መነሳሳት የሁሉ ነገር መነሻ ነው!
በአንድ ወቅት የተከናወነ አስቂኝና አስገራሚ ታሪክ እንደሆነ ይነገራል፡፡
በአሜሪካ ግዛት ውስጥ ባለች አንዲት ከተማ ውስጥ በሚገኝ አንድ የሕዝብ መናፈሻ ውስጥ ለሚዝናኑ ሰዎች መገልገያነት በተዘጋጀው የእንጨት አግዳሚ ወንበር ላይ አንድ እድሜው በአርባዎቹ አካባቢ ያለ ሰው በትካዜ አቀርቅሮ ተቀምጧል፡፡ ይህ ሰው በንግድ ስራ የተወሰኑ አመታትን አሳልፏል፡፡ በዚያ ተቀምጦ የሚያስበው በወቅቱ ስላለበት የገንዘብ ሁኔታ ነው፡፡
ይህ ነጋዴ ብዙ በገንዘብ የማደግ ሙከራዎችን አድርጎ ያልተሳካለት ሰው ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን ምንም እንኳን የተወሰነ የገንዘብ አቅም ቢኖረውም ምናልባት አንድን ነገር ሞክሬ እንዳልከስርና ያለችኝን እንዳላጣ በማለት በባንክ ውስጥ አስቀምጦ በስራ ፈትነት ወዲህና ወዲያ ይንከራተታል፡፡
ነጋዴው ወደ እርሱ ቀረብ ያለ የኮቴ ድምጽ ስለሰማ አንገቱን ካቀረቀረበት ቀና አድርጎ ሲመለከት አጠገቡ አንድ ሰው ቆሞ ያይና ከነበረበት ተመስጦ ይባንናል፡፡ ይህ ሰው ጥሩ የለበሰና መልከ መልካም ገጽታ ያለው ሰው ነው፡፡
ሰውየው፣ “አንገትህን አቀርቅረህ የተቀምጥከው ለምድን ነው?” ብሎ ጠየቀው፡፡ ነጋዴውም፣ “ብዙ ሙከራዎችን አድርጌ ስላልተሳካልኝ ትንሽ አዝኛለሁ፡፡ ስላለፈው ታሪኬና አሁን ስላለሁበት ሁኔታ እንዲሁ በትካዜ እያሰብኩ ነው” አለው፡፡
ሰውየው፣ “ሮክፌለር (Rockefeller) ስለሚባል የአሜሪካ ቀንደኛ ሚሊየነርና የበጎ አድራጎት ሰው ሰምተህ ታውቃለህ?” አለው፡፡ ነጋዴውም፣ “ስለዚህ ሚሊየነር ሰው ያልሰማ አሜሪካዊ አለ ብለህ ነው? አዎን፣ እኔም ቢሆን በስምና በዝና አውቀዋለሁ እንጂ ምን እንደሚመስል እንኳ አላውቅም” በማለት መለሰለት፡፡
ሰውየውም በመቀጠል፣ “ሮክፌለር ማለት እኔ ነኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ በእንደዚህ አይነት መናፈሻዎች በመዘዋወር ያዘኑና ለብቻቸው የተቀመጡ ሰዎችን በማነጋገር ችግራቸውን ማቃለል እወዳለሁ፡፡ ምን ማድረግ እንደፈለክ ብትነግረኝ ለዚያ የሚሆን በቂ ገንዘብ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ነጋዴው የሚሰማውን በማመንና ባለማመን ሃሳብ መካከል እየታገለ ቀስ በቀስ የልቡን ያለፈበትን አስቸጋሪ ጎዳናና ያለውን ምኞት ሁሉ ዝክዝክ አድርጎ አጫወተው፡፡
