ar
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

إظهار المزيد
637
المشتركون
لا توجد بيانات24 ساعات
-37 أيام
-1130 أيام
أرشيف المشاركات
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤           ❤ #መጋቢት ፫ (3) ቀን። ❤ እንኳን #ለእስክንድርያ_ሃምሳ_ስምንተኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለብፁዕ_ወቅዱስ_ለአባ_ቆዝሞስ ለዕረፍት በዓልና ከፎንዮስ አገር ለሆነ #ለአባ_በርፎንዮስ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                  ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ቆዝሞስ፦ ይህም እውነተኛና ንጹሕ፣ የዋህ ርኅራኄው የባዛ የቤተ ክርስቲያንንም መጻሕፍትና ትርጓሜያቸውን የሚያውቅ ነበር። እግዚአብሔር በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ ለሊቀ ጵጵስና ሹመት መረጠው የግብጽ ንጉሥ መቅትር በነገሠ በዐሥራ ስምንት ዓመት ሊቀ ጳጳሳት ሁኖ ተሾመ። ❤ በተሾመም ጊዜ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንጋዎች በፈሪሃ እግዚአብሔር በጥበብ ጠበቃቸው። ለእርሱ ከሚገባው ከግብሩ ገንዘብ የሚተርፈውን ለጦም አዳሪዎች ይሰጣቸው ነበር ደግሞም ለቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ማሠሪያ ያወጣ ነበር። ❤ መልካም ተጋድሎውንም በአየ ጊዜ ሰይጣን ያለ ኀዘን አልተወውም ነገር ግን የሚያዝንበትን ምክንያት በላዩ አመጣ። ይኸውም እንዲህ ነው ጴጥሮስ የሚባል ጳጳስ ለኢትዮጵያ አገር ሹሞ ነበር  አባ ጴጥሮስም ወደ ኢትዮጵያ በደረሰ ጊዜ ጥቂት ዘመን በሰላም ኖረ። ከዚህም በኋላ የኢትዮጵያ ንጉሥ ታመመ አባ ጴጥሮስንም ጠርቶ ሁለቱን ልጆቹን አቀረበ ዘውዱንም ከራሱ ላይ አንስቶ ለአባ ጴጥሮስ ሰጠው "እንሆ እኔ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እሔዳለሁ እንሆም ሁለቱ ልጆቼ በፊትህ ናቸው አንተም ከሁለቱ አንዱን ከእኔ በኋላ አንግሥ" አለው። ንጉሡም ካረፈ በኋላ ጳጳሱ መንኳንንቱና የጦር ሥራዊቱ አለቆችና የመንግሥት ሠራዊት አለቆች ተማከሩ እርስ በርሳቸውም ለመንግሥት የሚሻል የሚያንሰው ነው ተባባሉ። ጳጳሱ አባ ጴጥሮስ ታናሹን የንጉሥ ልጅ ቀብቶ አነገሠው በኢትዮጵያ መንግሥት ዙፋን ላይም አስቀመጠው ጥቂት ዘመንም በሰላም ኖረ። ❤ በዚያም ወራት ከሶርያ አገር በሆኑ በሁለት መነኰሳት ልብ ሰይጣን አደረ ከአባ እንጦንስ ገዳም እስከ ሚደርሱ ከቦታ ወደቦታ ይዞሩ ነበር። በዚያም በአባ እንጦንስ ገዳም ጥቂት ቀኖች ተቀመጡ ስለ ሥራቸውም ክፋት አባረሩአቸው። ከዚያም በኋላ አንዱ ጳጳስ ሁለተኛውም ረዳት ሊሆን እርስ በርሳቸው ተስማሙ። ተነሥተውም ወደ ኢትዮጵያ ደረሱ። የሐሰት ጽሑፍንም ጻፉ ያ ጽሑፋቸውም እነርሱ ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ከአባ ቆዝሞስ ዘንድ ተሹመው እንደ መጡ የሚገልጥ ነበር። በዚያ ጽሑፍም "እኛ ያልሾምነውና ወደ እናንተ ያልላክነው ራሱን ጳጳስ ያደረገ ስሙ ጴጥሮስ የተባለ ሰው ወደ እናንተ እንደመጣ ሰምተናል እርሱ ሐሰተኛ ነው እንጂ እውነተኛ አይደለም። ይህን ጽሑፍ ይዞ የሚመጣው ግን ስሙ ሚናስ የሚባል ጳጳስ በእውነት እኛ የሾምነውና ወደ እናንተ የላክነው እውነተኛ ነው" አሉ። ሁለተኛም እንዲህ ብለው ጻፋ "ጳጳሱ ጴጥሮስ ታላቁን ትቶ ታናሹን የንጉሥ ልጅ አነገሠው ይህም የማይገባ ነው ዐመፅ ነውና"። ❤ እሊህም ክፋዎችና ሐሰተኞች ሁለቱ መነኰሳት ሚናስና ፊቅጦር የሐሰት ጽሑፋቸውን ሳይጽፉ ወደ ጳጳሱ ጴጥሮስ ደርሰው ወርቅ ይሰጣቸው ዘንድ ፈለጉ እርሱም ምንም አልሰጣቸውም። ይህንንም የከፋና የረከሰ ሥራ ሰይጣን አስተማራቸው። የሐሰት ደብዳቤም ጽፈው ወደ ታላቁ የንጉሥ ልጅ ወሰዱ እርሱም ከጥቂት ሰዎች ጋር ለብቻው ይኖር ነበር እነዚያንም የሐሰት ደብዳቤዎች አነበቡለት እጅግም ደስ አለው። ❤ ከዚህም በኋላ ብዙ ሠራዊት ሰብስቦ እሊያን የሐሰት ደብዳቤዎች በፊታቸው አነበበላቸው ከንጉሡ ወንድሙ ጋራም ጦርነት ገጥሞ ድል አደረገው፤ ወንድሙንም አሠረው የመንግሥቱንም ሥልጣን ያዘ እንዲሁም ጳጳሱን ጴጥሮስን አሠረው በሩቅ አገርም አጋዘው ያንንም ሐሰተኛ ሚናስን በጳጳሱ በጴጥሮስ ፈንታ አስቀመጠው። ❤ ከጥቂት ቀንም በኋላ ሐሰተኞች ፊቅጦርና ሚናስ እርስ በርሳቸው ተጣሉ ፊቅጦርም በመንበረ ጵጵስና ያለውን ገንዘብ ሁሉ ሰርቆ ወደ ግብጽ አገር ሸሽቶ ሔደ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ካደው። ከመንበረ ጵጵስናው የሰረቀውንም ገንዘብ ሁሉ እግዚአብሔር የማይወደውን ሥራ በመሥራት አጠፋው። ❤ ሊቀ ጳጳሳት ቆዝሞስም ሐሰተኛ ሚናስ ያደረገውን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ደብዳቤም በመጻፍ አውግዞ ለየው። የኢትዮጵያ ንጉሥ ሰምቶ እጅግ አዘነ ሐሰተኛው ሚናስንም ይዞ ገደለው። ጳጳሱ ጴጥሮስንም ከተሰደደበት ይመልሱት ዘንድ መልክተኞችን ላከ ግን ሙቶ አገኙት። ❤ ይህም ነገር በሊቀ ጳጳሳት በቆዝሞስ ዘንድ ተሰማ ሁለተኛም ጳጳስ አልሾመላቸውም ከእርሱም በኋላ የነበሩ ሊቃነ ጳጳሳት አባ መቃርስ፣ አባ ታውፋንዮስ፣ አባ ሚናስና አባ አብርሃም በእነዚህ ዘመን ከ911 ዓ.ም እስከ 995 ዓ.ም ድረስ ለሰማንያ አራት ዓመታት ያህል ለኢትዮጵያ ሰዎች ጳጳስ ተሹሞ አልተላከላቸውም። ❤ የኢትዮጵያ ንጉሥ ግን የጳጳሱ የጴጥሮስ ረዳት የነበረውን ወስዶ በመምህርህ ፈንታ ጳጳስ ሁነህ ተቀመጥ አለው። እርሱም እኔ ጳጳስ ልሆን አይገባኝም የሐዋርያትንም ሥርዓት ተላልፌ ይህን ሥራ አይቻለኝም ግን ልቀቀኝና ወደ ግብጽ ልሒድ ጳጳስ እንዲሾምላችሁም ሊቀ ጳጳሱን እለምነዋለሁ ከዚህም በኋላ ወደ እናንተ እመለሳለሁ እያለ ንጉሡን ማለደው። ንጉሡም ወደ ግብጽ እንዲሔድ አላሰናበተውም ያለ ውዴታው ወስዶ የጵጵስናውን ልብስ አለበሰው እንጂ። የጵጵስናውንም ሥራ እንዲሠራ አደረገው። ❤ አባ ቆዝሞስም እጅግ ሸመገለ የሹመቱም ዘመን ደኅንነትንና ሰላምን የተመላ ነበር በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበርም ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ በሰላምም መጋቢት 3 ቀን ዐረፈ። እግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛን በአባ ቆዝሞስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት 3 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለከ_በርፎንዮስ_አብ። ምሉዐ ጥበብ። ከመ ማኅቶት ዘአስተርአይከ ለሀገረ ፍንዮስ ሕዝብ። ለመርዓ ስምከ ኀበ ይትገበር ከብካብ። ረስየኒ እትረከብ በልብስ ሕፁብ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_3።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወባሕቱ መከሩ ይሥዐሩ ክብርየ። ወሮፅኩ በጽምእየ። በአፉሆሙ ይድኅሩ ወበልቦሙ ይረግሙ"። መዝ 61፥4። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ተሰ 1፥3-ፍ.ም፣ 2ኛ 2ኛ ጴጥ 3፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 4፥13-27። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 12፥25-38። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ወራትና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።           

“መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ” በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሐዱ አምላክ አሜን !! ‹‹ወነአምር ከመ ለእመሂ ተነሥተ ቤተ ማኅደርነ ዘበምድር ዘውእቱ ሥጋ ብነ ሕንጻ በኀበ እግዚአብሔር በሰማያት ዘኢገብሮ እደሰብእ፡- በምድር ያለው ማደሪያ ቤታችን ቢፈርስም በሰማይ በእግዚአብሔር ዘንድ የሰው እጅ ያልሠራው ዘለዓለማዊ ቤት እንዳለን እናውቃለን፡፡›› (2ቆሮ. 5፡1)በልዩ ልዩ ጊዜያት ዐረፍተ ዘመን የገታቸውን ወገኖች ልንሸኝ እንችላለን፤ የአንዳንድ ሰዎች ሞት ግን ከልብ ቶሎ የማይወጣ፤ ለዘመናትም በህሊና መዝገብ ላይ የሚቆይ ነው፡፡ በመሆኑም የሚከተሉት ሃይማኖት ወይም መርጠው ያልተወለዱበት አካባቢ እንደበደል ተቆጥሮባቸው ከየአቅጣጫው በሚሰነዘረው ጥቃት በሚገደሉ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች፣ ምእመናን በአጠቃላይ የሰው ልጆች ኀዘን ልባችን በትካዜ ውስጥ በገባበት በዚህ ወቅት በመንፈሳዊ ሕይወቱ እና በትጋቱ ለቤተ ክርስቲያን ተስፋ የነበረው፤ ለበርካታ ዓመታትም በገጠር፣ በከተማ፣ በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ እየተዘዋወረ ወንጌለ መንግሥትን ሲያስተምር የቆየው የመንፈስ ቅዱስ ልጃችን መ/ር ዘለዓለም ወንድሙ ለመንፈሳዊ አገልግሎት በተጓዘባት ሰሜን አሜሪካ ባጋጠመው ሕመም ከዚህ ዓለም ድካም በሥጋ ማረፉን ስንሰማ ታላቅ ድንጋጤ ፈጥሮብናል፡፡ በእርግጥ መምህር ዘለዓለም ወንድሙ ስመ ጥምቀቱ ወልደ ሰማእት በሥጋ ከእኛ ቢለይም ያለዋጋ የተቀበለውን የእግዚአብሔር ቃል ለምእመናን በማስተማር አደራውን በሚገባ ተወጥቶአልና በሰማይ ወደሚጠብቀው ዘለዓለማዊ ስፍራ በክብር እንደሚገባ እናምናለን፡፡ የመልካም ሰዎች መጉደል ለሀገር በተለይም ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን የነገ ዕጣ ፈንታ የሚያስጨንቅ ቢሆንም ሁሉን የሚችል አምላክ ተተኪዎችን እንዲያዘጋጅልን በመጸለይ፤ ለመንፈስ ቅዱስ ልጃችን ቤተሰቦች፣ ወዳጅ ዘመዶችና ምእመናን መጽናናትን እየተመኘን አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የአገልጋዩ ወልደ ሰማዕትን ነፍስ በመንግሥቱ ያሳርፍልን፤ “እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ” ወስብሐት ለእግዚአብሔር  ኣሜን!               አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣              የካቲት 30 ቀን 2018 ዓ.ም.                 አዲስ አበባ፣ ኢትዮጲያ

ፍቁረ እግዚእ ሚዲያ Fikure Egzi Media – FEM: የብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ሊቀ ጳጳስ ወላጅ እናት የእማሆይ አጸደ ማርያም ሥርዓተ ቀብር ተፈፀመ።  በሆሳዕና መንበረ ጵጵስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን በተፈፀመው በዚሁ የእማሆይ አጸደ ማርያም ሥርዓተ ቀብር ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሓፊን የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል። በተመሳሳይ የጠቅላይ ቤተክህነት የሥራ ኃላፊዎችና ሰራተኞች ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎችና ሰራተኞች ፣ የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎች ፣ የሀድያ ስልጤ አህጉረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎችና ሰራተኞች፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፤የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤና የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሥራ ኃላፊዎች ፤ ምእመናንና የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚሁ ጊዜ ትምህርተ ወንጌል የሰጡት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የሸካ ቤንች ማጅ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲህ ባለ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ፤ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ታጅበው በደመቀና ባማረ መርሐ ግብር መሸኘት መታደል መሆኑን ጠቁመዋል። ብፁዕነታቸው አክለውም "እናታችን አረፉ ነው የሚባሉት ሞቱ አይባልም ፤ ሞቱ የሚባሉት ሲሰርቁ ፣ ሲገሉ ፣ ሲያስለቅሱ  የኖሩ ሰዎች ናቸው ሞቱ የሚባሉት ፤ በወዲያኛው ዓለም መልካም ነገር አይቆያቸውም እና ተድላ ደስታቸውን በከንቱው ዓለም ጨርሰውታል ፤ በወዲያኛው ዓለም የሚቆያቸው ነገር የለም" ብለዋል። ከዚህ በመለስ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባና ሀድያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙትን ብፁዓን  ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንን እና ሁሉንም አካላት አመስግነዋል። በሆሳዕና መንበረ ጵጵስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን መጋቢት 2 ቀን 2018 ዓ.ም ሥርዓተ ቀብራቸው የተፈፀመላቸው የብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ወላጅ እናት እማሆይ አጸደ ማርያም ከአባታቸው ከአቶ መንገሻ ጋሻው በዛ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ እጥፍወርቅ ፈጅር  ጥር 21 ቀን 1928 ዓ.ም ተወልደው  ባደረባቸው ሕመም በተለያዩ ሆስፒታሎች በሕክምና ሲረዱ ቆይተው የካቲት 29 ቀን 2018 ዓ.ም በተወለዱ በ90 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም ማረፋቸውን ታሪካቸው ያስረዳል። 

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤           ❤ #መጋቢት ፪ (2) ቀን። ❤ እንኳን #ለኒቅዮስ_ኤጲስቆጶስ ለአቅፋስ ከተማ ሹም ለሆነ ለዮልስዮ ስሙ አውካሪስጦስ የሚባል እጆቹና እግሮቹ ሽባ የሆነ ልጅ ለፈወሰው ለታላቁ አባት #ለአባ_መከራዊ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና ለሮሀ አገር ለሆነ የተሰወረውን ለሚያይ #ለቅዱስ_ጎርጎርዮስ ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ለአባ_መከራዊ፦ይህም አባት በግቡጽ ደብቡ ከምትገኝ ከእስሙናይ ከታላላቆቹቿ ወገን ነው። ለኒቅዮስ ከተማም ኤጲስቆጶስነት ተሾመ። የስደቱና የመከራ ወራት በሆነ ጊዜም ስሙ ዮፋንስ የሚባል መኰንን ወደዚያች አገር ከንጉሥ ተልኮ መጣ። የክርስቲያን ወገኖችንም ያሠቃይ ዘንድ ጀመረ። የዚህንም የቅዱስ ኤጲስቆጶስ አባ መከራዊን ዜና ሰምቶ ወደርሱ ያመጡት ዘንድ ወታደሮቹን ላከ እርሱም ወደ መኰንኑ ከመሔዱ በፊት ወደ ቅዱስ መሠዊያው ገባ እጆቹንም ዘርግቶ ጸለየ። ንዋየ ቅዱሳቱንና የመቅደሻውን ልብሶች በመቅደሱ ውስጥ አኖረ። ከዚያም በኋላ ቤተ ክርስቲያን ይጠብቅ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ ማለደ። በላያችሁ የጽዮን ልጅ ደጆች ሆይ ለእግዚአብሔር ቤት ማገልጊያ የሆነ ንዋየ ቅድሳቱን ጠብቁ እያለ ታላቅ ልቅሶ በማልቀስ ጮኸ። ❤ ከዚህም በኋላ ከንጉሥ መልክተኞች ጋራ ወጥቶ ሔደ። ወደ መኰንኑም ቀረበ። ስለ ስሙና ስለ አገሩ ስም ስለ ሥራውም ጠየቀው። የኒቅዮስ ከተማ ኤጲስቆጶስ እንደሆነም ባወቀ ጊዜ እንዲገርፉትና እንዲያጐሳቁሉት ብርና እርሳስም አቅልጠው በአፉ እንዲጨምሩ አዘዘ። እግዚአብሔር የሚያጸውና የሚያስታግሠው ሆነ። ያለ ጉዳትም በጤንነት መልሶ ያነሳው ነበር። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ገዥ ወደ ኄርሜኔዎስ ሰደደው። እርሱም ቅዱስ አባ መከራዊን እንዲአሥሩት አዘዘ። ❤ እግዚአብሔር በእጆቹ ብዙዎች ድንቆች ተአምራትን አደረገ ከአተአምራቱም አንዱ ለአቅፋስ ከተማ ሹም ለሆነ ለዮልስዮ ስሙ አውካሪስጦስ የሚባል እጆቹና እግሮቹ ሽባ የሆነ ልጅ ነበረው አባ መከራዊም በላዩ ጸለየ። ከደዌውም አዳነው። ከዚህ በኋላ በዮልዮስ ቤት ቀድሶ ለአማንያን ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ስለ ሥጋውም እንዲአስብና ገድሉንም እንዲጽፍለት ከዮልዮስ ጋር ስምምነት አደረገ። ❤ መኰንኑ ኄርሜኔዎስ አባ መከራዊ ስለ አደረጋቸው አስደናቂ ተአምራት በሰማ ጊዜ በተለያየ ሥቃይ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ። ሕዋሳቶቹ እስቲቆራረጡ በመኰራኵሮች ውስጥ አስገብተው  አሠቃዩት። ለነጣቂዎች አንበሶችም ጣሉት በባሕርም አሠጠሙት በእሳት ምድጃ ውስጥም ጨመሩት። ቅዱስ አባ መከራዊ በሥቃዩ ሁሉ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የሚታገሥና የሚጸና ሆነ። ጌታም ያለጉዳት መልሶ በጤንነት ያስነሣው ነበር። ❤ የእመቤታችን የድንግል ማርያም ቤተ ክርቲያን የምታገለግል አንዲት ድንግል እኅትም ነበረችው። ሁለት ወንድምችም ነበሩት የአንደኛው ስም ዮሐንስ የሁለተኛውም ይስሐቅ ይባላል በእሥርቤትም ሳለ ወደርሱ መጡ አንተ ስለ አባታችን ፈንታ አባት ሁነኸን ነበር፤ እነሆ የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ ትተኸን ትሔዳለህ እያሉ በፊቱ አለቀሱ። እርሱም አጽናንቶ ወደ ቤቶቻቸው አሰናበታቸው። ❤ ዮልዮስም "የዚህን ሽማግሌ ሞት በጽሑፍ እዘዝ ከእርሱም ታርፋለህ"ብሎ መኰንኑን መከረው። ቃሉንም ተቀብሎ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊል ተቀዳጀ። ዮልዮስም የቅዱስ አባ መከራዊን ሥጋ ወስዶ በከበሩ በወርቅ መስቀል አደረገ ወደ አገሩ ወደ ኒቅዮስም ከአገልጋዮቹ ጋራ ሰደደው። መልካም ነፋስም ሆኖላቸው መርከቢቱ ፈጥና ሔደች፤ በከተማውም በር አንጻር ደርሳ ቆመች። ቀዛፊዎችም ሊያንቀሳቅሱዋት ፈልገው ነበር ግን አልተቻላቸውም አብዝተው በደከሙም ጊዜ ሥጋዬ በውስጡ እንዲኖር እግዚአብሔር የፈቀደው ቦታ ይህ ነው የሚል ቃል ከበድኑ ወጣ። ይህንንም ለአገር ሰዎች ንገሩአቸው የሰሌን ዝንጣፊም እየያዙ ወደርሱ መጡ በአገራቸውም ውስጥ እርሱ በመረጣት ቦታ እስከ አኖሩት ድረስ በታላቅ ክብር ተሸክመው ወሰዱት። ❤ መላው የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ ሠላሳ አንድ ሆነ። መጻሕፍትን እስከተማረ ድረስ ስምንት ዓመት በዲቁና ሹመት ሃያ አራት ዓመት፤ ከዚያም ቅስና ተሹሞ በቅስና አገልግሎት ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ከዚያም በኋላ ኤጲስቆጶስ ሁኖ ተሾመ። በዚያም ስልሳ ዘጠኝ ዓመት ኑሮ መልካም ተጋድሎውን ፈጸመ። የሕይወትን አክሊልንም ከክብር ባለቤት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርሰቶስ ዘንድ ተቀበለ። ጸሎቱ በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘላለም ይኑር አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የሮሀ_አገር_የተሰወረውን_የሚያይ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ፦ ይህም ቅዱስ ሰው አስቀድሞ ዐመፀኛና ኃጥእ ነበር። ከዚህም በኋላ ተመልሶ መነኰሰ። የጻድቃንን ማደሪያና ብዙ ዋጋቸውን የኅጥአንንም ኵነኔና አየራሱ የሆኑ ሥቃያቸውን እግዚአብሔር እስከ አሳየው ድረስ ብዙ ተጋደለ እግዚአብሔር በጸሎቱ ይማረን አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት2 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለጎርጎርዮስ አመ ፃመወ ወተግሀ። መልዕልተ ደብር ዘሀገረ ሮሀ። መካነ ኃጥአን ብካየ ወመካነ ጻድቃን ፍሥሐ። ዘበበፆታሁ ነጺሮ ብዙኃ። ለእለ ውስተ ምድር ሰበከ ንስሐ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_2።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አፉሁ ለጻድቅ ይትሜሐር ጥበበ። ወልሳኑ ይነብብ ጽድቀ። ወሕገ አምላኩ ውስተ ልቡ"። መዝ 36፥30-3። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 1፥8-18፣ 1ኛ ዮሐ 1፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 8፥14-26። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥20-31። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ  ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ወራትና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።                 

#የብፁዕ_አቡነ_ሕርያቆስ_ወላጅ_እናት_እማሆይ_አጸደ_ማርያም_ዐረፉ መጋቢት ፩/፳፻፲፰ ዓ/ም የብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ እና ሀዲያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወላጅ እናት እማሆይ አጸ
#የብፁዕ_አቡነ_ሕርያቆስ_ወላጅ_እናት_እማሆይ_አጸደ_ማርያም_ዐረፉ መጋቢት ፩/፳፻፲፰ ዓ/ም የብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ እና ሀዲያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወላጅ እናት እማሆይ አጸደ ማርያም ከድካመ ሥጋ ዐረፉ። በሀዲያ ሆሳዕና ከተማ ልጆችን ወልደው በክብር ያሳደጉ ከመሆናቸው በላይ "በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከብዙ ሚሊዮኖች ለአንድ የሚታደለው የሊቀ ጵጵስና ማዕረግ ያገኙትን ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስን ለቤተ ክርስቲያን ዐሥራት አድርገው ያበረከቱ ታላቅ እናት ናቸው። ሥርዐተ ቀብራቸው በሀዲያ ሆሳዕና ከተማ በነገው ዕለት እንደሚፈጸም ተገልጿል። ኦ እግዚኦ አዕርፍ ነፍሰ አመትከ አጸደ ማርያም ሀገረ ሕይወት መንግሥተ ሰማያት ያውርስልን። በአብርሃም በይስሐቅ በያዕቆብ ዕቅፍ ያኑርልን። ለብፁዕ አባታችን እና ለቤተሰቦቻቸው እግዚአብሔር አምላክ መጽናናትን እንዲያድልልን የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ይመኛል።

