ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
الذهاب إلى القناة على Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
إظهار المزيد637
المشتركون
لا توجد بيانات24 ساعات
-37 أيام
-1230 أيام
أرشيف المشاركات
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፫ (13) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_አባት_ቆቅ ሲመገብ ለነበሩት #ለአባ_መቃርስ ወደ ብሔረ ሕያዋን ለገባበት በዓል፣ በስላሞች ዘመን በሰማዕትነት ለዐረፈ #ለአባ_በጽንፍርዮስና ከላይኛው ግብጽ ለሆነ #ለቅዱስ_አባት_ለአባ_አብራኮስ ለዕረፍታቸው በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦#ቅድስት_ሐና እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸነሰቻት የሚሉ አሉ፣ በደብረ ቀልሞን ከሚኖር ከገዳማዊ #ከአባ_ሚካኤል ዕረፍት፣ #ከሰማዕት_ቅዱስ_አብራቂስ_ከሐርስፎስ፣ #ከመኰንኑ_ቆርኔሌዎስ_ከወርቅጥጶስና_ከአፍሬ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቆቅ_ሲመገብ_የነበረው_አባ_መቃርስ፦ ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ሕያው እግዚአብሔርን መከተል ፈልገ የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት መጻሕፍትንም ተማረ የዚህንም ዓለም ኃላፊነቱን ለጻድቃንም በጎ ዋጋ ለኃጥአን ቅጣት እንዳለም አስተዋለ ስለዚህም ዓለምን ትቶ በአንድ ገዳም ውስጥ መነኰሰ ከዚያም ወጥቶ የዐሥር ቀን ጎዳና ተጓዘና በውስጡ ኲዕንትና ቆቆች ውኃም ካለበት ተራራ ደረሰ። አስቦ እንዲህ አለ "ኵዕንት ወደመልቀም ብሰማራ የስግደቴና የጸሎቴ ሥራ ይቋረጣል ሰብስቦ የሚያስገባልኝ ረዳት የለኝም ብቸኛ ነኝኛ ሥጋ አትብላ ያለውስ የባልንጀራችንን ሥጋ በሐሜት የምንበላውን አይደለምን ሌላ ምግብም እንደሌለኝ ፈጣሪዬ ያውቃል" ብሎ ከዚያችም ዕለት ወዲህ ቆቆችን የሚያጠምድ ሁኖ በየቀኑ አንዳንድ የሚያዙለት ሆነ። እርሳቸውንም እየተመገበ ከዚያ ውኃም እየጠጣ በማመስገን ኖረ በቀንና በሌሊትም በጸሎትና በስግደት በመትጋት ወደ እግዚአብሔርም እየለመነ ብዙ ዘመናት ኖረ የሰውንም ጽምፅ አይሰማም የሰውንም ፊት አያይም ሐሜትንም ሆነ ስድብን በማንም ላይ አብሮ አይነጋገርም ከሰው ጋር ከልሆነ በቀር ሰይጣን አይመጣም ይባላልና።
❤ ከዚህም በኋላ ከቊስጥንጥንያ ከተማ አንድ መነኵሴ ዋሻ እየፈለገ አባ መቃርስ ከአለበት ደርሶ ቆቅን ሲያጠምድ አየው ያን ጊዜ አልታገሠም ግን ወንድሙን በሐሜት እስከሚገድለው ቸኰለ ወደ የቊስጥንጥንያ ከተማ ወደ ሊቀ ጳሳሳቱ ተመልሶ እንዲህ ብሎ ነገረው "እኔ ዋሻ እየፈለግሁ ወደ በረሀ ሔድሁ በዚያም ሥጋ ሊበላ ቆቅን ሲያጠምድ መነኵሴውን አየሁት የሚሠራውን ሲያዩ በአሕዛብ ዘንድ ሊያስነቅፈን ነው" አለው።
❤ ሊቀ ጳጳሳቱም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ነገሩ እውነት እንደሆነ ያውቅ ይረዳ ዘንድ ከዚያ ከነገረው መነኰሴ ጋር ሌላ መነኵሴ ላከ። እነርሱም በጒዞ ላይ በጐዳና ሳሉ ገና ሳይደርሱ አባ መቃርስ እንደልማዱ ወደ ወጥመዱ ሔደ በአንዲት ወጥመድ የተያዙ ሦስት ቆቆችን አገኘ እንዲህም ብሎ አሰበ "ጌታዬ እሊህን የሰጠኝ እኔን ሊፈትነኝ ነውን። ወይስ ከዚች ዕለት በፊት ሆዴ ያልጠገበች ኑራለችን ወይስ ለሌላ ነው እንዳልል በዚህ በረሀ ውስጥ ከሰው ወገን ያየሁት የለም"። እንዲህም እያሰበ ሳለ ከሊቀ ጳጳሳቱ የተላኩት እሊህ መነኰሳት ደረሱ በአያቸው ጊዜ ደስ አለው "ችግረኞነቴን አውቀህ ለአገልጋዩችህ ቅዱሳን ምግባቸውን የሰጠኸኝ አቤቱ አመሰግንሃለሁ" ብሎ ሰገደ። እነርሱ ግን ማዕድ ሠርቶ አዘጋጅቶ እስከአቀረበላቸው ድረስ ይጠቃቀሱበት ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ አቅርቦላቸው "ንሱ አባቶቼ ባርኩና ተመገቡ" አላቸው እርሱም የራሱን ድርሻ ይዞ እስከጨርስ ያለ መነጋገር በጸጥታ ተመገበ። ከዚህም በኋላ ዓይኖቹን ቀና ቢያደርግ እንዳልበሉ አየ "አባቶቼ እንዴት አልበላችሁም" አላቸው "እኛ መንኰሳት ስለሆን ሥጋ አንበላም ትኅርምትም አለን" አሉት እርሱም ተዋቸው አላስገደዳቸውም እነዚያን ያበሰላቸውን ቆቆች አንሥቶ ሦስት ጊዜ እፍ አለባቸው ያን ጊዜም ድነው በረሩ ወደ ቦታቸውም ሔዱ እነዚያ መነኰሳትም ይህን ተአምር አይተው ደነገጡ "የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ በደላችንን ይቅር በለን ብለው" ሰገዱለት እርሱም "የሁላችንንም በደል እግዚአብሔር ይቅር ይበለን" አላቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ አገራቸው ተመልሰው ያዩትን ይህን ድንቅ ተአምር ለሊቀ ጳጳሳቱ ነገሩት እርሱም ሰምቶ አደነቀ ወደ ንጉሡም እንዲህ ብሎ ላከ "በዘመናችን ጻድቅ ሰው መነኰስ ተገኝቷልና አንተም ና ሒደን በረከቱን እንድንቀበል" አለው። ወዲያውኑ ንጉሥ ከሠራዊቱ ጋር ተነሣ ሊቀ ጳጳሳቱም ከካህናቱ ጋር አባ መቃርስ ወዳለበት እነዚያ መነኰሳት እየመሩአቸው ሔዱ ወደርሱም ሲቀርቡ ወደ ብሔረ ሕያዋን ያደርሰው ዘንድ መልአክ አንሥቶ በክንፎቹ ተሽክመው ሲያርግም በአዩ ጊዜ "የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ ባርከን የምንድንበትን አንዲት ቃል ንገረን" ብለው ጮኹ። እርሱም "ከሐሜትና ከነገር ሥራ አንደበታችሁ ይከልከል። ካህን ብዙ ባይማር ትዕቢትና መታጀር ባልመጣበት ነበር መነኵሴም ትኅርምት ባያበዛ ባልተመካም ነበር ርስበርሳችሁ ተፋቀሩ እግዚአብሔርም አድሮባችሁ ይኑር" አላቸው። ይህንንም ብሎ ዐረገ ከዐይናቸውም ተሠወረ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ መቃርስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_በጽንፍርዮስ፦ ይህም የከበረ መነኰስ በምስር አገር በወንዝ ዳር በአለች በሊቀ መላእክት በቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መንኵሶ ታላቅ ተጋድሎን ሲጋደል ኖረ ስቀናች ሃይማኖትም ከእስላሞች መሳፍንት ጋር ተከራከረ የጌታችን ክርስቶስንም መለኮቱን ገለጠላቸው አምላክነቱንም አስረዳቸው ስለዚህም እስላሞች በአፈሩ ጊዜ ተቆጡ ጽኑዕ ሥቃይንም አሠቃዩት ራሱንም በሰይፍ ቆረጡ የሰማዕትነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም አባ በጽንፍርዮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_አብራኮስ፦ ይህም ቅዱስ አባት ከላይኛው ግብጽ ነው። ዕድሜው ሃያ ዓመት ሲሆን መንኵሶ መልካም የሆነ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ። ሰይጣንም ከእርሱ ጋር በመጣላት በተሸነፈና በደከመ ጊዜ በእርሱም ላይ ምንም ምን ማድረግ ባልተቻለው ጊዜ ፊት ለፊት ተገልጦ መጥቶ "እነሆ ከዚህ ዕድሜህ ሌላ ኀምሳ ዓመት ቀረህ" አለው። በዚህም ወደ ስንፍና ሊጥለው ወዶ ነው ሽማግሌውም እንዲህ ብሎ መለሰለት "አሳዘንከኝ እኔ ሌላ መቶ ዓመት እኖር ዘንድ ስለአሰብኩ ቸለል ብያለሁ አንተ እንዳልከው ከሆነ ከቀድሞው እጅግ አብዝቼ እጋደል ዘንድ ይገባኛል"። ከዚህም በኋላ ተጋድሎውንና በገድል መጸመድ አበዛ ሰባ ዓመታትም ከተጋደለ በኋላ በዚያች ዓመት ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ አብራኮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ13 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለመቃርዮስ_ዘተመሥጠ_መልዕልተ። በቅድመ ጉቡአን ይንብብ ዘይብል ቃላተ። እምኢያእመሩ ትዕቢተ ወዘይመስሎ ትምክህተ። እመ ኢያፈድፈደ ካህን ትምህርተ። ወእመ ኢያብዝኀ ካዕበ መነኰስ ትኅርምተ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የታኅሣሥ_13።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፫ (13) ቀን።
❤ እንኳን #ለሊቀ_መላእክት_ለፈታሔ_ማሕፀን_ለቅዱስ_ሩፋኤል ለቅዳሴ ቤቱና ተአምር ላደረገበት ዓመታዊ መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የመላእክት_አለቃ_የከበረ_መልአክ_የቅዱስ_የሩፋኤል_የቅዳሴ_ቤት_ክብርና_ያደረገው_ተአምር፦ ከእስክድርያ ውጭ በደሴት የታነፀች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት፦ ይህም እንዲህ ነው ሀብታም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበር። ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረች በጥቅምት ወር ዐሥራ ስምንት ቀን እንደጻፍን የወርቅ መዝገብ ተገለጠ።
