ_ዳዊትን በሳኦል ፈንታ እንዲሾመው ለሳሙኤል ለነገረበትና #ዳዊት_ጎልያድን_በሚገድልበትን ልዩ ኃይል እዲሰጠው ለረዳበት ለወራዊ መታሰቢያ በዓል፣ #ለእስክንድርያ_ዐሥራ_ሁለተኛ ለሆነ ሊቀ ጳጳሳት ለንጹሕ ለድንግል ከሚስቱ በአንድነት ሲኖር ለ48 ዓመታት የጠባይን ፍላጎት ድል ለነሳ፤ ባሕረ ሀሳብ ለቀመረ (ላዘጋጀ) ለታላቁ አባት #ለአባ_ድሜጥሮስ ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከጻድቃን_ከጴጥሮስና ከተወራራሽ #ጳውሎስ_ከዲዮናስዮስ_ከያዕቆብ_ከአቡጥፋ፣ #ከቴዎድሮስና_ከሚናስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #በዚች_ዕለት_የመላእክት_አለቃ የከበረ መልአክ #የቅዱስ_ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚችም ቀን ወደ ነቢይ ሳሙኤል እግዚአብሔር ልኮታልና የዳዊት አባት ወደሆነ በቤተ ልሔም ወደሚኖር ወደ እሴይ ቤት ይሔድ ዘንድ በቂስ ልጅ በሳኦልም ፈንታ ለእስራኤል ልጆች እንዲነግሥ ልጁ ዳዊትን ይቀባው ዘንድ አዘዘው።
🌹 ሳሙኤልም ወደ እሴይ ቤት ሔዶ "ልጆችህን ሁሉንም አቅርብልኝ" ብለው እሴይም ከዳዊት በቀር ሁሉንም አቀረባቸው እርሱ በእርሻ ውስጥ በጎችን ይጠብቅ ነበርና። ሳሙኤልም የመንግሥት ቅባት ያለበትን ብልቃጥ በራሳቸው ላይ ከፍ ከፍ በአደረገ ጊዜ እግዚአብሔር አልመረጣቸውም። ሳሙኤልም እሴይን "ልጆችህ እነዚህ ብቻ ናቸውን" አለው ዕሴይም "በጎች የሚጠብቅ አንድ ትንሽ ልጅ አለ" አለው።
🌹 ሳሙኤልም ደግሞ ዕሴይን "እሱ ሳይመጣ ምሳ አልበላምና ልከህ አስመጣው" አለው። እሱም ልኮ አስመጣው መልኩም ቀይ ዐይኖቹም የተዋቡ አርአያውም ያማረ ነው እግዚአብሔርም ሳሙኤልን "ይህ ይበልጣቸዋልና ተነሥተህ ቅባው" አለው። በዚያንም ጊዜ ሳሙኤል የመንግሥት ቅባት ያለበትን ቀንድ አምጥቶ በወንድሞቹ መካከል ቀባው ከዚያችም ቀን ጀምሮ ለሁል ጊዜ የእግዚአብሔር መንፈስ በዳዊት ላይ አደረበት በእስራኤል ልጆችም ላይ ነገሠ።
🌹 ደግሞ ሁለተኛ በዚች ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ሚካኤልን ወደ ዳዊት ላከው ረዓይታይ ጎልያድን እስኪገድለውና የእስራኤልን ልጆች እስከሚያድናቸው ረድቶ ኃይልን ሰጠው።
✝ ስለዚህም የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን እናደርግ ዘንድ የቤተክርስቲያን መምህራን አዘዙን። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌹 #የእስክንድርያ_ዐሥራ_ሁለተኛ_ሊቃነ_ጳጳሳት #አባ_ድሜጥሮስ፦ ይህም አባት አስቀድሞ መጻሕፍትን ያልተማረ ሕዝባዊ ገበሬ ነው በወላጆቹ የወይን አታክልት ቦታዎች ውስጥ የሚሠራ ሆነ ከታናሽነቱም ሚስት አጋብተውት ከእርሷ ጋር አርባ ስምንት ዓመት ኖረ ድንግልናቸውን በንጽሕና የጠበቁ ናቸው የተሠወረውን ከሚያውቅ እግዚአብሔር በቀር ይህን የሚያውቅ የለም።
