ar
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

إظهار المزيد
636
المشتركون
-124 ساعات
-37 أيام
-1330 أيام
أرشيف المشاركات
🌹 በዚያንም ጊዜ ሮማኖስ መኰንኑን እንዲህ አለው "እነሆ ስንፍናህን እዘልፍ ዘንድ ፈጣሪዬ አፌን ከፈተ እውነት ነገርን ብታውቅ ለእግዚአብሔር እንሰግድ ዘንድ ይገባ እንደሆነ ወይም ለአማልክት እንዲነግረን ሕፃን ልጅ እንዲአመጡ እዘዝ" መኰንኑም ታናሽ ሕፃንን እንዲአመጡ አዘዘ መኰንኑም ሕፃኑን "ስግደት ለማን እንዲገባ ዕውነቱን ንገረን" አለው። ሕፃኑም "ልብ የሌለህ ደንቆሮ መኰንን በአንዲት ቃል ዓለሙን ሁሉ ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር ስግደትና አምልኮ እንዲገባ አታውቅምን" አለው። 🌹 መኰንኑም ሕፃኑን ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ የሕፃኑም እናት ልታየው መጣች ሕፃኑም እናቱን "ተጠምቻለሁና ውኃ አጠጭኝ" አላት። እናቱም "ልጄ ሆይ ከዚህ ውኃ የለም ነገር ግን ወደ ሕይወት ውኃ ሒድ" አለችው። 🌹 በዚያንም ጊዜ የሕፃኑን ራስ በሰይፍ እንዲቆርጡ የቅዱስ ሮማኖስንም ምላሱን ከግንዱ እንዲቆርጡ መኰንኑ አዘዘ። ያን ጊዜ መኰንኑን ይዘልፍ ዘንድ ለአባ ሮማኖስ ረቂቅ አንደበት ተሰጠው ሲዘልፈውም መኰንኑ ሰምቶ ምላሱ እንዳልተቆረጠ ተጠራጠረ። ወታደሩንም ጠርቶ "ምላሱን ያልቆረጥክ ለምንድን ነው" አለው ወታደሩም "የምላሱን ቁራጭ ያመጡ ዘንድ እዘዝ" አለው አምጥተውለትም አይቶ መኰንኑም ወደ ወህኒ ቤት አስገብተው በዚያ አንቀው እንዲገድሉት አዘዘ። እንዲህም ምስክርነቱን ፈጽሞ የምስክርነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም  በመስተጋድል በመኰስ ቅዱስ ሮማኖስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይረውዩ እምጠለ ቤትከ። ወትሠቅዮሙ እምፈለገ ትፍሥሕትከ። እስመ እምኀቤየ ነቅዐ ሕይወት"። መዝ 35፥8-9 የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 1፥7-12፣ 1ኛ ጴጥ 1፥6-10  እና የሐዋ ሥራ 20፥30-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 22፥15-22። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ ቴዎፍሎስ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።             

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፲፰ (18) ቀን። 🌹 እንኳን #ለእስክድርያ_ሃያ_ሦስተኛ_ሊቀ_ጳጳስ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ቴዎፍሎስና ክርስቲያኖችን በአሳደደ በመኰንን አስቅልጵያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ለዐረፈ ለከበረ #ለመነኰስ_ቅዱስ_ሮማኖስ ለዕረፍታቸው በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከሰማዕት_ቅዱስ_ዮሐንስ፣ #ከቅዱሳን_አድራኒ_ከአርቴማዎስ_ከአርስጦስ #ከሉዲኖስ_ከአስማኒትና _ከሰባቱ ልጆቿ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                            ✝ ✝ ✝ 🌹 #የእስክንድርያ_ሃያ_ሦስተኛ_ሊቀ_ጳጳሳት #አቡነ_ቴዎፍሎስ፦ ይህም አባት ንጉሥ ቴዎዶስዮስ በነገሠ በስድስተኛ ዓመት ተሾመ በወንጌላዊ ማርቆስም ወንበር ሃያ ስምንት ዓመት ኖረ። 