❤ በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላእክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት። ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት። ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና። የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው። ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ስም ጮኹ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው "እግዚአብሔር አዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም"። አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ አልታወከም በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሩፋኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጒሜን 3 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የበዓሉ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ። ከመ ይዕቀቡከ በኵሉ ፍናዊከ። ወበእደሆሙ ያነሥኡከ"። መዝ 90፥10-11 ወይም 36፥4 የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 16፥16-25 ወይም ማቴ 10፥26-34።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለጌታችን_ለአምላካች_ለመድኃኒታችን #ለኢየሱስ_ክርስቶስ ለንዑስ በዓል ለአንዱ #ለስብከት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በፍቅር አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፪ "#ወልዶ_መድኅነ_ንሰብክ ዘእምቅድመ ዓለም ሀሎ፣ አዝ፤ #አክሊለ_ሰማዕት_ሠያሜ_ካህናት ወተስፋ መነኰሳት #ወልዶ_መድኅነ_ንሰብክ ወልዶ መድኅነ ንሰብከ"። ትርጉም፦ ቅድመ ዓለም በክብር በጌትነት የነበረ ዛሬም ያለ ወደ ፊትም ዓለምን አሳልፎ የሚኖር #መድኃኒት_ልጁን_እንሰብካለን እርሱም #የሰማዕታት_ዘውድ_ነው_የካህናት_ሿሚ_ነው፣ የመነኰሳት ተስፋ ነው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው።
✝ ✝ ✝
❤ #ስብከት፦ ይህች ዕለት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት "ስብከት" ትባላለች:: ስብከት ማለት በቁሙ "የምስራች አዲስ ዜና መንገርን" የሚመለከት ሲሆን ዋናው ምሥጢር ግን ከነገረ ድኅነት (ከመዳን ትምሕርት) ጋር የተገናኘ ነው።
❤ በዚህ ዕለት (ሳምንት) ሁሉም ነቢያት ከነ ትንቢታቸው ይታሰባሉ። ዘመነ ስብከትም ከታኅሣሥ 7 እስከ 13 ያለውን ይይዛል። በእነዚህ ቀናት ውስጥ በአንዱ እሑድ በሚውለበት ቀን ማኅሌት ተቁሞ ስብከት ተብሎ ይከበራል።
❤ ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሀብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ። በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ፤ በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት። በኋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው።
❤ ከዚህ በኋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር። ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር፤ ሱባኤ ይቆጠር፤ ምሳሌም ይመሰል ገባ።
❤ ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ። ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል። ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት/ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል።
❤ ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም፤ በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል። እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል። መድኅን ክርስቶስም ተወልዶ አድኗቸዋል::
❤ ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር)፤ መጻዕያትን (ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው። ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው በጸጋ ይሰጠዋል። እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ።
❤ ዘመነ ነቢያት ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም። በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ። (የሐዋ ሥራ 11፥27) ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ፣ ይገስጻሉ።
ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል::
"እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር፤ ወተናጸሩ ገጸ በገጽ፤ መንፈስን ንጹሕ በማድረግ ነቢያት እግዚአብሔር አይተውታልና ፊት ለፊት ተያይተዋልና"። እንዳለ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም።
❤ የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ፤ አንዳንዶቹም በእሳት፣ አንዳንዶቹም በሰይፍ፣ አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል። ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል።
❤ ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል:: ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ፤ እናንተ በድካማቸው ገባችሁ" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል። ዮሐ. 4፥36
❤ ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል፣ ሽተዋልም። "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ" እንዳለ ጌታ በወንጌል። (ማቴ. 13፥16፣ 1ኛ ጴጥ 1፥10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው፤ ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ።
ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት 15ቱ አበው ነቢያት፣ 4ቱ ዐበይት ነቢያት፣ 12ቱ ደቂቀ ነቢያትና ካልአን ነቢያት ተብለው በ4 ይከፈላሉ።
❤ "15ቱ አበው ነቢያት" ማለት፦
1 ቅዱስ አዳም አባታችን
2 ቅዱስ ሴት
3 ቅዱስ ሔኖስ
4 ቅዱስ ቃይናን
5 ቅዱስ መላልኤል
6 ቅዱሴ ያሬድ
7 ቅዱስ ኄኖክ
8 ቅዱስ ማቱሳላ
9 ቅዱስ ላሜሕ
10 ቅዱስ ኖኅ
11 ቅዱስ አብርሃም
12 ቅዱስ ይስሐቅ
13 ቅዱስ ያዕቆብ
14 ቅዱስ ሙሴና
15 ሳሙኤል ናቸው።
✝ "4ቱ ዐበይት ነቢያት"
1 ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል
2 ቅዱስ ኤርምያስ
3 ቅዱስ ሕዝቅኤልና
4 ቅዱስ ዳንኤል ናቸው።
❤ "12ቱ ደቂቀ ነቢያት"
1 ቅዱስ ሆሴዕ
2 ቅዱስ አሞጽ
3 ቅዱስ ሚክያስ
4 ቅዱሴ ዮናስ
5 ቅዱስ ናሆም
6 ቅዱስ አብድዩ
7 ቅዱስ ሶፎንያስ
8 ቅዱስ ሐጌ
9 ቅዱስ ኢዩኤል
10 ቅዱስ ዕንባቆም
11 ቅዱስ ዘካርያስ
12 ቅዱስ ሚልክያስ ናቸው።
❤ "ካልአን ነቢያት" ደግሞ፦
1 ቅዱስ ኢያሱ
2 ቅዱስ ሶምሶን
3 ቅዱስ ዮፍታሔ
4 ቅዱስ ጌዴዎን
5 ቅዱስ ዳዊት
6 ቅዱስ ሰሎሞን
7 ቅዱስ ኤልያስ
8 ኤልሳዕ ሌሎችም ናቸው።
❤ ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ፦
1 የይሁዳ (ኢየሩሳሌም)
2 የሰማርያ (እሥራኤል)
3 የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ።
❤ በዘመን አከፋፈል ደግሞ፦
1 ከቅዱስ አዳም እስከ ቅዱስ ዮሴፍ (የዘመነ አበው ነቢያት)።
2 ከሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴ እስከ ነቢዩ ቅዱስ ሳሙኤል (የዘመነ መሳፍንት ነቢያት)።
3 ከቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ዘሩባቤል ያሉት (የዘመነ ነገሥት ነቢያት)።