🌹 ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ዮልያኖስ ዕረፍቱ በቀረበ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለት። ከእርሱ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆነውን በምልክት ገለጠለት እንዲህም አለው "ነገ የወይን ዘለላ ይዞ ወደ አንተ የሚገባ ሰው አለ ከአንተ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆን እርሱ ነውና ያዘው አትተወው"። በዚያችም ቀን ድሜጥሮስ ወደ አታክልቱ ቦታ ገባ ያለ ጊዜው ያፈራ የወይን ዘለላ አገኘ ያንንም የወይን ዘለላ በረከት ሊቀበልበት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮልዮስ ይዞት ሔደ። በዚያንም ጊዜ አባ ዮልዮስ ድሜጥሮስን በእጁ ይዞ ለሕዝቡ ሁሉና ለኤጲስቆጶሳት አሳልፎ ሰጠው "ከእኔ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት የሚሆናችሁ ይህ ነው ስለ ርሱ ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ ነግሮኛልና ይዛችሁ ሹሙት" አላቸው።
🌹 ከዚህም በኋላ አባ ዮልዮስ በዐረፈ ጊዜ የጸሎቱን ሥርዓት ፈጽመዉለት ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ያን ጊዜ መንፈስ ቅዱስ መላበት የቤተ ክርስየቲያን የሆኑ የብሉያትና የሐዲሳት መጻሕፍትን አንብቦ ተረጐማቸው ብዙዎች ምሥጢራትም ተገለጡለት።
🌹 ከዚህም በኋላ ባሕረ ሐሳብ የተባለውን የዘመን መቊጠሪያ ሠራ ከእርሱ በፊት የነበሩ የክርስቲያን ወገኖች የመድኃኒታችን የጥምቀቱን በዓል ጥር ዐሥራ አንድ ቀን አክብረው በማግስቱ የከበረች አርባ ጾምን ጀምረው እስከ የካቲት ሃያ ሁለት ቀን ድረስ ይጾማሉ። ከዚያም በኋላ መጋቢት ሃያ ሁለት ቀን የሆሣዕናን በዓል አክብረው በማግስቱ የሕማማትን ሰሞን ጾም ጀምረው ይጾማሉ። ከሐዋርያትም ዘመን ጀምሮ እስከርሱ ዘመን እንዲህ እያደረጉ ኖሩ።
🌹 እርሱም እንዲህ ሠራ የከበረች የጌታችን ጾም መግቢያዋ ከሰኞ ቀን እንዳይፋለስ ፍጻሜውም በዐረብ ቀን ከዚህም የሆሣዕናን በዓል አያይዞ ሠራ በሚቀጥለው ሰኞ ቀን የሕማማት ጾም ተጀምሮ እንዲጾም የስቅለቱም በዓል ከዐርብ ቀን እንዳይፋለስ የከበረች የትንሣኤውና የጰራቅሊጦስም በዓል ከእሑድ ቀን የዕርገቱም በዓል ከሐሙስ እንዳይፋለስ።
እንዲሁም አዘጋጅቶ ለኢየሩሳሌም አገር ለሮሜ ሀገር ለኤፌሶንና ለአንጾኪያ ሀገር ሊቃነ ጳጳሳት ለየአንዳንዳቸው ላከላቸው። እነርሱም በደስታ ተቀብለው ሠሩበት እስከዚችም ቀን ጸንቶ ኖረ።
🌹 በቊርባን ቅደሴ ጊዜም ዘወትር ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያየው ሆነ። የሕዝቡ ኃጢአታቸው በፊቱ ግልጥ ሆነ ስለዚህም የማይገባቸውን ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል ይመልሳቸዋል እንዲህም ይላቸዋል "ሒዱ ንስሐ ግቡ ከዚያም በኋላ መጥታችሁ ሥጋውና ደሙን ተቀበሉ"።
ስለዚህም ነገር ብዙ ሕዝቦች ኃጢአት ከመሥራት የሚጠበቁ ሆኑ ልባቸው የደነደነ ሌሎች ግን ጠሉት እርስ በርሳቸውም እንዲህ ተባባሉ። "ይህ ሰው ሚስት አግብቶ ሚስቱም ከእርሱ ጋር ትኖራለች ሳይገባውም በወንጌላዊው ማርቆስ ወንበር ተቀምጠ ከንጹሕ ድንግል በቀር አይሾምበትም ነበርና እኛንም ኃጢአተኞች ናችሁ ብሎ ይገሥጸናል"።
