ch
Feedback
yero's reflections/ የየሮ ንጽረቶች

yero's reflections/ የየሮ ንጽረቶች

前往频道在 Telegram

ይህ ቻናል በተለየዩ ጉዳዮች ላይ የራሴን ምልከታ የማሰፍርበት ነው። በጽሑፎቹ መንፈሳዊ፣ ሃገራዊና ማህበራዊ ነክ ጉዳዮች ይዳሰሳሉ። መልካም የሆነ ተጽዕኖ መፍጠር ከቻለ ብዕሬ ለምን ይለጎም?

显示更多
305
订阅者
无数据24 小时
-17 天
-130 天
帖子存档
በ2015ዓ/ም የተቀየማችሁኝ ሰዎችህ ካላችሁ ምን እንዳስቀየምኳችሁ በትክክል አስረዱኝና ያጠፋሁት ነገር ካለ ከልቤ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ካለ ጥፋቴ ከተቀየማችሁኝ ደግሞ እንደአስፈላጊነቱ ላስረዳችሁ እችላለሁ። ያም ሁኖ ካልተረዳችሁኝ......እንግዲህ ምን አደርጋለሁ የመቀየም መብታችሁን አከብርላችኋለሁ። ባላጠፋሁት ግን ይቅርት አልጠይቅም። "ያስቀየምኳችሁ ካልችሁ ይቅርታ አድርጉልኝ።" ማለት ጠላት ሊኖር ይችል ይሆናል በሚል ኢላማ አልባ ጥይት መተኮስ እንደማለት ነው። ይቅርታ ለጥፋታችን ሃላፊነት መውሰድና ዳግም ላለማጥፋት በተጸጸተ ልብ ለተበዳይ የሚቀርብ ነው ።

ከዚህ በፊት እንደገለጽኩት ለአንድ ዓመት ለሁለት ሰው የሚቆይ የmentorship program እንዳዘጋጀሁ አሳውቄ ነበር። የዚህ  Program ዋና አላማ ወጣቶቹን በሁለንተናዊ መስክ እንዲያድጉና እንዲበቁ ማገዝ ነው። ፕሮግራሙ ለአንድ ዓመት ብቻ  የሚዘልቅ ይሆናል።በፕሮግራሙ Highschoolና ከዛ በታች ያሉ ታዳጊዎችን አያካትትም። ተማሪ ከሆኑ ኮሌጅ ወይንም ዩኒቨርስቲ አሊያ ደግሞ በስራ አለም ላይ ያሉ መሆን ይኖርባቸዋል።  ፕሮግራሙ በሳምንት 30 ደቂቃ/በወር 2ሰዓት/ ድረስ የሚሰጥበት ሲሆን ግንኙነቱ በስልክ ከተቻለ በአካል ሊሆን ይችላል። በዚህ ፕሮግራም መጠቀም የሚፈልግ ሰው በትክክልም መሰጠጥ ያለው ሊሆን ይገባል። በቂ ያልሆነ መሰጠጥ/በቂ ምክንያት ያልተሰጠበት/ ከታየ ፕሮግራሙ ይቋረጣል። በዚህ Program ተሳታፊ መሆን የምትፈልጉ የዚህ ቻናል ተከታዮች 1)  ማንነታችሁን በዝርዝር የሚገልጽ አንድ አንቀጽ /paragraph/ ጽሁፍ 2) ከፕሮግራሙ የምትጠብቁትንና የምትፈልጉትን የሚገልጽ አንድ አንቀጽ /paragraph/ ጽሁፍ። በዚህ @yeroochristian እስከ ጱጉሜ 6/ሰኞ/ ምሽት ድረስ በመላክ apply ማድረግ ትችላላችሁ።

ለወር ገደማ የኢንተርኔት አገልገሎት በሌለበት አከባቢ በመክረሜ ተጠፋፍተን ለመሰንበት ተገደን ነበር። አሁን ተመልሼለሁ.... ዓመቱ እየተገባደደ ነው፤ አዲስ ብለን የጀመርነው አርጅቶ በአዲስ ሊተካ ነው፣ እኛስ ዬት ጋር ሁነን ይሁን?