4 ከቅዱስ ዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ (የዘመነ ካህናት ነቢያት) ይባላሉ። ምንጭ፦ ከዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ ፔጅ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ፈኑ እዴከ እምአርያም። አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ። ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ ነኪር"። መዝ 143፥7። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 1፥1-ፍ.ም፣ 2ኛ ጴጥ 3፥1-10 እና የሐዋ ሥራ 3፥17-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 1፥44-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ነው። መልካም የስብከት በዓልና የነቢያት (የገና) ጾም ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ እርሱ ግን ከክፋ ሐሳቡ ተመልሶ ትምርታቸን አልተቀበለም። አውግዘውም ከምእመናን ለዩት በትምህርቱ የሚያምኑትንም ሁሉ ለዩአቸው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ12 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ጻድቅሰ ከመ በቀልት ይፈሪ። ወይበዝኅ ከመ ዘግባ ዘሊባኖስ። ትኩላ እሙንቱ ውስተ ቤተ እግዚአብሔር"። መዝ91፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 6፥6፥19-ፍ.ም።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፪ (12) ቀን።
❤ እንኳን #ለመላእክት_አለቃ_ለቅዱስ_ሚካኤል ለወራዊው በዓል መታሰቢያና ከሃዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ሰማዕትነት ለተቀበሉ #ለቅዱሳን_ለአንቂጦስና_ለፎጢኖስ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ ሰላምና በጤና አደረሰን። በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከአባ_ነድራ፣ ከደብረ እስዋን ከታማኙም #ከቅዱስ_ዮሐንስ ከመታሰቢያቸው፣ ስለ ቀሲስ ብናጥስ በሮሜ አገር ከተሰበሰብ ከኤጲስ ቆጶሳት፣ ከቀሳውስትና ከዲያቆናት፣ ከዕረፍታቸው፣ #ከቅዱሳን_ሰማዕት_ከአውሲስና_ከእንጦንዮስ፣ ከሮሜው #ከአባ_መሐር ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #በዚች_ቀን_የመላእክት_አለቃ_የቅዱስ_ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚች ቀን በዚህ ወር እግዚአብሔር ወደባቢሎን አገር ላከው የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ሦስቱን ልጆች አናንያን አዛርያንና ሚሳኤልን ከእሳት ማንደጃ ውስጥ በጣላቸው ጊዜ አራተኛ ገጽ ሁኖ ታየ። የእሳቱም ነበልባል አርባ ዘጠኝ ክንድ ያህል ወላይ ከፍ ከፍ አለ የጨመሩአቸውን ሰዎችና እሳት የሚያንዱትን አቃጠላቸው ይህም የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል የእሳቱን ነበልባል በበትሩ መትቶ ከሠለስቱ ደቂቅ ላይ አጥፍቶ አዳናቸው ምንም አልነካቸውም እንደ ቀዘቀዘ እንደ ጧት ጤዛ አድርጎታልና።
❤ በዚያንም ጊዜ የአባቶቻችን ፈጣሪ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እያሉ ስድስት ቃላትን ተናገሩ በዚህም ከስድስት መቶ ዓመት በኋላ ክርስቶስ እንደሚወለድ ትንቢት ተናገሩ። ከዚህም በኋላ የጌታ እግዚአብሔር ሥራዎቹ ሁሉ ያመሰግኑታል እርሱ ለዘላለሙ ምስጉን ልዑልም ነው እያሉ ሠላሳ ሦስት ጊዜ አመሰገኑት በዚህም በምድር ላይ ሠላሳ ሦስት ዓመት ክርስቶስ እንደሚኖር አመለከቱ።
❤ ስለዚህም አባቶቻችን የቤተ ክርስቲያን መምህራን የመላእክት አለቃ የሆነ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ እንድናደርግ ሥዓትን ሠሩ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_ሰማዕታት_አንቂጦስና_ፎጢኖስ፦ ይህም ሰማዕት አንቂጦስ ንጉሡ ምእመናንን ያሥራቸው ዘንድ አሠርቶ በፊቱ ያኖራቸውን የሥቃይ መሣሪያዎች በአየ ጊዜ በቆራጥነት ከሕዝብ መካከል ተነሥቶ ንጉሡን ተከራከረው ንጉሡም አሥረው ወደ ጨዋታ ማያ ቦታ አውጥተው ክፉውን አንበሳ እንዲለቁበት አዘዘ። አንበሳውም ወደርሱ በደረሰ ጊዜ እጁን ዘርግቶ ፊቱንና ጒንጩን አሻሽቶ ተወው ንጉሡም ከይቶ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ወታደሩም ሰይፉን በመዘዘ ጊዜ ተንቀጠቀጠ መንቀሳቀስም ተሳነው ሁለተኛም ሰውነቱ ፈጥና እንደትቆራረጥ ከበታቹ የእሳት ፍም ወደተነሠነሠበትና ቆራርጦ የሚለያይ መሣሪያ ወዳለው መንኰራኵር ውስጥ እንዲጨምሩት አዘዘ እግዚአብሔርም ከዚህ አድኖት ያለ ጉዳት በጤና አስነሣው።
❤ ዳግመኛም በውስጧ እርሳስ ወደአፈሉባት ጋን ውስጥ እንዲጨምሩት አዘዘ ሕዝቡም እያዩ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ከጋኑ ውስጥ ነጥቆ በዲዮቅልጥያኖስ ፊት አቆመው ፎጢኖስም ይህን ድንቅ ተአምር በአየ ጊዜ ልብሱን ጥሎ ተነሥቶ ወንድሙን አንቂጦስን ሳመው። "ከዳተኛውንም ንጉሥ አንተ ጐስቋላ ወንድሜን እንዴት ታሸንፈዋለህ" ብሎ ረገመው ዲዮቅልጥያኖስም ሰምቶ በአንገታቸው ዛንጅር በእግሮቻቸው እግር ብረት አግብተው ወደ ወህኒ ቤት እንዲጨምሩአቸው አዘዘ።
❤ ከዚህም በኋላ ሥጋቸው ሁሉ ይበታተን ዘነድ ጥፍር በአለው ብረት እንዲሰነጣጥቋቸው አዘዘ ዳግመኛም ወደ ጨዋታ መስክ ወስደው በድንጋይ ይወግሩአቸው ዘንድ አዘዘ። ምንም ምን የነካቸው የለም ዳግመኛም በብዛት ገርፈው በቊስላቸው ውስጥ ጨው ጨመሩ ሦስት ቀንም ወደ አንደዱበት የውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥ ጨመሩአቸው እርሱም እንደ ቀዘቀዘ ጠል ሆነላቸው የውሽባ ቤቱንም በከፈቱት ጊዜ የእግዚአብሔርን ገናናነት ሲነጋገሩ አገኙአቸው።
❤ ከዳተኛው ንጉሥም በአየ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ነበልባሉም ከፍ ከፍ እስከሚል በማንደጃው ውስጥ እሳትን አንድደው ቅዱሳኑን ወደዚያ ይጥሏቸው ዘንድ አዘዘ በውስጡም ቁመው ረጅም ጸሎትን አደረጉ አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ፊታቸውን አማተቡ ነፍሳቸውንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ። ሥጋቸውም ከቀኑ ሁለት ሰዓት ጀምሮ እስከ ሌሊቱ ስድስት ሰዓት ድረስ በእሳቱ ፍም ላይ ነበር የነካው ነገር የለም የራሳቸው ጠጒር እንኳን አልተቃጠለም ምእመናንም ሥጋቸውን በሌሊት ወሰዱ ለክብራቸውም እንደሚገባ ገንዘው በመልካም ቦታ ቀበሩአቸው። ከእሳቸውም አስደናቂዎች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አንቂጦስና ፎጢኖስ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የቅዱሳን_ኤጲስቆጶሳት_የቀሳውስትና_የዲያቆናት የአንድነት ስብሰባ በሮሜ ከተማ፦ ይህም የሆነው ከሀዲው ዳኬዎስ በነገሠ በመጀመሪያው ዓመት በሮሜው ሊቀ ጳጳሳት በቆርኔሌዎስ የሹመት ዘመን በእስክድርያ ሊቀ ጳጳሳት በዲዮናስዮስ ዘመን በላንድዮስም በአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ሁኖ ሳለ ግርማኖስም በኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ሁኖ ሳለ ነው። ይህም የሆነበት ምክንያት በስደት ጊዜ የካደ ቢኖር ወይም በዝሙት የወደቀ ወይም በየአይነቱ በሆነ ኃጢአት ቢሰናከል በንስሐ ሊቀበሉት አይገባም በማለቱ ስለ ቀሲስ ብናጥስ ነው።
❤ አባት ቆርኔሌዎስ ስለዚህ አንድ ጊዜ ዳግመኛም ሦስተኛም ጊዜ ገሠጸው መከረውም ግን አልሰማውም ስለዚህም ስልሳ ኤጲስቆጶሳትን መጻሕፍትን የተማሩ ዐሥራ ስምት ቀሳውስትና አርባ ዲያቆናትን በርሱ ላይ ሰበሰበ። እርሱም ስለዚህ ነገር ብናጥስ ቀሲስን ተከራከሩት ቀስሲ ብናጥስም ምክንያት አድርጎ የተነሣው ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን ሰዎች በስድስተኛው ምዕራፍ "ጥምቀትን ከተቀበሉ በኋላ ከሰማይ የሚሰጥ ጸጋውን ከቀመሱ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ አንድ ከሆኑ በኋላ አይቻልም። መልካሙንም የእግዚአብሔርን ቃልና በኋላ የሚመጣውን የዓለምን ኃይል ከዐወቁ በኋላ ንስሓቸውን ሊአድሷት የእግዚአብሔርን ልጅ ሊሰቅሉላቸው ሊዋርዱላቸው ዳግመኛ ሊወድቁ አይገባም" ያለውን ኃይለ ቃል ምክንያት አድርጎ ነው።