🌹 በዘመኑ ብዙ መጻሕፍትን የተረጎመ ከእሳቸውም የወንጌላዊ ዮሐንስን ራእይና የሐዋርያ ጳውሎስን መልእክት የተረጎመ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ተነሣ ዳግመኛም ለደሴተ ቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ የሆነ ኤጲፋንዮስ ነበረ። 🌹 በዘመኑም ሰባቱ ደቂቅ ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዓመት ከአንቀላፉ በኋላ ተነሡ። ይህም አባት የሐዋርያዊ ሊቀ ጳጳሳት አባት አትናቴዎስ ደቀ መዝሙር ነው የቤተ ክርስቲያንንም መጻሕፍትና ሥርዓቱን ሁሉ እየተማረ በእርሱ ዘንድ አደገ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጢሞቴዎስም በዐረፈ ጊዜ ይህ አባት በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ አዋቂና አስተዋይም ስለሆነ ስለ ፍቅር ስለ ርኅራኄ ከንሰሐ በፊት ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል መጠበቅ ስለ ሚገባ ስለ ሙታን መነሣትና ለኃጥአን ስለ ተዘጋጀ ስለዘላለማዊ ሥቃይ ሌሎችም ጠቃሚ የሆኑ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ። 🌹 ቅዱስ ቄርሎስም ለዚህ አባት ቴዎፍሎስ የእኅቱ ልጅ ነው እርሱም በበጎ አስተዳደግ አሳደገው የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት አስተማረው።ከዚያም በኋላ ወደ አባ ሰራብዮን ላከው አባ ሰራብዮንም መንፈሳዊ ተግባርን ሁሉ አስተማረው። 🌹 በአትናቴዎስም ዘመን አስቀድሞ እንዲህ ሆነ "በጎ ዘመን ባገኝ ይህን ኮረብታ ባስጠረግሁት ነበር። ለከበሩ ለመጥምቁ ዮሐንስና ለነቢይ ኤልሳዕም ቤተ ክርስቲያን በሠራሁም ነበር" ሲል ይህ አባት ቴዎፍሎስ አባ አትናቴዎስን ይሰማው ነበር። በሹመቱ ወራትም ይህን ነገር አስታውሶ የሚያዝንና ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን የሚጸልይ ሆነ። 🌹 በዚያ ወራትም ባሏ ብዙ ገንዘብ ትቶላት የሞተ አንዲት ባለጸጋ ሴት ከሮሜ አገር መጣች ሁለት ልጆቿም ከእርሷ ጋር አሉ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስንም ሲያዝን አየችውና "ክብር አባት ሆይ ምን ያሳዝንሐል" አለችው። እርሱም "ብዙ ወርቅ በዚህ ኮረብታ ውስጥ እያለ ድኆች ይራባሉና" አላት እርሷም "አንተ ስለ እኔ ጸልይ እኔም አስጠርገዋለሁ" አለችው። 🌹 ይህንንም ብላ ያን ኮረብታ አስጠረገችው በውስጡም በደንጊያ ሠሌዳ እየአንዳንዱ የተከደኑ ሦስት ሣጥኖች ተገለጡ። በላያቸው ቴዳ ቴዳ ቴዳ የሚል ተጽፎባቸዋል አባ ቴዎፍሎስም በአየው ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ምሥጢራቸውን አውቆ "ቴዳ ማለት የጌታ ስም ነው ይህም ለድኆች ይገባል" አለ "ሁለተኛውም ቴዳ የንጉሥ ቴዎዶስዮስ ነው ሦስተኛውም ቴዳ ቴዎፍሎስ ማለት ነው። የእኔ ገንዘብ ስለሆነ በዚህም አብያተ ክርስቲያናትን እሠራለሁ" አለ። እሊህም ሣጥኖች በመቄዶንያዊው ፊልጶስ ልጅ በንጉሥ እስክንድር ዘመን እንደ ተቀበሩ የዘመን ቊጥር ተገኘ እርሱም ሰባት መቶ ዘመናት ነው። 