"እንደው አንተ ልጅ ሰው ሁነህ ያገባህ ቀን ለቅዱሱ ገብርኤል ነው ስለቴን የማስገባው።" አሉ እማማ ገንዘቤ ወደ ስራ ለመውጣት እየተቻኮልኩ አስቸጋሪውን የቤቴን በር ለመቆለፍ ስታገል። እዩልኝ እማማ ገንዘቤ በጠዋቱ ይህንን ርዕስ አንስተው 'ሲነጅሱኝ'። ቀጠሉና "ሴቱ ከሆነ ሞልቷል፤ ግራ ቀኝህን አታይም?" አሉኝ ከእኔ ክፍል በስተቀኝና በስተግራ ያሉትን ቤቶች በአገጫቸው እየጠቆሙ። ፈገግ አስባሉኝ፤ እኔ ከተከራየሁበት ክፍል በስተቀኝና በስተግራ የተከራዩትን ሴቶች መጠቆማቸው ነው። 'ላክስ ባላገቡ ኮረዳዎች መሃል ተከብቤ ነው የምኖረው?' አልኩ ለራሴ። ግን እማማ ገንዘቤ ሁለት ሰው በአንዴ እየጠቆሙ ለቅዱስ ገብርኤል ስለት መሳል ምን የሚሉት ነገር ነው። ሁለት ሴት አመልክተው ተነስተው ከሁለቱም ጋር ብሆን መልአኩ ቁጣውን እንዲያወርድብኝ ነው? አሁን ስንት የሚሳሉለት ነገር እያለ እማማ ገንዘቤ እኔ እንዳገባ ይሳላሉ? "በእርግጥ ልብ እንጂ መቼ ሴቱ ጠፋፋፋፋፋ..." አሉ፤ አሽሙር መሆኑ ነው። "በቅርቡ ጠብቁ ማዘር፤ ጥቂት ጊዜ ብቻ፤ አሁን ለማግባት ወስኛለሁ።" አልኳቸው ከበረንዳዬ እየወረድኩ፤ የ'አግባ' ንዝነዛቸውን እንዲያቆሙልኝ። "እኮ አንተ ልታገባ? እኮ አንተ ልብ ገዝተህ?" ሲሉ ልጃቸው ሩት ሳቋን ለቀቀችው። አሁን ይሄ ያስገለፍጣል? ማለቴ ያስቃል? ትክ ብዬ ሩትን ሳያት ስትስቅም ያምርባታል ለካስ። አይ ትገልፍጥ ፈቀድኩላት። ግን እማማ ቅድም ጎረቤቶቼን በአገጫቸው ሲጠቁሙ ሩትን የመሰለች ቆንጅዬ ልጅ አለመጠቆማቸው አስከፋኝ። ግን ሩትን ለማየትም ሆነ ለመምረጥ የእርሳቸው ጥቆማ አለማስፈለጉ ሲታወሰኝ ቅያሜዬ ጠፋ። "ኧረ ማሚ በወጣ በገባ ቁጥር እየነዘነዝሽው ልትገድዪው ነው" አለች የሀዘኔታ አይነት እይታ እየለገሰችኝ። "የእኔ አዛኝ" አልኩ እይታዋ አንጀቴን ቢበላው። እማማ ገንዘቤ አሁን ሩትን ባገባት ለመልአኩ ገብርኤል የተሳሉትን ስለት ያስገባሉ? አይመስለኝም፤ እንደውም ከመቅደስ ደጃፍ ተንበርክከው እንባቸውን እየረጩ "ምን ነው ፈጣሪዬ? አመስግኜ ሳልጨርስ እንዲህ ጉድ ታደርገኝ? ምን አደረኩህ አምላኬ?" እያሉ ይገኛሉ። ምክንያቱም ልጃቸው ሩት ውጪ ሃገር ያለ እጩኛ አላታ፤ እርሱም በቅርቡ መጥቶ እንደሚያገባት ይጠበቃላ። እማማም በልጃቸው እጩኛ እጅግ ደስተኛ ናቸዋ፤ ደስተኛ ብቻ ሳይሆኑ ለሰፈሩ ሰው ሁሉ በኩራት መለፈፍ ከጀመሩ ሰንብተዋላ። "እንኳን ዝም ብለነው ነዝንዘነውም በሰማ፤ ይኸው እዚህች ቤት ከገባ ስምንተኛ ዓመቱ፤ መለስ ቀለስ ከማድረግ ያለፈ አንዳች ቁም ነገር መቼ አለውና። በጊዜ አንዷን አግብቶ አይወልድም? ልጅ በልጅነት ነው" አሉ እማማ ገንዘቤ። ሩት ይህንን ስትሰማ የእፍረት አይነት ፈገግታ ፈገግ አለች "መለስ ቀለስ ከሚያደርጋቸው" የሚለው አስቋት ወይ አሳፍሯት ነው። እኔም እንዳፈረ ሰው አንገቴን አዘቅዝቄ፤ "በሉ ደህና ዋሉ" ብዬ ወደ ስራዬ ሽልክ። ሩት ግን ስትስቅም ስታፍርም ደስ ትላለች። እንደው ምክንያት ስፈልግ እንጂ ሩት ብትኮሳተርም፣ ብታለቅስም፣ ብትቆምም ብትቀመጥም ደስ ማለቷ የማይቀር ነው። "ተውውውውው" አልኩት ለራሴ፤ ቀጥሎ ምን ላስብ እንደሆነ ገብቶኛል፤ አንዴ ማሰብ ከጀመርኩ ደግሞ ምን ሊከተል እንደሚችል አይጠፋኝም። "ተው፤ ከደጓ ወዳጄ እማማ ገንዘቤና ቤተሰባቸው ጋር እንዳታቀያይመኝ" አልኩት ራሴን። ግን ልጃቸውን ማግባቴ የሚያስቀይም ነገር ነው? በእርግጥ አንድ ቤታቸው ተከራይቶ ከሚኖር፤ በዛ ላይ 'መለስ ቀለስ' የማድረግ ልማድ ካለው ሰው ይልቅ ዲያስፖራውን መምረጣቸው የሚጠበቅ ነው። ሁኖም እማማ ገንዘቤ "ከማላውቀው መልአክ የማውቀ ሰይጣን ይሻለኛል" ይሉ የለ። እኔ ደግሞ ከሰይጣኑ እሻላለሁ። እስካሁን ስለ ሩት እያሰብኩ ነው? በቃ ደጓ እማማ ገንዘቤን ላስቀይማቸው ነው። ......ይቀጥላል