❤ እሊህ አባቶችም እንዲህ ብለው መለሱለት "ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ንስሓ ስለማገባ ሰው ይህን አላለም በኃጢአት በወደቀ ጊዜ በየጊዜው የክርስትና ጥምቀትን ስለሚጠመቅ ነው እንጂ ስለዚህም ሐዋርያው እንዲህ የሚለውን ቃል አስከተለ ዳግመኛ የእግዚአብሔርን ልጅ ሊሰቀሉላቸው ሊያዋርዱላቸው ይገባልን? መከራ መስቀሉ አንድ ጊዜ ብቻ ናትና ንስሓ ግን በሁሉ ጊዜ ትገኛለች። አንተ እንደምትለው ከሆነ በኃጢአት የወደቀ ዳዊትን ጌታችንን ክዶት የነበረ ጴጥሮስን ንስሓ አልተቀበለምን? አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ሀብት አልሰጠውምን? በምእመናንስ ላይ በከንቱ ሾመውን? በእጁ የሠራው ሁሉ የተጠመቀውም የጠፋ ነውን? አንተ እንደምትለው ይህ ስንፍናና ድንቁርና ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን ግን ሃይማኖቱን ለካደ ወይም በኃጢአት ለወደቀ ለሁሉም ንስሓን ሠርቷል "ብናጥስ ሆይ ከዚህ ከረከሰና ከከፋ ምክርህ ተመልሰህ ንስሓ ግባ ለእግዚአብሔርም ለራስህና ለሰውም ሁሉ ጠላት አትሁን"።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፪ (12) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያኑ_ጻድቃን ታላቁ ዋልድባ ገዳምን ላቀኑ ምድራን እንደ መሶበ ወርቅ ከፍ አድርገው ላስባረከ አራዊተ እንስሳ ለሚታዘዝላቸው አንበሳን እንደ ፈረስ ሲያገለግላቸው ለነበረ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ_ለዕረፍት_በዓል፣ #ለዳግማዊ_ቂርቆስ_ለቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ_ልጅ ብሔረ ብፁዓን ለገባበት መታሰቢያ ቀንና ከአጽማቸው ጠበል ላፈለቁት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ቶማስ ለዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ፦ ለዚህም ቅዱስ የአባ ስም እስጢፋኖስ የእናቱ ስም አመተ ማርያም ነው። እነርሱም በዘመድ የከበሩ ደጎች ናቸው በአክሱም6 ምድርም ወለዱት በአደገ ጊዜም የቤተ ክርስቲያንን መጸሐፍት አስተማሩት አባቱና እናቱም በሞቱ ጊዜ ወደ ደብረ በንኰል ገዳም ወደ አባ መድኃኒነ እግዚእ ሒዶ የምንኵስና ልብስን ለብሶ በጾምና በጸሎት እየተጋደለ ኖረ። ፈጽሞ ከሻገተ ጎመን በቀር አይበላም የሚጠጣውም ውኃ ነው እህል በመፍጨትና ውኃ በቅዳት ሥራ መነኰሳትን ይረዳቸው ነበር።
❤ ዘመዶቹም ወደርሱ እየመጡ በአስቸገሩት ጊዜ ወደሌላ ቦታ ሔደ እግሮቹም እስቲያብጡ ድረስ በጾም በስግደት በመቆም ተጋደለ ከዚያም ወደሌላ በረሀ ሒዶ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት ምንም ምን ሳይቀምስ ኖረ አንበሶችና ነብሮች የሚያስፈሩም አራዊት ሁሉ ወደርሱ በመምጣት ይሰግዱለታል የእግሮቹን ትቢያ ይልሱ ነበር። በአንዲት ዕለትም በጐዳና ሲጓዝ ታላቅ ወንዝን ውኃው መልቶ አገኘ መጽሐፍና እሳትም ከእርሱ ጋር ነበር ጸሎትንም አድርጎ ወደ ውኃው ገባ ውኃውም ዋጠውና ወደታች አወረደው በእግዚአብሔርም ኃይል ወደማዶ በጣለው ጊዜ መጽሐፉ ሳይደመሰስ እሳቱም ሳይጠፋ አገኘው።
❤ ሰይጣንም በሚያስፈራ አራዊት እየተመሰለ ይፈታተነው ነበር እርሱ ግን ፈጣሪውን በመታመን ልቡ የታሠረና የጸና ስለሆነ አይፈራም። እርሱም ሲጸልይ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ መጣ በምራቁም መላ ሕዋሳቱን ቀብቶ ኃይልን አሳደረበት ከዚያችም ዕለት ጀምሮ እግሮቹን የሚያሥር ሆነ። ማቅንም ለብሶ በየሌሊቱ ሁሉ ከውኃ ውስጥ በመግባት የዳዊትን መዝሙር አምስት ጊዜ ያደርሳል ቊጥር በሌለውም ግርፋት ጀርባውን ይገርፍ ነበር።
❤ አንበሶችም በበዓቱ አጠገቡ ይሰማራሉ እርሱም አካላቸውን ይሰፍራል ይለካል ቊስላቸውንም በጥቶ እሾህና አሜከላ ያወጣላቸዋል። ከዚህም በኋላ ብዙ ደቀ መዛሙርት ወደርሱ ተሰበሰቡ በተጋድሎም ተጠመዱ ከእርሳቸውም የመጀመሪያው አባ ዘሩፋኤል ነው። በአንዲትም ዕለት በገዳመ ለጋስ የሚኖር ከአባ ገብረ መስቀል ጋር ተገናኘ ከዚህም በፊት አልተያዩም ነበር የእግዚአብሔርንም ገናናነት ሲጨዋወቱ ዋሉ በራት ጊዜም ጸሎትን ሲያደርጉ የተዘጋጀ ማዕድ ወርዶላቸው ተመግበው እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
❤ ከዚህም በኋላ በአንዲት ዕለት ከአንድ ገዳማዊ ጋር ተገናኘ እግዚአብሔርም ያደረገላቸውን ምሥጢር በሚነጋገሩ ጊዜ አባታችን አባ ሳሙኤል እንዲህ አለ "እንሆ እኔ በአርያም ቁሜ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የአምላክን መንበር ሳጥን ዐሥራ ሁለት ዓመት ሆነኝ"። ለመቀደስም በሚገባ ጊዜ ኅብስትና ወይንን የተመላ ጽዋ ይወርድለታል። የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ውዳሴዋን ሲያነብ ክንድ ያህል ከምድር ወደ ላይ ከፍ ከፍ ይላል እመቤታችን ማርያምም ወደ ርሱ መጥታ የሚያበራ ዕንቊንና ንጹሕ ዕጣንን ሰጠችው።
❤ ፍልሰቱም ሲቀርብ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በክንፎቹ ተሸክሞ አወጣው ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን ተድላዋን ሁሉ አሳየው ወደ ልዑል እግዚአብሔርም ዙፋን ፊት አቅርቦት ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውንም ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ተቀበለ ወደ በዓቱም ሲመለስ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው ከዚህም በኋላ ታኅሣሥ12 ቀን በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ሳሙኤል ጸሎት ይማረን በረከቱ ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ12 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #ዳግማዊ_ቂርቆስ_ዘብሔረ_ቡልጋ፡- የታላቋ እናት የቅድስት ክርስቶ ሠምራ የመጨረሻ ልጇ ነው። አባቱ ሠምረ ጊዮርስ የተባለ ጻድቅ ጻድቅ ሲሆን እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ዐሥራ አንድ ልጆችን ወልዳ በትዳሯ እጅግ የተመሰገነች ሆና ትኖር ነበር።
❤ ከዕለታት አንድ ቀን እንዲህ ሆነ ብፅዕት ቅድስት እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ከአገልጋዮቿ መካከል አንዷ ምግባሯ የከፋ ነበርና በጣም ስላበሳጨቻት በዚያች አገልጋይ አፍ ውስጥ የእሳት ትንታግ ጨመረችባት፡፡ ያም የእሳት ትንታግ እስከ ጉሮሮዋ ዘለቀና አገልጋይዋን ገደላት፡፡ በዚህ ጊዜ ብጽዕት ክርስቶስ ሠምራ ደንግጣ ወደ ሌላ ክፍል ገባችና ኃጢአቷን ለእግዚአብሔር እየተናዘዘች እጅግ በጣም አዝና ጥፋቷ እንደ ጸጸታትና እግዚአብሔር አምላክም በእጇ የሞተችውን አገልጋይዋን ከሥጋዋ አዋሕዶ ቢያሥነሳላት ያላትን ገንዘብና ሀብት ትታ ባላት ዘመኗ ሁሉ አገልጋዩ እንደምትሆን ብጽዓት (ስዕለት) አደረገች፡፡ እግዚአብሔርም ጸሎቷን ሰምቶ አገልጋይዋን ከሞት አሥነሳለት፡፡ እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ "ልመናዬን ቸል ያላለ ቸርነቱንም ከእኔ ከባሪያው ያላራቀ አምላክ ይክበር ይመስገን" ብላ በታላቅ ምስጋና እግዚአብሔርን ካመሰገነች በኋላ አስቀድማ የገባችውን ቃል አስባ ልብሰ ምንኩስናዋን አዘጋጀች፡፡ ሕፃን ልጅዋንም ይዛ ወደ ደብረ ሊባኖስ ሄደች፡፡ ስትሄድም በልስላሴና በእንክብካቤ የኖረ እግሯ ከመንገዱ ብዛት ከእንቅፋቱም የተነሳ ፈለግ ሲያወጣ ሥጋውን እየቆረጠች ስትጥለው ደሟ መሬት ለመሬት እየፈሰሰ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ደረሰችና አስቀድማ ያዘጋጀችውን ልብሰ ምንኩስናዋን ለብሳ ከሴቶች ገዳም ገባች፡፡
❤ ቅድስት እናታችን ይዛው የተሰደደችውን የ3 ዓመቱ ሕፃን ግን ወንድ ስለሆነ ከደጅ ላይ አስቀምጣው ስለገባች ሕፃኑ አምርሮ አለቀሰ፡፡ በዚህም ጊዜ ከመነኮሳይያቱ አንዲቷ "ሕፃኑ ሲያለቅስ ከሚያድር" ብላ ወደ በአዓቷ ልታስገባው ስትል የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ሕፃኑን ነጥቆ ወስዶ በገነት አስቀመጠው፡፡ እርሱም ታኅሣሥ 29 ቀን ተወልዶ በ3 ዓመቱ ታኅሣሥ 12 ቀን ብሔረ ብፁዓን ገብቷል፡፡ እጅግ አሳዛኝ ገድሉ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ይገኛል፡፡ ምንጭ፦ ገድለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራና መዝገበ ቅዱሳን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለከ_ዘፈረይከ_ሕገ። #ሳሙኤል_ዘኮንከ ለአስካለ ወይን ሐረገ። በረድኤትከ ክፍለኒ ወእደ ሀሎከ ዐሪገ። ረድኤትከሰ ወለተ ከለባት መዘገ። ምስለ ክቡራን ከመ ተሀሉ ደርገ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የታኅሣሥ_12።
ጨካኝና ኃይለኝ ነው" እያለ መከራቸው፡፡ እግዚአብሔርንም ይህን የሚናገራቸው ሰይጣን መሆኑን ገለጸላቸውና "አንተ የሐሰት አባት ሁልጊዜ የእግዚአብሔርን ሀሳብ ትቃረናለህ" ብለው በገሠጹት ጊዜ መልኩን ለውጦ ጥቁር ባሪያ ሆነ፡፡ "እነሆ ከንጉሡ ጋር አጣልቼ ደማችሁን እንዲፈስ አደርገዋለሁ" ብሎ ወደ ከሃዲው ንጉሥ ወደ ዲዮቅልጥያኖስ ዘንድ ሄዶ "ፊቅጦርንና ገላውዴዎስን ካልገደልካቸው በአንተ ላይ ይነሱብሃል፣ አንተንም ገድለው መንግሥትህን ይወስዳሉ፣ እነርሱም የመንግሥት ልጆች መሆናቸውን ዕወቅ" አለው፡፡
