ch
Feedback
The Legal Oracle(Ye_Hig Mahider)

The Legal Oracle(Ye_Hig Mahider)

前往频道在 Telegram
1 978
订阅者
+1124 小时
+887
+1 26730
帖子存档
መሠረታዊ የሕግ ስህተት እና የአጣሪ አጣሪ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁጥር 1234/2013 አንቀጽ 28 (3) ምን አስቦ ነው?  ሁለት ጊዜ የማጣራት ስራ እንዲሰራ?፣  ድሮውም ሆነ አሁን ያለው የሰበር አጣሪ ችሎትና የባለ 5/7 ዳኞች ሰበር ችሎት በተጨባጭ የሰሩት ወይም አሁን እየሰሩ ያሉት እንዴት ነው?፣  የሰበር አቤቱታ ወደ 5 ዳኞች ሰበር ችሎት በሰበር አጣሪ ችሎት ከተመራለት በኋላ የሰበር ተጠሪን ሳይጠራ ባለ 5 ዳኞች ሰበር ችሎት ጉዳዩ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት የለበትም ተብሎ ሊዘጋ ይችላልን?፣  አመልካችና ተጠሪ የሚከራከሩት ጭብጥ የሚለው በሰበር አጣሪ ነው ወይስ በባለአምስቱ ዳኞች ሰበር ሰሚ ችሎት?፣  ባለ ሶስት ደኞች ሰበር አጣሪ ችሎቱ ለተጠሪ መጥሪያ መላክ አይችልም ማለት ነው?፣  በዚህ ረገድ አሁን እየተሰራ ያለው አጣሪ ችሎቱ ጭብጥ መስርቶ ጉዳዩን ለባለአምስቱ ዳኞች እንዲቀርብ እና ተጠሪም በጭብጡ መሰረት መልስ በጽሁፍ እንዲሰጥበት ተገልጾ መጥሪያ ወጪ ማድረግ አይደለንም?...ከሆነስ ከሕግ ውጪ ነው የሚሰራው ማለት ነው?  በአጠቃላይ የተጠቃሹ ንዑስ ድንጋጌ አቀራረጽ የሰበር አቤቱታ በሚታይበት ስርዓት ውስጥ የማጣራቱ ሂደት ሁለት ጊዜ (በባለ ሶስት እና በባለ አምስት ዳኞች ሰበር ችሎት) ሊታይ እንደሚገባ፣ ጭብጥ መስርቶ ተጠሪን መጥራት የሚችለው ባለአምስቱ ዳኞች ሰበር ሰሚ ችሎት መሆኑን በሚያስገነዝብ መልኩ የተደነገገ ሁኖ የሚታይ ሲሆን በተጨባጭ እየተሰራ ያለው ግን እንደ ንዑስ ድንጋጌው አገላለጽና አነጋገር አይደለም፡፡  ስለሆነም ድንጋጌው ሕጉን በማርቀቅ ሂደት በተከሰተ ግድፈት (Poor Drafting) የተቀመጠ ነው? ወይስ ሆነ ተብሎ የማጣራቱን ሂደት ጥብቅ ለማድረግ የመጣ አዲስ አካሄድ ነው?፣ ባለ 5 ዳኞች ሰበር ሰሚ ችሎት ባለ 3 ዳኞች የሰበር አጣሪ ችሎት ዳኞች በአዋጁ አንቀጽ 2 (4) እና 10 መሰረት ጉዳዩ በሰበር ችሎቱ ሊታይ የሚገባው ነው ብለው ከወሰኑ በኋላ ይኼው ውሳኔያቸው በባለ 5 ዳኞች ታይቶ ውድቅ የሚሆን/ሌላ ጭብጥ ተመስርቶ ተጠሪ የሚጠራ ከሆነ የባለ 3 ዳኞች አጣሪ ችሎት አስፈላጊነትስ የቱ ላይ ነው?...... ብዙ ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ይመስለኛል፡፡ ለማንኛውም የአዋጁ ድንጋጌ ይዘት የሚከተለውን ይመስላል፡፡ 1234/2013 አንቀጽ 28 (1)፡- የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ለሰበር ችሎት የሚቀርቡ ጉዳዮችን ክርክር አመራር ሥነ ሥርዓትን በተመለከተ የሚያወጣው ደንብ እንደተጠበቀ ሆኖ ፤ በዚህ አዋጅ አንቀጽ ፲ መሠረት አቤቱታ በሰበር የሚሰማው አስቀድሞ ሶስት የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች የተሰየሙበት ችሎት ውሳኔው በዚህ አዋጅ አንቀጽ ፪ ንኡስ አንቀጽ (፬) እና አንቀጽ ፲ ላይ በተመለከቱት መሠረት በሰበር ችሎት መታየት አለበት ብሎ ሲወሰን ነው፡፡ ብሎ ይደነግጋል፡፡ ንዑስ ቁጥር ሶስት ደግሞ፡- በአማርኛው ቅጅ፡- -የሰበር ችሎቱ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (፩) መሰረት የተመራለትን ጉዳይ መርምሮ አቤቱታ በቀረበበት ጉዳይ ላይ ያስቀርባል ብሎ ከተረዳ ጭብጥ በመያዝ በተጠሪ መልስ እንዲሰጥበት በአመልካች ከቀረበው የሰበር ማመልከቻ እና መጥሪያ ጋር ይልካል፡፡ ይላል፡፡ በእንግሊዝኛው ቅጅ ደግሞ፡- -When the Cassation Division to which the application is referred concludes upon examination of the application that the case has a merit, it shall frame issue and send the same with the Cassation application and summon to the respondent to reply in writing. ብሎ ያስቀምጣል፡፡ ሌላው የሠበር አጣሪ የሰበር አቤቱታውን በቃል ሲሰማ የሕግ ባለሙያ ያልሆነ አቤት ባይን እስኪ መሠረታዊ የሕግ ስህተት አስረዳ ብሎ የሚጠይቅበት አሰራር የሕግ መሠረቱ ምንድን ነው?፣ ከሰበር ዓላማ ጋርስ ይሄዳል? አጣሪ ችሎቱ አቤቱታውን ከሠማ በኋላ ውጤቱን በሬ/ጽ/ቤት ተከታታሉት !የሚለው አሰራር ምንጩ ሕግ ነውን? ፣ ለአቤቱታ አቅራቢ ጥሩ ያልሆነ የምርመራ ውጤቱ ወዲያውኑ ቢነገረው ሊደነግጥ/ሊጮህ ይችላል ብሎ አስቦ ይሆን? በግልጽ ችሎት የመሰማት መብትስ ውጤቱን መስማትንም አያካትትምን? ለነገሩ አያስቀርብም የሚል ውጤት ወዲያው ሲነገራቸው መድኃኒት የጠጡና የወደቁ፣ ግቢውን በጩኸት የቀወጡ ....ተዝለፍልፈው የወደቁ ...ባለጉዳዮች ያጋጥሙ እንደነበር አስታውሳለሁ:: የሆነ ሁኖ ሕግ ገዥ መሆን የለበትም ወይ? ባለ አምስት ዳኞች ችሎትስ የፍርድ አጻጻፍና አገላለጽ ሥርዓቱ በልማድ/ከመደበኛው የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕጉ) የመጣ ነው ወይስ ችሎቱ በአሰራር ያዳበረው?.....የልዩነት ሐሳብ አጻጻፍና አገላላጽስ ተገቢነት አለው?....ወዘተ የዳኞች አመዳደብስ?....... NB:_ የኢትዮጵያ የሠበር እና የአስገዳጅ ሕግ ትርጉም ስርዓት በሚለው መጸሐፌ(coming soon) የእኔን አቋም በዝርዝር አስቀምጬአለሁ! _ ለጊዜው መፋትሔው አፋጣኝ የሕግ ማሻሻያ ማስደረግ (by initiative of FSC) ይመስላል።

_N.B (some useful Tips From Code of Civil Procedure: book by Jatindra Kumar Das) - Rules of Procedure are intended to be a handmaid to the administration of Justice. A Party cannot be refused just merely because of some mistakes, negligence, inadvertence or even infraction of the rules of procedure....... - Procedure is mere machinery and its object is to facilitate and not to obstruct the administration of justice. - We must always remember that procedural law is not to be a tyrant, not an obstruction but aid to justice. It has been wisely observed that procedural prescriptions are the handmaid and not the mistress, a lubricant, not a resistant in administration of justice

የሰበር ችሎቱ አስገዳጅ የህግ ትርጉሞችን መነሻ በማድረግ በወንጀል ጉዳይ የመከላከያ ማስረጃ መለኪያ መጠን በሚል አርዕስት የተሰነድ አርቲክል ነበረኝ(ያልታተም ግን ለህትመት ዝግጅት ላይ ያለ)፡፡ ሆኖም ፓርላማው በዛሬው ስብሰባ የወ/መ/ስ/ስ/ህጉን በአዲስ ህግ ሊተካ ይችላል የሚል መረጃ ወጥቷል፡፡ ከአርክቲክል ውስጥ ይህ ክፍል ተቀምጦ ነበር፡፡ እስቲ አዲሱ ህግ ምን ይዞ ይመጣ ይሆን? ከሚል የተለጠፈ ነው፡፡ ....... ፰ ሂሳዊ ምልከታዎች እና የመፍትሔ ሃሳቦች (RECOMMENDATIONS) ሀ. ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት፡ ሰበር ሰሚ ችሎቱ በሌላ አጋጣሚ አቋሙን መከለስና፤ ጥርጣሬን "መፍጠር" የሚለውን በተከሳሽ ላይ ሸክም የሚጥለውን ቃል መተው፣ መከላከያው የማስረዳት ሸክም እንደሌለበት ማረጋገጥ፣ እና የመጨረሻው መለኪያ የሚተገብረው በአንቀጽ 149 ላይ ሁሉንም ማስረጃዎቹ ከታዩ በኋላ መሆኑን ግልፅ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ እንዲሁም የፍሬ-ነገርና የህግ ጥያቄን ለመለየት የፈረንሳይን የህግ ባህሪ መስጠት (Qualification juridique des faits) ዶክትሪን መቀበልን ሊያስብበት ይገባል፡፡ ለ. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት (በረቂቅ ሥነ-ሥርዓት ሕጉ ላይ)፡ ፓርላማው ረቂቅ የወንጀል ሥነ-ሥርዓት ህጉን ከማፅደቁ በፊት የሚከተሉትን መሰረታዊ ማሻሻያዎች ማድረግ አለበት፡- 1. የአንቀጽ 386(2) "በበቂ ሁኔታ" የሚለው አሻሚ ሐረግ ወጥቶ፣ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ባለው "ከምክንያታዊ ጥርጣሬ በላይ" (Beyond Reasonable Doubt) በሚለው ደፍሮ ሊተካ ይገባል፡፡ 2. ተከሳሹ "በቂ ጥርጣሬ መፍጠር አለበት" የሚለው አንቀጽ 390(1) ሙሉ በሙሉ ተሰርዞ፣ "በአጠቃላይ የቀረበውን ማስረጃ ፍርድ ቤቱ ሲመዝን ምክንያታዊ ጥርጣሬ ካለ ተከሳሹ የጥርጣሬው ተጠቃሚ ይሆናል" በሚል መስተካከል አለበት፡፡ 3. አንቀጽ 386(3) (የቅጣት ማክበጃን በፍትሐብሔር ሚዛን ማረጋገጥ) ሕገ-መንግሥታዊ ጥሰት ያለበት በመሆኑ ሊሰረዝ ይገባል፡፡ ፱.ማጠቃለያ የፌ.ጠ.ፍ/ቤት ሰበር መዝገብ ቁጥር 235007 በማስረጃ አቀራረብ ቅደም-ተከተል ላይ የሰጠው ብይን ትክክለኛ ቢሆንም፤ ለመከላከያ ያወጣው የማስረጃ መለኪያ የኢትዮጵያን የወንጀል ሥነ-ሥርዓት መዋቅር (Architecture) አደጋ ላይ የሚጥል ነው፡፡ የ1954ቱ ሥነ-ሥርዓት ህግ በአንቀጽ 141 ስር "ካልተስተባበለ" የሚለውን ሀረግ መጠቀሙ የሚያሳየው የመነሻ ማስረጃ (Prima facie) መለኪያን እንጂ የመጨረሻውን የወንጀል መለኪያ አለመሆኑን፣ እና መከላከያ (በአንቀጽ 142) "ተገቢ ጥርጣሬ መፍጠር" እንደማይጠበቅበት የዶክትሪን ትንታኔው አሳይቷል፡፡ ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት ይህ አደገኛ የዳኝነት ስህተት በአዲሱ ረቂቅ የወንጀል ሥነ-ሥርዓት ህግ ውስጥ በቀጥታ ህግ ሆኖ የሚጸድቅ ከሆነ እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡ የወንጀል ማስረጃ መለኪያ አንድ ወጥ እንጂ የተከፋፈለ አይደለም፤ በተከሳሹ ላይ የሚያስቀምጠው ምንም ዓይነት የማስረዳትም ሆነ ማስረጃ የማቅረብ ሸክም የለም (ተከሳሹ የጥርጣሬ ተጠቃሚ ብቻ ነው)፡፡ ሰበር ሰሚ ችሎቱ ይህንን ግድፈት እስካላረመው፣ እና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አዲሱን ረቂቅ ህግ (በተለይ አንቀጽ 386፣ 389 እና 390ን) ሳይከለስ ካፀደቀው፣ የኢትዮጵያ የወንጀል ፍትህ ሥርዓት በሕገ-መንግሥትና በዓለም አቀፍ ህግ ከተጣለበት ግዴታ በተቃራኒ የማስረዳት ሸክምን በስውርም ሆነ በግልፅ ከዐቃቤ ህግ ወደ ተከሳሽ የሚያሸጋግርበት የታሪክ ምዕራፍ ይከሰታል ማለት ነው፡፡ የወንጀል ፍትህ የወርቅ ክር የሆነው በንፁህና የመገመት መብት በአለም አቀፍ ደረጃ በሰፊው ተቀባይነት ያለው ሰብአዊ መብት በመሆኑ ከዳኝነት ስህተትም ሆነ ከሕግ አውጪው ግድፈት የፀዳ፤ የተሻለ የህግ ጥበቃ የሚያሻው ትልቅ መብት ነው፡፡