የሁለት ዓመት ጉዞዬን አስመልክቶ አብራችሁኝ በዚህ ቻናል ለዘለቃችሁ ወዳጆቼ ልብ የወለደው ተከታታይ ጽሁፍ ላቀርብ ፈቀድኩ። ጽሁፉ ምን ያህል ክፍል እንዳለው አንባቢያን እንዲወስኑ እድል ለመስጠት አስብኩ። እናም እስከ ሌሊቱ አራት ሰዓት "react" በሚያደርገው ሰው ቁጥር ያህል ክፍል ይኖረዋል።

"....በሂደት ስለራሴ ያለኝ ምልከት እየተቀየረ መጣ፤ በተለይ በጥልቀት ራሴን መመልከትና ማጥናት በጀምርኩባቸው ወራቶች። ስለ ራሴ የነበረኝ እውቀት በፍጹም ጥልቅ  እንዳልነበረ በአመዛኙ ደግሞ ልክ እንዳልነበረ መረዳት ጀመርኩ። ልጅነቴንና አስተዳደጌን ሳይቀር መለስ ብዬ ቃኘሁ፤ የማላውቀው ልጅነት ተዘልሎ ጠበቀኝ። የሕይወት መንገድ በእያንዳንዱ እጥፋት ላይ በሕይወቴ ያዝረከረከውንና ተጽዕኖውን ለመረዳት ሞከርኩ፤ ከማስበው በላይ ነበር። ከሞላ ጎደል አሁን ላይ ያለው "እኔ" እንዴት እንደተሰራ በትክክል እየተረዳሁ መጣሁ። ራሴን ገልጬ ለማንበብ በጣርኩ ልክ ከማላውቀው "እኔ" ጋር እፋጠጥ ነበር፤ የማላውቃቸው ገጾች፣ የማላውቃቸው ማንነቶች። ለራሴ የነበረኝ ምልከታና የራስ ምስል ፍጽሞ የተዛባ ነበረ። ራሴን እየተረዳሁ በሄድኩ ቁጥር ግን በሕይወቴ ጥያቄ ለነበሩ ብዙ ነገሮች መልሱ "ራሴ" ሁኖ አገኘው ጀመር። ለብዙ ውድቀቶችና ለብዙ ስህተቶች ተጠያቂው ይሄው "ራሴ" ነበር። ለካስ የራሴው ጠላት ራሴው፤ የራሴ እንቅፋት ራሴ ሁኜ ነበር የምኖረው። በተቃራኒው ለእነዚህ ሁሉ ችግሮች ቅሬታ አቅራቢና አማራሪ ያው "ራሴው" ሁኖ መኖሩ ግርምት ይፈጥር ነበር። "አለማወቅ ደጉ" ይላሉ...አይ አይ "አለማወቅ ክፋቱ ነው" መባል ያለበት። ከዚህ ሁሉ በኋላ ምን ማድረግ ነበረብኝ? ይህንን ማንነት ተቀብሎ ወደፊት መቀጠል? በፍጹም! ያንን አላደረኩም። እናም አስቸጋሪ ቢሆንም አንድ ውሳኔ ላይ ደረስኩ፤ እርሱም ይህንን "እኔነት" አፍርሶ አዲስ ማንነት መገንባት። እንዳሰብኩት ቀላል አልነበረም፤ ለሁለት ለሶስት አስርት ዓመታት የተገነባ ስብዕና በቀላሉ ተንዶ እንደ ቀልድ አይገነባም። ግን የግድ መሆን ነበረበትና ከባዱንም መንገድ አሃዱ አልኩ። እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፤ በጉዞዬ የማይቻሉ የሚመስሉ ብዙ ነገሮች እንደሚቻሉ ተረዳሁ።......" ከራስ የተደረገ ምክር (ያለፉት የሁለት አመታት ጉዞ ቅኝት) የተቀነጨበ