❤ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም ቅዱስ ገላውዴዎስን አስጠርቶ የአባቱን ሹመት እንደሚሾመው ቃል ከገባለት በኋላ ለጣዖቱ እንዲሠዋ አዘዘው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስ ግን በድፍረት ጣዖቱንና ንጉሡን ሰደባቸው፡፡ የቅዱስ ፊቅጦር አባት ኅርማኖስ የተባለው ባለሟሉ "እንደ ልጄ ፊቅጦር ዐመፀኛ ነውና ወደ እስክንድርያ ልከነው በዚያ እንዲገድሉት እናድርግ" ብሎ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስን መከረው፡፡ አሠቃይተው እንዲገድሉትም ከደብዳቤ ጋር አድርገው ወደ እንዴናው ሀገር ዥ ወደ ጨካኙ አርያኖስ ላኩት፡፡
❤ አርያኖስም ቅዱስ ገላውዴዎስን ባየው ጊዜ ደንግጦ በክብር ተቀበለው፡፡ እጅ ነሥቶም ከሳመው በኋላ "ጌታዬ ስለምን የንጉሡን ትእዛዝ ትተላለፋለህ?" እያለ መከረው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስም "ንጉሡ ያዘዘህን ትእዛዝ ልትፈጽም እንጂ በነገርህ ልታስተኝ አልተላኩም" አለው፡፡ መኰንኑም እስኪቆጣ ድረስ ብዙ ጊዜ እያባበለው ተነጋገሩ፡፡ ከዚህም በኋላ አርያኖስ እጅግ ተቆጣና በያዘው ጦር ወግቶ ቅዱሱን ገደለው፡፡ ቅዱስ ገላውዴዎስም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ፡፡ ምእመናንም የመከራው ዘመን እስኪፈጸም ቅዱስ ሥጋውን ወስደው ከቅዱስ ፊቅጦር ጋር በሣጥን አኖሩት፡፡ የቅዱስ ፊቅጦርም እናት ቅድስት ሶፍያ ወደ እንዴና ሀገር መጥታ የሁለቱን ቅዱሳን ሥጋቸውን ወደ አንጾኪያ ወስዳ በክብር አኖረችው፡፡
❤ የዚህ ታላቅ ሰማዕት የቅዱስ ገላውዴዎስ ገዳም በሀገራችን የሰሜኑ ክፍል ከባሕርዳርና ወደ ጎንደር በሚወስደው መንገድ ላይ ይገኛል፡፡ ገዳሙን ለየት የሚያደርገው ነገር በገዳሙ ክልል ውስጥ የተቀበረ ሰው አስክሬኑ በቀጣዩ ቀን ይሰወራል፡፡ ወደየት እንደሚሄድም አይታወቅም፡፡ ማንኛውም አስክሬን በተቀበረ በማግሥቱ በቦታው ላይ ፈጽሞ አይገኝም፡፡ ይህ አሁንም ድረስ በግልጽ የሚታይ ነው፡፡ ከሰማዕቱ ከቅዱስ ገላውዴዎስ ረድኤት በረከትን ያሳትፈን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡ ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳንና የሰኔ 11 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይነግሩኑ እለ ውስተ መቃብር ሣህለከ። ወጽድቀከኒ ውስተ ሞትኑ። ይትዐወቅኑ ውስተ ጽልመት መንክር"። መዝ 87፥11-12። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 12፥9፣ 1ኛ ጴጥ 4፥6-12 እና የሐዋ ሥራ 17፥28-ፍ.ም። የሚበበው ወንጌል ማቴ 6፥7-17። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ገላውዴዎስ የልደት በዓልና የነቢያት የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲፩ (11) ቀን።
❤ እንኳን #ለየግብጽ_ደቡብ_ከሆነ_ከመጺል አውራጃ ከሬስ ከተማ ሰዎች ወገን ለሆነ በሌሊት እንዲሁም በቀን ሁለት ሺህ አራት መቶ ጊዜ አቡነ ዘበሰማያ ይጸልይ ለነበረ #ለቅዱስ_አባ_በኪሞስ ለዕረፍት በዓልና በጦርነት ድል አድራጊው ከቤተ መንግሥት ወገን ለሆነ #በንፅህናው_የመላእክት አርአያ ላለው ለተባለ ለከበረ ለሰማዕት #ለቅዱስ_ለገላውዴዎስ_ለልደት በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከኤጲስ ቆጶስ #አባ_በርተሎሜዎስና_ከሰማዕቱ_ከቅዱስ_በጥላን እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_በኪሞስ፦ ይኸውም ቅዱስ አባት የግብጽ ደቡብ ከሆነ ከመጺል አውራጃ ከሬስ ከተማ ሰዎች ወገን የሆነ ነው፡፡ እርሱም የአባቱን በጎች የሚጠብቅ ነበር፡፡ ዕድሜውም ዐሥራ ሁለት ዓመት በሆነው ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ በጐልማሳ አምሳል ተገለጠለትና "በአንድነት ሄደን እንመነኩስ ዘንድ ትሻለህ?" አለው፡፡ እርሱም "አዎን አለ" ሁሉቱም ተስማምተው አብረው ወደ አስቄጥስ ገዳመ ተጓዙ ሦስት አረጋውያን መነኰሳት አገኙ አባ በኪሞስ ከእነርሱ ጋር ሃያ አራት ዓመታትን ኖረ፡፡
❤ ከዚህም በኋላ አባ በኪሞስ ከዚያ ተነሥቶ የሦስት ቀን ጎዳና ያህል ተጓዘና ሩቅ ወደሆነ በረሀ ውስጥ ገባ ሰይጣናትም በእሪያዎችና በዘንዶዎች አምሳል ሆነው መጡበት፡፡ ሊነክሱትም አፋቸውን ከፍተው ከበቡት እርሱ ግን የአጋንንት ሐሳብ ዐውቆ በእግዚብሔር ኃይል እፍ አለባቸው በዚያን ጊዜ ተበተኑ፡፡ እርሱም ወንዝ አግኝቶ ሰባት ሰባት ቀን እየጾመ በዚያ ሦስት ዓመት ኖረ፡፡ በሱባኤው መጨረሻ በመሀል በእጁ ተምር ያንን ይመገባል ውኃም በጥቂቱ ይጠጣል። በሌሊት ሁለት ሺህ አራት መቶ ጊዜ በቀንም እንዲሁ ሁለት ሺህ አራት መቶ ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን ይጸልያል፡፡
❤ ከዚህም በኋላ አርባ አባር ቀን እየጾመ ሃያ አራት ዓመታት ያህል ኖረ፡፡ አርባውም ቀን ሲፈጸም አንድ ጊዜ ይመገባል፡፡ ከዚህም በኋላ ቆዳው ከዐንጥንቱ ጋር እስኪጣበቅ ሰማንያ ቀን ጾመ፡፡ በዚህም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ይበላና ይጠጣ ዘንድ እንጀራና ውኃን አመጣለት ያም ውኃና እንጀራ ሳያልቅ እስከ አረፈ ድረስ ብዙ ዓመታት ሲመገበው ኖረ፡፡ ፈጣሪ እግዚአብሔር በሌሊት ራእይ ተገልጦ ወደ አገሩ እንዲመለስ አዘዘው፡፡ እርሱም ወደ ሀገሩ ተመልሶ በዚያች ትንሽ በዓት አበጅቶ መኖር ሲጅር ብዙዎች ወደ እርሱ መጥተው ፈውስን የሚያገኙ ሆኑ፡፡ እርሱም ጣዕም ባለው አንደበቱ ወንጌልን እያስተማራቸው ድውያንንም ሁሉ የሚፈውሳቸው ሆነ፡፡
❤ በአንዲት ዕለትም የታዘዘ መልአክ መጥቶ አባ በኪሞስን ነጥቆ ወስዶ ወደ ኤፍራጥስ ምድር አደረሰው፡፡ የዚያች አገር ሰዎች ሕግን በመተላለፍ ከእውነተኛ ሃይማኖት ወጥተው ነበርና፡፡ አባ በኪሞስም አስተምሮ ወደ ቀናች ሃይማኖትና ወደ በጎ ምግባር መለሳቸውና ወደ ሀገሩ ተመለሰ፡፡ በአንዲት ዕለትም ሸጦ የዕለት ምግቡን ያገኝ ዘንድ አገልግሎችን ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲሄድ በጎዳና ላይ ደክሞት አገልግሎቹን አስቀምጦ ያርፍ ዘንድ ተቀመጠ፡፡ ወዲያውም ከአገልግሎቹ ጋር የእግዚአብሔር ኃይል ተሸክሞ ወስዶ ከሚሸጥበት ቦታ አደረሰው፡፡
❤ በዚያንም ወቅት አባ ሲኖዳ ከፍተኛ የዕንቁ ባሕርይ ምሰሶ በራእይ አየና "ይህ ታላቅ ግሩም የሆነ ምሰሶ ምንድነው?" ብሎ ደነገጠ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና "ይህ አባ በኪሞስ ነው" አለው፡፡ አባ ሲኖዳም አባ በኪሞስን ያገኘው ዘንድ ወደ እርሱ አገር በእግሩ ተጓዘ፡፡ ከዚያችም ቀን በፊት ከቶ አላየውም ነበር፡፡ ሄዶም ባገኘው ጊዜ ሁለቱ ቅዱሳን ሰላምታ ተሰጣጡ። አባ በኪሞስም ወጥ ሊአበስል ወደደ አባ ሲኖዳንም "ይቺን እንስራ ያዛትና ሔደህ ውኃ ቀድተህ መልተህ አምጣልኝ" አለው። በዚያንም ጊዜ አባ ሲኖዳ ተነሣና ያቺን እንስራ ተሸክማት ውኃውንም ቀድቶ መልቶ አመጣለት ወጡንም ፈልቶና በስሎ አገኘው በዚያንም ጊዜ አባ በኪሞስ መሆኑን አወቀ ከእርሱም ጋር ሰላምታን ደገመ እጅ በመነሣሣትም ሰላምታ ተለዋወጡ። ከዚህም በኋላ ሲኖዳ ስለርሱ ያየውን ራእይ ነገረው በእርሱም ዘንድ ጥቂት ቀኖች ኖረ።
❤ ዳግመኛም በአንዲት ዕለት አብረው ሲጓዙ አንድን የሞተ ሰው ራስ ቅል አገኙና አባ ሲኖዳ በበትሩ ነቅነቅ አደረገውና "ምውት ሆይ! ያየኸውን ትነግረን ዘንድ በጌታችን ስም ተነሥ" አለው፡፡ ወዲውም ነፍሱ ወደ ዐፅሙ ተመልሳ ሥጋ ለብሶ ተነሣና ሰገደላቸው፡፡ በሲኦል ያየውንም ሁሉ በዝርዝር ነገራቸው፡፡ በየወገናቸው በሲኦል ውስጥ የሚሠቃዩትንና እርሱም የማያምን አረማዊ መሆኑን ነገራቸው፡፡ ዳግመኛም "ክብር ይግባውና በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያመኑ ትእዛዙን ግን ያልጠበቁ በአሕዛብ ሥራባ በአረማውያን ርኩሰት የኖሩ በሲኦል ከእኛ በታች የሚኖሩ ክርስቲያኖች አሉ" ብሎ ነገራቸው፡፡ ቅዱሳኑም "በል ተመልሰህ ተኛ" አሉትና እንቀድሞው ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ ሲኖዳ አባ በኪሞስን ተሰናብቶ ወደ አገሩ ተመለሰ፡፡