🌹 በአንዲት ሌሊትም ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ወደርሱ መጥቶ "ድሜጥሮስ ሆይ ራስህን ብቻ ማዳንን አትሻ ወገኖችህም ይጠፋ ዘንድ አትተው ነፍሱን ስለ መንጋዎቹ አሳልፎ ለሞት የሚሰጥ እርሱ ቸር ጠባቂ እንደሆነ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል የተናገረውን አስብ" አለው። ድሜጥሮስም መልአኩን "ጌታዬ የምትለኝ ምንድን ነው" አለው መልአኩም "በአንተና በሚስትህ መካከል ተሰውሮ ያለውን ምሥጢር ለወገኖችህ ግለጽ" ብሎ መለሰለት።
🌹 ከዚህም በኋላ ሕዝቡን አሰባሰባቸው ሊቀ ዲያቆኑንም "ወጥተው ወደ ቤታቸው እንዳይገቡ ሕዝቡን ንገራቸው" አለው ራሱም ቅዳሴውን ቀደሰ ሁለተኛም ዕንጨቶችን ሰብስበው እሳትን እንዲአነዱ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ። ያን ጊዜ ይህ አባት ተነሥቶ ከሚነደው እሳት መካከል ገብቶ ለረጅም ጊዜ ቁሞ ጸለየ ከእሳቱም ፍም አንሥቶ በሚከናነብበት ቀጸላ አደረገ ሚስቱንም ጠርቶ "መጎናጸፊያሽን ዘርጊ" አላት በዚያም የእሳቱን ፍም ጨመረ በእሳቱም መካከል በአንድነት እየጸለዩ ቆሙ ሕዝቡም እጅግ ያደንቁ ነበር።
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፲፪ (12) ቀን።
🌹 እንኳን #ከዐሥራ_ሁለቱ_ሐዋርያት ለአንዱ ለሆነው #ለወንጌላዊ_ለቅዱስ_ማቴዎስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ሐዋርያው_ወንጌላዊ_ቅዱስ_ማቴዎስ፦ ይህም እንዲህ ነው በብዙ አገሮች ውስጥ አስተምሮ ብዙዎች ሰዎችን እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ ከመለሰ በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ወደ ካህናት አገር እንዲሔድ አዘዘው። ተጒዞም ወደ ከተማው መግቢያ ደጅ በደረሰ ጊዜ አንድ ወጣት ብላቴና አገኘ ወደ ከተማው ለመግባት እንዴት እንደሚችል ጠየቀው ወጣቱ ብላቴናም እንዲህ ብሎ መለሰለት "አንተ ግን ራስህንና ጽሕምህን ካልተላጨህ በእጅህም ዘንባባ ካልያዝክ መግባት አትችልም"። ይህም ነገር ለሐዋርያ ማቴዎስ አስጨንቆት ሲያዝን አስቀድሞ ያነጋገረው ያ ወጣት ብላቴና ዳግመኛ በስሙ ጠራው። ሐዋርያውም "ወዴት ታውቀኛለህ" አለው እርሱም "እኔ ጌታህ ኢየሱስ ነኝ አሁንም እንደ ነገርኩህ አድርግ እኔም ከአንተ ጋር አለሁ ከአንተም አልርቅም" አለው።
🌹 ከዚህም በኋላ ጌታችን እንዳዘዘው አድርጎ ወደ ካህናት አገር ገባ ለአማልክት ካህናት አለቃቸው ከሆነ ከአርሚስ ጋር ተገናኘ ከእርሱም ጋር ስለ አማልክቶቻቸው ተነጋገረና ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ጣዖቶቻቸውን አቃጠላቸው እንዲህም አላቸው። "ራሳቸውን ማዳን ያልቻሉ ሌላውን እንዴት ያድናሉ" በዚያንም ጊዜ ከአርሚስ ጋር ብዙዎች ሰዎች አምነው አጠመቃቸው ከሰማይም ማዕድ አውርዶ መገባቸው።
የሀገሩም ንጉሥ ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ ከአርሚስ ጋር ሐዋርያውን ወደ እሳት ጨመረው ጌታችንም አዳናቸው።