በመሠረቱ ሴቶች ጥሩዎች ናቸው! መልካም ቅዳሜ

ለዚህ ቻናል ተከታዮች አንድ መልካም ዜና ይዤ መጥቼአለሁ። ይህም የዚህ ቻናል ተከታይ ለሆኑ ሁለት ሰዎች (አንድ ወንድና አንድ ሴት) ለአንድ ዓመት የሚቆይ ለ2016ዓ/ም ነጻ የmentorship Program ለመስጠት አቅጄለሁ። ዋናው አላማ ወጣቶች ሁለንተናዊ እድገት ማምጣት በሚችሉበት መንገድ ማገዝና ማብቃት ነው። ከሰሞኑ ዝርዝር ሁኔታውን ይዤ እመለሳለሁ፤ ፍላጎትና የእውነት መሰጠት ያላችሁ ወጣቶች አስቡበት። ከላይ እንዳልኩት mentoring እንጂ የCounseling አገልግሎት አለመሆኑን ልብ በሉ።

አንድ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንዳለሁ በተረዳሁበትና ከዚያም ሁኔታ መውጣት እንዳለብኝ በወሰንኩ ጊዜ የቅርቤ ለምላቸውና ሊያግዙኝ ለሚችሉ ሁለት ወዳጆቼ በተናጥል አማከርኳቸው፤ እርዳታቸውንም ጠየኩ። ያለሁበትን አደገኛ ሁኔታ አስረዳኋቸው (ያውም ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ)፤ ከዛ አደገኛ መስመር መውጣት እንዳለብኝ ገለጽኩላቸው። በመጨረሻም ከእነርሱ የምፈልገውን አስከተልኩ "ያለሁበትን ሁኔታ ተረድታችኋል፤ እናም ይህንን ነገር መቀየር አለብኝ። ታዲያ ይህ ውሳኔዬ ቀላል እንደማይሆን እናንተም ትረዳላችሁ። ውሳኔዬን ብዙ ሰው አይቀበለውም። የተለያዩ ግፊቶችና ጫናዎች ከፊት ይጠብቁኛል፤ እኔም ውሳኔዬ ትክክል መሆኑን ጥያቄ ውስጥ የማስገባበት አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል። ምናልባት ውሳኔዬን በምጠራጠርበት ወቅት ውሳኔዬ ትክክል እንደሆነ እንድትነግሩኝ፤ ወደኋላ እንዳላፈገፍግ እንድታግዙኝ፤ ከጎኔ እንድትቆሙ እፈልጋለሁ። ምክንያቱም ከዚህ አደገኛ ሁኔታ የግድ መትረፍ አለብኝ" ከአንድ ቀን በኋላ ለውጦችን እንዳደረኩ መጀመሪያ የነገርኳቸው ለእነዚህ ወዳጆቼ ነበር። ከሁለቱም ያገኘሁት መልስ ግን ተመሳሳይ ነበር "ያሳዝና፤ ባታደርገው ጥሩ ነበር።" የሚል። የመጨረሻው የሰው አጋዥ ምሽግ ተናደ፤ ሁሉን ነገር ብቻዬን ለመጋፈጥ ተገደድኩ። እግዚአብሔር የተመሠገነ ይሁንና አሸነፍኩ። ከዛን ጊዜ ጀምሮ አንድ ነገር ይገባኝ ጀመር፤ ምንም ይፈጠር ምንም፤ በምንም ሁኔታ ውስጥ ራሴ ለራሴ ልኖርለት እንደሚገባ። እናም ረጅሙንና አድካሚውን ውጣ ወረድ የበዛበት ጎዳና ከራሴ ጋር በጽናት ተጓዝኩ። ያን ሁሉ አልፌ እዚህ ደረስኩ። ከራስ የተደረገ ምክር (ያለፉት የሁለት አመታት ጉዞ ቅኝት) የተቀነጨበ