❤ ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ቅዱስ አባ በኪሞሰሰ አገልጋዩን ጠርቶ የሥጋውን መቅበሪያ ቦታ አሳየው፡፡ ወዲያውም በሆድ ዝማ ሕመም ጥቂት ታመመና፡፡ ቅዱሳንን በአንድነት ወደእርሱ ሲመጡ አያቸው፡፡ በዚያንም ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። መላእክትም ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከአደረሷት እያመሰገኑና እየዘመሩ አሳረጓት፡፡ መላ ዕድሜውም ሰባ ዓመት ሆነ ዐሥረሠ ሁለት ዓመት በዓለም ውስጥ ሃምሳ ስምንት ዓመት በምንኩስና ሥራ ኖረ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት በአባ በኪሞስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ11 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #ታላቁ_ሰማዕት_ቅዱስ_ገላውዴዎስ፡- ገላውዴዎስ ማለት "ዕንቈ ጳዝዮን" ማለት ነው፡፡ የመላእክት አርአያ ያለቅ ቅዱስ ገላውዴዎስ አባቱ አብጥልዎስ የሮሙ ንጉሥ የኑማርያኖስ ወንድም ነው፡፡ አባቱን የአንጾኪያ ሰዎች እጅግ ይመኩበትና ይወዱት ነበር፡፡ በሕይወት እያለም በጦርነት ድል ሲያደርግ የሚያሳይ ሥዕሉን በከተማው ላይ አሠርተው ያከብሩት ነበር፡፡ ልጁ ቅዱስ ገላውዴዎስ ግን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየተማረ አደገ፡፡ የሮሙ ንጉሥም ዜናውን ሰምቶ ሊያየው ወደደና ልጁን እንዲልክለት መልእክት ላከ፡፡ ሄዶ ሲያየውም ንጉሡ ከነሠራዊቱ ወጥቶ በክብር ተቀበለው፡፡
❤ ጣዖት አምላኪ የሆኑ የቁዝና የሌሎችም ሀገሮችን ቅዱስ ገላውዴዎስ ድል እያደረጋቸው ጣዖቶቻቸውንም ይሰባብርባቸው ነበር፡፡ ወደ አንጾኪያም በተመለሰ ጊዜ ዲዮቅልጥያኖስ ጌታችንን ክዶ ጣዖት ማምለክ መጀመሩን ባየ ጊዜ እጅግ አዘነ፡፡ ከቅዱስ ፊቅጦርም ጋር ሆነው የመጻሕፍትን ቃል ዕለት ዕለት ያነቡ ነበር፡፡ ሁለቱም ስለ ጌታችን ክብር ሰማዕት ሆነው ደማቸውን ያፈሱ ዘንድ በምክር ተስማሙ፡፡ ሰይጣንም በሽማግሌ አምሳል ተገልጡ ያዘነላቸው በመምስል "ልጆቼ ሆይ መልካም ጎልማሶች ናችሁ፣ የነገሥታት ልጆችም ናችሁ፣ እኔ ስለ እናንተ አዝንላችኋለሁ ስለዚህም ከንጉሡ ጋር ተስማምታችሁ አማልክቶቹን እያጠናቸሁ ትእዛዙንም እየፈጸማችሁ ኑሩ፡፡ ነገር ግን ክርስቶስን በቤታችሁ አምልኩት ይህ ዲዮቅልጥያኖስ ግን እጅግ
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዘረወ ወወሀበ ለነዳይ። ወጽድቁኒ ይነብር ለዓለም። ወይትሌዓል ቀርኑ በክብር"። መዝ 109፥9። የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 1፥5-12 ወይም 1ኛ ቆሮ 9፥1-15፣ 1ኛ ዮሐ 2፥20-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 20፥16-22። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 6፥1-5። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ኒቆላዎስ፣ የአባ ጥዋሽ የቅድስት ሱርስት፣ ቅዱሳን ሰማዕታት ተላስስና አልዓዛር የዕረፍታቸው በዓል፣ አቡነ ሳዊሮስ የሥጋ ፍልሰት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝ ✝ ✝
❤ #የአንጾኪያ_አገር_ሊቀ_ጳጳሳት_የቅዱስ
#አባ_ሳዊሮስ_የሥጋ_ፍልሰት_ከእስክድርያ_ወጪ_ወደሆነች_ደብረ_ዝጋግ_ገዳም፦ እንዲህም ሆነ ይህ ቅዱስ አባት በአገረ ስሓ አምላክን በሚወድ ክርስቲያን ባለጸጋ ስሙ ዱራታዎስ በሚባል ሰው ዘንድ በዐረፈ ጊዜ እርሱም ከምእመናን ሰዎች ጋር በመርከብ አሳፍሮ ላከው በጥልቅ ባሕር ላይ እንጂ በአነስተኛ ሸለቆ እንዳይሔዱ ከዚያም በወደቡ እንዲወጡ አዘዛቸው።
❤ ወደ ደቡባዊ ባሕረ ቅርጣስ በደረሱ ጊዜ የቅዱሱም ሥጋ ከእርሳቸው ጋር ሳለ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ጥቂት እንደተጓዙ መርከቡን የሚሸከም ውኃ አላገኙም መርከቡንም እየጐተቱ ታላቅ ድካምን ደከሙ መርከባቸውንም ወደ ኋላ ይመልሱ ዘንድ አሰቡ ግን አልተቻላቸውም ፈጽሞ አዘኑ ደነገጡም ዕውቀታቸውም ተሠወራቸው ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር የእስራኤል ልጆች ከጠላቶቻቸው ፊት ሰውሮ በኤርትራ ባሕር ውስጥ መንገድ ገልጦ ያላለፋቸው እርሱ የቅዱስ ሳዊሮስን ሥጋ መለካውያን ከሆኑ ከከሀድያን ሰዎች ሠወረ እነርሱ በሕይወቱ ሳለ ይጠሉት ነበርና እንዲሁ ከሞተ በኋላ ቃሉ እንደ ሰይፍ የሚቆራርጣቸው ሆነ።
❤ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ከተአምራቱ ገለጠ ያቺን መርከብ ወደሚወጡበት ወደብ እስከምትደርስ በጥቂት ውኃ ላይ ሰባት ምዕራፍ ያህል እንድትጓዝ አደረጋት ገዳም ከዚያም ተሸክመው ወደ ደብረ ዝጋግ ገዳም አድርሰው ያ ባለጸጋ ዱራታዎስ በሠራለት ቦታ ውስጥ አኖሩት በግብጽ አገርም ታላቅ ደስታ ሆነ ይልቁንም በእስክንድርያ ከተማ። እግዚአብሔርም ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራቶችን ገለጠ በሕይወቱ ሳለ ከጥርሶቹ የወደቀች አንዲት ነበረች የደብረ ዝጋግ ገዳም አንድ መነኵሴ አንሥቶ በሐር ጨርቅ ጠቅልሎ አኖራት እርሷም ለታመሙ ሕዝቦች የምትፈውስ ሆነች እነርሱም ወደ እስክንድርያ አገር ያመጧትና በበሽተኞች ላይ ያኖሩዋታል እነርሱም ይድናሉ። እግዚአብሔርም ቅዱስ ሳዊሮስን በሕይወቱ ካለበት ጊዜ ይልቅ ከሞተ በኋላ እጅግ ከፍ ከፍ አደረገው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሳዊሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ኒቆላዎስ፡- አባቱ ኤጲፋንዮስ እናቱ ዮና ይባላሉ፡፡ እርሱም ሜራ በምትባል አገር እጅግ ባለጸጎች ሆነው የሚኖሩ ደጋግ ሰዎች ናቸው፡፡ እጅግ ባለጸጎች ቢሆኑም ልጅ ስላልነበራቸው እያዘኑ እግዚአብሔርን በመለመን ብዙ ዘመን ኖሩ፡፡ የመውለጃ ጊዜአቸውም ባለፈ ጊዜ ስለ ልጅ መለመናቸውን አቆሙ፡፡ እግዚአብሔር ግን በመጨረሻ ዘመናቸው የተባረከ ይህን ኒቆላዎስን ሰጣቸው፡፡ እግዚአብሔርም በልጃቸው ላይ የጽቅን ሥራ ገለጠ፡፡ ልጁ ገና እንደተወለደ ተነሥቶ በእግሮቹ ቆሞ በሰዎች መካከል ለሁለት ሰዓት ያህል ቆመ፡፡ ይህም ለመንደሳዊ ሥራ የተነሣ ቅዱስ መሆኑን ያጠይቃል፡፡ በሕፃንነቱም የሐዋርያትን ትምህርት ፈጽሞ ረቡንና ዓርብን በመጾም እስከ ዘጠኝ ሰዓት የእናቱን ጡት አይጠባም ነበር፡፡
❤ ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ለመምህር ሰጥተውት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ ተማረ፡፡ ወደ ገዳምም ገብቶ ማንም እንደ እርሱ ሊሠራው የማይችለውን ጽኑ ገድል ተጋደለ፡፡ ዘጠኝ ዓመትም በሆነው ጊዜ ቅስና ተሾመና ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን ማድረግ ጀመረና ሕመምተኞችን ሁሉ የሚፈውሳቸው ሆነ፡፡ አንድ ባለጸጋ በሀገሩ ነበር፡፡ እርሱም የዕለት እራት ድረስ ፈጽሞ ድኃ ሆነ፡፡ አራት ሴት ልጆችም ነበሩትና እነርሱን ስለድኅነቱ የሚያገባቸው ጠፋ፡፡ ባለጸጋ የነበረውም ሰው የዝሙት ሙት ሠርቶ በዚያ ልጆቹ እያመነዘሩ በዝሙት ዋጋ ይኖሩ ዘንድ ይህንን የረከሰ ሀሳብ ሰይጣን አሳሰበው፡፡
❤ እግዚአብሔር ግን የዚያን ባለጸጋ የነበረ ሰው ክፉ ሀሳብ ለአባ ኒቆላዎስ ገለጠለት፡፡ አባ ኒቆላዎስም ከአባቱ ገንዘብ ላይ መቶ የወርቅ ዲናር ወስዶ በሌሊት ማንም ሳያየው ወደዚያ ባለጸጋ ወደነበረው ሰው ቤት ሄዶ በበሩ ሥር አስቀምጦለት ተመለሰ፡፡ ባለጸጋ የነበረውም ሰው ወርቁን ወስዶ እጅግ ደስ ብሎት ታላቂቱን ልጁን አጋባት፡፡ አሁንም ለ2ኛ ጊዜ አባ ኒቆላዎስ መቶ የወርቅ ዲናር አስቀመጠለትና ሰውየውም ሌላኛዋን ታላቅ ልጁን ዳራት፡፡ አባ ኒቆላዎስም ለ3ኛ ጊዜ እንዲሁ አደረገ፡፡ ባለጸጋውም በስተመጨረሻ "ይህን የሚያደርግልኝ የእግዚአብሔርን ሰው ማየት አለብኝ" ብሎ ቁጭ ብሎ እያደረ በሌሊት የሚመጣውን መጠበቅ ጀመረ፡፡ አባ ኒቆላዎስም ለ4ኛ ጊዜ ወርቁን ሲያኖርለት አገኘውና ወድቆ ሰገደለት፡፡ "ከገንዘብና በኃጢአት ከመውደቅ አድነኸኛልና ዋጋህ ፍጹም ነው" ብሎ አመሰገነው፡፡ አባ ኒቆላዎስ በአካባቢው ባለው ዛፍ ላይ አድረው በሰውየው ላይ መከራ ያመጡበትን አጋንንት አባረራቸው፡፡ በዚያ የነበሩ ሕመምተኞችንም አዳናቸው፡፡ ዳግመኛም ጥቂት እንጀራን አበርክቶ ብዙ ሕዝቦችን አጠገባቸው፡፡ እጅግ የበዛ ትራፊም ተመልሶ ተነሣ፡፡
❤ ከዚህም በኋላ አባ ኒቆላዎስ ኤጲስቆጶስነት ከመሾሙ አስቀድሞ የክህነት ልብስንና ብርሃንን የለበሰ ሰው በዙፋን ላይ ተቀምጦ በራእይ አየና "ይህንን የክህነት ልብስ ለብሰህ በዙፋኑ ተቀመጥ" የሚል ድምጽ ሰማ፡፡ ለሁለተኛ ጊዜም እመቤታችን ተገልጣለት የክህነትን ልብስ ስትሰጠው ጌታችንም የከበረች ወንጌልን ሲሰጠው አየ፡፡ ከዚህም በኋላ የሜራ አገር ኤጲስቆጶስ በሞት ባረፈ ጊዜ የታዘዘ መልአክ ለሮሜው አገር ሊቀ ጳጳስ ተገለጠለትና ስለ አባ ኒቆላዎስ መልኩንና ስሙን በዝርዝር ነገረው፡፡ እርሱም ለሕዝቡ ሁሉ ነገራቸው አባ ኒቆላዎስን ወስደው በሜራ አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት፡፡