🌹 ከዚህም በኋላ በሚአሠቃያቸው ነገር ሲአስብ እነሆ ልጁ እንደ ሞተ ነገሩት እጅግም አዘነ። ሐዋርያ ማቴዎስም "ልጅህን እንዲያስነሡት ወደ አማልክትህ ለምን አትለምንም" አለው ንጉሡም "የሞተ ማንሣት እንዴት አማልክት ይችላሉ" ብሎ መለሰ። ቅዱስ ማቴዎስም "ብታምንስ የእኛ አምላክ ልጅህን ማሥነሣት ይችላል" አለው። ንጉሡም "ልጄ ከተነሣ እኔ አምናለሁ" አለ በዚያን ጊዜ ሐዋርያው ክብር ይገባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየና የንጉሡን ልጅ ከሞት አስነሣው። ንጉሡም ክብር ይግባውና በጌታችን አመነ የአገር ሰዎች ሁሉም አመኑ የቀናች ሃይማኖትንም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ካህናትንም ሾመላቸው ከዚህም በኋላ ወደ ሌሎች አገሮች ሒዶ ወንጌልን አስተማረ።
🌹 ከዚህም አስቀድሞ በደመና ተነጥቆ ብሔረ ብፁዓን ገብቷል ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስን ሁል ጊዜ በየበዓላቸው ወደ እነርሱ ሲመጣ አየው ከእርሱም ጋር መቶ አርባ ሽህ ሕፃናት አሉ መላእክትም ሁሉ በዙሪያው ቁመው ያመሰግኑታል። በብሔረ ብፁዓን ስለ ሚኖሩ ወገኖችም ድንቅ ስለሆነ ሥራቸው ሁሉ ከሐዋርያው በኋላ ወደርሳቸው የገባ ዘሲማስ ቀሲስ ምስክር ሆነ።
🌹 ከዚህም በኋላ የሐዋርያው የተጋድሎውና የምስክርነቱ ፍጻሜ ሲቀርብ ወደ አንዲት ከተማ ገብቶ አስተማረ ብዙዎችንም አሳመነ አገረ ገዢውም ይዞ ከወህኒ ቤት ጨመረው። በዚያም አንድ እጅግ የሚያዝን እሥረኛ አይቶ ስለኀዘኑ ጠየቀው እርሱም ብዙ የሆነ የጌታው ገንዘብ ከባሕር እንደ ሠጠመበት ነገረው ሐዋርያ ማቴዎስም "ወደ ዕገሌ ባሕር ዳርቻ ሒድ ወርቅን የተመላ ከረጢትንም ታገኛለህ ያንንም ወርቅ ወስደህ ለጌታህ ስጥ" አለው።
🌹 ስለዚህም ድንቅ ተአምር ብዙዎች ክብር ይግባወና በጌታችን አመኑ። መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ቅዱስ ማቴዎስንም ራሱን እንዲቆርጡ ሥጋውንም ለሰማይ ወፎች እንዲጥሉ አዘዘ። ከከተማውም አውጥተው ቈረጡት ምእመናንም በሥውር መጥተው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው በቅዱስ ማቴዎስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 12 ስንክሳር።
✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨
ውድ የ/ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት አባላት እና የ7ኛ ክፍል ተማሪዎች በሙሉ እንኳን ለዚህች ውድ የምርቃት ቀናችሁ በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን 🙏
እንደሚታወቀው ሰንበት ት/ቤታችን በ2017 ዓ.ም በበጋ እና በክረምት ሲሰጥ የነበረውን ተከታታይ የ7ኛ ክፍል ትምህርት ስትማሩ የነበራችሁ ሁላችሁ ለዚህ የምርቃት ቀን በመድረሳችሁ ሰንበት ት/ቤታችን እንኳን ደስ አላችሁ ልትል ትወዳለች::
ስለዚህ እሑድ ጥቅምት 16 2018 ዓ.ም እናንተን ለማስመረቅ ዝግጅቷን ጨርሳለች:: ስለሆነም በእለቱ ከቅዳሴ በኃላ 4:00 ላይ ነጭ ለብሰው በሰንበት ት/ቤታችን አዳራሽ እንዲገኙ ስንል በአምላከ ቅድስት አርሴማ ስም እንጠይቃለን::