" በቀንና በሌሊትም ይሄዱ ዘንድ፥ መንገድ ሊያሳያቸው ቀን በደመና ዓምድ፥ ሊያበራላቸውም ሌሊት በእሳት ዓምድ እግዚአብሔር በፊታቸው ሄደ። " (ዘጸ 13:21) አቤቱ ምንም ያወቅን ብንመስል ምንም እንደተጠበብን ቢሰማን አንተ ካልመራኸን በቀናው ጎዳና መጓዝ አንችልምና ቀንተሌት ምራን! መንገድ ልታሳያቸው ቀን በደመና ዓምድ ሕዝብህን የመራህ አምላክ ነገር ሁሉ የተቃናና የተገለጠ በሚመስልበት የእድሜያችን ብረሃናማ ወራቶች አትለየን። ሁሉ መልካም ቢመስለንም፣ ሁሉ የሚታይና የምንረዳው አድርገን ብንቆጥረውም የእውቀታችን ጥግ ሁሉን አጥርቶ አያሳየንምና ከምሪትህ አታውጣን። በሌሊት ለሕዝብህ ልታበራላቸው በእሳት ዓምድ ከፊታቸው የሄድክ አምላክ ነገሮች በሚጨላልሙበት፣ በድንግዝግዝ በምንከበብበት የሕይወት ምዕራፋችንም ብረሃንህ ይብራልን። በሞት ጥላ መካከል እንኳን ብንሄድ ነፍሳችንን መልሰህ ስለስምህ በጽድቅ መንገድ ምራን። መልካም እረኛ የሆንክ አምላክ ለእኛ ከእኛ ይልቅ ታስባለህና በወደድክበት መንገድ ውሰደን፤ መልካም የሆነውን ታውቅልናለህና በመልካሙ መሰማሪያ አሰማራን። እናምንሃለን!

በሕይወት ጉዞ ማንም ሰው እስካያስፈልገኝ ድረስ ጠንካራ ለመሆን ታግያለሁ። ብቻዬን መቆም የምችል ሰው ለመሆን፤ አዎ መላ አለም በግራ ቁሞ ቢጻረረኝ በቀኝ ለመቆም የማላወላዳ ለመሆን። ብቻዬን በልበ ሙሉነት ለመጎዝ የምደፍር.... ሁኖም እኛ ሰዎች የተፈጠርነው ብቻችንን ለመሆን አይመስለኝም። ብቻ መጓዝ ብንችልም ብቻ መጓዝ አይደላንም። በርትተን ስለብርታታችን ብዙሃን ከበው እያጨበጨቡልን ቀርቦ "አይዞን" የሚለን እንፈልጋለን። በእኛ ተከልሎ የሚጓዝ በሞላበት "አትፍራ" የሚለንን መስማት እንፈልጋለን። ብዙዎችን እያሳቅን አብሮን የሚያነባ እንፈልጋለን። ብቻ የእኛ በምንለው አጥር አብሮን የሚዘልቅ የነፍስ ወዳጅ እንፈልጋለን። ምክንያቱን አላውቅም፤ የሆነ ሁኖ ማንንም ባለመፈለግና ሰው በመፈለግ መሃከል ስማጠን ራሴን አገኛለሁ። ምናልባት ነገ ማለዳ ማንንም ከማልፈልግበት ጥንካሬ ጋር ራሴን ላገኝ እችላለሁ፤ ግና ያ ጥንካሬ እስኪመሽ ከእኔ ጋር መቆየቱን እንጂ......ግን ግን ሰው መፈለግ መድከም ነው? አይመሰለኝም! ስሪታችን ሰው ፋላጊ ተደርጎ ይመስለኛል......እና ሰው መፈለግ ጥንካሬ ሊሆን ነው?

"Remember: if no resistance or obstacles face you, you must create them."