ህጋዊ ጉዳዮች ማብራሪያ ይህ አጭር እይታ በአዋጅ ቁጥር 818/2006 እና በደንብ ቁጥር 324/2006 መሰረት አንድ ሰነድ “ህጋዊ የይዞታ መብት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት” ተብሎ ህጋዊ ተቀባይነት እና የካዳስተር ምዝገባ ተፅዕኖ እንዲኖረው የሚያስገድዳቸውን ሦስት መሰረታዊ የህግ ቅድመ-ሁኔታዎች ያቀርባል። እነዚህ ጉዳዮች በህግ ትንታኔ እንደሚከተለው ይብራራሉ፡- ይህ አዋጅ ከ11/11/2017 ዓ/ም ጀምሮ ስራ ላይ በዋለው የከተማ መሬት ይዞታ እና መሬት ነክ ንብረት ለመመዝገብ በወጣ አዋጅ ቁጥር ፩ሺ፫፻፹፩/፪ሺ፲፯(1381/2017) መተካቱን ቅድሚያ ያስተውሉ፡፡ አዋጅ ቁጥር 818/2006ን ለማብራራት የተፈለገው ሰበር ችሎቱ የቀደመውን የህግ ትርጉም ለመለወጥ ስለተጠቀመበት የውሳኔውን ትችት አንባቢው በሚገባ እንዲረዳው ታስቦ ነው፡፡ አስቀድሜ ለጥፌ የነበርኩትን የሰበር ውሳኔ ትችት ከማንበባችሁ እና ኮሜንት ከመስጠታቸሁ በፊት ይህችን አጭር ማብራሪያ ለግንዛቤ ያክል አንብቧት፡፡ 1. የይዞታ ማረጋገጥ (Adjudication) ሂደት የህግ ግዴታ በካዳስተር ህጉ መሰረት ምዝገባ የሚከናወነው ከዚህ ሂደት በኋላ ብቻ ነው። ይህ ሂደት በህግ የተደነገገው ሦስት ዋና ዋና ነገሮችን ያካትታል፡-  የህዝብ ተሳትፎ እና የይፋ ማስታወቂያ፡- በደንቡ አንቀጽ 17 መሰረት፣ ምዝገባ ከመጀመሩ ቢያንስ 15 ቀናት በፊት የይፋ ማስታወቂያ በህጋዊ መንገድ መወጣት አለበት። ይህ የህግ ግዴታ ተቃውሞ ያላቸው ወገኖች መብታቸውን የሚጠይቁበትን ህጋዊ ጊዜ ያረጋግጣል።  የድንበር መለካት እና ምልክት ማድረግ፡- መሬቱ በሳይንሳዊ/ጂኣይኤስ ዘዴ በትክክል መለካትና የድንበር ምልክቶች በስፍራው መደረግ አለባቸው። ይህ የመሬቱን ፊዚካል ክልል ከሌሎች ጋር ለመለየት የሚያስችል የህግ መሰረት ነው።  የቅሬታ ሰሚ ሂደት፡- በደንቡ አንቀጽ 22 መሰረት ተቃውሞ ካለ በቀበሌ/ክፍለ ከተማ ደረጃ በሚቋቋመው የማረጋገጥ ቅሬታ ሰሚ ጉባኤ መወሰን አለበት። ይህ ሂደት ሳይጠናቀቅ ምዝገባ በህግ የተከለከለ ነው። 2. የቦታ ልዩ መለያ ቁጥር (Unique Parcel Identification Code) ህጋዊ ጠቀሜታ በአዋጁ አንቀጽ 8 እና በደንቡ አንቀጽ 61(1)(ሀ) መሰረት፣ እያንዳንዱ የሚመዘገብ የመሬት ቁራጭ ልዩ የሆነ ድጋሚ ሊሰጥ የማይችል መለያ ቁጥር ይኖረዋል። ይህ ቁጥር በካዳስተር መሰረታዊ ካርታ (Cadastral base map) ላይ የሚመሰረት ሲሆን፣ የመሬቱን ህጋዊ ማንነት እና የመዝገብ ተዓማኒነት የሚያረጋግጥ ዋና የህግ መሳሪያ ነው። ይህ ስርአት ከሌለ፣ የተደራቢ ወይም የተጋራ ሰነድ መፈጠር በቴክኒካል እና በህጋዊ ደረጃ የማይቀር ውጤት ይሆናል። 3. ህጋዊ የምዝገባ ሰርተፊኬት አሰጣጥ ህጋዊ ሂደት ከላይ የተጠቀሱት የማረጋገጥ እና የመለያ ቁጥር ሂደቶች ሙሉ በሙሉ ከተጠናቀቁ በኋላ ብቻ፣ በአዋጁ አንቀጽ 33 እና በደንቡ አንቀጽ 61 መሰረት ህጋዊ መዝጋቢ ተቋም (Registering Institution) ሰርተፊኬቱን ይሰጣል። ሰርተፊኬቱ የግዴታ የባለመብቱን ሙሉ ስም፣ የቦታውን ልዩ መለያ ቁጥር፣ የይዞታ መብትና ግዴታዎችን በግልጽ የያዘ እና የህግ ማህተም ያለበት መሆን አለበት። ይህ ሂደት “ምዝገባ” በመባል የሚታወቀውን የህግ ተጽዕኖ ያመጣል። የህግ ትንታኔ ማጠቃለያ በአጠቃላይ ክላይ ባጭሩ የተቀመጠው ህጋዊ ጉዳይ የሚያሳየው በአዋጅ 818/2006 ስር “ምዝገባ” ወይም “የተመዘገበ ሰርተፊኬት” የሚለው ቃል ቀላል የአስተዳደር የይዞታ ማስረጃ መስጠትን አይገልጽም። ይልቁንም፣ ይህ ቃል የተወሰኑ ጥብቅ የህግ ስነ-ስርአቶችን (ማለትም ማረጋገጥ፣ ልዩ መለያ ቁጥር፣ እና በተመረጠ ተቋም የመጨረሻ ምዝገባ) ያለፈ ህጋዊ ተግባርን ብቻ ያመለክታል። ስለሆነም፣ አንድ ፍርድ ቤት የቅድሚያ መብትን ለመወሰን የአዋጁን አንቀጽ 43 ድንጋጌን ቢጠቀምም፣ በመጀመሪያ ደረጃ ተከራካሪዎቹ ያቀረቡት ሰነድ ከላይ የተገለጹትን ህጋዊ ቅድመ-ሁኔታዎች ያሟላ መሆኑን ማረጋገጥ የህግ ግዴታ ነው። ያለዚህ ማረጋገጫ የተሰጠ “ምዝገባ” በህጉ መሰረት ተቀባይነት የለውም።

ክስተትን በደረቅ የህግ ፊደል (Legal Formalism) ከመፍታት ባለፈ ማዘጋጃ ቤቶች ለፈጠሩት መዋቅራዊ ብልሹ አሰራር ቀጥተኛ ሀላፊነት የሚወስዱበት፣ በቅን ልቦና የገነቡ ዜጎች ከመፈናቀል የሚድኑበት እና የተሟላ ካሳ የሚያገኙበት ማህበራዊ ፍትህን (Social Justice) ያረጋገጠ የህግ ትርጉም እና የተቋማት ማሻሻያ የግድ ይላል። ማስታወሻ፡-ይህ ትችታዊ ምርመራ (case comment) ለትምህርታዊ ዓላማ የተዘጋጀ ሲሆን ውሳኔውን ከሕግ ንድፈ-ሃሳብና ከተግባር አንጻር ለመመርመር ያለመ በመሆኑ የህግ ምክር አገልግሎትን አይተካም፡፡

መዝገብ አመልካቾች ያሉ ግለሰብ ሴቶችን፣ አረጋውያንን እና በኢኮኖሚ የተገለሉ ሰዎችን በስርአት ደረጃ ይጎዳል። ይህ የፆታ እና የማህበራዊ መደብ እይታ በውሳኔው ውስጥ ፍፁም አልተንፀባረቀም። በተጨማሪም፣ ችሎቱ ቤታቸውን ለሚያጡ ወገኖች መፍትሔ ይሆናል ብሎ የፍ/ብ/ህ/ቁጥር 1198ን እና በአዋጅ 818/2006 አንቀጽ 40 የተመለከተውን የዋስትና ፈንድ (Security Fund) ማጣቀሱ የህግ ቃል ኪዳን እና የተቋማዊ እውነታን ክፍተት ያሳያል። በአብዛኛዎቹ የአገራችን አካባቢዎች ይህ የዋስትና ፈንድ ፈፅሞ አልተቋቋመም። ያልተቋቋመን ፈንድ ጠይቁ ማለት በተግባር የማይደረስ የፍትህ ተደራሽነት እንቅፋት ነው። የህግ ስርአቱ ፍትሀዊነት የሚለካው ደግፎ በያዘው የተቋማት አሰራር መሆኑን ስነ-ማህበረሰብ ያስገነዝበናል። ከማህበራዊ እምነት እና የተቋማት ህጋዊ ቅቡልነት አኳያም ውሳኔው ትልቅ ክፍተት ያለበት ሁኖ ይታያል። ዜጎች መንግስታዊ ሰነዶችን ተቀብለው፣ በኋላ ግን ለቀድሞ ተመዝጋቢዎች ቅድሚያ በመሰጠቱ ሰነዶቻቸው ውድቅ ሲደረጉ፣ በመንግስት ማረጋገጫ ላይ መተማመን አይቻልም የሚል አደገኛ መልዕክት ይተላለፋል። ይህ የእምነት መሸርሸር ማህበራዊ ትስስርን ያናጋል። ቀድሞ የነበረው የግንባታ ቅድሚያ መርህ መደበኛ ተቋማት አስተማማኝ ባልሆኑበት አውድ ውስጥ ራስን የመርዳት (Self-help) ጥረትን እንደ ህጋዊ ስትራቴጂ እውቅና የሰጠ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። መደበኛ ስርአቱ እምነት የሚጣልበት አማራጭ ሳያቀርብ የራስ-እርዳታን ማፈን ማህበራዊ ግጭትን ሊጨምር ይችላል። ከዚህም በላይ፣ የዚህ ዓይነቱ ውሳኔ ተጨባጭ ማህበራዊ መዘዝ ቤተሰብን ከመኖሪያ ማፈናቀል፣ የልጆችን ትምህርት እና የማህበረሰብ ትስስርን ማናጋት በመሆኑ ፍርድ ቤቶች ህግን ሲተረጉሙ የህጉን ሰብአዊ ወጪዎች (Human cost) ሊገነዘቡ ይገባል። ችሎቱ በውሳነው 5. ማጠቃለያ ምንም እንኳን ችሎቱ ለጉዳዩ በቀጥታ ተፈጻሚ የሚሆኑ ሕጎችን በአግባቡ ከመለየትና ውሳኔውን ከሕግና ማኅበረሰብ (Law and Sociology) ትንተና መነጽር ከመመርመር አንጻር ድክመት ቢታይበትም፣ ችሎቱ ቀደም ሲል በሰ/መ/ቁ. 186946 ጸንቶ የነበረውን ትርጉም ለመሻር ሲወስን ያሳደረው አስተሳሰብ ከበርካታ ምክንያታዊ ግምቶች የተነሳ ነው ለማለት ይቻላል። ችሎቱ በቀዳሚነት ያነጣጠረው ሕግ አውጭው በአዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 43 ላይ "ቀድሞ ያስመዘገበው ቅድሚያ ይሰጠዋል" የሚል ግልጽ ድንጋጌ ባስቀመጠበት ሁኔታ ፍርድ ቤቱ ራሱ ከዚህ ድንጋጌ ውጪ ሆኖ "ቀድሞ ያገነባው ቅድሚያ ይሰጠዋል" የሚል ምትክ ደንብ ማስቀመጡ የሥልጣን ክፍፍልን (separation of powers) የሚጥስ ድርጊት መሆኑን በማረም ወደ ሕግ አውጭው ግልጽ ፈቃድ መመለስ ላይ ነው። ከዚህ ጎን ለጎን ችሎቱ ቀደም ሲል ጸንቶ የነበረው "ቀድሞ ገንብቶ ያለው ባለመብት ነው" የሚለው መርህ ተከራካሪ ወገኖች ተሽቀዳድመው ቤት እንዲገነቡ የሚያደፋፍር የተዛባ ማበረታቻ (perverse incentive) መፍጠሩን ፣ ህገ ወጥ ግንባታን ማስፋፋቱን፣ ክርክርን ማብዛቱን፣ ሀብት ማባከኑን በመገንዘብ ይህን ማበረታቻ አስቀርቶ ግልጽና ተገማች (predictable) የሆነ መመዘኛ ማለትም የምዝገባ ቅድሚያ በማስቀመጥ የሕግ ርግጠኝነትን (legal certainty) ለማጠናከር ታስቦ ነው። ችሎቱ በተጨማሪ "ማንም ከሌለው በላይ ለሌላ ሊሰጥ አይችልም" ከሚለው ዓለም አቀፍ የሕግ መሠረታዊ መርህ ታሳቢ ያደረገ በሚመስል መልኩ ቀድሞ ለተመዘገበው ባለይዞታ የተመደበን ቦታ ዝቅተኛ ደረጃ ያሉ የመሬት ጽ/ቤቶች ዳግም ለሌላ ሰው ለመመደብ ሥልጣን ስላልነበራቸው ሥልጣን-አልባ ተግባር ሕጋዊ ውጤት ሊያስከትል አይገባም፤ ተቋማዊ ስህተት ወደ ግለሰባዊ መብት ሊለወጥ አይችልም፣ የሚለው ምክንያትም ከችሎቱ አስተሳሰብ ጀርባ ያለ ይመስላል። ይህ ሁሉ ሲባል ችሎቱ ለተጎዳው ሁለተኛ ካርታ ያዥ ያለ ፍትሕ ይቀራል ብሎ ያላሰበ መሆኑንም ከውሳኔው ማንበብ ይቻላል፤ፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1198 እና አዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 40 በመጥቀስ ተጎጂው ከመንግሥት ካሣ የመጠየቅ መብት እንዳለው ማመልከቱ "ባለመብት ማን ነው?" ከሚለው ጭብጥ ባሻገር "ተጎጂው ምን ያግኝ?" የሚለውንም ጭብጥ ለማንሳት ጥረት ማድረጉን ያሳያል( ምንም እንኳን ይህ ካሣ ተግባራዊ የሚሆንበት ሥርዓት ባይዘረጋም)። በጥቅሉ ችሎቱ ሕገ ወጥ ድርጊት ላይ ተመሥርቶ ሕጋዊ መብት ሊመሠረት አይገባም የሚለውን ሁለንተናዊ መርህ ማጽናት ያለመ ይመስላል፡፡ ይኸውም ተደራቢ ካርታ ይዞ ቀድሞ በመገንባት ብቻ ባለመብት መሆን ሕገ ወጥ ድርጊትን ማበረታታት ስለሆነ ይህን መንገድ ዘግቶ ፎርማል ምዝገባን ብቸኛ የቅድሚያ መሠረት ማድረግ ችሎቱ ለውሳኔው ያስቀመጠው ማዕከላዊ ሎጂክ(Ratio Decidendi) ነው ለማለት ይቻላል:: ሆኖም ይህ ሎጂክ ትክክለኛ ቢሆንም ችሎቱ ለጉዳዩ ተፈጻሚ የሚሆኑትን ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ባለመለየቱና ውሳኔውን ሕጉ ከሚገኝበት ማኅበራዊ አውድ (social context) ጋር ባለማገናዘቡ ውጤቱ ከታለመው ግብ ያነሰ ሆኗል። ችሎቱ በአዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 43(3) ላይ የተቀመጠውን "በመጀመሪያ መብቱን ያስመዘገበ ሰው ቅድሚያ ይሰጠዋል" የሚለውን ጥብቅ የካዳስተር መርህ ወስዶ፣ መደበኛ የካዳስተር ምዝገባ (Formal Registration) ባላደረጉ፣ ነገር ግን በተራ የአስተዳደር አሰራር የድሮ ካርታ (Administrative allocations/Kartas) በያዙ ተከራካሪዎች ላይ ተፈፃሚ አድርጎታል። በህግ ትንታኔ (Legal Analysis) መነፅር፣ በአዋጅ 818/2006 ስር "ምዝገባ" (Registration) ማለት በህዝብ ተሳትፎ ታይቶ፣ ድንበሩ በጂ.ፒ.ኤስ (GPS) ተለክቶ፣ ልዩ መለያ ቁጥር ወጥቶለት፣ በመዝጋቢ ተቋም (Registering Institution) ህጋዊ መዝገብ (Legal Register) ላይ መስፈር ማለት ነው። ችሎቱ ይህንን ጥብቅ የህግ ትርጓሜ ወደ ጎን በመተው፣ የማዘጋጃ ቤት እና የቀበሌ ሹማምንት የሰጡትን ማንኛውንም ተራ ካርታ እንደ "ምዝገባ" ቆጥሮ አንቀጽ 43ን ተግባራዊ ማድረጉ፣ የህጉን (የአዋጁን እና የደንቡን) መሰረታዊ ፅንሰ-ሀሳብ (Legislative Intent) የሳተ ነው። የችሎቱ ውሳኔ (ማህበሩ ቀድሞ ካርታ ስለተሰጠው ቅድሚያ አለው የሚለው አቋም) ፍትሀዊነትን ለማምጣት የተሞከረ ቢሆንም፣ በተጨባጭ ግን ህጋዊ የካዳስተር ሰርተፊኬት ላልሆኑ ሰነዶች (Non-cadastral documents)፣ የካዳስተር ህግን (Cadastre Law) ወደኋላ በመመለስ (Retroactively) ተግባራዊ ማድረግ ሆኖ እናገኘዋለን። እንዲሁም የአዋጅ 818/2006ʽንʽ እና ደንብ 324/2006ʽንʽ ከመሸጋገሪያ ድንጋጌዎቻቸው ውጭ በማውጣት፣ መደበኛ የካዳስተር ማረጋገጥ ሂደት ላላለፉ ነባር የአስተዳደር ካርታዎች ላይ የካዳስተር የቅድሚያ ምዝገባ መርህን ተፈፃሚ ማድረጉ ትልቅ የህግ ስህተት ነው። ከዚህም በተጨማሪ ከህግ እና ከስነ-ማህበረሰብ (Law and Sociology) አንፃር፣ ውሳኔው የሚተገበረው በቢሮክራሲያዊ ብልሹነት፣ ለመደበኛ ተቋማት በእኩል አለመድረስ፣ እና በህጋዊ መፍትሔዎች እና በተቋማዊ አቅም መካከል ጥልቅ ክፍተት (የዋስትና ፈንድ አለመኖር) ባለበት ማህበራዊ አውድ ውስጥ መሆኑን ችሎቱ ዘንግቷል። በመሆኑም የህግ ስርአቱ ማህበራዊ ተግባሩን እንዲወጣ ከተፈለገ የህግ ዶክትሪን ከሚመለከታቸው የመሸጋገሪያ ህጎች ጋር መጣጣም አለበት። በተጨማሪም፣ የተደራቢ ካርታ