በእለቱም:
📌ዝማሬ
📌 ቃለ ወንጌል
📌ስለአዲሱ የትምህርት ዘመን ገለፃ
📌የተማሪዎችን ውጤት የሚገልፅ ሰርተፍኬት ይበረከታል
📌 በትምህርታቸው ጥሩ ውጤት ላመጡ ተማሪዎች ማበረታታቻ ሽልማት የሚሰጥ ይሆናል
ትምህርት ክፍል
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፲፩ (11) ቀን።
🌹 እንኳን #ለገድለኛዋ_ለቅድስት_ጲላግያ ለዕረፍት በዓል፣ #ለአንጾኪያ_ሊቀ_ጳጳሳት ለቅዱስ አባት #ለአባ_ያዕቆብ ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከሰማዕት_አርማሚ ከመታሰቢያው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ገድለኛዋ_ቅድስት_ጲላግያ፦ ይቺም ከአንጾኪያ አገር የሆነች ናት ወላጆቿም ከሀድያን ናቸው እርሷም አስቀድማ ከረከሰ ሃይማኖቷ ጋር በረከሰ ሥራ ጸንታ መኖርን ገንዘብ አደረገች። እርሷም በመሸታ በጨዋታ ቤት በመዋል ስትሣለቅና ስታመነዝር ስትዘፍንም ትኖራለች።
🌹 በአንዲት ቀንም የገሀነም እሳትና የዘላለም ሥቃይ እንደሚጠብቃቸው እያሳሰበ ዝንጉዎችንና አመንዝራዎችን ሲገሥጻቸው ኤጲስቆጶስ ጳውሎስን ሰማችው ምክሩም በልቧ አደረ።
🌹 ከዚህም በኋላ ወደርሱ ሒዳ የሠራችውን ሁሉ ተናዘዘች እርሱም አጽናንቶ የቀናች ሃይማኖትን አስተማራትና አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃት። በቀደመው ሥራዋም እየተጸጸተች በጾም በጸሎት በስግደት ሰውነቷን ማድከም ጀመረች።
🌹 ከዚህም በኋላ የወንድ ልብስ ለብሳ ወደ ኢየሩሳሌም ሒዳ በከበሩ ቦታዎች ሁሉ ሰግዳ ሁሉንም ቦታዎች ተሳለመች ወደ ኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳትም ተመለሰች። እርሱም ከኢየሩሳሌም ከተማ ውጭ ከደናግል ገዳማት ወደ አንዱ ላካት የምንኵስናንም ልብስ ለብሳ በጽኑዕ ገድልም ተጠምዳ ሠላሳ ዓመት ያህል ኖረች እግዚአብሔርንም አገልግላ በሰላም ጥቅምት 11 ቀን ዐረፈች። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ጲላግያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌹 #የአንጾኪያ_ሊቀ_ጳጳሳት ቅዱስ አባት #አባ_ያዕቆብ፦ ይህም ቅዱስ ብዙ መከራ ደርሶበታል ስለ ቀናች ሃይማኖቱ አርዮሳውያን አሳደውት በደሴት ብዙ ወራት ኖረ።
🌹 ከዚህም በኋላ የአንጾኪያ ምእመናን ሰዎች ተሰብስበው መከሩ። መልእክትም ልከው ወደ እነርሱ መልሰውት ጥቂት ቀኖች ኖረ። ከዚህም በኋላ ሁለተኛ አርዮሳውያን ተነሡበት አሳደዱትም በስደትም ውስጥ ሰባት ዓመት ኑሮ በዚያው ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 11 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኀይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 1 ጢሞ 4፥9-ፍ.ም፣ ያዕ 3፥1-5 እና የሐዋ ሥራ 20፥28-31። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥11-17። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፲፩ (11) ቀን።