አዎ፤ ያኔ ድሮ ሕይወት... ቀላል እንዲሆን እጅግ እታገል ነበር፤ ሁኖም የታገልኩትን ያልህ ነበር የከበደው። ሕይወትን ለማቅለል ፈተናውና ተግዳሮቱን ለማቀዝቀዝ ብዙ ርቀት እየደከመኝም እየታከተኝም ተጉዣለሁ። ሁኖም የሕይወት ክብደት የምሸከምበት አቅም እስከማላገኝ ድረስ ክብደቱ ጨመረ እንጂ ለመቅለል አልፈቀደም። አዎ በእነዛ ዘመናት....በአእምሮዬ ውስጥ በቀላሉ መልስ የማላገኝላቸው ጥያቄዎች ነበሩ። የክሽፈቴን ምክንያቶች፣ የተግዳሮቶቼን ብዛቶች፣ የሽንፈቴን ጥልቀቶች እያመነሸጉ እጓዝ ነበረ። በሕይወት ውስጥ ተለይቼ የምጠቃ እስኪምስለኝ ድረስ ሁሉ ነገር ወደ እኔ ይወረወር ነበር። ሌሎች በቀላሉ ያልፉት የነበረውን መሰናክል አእላፍ ጊዜ ብዘለው መሻገር አለመቻሌ በሕይወት ውስጥ ደካማና ተጎጂ አድርጌ ራሴን እንድቆጥር ሁኜ ነበር። ያን ጊዜ.....የእነዚህ ፈተናዎች ምክንያታቸው እንኳን ሊገባኝ አይችልም ነበር። ምክንያቱም ታግያለሁ፣ ሁሉን ጥሩ ለማድረግ ቀን ተሌተ ጥሬለሁ። ግና ጥረቴና ልፋቴ ጉም ከመዝገን ባለፈ ሕይወትን ፈጽሞ ሊያቀልልኝ አልቻለም። እናም በእነዛ ወራት ሆኑብኝ ለምላቸውና በሕይወቴ ለሚያልፉ ነገሮች ተጠያቂ የማደርገው ማጣቴ ደግሞ ሌላ ራስ ምታት ነበር። ትናንት ያደናቀፈኝ ድንጋይ ዛሬም ሲያደናቅፈኝ ድንጋዩ እኔ እንዳልሆን የሚል ሌላ ፍረሃት። ብዙ መገፋት፣ብዙ ውድቀት፣ ብዙ ስብራት፣ ቆጥሬ የማልዘልቃቸው "ብዙዎች" በሕይወቴ ተፈራርቀዋል። በመላ አለም ከእኔ ወዲዪ አሳዛኝ ያለ እስከማይመስለኝ አሊያም የባሰ አሳዛኝ እንዳለ እስከማይሰማኝ ድረስ ሂጄለሁ። በሕይወት ተስፋ ቆርጬ አውቃለሁ፤ የመኖር ትርጉም ጠፍቶብኝ ከመኖር ማፈግፈግ ጀምሬ አውቃለሁ። ሁሉ ነገር እነደዛ ነበር በሕይወቴ ሁሉ ነገር መቀየር እስከጀመረበት.... እስከ ቅርብ ጊዜ። ሁሉ ነገር ተቀየረ? አዎ! እንዴት? ሕይወት ቀላል ሁኖ? በፍጹም ሕይወት ቀላል ሁኖ ወይም የሕይወቴን ጎዶሎ ይሞሉታል ያልኳቸውን በማግኘቴ አልነበረም። ሁሉ ነገር መቀየር የጀመረው ሕይወትን በትክክል እንድረዳ እግዚአብሔር አይኖቼን የሲከፍት ነበር። ሕይወት በምድር ሰልፉ እጅግ ብዙና በተግዳሮት የተሞላ፤ በምድር እስካለን የማያልቅ ፈተና የማያልቅ ተግዳሮትና የማያልቅ ዳገት ሊወገዱ የሚይችሉ እውነታዎች መሆናቸውን መገንዘብ ስጀምር ነገሮችም መለወጥ ጀመሩ። ይሄ ሲገባኝ ነው ሕይወት ቀላል እንዲሆን የማደርገውን ትግል ማቆም የጀመርኩት፤ እኔ በሕይወት ውስጥ ለመትረፍ ወይንም ቀላል ሕይወት ለመኖር ሳይሆን ለመጋፈጥና ለመታገል ሕይወት የሚጠይቀውንም ዬትኛውን ዋጋ ለመክፈል የተፈጠርኩ የሕይወት ጦረኛ መሆኔ ሲገባኝ የነገሮች መልክ መቀየር ጀመረ። መራመድ ስጀምር ከባድ የመሰሉኝ ነገሮች ቀላል አይሆኑም ያልኳቸውም ነገሮች ኢመንት ሁነው ታዩኝ። እናም በእርሱ ጸጋ በእርሱ ጥበብ ሸካራውን ጎዳና በልበ ሙሉነት መራመድ ቀጠልኩ.......