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ #የተባረከ_የመጋቢት_ወር_ቀኑ_ዐሥራ_ሁለት ሲሆን ከሌሊቱ ሰዓት ጋር ትክክል ነው። ከዚህም በኋላ ይጨምራል።             ❤ #መጋቢት ፩ (1) ቀን። ❤ እንኳን #ላሜህንም_ለወለደው ለኄኖክ ልጅ #ለማቱሳላ_ለዕረፍቱ መታሰቢ በዓል፣ ለኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #ለአባ_በርኪሶስ_ለዕረፍቱ በዓልና #ለሰማዕቱ_ቅዱስ_እለእስክድሮስ_ለመታሰቢያ_በዓሉ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከመታሰበው፦ #ከቅዱስ_መርቆሬዎስ ከመታሰቢያ በዓሉ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                     ✝ ✝ ✝ ❤ #የኄኖክ_ልጅ_ማቱሳላ፦ ዕድሜውም ዘጠኝ መቶ ስልሳ ዘጠኝ ዓመት ሆነ። በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ አባ በርኪሶስ፦ ይህም አባት ክርስቲያኖችን በሚወዳቸው በቄሣር እለእስክድሮስ ዘመን መንግሥት ተሹሞ ሳለ ሐዋርያት ሲጠብቋቸው እንደነበር በበጎ አጠባበቅ ሕዝቡን ጠበቃቸው። ከጥቂት ቀን በኋላ እለእስክድሮስ ሞተ ከእርሱም በኋላ ቄሣር መክስምያኖስ ነገሠ። ክርስቲያኖችንም በጽኑ መከራ አሠቃያቸው ከእርሳቸውም ብዙዎችን ገዳላቸው። አገሮቻቸውን ትተው የተሰደዱም አሉ። ይህም አባት ሸሽቶ ወደ ገዳም ገባ ሕዝቡም ፈልገው አጡት። ከዚህም በኋላ ስሙ ዲዮስ የተባለ ሌላ ኤጲስቆጶስ በላያቸው ሾሙ። እርሱም በጥቂት ቀን ዐረፈ። ከዚያህ በኋላ ስሙ አግርንዲኖስ የሚባል ሌላ ኤጲስቆጶስ ሾሙ። የስደቱም ወራት በአለፈ ጊዜ ይህ አባት በርኪሶስ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ተመለሰ። አግርንዲኖስ የሚባል ሌላ ኤጲስቆጶስ ሹመው አገኛቸው። ወደርሳቸውም በደረሰ ጊዜ ሕዝቡ በመምጣቱ ደስ አላቸው አግርንዲኖስም ተልመሶ በመንበረ ጵጵስናው ላይ እንዲቀመጥ ለመነው በታላቅ ድካምም በወንበሩ ላይ አስቀመጡት። አግርንዲኖስም ዐረፈ። ❤ አባ በርኪሶስም እጅግ እስኪያረጅና እስኪደክም ድረስ ኖረ ወገኖቹንም ሌላ ኤጲስቆጶስ በላያቸው እንዲሾሙ ለመናቸው እነርሱም አይሆንም አሉ። በዚያም ወራት የቀጰዶቅያ ኤጲስቆጶስ ስሙ እለእስክድሮስ የሚባል አንድ ሰው ነበር። እርሱም በውስጥዋ ሊጸልይና ወዳገሩ ሊመለስ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ። ሥራውንም በጨረሰ ጊዜ የበዓሉም ቀኖች በተፈጸሙ ጊዜ ወዳገሩ ሊመለስ ወደደ። በመድኃኒታችን ትንሣኤ በዓል በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ መግቢያ ወደ ዕገሌ ደጃፍ ውጡ ወደ ደጃፋ መጀመሪያ የሚገባውን ያዙት፤ በጵጵስና ሥራም ይረዳው ዘንድ ከበርኪሶስ ጋር አድርጉት የሚል ቃል እንሆ ተሰማ። ወጥተውም ወደ ደጃፋ በደረሱ ጊዜ እለእስክድሮስን አገኙት ይረዳውም ዘንድ ያለ ፈቃዱ ከአባት በርኪሶስ ጋራ አደረጉት። እስከሚአርፍበትም ጊዜ አብሮት ኖረ። መላ የሕይወቱ ዘመን አንድ መቶ ዐሥራ ሰባት ዓመት ሆነ ኤጲስቆጶስነት ሳይሾም ሰማንያ አንድ ዓመት ኖረ በሹመቱም ላይ ሠላሳ ስድስት ዓመታትን ኖረ። እግዚአብሔር አገልግሎ መጋቢት1 በሰላም አረፈ። ጸሎቱና በረከቱ ከእኛ ጋር ለዘላለሙ ይኑር አሜን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_እለእስክድሮስ፦ ይህም ቅዱስ ሰማዕት የሮሜ አገር ሰው ነው ለእርሱ ባለመታዙና ለረከሱ ጣዖቶቹ ባለመሠዋቱ ከሀዲው መክስምያኖስ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው። እጅግ ከባድና ታላቅ የሆነ ደንጊያ በእጆቹና በእግሮቹ ላይ አሥሮ ሰቀለው። ብዙ ግርፋትንም ገረፈው ጐኖቹንም ቀደደ በፊቱም ላይ እሳት መብራት ጨመሩ። ሥቃዩንም ባልፈራ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕቲትን አክሊል ተቀዳጀ። የፈጣሪው በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት1 ስንክሳር።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አንተ ውእቱ ዘታገብእ ሊተ ርስትየ። አሕባለ ወረዉ ሊተ የአኀዙኒ። ወርስትየሰ እኁዝ ውእቱ ሊተ"። መዝ 15፥5-6። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ጢሞ 2፥1-17፣ ያዕ 1፥5፥15 እና የሐዋ ሥራ 15፥1-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥17-26። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም  የጾም ወራትና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።                  

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #የካቲት ፴ (30) ቀን። ❤ እንኳን #ለታላቁ_ነቢይ፣ ሰማዕት፣ ሐዋርያ ፣ካህን #ለመጥምቀ_መለኮት_ለቅዱስ_ዮሐንስ ሕግ አፍራሽ በሆነ በንጉሥ ኄሮድስ እጅ አንገቱን ከተሰየፈ በኋላ አንገቱ ክንፍ አውጥታ በዓለም ላይ በመዞር ዐሥራ አምስት ዓመት አስተምራ ከዐረፈች በኋላ በዓረቢያ ምድር #የከበረች_ራሱ_ለተገኘችበት ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ከሚታሰበው፦ ከእስክድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ከአባ_ሚናስ ከመታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የመጥምቁ_ቅዱስ_ዮሐንስ_የከበረች_ራሱ መገኘት፦ ይህም እንዲህ ነው ከሐዲ ኄሮድስ የከበረ ዮሐንስን ራሱን ይቆርጡት ዘንድ በአዘዘ ጊዜ በእሥር ቤት ራሱን ቆርጠው ወደ ኄሮድስ አቀረቧት እርሱም ለወገኖቹ በማሳየት በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ስለ አደረገው ሥራ እደሚያዝን ገለጠላቸው የክብር ዮሐንስንም ራስ በቤቱ ውስጥ አስቀራት። ❤ የፊተኛዪቱ ሚስቱ የንጉሥ አርጣ ልጅ ግን በአበረራት ጊዜ ወደ አባቷ መጥታ በፊቱ አለቀሰች ኄሮድስ በእርሷ ላይ ያደረገውን ሁሉ እርሷን አሳዶ የወንድሙን ሚስት ኄሮድያዳን እንዳገባ ነገረችው። በዚያንም ጊዜ ንጉሥ አርጣ ተቆጥቶ ተነሣ ሠራዊቱንም ሰብስቦ ወደ ገሊላ ዘመተ የገሊላንም አገሮች ሁሉ አጠፋ በእሳትም አቃጠለ። ❤ ንጉሥ ጢባርዮስ ቄሣር ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ኄሮድስ በአባረራት በልጁ ምክንያት ንጉሥ አርጣ ይህን እንዳደረገም በአስረዱት ጊዜ ስለዚህ ንጉሥ ጢባርዮስ ቄሣር ተቆጣ ኄሮድስንም ወደ ሮሜ ከተማ ወደርሱ አስቀረበው በእርሱም ምክንያት የአገሮች ጥፋት በመደረጉና ታላቁን ነቢይም ስለ መግደሉ ከሹመቱ ሻረውና እንድልኩ ወደሚባል አገር አጋዘው በዚያም በክፉ አሟሟት ሞተ። ❤ የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ግን በኄሮድስ ቤት ተቀብራ ትኖር ነበር ከዚህም በኋላ ንጉሥ ጢባርዮስ ጭፍሮቹን ልኮ የኄሮድስን ቤት አስፈረሰ ጥሪቱን ሁሉ ወሰደ ለሚያየውም ሁሉ አርአያና ተረት ሆነ ያለ ጣሪያና ያለ ደጃፍ ቀርቷልና ነጋዴዎችም መነሃሪያ አድርገው ያድሩበት ነበር። ❤ በዚያንም ወራት በገንዘብ ድኆች በሃይማኖት ባለጸጎች የሆኑ ሁለት ሰዎች ነበሩ እነርሱም ሊሰግዱ የከበረች የአርባ ቀን ጾምንም ሊጾሙ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዙ ይህም ከብዙ ዘመን በኋላ ነው። ምሽትም በሆነ ጊዜ ምድረ በዳ በሆነ በኄሮድስ ቤት ውስጥ አደሩ ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሳቸው ለአንዱ በሕልም ተገለጠለትና የከበረች ራሱ ያለችበትን ቦታ አስረዳው ወደቤቱም ተሸክሞ ይወስዳት ዘንድ አዘዘው በነቃም ጊዜ ራእይን እንዳየ ለባልንጀራው ነገረው። ቅዱስ ዮሐንስም ወደአመለከተው ወደዚያ ቦታ ተነሥተው በአንድነት ሔዱ በቆፈሩም ጊዜ የሸክላ ዕቃ አግኝተው ከፈቷት ያን ጊዜ እጅግ የሚመስጥ በጎ መዓዛ ወጣ የቅዱስ ዮሐንስንም ራስ አገኙዋት ከእርሷም ተባረኩ ወደ ሸክላው ዕቃ መለሱዋትና በፊቱ እንደ ነበረ አፉን ዘጉ ያም ሰው ከእርሱ ጋር ወደ ቤቱ ወሰዳት ታላቅ ክብርንም አከበራት ሁል ጊዜም የሚያበሩ መብራቶችን በፊቷ አኖረ። ❤ የዚያም ሰው ዕረፍቱ በቀረበ ጊዜ ለእኅቱ ነገራት እርሷ ቅድስና ስለአላት እርሱ ሲሠራው እንደነበረ ትሠራ ዘንድ አዘዛት እርሷም የምታከብራትና ሁል ጊዜ መብራትንም የምታበራ ሆነች። የቅዱስ ዮሐንስም ራስ ወደ አርዮሳዊ ሰው እስከ ደረሰች ድረስ ከአንዱ ሰው ወደ አንዱ ሰው የምትፋለስ ሆነች ይህም ሰው በከሀዲው አርዮስ እምነት ውስጥ እያለ የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ድንቆች ተአምራቶችን እንደምታደርግ ያስብ ነበር። ❤ የከበረ ዮሐንስም ከእርሱ የሚበልጥ ሰው በላዩ አስነሣበትና በዚያ ቦታ አሳደደው ያም ቦታ አባ ቄርሎስ በኢየሩሳሌም  አገር አባ አንያኖስ በአገረ ኀምዳ ኤጲስ ቆጶስነት እስከ ተሾሙ ድረስ ፈጽሞ ሰው የማይኖርበት ምድረ በዳ ሆነ። ቅዱስ ዮሐንስም ለአባ አንያኖስ በሕልም ተገልጦ የከበረች ራሱ ያለችበትን ቦታ ነግሮ አመለከተው አባ አንያኖስም ሒዶ እንደ ዛሬው ግንቦት ሠላሳ ከዚያ አወጣት ይህም የካቲት ሠላሳ ቀን ከአገኙዋት በኋላ ዳግመኛ ያገኙበት ነው። ❤ እንዲህም የሚል አለ የከበረ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ተናገረ ይህም ኄሮድስ በአዘዘ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ በእሥር ቤት ሳለ ራሱን በሰይፍ ቆርጠው በጻሕል አድርገው ወደ ኄሮድስ አመጡለት እርሱም ለኄሮድያዳ ልጅ ሰጣት እርሷም ለእናቷ ወስዳ ሰጠቻት። ይቺም የረከሰች አመንዝራ ልትዳስሣት በወደደች ጊዜ በወጭቱ ውስጥ ጠጒሩዋ ተዘርግቶ ወደ አየር በረረች በአየርም ሁና "የወንድምህን ሚስት ልታገባ አይገባህም" እያለች የምትጮኸ ሆነች እንዲህም እያለች ዐሥራ አምስት ዓመተት ኑራ በዓረቢያ ምድር ዐርፋ በዚያ ተቀበረች። ❤ ነጋድያንም በዚያ ቦታ የሚድሩ ሆነ በእግዚአብሔርም ፈቃድ ሁለት አማንያን ነጋዴዎች ወደዚያ ቦታ ደርሰው አደሩ ቅዱስ ዮሐንስም በሕልም ተገለጠላቸውና የከበረች ራሱን ያወጡ ዘንድ አዘዛቸው እነርሱም አወጡዋት ከእርሳቸውም ጋር ቤታቸው ወስደው ታላቅ ክብር አከበሩዋት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም መለኮትን በአጠመቀ በከበረ ቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን ልዩ የሆነች በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የካቲት 30 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_እብል_ለእርስከ_ክቡር። ዘተረክበ ዮም በንዋየ ጽቡር። #ዮሐንስ_ሠራሪ_ንጉሠ አዕዋፍ ንስር። ንሥአኒ በክነፊከ ወአዕድወኒ ለገብር። ከመ ኢያስቆቁ ቀዊምየ በጽንፋ ለባሕር"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የየካቲት_30።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ገሥፆሰ ገሠፀኒ እግዚአብሔር። ወለሞትሰ ባሕቱ ኢመጠወኒ። አርኅው ሊተ አናቅጸ ጽድቅ"። መዝ 117፥18። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 4፥7-ፍ.ም፣ 2ኛ ጴጥ 1፥19-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 13፥24-32። የሚነበበው ወንጌል ማር 6፥21-34። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ወራት። ለሁላችንም ይሁንልን።                   

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለዐቢይ_ጾም_አራተኛ_ሳምንት_ለመፃጒዕ እግዚአብሔር አምላክ በሰላም በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የመፃጒዕ_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፭ "#አምላኩሰ_ለአዳም_ለዕረፍት_ሰንበተ_ሠርዐ ወይቤልዎ አይሁድ በዓይ ሥልጣን ትገብር ዘንተ #ወይቤሎሙ_ኢየሱስ አነ እገብር አንትሙኒ እመኑ በግብርየ #አነ_ውእቱ_እግዚኣ_ለሰንበት_ወልድ_ዋሕድ ወይቤሎሙ ብውህ ሊተ ኅድግ በዲበ ምድር እስብክ ግዕዛነ ወእክሥት አዕይንተ ዕውራን አቡየ ፈነወኒ"። ትርጉም፦ #የአዳም_አምላክ_ሰንበትን_ለዕረፍት ሠራ፤ አይሁድ በምን ሥልጣን ይህን ታደርጋለህ አሉት፤ #ኢየሱስም_በራሴ_ሥልጣን_አደርጋለሁ፤ እናንተ ግን በሥራዬ እመኑ፤ #እኔ_የሰንበት_ጌታ_ነኝ፤ እኔ ወልድ ዋሕድ በምድር ላይ ኃጢአትን ይቅር እል ዘንድ፤ ነጻነትን እሰብክ ዘንድ #የዕውራንን_ዐይን_አበራ_ዘንድ የባሕርይ አባቴ ላከኝ አላቸው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #መፃጒዕ፦ አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት "መጻጒዕ" ይባላል። ፀግ0 ፤መጻጕዕ፦ በቁሙ ጎባጣ በጀርባው ላይ እንደ ሻኛ ያለው ደረቱ ከጉልበቱ የተጠጋ ሕመምተኛ በሽተኛ ማለት ነው። ❤ በዚህ ሣምንተ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድውያንን መፈወሱን ዕውራንን ማብራቱን የሚያነሳ መዝሙር ይዘመርበታል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጌትነቱ ምልክት በሕዝቡ ያሉ ድውያንን ሁሉ ይፈውስ ነበር። የተአምራቱም ዜና በሶርያ በአራቱ ማዕዘን ደረሰ ተብሎ በተነገረው መሠረት ቅዱስ ማቴዎስ 4፥23-25 አንደጻፈው ቀጥለን እናያለን በማቴ 8 ፥1-4 ከተራራ በወረደ ጊዜ ብዙ ሕዝብ ተከተሉት ለምጻም ቀርቦ ጌታ ብትወድስ ልታነፃኝ ትችላለህ እያለ ሰገደለት እጁንም ዘርግቶ ዳሰሰውና ንፃ አለው ወዲያውም ለምፁ ነፃ። በማቴ 8፥5-13 የመቶ አለቃውን ልጅ በቃሉ ፈወሰ፣ የጴጥሮስ አማት ከንዳድ ፈወሳት። በማቴ 8 ፥14 አጋንንት አወጣ ማቴ 8፥16ና በማቴ 8፥28 በዚህ ተአምራት የምንረዳው ቁም ነገር በሰዎች ያደሩ አጋንንት ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅ ብለው ማመናቸውን ነው። የሐዋ 19÷15፤ ያዕ 2÷19። ❤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፈወሳቸው ሕሙማን ብዙ ሲሆኑ ለምሳሌ ያህል ከላይ በጠቀስነው በማቴዎስ ምዕራፍ 8 ያሉትን እንዳዳነ ሁሉ በሌሎች ወንጌላውያን ምዕራፍና ቁጥርም በርካታ በሽተኞችን እንደፈወሰ ተገልጿል ከተፈወሱት ሰዎች መካከል የኻያ ሦስቱ ታሪክ ተገልጦአል ከእነርሱ ሌላ ኢየሱስ ሦስት ሙታንን አስነስቶአል አንደኛ የኢያኢሮስን ሴት ልጅ (ማቴ 9፥18-26) ሁለተኛ የመበለቲቱን ልጅ ፈወሳት (ሉቃ 7÷11-17) ሦስተኛውም ደግሞ አልዓዛር (ዮሐ 11፥43-44)፡፡ ❤ ክርስቶስ በአምስት አይነት መንገድ ሕሙማን ፈወሰ። 1) በቃሉ (ማቴ8፥16፡፡ ዮሐ 4÷50) 2) በመዳሰስ (ማቴ 8፥} ፣ ሉቃ 5÷13) 3) እጅ በመጫን(ማር 6፥5፣ 8፦22) 4) ጭቃን በመቀባት (ዮሐ 9÷6-7) 5) በልብሱ ጫፍ (ማቴ9፥20፡፡ 14፥36) ❤ እግዚአብሔር ፈዋሽ ነው (ዘጸ 15፥26) ፈዋሽነቱ ለሁሉ ቢሆንም በሰፊው የሚነገረው ግን በዮሐ 5÷5-15 ያለ በሽተኛ ነው። ይኸውም ኋላ ጌታችን ኢየሱስን በጥፊ የመታው ነው ብለው ሊቃውንት ይተረጉማሉ (ዮሐ 18፥22)። ምንጭ፦ ከመምህረሰ አምኃ ሥላሴ (መኩርያ ተስፍዬ) ፌስቡክ ገጽ የተወሰደ።                                                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር ይረድኦ ውስተ ዐራተ ሕማሙ። ወይመይጥ ሎቱ ኵሎ ምስካቢሁ እምደዌሁ። አንሰ እቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ"። መዝ 40፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 5፥1-ፍ.ም፣ ያዕ 5፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 3፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 5፥1-25። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበት (መፃጕዕ)ና የጾም ወራት። ለሁላችንም ይሁንልን።                  