🌹 ከዚህም በኋላ ያን የወርቅ ሣጥን ለንጉሥ ቴዎዶስዮስ ላከለት ስለዚያም የወርቅ መዝገብ አስረድቶ ቦታውን መጥቶ እንዲያይ አሳሰበው እርሱም በመርከብ ተጭኖ ወደ እስክንድርያ አገር መጥቶ ሁሉንም አየ የዚያንም ወርቅ እኵሌታ መለሰለት አባ ቴዎፍሎስም ብዙዎች አብያተ ክርስቲያንን ሠራ። አስቀድሞም በቅዱሳን በመጥምቁ ዮሐንስና በነቢይ ኤልሳዕ በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራ ሥጋቸውንም ከእስራኤል አገር አፍልሶ አምጥቶ በውስጧ አኖረ እርሷም የታወቀች ናት ዴማስ በሚባል ቦታ ሁለተኛም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በሀገሩ ምሥራቅ በኩል ሠራ ከዚህም በኋላ በሊቀ መላእክት ሩፋኤል ስም በደሴት ውስጥ ሠራ ሌሎችንም ብዙዎች አብያተ ክርስቲያን አሳነፀ። 🌹 ንጉሡም አብያተ ክርስቲያናትን ለመሥራት ያለውን የሊቀ ጳጳሳቱን ፍቅር አይቶ በግብጽ አገር ያሉትን የጣዖታት ቤቶችን ሁሉንም ሰጠው እርሱም ተቀብሎ አፈረሳቸውና በቦታቸው አብያተ ክርስተከያናትንና የእንግዶች ቤቶችን ሠራ ሁለተኛም ምድራቸውን ሁሉ ሰጠው። ይህም አባት ቴዎፍሎስ የክርስትና ጥምቀትን በሚያጠምቅ ጊዜ የብርሃን በትረ መስቀል በሚጠመቁት ላይ በመስቀል ምልክት ሲያማትብ ያይ ነበር። 🌹 ይህ አባት ቴዎፍሎስና ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ልጆች በሆኑበት ጊዜ ሁለቱም በአንዲት ሌሊት አንዲት የሆነች ራእይን እነርሱ እንጨቶችን እንደሚለቅሙ አዩ። ከእነርሱም አንዱ ንጉሥ እንደሚሆን ሁለተኛውም ሊቀ ጳጳሳት እንደሚሆን ያቺን ራእይ ተረጎሟት እንዲሁም ሆነ። ይህም አባት ቴዎፍሎስ ሊቀ ጵጵስና በተሾመባት በመጀመሪያዪቱ ዓመት ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ሃይማኖትን እናስተምራለን የሚሉ ሁሉ ሃይማኖታቸውን በመጽሐፍ ጽፈው ወደርሱ እንዲአቀርቡ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ። 🌹 ከዚህም በኋላ ንጉሡና ሊቀ ጳጳሳቱ ተነሥተው እነዚያን ጽሑፎች በመሠዊያው ላይ አድርገው ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ ጌታም ወልድ በመለኮቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ትክክል ነው ብሎ ከሚታመን በቀር ከውስጣቸው በቀናች ሃይማኖት የጸና እንደ ሌለ ገለጠላቸው። በዚያንም ጊዜ እሊህን የመናፍቃን መጻሕፍትን እንዲአቃጥሏቸው እነዚያንም መናፍቃን ከሚገዛው አገር እንዲአሳድዷቸው ንጉሥ አዘዘ። 🌹 ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም መጻሕፍትን ማንበብና መመርመር ያበዛ ነበር ስለዚህም የአውጋርዮስን መጻሕፍት አወገዘ ያወግዙ ዘንድም ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ወደዚህ አባት ወደ ቴዎፍሎስ ወደ ቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ወደ ኤጲፋንዮስ ወደ ኤዺስቆጶሳት ሁሉ በየሀገሩ ላከ። 