አሁን ላይ ያለኝ የትዳር አጋር መምረጫ መስፈርት ልክ እንደ ድሮ mathematics "let X=...." እንደሚባለው በ equation የሚጀምር ነው። "እንበልና" ብሎ፤ "እንበልና 7 ሚስት ባገባ" (ያው ስላልተፈቀደ እንበልና ነው የሚሆነው) የሚል equation። አላማው domainun ለማስፋት ነው። እናም እንስቶቹ scan የሚደረጉት 7 ሚስት ባገባ በሚል ነው። አንድ እንስት ከተገመገመች በኋላ የሚሰጣት ውጤት ከሚከተሉት ውስጥ ይሆናል። ልክ እንደ mathematics equation X=.... በጣም ሰቃይ ከሆነች ወይንም ውጤቱን ከሰቀለች "ይህቺ ከ7ቱ አንዷ መሆን ትችላለች" የሚል ነው። አለበለዚያ "7 ቢፈቀድልኝም ይህቺ ከ7ቱ አንዷ አትሆንም" የሚል grade ይሰጣታል። አንዳንድ ደግሞ አሉ "7ቱ ላይ ብትመረቅልኝም አያዋጣኝም" የሚያስብሉ። ማለት ሰባት ማግባት ቢፈቀድልኝና ሰባት ባገባ ከሰባቱ ውጪ እንደምርቃት ብትጨመር ራሱ የማታዋጣኝ😂 Grade አሰጣጡ ግን እንደምታስቡት ከባድ አይደለም። ያው ሰባት ኮታ ሲሰጥ ጥቂት የሚይባሉ ሴቶች "ከ7ቱ" ውስጥ ይገባሉ። ሰባት ውጥስ ለመገባት ያን ያህል የተካበደ መስፈርት የለውም፤ መልከ ግቡ ነች? ጸባዮ አብሮን ሊያኖረን ይችላል? Toxicity አለባት?  ለትዳሯንና ለባሏን ምን አይነት ቦታ ይኖራታል? እና ሌሎች መሠረታዊ ነገሮች ይታያሉ። ከዛ ባለፈ በቀላሉ ከአይኔ የምትገባ፤ ደስ ይምትል የሆነ የምትወደድ አይነት መሆኗ ትልቅ ነጥብ ያሰጣል። እና ጥያቄው 7 ስላልተፈቀደ "አንዷ ማን ልትሆን ነው? እርሷንስ በመስፈርት ልትለይ ነው?" የሚለው ነው። Fortunately, 7ቱ ውስጥ የገባች ሴት አንዷ የመሆን እድል አላት። ምክንያቱም በእኔ እይታ የማገባት ሴት exceptional አይደለችም። እንደ ማንኛውም ሰው ድክመቶች አሉባት፣ ፍጹምም ልትሆን አትችልም። ሲቀጥል ፍጹም ሴት ለትዳር አልፈልግም (በምርቃት ከሆነ ግን አይከፋም😂) ብቻ የማገባት ሴት የራሴ ምርጫዬ ናት፤ ከብዙሃን መካከል ትሁነኝ ብዬ የምወስዳት። ብዙ ሚስት ሊሆኑኝ የሚችሉ ሴቶች እያሉ ከእርሷ ጋ'ብቻ ልኖር የምወስንላት። በእርግጥ ላግባት ብዬ ከምመርጣት ሴት በውበትም በጸባይም ወይም ለእኔ ጥሩ ሚስት በመሆንም የሚሻሉ በርከት ያሉ "ሰባቱ" ውስጥ የሚገቡ ሴቶች ብዙሪያዬ መኖራቸው የማልክደው ሃቅ ነው። ሁኖም ይህንን ሁሉ እያወኩ አንዷን እመርጣለሁ። ምርጫዬ ከሁሉ የተሻለች፣ ብቸኛ አማራጭ ወይም ከእርሷ ሌላ ስሌለ ወይንም ስለማላገኝ ሳይሆን በቃ ስለምመርጣት ነው። እናም ለእኔ ትክክለኛው ፍቅር ይህ ነው! መልካም ዕለተ ቅዳሜ

በመሠረቱ ወንዶች ጥሩዎች ናቸው! መልካም ቀን

የገዛ ማስተዋላችን ቀናውን ጎዳና እንድንመርጥ አላደረገንም። ብርታትና ጥንካሬያችን ከመውደቅና ከመፍገምገም አልታደጉንም።  በራሳችን ፈቃድና ፍላጎት በጥፋት ቁልቁለት ስናዘግም፤ "ይበላችሁ" ብለህ አልተውከንም። በምክርህ አልተለየኸንም! አዎ፤ አስተምረኸንና መክረኸን ሕይወታችንን አቃንተሃል። እናም እናመሰግንህ ዘንድ ይገባናል! " የመከረኝን እግዚአብሔርን እባርካለሁ" (መዝ 16:7)

"Most of the issues of integrity we face are not big issues but small ones, yet the accumulated weight of our choices has an impact on our sense of self." Nathaniel Branden

