💚💛❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 💚💛❤
✝ 🌿🌹 ሐምሌ ፯ (7) ቀን።🌹🌿✝️
🌻🌹🌿🌹🌿🌹🌻
✝ ✝ ✝
💚💛❤ እንኳን ለአጋእዝተ ዓለም ለቅድስት ሥላሴ ወደ አብርሃም ቤት ለገቡበት የይስሐቅን መወለድ ለአበሰሩበት ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል፣ ለሮሜ ሊቀ ጳጳስ ለሐዋርያው ለቅዱስ አግናጥዮ ምጥው ለአንበሳ ለዕረፍት በዓልና ለባሕታውያን አለቃ ለሆነ ለመስተጋድል አባ ሲኖዳ ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከአባ መቃቢስ፣ ከአግራጥም ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
💚💛❤ በዚችም ቀን ልዩ የሆኑ ሦስቱ አካላት (አጋዝእተ ዓለም ሥላሴ) በኦሪት መጽሐፍ እንደተጻፈ ወደ አብርሃም ቤት ገብ ያቀረበላቸውን ተመገቡ የይስሐቅንም ልደት አሠሰሩት ባረኩት አከበሩትም። ለእግዚአብሔር ይስጋና ይሁን በአባታችን በቅዱስ አብርሃም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ታሪኩን በመጽሐፍ ቅዱስ ዘፍ 18 ላይ ያንብቡ።
✝ ✝ ✝
💚💛❤ የባሕታውያን አለቃ የሆነ መስተጋድል አባ ሲኖዳ፦ ይህም ቅዱስ በግብጽና በአክሚም አውራጃ ስሟ ስንላል ከምትባል ሀገር ከላይኛው ግብጽ ነበር። ስለእርሱም የመላእክት አምሳል የሆነ አባ ሐርስዮስ ትንቢት ተናገረለት። እርሱም ስለ ገዳም አገልግሎት ከመነኰሳት ጋር ሲሔድ የዚህን የቅዱስ ሲኖዳን እናት ውኃ ለመቅዳት ወጥታ አገኛት። ወደርሷ ሒዶ ሦስት ጊዜ ራሷን ሳማትና እንዲህ አላት "ዜናው በዓለሙ ሁሉ የሚሰማ የስሙ መዓዛ ከሽቱ የሚጥም የሆነ የሆድሽን ፍሬ እግዚአብሔር ይባርክ"።
💚💛❤ እነዚያ መነኰሳትም በአዩት ጊዜ አድንቀው "አባታችን አንተ የሴት ፊት ማየት ከቶ አትሻም ነበር ዛሬ ግን ከሴት ጋራ ትነጋገራለህ" አሉት። "ልጆቼ ሆይ ሕያው እግዚአብሔርን የእግዚአብሔርን ምሕረት ተስፋ የሚያደርግ ዓለሙ ሁሉ የሚጣፍጥበት ከዚች ሴት የሚወጣ የጨው ቅንጣት አለ" አላቸው።
💚💛❤ አንድ በገድል የጸና ጻድቅ ሰው መነኰስ ነበረ እርሱም መልሶ አባ ሐርስዮስን እንዲህ አለው "እግዚአብሔር ሕያው ነው አንተ ራሷን ትስም ዘንድ ወደዚያች ሴት በቀረብክ ጊዜ በእጁ የእሳት ሰይፍ የያዘ የእግዚአብሔርን መልአክ በዙሪያዋ አየሁት። ራሷንም በሳምካት ጊዜ ክብር ይግባውና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ ሆይ ሰላምታ ይገባሃል ሲልህ ደግሞም ከዚች ሴት የሚወለደው የተመረጡ ቅዱሳንን ሁሉ ልባቸውን ደስ ያሰኛል ወልደ እግዚአብሔርም ከርሱ ጋር ብዙ ጊዜ ይነጋገር ነበር ሲል ሰማሁት" አለ።
💚💛❤ በግንቦት ሰባት ቀን ይህ ቅዱስ አባ ሲኖዳ ተወለደ በአደገም ጊዜ አባቱ በጎች ስለነበሩት ለልጁ ለሲኖዳ እንዲጠብቃቸው ሰጠው ይህ ሲኖዳም ምሳውን ለእረኞች ሰጥቶ እስከ ማታ ድረስ ይጾም ነበር። በሌሊትም ከውኃ ዐዘቅት ውስጥ ወርዶ በዚያ ቁሞ እስቲነጋ ድረስ ሲጸልይ ያድር ነበር። በክረምትም ሆነ በቊር ሰዓት እንዲሁ ያደርግ ነበር። አባቱም የሲኖዳ እናት ወንድም ወደ ሆነው ወደ አባ አብጎል እጁን በላዩ ጭኖ ይባርከው ዘንድ ወሰደው። አባ አብጎልም በአየው ጊዜ የሕፃኑን እጅ አንሥቶ በራሱ ላይ አድርጎ "ሲኖዳ ሆይ ባርከኝ ለብዙ ሕዝብ ታላቅ አባት ትሆን ዘንድ የሚገባህ ሁነሃልና" አለው። አባቱም በአባ አብጎል ዘንድ ተወው።
💚💛❤ ከዕለታትም በአንዲቱ ቀን አባ አብጎል እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ ሰማ "እነሆ ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ አርሲመትሪዳ የባሕታውያን አለቃ ሁኖ ተሾመ"። ይህም ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ ብርሃን እስከሚሆን በበጎ አምልኮ ያለ ማቋረጥ በጾምና በጸሎት በስግደትና በመትጋት ታላቅ ተጋድሎ መጋደልን ጀመረ።