ችሎቱ የተመለከተበት መንገድ ከህግ መርህ/ ደንብ አንፃር ትልቅ ክፍተት አለበት። ህጉ በቅን ልቦና (Bona fide) በሚገነቡ እና በክፉ ልቦና (Mala fide) በሚገነቡ ሰዎች መካከል ግልጽ ልዩነት ያደርጋል። በዚህ ጉዳይ ላይ አመልካቾች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታቸውን የተቀበሉት ስልጣን ካለው የመንግስት አካል ሲሆን፣ የግንባታ ፈቃድ አውጥተው ቤታቸውን የገነቡ በመሆናቸው በቅን ልቦና የገነቡ ናቸው። ችሎቱ ይህንን የህግ ልዩነት ሳይመረምር፣ እነዚህን ሰዎች እንደ ተራ ወራሪ ቆጥሮ ማለፉ የህግ ትንታኔውን አጓድሎታል። በተጨማሪም ውሳኔው ህገ-መንግስታዊ ውጥረት ይፈጥራል። መንግስት ተደራቢ ካርታ ሲሰጥ፣ አንድ ዜጋ በሰነዱ ተማምኖ ጉልበቱንና ካፒታሉን አፍሶ በቅን ልቦና ቤት ከገነባ፣ ያፈራው ሀብት በህገ-መንግስቱ አንቀጽ 40(2) መሰረት የግል ንብረት ነው። ይህ ንብረት እንዲፈርስ ወይም እንዲወረስ ማዘዝ ይህንን ህገ-መንግስታዊ ዋስትና የሚጋፋ ይሆናል። ከስነ-ህግ አኳያ ችሎቱ ጥብቅ የሆነ የምዝገባ-ቅድሚያ መርህን መቀበሉ፣ የብዙ አገራት የህግ ባህል የይፋነት መርህ (Publicity) ተብሎ የሚጠራውን ሀሳብ ያንፀባርቃል። ነገር ግን የይፋነት መርህ፣ አስተማማኝ እና በተገቢው የሚሰራ የምዝገባ ስርአት መኖሩን አስቀድሞ ያስባል። የምዝገባ ስርአቱ ራሱ የስህተት ምንጭ በሆነበት ሁኔታ የቅድሚያ መብት መርህን በጭፍን መተግበር ህጋዊ እርግጠኝነትን ከማምጣት ይልቅ የፎርማሊዝም ፓራዶክስ (Paradox of Formalism) ይፈጥራል። የህግ ስርአቱ መብቶችን ለመወሰን በመደበኛ ምዝገባ ላይ ይበልጥ በተደገፈ ቁጥር፣ የምዝገባ ስህተቶች የሚያመጡት መዘዝ የዚያኑ ያህል አውዳሚ ይሆናል። የችሎቱ ውሳኔው ሁለተኛውን ካርታ ያዥ ቅን ልቦና (good faith) ስለመኖር አለመኖሩ ግምት ውስጥ ያላስገባ ሲሆን፣ ይህ ከፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1195 ያለው "ቅን ልቦና ያለው ባለይዞታ" (bona fide possessor) ጽንሰ ሐሳብ ጋር ይበልጥ ቢዋሐድ የተሟላ ይሆን ነበር። ሁለተኛው ካርታ ያዥ ስለ ቀዳሚው ይዞታ ምዝገባ ሳያውቅ (in good faith) ካርታ ወስዶ ከፍተኛ ወጪ ያወጣ ከሆነ፣ ይህ ሁኔታ ቅድሚያ ባይሰጠውም ለካሣው ስሌት ግን ግምት ውስጥ ሊገባ ይገባ ነበር። ችሎቱ ለዚህ ዝርዝር ነጥብ ግልጽ የሕግ መመሪያ አላስቀመጠም። ውሳኔው ቅድሚያ መብትን በምዝገባ ቅደም ተከተል መወሰኑን ቢገልጽም፣ ተደራቢ ካርታ ያዥው ግንባታ ካካሄደ ለዚያ ግንባታ ግምት ክፍያ (compensation for improvements) ስሌቱ በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1178 መሠረት የሚሰላ ስለመሆን አለመሆኑ፤ከአዋጅ ቁ. 818/2006 እና ፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1198 ጋር ያለውን መስተጋብር፣ በበቂ ሁኔታ አልተተነተነም። ችሎቱ ግለሰባዊውን (individual) ክርክር ለመደበኛው ሰበር ችሎት የመመለሱ ሂደትም ጉዳዩ ተጨማሪ ጊዜ ሊወስድ የሚችል መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን ይህም ለተከራካሪ ወገኖች ተጨማሪ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል። ችሎቱ ሕጋዊ መርሁን ካስቀመጠ በኋላ ለዋናው ነገሩም ራሱ ውሳኔ ቢሰጥ ቅልጥፍናና ውጤታማነቱን ያሳድግ ነበር ማለት ይቻላል፤ ምንም እንኳን ይህ ከስነ ስርዓት ሕግ አቀራረብ ጋር ሊጋጭ ቢችልም። 3. ክፍል ሁለት፡- የካዳስተር ህጎች አተገባበር እና ዶክትሪናዊ ግድፈት የሰበር ችሎቱ ውሳኔውን የመሰረተው የከተማ መሬት ይዞታ ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 818/2006ን እና አስፈፃሚ ደንብ ቁጥር 324/2006 ድንጋጌዎችን በመተግበር ቢሆንም፣ የህጎቹን አጠቃላይ ይዘትና አላማ በጥልቀት ስንመረምር፣ ችሎቱ ይህንን አዋጅ በዚህ የተደራቢ ካርታ ክርክር ላይ ተፈፃሚ ማድረጉ ፍፁም የህግ አተገባበርና አተረጓጎም ስህተት መሆኑን እንገነዘባለን። ይህ ዶክትሪናዊ ዝላይ (Doctrinal Leap) የተፈጠረው ችሎቱ የተከራካሪዎችን መደበኛ የአስተዳደር ካርታዎች በአዋጁ ከሚመራው ጥብቅ የካዳስተር ምዝገባ ጋር በማምታታቱ ሁኖ ይታያል። በአዋጁ እና በደንቡ መሰረት ህጋዊ የምዝገባ ሰርተፊኬት (Legal Cadastre Certificate) ለመስጠት እጅግ ጥብቅ የሆኑ ቅድመ-ሁኔታዎች አሉ። ምዝገባ ከመካሄዱ በፊት በህዝብ ተሳትፎ፣ በይፋ ማስታወቂያ፣ የድንበር ልኬት እና በቅሬታ ሰሚ ጉባኤ ማጣሪያ የሚታጀብ የይዞታ ማረጋገጥ (Adjudication) ሂደት መካሄድ አለበት። በመቀጠልም ለእያንዳንዱ መሬት ድጋሚ ሊሰጥ የማይችል የቦታው ልዩ መለያ ቁጥር (Unique Parcel Identification Code) ይሰጠዋል። ይህ ሁሉ ሲጠናቀቅ ብቻ መዝጋቢው ተቋም ህጋዊ የካዳስተር ሰርተፊኬት ይሰጣል። የቀደመውን የህግ ትርጉም በለወጠው መዝገብ ላይ ያሉት ተከራካሪዎቹ የያዙት ሰነድ ይህንን ሂደት ያለፈ ቢሆን ኖሮ፣ የይፋ ማስታወቂያ በሚወጣበት ጊዜ ቅሬታ ቀርቦ ተደራቢ ካርታ መፈጠር በተግባር የማይቻል ይሆን ነበር። እንዲሁም በማህበሩ እና በግለሰቦቹ መካከል የታየው የሳይት ቁጥር አሰጣጥ የድሮው መደበኛ ያልሆነ የአስተዳደር አከፋፈል እንጂ፣ በአዋጁ የተደነገገው ዘመናዊ የቦታው ልዩ መለያ ቁጥር አይደለም። በጣም አሳሳቢው የህግ ስህተት የሚመነጨው የህጉን የመሸጋገሪያ ድንጋጌዎች (Transitory Provisions) ፊት ለፊት ከመጣስ ነው። የአዋጁ አንቀጽ 55 እና የደንቡ አንቀጽ 74 በግልፅ እንደሚደነግጉት፣ አግባብነት ያላቸው መዝጋቢ ተቋማት ተቋቁመው የምዝገባ ስራን በተሟላ ሁኔታ ማካሄድ እስከሚጀምሩ ድረስ ነባሩ የምዝገባ ስርአት እና የአስተዳደር አሰራር ቀጥሎ ተግባራዊ ይሆናል። አመልካቾቹ መሬቱን የተቀበሉትና ካርታ ያወጡት በነባሩ የክፍለ ከተማ እና ቀበሌ መሬት አስተዳደር ጽ/ቤት ሲሆን፣ ይህ ሂደት በአዋጅ 818/2006 በተዘረጋው የካዳስተር ማረጋገጥና ምዝገባ ሂደት የተከናወነ አይደለም። ህጉ ራሱ የካዳስተር ስርአቱ እስኪዘረጋ በነባሩ ህግ መዳኘት ይቀጥላል እያለ፣ የነባር መሬት አስተዳደር ስህተትን ለማረም የአዲሱን የካዳስተር አዋጅ አንቀጽ 43 መተግበሩ ህጉን ካለመረዳት የመጣ የዳኝነት ስልጣን ግድፈት ነው የሚል ድምዳሜ ሊያስይዝ የሚችል ነው። 4. ክፍል ሶስት፡ ትንታኔ በስነ-ማህበረሰብ (Sociology) መነፅር ህግ ከማህበራዊ እውነታ ተነጥሎ በባዶ ውስጥ (in a vacuum) አይሰራም። በወረቀት ላይ ያለ ህግ እና በተግባር ላይ ያለ ህግ ልዩነት አላቸው። በሰ/መ/ቁ 246230 የተሰጠው ውሳኔ ለጉዳዩ አግባብነተ የሌለውን የካዳስተር ህግን ፊደል የተከተለ ቢመስልም፣ ከህግ እና ስነ-ማህበረሰብ (Sociology of Law) አንፃር ሲገመገም ግን ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ማህበራዊ እና ተቋማዊ እውነታዎች ጋር የተላተመ ነው። የተደራቢ ካርታ ክስተት የተናጠል ቢሮክራሲያዊ ስህተት ሳይሆን የኢትዮጵያ የከተማ መሬት አስተዳደር መዋቅራዊ መገለጫ ነው። ፈጣን የከተማ መስፋፋት፣ እርስበርስ የሚደራረቡ የአስተዳደር እርከኖች፣ እና የኪራይ ሰብሳቢነት ባህሪ ይህንን መዋቅራዊ ጥቃት (Structural Violence) ያመነጫሉ። የመንግስት መዋቅር በስርአት ደረጃ የሚጋጩ የንብረት መብቶችን ሲያመነጭ የሚፈጠረው ጉዳት በተለይም ተጋላጭ በሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ ከባድ ተፅዕኖ ያሳድራል። ከግንባታ-ቅድሚያ ወደ ምዝገባ-ቅድሚያ የተደረገው ሽግግር ከሀብት ክፍፍል አንፃር ገለልተኛ አይደለም። አዲሱ ህግ ብልጫ የሚሰጠው የቢሮክራሲ ስርአቱን ቀድሞ ለተወጣው አካል በመሆኑ፣ ከተቋማት ጋር ትስስር ያላቸውን እንደ ቤት ስራ ማህበራት ያሉ አካላትን ይጠቅማል። በሌላ በኩል፣ ካርታቸውን ከበታች አስተዳደር ያገኙትን እንደዚህ

አራሚው ሲሳሳት:- ተፈጻሚ ሕግን በትክክል ሳይለይ አስገዳጅ የህግ ትርጉም መለወጥ ተደራቢ ካርታ እና የፍትህ ሚዛን፡- የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ (ሰ/መ/ቁ 246230) ዶክትሪናዊ እና ስነ-ማህበረሰባዊ ትንታኔ በአቶ አልማው ወሌ ሚያዚያ 02 ቀን 2018 ዓ/ም 1. መግቢያ በቅድሚያ አዋጅ ቁጥር 818/2006 ከ11/11/2017 ዓ/ም ጀምሮ ስራ ላይ በዋለው የከተማ መሬት ይዞታ እና መሬት ነክ ንብረት ለመመዝገብ በወጣ አዋጅ ቁጥር ፩ሺ፫፻፹፩/፪ሺ፲፯(1381/2017) መተካቱን ያስተውሉ፡፡ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት 3ኛ( ባለሰባት ዳኞች ሰበር ችሎት 1ኛ፣ 2ኛ እና 3ኛ ተብሎ መደራጀቱን የሚያሳይ ተቋሚ ሰነድ መኖሩ የማይታወቅ ቢሆንም በተጠቃሹ መዝገብ ላይ ግን 3ኛ የሚል በመኖሩ የተወሰደ አገላለፅ መሆኑ ልብ ይሏል፣ ምናልባት ችሎቶቹ የተደራጁት በጉዳይ አይነት በመሆኑ ጉዳዩ ባለበት ችሎት ሰባት ዳኞች ሲሰየሙ ጥቅም ላይ የሚል ነው ሊገመት ይችላል) የሰበር ሰሚ ችሎት በሰባት ዳኞች ተሰይሞ በመዝገብ ቁጥር 246230 (መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም) የሰጠው ውሳኔ በኢትዮጵያ የከተማ መሬት ይዞታ ስነ-ህግ (Jurisprudence) ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት ነው። በመሰረቱ ውሳኔው ቀላል የሚመስል ነገር ግን እጅግ ጥልቅ መዘዝ ያለውን ጥያቄ ይመልሳል። ይኸውም የመንግስት አካላት ለአንድ የከተማ መሬት ተደራቢ ካርታ ሲሰጡ፣ የቅድሚያ መብት የሚኖረው የትኛው ባለመብት ነው፤ መሬቱ ላይ ቀድሞ ግንባታ ያካሄደው ወይስ ቀድሞ ያስመዘገበው? ለሚለው ጥያቄ፣ ቀደም ሲል በሰ/መ/ቁ 186946 ተሰጥቶ የነበረውን አስገዳጅ የህግ ትርጉም በመለወጥ፣ የቅድሚያ መብት የሚኖረው ቀድሞ ለተመዘገበው እንጂ ቀድሞ ለገነባው አካል አይደለም የሚል ቁርጥ ያለ ምላሽ ሰጥቷል። ይህ አካዳሚያዊ እና ሙያዊ የህግ ትንታኔ፣ የውሳኔውን ዶክትሪናዊ ጥንካሬ፣ ችሎቱ የከተማ መሬት ይዞታ ምዝገባ አዋጅን (አዋጅ ቁጥር 818/2006) እና ደንብን በተሳሳተ አውድ የተገበረበትን መሰረታዊ የህግ ግድፈት፣ እንዲሁም ውሳኔው በስነ-ማህበረሰብ (Sociology of Law) መነፅር ሲታይ የሚያስከትለውን መዋቅራዊ እና ማህበራዊ መዘዝ በጥልቀት ይመረምራል። 2. ክፍል አንድ፡ የህግ እና የዶክትሪን ትንታኔ የውሳኔው የህግ ማዕቀፍ በዋናነት የሚያጠነጥነው በከተማ መሬት ይዞታ ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 43 ላይ ነው። የዚህ ድንጋጌ ንዑስ አንቀጽ አንድ በማያሻማ ሁኔታ እንደሚያስቀምጠው፣ በአንድ ባለይዞታ ሊመዘገብ የሚገባን መብት ሁለት ሰዎች አግኝተው እንደሆነ፣ በመጀመሪያ መብቱን ያስመዘገበ ሰው ቅድሚያ ይሰጠዋል። የችሎቱ የህግ ትርጉም አሰጣጥ ዘዴ እጅግ ህገ ሰብዕ(ፖዚቲቪስት) (Positivist) በመሆን ግልፅ ለሆኑ ህጋዊ ድንጋጌዎች ትርጉም አያስፈልግም የሚለውን የሲቪል ህግ ስርአቶች ክላሲካል መርህ የተከተለ ነው። የውሳኔውን መሰረት በአንቀጽ 43 ላይ በማድረግ፣ ችሎቱ በዳኝነት ከተፈጠሩ የፍትሃዊነት መርሆች ይልቅ የህግ አውጪውን ፅሁፍ ቀጥተኛ ትርጉም ያስቀደመ ምንባባዊ ትርጉም (Textualist) አካሄድን መርጧል። ይህ አቀራረብ ዳኞች ከህግ በስተቀር በሌላ ሁኔታ እንደማይመሩ በሚደነግገው የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ-መንግስት አንቀጽ 79(3) ድጋፍ ያገኘ ሲሆን፣ ዓላማውም በችሎቱ እይታ ከህግ ድንጋጌ ጋር የሚቃረን የዳኝነት መርህ ፈጥሮ የነበረውን የሰ/መ/ቁ 186946 አቋም ውድቅ ማድረግ ነው። ይህ ውሳኔ ሰበር ሰሚ ችሎት ራሱ የሰጣቸውን አስገዳጅ ውሳኔዎች በሰባት ዳኞች አማካኝነት ለመለወጥ ያለውን ስልጣን የተገበረበት በመሆኑ ዶክትሪናዊ ፋይዳው የጎላ ነው። በቀድሞው መዝገብ (ሰ/መ/ቁ 186946) ችሎቱ፣ አንድ ሰው ከመንግስት አካል ካርታ ተቀብሎ መሬቱ ላይ ግንባታ ካካሄደ፣ ካርታው ከመጀመሪያው ባለመብት መሬት ላይ ተቆርጦ በህገወጥ መንገድ የተሰጠ ቢሆንም እንኳ፣ የመጀመሪያው ባለካርታ ቤቱ እንዲፈርስና ይዞታውን እንዲረከብ መጠየቅ አይችልም የሚል መርህ አስቀምጦ ነበር። ያ አቋም የተመሰረተው መሬት ላይ የይዞታ መብትን ብቻ በሚያውቀው የህገ-መንግስቱ አንቀጽ 40(3)፣ በፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 1178 እና 1179 አተረጓጎም፣ እና በቀድሞ አስገዳጅ ውሳኔዎች ላይ ነበር። የአሁኑ ችሎት ይህንን ትርጉም የለወጠው በመገንባት ብቻ በመሬት ላይ መብት እንደማይገኝ በሰ/መ/ቁ 242314 የተሰጠውን ውሳኔ ዋቢ በማድረግ እና በአዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 43 ድንጋጌን ተከራካሪዎች ባላነሱበት፣ የበታች ፍርድ ቤቶች ባልተረጎሙበትና ባልተገበሩበት ሁኔታ ውሳኔ ሰጪ ህግ አድርጎ በማቅረብ ነው። በበታች ፍርድ ቤቶች ጉዳዩ የታየበት የህግ አውድ በአዲሱ የፌዴራል ፍ/ቤቶች አዋጅ ቁጥር 1234/2013 አንቀፅ 2(4) እና 10 ድንጋጌዎች አግባብ ከመጀመሪያውኑ ከአጣሪ ችሎቱ አልፎ በአምስት ዳኛ እንዲታይ የተደረገበት አግባብም የራሱ የሆነ የህግ ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፡፡ የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ሕግን በመተርጎም ስህተት ወይም ለጉዳዩ አግባብነት የሌለውን ሕግ በመተግበር በክልል ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ውሳኔ ሲሰጥ ፌዴራል ሰበር ሰሚ ችሎቱ ጉዳዩን ለማስተናገድ ድርብ ማጣሪያ (double threshold) እንዲያሟላ ህጉ የግድ ይላል፡፡ በሌላ አገላለፅ ችሎቱ የክልል ጉዳዮችን የማየት ስልጣን የሚኖረው ከመሠረታዊ የሕግ ስህተት መኖር ባሻገር ጉዳዩ "ለሕዝብ ጥቅምና ለሀገራዊ ጠቀሜታ" ያለው መሆኑ ሲረጋገጥ ነው፡፡ ይህ ምንባብ ከመጀመሪያዎቹ ሁለት ምንባቦች ማለትም ሕገ መንግሥት ጥሰት (አንቀጽ 2(4)(ሀ)) እና አስገዳጅ ውሳኔ መተላለፍ (አንቀጽ 2(4)(ሸ))፣ በግልጽ ይለያል፡፡ ምክንያቱም ያ ሁለቱ ተጨማሪ ማጣሪያ ሳይጠይቁ ቀጥተኛ ሥልጣን ሲሰጡ ሦስተኛው ግን ሕግ አውጭው ሆን ብሎ ያስቀመጠው ʽጠባብ የሥልጣን በርʽ ነው፡፡ ዓላማውም በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ሥርዓት ውስጥ የክልል ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ነጻነት (regional judicial autonomy) ተከብሮ እንዲቆይ ተራ የሕግ ትርጉም ስህተቶች በክልሉ ፍትሕ ሥርዓት ውስጥ ራሳቸው እንዲታረሙ ለማድረግ ነው ተብሎ ይታመናል። ሆኖም ግን "ለሕዝብ ጥቅምና ለሀገራዊ ጠቀሜታ" የሚለው ሐረግ በአዋጁ ውስጥ ትርጉም ያልተሰጠው (undefined) በመሆኑ ችሎቱ ራሱ የራሱን ሥልጣን ወሰን ራሱ የሚወስንበት፤ ሊያሰፋውም ሊያጠበውም የሚችልበት፣ ያልተገደበ ውሳኔ አሰጣጥ ሥልጣን ሀረጉ በህጉ ውስጥ በመስፈሩ ተፈጥሯል። በሰ/መ/ቁ. 246230 ጉዳይ ላይ ይህ ምንባብ ቀጥተኛ ጠቀሜታ ይኖረው ነበር፡፡ ምክንያቱም አመልካቾች የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የፍ/ብ/ሕ/ቁ. 1178–1179 ድንጋጌዎችን እና የአዋጅ ቁጥር 818/2006 አንቀጽ 43ን "በመተርጎም ስህተት" ሰርቷል ብለው ቢከራከሩ ይህ ክርክር ከአንቀጽ 2(4)(ለ) ሥር ስለሚወድቅ ከአጣሪ ችሎቱ ጀምሮ የሰበር ችሎቱ ሥልጣኑን ለማስተናገድ ጉዳዩ "ለሕዝብ ጥቅምና ለሀገራዊ ጠቀሜታ" ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርባቸው ነበር፡፡ ሆኖም ከአጣሪ ችሎቱ ጀምሮ እስከ ባለሰባቱ ዳኞች የሰበር ችሎቱ ይህን ማጣሪያ ተግባራዊ ያደረጉበትን ሁኔታ በውሳኔው ውስጥ በግልጽ ባለመመልከቱ ወደፊት ተመሳሳይ የክልል ጉዳዮች ላይ ይህ ምንባብ እንዴት ተፈጻሚ እንደሚሆን ግልጽነት ይጎድላል። ይህ እንዲህ እንደተጠበቅ በሌላ ሰው መሬት ላይ የሚገነባን ሰው መብት የሚገዙትን የፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 1178 እና 1179 ድንጋጌዎችን

የተግባር ውጤቱ (The Practical Paradox)፡- በንድፈ-ሀሳብ ደረጃ "መብት አለማግኘት" እና "ክስ የማቅረብ መብትን ማጣት" የተለያዩ ቢሆኑም፤ በተግባር ግን አንድ ባለይዞታ ለ10 ዓመት ዝም ካለ፣ ህገ-ወጥ ገንቢው የይርጋ መቃወሚያ በማንሳት መሬቱን ለዘለዓለም ጠቅልሎ ይወስደዋል ማለት ነው። ሰበር ችሎቱ በሰ.መ.ቁ 242314 ላይ "መሬት በዝምታ አይተላለፍም" ብሎ በፊት በር የዘጋውን ታላቅ ሕገ-መንግሥታዊ መርህ፣ በሰ.መ.ቁ 244308 የይርጋ ውሳኔ ምክንያት በጓሮ በር መልሶ ከፍቶታል። ይህ ማለት በመሰረታዊ ሕግ (Substantive Law) የተከለከለው የመሬት ንጥቂያ፣ በሥነ-ሥርዓት (Procedural Law) ሕያው ሆኗል ማለት ነው። ክፍል ሦስት፡ ማጠቃለያ እና የመፍትሔ ሃሳቦች በዳኝነት ትርጓሜ የተፈጠረው ይህ የፅንሰ-ሀሳብ እና የተግባር መዛባት ዘላቂ እልባት እንዲያገኝ ሦስት ተቋማት ድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡-  የሕግ አውጪው (ፓርላማው)፡- የከተማ መሬት አስተዳደር አዋጅን ሲያወጣ፣ የከተማ መሬት ይርጋ ጊዜውን ልክ እንደ ገጠር መሬቱ (ከፍ/ብ/ህ/ቁ 1168 ጋር በማናበብ) 15 ዓመት እንዲሆን በግልጽ በሕግ ሊደነግግ ይገባል።  የፌዴሬሽን ምክር ቤት፡- በከተማ እና በገጠር መሬት ላይ የሚተገበሩ የተለያየ እርዝማኔ ያላቸው የይርጋ ሕጎች፣ አንድ አይነት ሕገ-መንግስታዊ መሰረት ካላቸው የእኩል ጥበቃ መብት አንፃር ምክንያታዊ ልዩነት (Rational distinction) ያላቸው መሆን አለመሆናቸውን በሕገ-መንግሥት ትርጓሜ ሊያጠራው ይገባል።  የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፡- ሰበር ችሎቱ ወደፊት በሚያገኛቸው ጉዳዮች የሰ.መ.ቁ 244308ን ውሳኔ ዳግም በ9 ዳኞች በመገምገም የሕግ ትርጉሙን ከ15 ዓመቱ የንብረት ይርጋ ጋር ሊያጣጥመው ይገባል። የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አምስትም ሆነ ሰባት ዳኞች የሚሰየሙባቸው የሰበር ችሎቶች የሚሰጧቸው አስገዳጅ የህግ ትርጉሞች በሀገሪቱ የፍትህ ሥርዓትና በዜጎች መሠረታዊ መብቶች ላይ ያላቸውን ሰፊ እና ዘላቂ አንድምታ (Consequence) ከግምት ውስጥ በማስገባት ከፍተኛ ተቋማዊ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል፤ በተለይም የችሎቶቹ ውሳኔዎች እርስ በእርስ እንዳይቃረኑ እና ሥርዓታዊ ወጥነት (Consistency) እንዲሁም ተገማችነት እንዲኖራቸው ለማድረግ፣ አዳዲስ ትርጉሞችን ሲሰጡም ሆነ ቀደምት ውሳኔዎችን ሲሽሩ የተናጠል የህግ አንቀፆችን ከመተርጎም ባለፈ አጠቃላይ የህገ-መንግስቱን መርሆችና የህግ ፍልስፍናውን (Doctrinal coherence) ያማከለ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ይህንንም በተግባር ለማሳካት ችሎቶቹ ውሳኔ ከማሳረፋቸው በፊት ጠንካራ የቅድመ-ውሳኔ የህግ ምርምር (Precedent analysis) በማድረግ እና ትርጉሙ ሊያመጣ የሚችለውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ በጥልቀት በመመርመር አርቆ አሳቢነት የተሞላበት የዳኝነት ጥበብን እንዲከተሉ በፅኑ ይመከራል። ተፃፈ፡- በአቶ አልማው ወሌ ሚያዚያ 6 ቀን 2018 ዓ/ም አዲስ አበባ