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #የካቲት ፳፱ (29) ቀን። ❤ እንኳን #ለአርሞኒ_አገር_ኤጲስቆጶስ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ለደረሰ ለከበረ #ለአባ_ቢላካርዮስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከእመቤታችን_ከቅድስት_ድንግል_ማርያም በሥጋ ከመወለዱ ከክብር ባለቤት #ለጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ_ከልደቱ_ከበዓለ_ወልደ በዓል መታሰቢያ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ቢላካርዮስ፦ ይህም አባት ፈጽሞ እስከ አረጀ ድረስ በተሾመበት ወንበር ብዙ ዘመናት ኖረ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትንም ደረሰ እሊህም ስለከበረች የልደቱ በዓልና ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ስለ ሞትና ስለ መቃብር፣ በኃጥአንም ላይ ስለ ሚደርስባቸው ሥቃይ፣ ስለ መድኃኒታችንም የረቀቀ ጥበብ ስለ ከበሩ በዓላትም ናቸው። ሕይወት በሆኑ ትምህርቶቹም ብዙ ነፍሳትን መሥዋዕትን አድርጎ ለእግዚአብሔር አቀረበ። ❤ በክርስቲያንም ወገኖች ላይ የስደትና የመከራ ወራት በሆነ ጊዜ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ስም ደሙን ሊያፈስ ወደደ ሕዝቡንም ሰብስቦ "በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ" አዘዛቸው ስለ ጌታችን ኢየሱስ ደሙን ሊያፈስ ይሻልና እነርሱ እንግዲህ "ፊቱን እንደማያዩት" ነገራቸው። ሰምተውም አለቀሱ ስለ መለየታቸውም እጅግ አዘኑ "የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ ለምን ትተውናለህ" አሉት። ማስቀረትና ማስተውም ባልተቻላቸው ጊዜ ከእርሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ መኰንኑ ሔደ በፊቱም ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ታመነ መኰንኑም ብዙ አሠቃየው። ❤ ሕዝቡም ብዙ ልመናን አብዝተው ለመኑት "ራስህን አድን ከከተማም ውጣ" አሉት እርሱም ልባቸውን ደስ ያሰኝ ዘንድ "በሥውር እወጣለሁ"አላቸው። በዚያች ሌሊት "ሰማዕትን ትሆን ዘንድ የተመኘኸውን በጎ ምክር ለምን ረሳህ" እንደሚለው ሰው ሁኖ ራእይን አየ። ከዚያም በኋላ ተመልሶ ለመኰንኑ ተገለጠለት በዚያንም ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ መኰንኑ የካቲት29 ቀን አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ሥጋውንም ምእመናን አንሥተው ወሰዱት ለኢጲስቆጶሳትም እንደሚገባው አክብረው ገንዘው በመቃብር አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ቢላካርዮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የየካቲት29 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_እብል_ለልደትከ_መድምም። እምድንጋሌ ሥጋ ኅቱም። #ኢየሱስ_ክርስቶስ_መድኃኔዓለም። ልብየ አንቅሕ ለስብሐቲከ አዳም። ለሥጋየሰ አኀዞ ድካም"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የየካቲት_29።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወኢሰምዑኒ ሕዝብየ ቃልየ። ወእስራኤልኒ ኢያፅምዑኒ። ወፈነውኩ ሎሙ በከመ ምግባሮሙ። መዝ 80፥11-12 ወይም መዝ 2፥7-8። ። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 22፥1-5 ወይም ሉቃ 2፥1-21።                                            

❤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጣላት በልጅዋ ምክንያት ስለ ደረሰባት ሀዘኖች አውርታላታለች፡፡ የፈለገችውንም እንድታደርግበት በእጅዋ ያለውን መስቀል ለቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ሰጥታታለች፡፡ በዚህም መስቀል ባሕር ከፍላ ደቀ መዛሙርቶቿን አሻግራለች፡፡ ❤ እናታችን የአባታችን የአባ ኤዎስጣቴዎስን ገድል በማንበብና በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል እርዳታ ባሕሩን በአጽፏ ተሻግራ ወደ አገረ ናግራን ሄዳለች፡፡ እንዲሁም በበትረ መስቀል እንደ ዘርዐ ቡሩክ ከባሕር ውስጥ የሰጠሙ የደቀ መዛሙርቶቿን መጻሕፍት ምንም ሳይሆኑ ማውጣት ችላለች፡፡ በሁሉም አገር እየዞረች ቅዱሳት መካናትን ትሳለም ነበር፡፡ ደብረ ደሞ ሄዳ "ሴቶች መውጣት አይችሉም" ቢሏት በሀዘን ስታለቅስ ቅዱስ ሚካኤል በሥውር ወስዶ አድርሷታል፣ አቡነ አረጋዊም ተገልጸውላት ባርከዋታል በዚያም ሥጋ ወደሙን ተቀብላለች፡፡ ❤ እናታችን ወደ ኢየሩሳሌምም ሄዳ ቅዱሳት መካናትን እየተሳለመች ለ7 ዓመታት ቆይታለች ቅዱስ ሚካኤልም በዓምደ ብርሃን እየመራት ተመልሳ ወደ አገራችን መጥታ በድጋሚ ከሱስንዮስ ጋር ተሟግታለች፡፡ ሙታንንም እያስነሳች እንዲመሰክሩላት ብታደርግም እርሱ ግን ከጥፋቱና ከክህደቱ ሊመለስ አልቻለም ነበር፡፡ የተለያዩ ተአምራትን በማድረግ መልእክቷንም በንስር አሞራ አድርጋ እየላከች ትመክረው ነበር ፡፡ ❤ በአንድ ወቅትም በአገራችን እህል መታጣት ሆነና ቅድስት እናታችን ዝክር የምታደርግበት እህል አጣች፡፡ደናግል ልጆቿንም ጠርታ ትንሽ ዱቄት እንዲያመጡላት ነግራቸው በእርሱ ጸሎት አድርጋበት "ወደ ቦታው መልሱት" አለቻቸው፡፡ በማግስቱም እንሥራው ጋኑ ሁሉ በዱቄት ተሞልቶ አግኝተውታል፡፡ የካቲት ኪዳነ ምሕረትንም በዓል በደስታ አክብረዋል፡፡ ❤ መልአኩም ከቅድስት አገር ኢየሩሳሌም መልሶ ወደ ኢትዮጵያ ካመጣት በኋላ ዛሬ ገዳሟ ካለበት ቦታ ስትደርስ ከቦታዋ ላይ ዓምደ ብርሃን ተተክሎ በቀስተ ደመና ተከቦ አይታ "ይህች ቦታ ምንታምር" ብላ ጠራቻት፡፡ በቦታውም ላይ በመድኃኔዓለም ትእዛዝ የቅድስት ኪዳነ ምሕረትን ቤተ ክርስቲያን በአንዲት ቀን ታህሣሥ14 ቀን በዕለተ ዓርብ ጧት በሰንሰል (በስሚዛ) እንጨት ጀምራ ማታ እንደተፈጸመ በ3ኛው ቀን እሁድ ታህሣሥ16 ቀን ቅዳሴ ቤቱ ሲከበር በድርገት (በቁርባን) ጊዜ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያምና ከእልፍ አእላፋት መላእክት ጋር ወርዶ መቅደሱን ሲባርክ መቅደሱ በ4ቱ ማዕዘን ለጌታ ሰገደ። ለጌታ እንደ ሰገደ ዛሬም ድረስ ይታያ፡፡ ❤ ጌታችንም "ይህ መቅደስሽ ሳይፈርስ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ይቆይልሻል፡፡ በዚህ ቦታ ሥጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ ኃጢአቱ ይሰረይለታል፡፡ በምድርም ስምሽን የጠራ፣ መታሰቢያሽን ያደረገ፣ የገድልሽን መጽሐፍ የጻፈ፣ ያጻፈ፣ ያነበበ፣ የተረጐመ ሁሉ ዓይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልቡና ያልታሰበውን ለነዚህ ሁሉ ዋጋቸውን እሰጣቸዋለሁ፡፡ ከሩቅም ከቅርብም ከቀኝም ከግራም መጥቶ መቅደስሽን ለተሳለመ ሁሉ እስከ 12ትውልድ ድረስ እምርልሻለሁ፡፡ላልምረው ቦታችን አላስረግጠውም፡፡ በረከቴም በእሱ ላይ በልጆቹም በንብረቱ ላይ ለዘለዓለሙ ይኖራል፡፡ ስለጾምሽ፣ ስለጸሎትሽ፣ ስለተጋድሎሽ፣ ስለ ስግደትሽ ሰባት አክሊል ሰጠሁሽ" አላት፡፡ ❤ ፃድቋ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ብዙ ገድል በሠራችበት ብዙ መነኰሳይያትን በአቋቋመችበት ገዳሟ በእመ ምዑዝ ኪዳነ ምሕረት ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ አንድነት ገዳም የካቲት29 ቀን ዐረፈች። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከቅዱሳን መላእክት ከጻድቃን ከሰማዕታት ጋር መጥቶ ነፍሷን ተቀብሎ ወደ ገነት ወስዶ አኖራት፡፡ ባረፈች ጊዜ በሥጋዋ ላይ ታላቅ የብርሃን ዓምድ ተተክሎ የታየ ሲሆን እንደ ፀሓይም ከጠዋት እስከ ማታ ያበራ ነበር፡፡ በመካነ መቃብሩዋም ላይ እስከ አርባ ቀን ድረስ ብርሃን ተተክሉ ታይቷል፡፡ ምንጭ፦ገድለ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ። ከእናታችን ከቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከት ያሳትፈን። በጸሎቷም ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ።                 