በአንዳንድ ግንኙነቶች ውስጥ በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ጥንዶች ሳይነጋገሩ መነጋገርም እንዳለባቸው ሳይረዱ በጉዳዮቹ ላይ በመናበብና በመስማማት ይፈሳሉ። በአንዳንድ ግንኙነቶች ውስጥ ግን ጥንዶቹ በተነጋገሩባቸውና በወሰኗቸው ነገሮች ላይ ሳይቀር ከውሳኔያቸው በተቃራኒ ሲያዘግሙ ይታያሉ። እናም የግንኙነቶች መልክ የሚወሰነው በመነጋገርና በመወያየት ብቻ ሳይሆን የጥንዶቹ ባህሪያት ውህደት በሚፈጥረው Dynamics ጭምር ነው።

እኔ ሳስብ በሶስት ደረጃ ነው፤ የመጀመሪያው በሽውታ ነው። ላስብ ብዬ ሳይሆን ራሱ ሀሳብ ወደ አእምሮዬ እየተመመ ሲያሳስበኝ። ይህ የመጀመሪያው ደረጃ እጅግ ብዙ እልፍ ሀሳቦችን የሚስተናገዱበት ቢሆንም እንደ ነገሩ እንጂ በጥልቀት የማላሰላስልበት ነው። ሁለተኛው ደረጃ ብዙን ጊዜ "Walk" እያደረኩ የማስበው ነው። እየተጓዝኩ ማሰላሰል ከመልመዴ የተነሳ በውድቅት ሌሊት ቤቴ ውስጥ ራሱ እየተንጎራደድኩ ነው የማስበው። ጎዳና ላይ ብቻዬን ሳዘግም ካያችሁኝ ሁነኛ ጉዳይ እያሰላሰልኩ ሊሆን ስለሚችል.....። ይሄኛው ደረጃ ላይ ፈልጌ የማስበው እኔ ነኝ፤ ምን ላስብ ብዬ አስባለሁ፤ ቢያንስ ስለምን እንደማስብ ወስኜ አስባለሁ። ሶስተኛውና በጥልቀት የማስብበት ደረጃ ግን ብዕርና ወረቀት ይዤ ማሰብ ስጀምር ነው። በብዕር እንደማሰብ የሚያስደምመኝ ነገር የለም። በሕይወቴ የተወዛገብኩባቸው ጉዳዮች ሲገጥሙኝ የማስባቸውና የማሰላስላቸው በብዕሬ ነው። እየጻፍኩ ሳስብ የጠሩ ሃሳቦችን አገኛለሁ፤ ስህተቴንና በዙሪያዬ እየተከናወነ ያለውን ሁሉ ልረዳ በምችልበትና በሚገባኝ መንገድ እረዳለሁ። ለዚያም ይመስለኛል መጽሀፍ የምወደው፤ ሰንፌ እተወው ካልሆነ እንጂ የምጽፈው ሀሳብ ብዙም አይነጥፍብኝም። ጽሁፍ ለእኔ ከፍተኛው የማሰብና የማሰላሰል ጣራዬ ነው። ነገሮችን ፍንትው አድርጎ ሊያሳየኝ የሚችል መስታወት። ግን ታዲያ እጅግ የሚገርመኝ ነገር መጽሐፍ እየወደድኩ በሕይወቴ እጅግ ጠቃሚ ነገር መሆን እየተገነዘብኩ እንኳን ብዙ ጊዜ አለመጻፌ ነው። በቂ ምክንያት ያለኝ አይመስለኝም፤ ምናልባት ስንፍና ቸልተኝነት። ይህንን ስመለከት አንዳንዴ የምንወዳቸውን ነገሮች ያላገኘንበት በቂ ምክንያቶች አለመኖራቸውን እጠረጥራለሁ። በሕይወታችን አስፈላጊ ከሆኑ ነገሮች ጋር ተራርቀን የምንቀረው መድረስ ስላልቻልን ብቻ ላይሆን ይችላል። ምናልባት ለምንወዳቸውና ለምንፈልጋቸው ነገሮች መሰጠት ባለብን መጠን አልተሰጠንም ይሆናል፤ ምናልባት ቸልተኛ ሁነን ይሆናል፤ ምናልባት አቅጣጫ ስተን ይሆናል። ብቻ ከብዙ ነገሮች የቀረነው እንድንቀር ተወስነን ብቻ ላይሆን ይችላል። ለማንኛውም ለምን እንደማልጽፍ እየጻፍኩ ላስብ ደህና ጻፉ ማለቴ ደህና እደሩ

"We must become what we wish to teach." Nathaniel Branden