በፊት በር የዘጋውን በጓሮ በር ከፈተው፡- የሰ.መ.ቁ 242314 እና 244308 የይርጋ ተቃርኖ፣ የመሬት ይዞታ መብት በመሠረታዊው ሕግ ሲሞት፣ በሥነ-ሥርዓት ሕግ እንዴት ሕያው ሆነ? ማሳሰቢያ፡- እነዚህን ሁለት ውስብስብ እና መሠረታዊ የሰበር ውሳኔዎች በማነፃፀር የተሟላ የውሳኔ ዳሰሳ (Case Comment) ማዘጋጀት ጥልቅ የሆነ ሳይንሳዊ የምርምር ሥነ-ዘዴን (Scientific methodology) የሚጠይቅ እጅግ ሰፊ የሕግ ርዕሰ-ጉዳይ ነው። ይሁን እንጂ፣ የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ የሕግ ዕውቀትንና ልምድን ለሁሉም ዜጋ ተደራሽ ማድረግ በመሆኑ፤ ትንታኔው ለማኅበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም እንዲስማማ፣ እንዲሁም የሕግ ሙያዊ ዳራ ለሌለው ማኅበረሰብ በቀላሉ እንዲረዳ ተደርጎ አቀራረቡ የተቀነበበ መሆኑን አንባቢያን እንዲገነዘቡልኝ እወዳለሁ። መግቢያ በቅርቡ በማኅበራዊ ሚዲያ (TikTok) አንድ የሕግ ባለሙያ ያቀረቡት ሞጋች ጥያቄ ይህን አጭር ምልከታ/ትንታኔ/ ለማዘጋጀት መነሻ ምክንያት ሆኖኛል። ጥያቄው በይዘቱ ሲጠቃለል "በሌላ ሰው ይዞታ ላይ ባለይዞታው ሳይቃወም ቤት/ህንፃ የገነባ ሰው፤ በሰ.መ.ቁ 242314 በይዞታው ላይ መብት ሊያገኝ አይችልም ቢባልም፣ በሰ.መ.ቁ 244308 በተሰጠው ትርጉም የ10 ዓመት ይርጋ መቃወሚያ ተጠቅሞ ከመሬቱ ላይ ሳይነሳ ሊቀር ይችላልን?" የሚል ነው። ይህ ጥያቄ የፌ/ፍ/ ቤት ሰባት ዳኞች በተሰየሙበት የሰበር ችሎት የተሰጡ ሁለት አስገዳጅ ውሳኔዎችን ጎን ለጎን ስናነፃፅራቸው የሚፈጠረውን ከፍተኛ የሕግ ፅንሰ-ሀሳብ (Doctrinal) እና የተግባር ተቃርኖ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። እንደ አንድ የሕግ ባለሙያ እነዚህ ውሳኔዎች የባለቤትነት እና የይዞታ መብትን ከመለየት፣ የንብረት ህግን ከህገ-መንግስቱ ጋር ከማጣጣም እንዲሁም የሕግ ተገማችነትን ከማሳደግ አኳያ የራሳቸው የሆኑ አያሌ ጥንካሬዎች እና ተቋማዊ ስምምነቶች እንዳሏቸው አምናለሁ። ይሁን እንጂ፣ የውሳኔዎቹን የጎሉ ጥንካሬዎች፣ የሚያጋሯቸውን ሕገ-መንግሥታዊ መሠረቶች እንዲሁም ሌሎች ጥቃቅን ክፍተቶች በተመለከተ ከዚህ ቀደም ባዘጋጀኋቸው እና በሌሎች የዳሰሳ ሰነዶች (Case Comments) ላይ በስፋት የተተነተኑ በመሆኑ፣ አንባቢያን እነዚያኑ ጽሑፎች መመልከት እንደሚችሉ እያሳሰብኩ፤ ይህ ትንታኔ በቀጥታ የሚያተኩረው ውሳኔዎቹ እርስ በእርስ በሚፈጥሩት መሠረታዊ የሕግ ተቃርኖ እና ተግባራዊ መዛባት (Central Theme) ላይ ብቻ ይሆናል። ክፍል አንድ፡ መሠረታዊ ተቃርኖዎች፡ የአመሳስሎሽ ትርጓሜው ችግር እና የከተማ-ገጠር መዛባት 1.1. ተቃርኖ ፩፡- የመብቱ ባህሪ እና የአመሳስሎሽ ድልድዩ መጋጨት ይህ የመጀመሪያው እና ዋናው የሕግ ፅንሰ-ሀሳብ ተቃርኖ ነው። በሰ.መ.ቁ 242314 ላይ ሰበር ችሎቱ የመሬት ይዞታ መብት "በነገር ላይ ያለ መብት" (Right in rem) መሆኑን እና ይህ መብት ከግለሰቦች የውል ግንኙነት (ፈቃድ ወይም ዝምታ) በዘለለ ሊፈጠር እንደማይችል በሚገባ ተንትኗል። ይሁን እንጂ ይኸው ችሎት በሰ.መ.ቁ 244308 ላይ የከተማ መሬትን ለማስመለስ የሚቀርብ ክስ የይርጋ ጊዜ ስንት ነው? ለሚለው ጥያቄ የሕግ ክፍተቱን ለመሙላት የተጠቀመው የአመሳስሎሽ (Analogy) ድልድይ፣ አራተኛው መጽሐፍ ላይ ያለውን የውል ወይም የግዴታ ሕግ (የፍ/ብ/ህ/ቁ 1845 የ10 ዓመት ይርጋን) ነው። የመሬት ይዞታ መብት በነገር ላይ ያለ (In rem) ከሆነ፣ ክሱ ሊለካ ይገባው የነበረው ከንብረት ሕጉ ራሱ ማለትም ይዞታን ያለማቋረጥ በመገልገል ባለመብት መሆንን (Adverse Possession) ከሚደነግገው የፍ/ብ/ህ/ቁ 1168 የ15 ዓመት ይርጋ ጋር ነበር። በአንድ ውሳኔ ላይ "የመሬት ይዞታ በውል አይፈጠርም" ብሎ የውል ሕግን ያገለለ ችሎት፣ በሌላ ውሳኔ ላይ መብቱ የሚታገድበትን የጊዜ ማዕቀፍ ከዚያው ከተገለለው የውል ሕግ መውሰዱ የከፋ ውስጣዊ ወጥነት-አልባነትን (Internal inconsistency) ያመላክታል። 1.2. ተቃርኖ ፪፡- የከተማ እና የገጠር መሬት የይርጋ መዛባት ሌላኛው ከፍተኛ ተቃርኖ የሚፈጠረው የሰበር ውሳኔ 244308’ን’ ከአዲሱ የገጠር መሬት አዋጅ (አዋጅ ቁጥር 1324/2016) ጋር ስናነፃፅር ነው። የሕግ አውጪው አካል ለገጠር መሬት ማስለቀቂያ ክስ የይርጋ ጊዜው 15 ዓመት መሆኑን ሲደነግግ፣ ሰበር ችሎቱ ለከተማ መሬት ያስቀመጠው አስገዳጅ የይርጋ ጊዜ ግን 10 ዓመት ብቻ ነው። በኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 40(3) መሠረት የከተማም ሆነ የገጠር መሬት የመብት ምንጭ አንድ ዓይነት ሆኖ ሳለ፤ የከተማ መሬት በ10 ዓመት፣ የገጠር መሬት ደግሞ በ15 ዓመት መታገዱ ሕገ-መንግሥታዊ የእኩልነት ጥያቄን ያስነሳል። ይህ አተገባበር በይርጋ ሕግ ፍልስፍና ደረጃም መሠረታዊ ጥያቄን ያስነሣል፡፡ የከተማ መሬት አስተዳደር በዘመናዊ ካዳስተር እና ጠንካራ የሰነድ ሥርዓት የተደገፈ በመሆኑ፣ ባለይዞታው መብቱን በቀላሉ ለማስረዳት የሚያስችል አስተማማኝ ማስረጃ በእጁ ይገኛል፤ ይሁን እንጂ በዚህ ሥርዓት ውስጥ ለሚነሳ ክርክር የተሰጠው የመብት ማስከበሪያ የይርጋ ጊዜ አጭር (የ10 ዓመት ጊዜ) ሆኖ እናገኘዋለን። በተቃራኒው፣ በበርካታ አስተዳደራዊ ክፍተቶች የተነሳ ደካማ ሥርዓት ባለውና በአብዛኛው በአረንጓዴ ደብተር ብቻ በሚረጋገጠው የገጠር መሬት ይዞታ ላይ፤ አርሶ አደሩ መብቱን ለማስረዳት ፈታኝ ሁኔታዎች ቢኖሩበትም፣ የተሰጠው የይርጋ ጥበቃ ግን ረዘም ያለ (የ15 ዓመት ጊዜ) ሆኖ ተደንግጓል። የይርጋ ሕግ ከሚቆምላቸው አይነተኛ ዓላማዎች አንዱ "በጊዜ ብዛት ማስረጃ እንዳይጠፋ መከላከል" መሆኑ በህግ ስነ-ምክንያት (Jurisprudence) በሚገባ ይታወቃል። ይህን መሠረታዊ አመክንዮ መነሻ በማድረግ አሁን ያለውን የህግና የትርጉም አተገባበር ስንመረምረው፤ ጠንካራ ሰነድ-ተኮር ሥርዓት ላለው የከተማ ይዞታ ያነሰ ጊዜ፣ እንዲሁም በአብዛኛው ሰነድ-አልባ ለሆነው የገጠር ይዞታ ደግሞ የበለጠ ጊዜ እንዲሰጥ መደረጉ ግልጽ የሆነ መዛባትን ይፈጥራል። በመሆኑም ይህ ሁኔታ፣ አሳማኝና ምክንያታዊ የፖሊሲ መሠረት (Rational policy basis) የሌለው ከመሆኑም ባሻገር፣ የሕግን ፅንሰ-ሀሳባዊ ወጥነት (Doctrinal consistency) በቀጥታ የሚያናጋ ሆኖ ይታያል። ክፍል ሁለት፡ የ’TikTok’ ጥያቄው እና የተግባር ተቃርኖው (በፊት በር የዘጋውን በጓሮ በር መክፈት) የቀረበውን ተግባራዊ ጥያቄ ለመመለስ የሰ.መ.ቁ 242314 መሠረታዊ መብትን (Substantive Right)፣ የሰ.መ.ቁ 244308 ደግሞ የመብት ማስከበሪያ ሥነ-ሥርዓትን/ይርጋን (Procedural/Remedial Right) የሚገዙ መሆናቸውን መለየት ግድ ይላል። ገንቢው የይርጋ መቃወሚያ ሊያነሳ ይችላልን? አዎ፣ ይችላል! ያለተቃውሞ የገነባው ሰው የሕጋዊውን ባለይዞታ ክስ ለማምከን የ10 ዓመቱን ይርጋ እንደ መከላከያ (Shield) ለማንሳት ሕጋዊ መሠረት አለው። ፍርድ ቤቱም መብቱን ለ10 ዓመታት በቸልተኝነት ያሳለፈውን ከሳሽ አቤቱታ በይርጋ ውድቅ ያደርገዋል። በውጤቱም፣ በመሬቱ ላይ ግንባታ ያካሄደው አካል የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ባይኖረውም ከይዞታው እንዲነሳ በሕግ አይገደድም።

 የአዋጅ ቁጥር 1156/2011 መግቢያ፦ የሕጉ መግቢያ "አስተማማኝ የኢንዱስትሪ ሰላም፣ ዘላቂ ምርታማነት እና የገበያ ተወዳዳሪነት አቅም" መፍጠርን ያወሳል። ለ28 ተከታታይ ቀናት ከሥራ ለቀረ ሠራተኛ አሠሪው የማረሚያ ማስጠንቀቂያ እንዲሰጥ ማስገደድ እነዚህን ሕጋዊ ግቦች በቀጥታ የሚያደናቅፍ ነው የሚል ምክን ያትም ችሎቱ አስፍሯል፡፡ የመጨረሻው ችሎቱ በአብላጫ ድምጽ ውሳኔውን የሰጠ ሲሆን መሰረታዊ ይዘቱም፡- 1. ቀድሞ የነበረው አስገዳጅ ውሳኔ:- የሰ/መ/ቁ 249795፣ በዚህ ውሳኔ የተለወጠ ሲሆን፣ የነበረው አስገዳጅነት እና በሌሎች መዝገቦች የተያዙ ተመሳሳይ አቋሞች ቀሪ ሆነዋል። 2. የአዋጅ ቁጥር 1156/2011 አንቀጽ 27(1)(ለ) አሁን ላይ በይፋ የተተረጎመው እንደሚከተለው ነው፡- • "አንድ ሠራተኛ በአዋጁ ከተመለከቱት ዕረፍቶችና ልዩ ልዩ ፈቃዶች ውጭ ለአምስት ተከታታይ የሥራ ቀናትና ከዚያ በላይ ለሆነ ጊዜ ከሥራ ላይ ከቀረ፣ አሠሪው የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ መስጠት ሳያስፈልገው የሥራ ውልን ያለ ማስጠንቀቂያ ለማቋረጥ ይችላል።" • ይህ የተወሰነው ጉዳይ የመጨረሻ እልባት (በፍሬ ነገሩ ላይ ውሳኔ) እንዲያገኝ ለመደበኛው ሰበር ሰሚ ችሎት ተመልሷል። የሚል ነው፡፡ 💡 ይህ ውሳኔ ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ ለምን ቢባል፡-  በሦስት አስገዳጅ ውሳኔዎች መካከል የነበረውን አደገኛ ግጭት ፈትቷል። በዚህም፦  በመላው ኢትዮጵያ ላሉ አሠሪዎች እና ሠራተኞች የሕግ እርግጠኝነትን/ተገማችነትን መልሷል።  ለሕግ ትርጓሜ የፓርላማ የውይይት ሰነዶችን (የሕግ አወጣጥ ታሪክን) መጠቀምን እንደ ትርጉም ስልት አድርጎ አስቀምጧል፤ይህ ቀላል የማይባል የአተረጓጎም ስልት እርምጃ ነው።  የሥራ ቦታ ዲሲፕሊን የኢንዱስትሪ ሰላም የማዕዘን ድንጋይ መሆኑን አጠናክሯል።  በኢትዮጵያ የዳኝነት ሥርዓት ውስጥ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰባት ዳኞች የራስን ስህተት የማረም አሠራር (Self-correction mechanism) ምን ያህል ኃይል ያለው እና በተግባር የሚሠራ መሆኑን አሳይቷል። ሆኖም በፍርድ አሁንም ያልተመለሱ አስፈላጊ ጥያቄዎች መኖራቸው ግን ይታያሉ፤ አንዳንድ ወሳኝ ክፍተቶችን ትቷል፡፡ ከእነዚህም መካከል፦  ከአቅም በላይ የሆነ ምክንያት (Force Majeure)፡- ሠራተኛዋ በእውነተኛ የፀጥታ አደጋ (በመንገድ መዘጋት) መታገቷን ተከራክራለች። ችሎቱ እውነተኛ የሆነ ከአቅም በላይ የሆነ ምክንያት ለረዥም ጊዜ ቀሪነትን ሕጋዊ ያደርገዋል ወይስ አያደርግም? በሚለው ላይ የመጨረሻ ብይን አልሰጠም። ስር ፍርድ ቤቶች በዚህ ጉዳይ ላይ መቸገራቸው አይቀርም።  የ "በቂ ምክንያት" መመዘኛ፡- አንድ ሠራተኛ ከሥራ የቀረበት ምክንያት በቂ መሆኑን ለማሳየት ምን አይነት ማስረጃ ማቅረብ አለበት? የሚለውና ቀላል የሚመስለው የህግ ጥያቄም በፍርዱ ግልጽ አይደለም። ዋና ማሳሰቢያ፡- o ለሠራተኞች፡- ያለፈቃድ ለ5 እና ከዚያ በላይ ተከታታይ ቀናት ከሥራ ከቀራችሁ፣ በኢትዮጵያ ሕግ መሠረት አሠሪው የሥራ ውላችሁን ወዲያውኑ እና ያለምንም ማስጠንቀቂያ ሊያቋርጠው ይችላል። መብታችሁንም ሆነ ግዴታችሁን ጠንቅቃችሁ እወቁ። o አሠሪዎች ደግሞ አሁን ላይ ለረዥም ጊዜ ያለፈቃድ ከሥራ በሚቀሩ ሠራተኞች ላይ እርምጃ ለመውሰድ የበለጠ ግልጽ የሆነ ሥልጣን አላችሁ። ነገር ግን ሁሉንም ነገሮች (የቀረባቸውን ቀናት እና ማስረጃዎች) በጥንቃቄ በሰነድ ማስደግፉ የግድ መሆኑ ማስተዋል እንደሚገባችሁ ችሎቱ አውጇል። o የ"በቂ ምክንያት" እና "ከአቅም በላይ የሆነ ሁኔታ" ጥያቄዎች በየግል ጉዳዮች ላይ አሁንም ክርክር ሊነሳባቸው ይችላል። o ለእኛ የሕግ ባለሙያዎች እና ለክቡራን ዳኞች ደግሞ አንድ ፍርድ ቤት የሕግ ትርጓሜን ከበርካታ ምንጮች እንዴት መተንተን እንደሚቻል ጠቃሚ አብነት ሰበር ችሎቱ አሳይቷል። የሕግ አወጣጥ ታሪክ (Legislative history) ከዚህ በኋላ በትርጓሜ መሣሪያዎቻችሁ ውስጥ በጽኑ ሊካተት ይገባል። ይህ ጽሑፍ ሕጋዊ ምክር (Legal advice) አይደለም። ለግልዎ/ለተቋምዎ ጉዳይ ብቃት ያለውን የኢትዮጵያ የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ ጠበቃ/ባለሙያ ያማክሩ።