🌹 ከዚህም በኋላ መልካም ጒዞውን በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔርንም አገልግሎ ጥቅምት 18 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ቴዎፍሎስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                                                        ✝ ✝ ✝ 🌹 #መነኰስ_ቅዱስ_ሮማኖስ፦ ይህም ቅዱስ ክርስቲያኖችን በአሳደደ በመኰንን አስቅልጵያኖስ ዘመን ሰማዕት የሆነ ነው። የክርስቲያን ወገኖችን መኰንኑ እንዳሳደዳቸው በሰማ ጊዜ ከቀሳውስትና ከዲያቆናት ጋር የክርስቲያን ወገኖችን ሁሉ በአንድነት ሰበሰባቸው ስለ ክርስቶስ ሃይማኖትም መክሮ አጸናቸው። 🌹 አስቅልጵያኖስም ይህን ሰምቶ እንዲአመጡት አዘዘ በፊቱም በቆመ ጊዜ አስቅልጵያኖስ "በወገን የከበርክ ሮማኖስ አንተ ነህን?" አለው ቅዱሱም "የወገን ክብር ምን ይጠቅመኛል ክብሬ ግን ክርስቶስ ነው" ብሎ መለሰለት። መኰንኑም ሰምቶ እንዲሰቅሉትና ጉንጮቹን ይሰነጣጥቁ ዘንድ አዘዘ ጉንጮቹንም ሲሰነጣጥቁት ምንም አልተናገረምና መኰንኑ ትዕግሥቱን አደነቀ።

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹                           ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_ለእስጢፋኖስ_በኵረ_ሰማዕታት #ሊቀ_ዲያቆናት ዐምደ ሃይማኖት #ቅድስተ_ሥላሴ ዘርእየ በዐይኑ ወልዱ ለአብ እንዘ ይነብር በየማኑ ተቃውሞቶ መዋግድ ዘስእኑ ነባቤ ጥበብ በልሳኑ ጽጉያተ ወጽዱላተ አቅማኀ ቃሉ ማዕከለ አይሁድ በውስተ ዐውድ ዘኮነ ሰማዕተ ወልድ"። ትርጉም፦ #የሰማዕታት_መዠመሪያ_የዲያቆናት_አለቃ፣ የሃይማኖት ምሰሶ፤ #የተለየች_ሦስትነትን_በዐይኑ ያየ፤ የአብ የባሕርይ ልጁ በቀኙ ተቀምጦ ያየ፤ መከራከሩን ጨፋጮች አይሁድ ያልቻሉ በአንደበቱ ጥበብን የሚናገር የቃሉ ፍሬዎችም ብርሃናውያትና ያበቡለት፤ በአይሁድ መኻከል በዐደባባይ ውስጥ የወልድ ምስክርን ኾኖ ለተገኘ #ለቅዱሰሰ_እስጢፋኖስ_ሰላምታ_ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በተአምኆ_ቅዱሳን_ላይ።           

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፲፯ (17) ቀን። 🌹 እንኳን #ለሀገረ_ቀምስ_ኤጲስቆጶስ #ለቅዱስ_ፊልያስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል፣ ለነቢዩ #ለቅዱስ_ሳሙኤል_እናት ለነቢይት #ለቅድስት_ሐና_ለልደቷ_መታሰቢያ_በዓል፣ #ለቅዱስ_ባስልዮስ_ወንድም_ለቅዱስ_ጎርጎርዮስ ለዕረፍቱ መታሰቢያ በዓልና #ለእስክንድር_አገር_ሠላሳ_አንደኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለቅዱስ_ዲዮስቆሮስ_ካልዕ ለዕረፍት በዓል መታሰቢያ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #በቆዳ_ገመድ_ከታሠሩ_ከደጋጋጎች ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                      ✝ ✝ ✝ 🌹 #የሀገረ_ቀምስ_ኤጲስቆጶስ_ቅዱስ_ፊልያስ፦ ይህንንም ቅዱስ በመኰንኑ ቊልቊልያኖስ ዘመን ወደ ፍርድ አደባባይ አቀረቡት ቊልቊልያኖስም "ለአማልክት ሠዋ" አለው። ፊልያስም "እኔ ከብቻው እግዚአብሔር በቀር ለአማልክት አልሠዋም" አለ። ቊልቊልያኖስም "እግዚአብሔር ምን አይነት መሥዋዕት ይሻል" አለ ፊልያስም "ቅን ትሑት የሆነ ንጹሕ ልቡናን ዕውነተኛ ፍርድን ቁም ነገርን እንዲህ ያለ መሥዋዕትን እግዚአብሔር ይወዳል" አለው። 