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #የካቲት ፳፱ (29) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊቷ_ጻድቅ በአጤ (ዐፄ) #ሱሱንዮስ አንገቷን ተሰይፈ ሰማዕት ከሆነች በኋላ #ቅዱስ_ሚካኤል ገነትንና ሲኦልን አሳይቶ 14ቀን በሰማያዊት ኢየሩሳሌም ከተቀመጠች በኋላ እንደገና እንደተኛ ወይም ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ከሞት ተነስታ ብዙ ገዳማትን (ታላቁን ገዳም ራማ ኪዳነ ምሕረትን) ላቀናች #ለታላቋ_ለጻድቅ_ወሰማዕት_ለቅድስት_ፍቅርተ_ክርስቶስ (እመ ምዑዝ) ለዕረፍቷ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #ጻድቅ_ወሰማዕት_ቅድስት-ፍቅርተ_ክርስቶስ (እመ ምዑዝ)፦ በጎንደር ክፍለ አገር ደራ ፎገራ አንበሳሜ ወረዳ ልዩ ስሙ አቡነ ሐራ ገዳም አጠገብ ኮክታ ማርያም ተብሎ በሚጠራው ቦታ ውስጥ ተወለደች፡፡ዛሬም ይህ አካባቢ እመ ምዑዝ መንደር ይባላል፡፡የአባቷ ስም ቅዱስ ላባ የእናትዋ ስም ቅድስት ወንጌላዊት ይባላል፡፡ እነዚህም ወላጆቿ እጅግ ደጋግ ሰዎች እግዚአብሔርን የሚፈሩ ለተራበ፣ ለተጠማ የሚያዝኑና የሚራሩ እንደ አብርሃምና እንደ ሣራ በጎ ምግባር ያላቸው ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን በረከት ሁሉ በሥራ ላይ የሚያውሉ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ልጅ ስላልወለዱ ወደፈጣሪያቸው ወደ እግዚአብሔር ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የለመኑትን የማይነሳ የነገሩትን የማይረሳ ቸር አምላክ ስለሆነ እንደ ቅድስት ሐና እመ ሳሙኤል ጸሎታቸውን ሰምቶ የተመረጠች ደግ ሴት ልጅ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ በሚያዚያ 4 ቀን ተፀንሳ ታኀሣሥ29 ቀን ከእነሱ ተወለደች፡፡ ስመ ጥምቀቷ ማርያም ጸዳላ የዓለም ስሟ ሙዑዚት ሲሆን ሙዑዚት ማለት ጣፋጭ ማለት ነው፡፡ (ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ደግሞ የቆብ ስሟ ነው።) ❤ በተወለደችም ጊዜ በእግርዋ ቆማ "በማኀየዊ ቸርነትህ ከጨለማ ወደ ብርሃን ላወጣኸኝ ለአብ ምስጋና ለወልድ ምስጋና ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል" ብላ አመሰገነች ከእግዚአብሔር የተላከ መነኵሴም ወደ እርሷ በመሄድ የዳዊትን መዝሙር፣ መጻሕፍትንና የቤተክርስቲያንን ትምህርት በሚገባ አስተምሯአታል፡፡ ❤ ቅድስት እናታችን አምላኳን አስከ መጨረሻው በድንግልና ማገልገል ብትፈልግም ዕድሜዋ ከፍ ሲል ቤተሰቦቿ ዘርዐ ክርስቶስ ከሚባል አገረ ገዥ ጋር በቤተክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል አጋቧት ፡፡ እርሷ ግን በጫጉላ ቤት ሳሉ በእኩለ ሌሊት ባሏን "ወንድሜ ሆይ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውን ነገር ድንግልናችንን እንጠብቅ" አለችው፡፡ እርሱም "እሺ" ብሏት ይህንን ተመካክረው በጸሎት ሲተጉ አደሩ፡፡ ለእግዚአብሔር እየተገዙ በጾም በጸሎት በንጽሕናና በድንግልና ኖሩ በሌሊትም ወደ፡ባሕር ውስጥ እየገቡ ጸሎት ያደርጉ ጀመር፡፡ በመጨረሻም እርሷ በጳጳሱ በአባ ማርቆስ እጅ ስትመለኵስ ባሏም ድንግልናውን እንደጠበቀ በሰማዕትነት አንገቱን ተሰይፎ አርፏል፡፡ እርሷ በነበረችበት ዘመን ንጉሥ ሱስንዮስ "ሁለት ባሕርይ" የሚለውን የረከሰ የሮማውያንን ሃይማኖት ሕዝቡ ሁሉ እንዲያምን በማወጁ ምክንያት በአገራችን ከፍተኛ የሆነ የሃይማኖት ግጭት ስለተነሣና ከ8ሺህ በላይ ክርስቲያኖች በግፍ ተጨፍጭፈው ሲያልቁ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ከእነ አቡነ ስምዖንና ከሌሎችም ቅዱሳንና ቅዱሳት ጋር ተሰልፋ ሰማዕትነትን ተቀብላ ለሃይማኖትዋ ምስክር ሆናለች፡፡ ባለቤቷ ዘርዐ ክርስቶስም በሰማዕትነት ዐርፎ ሰባት አክሊላት ወርደውለታል፡፡ ❤ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ሱስንዮስ በአደባባይ ሲያስገርፋቸው ሥጋቸው እየተቆራረጠ መሬት ላይ የወደቀውን የሰማዕታቱን ሥጋቸውን ሰብስባ "ይህን ለንጉሡ እጅ መንሻ ስጡልኝ" ብላ ላከችለት፡፡ "ይህ የሃይማኖ ፍሬ ነው፡፡ እኛስ አስከአሁን በሃይማኖታችን አለን፣ አንተ ብትገለን መከራም ብታደርስብን ሃይማኖታችንን አልካድንም፡፡ ነገር ግን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቸርነቱ ከሞት አስነሣን ይህን የሥጋዬን ቁራጭና የእህቶቼን የደናግላንን ሥጋ ብላው ፣ ደማችንን ጠጣ ሃይማኖትህ የከፋ፣ ሰነፍ፣ የረከስህ ነህ" ብላ ልካለታለች፡፡ መልእክተኞቹም ለንጉሡ ወስደው ሰጥተውታል፡፡ ሱስንዮስ አዋጁን እንዳወጀ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ስምዖንም ካህናትንና ክርስቲያን ልጆቻቸውን አነሳስተው እያስተማሩና እያጠነከሩ እያለ በጦር ተወግተው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ ❤ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ስምዖን በሰማዕትነት ከማረፋቸው በፊት ግን እነ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ፣ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስን፣ ቅድስት አካለ ክርስቶስን፣ ቅድስት እመ፡ወተትን ... ወዘተ አነሳስተው ንጉሡን መክረውታል፣ ገሥጸውታል፣ ንጉሡ ግን ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይልቁንም ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን የሃይማኖቷን ጽናት ስላየ ሥጋዋ እየተቆረሰ መሬት ላይ እስኪወድቅ ድረስ በብረት በትር አጥብቆ ያስገርፋት ጀመር፡፡ በመጨረሻም ምድር እየሰወረቻት ለመግረፍ የማይመቻቸው ቢሆን ከሌሉቹ ሰማዕታት ጋር አንገቷን በሰይፍ አስቆርጦታል፡፡ በዚህም ጊዜ ፍጹም ጨለማ ሆኖ ምድርም ተነዋወጠች፡፡ ስምንት ሺህ ዐሥር ቅዱሳንም በሰማዕትነት ዐረፉ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን አንገቷን በሰይፍ ቢቆርጧትም ነገር ግን ቅዱስ ሚካኤል ገነትንና ሲኦልን አሳይቶ 14ቀን በሰማያዊት ኢየሩሳሌም ከተቀመጠች በኋላ እንደገና እንደተኛ ወይም ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ከሞት አስነሥቶ ወደ ቦታዋ መለሳት፡፡ ❤ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ቅዱስ ሚካኤልም ከሞት ካስነሣት በኋላ መናኝ ሆና በየገዳሙና በየአድባራቱ እየሄደች ዓለምን ስትዞር ያቀናቻቸው ብዙ ገዳማት አሉ፡፡ ለምሳሌ ከተሰዓቱ ቅዱሳን አንዱ በሆኑት በአባ ጉባ ተመሥርታ በግራኝ ወረራ ጠፍታ የነበረችውን ራማ ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳምን አቅንታ የወንድና ሴቶች መነኰሳት በጋራ አብረው ይኖሩ የነበረ ቢሆንም የበጎ ሥራ ጠላት የሆነው ሰይጣን በማኀበረ መነኰሳቱ መካከል ሊፈጥር ያለውን ክፉ ፈተና ለእናታችን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተገልጾላት በገዳሟ ውስጥ የወንዶችና የሴቶች መነኰሳት መኖሪያ የተለያየ እንዲሆን አድርጋለች፡፡ ❤ ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌምም በመሄድ ላይ ሳለች በመንገድ ሰውን የሚበሉ ፍጡሮች ወደሚኖሩበት አካባቢ ስትደርስ 60 የሚሆኑ አገልጋዮቿን ለመብላት ይዘው ሳር ቅጠል እንዲበሉ በማድረግ ዓይናቸውን በጉጠት በማውጣት ለወራት በጨለማ ቤት ውስጥ ዘጉባቸው ሰይጣንንም ያመልኩ ነበርና ከ4 ወራት በኋላም በዓል አድርገው ለመብላት ከእሳት ውስጥ ጨመሩአቸው፡፡ እነርሱ ግን ምንም አልሆኑም፡፡ ያን ጊዜም "እናንተ ሰዎች ምንድን ናችሁ?" ብለው ጠየቋቸው፡፡ ቅድስት እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስም ክርስቲያን መሆናቸውንና እነርሱ የሥላሴ ሕንጻ የሆነውን የሰውን ልጅ መብላት እንደሌለባቸው ብትመክራቸው "ምን እንበላለን?" አሏት፡፡ እርሷም ከራማ ኪዳነ ምሕረት ስትነሳ የእህል ዘርን ለአገልጋዮቿ አስይዛ ስለነበር ከዚያ ስንዴ ወስዳ ዘራችው፡፡ስንዴውም በአንድ ቀን ተዘርቶ በቅሎ፣ ታጭዶ፣ ደርቆ፣ ተፈጭቶ ለምግብነት በቅቷል፡፡ ቅድስት እናታችንም ቀምሳ ስታቀምሳቸው እንደማር እንደ ወተት የሚጣፍጥ ሆኖላቸው በደስታ ተመግበውታል፡፡ ከዚያም እንደዚህ እያደረጉ እየሠሩ እንዲበሉ አስተምራ አስጠምቃቸው ስድስት አብያተ ክርስቲያናትን አሠርታላቸዋለች፡፡ወንጌልን፣ ስንክሳርን፣ ሃይማኖተ አበውን፣ ግንዘትን፣ መዝሙረ ዳዊትን፣ አርጋኖንን ሁሉ በእጅዋ ጽፋ አስቀመጠችላቸው፡፡