🌹 እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_የዓባይ_ውሃ ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ #በጸሎታቸው_አቁመውት ለነበሩ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ኤልያስ_ዘውቅሮ ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
🌹 #አቡነ_ኤልያስ_ዘውቅሮ፦ የትውልድ ሀገራቸው አክሱም ነው፡፡ የአቡነ አረጋዊ 3ኛ የቆብ ልጅ ናቸው፡፡ አባታቸው ውቅሮ የሚገኘው የጥንታዊው የአብርሃ ወአጽብሓ ቤተ መቅደስ አጣኝ ነበሩ፡፡ እኚህ ጻድቅ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ገድል አላቸው፡፡ በቀን 548 ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን እየጸለዩ 666 ጊዜ ይሰግዱ ነበር፡፡ ቅዱስ ያሬድ ዓባይ የሀገራችንን አፈርና ዛፉን ሁሉ ጠራርጎ ሲወስድ ቢመለከት ድምጹን ከፍ አድርጎ "ኦ አባይ አይቴ ተሐውር ወለመኑ ተሐዲጋ ለኢትዮጵያ" ብሎ ሲዘምር ዓባይ ቀጥ ብሎ ቆሟል፡፡ መልአኩም ወዲያው መጥቶ "ለምን ትደክማለህ? ለምንስ ተፈጥሮን ትከለክላለህ? ሕጉን አታፍርስ" ሲለው ቅዱስ ያሬድ ደንጎጦ "አጥፍቻለሁ ዓባይ ሆይ ሂድ የተፈጥሮ ግዴታህን ፈጽም" ብሎ አሰናብቶታል፡፡ የኢትዮጵያ ብርሃኗ ቅዱስ ያሬድ በዜማው ዓባይን ቀጥ አድርጎ እንዳቆመው ሁሉ አቡነ ኤልያስ ዘውቅሮም በጸሎታቸው ዓባይን ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ አድርገውት ነበር፡፡
🌹 ታቦተ አብርሃ ወአጽብሓን ይዘው ከኢትዮጵያ ጠረፍ ዳር ኑብያ ሄደው ድንጋይ ከዓባይ ዳር ደርድረው ታቦቱን አስቀምጠው ሥዕለ ማርያምን አድርገው መሥዋዕት ሰውተው "ዓባይ ከኢትዮጵያ እንዳትወጣ ገዝቼሃለሁ" ሲሉት ዓባይም ተመልሶ ቆሟል፡፡ ዓባይ ምድረ ኑብያን ሲያጥለቀልቃት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጾ "ለምን የእግዚአብሔርን ስነ ፍጥረት ታስጨንቃለህ?" ብሎ ተቆጣቸው፡፡ ጻድቁም "ውኃው ይሂድ ግን ዛፉን አፈሩን ይዞ ከኢትዮጵያ አይውጣ" ብለው መልአኩን ጠየቁት፡፡
🌹 ቅዱስ ገብርኤልም "ውኃ ሲሞላ ዛፉን ቅጠሉን ይዞ መጓዙን እንዴት ትረሳዋለህ? የጸሎት ጊዜህ ደርሷልና ወደ በዓትህ ተመለስ" ብሎ በቁጣ የእሳት ሰይፉን ሲያዛቸው ግዝታቸውን አንሥተው ታቦታቸውን ይዘው ወደ በዓታቸው ውቅሮ ተመልሰዋል፡፡ አባቶቻችን እንዲህ ናቸው እንኳን ሃይማኖት፣ ባህል፣ ታሪክ፣ ቅርስ፣ ስብዕና ማንነታችንን ይቅርና የሀገራችንን አፈር እንኳን ለባዕድ አሳልፈው የማይሰጡ ቅዱሳን ጻድቃን ነበሩ፡፡ ከአባታች ከአቡነ ኤልያስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።
🌹 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #ጥቅምት ፰ (8) ቀን።