⚖️ በአሠሪና ሠራተኛ ህግ አዋጅ ቁጥር 1156/2011 አንቀፅ 27(1(ለ)) ትርጉምና አተገባበር ላይ ሰባት ዳኞች በተሰየሙበት ሰበር ሰሚ ችሎት የተሰጠ አዲስ አስገዳጅ ትርጉም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አሠሪ እና ሠራተኛ ሊያውቀው የሚገባ! የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰባት ዳኞች ሰበር ሰሚ ችሎት በቅርብ ጊዜ ወዲህ ተቃርኖ ያላቸውን አስገዳጅ የህግ ትርጉሞችን በማረም ስራ ላይ የተጠመደ ይመስላል፡፡ በሰበር መዝገብ ቁጥር፡ 271726 ላይ መጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ/መ በዋለው ችሎት ደግሞ የኢትዮጵያ የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ላይ እጅግ ጉልህ ስፍራ ባለው ድንጋጌ ላይ ወሳኝ ትርጉም አሳልፏል፡፡ ይኸውም ሠራተኞች ያለፈቃድ ከሥራ ሲቀሩ የሚወሰደውን ሕጋዊ እርምጃ አቅጣጫ ሙሉ በሙሉ የሚቀይር ነው።  ሙሉ ታሪኩ እነሆ። 👇  ጉዳዩ በአጭሩ አመልካች ኤቶል ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ ኃ/የተ/የግ/ማኅበር እና ተጠሪ ወ/ሪት ቤተልሔም አያሌው ጤናው በሰበር መዝገብ ቁጥር፡ 271726 የተከራከሩበት ሁኖ ውሳኔ የተሰጠበት፡ መጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም.ነው፡፡  ምን ተፈጠረ? በተጠቃሹ መዝገብ ተጠሪ(ሠራተኛ) በአማራ ክልል ጎጃም ውስጥ የሚኖሩ ታማሚ እናቷን ለመጠየቅ የ7 ቀናት ፈቃድ ይሰጣታል። የፈቃድ ጊዜዋ ሲያልቅ ግን በነበረው የፀጥታ ችግር ምክንያት መንገዶች በመዘጋታቸው መመለስ አልቻለችም። ሁኔታውን ለድርጅቱ ኃላፊዎች እንድታሳውቅላት ለሥራ ባልደረባዋ ደወለች። የድርጅቱ የአስተዳደር ኃላፊም እንዲህ የሚል ምላሽ ሰጡ የተባለ መሆኑን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡ ተሰጠ የተባለው ምላሽም፦"መንገድ ከተዘጋ ምን ይደረጋል?" የሚል ይዘት ያለው መሆኑን ፍርዱ ይጠቁማል፡፡ በመጨረሻም የፈቃድ ጊዜዋ ካለቀ ከ28 ቀናት በኋላ ወደ ሥራ ተመለሰች። ነገር ግን አሠሪዋ፣ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 1156/2011 አንቀጽ 27(1)(ለ)ን በመጥቀስ ያለፈቃድ መቅረት ከጀመረችበት 5ኛው ቀን ላይ የሥራ ውሏን አቋርጦ ነበር። ሠራተኛዋ ክስ መሠረተች። የሕግ ትግሉም እስከ አገሪቱ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ድረስ ዘለቀ።  የሕግ ክርክሩ ጉዞው ሦስት ዙሮችን ያለፈ ሲሆን የመጀመሪያው ዙር የፌ/መ/ደ/ፍ/ቤት → አሠሪው አሸነፈ ፍርድ ቤቱ እንዳስተዋለው፡ ሠራተኛዋ ወደ ጎጃም የሄደችው በአውሮፕላን ነው። የፀጥታ ችግሩ እሷ ከመሄዷ በፊትም የነበረ ነው። ስለዚህ በተመሳሳይ መንገድ በአውሮፕላን መመለስ ትችል ነበር። የ28 ቀናት ቀሪነቷ = ያለ በቂ ምክንያት ነው። ስንብቱ = ሕጋዊ ነው። የሚል ዳኝነት የሰጠበት ነው፡፡ ቀጣዩና 2ኛው ዙር በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ደረጃ የተደረገ ሲሆን በዚህ የክርክር ደረጃ ሠራተኛዋ አሸነፈች፤ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የበታች ፍርድ ቤቱን የሕግ ትርጉሙን በመቀልበስ ዳኝነት የሰጠበት ነው፡፡ ይኸው ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ለውሳኔው መሰረት ያደረገው አቢይ ምክንያት” ምንም እንኳን ሠራተኛዋ ለ28 ቀናት ከሥራ ብትቀርም፣ አሠሪው ውሉን ከማቋረጡ በፊት በአንቀጽ 27(1)(ለ) መሠረት የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ የመስጠት ግዴታ ነበረበት። ምንም ማስጠንቀቂያ አልተሰጠም።” የሚል ሲሆን በድምዳሜው ስንብቱ = ሕገወጥ ነው በማለት በመፍትሔነትም የ6 ወር የካሳ ክፍያ ፣ የ3 ወር የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ እና የሥራ ስንብት ክፍያ እንድታገኝ ሲል ወሰኗል። 3ኛውና የመጨረሻው ዙር በባለአምስቱ ዳኞች የሰበር ሰሚ ችሎት የተካሄው ክርክር ሲሆን በዚህ የክርክር ደረጃ ችሎቱ የአስገዳጅ የህግ ትርጉም ውሳኔዎች ግጭት ያገኘበት ነው፡፡ ይኸው የሰበር ችሎቱ አቤቱታውን ሲመረምር ያገኘው አሳሳቢ ነገር እርስ በርስ በቀጥታ የሚጋጩ ሦስት አስገዳጅ የህግ ትርጉም ውሳኔዎች (ቅድመ-ውሳኔዎች) መኖራቸውን የሚመለከት ነው፡፡ እነዚህም፦  የሰ/መ/ቁ. 199956 እና 229194፦ በእነዚህ መዛግብት አሠሪው ለ5 እና ከዚያ በላይ ተከታታይ ቀናት ለቀረ ሠራተኛ ያለማስጠንቀቂያ የስራ ውል ማቋረጥ ይችላል ወይም ቅድመ ማስጠንቀቂያ አያስፈልግም የሚል አስገዳጅ የህግ ትርጉም የተሰጠባቸው ናቸው።  የሰ/መ/ቁ. 249795፡- በዚህ መዝገብ ደገሞ ለ5 እና ከዚያ በላይ ተከታታይ ቀናት ቢቀር እንኳ፣ አሠሪው ለእያንዳንዱ የቀረበት ቀን የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ ሳይሰጥ የሥራ ውል ማቋረጥ አይችልም በሚል አስገዳጅ የህግ ትርጉም ሰጥቶበት የነበረው መዝገብ ነው፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት አስገዳጅ የህግ ትርጉሞች ይዘት መረዳት የሚቻለው በአስገዳጅ የህግ ትርጉሞች መካከል ግጭት፣ መዘበራረቅ፣ የሕግ ትርጉም አለመረጋጋት የተሰተዋለ መሆኑን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ጉዳዩ በፌዴራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁጥር 1234/2013 አንቀጽ 26(2) መሠረት ለሰባት ዳኞች ችሎት ሊመራ እንደተቻለ ውሳኔው ያሳያል። የጉዳዩ ዋናው የሕግ ጥያቄ (ጭብጥ)፦ አንድ አሠሪ ከአምስት እና ከዚያ በላይ ለሆኑ ተከታታይ የሥራ ቀናት ያለፈቃድ ከሥራ የቀረን ሠራተኛ የሥራ ውል ከማቋረጡ በፊት የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ የመስጠት ሕጋዊ ግዴታ አለበት ወይ? የሚለው ሲሆን የሰባት ዳኞች ሰበር ሰሚ ችሎት የሚከተለውን አመክንዩዊ ትንተና በማስፈር ለጭብጡ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ችሎቱ በተቻለ መጠን ዘርፈ-ብዙ የሕግ ትንተና አቅርቧል። ማብራሪያውም ባጭሩ እንደሚከተለው የቀረበው ነው፡፡  የሕጉ ፊደላዊ ንባብ/textual Reading/:- የአዋጅ ቁጥር 1156/2011 አንቀጽ 27(1)(ለ) የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ መስፈርትን የሚያስተሳስረው በ6 ወር ጊዜ ውስጥ (ተበታትኖ) ለ5 ቀናት መቅረት ጋር ብቻ ነው:: ድንጋጌው አሰሪው የፅሁፍ ማስጠንቀቂያውን ከአምስት እና ከዚያ በላይ ለሆኑ ተከታታይ ቀናት ለቀረ ሰራተኛ እንዲሰጠው የአስገዳጅነት ይዘት የለውም፡፡ ሁለቱ የተለያዩ ሁኔታዎች ናቸው። የተለያዩ ሕጎችም ይተገበርባቸዋል።  የሎጂክ (አመክንዮ) መከራከሪያ፦ የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ የዲሲፕሊን ችግር/ጥፋት ማረሚያ መሣሪያ ነው፤ለሠራተኛው "ይህን ጥፋት እንዳትደግም" የሚል መልእክት ያስተላልፋል። ነገር ግን አንድ ሠራተኛ አሁንም ከሥራ ቀሪ ከሆነ እና ወደ ገበታው ካልተመለሰ፣ አሠሪው በቦታው የሌለን ሰው አግኝቶ ማስጠንቀቂያ ሊሰጠው አይችልም። ይህ በተግባርም ሆነ በሎጂክ የማይቻል ነው። ጥፋቱን አሁንም እየቀጠለ ላለ ሰው አሠሪው ማስጠንቀቂያ እንዲሰጥ ማስገደድ ምንም ዓይነት የሕግ (የዲሲፕሊን) ትርጉም አይሰጥም የሚል ማብራሪያ አስቀምጧል፡፡  መልካም ሊባል የሚል እርምጃ( የፓርላማ ሰነዶች (ቃለ-ጉባኤ) መጠቀም፦ ችሎቱ የሚደነቅና ብዙ ጊዜ የማይተገበር አካሄድ መከተሉን የሚያሳየው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውይይት ቃለ-ጉባኤዎች (የረቂቅ ሕጉ ሐተታ ዘምክንያት) እንዲቀርቡለት በማዘዝ የሕግ አወጣጥሰነዶቹም የሚከተለውን አረጋግጧል፡፡ ይኸውም፦"ማሻሻያው ለተከታታይ ቀሪዎች የማስጠንቀቂያ መስፈርት ለማምጣት የታሰበ አልነበረም። ይልቁንም አንዳንድ ሠራተኞች እስከ 4 ቀናት በመቅረት፣ በ5ኛው ቀን ተመልሰው 'ቆጠራውን በማቋረጥ'፣ እና እንደገና በመቅረት የሚጠቀሙበትን የሕግ ክፍተት ለመዝጋት የተነደፈ ነው።" የሚል መሆኑ ችሎቱ መረዳቱን በፍርዱ ላይ አስፍሮ ይገኛል፡፡ ከዚህም ተነስቶ የሰጠው ትርጉም፡ ሕጉ ይበልጥ ጥብቅ እንዲሆን እንጂ እንዲላላ አልተደረገም የሚል ነው።

የሚያስቀምጥ፣ ዳኞች እንደየግለሰቡ ልዩ የሥቃይ መጠን የሞራል ካሳውን ከፍ እንዲያደርጉ ሥልጣን (judicial discretion) የሚሰጥ፣ የእስር ቤት ወጪዎችን ከካሳ ላይ መቀነስን አጥብቆ የሚከለክል፣ እንዲሁም ከገንዘብ ክፍያ ባሻገር የሪከርድ ስረዛን፣ ሥነ-ልቦናዊ ሕክምናን እና የትምህርት ዕድልን ያቀፈ ሁለንተናዊ የጠጋኝ ፍትሕ (restorative justice) መፍትሔዎችን ማካተት ሊኖርበት እንደሚገባ የምሁራን የምርምር ስራዎች ያሳስባሉ። አሁን ፀደቀ የተባለው ይዘት ከላይ የተጠቀሰው ችግር ያለበት መሆኑ ሊጠቀስ ቢችልም የኢትዮጵያ ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በአንቀጽ 360(4) መሠረት ስለሚሰጥ ካሳ የሕግ ትርጉም ሥነ-ሥርዓቱን (jurisprudence) ሲያዳብር፣ በስህተት ለተፈረደባቸው ሰዎች የሚሰጡ የካሳ ሥርዓቶችን በተመለከተ ዓለም አቀፍ የንጽጽር ልምዶችን ቢፈትሽ እጅጉን ተጠቃሚ ይሆናል። በእንግሊዝ ሀገር በስህተት ለተፈረደባቸው ሰዎች የሚሰጠው የ‘ኤክስ ግራሽያ’ (ex gratia) የካሳ ሥርዓት ማለትም በአር (አዳምስ) እና በፍትሕ ሚኒስትሩ (R (Adams) v Secretary of State for Justice) መካከል በነበረው ክርክር ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሰጠው ውሳኔ በኋላ በአሁኑ ጊዜ ተግባራዊ መሆኑ ቢያበቃም⁵፣ በስህተት የተፈረደባቸውን ጉዳዮች ካሳ ለመተመን ያዳበራቸው ሰፊ መርሆች አሁንም ለንጽጽር ትንታኔ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው። በተመሳሳይ መልኩ፣ የካናዳ የክፍለ-ግዛት እና የፌዴራል የካሳ ሥርዓቶች፣ እንዲሁም በአተገባበራቸው ዙሪያ ያሉ አካዳሚያዊ ጽሑፎች፣ የኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶች በአንቀጽ 360 መሠረት ለሚያጋጥማቸው የነፃነት እና የክብር መጥፋት ጉዳቶችን ዋጋ ለመተመን የሚያስችሉ ጠቃሚ ማዕቀፎችን ሊያሳዩ ይችላሉ። VII. ማጠቃለያ የመጨረሻ ፍርድን እንደገና ማየት" የተሰኘው ምዕራፍ የረቂቅ ዝግጅት በሕግ ረገድ ጠንካራ፣ በሞራል ረገድ ተራማጅ(የሞራል ካሳ መጠን ትርጉም አልባ ቢሆንም)፣ እና በአካዳሚያዊ መመዘኛ ጥልቀት ያለው ነው። አጠቃላይ የወንጀል ሥነ-ሥርዓት እና የማስረጃ ረቂቅ ሕጉ በመጀመሪያ የረቂቅ ዝግጅት ወቅት የነበሩት ክፍተቶች (በቋሚ ኮሚቴው ከፍተኛ ማሻሻያዎች እንደታየው) ቢኖሩበትም፣ የዚህ ልዩ የሕግ መፍትሔ (extraordinary remedy) የመጨረሻ ቅርጽ ቢወጣ ለኢትዮጵያ የወንጀል ፍትሕ ሥርዓት ታሪካዊ የሆነ ግስጋሴን እንደሚወክል ይታመናል። ተጠቃሾቹ የረቂቅ ሰነዱ ድንጋጌዎች ንጹሐን ሰዎችን ነፃ የማውጣትን ፍጹም ሞራላዊ ግዴታን፣ የዳኝነት የመጨረሻነት አስፈላጊነት ጋር ያመዛዘኑ ሲሆን፣ ይህንም በመንግሥት ተጠያቂነት እና በጠጋኝ የካሳ ሥርዓት የተደገፈ ለማድረግ ተገቢውንና የተቻለውን ጥረት ያደረጉ ናቸው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ስለካሳው ስሌት በረቂቁ ሰነድ በተካተቱበት አግባቦች ከካሳው ባህርይና ከሌሎች አገራት ተሞክሮ ጋር በማነፃፀር ተገቢው ማሻሻያ ተደርጎ ድንጋጌዎቹ ቢወጡ በአገራችን የወንጀል ፍትህ ስርዓት አስተዳደር ሙሉዕ የሆነ አዎንታዊ ውጤት የሚያስከትሉ ሊሆኑ እንደሚችሉ ብዙዎችን የሚያስማሙ ይሆናሉ፡፡ ተፃፈ፦ በአልማው ወሌ ሚያዚያ 13 ቀን 2018 ዓ/ም