🌹 ቊልቊልያኖስም "የምትጋደል ስለ ነፍስ ነው ወይስ ስለ ሥጋ" አለ ፊልያስም "ስለ ነፍስና ስለ ሥጋ ነው እነርሱ በአንድነት ይነሣሉና" አለ። ቊልቊልያኖስም "የምትወዳት ሚስት የምትወዳቸው ልጆች ወይም ወንድምና ዘመድ አለህን" አለው ፊልያስም "ከሁሉም የእግዚአብሔር ፍቅር ይበልጣል" አለ። ቊልቊልያኖስም "እግዚአብሔር ከበጎ ሥራ የሠራው ምንድን ነው?" አለ ፊልያስም "እግዚአብሔር ያደረገልን ይህ ነው ሰማይና ምድርን በውስጣቸው ያሉትን ሁሉ ፈጠረልን። ዳግመኛም ከጠላታችን ከሰይጣን እጅ ያድነን ዘንድ ከሰማያት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ሁኖ ተወለደ የሕይወት መንገድንም በዓለም ውስጥ ተመላልሶ አስተማረ መከራንም በሥጋው ተቀብሎ ተሰቅሎ ሞተ በሦስተኛውም ቀን ተነሥቶ በአርባ ቀን ዐረገ ዳግመኛም ለፍርድ ይመጣል ይህን ሁሉ ስለ እኛ አደረገ"። 🌹 ቊልቊልያኖስም "አምላክ ይሰቀላልን ይሞታልን?" አለ ፊልያስም "አዎን የዘላለም ሕይወትን ይሰጠን ዘንድ ስለ እኛ ፍቅር ሞተ" አለው። ቊልቊልያኖስም እንዲህ አለው "እኔ እንዳከበርኩህ ልጣላህም እንዳልፈለግሁ አላወቅህምን አንተ በወገን የከበርክ እንደሆንክ አውቃለሁና አሁንም ለአማልክት ሠዋ በክፉ አሟሟት እንዳትሞት" አለው። ፊልያስም "እኔን ደስ ማሰኘት ከወደድክ እንዲያሰቃዩኝና እንዲገድሉኝ እዘዝ" አለው በዚያንም ጊዜ በሰይፍ ራሱን እንዲቆርጡት አዘዘ። 🌹 ሊገድሉት ሲወስዱትም ዘመዶቹና የሀገር ታላላቆች ወደርሱ መጡ ለመኰንኑም በመታዘዝ ለአማልክት እንዲሠዋ እጆቹን እግሮቹን እየሳሙ ለመኑት። እርሱ ግን "የጌታዬ ክርስቶስን መከራ መስቀልን ልሸከም እሔዳለሁና እናንተ አሳሳቾች ከእኔ ወግዱ" ብሎ ገሠጻቸው። 🌹 ከሚገድሉበትም ሲደርስ ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ እጆቹን ዘርግቶ ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየ ሕዝቡን አደራ ወደ ጌታ አስጠበቀና ተሰናበተ ከዚህም በኋላ ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ፊሊያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #ቅዱስ_የባስልዮስ_ወንድም_ቅዱስ_ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፦ ይህም ቅዱስ ጎርጎርዮስ እጅግ የተማረ አዋቂ ነበረ በደሴቶችም ላይ ኤጲስቆጶስነት ተሾመ እነሆ በዚህ ወር በዐሥራ አምስት ቀን የሆነውን ከገድሉ ጥቂት እንጽፋለን። ስለርሱም እንዲህ ተባለ እርሱ መሥዋዕቱን ለማክበር በሚቀድስ ጊዜ በመሠዊያው ላይ ሲወርድ መንፈስ ቅዱስን የሚያየው ሆነ ከዚህም በኋላ ኪሩብን አየው በደረቱም ውስጥ አቀፈው በመሠዊያውም ላይ ሳለ ወደ ዝምታና ተደሞ አደረሰው ሰዎችም ሁሉ ሥጋዊ እንቅልፍ የሚያንቀላፋ ይመስላቸው ነበር። 🌹 በኤጲስቆጶስነት ሹመት ሠላሳ ሦስት ዘመናት በተፈጸሙለት ጊዜ ወንድሙ ቅዱስ ባስልዮስ ሊጠይቀው መጣ እርሱ ከተጋድሎ ብዛት የተነሣ በጽኑ ደዌ የሚታመም ሁኖ ነበርና በቅዱስ ባስልዮስ መምጣት ደስ አለው። 