ch
Feedback
ማህደር ሚድያ ⛪️

ማህደር ሚድያ ⛪️

前往频道在 Telegram

ይህ ቻናል የ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አማራጪ ሚድያ በመሆኑ አለማቀፍ የመረጃ ስርጪት ላይ በትጋት ይሰራል።®@ማህደረ መገናኛ ብዙኃን

显示更多
1 695
订阅者
无数据24 小时
无数据7
无数据30
帖子存档
ማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል ባከናወነው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ከ7.5 ሚሊየን ብር በላይ መሰብሰቡን አስታወቀ፡፡ ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ታኅሣሥ 3 ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! የማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል ለሚያስገነባው ባለ ዐስራ ሁለት ወለል ሕንጻ ገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ኅዳር 30 ቀን 2016 ዓ.ም በግራንድ ኤልያና ሆቴል አካሂዷል። በመርሐ ግብሩ ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ(ዶ/ር)፣ የጅጅጋ ሱማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ሙሉጌታ ስዩም(ዶ/ር)፣ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ መምህር ዋሲሁን በላይ እና የአዲስ አበባ ማእከል ሰብሳቢ ዲ/ን ኃ/ማርያም መድኅን እንዲሁም  ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡ የሚገነባው አዲሱ ሕንጻ ማእከሉ ወጣት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በሙሉ አቅሙ በማስተማር የቤተ ክርስቲያን እና የሀገር ተረካቢ እንዲሆኑ ለማስቻል የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ እና በማእከሉ ለሚከናወኑ ልዩ ልዩ የሐዋርያዊ አገልግሎት፣ የሙያ አገልግሎት፣የሚዲያ ተደራሽነት እና ለቅዱሳት መካናት ተግባራት አቅም የሚፈጥር መሆኑ በዕለቱ ተገልጿል። በመርሐ ግብሩ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒውዮርክ እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ (ዶ/ር) ለሁሉ ነገር መሠረት እና ለምንፈልገው ለውጥ የምርምር እና የትምህርት ተቋማት ያስፈልገናል ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አክለውም የትምህርት፣ የጤና እና ሌሎች ትልልቅ ተቋማትን ለማቋቋም የማንንም ርዳታ ሳንጠብቅ ዐሥር ሚልዮን የምንሆን ኦርቶዶክሳውያን በዓመት ውስጥ ባሉን የፆም ወቅቶች ብቻ ለቁርስ ወጪ የምናደርገውን ብናዋጣ ዓላማችንን ማሳካት እንችላለን ብለዋል፡፡ በመልዕክታቸው መጨረሻ ላይም ይህ የአዲስ አበባ ማእከል ሕንጻ የዚህ ስኬት አካል ስለሆነ ሁላችንም የድርሻችንን ብንወጣ በአንድ ዓመት ውስጥ መጨረስ እንችላለን በማለት ተናግረዋል። የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም በበኩላቸው ይህ ዛሬ በአዲስ አበባ ማእከል እየተገነባ ያለው የወጣቶች ማእከል በአጠቃላይ ወጣቱ ትውልድ ስለ አገሩና ስለቤተ ክርስቲያኑ የሚመራመርበት፣ ዘመኑ ከሚያመጣቸው ፈተናዎች ተጠብቆ ለበጎ ነገር የሚነሳሳበት መሆኑን ተገንዝበን ምዕመናን ሁሉ ተረባርበን በአጭር ጊዜ ልናጠናቅቀው ይገባል በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። ሰብሳቢው አክለውም ማኅበሩ ባለፉት 32 ዓመታት  በሀገር ውስጥ እና በውጪ፣ በገጠርና በከተማ ውጤታማ ተግባራትን ማሳካት የቻለው በአባቶች ቡራኬ፣ በአባላቱ ጠንካራ ሥራ እና በምዕመናን ድጋፍ በመሆኑ ይህ ፕሮጀክት እንዲሳካ የሁሉም አካላት ርብርብ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ በዕለቱ በገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብሩ ላይ ከተገኙት ታዳሚዎች 7,500,000.00 (ሰባት ሚሊዮን አምስት መቶ ሽህ ብር) ቃል የተገባ ሲሆን ለዚህ በጎ ዓላማ ምዕመናን ሁሉ እንዲሳተፉ የሕንጻ ግንባታ ኮሚቴው ጥሪውን አቅርቧል፡፡

በዓታ ለማርያም ~ እመቤታችን ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት መታሰቢያ በዓል ! ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ታኅሣሥ 3 ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! ንጽሕተ ንጹሐን፣ ቅድስተ ቅዱሳን፣ ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተለዩ የተለየች፣ ከተከበሩ የተከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእናቷ ከቅድስት ሐናና ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄም በእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ ከተወለደችበት ዕለት ግንቦት ፩ ቀን ጀምሮ በወላጆቿ ቤት ለሦስት ዓመት ከኖረች በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ታኅሣሥ ፫ ቀን ‹‹በዓታ ለማርያም›› በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኢያቄምና ሐና የተሳሉትን ስእለታቸው አስታውሰው ወስደው ለቤተ እግዚአብሔር ሲሰጧትም ካህኑ ዘካርያስ ስለምግቧ ተጨነቀ፤ ሕዝቡንም ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ መልኩ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ‹‹ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ›› ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ነገር ግን ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን ‹‹እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›› አላት፤ በዚያም ጊዜ ቅድስት ማርያም እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መገባት፤ ከዚያም በክብር ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱና ሕዝቡም ‹‹የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር›› ብለው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፡፡ ለ፲፪ ዓመታትም ቅድስት ድንግል ማርያም ሰማያዊ ኅብስትና መጠጥ እየተመገበች በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡ በ፲፭ ዓመቷ ግን ለአቅመ ሔዋን በመድረሷ ከቤተ መቅደስ ትውጣልን በማለት አይሁድ በጠላትነት ተነሡባት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ይህን ሰምቶ እመቤታችንን እንዲህ ብሎ ጠየቃት፤ «ኦ ወለተ እስራኤል እፎ ትፈቅዲ ትንበሪ፤ ልጄ እንደምን ሆነሽ ልትኖሪ ትወጂያለሽ?» እርሷም «ከእግዚአብሐር በታች ያለኸኝ አባት አንተ ነህ፤ በዚያውም ላይ እናት አባቴ አደራ ያሉህ አንተን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልኝ» አለችው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ እንዲህ ብሎ አዘዘው፤ «ከነገደ ይሁዳ ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን በትራቸውን ሰብስበህ በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት ከቤተ መቅደስ አግብተህ ስትጸልይ እደር፤ በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት አውጣው፤ ምልክትም አሳይህአለው፡፡» እርሱም እንዳለው አድርጎ በማግሥቱ በትሮቹን አውጥተው ቢያዩ የአረጋዊው ዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩ ጫፍ ላይ «ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ፥ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት» የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም መጥታ በራሱ ላይ ዐረፈች፤ ስለሆነም ዮሴፍ እንዲጠብቃት ተወሰነ፡፡ ከዚህም በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤተ መቅደስ ወጥታ እስከተሰደደችበት ወራት ድረስ ዮሴፍ ቤት ኖረች፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልመኗ ክብሯ በሁላችን ላይ ይደርብን፤ አሜን፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በርቀት ትምህርት ሲያስተምራቸው የነበሩትን 155 ተማሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ኅዳር 30 ቀን 2016 ዓ.ም አስመረቀ፡፡ ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ታኅሣሥ ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! በጠቅላይ  ቤተክህነት  ጽርሐ ተዋህዶ በነበረው የምረቃ ሥነ ስርዓት ላይ  የቅዱስ  ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒውዮርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ (ዶ/ር)፣ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ሙሉጌታ ሥዩም (ዶ/ር)፣ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ መምህር ዋስይሁን በላይ፣ የማስተባበሪያ  ኃላፊዎች፣ ተመራቂዎች እና ጥሪ ተደረገላቸው  እንግዶች ተገኝተዋል፡፡ 121  ወንዶችና  34  ሴት ተመራቂ ተማሪዎች በኢ ለርኒግና በሞጁል በስምንት ማእከላት ትምህርታቸውን  መከታተላቸው  በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገልጿል፡፡ በዋናነት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ለመማር