❤ ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ አምለኮ ጣዖትን በግዛቱ ሁሉ ሲያውጅና የክርስቲያኖችን ደም እንደውኃ ሲያፈስ አባ ኒቆላዎስ ደግሞ ክርስቲያኖችን ያስተምራቸውና በሃይማኖት ያጸናቸው ነበር፡፡ ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ አባ ኒቆላዎስን ይዞ እጅግ ብዙ አሠቃየው፡፡ ነገር ግን ጌታችን ከመከራው ሁሉ እያዳነው ከቁስሉም ይፈውሰው ነበር፡፡ ንጉሡም እጅግ ቢያሠቃየውም ቅዱሱ ደግሞ መልሶ ጤነኛ ሆኖ ያገኘዋል፡፡ በዚህም ማሠቃየት ቢሰለቸው ወደ እሥር ቤት ጨመረው፡፡ እግዚአብሔርም ዲየቅልጥያኖስን አጥፍቶት ጻደቁን ቆስጠንጢኖስን እስካነገሰው ድረስ አባ ኒቆላዎስ በእሥር ቤት ብዙ ዓመታት ኖረ፡፡
❤ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስም የታሰሩትን ቅዱሳን ሁሉ በፈታቸው ጊዜ አባ ኒቆላዎስ ከእሥር ወጥቶ ወደ መንበረ ጵጵስናው ተመለሰ፡፡ ሕዝቡንም ስለቀናች ሃይማኖት አስተማራቸው፡፡ ሃይማኖታቸው የቀና እጅግ የከበሩ 318 ቅዱሳን በአርዮስ ጉዳይ በተሰበሰቡ ጊዜ ይህ ቅዱስ አባት አባ ኒቆላዎስ ከእነርሱ ውስጥ አንዱ ነው፡፡ እርሱም ከሌሎቹ ቅዱሳን ጋር ሆኖ አርዮስን አሳዶ የቀናች ሃይማኖትን ደነገገልን፣ ሥርዓትን ሠራልን፡፡ እርሱም ተጋድሎውን ፈጽሞ በዚህች ዕለት ታኅሣሥ10 በሰላም ዐረፈ፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ኒቆላዎስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ትደርብን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 10 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፲ (10) ቀን።
❤ እንኳን ለቅዱሳን ሰማዕታት #ለተላስስና_ለአልዓዛር ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍት በዓል፣ ከታናሽነቱ ጀምሮ ጃንደረባ ለሆነ #ለአባ_ጥዋሽ ለዕረፍት በዓል፣ ከቊጥስጥንጥንያ አገር ለከበሩ ሰዎች ልጅ ለሆነች #ለቅድስት_ሱርስት ለዕረፍት በዓል፣ ለአንጾኪያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ለነበረ #ለቅዱስ_አባ_ሳዊሮስ ከእስክንድርያ አገር ወጪ ወደሆነች ደብረ ዝጋግ ገዳም ሥጋው ለፈለሰበት በዓልና ለከበረ አባት ጻድቅ ኤጲስቆጶስ የስሙ ትርጓሜ የሕዝብ አሸናፊ ለሆነ #ለአባ_ኒቆላዎስ_ለዕረፍት_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከእስክንድርያ አገር ስልሣኛ ሊቀ ጳጳሳት #ከአባ_ታውፋኔዎስ ዕረፍት፣ ከቅዱሳን #ከሜልዮስና_ከታውፍያ ከዕረፍታቸው መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_ሰማዕታት_ተላስስና_አልዓዛር፦ ይህም ተላስስ ከነነዌ አውራጃ ከባቢሎን ሰዎች ወገን ነው የፋርስ ንጉሥ ሳቦርም ይዞት "ለእሳት ስገድ ለአማልክትም ሠዋ" አለው ቅዱስ ተላስስም " እኔስ ለፈጣሪዬ እግዚአብሔር እሰግዳለሁ ለእርሱም እሠዋለሁ እንጂ ለጣዖት አልሠዋም" አለው። ያስፈራውም ዘንድ የቅጣት መሣሪያዎችን አስመጣ እርሱ ግን አለሰፈራም መቶ ግርፋትም ለረዥም ጊዜ እንዲገርፋት አዘዘ ከዚህም በኋላ "ተላስስ ሆይ ከዚህ ሥቃይ እንድታርፍ ለአማልክት ሠዋ" አለው እርሱም "ፈጣሪዬ ስለሚጠብቀኝ ለእኔ ሥቃይህ አልታወቀኝም" አለው።
✝ በዚያንም ጊዜ ሁለት መቶ ጊዜ ገረፉት በዐይኖቹም ውስጥ የብረት ችንካሮችን ተከሉ መናገርም እስከሚሳነው በነሐስ መክደኛ ሸፍነው ደበደቡት ራሱንም በሰይፍ ቆረጡ። ከዚህም በኋላ አልዓዛርን አቀረቡት ንጉሥ ሳቦርም "ለአማልክት ሠዋ" አለው ለረከሱ አማልክቶቹም መሠዋትን እምቢ ባለው ጊዜ ወዲያውኑ ወደ እሳት ወረወረው ያማረ ምስክነቱንም ፈጸመ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕታት ቅዱሳን ተላስስና አልዓዛር ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ጥዋሽ፡- ይኽም ቅዱስ ከልጅነቱ ጀምሮ ድንግል ሆኖ በምንኵስና በታላቅ ተጋድሎ የኖረ ነው፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ወደ እስክንድርያ ሲጓዝ በመንገድ ላይ አንዲት አይሁዳዊት ሴት ስታለቅስ አገኛትና ምን እንደሆነች ጠየቃት፡፡ እርሷም "ክርስቲያን መሆን እሻ ነበር" አለችው፡፡ አባ ጥዋሽ የነፍሱን ጥቅም አስቦ ሊተዋት ነበር ግን ሴቲቱ መዳን እየፈለገች ቢተዋት በእግዚአብሔር ዘንድ ታላቅ በደል እንዳይሆንበት ከእርሱ ጋር ወሰዳትና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃት፡፡
❤ ከዚህም በኋላ አባ ጥዋሽ ከሴቲቱ ጋር ሆኖ በየገበያው ቦታ ሁሉ እየዞሩ ነለዳያን ይመጸውቱ ጀመር፡፡ የእስክንድርያ መነኰሳትም እርሷ ሚስቱ እንደሆነች አስበው በዚህ ተሰነካከሉበት፡፡ ይዘውትም ሊቀ ጳጳሳቱ አባ ዮሐንስ ዘንድ አቀረቡት፡፡ አባ ዮሐንስም ሁለቱን ተያይተው እንዲታሰሩ አዘዙ፡፡ በዚያችም ሌሊት ሊቀ ጳጳሳቱ አባ ዮሐንስ በሕልማቸው አባ ጥዋሽ የቆሰለ ጀርባውን እያሳያቸው "ያለበደሌ ለምን አቆሰልከኝ?" ሲላቸው ተመለከቱ፡፡ አባ ዮሐንስም በነቁ ጊዜ አባ ጥዋሽን አስመጥተው በግርፋት ብዛት የቆሰለ ጀመርባውንና ፍጹም ድንግል መሆኑን አይተው እጅግ አዝነው አለቀሱ፡፡ "ይቅር በለኝ" ብለው በፊቱ ወደቁ፡፡ ከዚያም አባ ጥዋሽን ያመጡትንና የደበደቡትን ሰዎች ከማዕረጋቸው አውርደው ለ3 ዓመታት ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ከመቀበል ከለከሏቸው፡፡ ካሳ ይሆነውም ዘንደ ለአባ ጥዋሽ ብዙ ገንዘብ ቢሰጡት እርሱ ግን ምንም ሳይቀበል ወደ በዓቱ ተመልሶ ሄዶ ተጋድሎውን ፈጽሞ በዚህች ዕለት ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ጥዋሽ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_ሱርስት፡- ይኽችም ቅድስት ከቁስጥንጥንያ አገር እጅግ ከከበሩ ወገኖች የአንዱ ልጅ ናት፡፡ ለአንድ ለከበረ ሰው ልጅ በታጨች ጊዜ አባቷን "አባቴ ሆይ! አስቀድሜ ወደ ቤተ መቅደስ ሄጄ እሰግድ ዘንድ ፍቀድልኝ በምመለስበት ጊዜ እግዚአብሔር እንደፈቀደ ይሁን" አለችው፡፡ አባቷም "አስቀድመሽ ወደ ባልሽ ግቢ፣ ሰርግሽ ከተፈጸመ በኋላ ከእርሱ ጋር ወደ ወደድሽው ሄደሽ ስዕለትሽን ትፈጽሚያለሽ" አላት፡፡ እርሷም መልሳ "በድንግልናዬ ሳለሁ ወደዚያች የከበረች ቦታ ሄጄ ልጸልይ ለእግዚአብሔር ቃል ገብቻለሁና ቃሌን ብዋሽ ፈጣሪ በእኔ ላይ ይቆጣል" ስትለው አባቷ ከሚያገለግሏት ወንዶችና ሴቶች አሽከሮች ጋር ለምጽዋትም የምትሰጠው 300 የወርቅ ዲናር ሰጥቶ ላካት፡፡
❤ ቅድስት ሱርስትም እዚያ በደረሰች ጊዜ የከበሩ ቦታዎችን ሁሉ እየዞረች ተሳለመች፣ ወደ ግብጻውያን ገዳምም በደረሰች ጊዜ አንድ አረጋዊ መነኩሴ ማቅ ለብሶ አገኘችውና የልቧን ሀሳብ ሁሉ ማለትም ልትመነኩስ እንደምትፈልግ ነገረችው፡፡ እርሱም "የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን" አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሊሄዱ በተዘጋጁ ጊዜ ወደ ስውር ቦታ ገብታ ለወላጆቿ "እኔ ሰውነቴን ለእግዚአብሔር አቅርቤያለሁ አታገኙኝምና አትፈልጉኝ" ብላ ደብዳቤ ጻፈች፡፡ ደብዳቤውንም በልብሷ አሥራ ከዕቃ ውስጥ አኖረችው፡፡ ሰዎቹም ከእነርሱ ጋር አብራ የምትሄድ መስሏቸው ዕቃ ጭነው በቀደሟት ጊዜ አንዱን አገልጋይ ይዛ አስቀረችውና "ወደ ጎልጎታ ገብቼ ልጸልይ እሻለሁና" ብላ ምሥጢሯን እንዲጠብቅ ነገረችው፡፡
❤ ከዚህም በኋላ ወደዚያ ሽማግሌ መነኩሴ ዘንድ ተመልሳ የያዘችውን 300 የወርቅ ዲናር ለድኆችና ጦም አዳሪዎቸ እንዲያከፋፍለው ሰጠችውና ያመነኵሳት ዘንድ ለመነችው፡፡ እርሱም ጽናቷን አይቶ ፈቃደ እግዚአብሔርም መሆኑን ዐውቆ ራሷን ላጭቶ የምንኩስና ልብስ አለበሳት፡፡ እርሷም እግዚአብሔር ወደፈቀደላት ወደ አንዲት ዋሻ ሄዳ በዚያ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረች፡፡ በዚህም ጊዜ ዕድሜዋ ገና 12 ዓመት የነበረ ቢሆንም የሰውን ፊት ሳታይ በዚያች ዋሻ ውስጥ ለ27 ዓመታት በተጋድሎ ኖረች፡፡
❤ ቃህራ ከሚባል አገር በገድል ሥራ የሚኖር ሲላስ የሚባል መነኰስ ነበር፡፡ በቀልሞን ዋሻ የሚኖር አንድ ጓደኛ መነኰስ አለውና ፋሲካ በደረሰ ጊዜ እርሱን ጎብኝቶ በረከት ለመቀበል ሄደ፡፡ በሄደም ጊዜ አላገኘውምና እርሱን ፍለጋ ተራራ ለተራራ ዞረ፡፡ በዚያም የእግር ዱካ አገኘና ዱካውን ተከትሎ በመሄድ መግቢያው ላይ ሲደርስ "የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ ባርከኝ" አለ፡፡ ከውስጥም ያለው ድምጽ ስሙን ጠርቶት "ሲላስ ሆይ አንተ ካህን ነህና ልትባርከኝ ይገባል" አለው፡፡ ሲላስም ወደ ውስጥ እንደገባ ቅድስት ሱርስትን አገኛት፡፡ እርሷም ምሥጢሯን ሁሉ በዝርዝር ነገረችው፡፡ ወዲያውም በዚች ቀን ታኅሣሥ10 በሰላም ዐረፈች፡፡ ሲላስም በዚያች ዋሻ ውስጥ በክብር ገንዞ ቀበራት፡፡ ገድሏንም ጻፈላት፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ሱርስት ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