🌹 እንኳን #ለሽማግሌው_አባት_ለአባ_መጥራ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍት በዓል፣ ከርእርሱ ጋር ብዙዎችን በሰማዕትነት ለዐረፋበት በዓልና #ተርታ_ነገርንም_እንዳይናገር_ደንጊያ_በአፉ_ጎርሶ_ለኖረ_ለባሕታዊ_ለአባ_አጋቶን_ለመታሰቢያው_በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱስ_ባኮስና #ከቅድስት_በላግያ በሰማዕትነት ከዐረፋ፣ #ከአባ_ሖር ከመታሰቢያውና ሰማዕትነት ከሆኑ ከልጆቹና #ከሶስና ይምሕው በሚባል አገር ከመታሰቢያቸው ከሆነ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ሽማግሌው_አባት_አባ_መጥራ ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት፦ ይህም ቅዱስ ከእስክንድርያ አገር አማኒ ክርስቲያን ነው። ከሀዲ ንጉሥ ዳኬዎስ በነገሠ ጊዜ የጣዖትን አምልኮ አቁሞ የክርስቲያንን ወገኖች አሠቃያቸው። ትእዛዙም ወደ እስክንድርያ አገር ደርሶ ሰዎቿን ሁሉንም አሠቃያቸው የብዙዎች ምእመናንንም ደማቸውን አፈሰሰ። ያን ጊዜ ክርስቲያን እንደ ሆነ ቅዱስ መጥራን በመኰንኑ ዘንድ ወነጀሉት፤ መኰንኑም ወደርሱ አስቀረበው እርሱም ብቻውን እውነተኛ አምላክ እንደ ሆነ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ።
🌹 መኰንኑም "ለአማልክት ስገድ እኔም ብዙ ገንዘብን እሰጥሃለሁ ታላቅ ክብርንም አከብርሃለሁ" አለው። እርሱም ቃል ኪዳኑን አልተቀበለም "ኪዳንህና ገንዘብህ ካንተ ጋራ ወደ ጥፋት ይሒድ" አለው እንጂ። መኰንኑም በእርሱ ላይ ተቆጥቶ "እኔ በጽኑዕ ሥቃይ እቀጣሃለሁ" አለው።
🌹 ቅዱስ መጥራም ፈርቶ ከበጎ ምክሩ አልተመለሰም እንዲህም አለው እንጂ "እኔ ሰማይና ምድርን ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር እሰግዳለሁ። ለረከሱ ጣዖታት ከደንጊያና ከዕንጨት ለተሠሩ ለማያዩ ለማይሰሙ ለማይናገሩ ለማያሸቱ ለማይንቀሳቀሱ እንሰግድ ዘንድ እንዴት ይገባል" አለው። መኰንኑም በሰማ ጊዜ አፈረ። ጽኑ ግርፋትንም እንዲገርፉት አዘዘ።
🌹 ከዚህም በኋላ በክንዱ ሰቀሉት በደረቀች ሽመልም ጎኖቹን ሠነጠቁ ቀደዱትም ክብር ይግባውና ጌታ ኢየሱስም አዳነው። ያለ ጥፋትም በጤንነት አስነሣው መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ከከተማውም አውጥተው የከበረች ራሱን ቆረጡ። ሌሎች ብዙዎች ሰማዕታትንም ከእርሱ ጋር ራሶቻቸውን ቆረጡ። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ መጥራ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ባሕታዊ_አባ_አጋቶን፦ ይህም አባት ወደ ቲቤያድ ገዳም ሲመጣ ገና ሕፃን ነበር። ያሳደገው ያስተማረው አባ ጴማን ነው። በመቀጠልም ወደ አስቄጥስ ተጉዞ ከአባ እስክድር እና ዞይለስ ጋር ለጥቂት ጊዜ ኖሯል። ገዳመ አስቄጥስ ለመጀመርያ ጊዜ ሲጠፋ አባ አጋቶን ከደቀ መዝሙሩ ከአባ አብርሃም ጋር በመሆን ከደብረ ትሮኤ ሳይርቅ ከዓባይ ወንዝ አጠገብ መኖር ጀመረ።