ፍላጎት ላላቸው  ኦርቶዶክሳውያን እና በሌላ እምነት ውስጥ ላሉ ወገኖች ባሉበት ቦታ በአመቺ ቴክኖሎጂ ትምህርቱ  እንደሚሰጥም ተጠቁማል፡፡  ማኅበረ ቅዱሳን በትምህርትና  ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስታባበሪያ በኩል ምእመናን በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ፣ የጠፉትን ወገኖች ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስና አዳዲስ አማንያንን ማስተማር የቅድስት ሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ  ማድረግ ተቀዳሚ ተግባሩ ነው። በማለት መልእክት ያስተላለፉት  የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ሙሉጌታ ሥዩም (ዶ/ር)  ናቸው፡፡ ሰብሳቢው  አክለውም ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት፣ የስብከት  ኬላ መሥራት፣ የተዘጉ አብያተ  ክርስቲያናትን ማስከፈት፣ ጠረፋማ  በሆኑ የሀገሪቱ ክፍሎች ለመምህራን ወርሀዊ ድጎማ በማድረግ  ረገድ ዘርፈ ብዙ ሥራ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ በዕለቱ በክብር እንግድነት የተገኙት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና  የኒውዮርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ (ዶ/ር)  ክርስትና በእውቀት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡  አንድ  ክርስቲያን  የሚያቀውን በሕይወት መግለጥ አለበት ሲሉ መልእክታቸውን  አስተላልፈዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በተጨማሪ  እንደገለጹት ቅድስት ቤተክርስቲያን  የታሪክ  ባለቤት በመሆኗ የሐዋርያትን ሕይወት ዛሬ በመኖር  ልንደግመው ይገባል ብለዋል፡፡ በዕለቱ  ያነጋገርናቸው ተመራቂዎች በበኩላቸው ማኅበረ ቅዱሳን  ላመቻቸላቸው  የትምህርት እድል በማመስገን  ትምህርቱ  የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን  ዶግማ ፣ ቀኖና ፣ ሥርዓትና  ትውፊት ላይ  የካበተ እውቀት እንዳስጨበጣቸው ለጣቢያችን  ተናግረዋል፡፡ ተማሪዎቹ በተመቻቸላቸው  ሥርዓተ ትምህርት መሠረት  የሥነ ፍጥረት ትምህርት፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ፣ ትምህርተ ክርስትና፣ ምሥጢራተ ቤተክርስቲያን፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር መግቢያ መከታተላቸው  ታውቋል፡፡

ልዩ ልዩ የቤተ እምነት መሪዎች በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እና በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተመጻሕፍት ወመዘክር ጉብኝት አደረጉ ! ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ታኅሣሥ 2 ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አባል ቤተ እምነቶች በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እና በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተመጻሕፍት ወመዘክር ጉብኝት አድርገዋል። ለቤተ እምነት መሪዎቹ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አዳራሽ በብፁዕ አቡነ ሄኖክ ሊቀ ጳጳስ የእንኳን ደኅና መጣችሁ ንግግር ተደርጎላቸዋል ብፁዕነታቸው ከእንኳን ደኅና መጣችሁ ንግግራቸው ጎን ለጎን ቤተ ክርስቲያናችን ስለምትመራበት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አደረጃጀት እና አሠራር ገለጻ በማድረግ አጠቃላይ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን የአስተዳደር ሂደት አስመልክቶ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ገለጻ አድርገዋል። ልዑካኑ በኢትኖጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሥር የሚገኘውን ሙዚየም ጎብኝተዋል። የሁሉም ቤተ እምነት መሪዎች ባደረጓቸው ንግግሮች በተደረገለቻው አቀባበል መደሰታቸውን እና እናት ቤተ ክርስቲያንን በዚህ መልኩ ለማየት እድሉን በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን አማራጭ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤ/ክ ድምፅ ✍️ የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የቴሌግራም ቻናል፦ https://t.me/jimmadiocese ✍️ የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የፌስቡክ ገጽ፦ https://www.facebook.com/jimmadiocese ✍️ ትክክለኛውን የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የማኅበራዊ ድኅረ ገጽ ለኦርቶዶክሳውያን በሙሉ ያጋሩ!