💚💛❤ ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ለአባ አብጎል የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና የኤልያስን አስኬማ የሠለስቱ ደቂቅን ቆብና የመጥምቁ ዮሐንስን ቅናት አመጣለት። እንዲህም አለው "እንድትጸልይና የምንኵስና ልብስ ለሲኖዳ እንድታለብሰው እግዚአብሔር አዝዞሃል"። ያን ጊዜም አባ አብጎል ተነሥቶ ጸለየ የምንኵስና ልብስንም አለበሰው።
💚💛❤ ከዚህም በኋላ ተጋድሎውን አበዛ። ለመነኰሳት፣ ለመኳንንት፣ ለሕዝባውያንና ለሴቶች ለሰዎች ሁሉ መመሪያ የሚሆን ሥራትን ሠራ። በኤፌሶንም የሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ ስለ ከሀዲው ንስጥሮስ በተደረገ ጊዜ ከማኅበሩ አባት ከሊቀ ጳጳሳት ቄርሎስ ጋራ ወደ ጉባኤው ሔደ ንስጥሮስም ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው አሳደዱት።
💚💛❤ ከዚህ በኋላም ወደ ሀገራቸው በመመለሻቸው ጊዜ መርከበኞች ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋራ አትሳፈርም ብለው አባ ሲኖዳን ከለከሉት እርሱም ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ማለደ። ወዲያውኑም ደመና መጥታ ተሸከመችውና አባ ቄርሎስ በመርከቡ ውስጥ እያለ በበላዩ በአንጻሩ አደረሰችው። "አባቴ ሆይ ሰላም ለአንተ ከአንተ ጋራ ላሉትም ይሁን" ብሎ ሰላምታ አቀረበ። በመርከብ ያሉት ሁሉም "ላንተም ሰላም ይሁን በጸሎትህም አትርሳን" አሉት። እጅግም አደነቁ ለሚፈሩት ይህን ያህል ጸጋ የሚሰጥ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
💚💛❤ ወደ ገዳሙም ደርሶ ከልጆቹ መነኰሳት ጋራ የመንፈቀ ሌሊትን ጸሎት አደረገ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ብዙ ጊዜ ወደርሱ እየመጣ ያነጋግረው ነበር። እርሱም የመድኃኒታችንን እግሩን ያጥበው ነበር እጣቢውንም ይጠጣ ነበር ጌታችንም ብዙ ምሥጢራትን ገለጠለት ትንቢቶችንም ተናገረ።
💚💛❤ ከዚህም በኋላ ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ ሐምሌ ሰባት ቀን ተኛ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መጥቶ እያረጋጋው በእርሱ ዘንድ ተቀመጠ። ብፁዕ አባ ሲኖዳም ጌታችንን እንዲህ አለው "ጌታዬ ፈጣሪዬ ልዩ ሦስትነትህንና ጌትነትህን ስለሚነቅፉ ከሀድያን ወደ ጉባኤው እሔድ ዘንድ እንዲጠሩኝ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ እኔ ልኳልና እንደቀድሞው ታጸናኛለህን?"። ጌታችንም በጸጋና በጥዑም ቃል እንዲህ ብሎ መለሰለት "ወዳጄ ሲኖዳ ሆይ ሌላ ዕድሜ ትሻለህን?። እነሆ ዕድሜህ ሁሉ መቶ ሃያ ዓመት ከሁለት ወር ሁኖሃል ዕድሜህ ዘጠኝ ዓመት ሲሆን አስኬማን ለበስኽ ከዚያ በኋላ መቶ ዐሥራ አንድ ዓመት ከሁለት ወር ኖርኽ አሁንስ ድካምህ ይብቃህ" ይህንንም ብሎ ጌታችን በክብር ዐረገ።
💚💛❤ በዚያንም ጊዜም የቅዱሳን አንድነት ማኅበር ወደርሱ መጡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ዳግመኛ አየው ልጆቹንም ክብር ይግባውና "ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ እሰግድ ዘንድ አንሱኝ" አላቸው አንሥተውትም ሰገደለት። ከዚህም በኋላ ዳግመኛ እንዲህ አላቸው "ወደ እግዚአብሔር አደራ አስጠብቅኋችሁ ነፍሴም ከዚህ ከደካማው ሥጋዬ የምትለይበት ጊዜ ደርሷል እኔም ለአባታችሁ ለዊዳ እንድትታዘዙ አዝዛችኋለሁ ከእኔ በኋላ ጠባቂያችሁ እርሱ ነውና" አላቸው።
💚💛❤ ለልጆቹም ይህን በተናገረ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ "የመረጥሁህ ሲኖዳ ሆይ ብፁዕ ነህ ቸርነቴም ይደረግልሃል በሕይወትህ ዘመን ሁሉ አንተ የምወደውን ሥራ ሠርተሃልና እንግዲህ ወደ ዘለዓለም ተድላ ታርፍ ዘንድ ወደእኔ ና" አለው። ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በአባ ሲኖዳ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።