🌹 አንድ ጊዜ ስለ አባ አጋቶን፡ትሕትና የሰሙ መነኰሳት ሊያዩት መጡ። የቁጣ ስሜቱን ወተውንና አለመተውን ለማረጋገጥ ብለው "አመንዝራውና ትዕቢተኛው አጋቶን ማለት አንተ ነህ?" አሉት። አባ አጋቶንም "አዎ ትክክል ነው" አላቸው። ቀጥለውም "ፍሬ የሌለው ነገር ዘወትር የምታወራ አጋቶን ማለት አንተ ነህ?" አሉት "አዎ ነኝ" አላቸው። "መናፍቅ አጋቶን ማለት አንተ አይደለህምን?" ሲሉ ጠየቁት ያን ጊዜ ግን "መናፍቅስ አይደለሁም" ሲል መለሰላቸው። በዚህ ጊዜ "እስካሁን የተናገርንብህን ሁሉ ተቀብለህ የመጨረሻውን ለምን ተቃወምክ?" አሉት። አባ አጋቶንም "የመጀመሪያያዎቹን ወቀሳዎች ለነፍሴ ተስማሚዎች ናቸውና ተቀበልኳቸው። ኑፋቄ ግን ከእግዚአብሔር መለየት ነው እናም እኔ ከፈጣርዬ መለየት አልፈልግም" አላቸው። በዚህ የተነሣም የርሱ ሕይወት አስደነቃቸው።
🌹 አንድ ቀን አባ አጋቶን በእጁ የሠራቸውን ነገሮች ለመሸጥ ወደ ገበያ ሲወጣ በመንገድ ዳር አንድ ሽባ ሰው አገኘ። ሽባውም የት እንደሚሄድ አባ አጋቶንን ጠየቀው። "አንዳንድ ነገሮች ለመሸጥ ወደ ገበያ እሔዳለው" አለው። ሽባው ሰውም "እባክህ ተሸከምህ ወደዚያ ውሰደኝ" ሲል ለመነው። አባ አጋቶንም ያንን ሰው ተሸክሞ ወደ ከተማ ወሰደው። ሽባው ሸውዬ "ዕቃዎችን ከምትሸጥበት ቦታ አጠገብ አኑረኝ" አለው። አባ አጋቶንም እንደዚያው አደረገው። አባ አጋቶን የመጀመርያውን ዕቃ ሲሸጥ "ምን ያህል ሸጥከው?" ብሎ ሽባው ሰው ጠየቀው። እርሱም ዋጋውን ነገረው። ያም ሽባ ሰው "እባክህ ዳቦ ግዛልኝ" ሲል ለመነውና ገዛለት።
🌹 አባ አጋቶን ሁለተኛው ዕቃ ሲሸጥ "ምን ያህል ሸጥከው" ሲል ያሰው ጠየቀው። እርሱም ዋጋው ነገረው "እባክህ ይህን ነገር ግዛልኝ" ሲል ለመነው። አባ አጋቶንም ገዛለት። በዚህም መልኩ ሁሉንም ዕቃዎች ሸጦ በጨረሰ ጊዜ ያሽባ ሰው "ወደ በዓትህ ትመለሳለህን?" ሲል ጠየቀው "አዎ" "እንግደውስ እባክ ቀድሞ ወደአገኸኝ ስፋራ አዝለህ መልሰኝ" አለው። አባ አጋቶንም ያን ሽባ ሰው ተሸክሞ ወደ ቀድሞ ቦታው መለሰው። በዚህ ጊዜ ሽባው ሰው "አባ አጋቶን በሰማይና በምድር በረከት ተሞላህ" ብሎ ተናገረው። ወድያው አባ አጋቶን አይኑን አንስቶ ሽባው ቢያየው በቦታው የለም። ሊፈትነው ይህን ያደረገው መልአከ እግዚአብሔር ነበር። ከአባታች ከአባ አጋቶን እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን!። ምንጭ፦ በበረሐው ጉያ ውስጥ ከሚለው መጽሐፍ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ከጻፈው።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰላም_ለመጥራ_ምስለ_ሰማዕታት_ማኅበሩ። አመ አሰፈዎ መኰንን ከመ ይጸግዎ ሀብታተ ክቡሩ። ዘኢተመይጠ ምንተኒ እምነ ሠናይ ምክሩ። በሕለት ይቡስ እስከ ገቦሁ ሰቈሩ። ወእስከ በሰይፍ ክሣዶ መተሩ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_8።
✝ ✝ ✝
🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር ኢያስተጼንሶሙ እምበረከቱ ለእለ የሐውሩ በየውሀት። እግዚኦ አምላከ ኃያላን። ብፁዕ ብእሲ ዘተወከለ ኪያከ"። መዝ 83፥11-12። የሚነበቡት መልዕክታት ፊሊ 1፥19-ፍ.ም፣ ያዕ 1፥2-7 እና የሐዋ ሥራ 14፥19-ፍ.ም የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 21፥12-21። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