በወቅታዊ ጉዳይ ዙሪያ ከቋሚ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ በስመአብ፣ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን፡፡ በወቅታዊ ጉዳዮች ከቋሚ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፥ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን” ሮሜ 8፡35-36 ቤተ ክርስቲያን ልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራን፣ ሞትንና ስደትን፣ የመቀበል ታሪኳ ዛሬ የተጀመረ ባይሆንም በአሁኑ ጊዜ የሰው ልጅ ይኽንና መሰል መተኪያ የሌለው ሕይወት የሚያጠፋና ሥጋት ላይ የሚጥሉ ተፈጥሮአዊ፣ ሰብዓዊ ክብሩን የሚያራክስ ተግባራት እንዳይደገሙ ለማድረግ በሚጥርበት ዓለም ችግሩ በተለይም በሀገራችን እየተባባሰ መቀጠሉ እጅግ ያሳስበናል፡፡ በአርሲ ዞን በሹርካ ወረዳ ሶሌ ሚካኤል፣ በዲገሎ ማርያም፣ በሮቤ እንደቶ ደብረ ምጥማቅ ማርያም አብያተ ክርስቲያናት ላይ በተለያዩ ጊዜያት ሠላሳ ስድስት፣ እንዲሁም በሶሌዲገሉና ጢጆለቡ በተባሉ ቀበሌዎች ሃያ ስምንት ኦርቶዶክሳዊያን ከየቤታቸው ተለቅመው ሰማዕትነትን ሲቀበሉ ከእነዚህም ሰባቱ ሴቶችና ሃያ አንዱ ወንዶች ናቸው፡፡ በዚህ ጥቃት የሰባ ዓመት አዛውንትና የሃያ ስምንት ቀን ጨቅላ ሕጻናት ይገኛሉ፡፡ ከጥቂት ቀናት በፊትም በዲገሉ ማርያም ቤተክርስቲያን አምስት ምእመናን ሰማዕት ሲሆኑ የሦስት ምእመናን ቤት ተቃጥሏል። በሮቤ አንዲቶ ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም አጥቢያ በዓለ ድንግል ማርያምን አክብረው በመመለስ ላይ የነበሩ ሦስት ኦርቶዶክሳዊያን ጨለማን ተገን ባደረጉ ገዳዮች ሰማዕትነት የተቀበሉ መሆኑን ከሀገረ ስብከቱ ሪፖርት ደርሶን ከሐዘናችን ገና ሳንጽናና ይባስ ብሎ በማዕከላዊ ጐንደር ሀገረ ስብከት የጐንደር ዓቢየ እግዚእ ኪዳነ ምሕረት የአቋቋም መምህር የሆኑት መምህር ፍሥሐ አለምነው ባልታወቀ ግለሰብ በድንጋይ ተወግረው መገደላቸው እና ኅዳር 29 ቀን 2016 ዓ.ም. ከሌሊቱ 11፡00 ላይ የማዕከላዊ ጐንደር ዞን ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት በኲረትጉሃን ዘርዓዳዊት ኃይሉ ባልታወቁ ግለሰቦች በጥይት ተመተው መገደላቸው በእጅጉ ከማዘናችንም በላይ የጉዳዩን አሳሳቢነት የሚያረጋግጥ አድራጐት ሆኗል፡፡ በዚህ መግለጫ በቅርብ የተፈጸመውን ለማቅረብ ተሞከረ እንጅ ተመሳሳይ ግድያና፣ ስደት፣ የንብረት ውድመትና መፈናቀል የየዕለት ዜናችን ከሆነ ሰንብቷል፡፡ ለአብነትም ያህል በወለጋ፣ በጐንደር፣ በጐጃም፣ በወሎ፣ በሰሜን ሸዋ፣ በመሳሰሉት እየተፈጸመ ያለው ድርጊት መንግሥትና ሕገ መንግሥት ባለበት ሀገር፣ የውጭ ወራሪና ድንበር ተሻጋሪ ጠላት ሳይኖርብን፣ እርስ በርሳችን በምናደርገው መጠፋፋት፣ ሃይማኖት ተኮር ጥላቻዎች፣ የንፁሐን ሕይወት መቀጠፉና የሀገርን ሀብት መውደሙ እኛንም ሆነ በመላው ዓለም መፍቀሬ ሰብእ የሆኑ የሰብዓዊ ክብር አስጠባቂ ተቋማትን ሳይቀር ማሳዘኑ ቀጥሏል፡፡ ይህ ሁኔታ በታሪክ ከመመዝገቡ በላይ የዜጎች በሕይወት የመኖር፣ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ የመሥራት፣ የአካልና የንብረት ደኅንነታቸው መጠበቅ፣ የሃይማኖትና የእምነት ነፃነት መከበር፤ የዜጎች ሁለንተናዊ ደኅንነት የመጠበቅና