ሰውየው ምንም ሳይወላውል አጠገቡ ከተቀመጠ በኋላ በእጁ ያንጠለጠለውን የሰነድ ቦርሳ በጉልበቱ ላይ አስቀምጦ በመክፈት አንድን የቼክ ደብተር አወጣ፡፡ በዚያም ቼክ ላይ የነጋዴውን ስም ጠይቆ ካሰፈረ በኋላ አንድ ሚልየን ዶላር ጽፎ በመስጠት እንዲህ አለው፡፡ “ይህንን አንድ ሚልየን ዶላር በምትፈልገው የንግድ መስክ ላይ አውለውና ሕይወትህን አሻሽል፡፡ እቅድ ለማውጣት ጊዜ ስለሚፈጅ እስከ አንድ አመት ድረስ ይህንን ቼክ ባታወጣውም ችግር የለውም፡፡ ብሩ ለአንተ ተቀምጦ ይጠብቅሃል” አለውና ወዲያው ከፊቱ ተሰወረ፡፡
የሚያስበውንና የሚያደርገውን ያጣው ይህ ነጋዴ በደስታ ተነስቶ ወደቤቱ በመሄድ ማሰብ ጀመረ፡፡ ለራሱም እንዲህ አለ፣ “አሁን ይህንን አንድ የሚሊየን ዶላር ቼክ በቤቴ አስቀምጥና ባንክ ያለኝን ገንዘብ በድፍረት በማውጣት አንድን ንግድ እጀምራለሁ”፡፡ ቀደም ብሎ ያስብ የነበረው ንግድ ስለነበረ ቼኩን እቤቱ አስቀምጦ ባንክ ያለውን ገንዘብ በማውጣት በድፍረት መነገድ ጀመረ፡፡ አመት ባልሞላው ጊዜ ውስጥ በጣም ብዙ ብር አተረፈ፡፡ በእጁ ላይ ባለው የገንዘብ መጠን በሚገባ ከተደላደለ በኋላ አንድ ቀን ቼኩን ለማውጣት ወደባንክ ሲሄድ ቼኩ እውነተኛ ቼክ እንዳልሆነ ነገሩት፡፡
በነገሩ ተደናግጦ ወደቤቱ ሲመለስ እግረ መንገዱን ወደዚያ መናፈሻ ቦታ ጎራ ብሎ ስለሆነበት ነገር ትንሽ ማሰብ ፈለገና ወደመናፈሻው ሲሄድ፣ ያንን ቼክ የሰጠውን ሰው ለሌላ ሰው ተመሳሳይ ነገር ሲያደርግ ተመለከተው፡፡ በማየት ላይ ባለው ነገር ተገርሞ ጠጋ ብሎ ማዳመጥ ሲጀምር በእርሱ ላይ የሆነው ነገር በሌላም ሰው ላይ እየተደገመ እንደሆነ ተመለከተ፡፡ ምን ማድረግ እንዳለበት ሲያስብ ሶስት በእድሜ ጠና ያሉ ሰዎች እየተሯሯጡ መጥተው ይህንን “ሮክፌለር ነኝ” ባይ ሰው እጁን ይዘው፣ “እንደዚህ አይነት ነገር ሁለተኛ እንዳታደርግ አልተነገረህም?” በማለት እያዋከቡ ወሰዱት፡፡ ለካስ ይህ ሰው የአእምሮ ሕመምተኛ ሰው ነበር፡፡ ይህንን ሮክፌለር ነኝ በማለት የሚያታልልበትን ቼክ የት እንዳሳተመው ባይታወቅም ቼኩን ለሰዎች እየሰጠ የውሸት ተስፋ በመስጠትና በማታለል ይታወቃል፡፡
ነጋዴው ሁኔታው ቢያበሳጨውም አንድ እውነታ ግን ፍንትው ብሎ በራለት፡፡ በእጁ ያለውን ገንዘብ አውጥቶ እንዳይከስር በመፍራት ከመንቀሳቀስ ታስሮ በነበረበት ጊዜ በዚህ ሰው የውሸት ተስፋ ምክንያት ልክ ብዙ ገንዘብ እንዳለው ወደማመን በመምጣቱ በድፍረት ስራ ውስጥ ገባ፡፡ ከዚህ የተነሳ አትራፊ የሆነን ንግድ በአንድ አመት ውስጥ መሰረተ፡፡ ምንም እንኳን “አንድ ሚልየን ዶላር” የሚለው ቼክ ባዶ ቢሆንም፣ ምንም እንኳን ሰውየው የዋሸው ውሸት ቢያበሳጨውም፣ በዚያ ምክንያት ግን በመነሳሳት አሁን ያለበት ትልቅ ደረጃ ደርሷል፡፡
ይህ ታሪክ አንዳንድ ጊዜ የሚያስፈልገን የገንዘብ ብዛት ሳይሆን የውስጥ መነሳሳትና የአመለካከት ለውጥ እንደሆነ ጠቋሚ ነው፡፡
ምንጭ ዶ/ር ኢዮብ ማሞ!