❤ ቅዱስ አባ በአሚንም ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ የሞት ደዌን ታመመ መነኰሳቱንም ሁሉ ሰብስቦ ዕድሜው እንደ ቀረበ ነገራቸውና አጽናናቸው እነርሱም ከእርሱ ስለመለየታቸው አዘኑ ከዚህም በኋላ በፈጣሪው እግዚአብሔር እጅ ነፍሱን ሰጠ። መነኰሳቱም እንደሚገባ እያመሰገኑና እየዘመሩ መልካም አገናነዝን ገንዙት ሥጋው በእምነት ወደርሱ ለሚመጣ ሁሉ መጠጊያ ሆነ ወይም በቀናች ሃይማኖት ጸንቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሒዶ በስሙ ለሚለምን ሁሉ የለመነው ይሆንለታል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ በአሚን ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የታኅሣሥ 9 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወቀተሉ ፈላሴ። ወይቤሉ ኢይሬኢ እግዚአብሔር። ወኢየአምር አምላከ ያዕቆብ። መዝ 93፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ተሰ 2፥13-ፍ.ም፣ ያዕ 5፥8-12 እና የሐዋ ሥራ 3፥22-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል 5፥25-35። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ በአሚን የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ታኅሣሥ ፱ (9) ቀን።
❤ እንኳን #ያለደምን_መፍሰስ_ሰማዕትነት ለተቀበለ ታማኝ ለሆነ #ለቅዱስ_አባት_ለአባ_በአሚን ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከቅዱሳ #ከበድላም_ከአርምያና_ከዘካርያስ ከዕረፍታቸው መታሰቢያ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_በአሚን፦ እርሱም በደቡብ ግብጽ በእስሙናይን አውራጃ ለአገረ ቴርሳ አቅራቢያ ከሆኑ ከሐፂብ ተወላጆች ወገን ነው ለአንድ ባለጸጋም በጅሮንድ ሆኖ ሳለ ስለ ንጽሕናውና ስለ ቅድስናው በሁሉ ዘንድ ተወዳጅ ሆነ የባለ ጸጋውም ሚስት አባ በአሚንን እጅግ የምትወደውና የምትተማመንበት ሆነች።
❤ እርሱ ግን የዚህን ዓለም ፍጻሜ አሰበ የባለ ጸጋውንም አገልግሎት ትቶ ወደ ገዳም ሒዶ መነኰሰ ባለጸጋውም መሔዱን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ሚስቱንም ይዞ አባ በአሚን ወዳለበት በአንድነት ሔዱ ወደ እርሳቸው እንዲመለስም ለመኑት እንዲህም አሉት "ከአንተ እንለይ ዘንድ ከቶ አንችልም ስለዚህ አንተውህም" አሉት። አባ በአሚንም "እኔ ራሴን ብፅዓት አድርጌ ለእግዚአብሔር ሰጥቻለሁ እኮን" አላቸው። ይህንንም ሲሰሙ ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑ ትተውት ተመለሱ።
❤ ከዚህም በኋላ በአማረ ተጋድሎ ሁሉ ታላቅ ተጋድሎን በመጋደል ብዙ ዘመናት እግዚአብሔርን አገለገለው። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ሁኖ ደሙን ሊአፈስ ወዶ ወደ እንዴናው ከተማ ሒደ ብዙዎች ምእመናንንም ሲአሠቃዩአቸው አገኛቸው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ጽኑ ሥቃይንም አሠቃዩት ሥጋውን በእሳት ለበለቡ ሕዋሳቱንም ሠነጣጥቀው ከመንኰራኵር ውስጥ ጨመሩት ዳግመኛም በአጋሏቸው የብረት ዘነሰጎች አቃጠሉት በዚህም ሁሉ ጸና ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስን ክርስቶስም ያለ ጉዳት በጤና ያስነሣው ነበር።
❤ እንዲህም እየተሠቃየ ሳለ ጣዖት የሚመለክበት ወራት አለፈና ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ ነገሠ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ዲዮቅልጥያኖስ ያሠራቸውን እሥረኞች ሁሉ እንዲፈቷቸው አዘዘ ጌታችንም ለአባ በአሚን ተገለጠና ከሰማዕታት ጋር እንደቆጠረው አስረዳው። ንጉሥ ቈስጠንጢኖም ከእርሳቸው ቡራኬ ሊቀበል ሽቶ ከውጣቸው ሰባ ሁለት እሥረኞችን ወደርሱ ያመጡ ዘንድ አዘዘ አባ ኖብ ከእርሳቸው ጋር በዚያ ነበር ከእርሳቸውም አንዱ ይህ አባ በአሚን ነው።
❤ ከዚህም በኋላ ከእሥሙናይን ውጭ በሆነች ገዳም የሚኖር ሆነ ጌታችንም ታላቅ ጸጋን ሰጥቶት በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውሳቸው ሆነ ዜናውም ቦታው ሁሉ ተሰማ። በዚያም ወራት የሮሜ ንጉሥ ሚስት የሆነች አንዲት ንግሥት ነበረች እርሷም ከእርሷ ጋር ስለሚኖር የወንጌላዊውን ዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ ሁል ጊዜ የሚያነብላት የሆነ እግዚአብሔርን ስለሚፈራ ስለ አንድ ዲያቆን እጅግ የታመመች ናት ከንጉሥ ሹሞች አንዱ በቀናበት ጊዜ ወደ ንጉሡ ሒዶ "ጌታዬ ሁል ጊዜ የዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ በማንበብ እያመካኘ ከእመቤቴ ንግሥት ጋር ይተኛል" አለው።
❤ ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ በዚያንም ጊዜ ተነሥቶ ንግሥቲቱ ወዳለችበት ቤተ መንግሥት ገባ ያንንም ዲያቆን በፊቱ ቁሞ የዮሐንስን የራእይ መጽሐፍ ሲያነብ አገኘውና ከነመጽሐፉ ወስደው ዲያቆኑን ከባሕር እንዲአሠጥሙት አዘዘ ሁለት ሰዎችም በታናሽ ጀልባ ጭነው ወስደው ከባሕር መካከል ወረወሩት ወዲያውኑ ብርሃንን የለበሰ ሰው ከሰማይ ወርዶ ያንን ዲያቆን ከመጽሐፉ ጋር ነጥቆ ወስዶ ከአንዲት ደሴት ላይ አኖረው እነዚያ ሁለት ሰዎች ሲያዩ ነበር እጅግም እያደነቁ ተመለሱ ያዩትንም ለንጉሡ አልነገሩትም።
❤ ንግሥቲቱም በዲያቆኑ ላይ የተደረገውን በአየች ጊዜ እጅግ አዘነች በእርሷም ደዌ ጸናባት ሆድዋም ቈስሎ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረች ወደርሷም ብዙ ጥበበኞች ባለመድኃኒቶች መጥተው ነበር ግን ሊፈውሷት አልቻሉም አንድ አዋቂ ሰውም እንዲህ ብሎ መከራት "በግብጽ አገር ወደሚኖሩ ቅዱሳን ብትሔጂ ከደዌሽ በተፈወስሽ ነበር"። በዚያን ጊዜ ተነሣች ከእርሷም ጋር ብዙ ሠራዊት አለ ወደ ግብጽ አገርም ደርሳ ገዳማቱንና አብያተ ክርስቲያንንም ሁሉ ዞረች ግን አልዳነችም።
❤ ወደ እንዴናው ከተማም በደረሰች ጊዜ ስለ መምጧቷ የአገሩ መኳንንት አደነቁ እርሷም ችግርዋን ሁሉ ነገረቻቸው እነርሱም ወደ ቅዱስ አባ በአሚን እንድትሔድ መከሩዋት በመርከብም ተሳፍራ ወዲያውኑ ቅዱስ አባ በአሚን ወዳለበት ገዳም ደረሰች "እንሆ ንግሥት ወዳንተ መጥታለች ከአንተም ልትባረክ ትሻለች" ብለው ነገሩት እርሱም "ከምድር ንግሥት ጋር ምን አለኝ" ብሎ መውጣትን እምቢ አለ መነኰሳትወደርሷ እንዲወጣ አጽንተው ለመኑትና ወጣ በአየችውም ጊዜ ከእግሩ በታች ወድቃ ሰገደችለት እርሱም በዘይት ላይ ጸልዮ ቀባት በዚያንም ጊዜ ዳነች። ቅዱስ አባ በአሚንም "ንጉሥ ከባሕር በአሠጠመው በዚያ ዲያቆን ምክንያት ይሁ ሁሉ እንደደረሰብሽ ዕወቂ እርሱ ግን በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት ይኖራል የአቡቀለምሲስ ዮሐንስ የራእይ መጽሐፍም ከእርሱ ጋር አለ" አላት። ንግሥቲቱም ሰምታ እጅግ አደነቀች ደስ አላትም ስለዚያ ዲያቆን በሕይወት መኖርና እርሷም ፈውስ ስለማግኘቷ ለቅዱስ አባ በአሚንም እጅ መንሻ ብዙ ገንዘብ አቀረበችለት ከንዋየ ቅድሳት በቀር ምንም ምን ገንዘብ አልተቀበለም።
❤ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔርን እያመሰገነች ወደ ሮሜ አገር ተመለሰች በእርሷ ላይ የሆነውን ሁሉ ወደ ባሕር ስለ አሠጠሙት ስለዚያ ዲያቆንም እርሱም እስከ ዛሬ በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት እንዳለ ለንጉሡ ነገረች። ንጉሡም ይህን ነገር ሰምቶ እጅግ አደነቀ ይፈልጉትም ዘንድ መልክተኞችን ላከ በደሴትም ውስጥ በሕይወት አገኙት መጽሐፉም ከርሱ ጋር አለ ተመልሰውም ለንጉሡ ነገሩት ሁለተኛም ወደርሱ እንዲመጣ እየማለደ ላከ ከመልክተኞችም ጋር ወደ ንጉሡ መጣ ንጉሡም በአየው ጊዜ ታላቅ ደስታ አደረገ ከእግሩ በታችም ወድቆ "በአንተ ላይ ስለአደረግሁት በደል ይቅር በለኝ" አለው እርሱም "በአንድነት እግዚአብሔር ይቅር ይበለን" አለ። ከዚህም በኋላ ያ ዲያቆን በሮሜ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ያንንም የዮሐንስ አቡቀለምሲስ ራእይ ተረጐመው።
❤ ቅዱስ አባ በአሚንም በቀንና በሌሊት ያለማቋረጥ የሚጋደል ሆነ። በአቅራቢያውም አንድ ደግ ኤጲስቆጶስ አለ በአንዲት የሰማዕታት ገዳም ከምእመናን ጋር በዓልን ሲያደርግ አርዮሳውያንም ለራሳቸው ሐሰተኛ ኤጲስቆጶስ ይዘው ሕዝቡን የሚያስቱ ሆኑ የአገሩም ኤጲስቆጶስ ወደ አባ በአሚን መጥቶ ስለ እሊህ ከሀድያን ምክር የደረሰበትን ኃዘኑን ሁሉ ነገረው። የሰማዕታትም በዓል በሆነ ጊዜ የእሊህን ከሀድያን ምክር እግዚአብሔር ይበትን ዘንድ ቅዱስ አባ በአሚን ከሕዝቡ ጋር በመለመንና በመስገድ ጸለየ ከዚህም በኋላ የሽመል በትር ያዘ ሕዝቡም ሁሉ እየአንዳዱ በትሮችን ይዘው ወደእነዚያ ከሀድያን ሔዱ ከሀድያንም በአዩ ጊዜ ተበተኑ ወደዚያ ዳግመኛ አልተመለሱም እግዚአብሔር ምክራቸውን በትኖባቸዋልና።