 በሌላ ሰው የሚሰጥ ታዓማኒነት ያለው የጥፋተኝነት እምነት ቃል፡- በነፃ የተለቀቀ ሌላ ሰው ከፍርድ ቤት ውጭ ወንጀሉን መፈጸሙን ካመነ፣ በስህተት የተፈረደበት ሰው ይህንን እንደ ምክንያት ሊጠቀምበት ይችላል።  የተጭበረበረ/የሐሰት ማስረጃ፡- የመጀመሪያው ፍርድ የተገኘው በሐሰተኛ ምስክርነት ወይም በተፈበረከ ማስረጃ መሆኑ ሲረጋገጥ ፍርዱን እንደገና ማየትን ይፈቅዳል። ፍርድን እንደገና ለማየት ታስቦ የተቀመጡት ምክንያቶች ሲታዩም ጥብቅ መሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል። ምክንያቱም አዲሱ ማስረጃ "በማያጠራጥር ሁኔታ (ፍርዱ) አይሰጥም ነበር የሚያስብል" መሆን አለበት ብሎ መስፈርቱን ከፍ በማድረግ፣ ሕጉ መሠረተ-ቢስ ለሆኑ አቤቱታዎች በሩ ክፍት እንዳይሆን ይከላከላል። በዚህም በዳኝነት ቅልጥፍና እና በፍትሕ መካከል ፍጹም የሆነ ሚዛን ለመጠበቅ መታሰቡን ያሳያል። V. የጊዜ ገደብ አለመኖር፡- የይርጋ ጊዜን ማስቀረት (አንቀጽ 358) የረቂቅ ሰነዱ አንቀጽ 358(1) "ፍርዱ እንደገና እንዲታይ የሚቀርብ ማመልከቻ በማንኛውም ጊዜ ማቅረብ ይችላል" ይላል። በዚህ ክፍል ውስጥ ከሚገኙት እጅግ ጠንካራ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ ይህ አንዱ ሊሆን ይችላል። የዲ.ኤን.ኤ (DNA) ማስረጃዎች ወይም ምስክሮች ቃላቸውን መቀየራቸው በርካታ አሥርት ዓመታት በኋላ ሊከሰቱ እንደሚችሉ በመገንዘብ፣ አርቃቂዎቹ ለዚህ መፍትሔ የሚሆን ማንኛውንም የይርጋ ጊዜ አስወግደዋል። እንዲህ አይነት የህግ ማረቀቅ አካሔድም ‘ፍትሕ የማብቂያ ጊዜ (expiration date) የላትም የሚለውን ጥልቅ ሃሳብ ተጨባጭ የሆነ ትርጉም እንዲኖር የሚያደርግ ነው። VI. ጠጋኝ ፍትሕ (Restorative Justice) እና የመንግሥት ኃላፊነት (አንቀጽ 360) አንድ የጥፋተኝነት ፍርድ ሲሻር ረቂቅ ሰነድ በአንቀጽ 360 ጠንካራ የሆነ የካሳ ሥርዓትን ለመዘርጋት አስቧል፡-  ቁሳዊ እና ሞራላዊ ካሳ (360(1))፡- በስህተት ተፈርዶበት የነበረው ሰው በግፍ ላሳለፈው ጊዜ ከመንግሥት ተመጣጣኝ ካሳ የማግኘት መብት አለው።  ከሞት በኋላ የሚሰጥ ካሳ (360(2))፡- እጅግ በሚያሳዝን ሁኔታ፣ የተሳሳተው ፍርድ የሞት ቅጣት ሆኖ ተፈጻሚ ከሆነ፣ ካሳው ለትዳር ጓደኛ ወይም ለወራሾች ይከፈላል። ይህ የሞት ቅጣት ሊቀለበስ የማይችል ገዳይ ስህተት (fatal flaw) ሊኖረው እንደሚችል በግልጽ የተቀመጠ ማሳያ ነው።  የመንግሥት ይቅርታ (360(3))፡- "መንግሥት ተጎጂውን፣ የትዳር ጓደኛውን ወይም ወራሾቹን ለደረሰባቸው ጉዳት ይቅርታ ይጠይቃል።" አንቀጽ 360 የጠጋኝ ፍትሕ (Restorative Justice) ከፍተኛ ማሳያ (Masterclass) ነው። የገንዘብ ካሳ ክፍያ (በአንቀጽ 360(4) በፍትሐብሔር ሕጉ መሠረት) በአንዳንድ ባደጉ የሕግ ሥርዓቶች የተለመደ ቢሆንም፣ በሕግ በተደነገገ አስገዳጅነት መንግሥት ይፋዊ ይቅርታ እንዲጠይቅ ለማድረግ መታሰቡም በዓለም አቀፍ ደረጃ እጅግ በጣም አነስተኛ ከሚባሉት አሠራሮች አንዱ ነው። ይህ ድንጋጌ ተቋማዊ ተጠያቂነትን ለማስፈን እና ነፃ የተደረገው ግለሰብ ሥነ-ልቦናዊ ማገገም (psychological rehabilitation) እንዲያገኝ በእጅጉ የሚረዳ ነው። ይሁን እንጂ አጠቃላይ የፍትሐብሔር ሕግ የካሳ ማዕቀፍን በስህተት ለተፈረደባቸው ሰዎች በሚሰጥ የካሳ ክፍያ ጉዳዮች ላይ በጥቅሉ (በጅምላ) መተግበር የራሱ የሆኑ ተግዳሮቶች ያሉት መስሎ ይታየኛል፡፡ በፍ/ህጉ ከአንቀጽ 2028 እስከ 2163 ባሉት ድንጋጌዎች ሥር የፈረንሳይን የሲቪል ሕግ የጥፋት ኃላፊነት (delictual liability) ወግ በዋናነት መሠረት አድርጎ የተቀረጸው የኢትዮጵያ ፍትሐብሔር ሕግ ከውል ውጪ ያለ ኃላፊነት (extra-contractual liability) ማዕቀፍ፣ የተነደፈው እንደ የፍትሐብሔር ጥፋቶች (tortious acts)፣ የንብረት ጉዳት እና የውል ጥሰት ላሉት የተለመዱ የፍትሐብሔር በደሎች ካሳን ለመተመን በመሆኑ፣ በስህተት ተፈርዶባቸው ለቆዩ ሰዎች የሚቀርብን የካሳ ጥያቄ ልዩ ባህሪያት ሊያስተናግድ ይችላል የሚል እምነት የለኝም፡፡ በስህተት ታስሮ ለባከኑ ዓመታት የሚከፈልን ካሳ መተመን፣ በመደበኛው የፍትሐብሔር ሕግ የካሳ ስሌት ውስጥ ግልጽ አቻ የሌላቸውን ጉዳዮች ከግምት ውስጥ ማስገባትን ይጠይቃል። እነዚህም፦ የነፃነት የራሱ የገንዘብ ዋጋ፣ ሰዎች በኢኮኖሚያዊ አምራች ዕድሜያቸው በመታሰራቸው ምክንያት የሚደርስባቸውን የረጅም ጊዜ የገቢ ብክነት ማስላት፣ በሙያዊም ሆነ በግል ሕይወታቸው ላይ የሚደርሰውን የስም መጥፋት ጉዳት በገንዘብ መተመን፣ እንዲሁም በስህተት መታሰር የሚያስከትለውን ጥልቅ ሥነ-ልቦናዊ መዘዝ መገምገም......ወዘተ የሚጠይቁ መሆናቸውን በዘርፉ የተደረጉ የምሁራን ስራዎች ያሳስባሉ፡፡ ከሁሉም በላይ የሞራል ካሳን በተመለከተም የፍ/ህጉ ድንጋጌዎች ተፈፃሚ ሊሆን የሚችልበት አግባብ መካተቱ በፍ/ህጉ አንቀፅ 2116(3) ስር የሞራል ካሳ ከፍተኛው/ጣሪያው ብር 1000(አንድ ሺህ) በሆነበትና ይህ የገንዘብ መጠን አሁን ካለው የብር ጥንካሬ አንፃር ሲታይ በዚህ ረገድ የተቀመጠውን የካሳ አይነት ምጣኔው እንዲሰላበት ማጣቀሻ ከሆነው ህግ ጋር ተጣምሮ ሲነበብ መብትን ሰጥቶ ተግባራዊ ተጨባጭነቱን ትርጉም አልባ የሚያደርግ ስርዓት መዘርጋቱን የሚያሳይ እና በተዘዋዋሪም የሞራል ካሳ መብትን እንደመንፈግ የሚቆጠር ነው፡፡ ህግ አዋጪው ከወንጀል ጉዳይ ባህርይ በመነሳት ያላግባብ የታሰረ ሰው ሊደርሱበት ለሚችሉትን ጉዳቶች ካሳ ሲወሰን እግምት ውስጥ ሊገቡ የሚገባቸውን አግባቦች አመለካች በሆነ መልኩ አስቀምጦ ቁሳዊውንና የሞራል ካሳ መጠኑን የዳኝነት አካሉ እንዲወሰን ቢያደርገው ህጉን ፍትሃዊ፣ ምክንያታዊና ለረዥም ጊዜ ስራ ላይ እንዲውል ያስችል ነበር የሚል እይታ አለኝ፡፡ ህግ አውጪው ረቂቁ ላይ በተደረገው ውይይት በዚህ ረገድ የተመረጠውን የካሳ አሰላል ስሌት ለምን እንደመረጠውም ማብራሪያው አያሳይም፡፡ የሰው ልጅን የነፃነት እጦት እና ሥቃይ በገንዘብ መተመን እጅግ ፈታኝ መሆኑ የሚታመን ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከላይ እንደተጠቀሰው በስህተት ለተፈረደባቸው ሰዎች የሚሰጥ ካሳ በዓለም አቀፍ የሕግ ሥርዓቶች በዋናነት በቁሳዊ (የገቢ ብክነት) እና በሞራላዊ (ሥነ-ልቦናዊ ስብራት) ጉዳቶች ተከፍሎ የሚሰላ መሆኑን የምርምር ስራዎች ያስረዳሉ። የካሳ አወሳሰን የንጽጽር ልምዶችን ስንፈትሽ፤ በኮመን ሎው (Common Law) ሥርዓት እንደ ቴክሳስ ያሉት የአሜሪካን አገር ግዛቶች ከፍተኛ የሆነ ሕጋዊ የመነሻ ተመን (statutory base rate) እና የዕድሜ ልክ አበል ሲተገብሩ፣ እንግሊዝ በበኩሏ የካሳ ጣሪያ በማስቀመጥ እና በእስር ወቅት 'ያልወጣን የኑሮ ወጪ' ከካሳው ላይ በመቀነስ አወዛጋቢ አካሄድን ትከተላለች። በሲቪል ሕግ (Civil Law) ደግሞ፣ ጀርመን ለሞራል ጉዳት እጅግ አነስተኛና ቋሚ የቀን ተመን በመቁረጥ ለቁሳዊ ጉዳት ጥብቅ የማስረጃ ሸክም ስትጭን፤ ፈረንሳይ ግን ከማንኛውም ጣሪያ ነፃ በሆነና በተበዳዩ ግላዊ ሥቃይና ባመለጠው ዕድል (loss of opportunity) ላይ በተመሠረተ የዳኝነት ግምገማ (individualized judicial assessment) ትመራለች። በመሆኑም፣ እጅግ የላቀው የካሳ ማዕቀፍ የእነዚህን አካሄዶች ጠንካራ ጎን ያጣመረ ቅልቅል (hybrid) ሥርዓት ነው ተብሎ ይመከራል። ይኸውም፤ ተበዳዩን ለጥብቅ የማስረጃ ሸክም ሳይዳርግ ክብሩን የሚመልስ ከፍተኛ ሕጋዊ የመነሻ ተመን (statutory floor)