🌹 ቅዱስ ጎርጎርዮስም እንደ ልማዱ ሊቀድስ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ የከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያም ተገለጸችለትና "ዛሬ ወደኔ ትመጣለህ" አለችው የቊርባኑንም ቅዳሴ ሲጨርስ ሕዝቡ በቀናች ሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ ይመክራቸውና ያስተምራቸው ዘንድ ወንድሙን ባስልዮስን ለመነው እርሱም እንደሚያንቀላፋ ሆነ በቀሰቀሱትም ጊዜ ሙቶ አገኙት ቅዱስ ባስልዮስም ሣጥን እንዲሠሩለት አዘዛቸው። ጸሎታትንም በመጸለይ መዝሙራትንም በመዘመር በማመስገንም እንደሚገባ ገንዞ በመቃብር ውስጥ አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ጎርጎርዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 21 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #የእስክንድርያ_አገር_ሠላሳ_አንደኛ_ሊቀ_ጳጳሳት #አባ_ዲዮስቆሮስ_ካልዕ፦ ይህም አባት በዘመኑ ካሉ ትውልድ እርሱን የሚመስል ያልተገኘ በጠባዩ ቅን የዋህ በእውቀቱ አስተዋይ በበጎ ሥራው ፍጹም የሆነ ነው። 🌹 በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ መልእክትን ጽፎ ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጰሳት ቅዱስ ሳዊሮስ ላካት። እርሱም ልዩ ሦስት የሆኑ ሥላሴ በመለኮት አንድ እንደሆኑ እየገለጠና እያሳሰበ ነው። ስለ ወልደ እግዚአብሔርም ሰው መሆን እርሱ ፍጹም ሥጋን ነባቢትና ለባዊት ነፍስን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ነሣ በመለኮቱና በትስብእቱም አካል ያለው አንድ ልጅ እንደሆነ ከተዋሕዶውም በኋላ በሥራው ሁሉ የማይለያይ ጭማሪ ወይም ጉድለት የሌለው ነው። መልእክቱም ወደ ቅዱስ አባት ሳዊሮስ በደረሰች ጊዜ አነበባትና ፈጽሞ ደስ ተሰኘባት ለአንጾኪያም ሕዝብ አስተማረባት ሁሉም ደስ አለቸው። 🌹 ከዚህም በኋላ አባ ሳዊሮስ ለአባ ዲዮስቆሮስ የመልእክቱን መልስ እንዲህ ብሎ ጻፈ። "በኒቅያ ከተማ ተሰብስበው ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ ቅዱሳን አባቶቻችን በቀናች ሃይማኖት አጽንተው የሠሩዋትን ቤተ ክርስቲያኑን እንድትጠብቅ ለዚች ለከበረች አገልግሎት የመረጠህ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ። ዳግመኛም በዚሁ እንዲጸና ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ እንዳይል አስገነዘበው ደግሞም በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ ሕዝቡን ሁል ጊዜ አስተምራቸው" አለው። 🌹 የአባ ሳዊሮስም መልእክት ወደ አባ ዲዮስቆሮስ በደረሰች ጊዜ ደስ ተሰኘባት በሁሉ ቦታም እንዲአስተምሩባት አዘዘ ይህም አባት ሕዝቡን ሁል ጊዜ የሚያስተምራቸው ሆነ። ሁል ጊዜም ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ ያስተምራቸዋል ኤጲስቆጶሳቱንና ካህናቱንም መንጋዎቻቸውን ስለ መጠበቅ ያዛቸዋል መልካም አገልግሎቱንም አድርሶ እግዚአብሔርንም ደስ አሰኝቶ አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ዲዮስቆሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

🌹🌹🌹ማህሌተ ጽጌ ሣልሣይ 🌹🌹🌹
+9
🌹🌹🌹ማህሌተ ጽጌ ሣልሣይ 🌹🌹🌹