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤           ❤ #የካቲት ፳፰ (28) ቀን። ❤ እንኳን #ለአርእስተ_አበው_ለቅዱሳን #ለአብርሃም_ለይስሐቅና_ለያዕቆብ ለበዓላቸው መታሰቢያና #ለሮማዊ_ቅዱስ_ቴዎድሮስ በነገሥታት መክሲሞስና መክስምያኖስ ዘመን ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱስ_ቴዎድሮስ_ማኅበር ከሆኑ #ስድስት_ሺህ_ሦስት_መቶ_አራት ሰዎች በሰማዕትነት ከዐረፉ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                          ✝ ✝ ✝ ❤ #ሮማዊው_ሰማዕቱ_ቅዱስ_ቴዎድሮስ፦ እርሱም ከእስያ አውራጃ አስጢር ከሚባል አገር ነው። ይህንንም ቅዱስ በነገሥታት ዘንድ አማልክትን በማምለክ እርሱ እንደማይስማማ ወነጀሉት በዚያንም ጊዜ አስጠርተው "ለአማልክት ለምን አትሰግድም" አሉት፡እርሱም "እኔ ክርስቲያን ነኝ ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አላመልክም" ብሎ መለሰላቸው። የበርብዮስጦስ፡ ልጅን ጉሥም "ለአማልክቶቼ ብትገዛ በጭፍራዎቼና በመኳንቶቼ ሁሉ ላይ አለቃ አድርጌ እሾምሃለሁ ብዙ ወርቅና ብር የከበሩ ልብሶችንም እሰጥሃለሁ" አለው ቅዱስ ቴዎድሮስም "ወርቅህና ብርህ ለጥፋት ይሁንህ እኔስ በንጉሤ በሕያው እግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ባለጸጋና አለቃ ነኝ" አለው። ❤ ንጉሥም "ለአምላክህ ልጅ አለውን?" አለው የከበረ ቴዎድሮስም "አዎን ከመለኮቱ ባሕርይ የተገኘ ከእርሱ ጋር ዓለምን የፈጠረ በእውነት ልጅ አለው" ብሎ መለሰለት ንጉሡም "አምላክህን ብናውቀው ልናገኘው እንችላለን" አለው ቅዱስ ቴዎድሮስም "ወደርሱ ከተመለስክ እንደ እኔ ጭፍራ ትሆናለህ የተወደደ መሥዋትም ያደርግሃ" አለው። ንጉሡም "ነገር አታብዛ ብዙ ገንዘብ እሰጥ ዘንድ ለአማልክቶቼ መሥዋዕትን አቅርብ እንጂ" አለው የከበረ ቴዎድሮስም ንጉሡን ረገመው ጣዖታቱንም ሰደበ በዚያንም ጊዜ ንጉሡ ተቆጣ። ልብሱንም እንዲገፉት በትምህርቱም ከአመኑ አሕዛብ ጋር በጨለማ ቤት ያሥሩት ዘንድ አዘዘ። የከበረ ቴዎድሮስም ጸለየ በሌሊትም ወጣ ዕንጨቶችንም ሰብስቦ ጣዖቶችን ሁሉ አመድ እስኪሆኑ ድረስ አቃጠላቸው እንዳይሰሙ በአገልጋዮቻቸው ላይ እግዚአብሔር ከባድ እንቅልፍ አሳድሮባቸዋልና። ❤ ለንጉሡም በነገሩት ጊዜ አጽንቶ አሠረውና ልዩ ልዩ በሆነ በጽኑ ሥቃይ አብዝቶ ያሠቃየው ዘንድ ለመኰንኑ ሰጠው መኰንኑም እንዲህ አለው "ለንጉሥ ለምን አትሠዋም" የከበረ ቴዎድሮስም "እኔስ ለረከሱ አማልክት አልሠዋም ለከሀዲ ንጉሥም አልታዘዝም" ብሎ መለሰለት። መኰንኑም ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ከወንበሩ ላይ ተነሥቶ እንደ ነብር ተወርውሮ አንገቱን አነቀውና የከበረ ቴዎድሮስን በምድር ላይ ጥሎ ፊቱን ጸፋው በእግሮቹም ረገጠው እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ላከለት መኰንኑንም ገድሎ ከምድር ዐዘቅት አሠጠመው ለከበረ ቴዎድሮስም በእስያ አገር ውስጥ እየተዘዋወረ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት እንዲአስተምር መንፈሳዊ ፀዓዳ ፈረስ ሰጠው። ንጉሡም ይህ በሰማ ጊዜ የከበረ ቴዎድሮስን ከነፈረሱ እንዲይዙት በትምህርቱም የአመኑትን ሁሉ እንዲገድሉ መቶ ፈረሰኞች ወታደሮቹን ላከ። ከሴቶችና ከልጆች በቀር ስድስት ሺህ አርባ ስምንት ሰውን ገደሉ። ሊይዙትም ወደ ቅዱስ ቴዎድሮስ በደረሱ ጊዜ ፈረሱ በላያቸው ተወረወረ ከአፉም እሳትን አውጥቶ አመድ እስኪሆኑ አቃጠላቸው ነገር ግን ሌሎች አግኝተው ያዙትና ወደ ንጉሥ ወሰዱት እርሱም ወደ እሥር ቤት እንዲአስገቡት እንዳይበላና እንዳይጠጣም ደጃፎችን እንዲዘጉበት አዘዘ። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጸለትና ቃል ኪዳን ሰጠው በዚያንም ጊዜ ከእሥር ቤት አውጥተው ዘቅዝቀው ሰቀሉት ደሙ እንደ ውኃ እስቲፈስ ከላም ቆዳ በተሰራ ጅራፍ ገረፉት ደሙ የነካቸውም ብዙ በሽቶኞች ዳኑ ተዓምራቱንም ያዩና የሰሙ በጌታችን አመኑ በዚያችም ቀን መቶ አርባ ስምንት ሰዎች ተገደሉ። እሊህን የተገደሉትንም ሰማዕታት ወደ እሳት ማደጃ ውስጥ ከእርሱ ጋር ጨመራቸው በዚያንም ጊዜ ነፋስ ነፈሰ መብረቅና ነጐድጎድም ሆነ እሳቱንም አቀዝቅዞት የከበረ ቴዎድሮስ ምን ሳይነካው ከእሳት ውስጥ ወጣ። ❤ ከዚህም በኋላ ንጉሡ የሚያደርግበትን በአጣ ጊዜ ኃምሳ አራት ልጥር የሚመዝን ልጓም አምጥተው አፉን እንዲለጒሙት እግሮቹንና እጆቹንም በችንካር ቸንክረው ለአንበሳ እንዲጥሉት አዘዘ። አንበሳውም እንባውን እያንጠባጠበ እንደ ሰው አለቀሰለት እንጂ ምን አልነካውም ጌታችንም ተገለጠለትና ስሙን ለሚጠራ፣ መታሰቢያውን ለሚያደርግ፣ ገድሉንም ለሚጽፍ እድል ፈንታውም ከእርሱ ጋር በመንግሥተ ሰማያት ያደርግ ዘንድ ቃል ኪዳን ሰጠው ከዚህም በኋላ የሁለት መቶ ሰው ሸክም እንጨት፣ መቶ ልጥር ባሩድ፣ መቶ ልጥር የዶሮ ማር፣ መቶ ልጥር ነሐስ አመጡ ከማንደጃውም ጨምረው እጅግ እስከሚግል አነደዱት ጸሎቱንም ከፈጸመ በኋላ ቅዱስ ቴዎድሮስን ወደ ነደደው እሳት ወረወሩት ምስክርነቱንም የካቲት28 ፈጸመ። ❤ የመላእክት አለቆች ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ነፍሱን ተቀበሉት በሦስት አክሊላትም አቀዳጁት ሥጋውንም አውሳብያ የተባለች የመኰንኑ ሚስት ወሰደች ዋጋው ብዙ በሆነ ሽቱም ገነዘችውና ወደ ገላትያ ወሰደችው በዕብነ በረድ ሣጥንም አድርጋ በዚያ ቀበለችው ቤተ ክርስቲያንም ሠራችለት ከሥጋውም ታላላቆች ድንቆች ተዓምራቶች ተገለጹ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቴዎድሮስ በጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላላሙ አሜን። ምንጭ፦ የካቲት 28 ስንክሳር።                                                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለክሙ_አምዓት_ስሳ። ወበበዐሠርቱ ሠላሳ #ማኅበራነ_ቴዎድሮስ_ማር_መኵሴ_ቴዎድሮስ ዕጓለ አንበሳ። እምኂሩትክሙ ብየ ኃሠሣ። ታናሕስዩ ሊተ ክቡደ አበሳ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የየካቲት_28።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዘሠርዓ ለአብርሃም። ወመሐለ ለይስሐቅ። ወአቀመ ስምዐ ለያዕቆብ"። መዝ 104፥9። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥8-22፣ ያዕ 3፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 7፥1-17። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 20፥37-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ወራት። ለሁላችንም ይሁንልን።