የማስጠበቅ ግዴታ ያለባቸውን አካላት በሙሉ በምድርም ሆነ በሰማይ ተጠያቂ የሚያደርግ ጉዳይ ነው፡፡ እየተፈጠረ ባለው አስከፊ መከራ፣ በጭካኔ የተሞላ ድርጊት፣ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ማጣት የዜጎችን ሕይወት፣ አካልና ንብረት፣ የእምነት ተቋማትን፣ መተኪያ የሌላቸው የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ቅርሶችና መስሕቦችን ሲያወድም፣ በሀገር ሁለንተናዊ ደኅንነትና በሕዝቦች ትሥሥር ላይ የፈጠረው አለመተማመን በቀላሉ የማይመለስ አደጋ ነው፡፡ ይኽ እንደተጠበቀ ሆኖ ከተከሰተው ረሀብ፣ ድርቅ፣ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነት በተጨማሪ በየቦታው በተፈጠሩ አለመረጋጋቶችና ግጭቶች ምክንያት በርካቶች ቀያቸውን ለቀው፣ መነኰሳት ገዳማትን ትተው ተሰደዋል፤ ወላድ እናቶች፣ ሕሙማንና አረጋውያን በሕክምና እጦት እያለቁ ነው፣ ሕፃናትና ወጣቶች ከጤናማ እድገትና ከትምህርት ገበታ ተደናቅፈዋል፣ በመሆኑም ፩. ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ከግጭትና ከጦርነት፣ ከርስ በርስ መገዳደል ወጥተው በውይይትና በምክክር፣ በኃላፊነትና በተጠያቂነት ስሜት የታላቋን ሀገር መልካም ስምና ክብር እንዲሁም የዜጎቿን ሁለንተናዊ ደኅንነት የመጠበቅና የማስጠበቅ ተግባር ቅድሚያ እንዲሰጡ በጥብቅ እናሳስባለን፡፡ ፪. በቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ንፁሐን ምእመናንና ተቋማት ላይ ያተኮሩ ጥቃቶች በአስቸኳይ እንዲቆሙ፣ መንግሥትና የሚመለከታችሁ ሁሉ ዋስትና እንድትሰጡ፣ ወንጀል ፈጻሚዎችም ለፍርድ እንዲቀርቡ፣ ድርጊቱንም መላው ዓለም እንዲያወግዘው ቋሚ ሲኖዶስ በአጽንዖት ይጠይቃል፡፡ ፫. ከቤተ ክርስቲያን አልፎ የሀገርና የዓለም ሀብት የሆኑ ቅዱሳን መካናት፣ እንደ ዝቋላ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም፣ አሰቦት ደብረ ወገግ አቡነ ሳሙኤል ገዳም እና አካባቢው፣ ደብረ ሮሐ ቅዱስ ላሊበላ ገዳምና አካባቢው የመሳሰሉ ሁሉ ታላላቅ አድባራትና ገዳማት አደጋ የተጋረጠባቸው በመሆኑ ልዩ ጥበቃ እንዲደረግላቸው እናሳስባለን። ፬. በመጨረሻም በየቦታው የሚያጋጥሙ ተመሳሳይ ጥቃቶችን ለማስቀረት ይቻል ዘንድ የሚመለከታቸው አካላት ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ለቅድመ ወንጀል መከላከል ሥራ ቅድሚያ በመስጠት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ እያሳሰብን ለቅድመ ወንጀል መከላከል ሥራው መሳካትም በየደረጃው ያላችሁ አህጉረ ስብከት የስጋት መረጃዎችን ለሚመለከተው ሁሉ በማሳወቅ ግዴታችሁን እንድትወጡ በጥብቅ እናሳስባለን፡፡ ልዑል እግዚአብሔር አምላካችን ለሞቱት የተዋሕዶ ኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን አስበ ሰማእትታን እንዲከፍልልን፣ ለወገኖቻቸው ሁሉ መጽናናት እንዲሰጥልን፣ ስለስሙና ስለሰብዓዊ ማንነታቸው በመከራና ሥጋት ወስጥ ለሚገኙ ወገኖቻችን ሁሉ ጽናቱንና ብርታቱን እንዲሰጥልን፣ አጥፊዎችን እንዲገስጽልን፣ ስደትና አለመረጋጋትን እንዲያርቅልን፤ የሀገራችንን አንድነትና ሰላም፣ የቅድስት ቤተክርስቲያንን ሕልውና እንዲጠብቅልን የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ የበኩረ ትጉኃን ዘርዓዳዊት የቀብር ሽኝት ሥነ ሥርዓት በጎንደር ከተማ ተካሄደ ! ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ታኅሣሥ 1 ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ የነበሩት የበኩረ ትጉሃን ዘርዓዳዊት የቀብር ሽኝት ሥነ ሥርዓት በጎንደር ከተማ ተካሄደ። በሸኝት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የጎንደር ከተማ አስተዳር ምክትል ከንቲባ  ወ/ሮ ደብሬ የኃላ እንደተናገሩት  በበኩረ ትጉኃን ዘርዓ ዳዊት ህልፈተ ህይወት የተሰማቸውን  ሃዘን ገልፀው  አባታችን  በህይወት እያሉ መልከም ሥራዎችን ሰርተዋል ብለዋል። ወንጀለኞችን  ለመያዝ የምርመራ ቡድን ተቋቁሞ እየተሰራ ሲሆን ሕብረተሰቡ ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመቀናጅት ወንጀለኞችን ለፍርድ ለማቅረብ በትብብር ሊሰራ ይገባል ብለዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ በመምህር በኩረ ትጉሃን ዘርዓዳዊት ዕረፍት የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን ገልጸዋል። የቤተክርስቲያን ዐይን ነበሩ የሀገረ ስብከታችን ሥራ አስኪያጅ ያሉት ብፁዕነታቸው ሥራ ወዳድ እና ሰው አክባሪ አባት ነበሩ ብለዋል። ብፁዕነታቸው ተጠርጣሪዎችን ሕዝቡ አጋልጦ ሊሰጥ እንደሚገባው አባታዊ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል ሲል የጎንደር ከተማ ኮሙኒኬሽን ነው የዘገበው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ነገ መግለጫ እንደሚሰጥ አሳወቀ ! ⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜️⚜⚜ ኅዳር 30 ቀን 2016 ዓ.ም (ጅማ፤ ኢትዮጵያ) @የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን!! የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ነገ መግለጫ ይሰጣል። መግለጫው በምን ጉዳይ ላይ ትኩረት እንደሚያደርግ ባይገለጽም በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሆነ ተነግሯል። ከቀኑ 9:00 ሰዓት ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ ለሚሰጠው መግለጫ መንግስታዊ፣ መንግስታዊ ላልሆኑና በቤተክርስቲያኗ ህዝብ ግንኙነት ለተመዘገቡ መገናኛ ብዙሃን በስፍራው እንዲገኙ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን አማራጭ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤ/ክ ድምፅ ✍️ የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የቴሌግራም ቻናል፦ https://t.me/jimmadiocese ✍️ የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የፌስቡክ ገጽ፦ https://www.facebook.com/jimmadiocese ✍️ ትክክለኛውን የጅማ ሀገረ ስብከት መገናኛ ብዙኃን የማኅበራዊ ድኅረ ገጽ ለኦርቶዶክሳውያን በሙሉ ያጋሩ!

ማህደር ሚድያ ⛪️ - Telegram 频道 @jimmadiocese 的统计与分析