በወንጀል ጉዳይ የመጨረሻ ፍርድን እንደገና ማየት፡- በ2013 ዓ/ም በፓርላማው ለመጀመሪያ ንባብ ከበቃ በኋላ በቅርቡ ስለመፅቁ ይፋ በሆነው የወ/መ/ህግ ስነ ስርዓትና የማስረጃ ህግ ሰነዱ በረቂቅ ደረጃ ላይ እያለ በተካተቱት ድንጋጌዎች((ከአንቀጽ 356-360) ላይ የተደረገ አጭር ምልከታ ማሳሰቢያ፦‘በረቂቅ ደረጃ ላይ እያለ’ የሚለውን ሐረግ ለመጠቀም የተገደድኩት ህጉ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ስላልወጣ እና ከዝርዝር እይታ በኋላ በይዘቱም ሆነ በአናቅፅት አቀማመጥ ላይ ለውጥ ወይም ሽግሽግ ሊኖር ስለሚችል በመገመት ነው፡፡ ስለሆነም ፅሁፍ ይህን ታሳቢ ተደርጎ የተዘጋጀ ሲሆን ለወደፊቱ ደግሞ የፀቀውን ህግ ሙሉ ይዘት መሰረት በማድረግ በርዕሰ ጉዳይ ላይ ተገቢው ምልከታ የሚከናወንበት ይሆናል፡፡ የዚህ ፅሁፍ ፋይዳው መሰረተ ሃሳቡ ላይ በህግ ትምህርት ቤትና በስራ ዓለም የነበረንና ያለንን ግንዛቤ ለማስታወስ እና ረቂቁ ስለጉዳይ ባለበት ሁኔታ የሚወጣ ከሆነ ጉድለቱን በመመርመር ለወደፊቱ ማስተካከያ ለመጠቆም ነው፡፡ እንዲሁም ጽሑፉ ሲዘጋጅ የተለያዩ ማጣቀሻ ሰነዶች ጥቅም ላይ የዋሉ ቢሆኑም ጽሁፍ ለፌስቡክ ተደራሽነት በሚያመች መልኩ የተከለሰ በመሆኑ ለቦታ አጠቃቀም ሲባል በጽሁፉ መጨረሻ ላይ ዝርዝሩን ላለማስቀመጥ የተገደድኩ ስለመሆኑ ውድ ወዳጆቼ እንድትገንዘቡ አደራ እላለሁ፡፡ I. መግቢያ፡- አጠቃላይ የወንጀል ፍትሕ ሥርዓት ከፖለቲካ ጋር የጠበቀ ቁርኝት ያለው ከመሆኑም በላይ በሰው ልጆች የሚመራ ተቋማዊ አሰራር እንደመሆኑ መጠን ፈጽሞ ከስህተት የጸዳ ሊሆን አይችልም። የፍርድ የመጨረሻነት (Finality of Judgment) መርህን ብቻ አጥብቆ በመያዝ አዲስ ለሚፈነጥቁ ንጹሕነትን አረጋጋጭ እውነታዎች የሕግ በሮችን ሙሉ በሙሉ መዝጋት፣ ንጹሐን ዜጎች በግፍ ዘብጥያ እንዲማቅቁ የሚያደርግ እጅግ የከፋ የሥርዓቱ የሞራል ውድቀት ነው። የዚህን ችግር አሰቃቂ ስፋት (dimension) ለመገንዘብ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ በ'ኢኖሰንስ ፕሮጀክት' (Innocence Project) አነሳሽነት በዘመናዊ የዲ.ኤን.ኤ (DNA) ቴክኖሎጂ ታግዘው ከበርካታ አሥርት ዓመታት የሞት ፍርድ እና የእድሜ ልክ እስራት በኋላ ነፃ የወጡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ንጹሐንን እውነተኛ ታሪክ (real cases) መመልከት በቂ ሲሆን፤ በሀገር ውስጥም ቢሆን በተሳሳተ ምስክርነት ወይም በምርመራ ግድፈቶች ምክንያት ነፃነታቸውን ለዓመታት የተነጠቁ ዜጎች መኖራቸው የዚሁ መሪር እውነት አካል ነው። በመሆኑም ዘመናዊ መንግሥታት ይህንን ሊቀለበስ የማይችል የፍትሕ መጓደል፣ የሕግ ሥርዓቱን ቋሚነትና መረጋጋት (Legal Certainty) ከማረጋገጥ ብርቱ ፍላጎት ጋር ሚዛን ለመጠበቅ ሲሉ፣ እንደ "የመጨረሻ ፍርድን እንደገና ማየት" (Review of Judgment) የመሳሰሉ ልዩ የሕግ መፍትሔዎችን (extraordinary remedies) ሥርዓት ይዘረጋሉ፤ ይኸውም መዝገቡ ከተዘጋ በኋላም ቢሆን መሰረታዊ ፍትሕ (Substantive Justice) ከሥነ-ሥርዓታዊ ደንቦች ልቆ መውጣት እንዳለበት የሚያረጋግጥበት የፍትሕ ሥርዓቱ የሕሊና ሚዛን (safety valve) ሆኖ ያገለግላል። መጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ/ም በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መፅደቁ የታወጀው ሰነድ ላይ በረቂቅ ደረጃ ላይ እያለ "የመጨረሻ ፍርድን እንደገና ማየት" በሚለው ርዕስ ሥር የተካተቱት ድንጋጌዎች የመጨረሻ የጥፋተኝነት ውሳኔ ከተሰጠ በኋላ የሚቀርብን ልዩ የሕግ መፍትሔ (post-conviction remedy) በአገሪቱ የወንጀል ፍትህ አስተዳደር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ሥርዓት ለመዘረጋት ታስበው የገቡ ናቸው። ይህ አሰራር አዲስ በተገኙ፣ ንጹሕነትን ሊያረጋግጡ በሚችሉ ማስረጃዎች ላይ ተመሥርቶ የመጨረሻ እና አስገዳጅ የሆነን የወንጀል ፍርድ እንደገና ለመመርመርና ፍንትው ያለ ሀቅን ለማረጋገጥ ያስችላል በሚል እምነት የተካተተ መሆኑ ይታመናል። II. የመሰረታዊ ፍትሕ (Substantive Justice) እና የፍርድ የመጨረሻነት (Ne bis in idem) ፍልስፍናዊ ንፅፅር (አንቀጽ 356) በረቂቅ ደረጃ የነበረው የህግ ሰነዱ በአንቀጽ 356 የዚህን ሂደት ዓላማ በግልጽ ሲያስቀምጥ፡ "በተዛባ ፍርድ ንፁኃን እንዳይቀጡ ፍርዱን ለማረም ነው" ይላል። ይህ ድንጋጌ ከሥነ-ሥርዓታዊ የፍርድ የመጨረሻነት (Ne bis in idem) መርህ ይልቅ ለመሰረታዊው እውነት (Substantive truth) የተሰጠን ፍልስፍናዊ የበላይነት ያሳያል። በብዙ የሕግ ሥርዓቶች ውስጥ የሕግ ሥርዓቱን መረጋጋት ለማረጋገጥ ሲባል የፍርድ የመጨረሻነት መርህ በጥብቅ የሚጠበቅ መሆኑን የምርምር ስራዎች ያሳያሉ፡፡ ይሁን እንጂ የአዲሱ ሕግ ረቂቅ የነበረው ሰነድ የሰው ልጅ የፍትሕ ሥርዓት ሊሳሳት የሚችል መሆኑን አምኖ በመቀበል ተረቅቋል። በእርግጥም ንጹሕ የሆኑ ሰዎችን ነፃ ማውጣትን ቅድሚያ በመስጠት፣ የኢትዮጵያ ሕግ አውጪ ዘመናዊ እና ተራማጅ ከሆኑ የወንጀል ፍልስፍናዎች ጋር የተጣመረ ህግ ለማውጣት የሚያስችል ረቂቅ የተዘጋጀ ሲሆን፣ የአንድ ክስ መዝገብ መዘጋት መቼም ቢሆን ከእውነት ሊበልጥ እንደማይችልም የሚያረጋገጥ ክስተት ሁኖ ብቅ ብሏል! ተብሎ የሚወደስ መሆኑ ይገመታል። III. ሰፊ የአቤቱታ ማቅረብ መብት (Standing) እና የዓቃቤ ሕግ ግዴታ (አንቀጽ 357(1)) የረቂቅ ሰነዱ አንቀጽ 357(1) ፍርዱ እንደገና እንዲታይ ማመልከቻ የማቅረብ መብትን ለፍርደኛው፣ ለወኪሉ፣ ለቤተሰቡ ወይም ለዐቃቤ ሕግ ይሰጣል። በዚህ ድንጋጌ ውስጥ ዐቃቤ ሕግን ማካተት እጅግ የሚመሰገን የህግ ማረቀቅ ጥበብ ምርጫ ነው ተብሎ ይታመናል። ይህ አካሄድ የአንድ ዐቃቤ ሕግ ዋነኛ ግዴታ ፍርድ ማሰጠት ሳይሆን ፍትሕን መፈለግ ነው የሚለውን ሥነ-ምግባራዊ መርህም በተግባር እንዲጠናከር ህግ አውጪው ማለሙንም የሚያስገነዝብ ነው። አንድ ዐቃቤ ሕግ ከፍርድ በኋላ አንድ ንጹሕ ሰው መታሰሩን ከተረዳ፣ ይህ ድንጋጌ ዐቃቤ ሕጉ ራሱ ቀድሞ ያገኘውን የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዲሻር በንቃት እንዲንቀሳቀስ ሕጋዊ ሥልጣን (statutory mandate) እንዲኖረው የሚያችል መሰረታዊ መደላድል ነው። IV. ጥብቅ ነገር ግን ተራማጅ የሆኑ የክለሳ ምክንያቶች (አንቀጽ 357(2)) ረቂቅ ሰነዱ ፍርዱን እንደገና ለማየት የሚያስችለው አዲሱ ማስረጃ የመጀመሪያውን ውጤት ሊቀይር የሚችል መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ምክንያቶችንም በዝርዝር አስቀምጧል፡- እነዚህም፦  ነፃ ሊያደርግ የሚችል አዲስ ማስረጃ እና  አዲስ ሳይንሳዊ ማስረጃ፡ ይህ ድንጋጌ በፎረንሲክ ሳይንስ የሚመጡ ዕድገቶችን (ለምሳሌ፡ ከፍርድ በኋላ የሚደረግ የዲ.ኤን.ኤ (DNA) ምርመራ) በግልጽ ያስተናግዳል። ይህም በመጀመሪያው የፍርድ ሂደት ወቅት በነበረው የቴክኖሎጂ ዘመን ብቻ ተወስኖ እንዳይቀር የሚከላከል ወሳኝ ዘመናዊ አሰራር ነው።  የዳኝነት ሙስና/የሥነ-ምግባር ግድፈት፡- አንድ ሰው ጉዳዩን የተመለከተው የመጀመሪያው ዳኛ ጉዳዩን በማዛባቱ በወንጀል ጥፋተኛ ከተባለ፣ ፍርዱ ሊሻር እንደሚችል ያሳያል። ይህ የዳኝነቱን ሥርዓት ታማኝነት ለመጠበቅ የሚያስችል መሆኑ ይታመናል።

ርዕስ: የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር አጣሪ ችሎት፡ "የበር ጠባቂነት" ሚና እና የቃል ክርክር አተገባበር ተግዳሮቶች 1.    መግቢያ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ መንግስት ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በሀገሪቱ የዳኝነት ስርዓት ውስጥ ልዩ ስልጣን ሰጥቶታል። የዚህ ችሎት ዋና ሚና ከስር ፍርድ ቤቶች በሚሰጡ ውሳኔዎች ላይ የሚፈጸሙ "መሰረታዊ የህግ ስህተቶችን" በማረም የህግ ትርጓሜ ወጥ እንዲሆን ማስፈን ነው። በአዋጅ ቁጥር 1234/2013 መሰረት የተቋቋመው የሰበር አጣሪ ችሎት፣ በሶስት ዳኞች የሚዋቀር ሲሆን፣ አምስት ዳኞች ለሚሰየሙበት የሰበር ችሎት የሚቀርቡ አቤቱታዎችን በማጣራት “የበር ጠባቂነት” ሚና ይጫወታል። ይህ አሰራር የስራ ጫናን በመቀነስ የሰበር ችሎቱን ቅልጥፍናና ጥራት ለማሳደግ ያለመ ነው። 2.   የሰበር አጣሪ ችሎት ሚና እና ስልጣን የሰበር አጣሪ ችሎት ሁለት ዋና ስልጣኖች አሉት፡- 2.1   መሰረታዊ የህግ ስህተት የለም ብሎ ካመነ አቤቱታውን ውድቅ ማድረግ እና 2.2  መሰረታዊ የህግ ስህተት እንዳለ ካመነ ጉዳዩን ለአምስት ዳኞች ሰበር ችሎት ማስተላልፍ። በ2.1 በተጠቀሰው ስልጣኑ ችሎቱ የመጨረሻ የዳኝነት ውጤት የሚሰጥ አካል ሆኖ ያገለግላል። 3.   የቃል ክርክር አሰራር እና ተግዳሮቶች የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ሥነ-ሥርዓት መመሪያ ቁጥር 17/2015 አንቀጽ 6(2) አመልካች በአጣሪ ችሎት ፊት ቀርቦ በቃል እንዲሰማ ይደነግጋል። ሆኖም ድንጋጌው ይህ የቃል ክርክር በጽሑፍ ሊመዘገብ እንደሚገባ ያስቀመጠው ግዴታ የለም፡፡ ሰበር አጣሪ ችሎቱ አሰራር የሚያሳየውም የቃል ክርክሩ የማይመዘገብ መሆኑ ነው፡፡ የችሎቱ የውሳኔው ትዕዛዝም የአመልካችን የቃል ክርክር መሰረታዊ ይዘት አያንፀባርቅም። ይህ አሰራር በተለያዩ ባለድርሻ አካላትና አግባብነት ካላቸው መርሆዎች አኳያ የሚከተሉት ጥያቄዎች ሲነሱበት ይታያል፡፡ እነዚህም፦ Ø ግልጽነትና ተጠያቂነትን በሚመለከት በህግ እንዲካሄድ የታዘዘ የቃል ክርክር መመዝገብ ሲገባው አለመመዝገቡ ግልጽነትንና ተጠያቂነትን ያጓድላል የሚል፣ Ø በዳኞች እይታ ዳኞች የቃል ክርክሩን ዓላማ የአመልካችን የሰበር ማመልከቻ ይዘት በፍጥነት ለመረዳት እንጂ ሁሉንም ነገር ለመመዝገብ አይደለም በሚል የሚቀርብ ማብራሪያ፣ Ø ከህግ ባለሙያዎች በኩል ደግሞ የቃል ክርክሩን " በችሎቱ ምንም አይነት ዋጋ ላይሰጠው ከንቱ ድካም እና ወደ ባዶ ስፍራ እንደ መጮኽ" ነው በሚል የሚቀርብ ቅሬታ እንዲሁም ክርክሮቻቸው ለምን ውድቅ እንደሆኑ ለማወቅ መንገድ እንደሌላቸው  የሚያነሱት ምክንያት፣ Ø ከህገ-መንግስታዊ መርሆዎች አንፃር ደግሞ ፍትሐዊና ግልጽ የፍርድ ሂደት የማግኘት መብት፣ በምክንያት የተደገፈ ውሳኔ የማግኘት መብት እና የመረጃ ሙሉነት መርሆዎች በዚህ አሰራር የሚጣሱ ናቸው የሚሉት ምክንያቶች፣ እና Ø ከፍትህ ተደራሽነት መርህ አንፃር ሲታይ ደግሞ ክርክሩ ሳይመዘገብ ውሳኔ መስጠት የዘፈቀደነት ስሜት በመፍጠር በፍትህ ስርዓቱ ላይ ያለውን የህዝብ አመኔታ ሊሸረሽር ይችላል የሚሉት ናቸው፡፡ 4.   የመፍትሄ ሀሳቦች የሰበር አጣሪ ችሎትን አሰራር ለማሻሻል የሚከተሉት እርምጃዎች ሊወሰዱ ይችላሉ፡- § የመመሪያ ማሻሻያ:- በሰበር ሥነ-ሥርዓት መመሪያ አንቀጽ 6 ስር የቃል ክርክሮች በድምጽ እንዲቀረጹ ወይም መሰረታዊ ነጥቦች በጽሑፍ እንዲመዘገቡ መደንገግ፣ § የውሳኔ አሰጣጥ ግልጽነት:- አጣሪ ችሎቱ ውድቅ በሚያደርጋቸው አቤቱታዎች ላይ አመልካቹ ያቀረባቸውን ዋና ዋና የህግ ክርክሮች በመጥቀስ ለምን መሰረታዊ የህግ ስህተት እንዳልሆኑ እንዲገልጽ በሚያስገድድ መልኩ መመሪያውን ማሻሻል፣ § የውስጥ መመሪያ: - የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአጣሪ ችሎት ሰብሳቢ ዳኞች/መዝገቡን የያዘው የችሎቱ ዳኛ የቃል ክርክር ማጠቃለያ በመዝገብ ላይ እንዲያሰፍሩ የሚያስገድድ የውስጥ መመሪያ ማውጣት/የመግባቢያ ሰነድ ማዘጋጀት፣ § የቴክኖሎጂ አጠቃቀም: - በየችሎት ክፍሎች ውስጥ ቀላልና ወጪ ቆጣቢ የሆኑ የቃል ክርክሩን ወዲያውኑ ወደ ፅሁፍ ቀይሮ ግልባጩን ከመዝገቡ ጋር ለማያያዝ የሚያስችል ቴክኖሎጂዎችን ማሟላት፣ § የጉዳይ አስተዳደር ማሻሻያዎች: - የአጣሪ ችሎቶች ብዛት፣ የጉዳዮች ቀጠሮ አያያዝ እና ተያያዥ የስራ ሂደቶችን ማሻሻል .... ወዘተ ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ 5.    መደምደሚያ የሰበር አጣሪ ችሎት ለቅልጥፍና እና ውጤታማነት ቢታሰብም አሁን ያለው የቃል ክርክር አሰራር የፍትሐዊነትን፣ የግልጽነትን እና በምክንያት የተደገፈ ውሳኔ የማግኘት መብትን አደጋ ላይ የጣለ ነው ሊባል የሚችል ነው፡፡ በማናቸውም እርከን የሚገኙ የዳኝነት አካላት የስራ ጫናን ለማስተዳደር የሚያስችል አሰራርና ስትራቴጂ መከተል ተገቢ ቢሆንም የዳኝነት ስርዓቱን መሰረታዊ መርሆዎች በመጠበቅ እንጂ መርሆዎችን መስዋዕት በማድረግ ሊሆን አይገባም። ከላይ የተጠቀሱት የመፍትሄ ሃሳቦች ወይም ሌሎች አማራጭ መንገዶች ተግባራዊ ከሆኑ የሰበር አጣሪ ችሎት የ’’በር ጠባቂነት’’ ሚናውን (Gate keeping Role) ይበልጥ በብቃትና በፍትሐዊነት እንዲወጣ ያስችለዋል ተብሎ ይገመታል፡፡ የዚህ ፅሁፍ ሙሉ ይዘት በFB  ገፄ(https://lnkd.in/ddBgHbch) አስቀድሞ የተለጠፈ በመሆኑ ያንኑ ሰነድ እንዲመለከቱ እያሳወቅሁ ርዕሰ ጉዳዩን በተመለከተ ገንቢ ሀሳብዎትንና እና አስተያየትዎትን እንዲሰጡበት በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