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹              🌹 #ጥቅምት ፲፮ (16) ቀን። 🌹 እንኳን #ለኢትዮጵያኑ_ጻድቃን ለአርባ ስምንት ዓመታት ከሰው ጋር ሳይነጋገሩ በዝምታ ብቻቸው ለኖሩ #ነብር_ሰባት_ዓመት_ውሃ_ሲቀዳላቸው ሲያገለግላቸው ለነበሩ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_አሮን_ዘአርምሞ ለዕረፍት በዓልና #በሰሜን_ሸዋ_መራቤቴ_እንሳሮ በቆላማው ክፍል የሚገኘው፤ የስውራን ግኁሳን ባሕታውያን መኖርያ የሆነውን፤ #ዓመቱን_ሙሉ_ከበሮ_የማይመታበት ታላቁ ገዳም #ጀር_ቅድስት_ሥላሴን_ለመሰረቱት ለኮከበ ገዳም ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ኢያሱ_ለዕረፍታቸው መታሰቢያ ዓመታዊ በዓል በሰላምና በጤና እግዚአብሔር አምላክ አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #አቡነ_አሮን_ዘአርምም፦ መጽሐፍ አሮን ዘከትሞ ወዘአርምሞ ይላችዋል። የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ተንቤን ነው። ለ48 ዓመታት ከሰው ጋር ምንም ሳይነጋገሩ በዝምታ ብቻ የኖሩ ታላቅ አባት ሲሆኑ ቀዳማዊ ዘኢትዮጵያ ከተባሉት የመጀመርያዎቹ ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ናቸው። ቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑ ርግብ ዕጣን ታመጣላቸው ነበር። ምግባር ቱሩፋታቸው እጅግ ያማረው እኚህ አባት በዘመናቸው ድርቅ በሆነ ጊዜ የእህል እጦት ሆኖ ሕዝቡን ሰብስበው እግዚኦታ ካደረሱ በኋላ የሀገሩን ሁሉ ጎተራ በተአምራት በእህል ሞልተው አትረፍርፈውታል። በዚህም አስገራሚ ተአምራቸው ሕዝቡንም ከችግርና ከርሃብ አድነውታል። 🌹 አቡነ መድኃኒነ እግዚአ ዘደብረ በንኰል አህያቸውን የበላባቸውን አንበሳ በአህያው ምትክ ሰባት ዓመት ውኃ እንዳስቀዱት ሁሉ አቡነ አሮንም ነብርን ሰባት ዓመት ውኃ እያስቀዱ እንዲያገለግላቸው አድርገውታል። ሌሎች የዱር አራዊትም ያገለግሏቸው ነበር። በአንድ ወቅት በሀገሩ ድርቅ ሆኖ ሰው ግማሹ ተሰዶ ግማሹ ደክሞ ስለነበር ጻድቁ ግን የዱር አራዊትን ጠርተው ሠራተኛ አድርገው በማዘዝ ጥንቸልን ውኃ በማስቀዳት፣ ጅብን ጭቃ በማስረገጥ፣ አንበሳን በአናጺነት እንዲሠራ፣ ነብርን ደግሞ አቀባይ በማድረግ እያዘዙ በማሠራት በእመቤታችን ስም እጅግ አስደናቂ ቤተ ክርስቲያን መስከረም 10 ቀን ሠርተዋል። የአቡነ አሮን ዘአርምሞ የአንድነት ገዳማቸው ትግራይ ሽሬ ውስጥ ይገኛል። ምንጭ፦ መዝነበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍና ቅዱሳን በዓላት።                            ✝ ✝ ✝ 🌹 #አቡነ_ኢያሱ፦ አስደናቂው ገዳማቸው ዛሬም በስውራን ግኁሳን ባሕታውያን የተመላ ቃል ኪዳን ያልተሻረበት ግዝት ያልተነሳበት የቅዱሳን በዓት የሆነው በሰሜን ሸዋ መራቤቴ እንሳሮ በቆላማው ክፍል የሚገኘው በመሰላል የሚወረደው ደብረ ቅዱሳን መካነ ሱባኤ ወተመስጦ ጀር ቅድስት ሥላሴ ገዳም።ገዳሙ በአፄ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት የተመሠረተ ታላቅ የምናኔ ቦታ ነው። 🌹 ለሀገር ሰላም ለሕዝበ ክርስቲያን ደሕንነት የሚጸልዮ ባሕታውያን የመሉበት ነው ዛሬም የጠመመ የሚያቀኑ ያዘነ የሚያጽናኑ ስውራን እግዚአብሔር ለፈቀደለት የሚገለጡለት ቅዱስ መካን። 🌹 ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ብዙ ገጸ በረከት የሰጡበት ፈጻሜ መንግሥት አፄ ኃይለ ሥላሴ በክቡር አባቴ ሐና ጅማ መሪነት ገዳሙ ድረስ በመሰላል ወርደው ቡራኬ የተቀበሉት በየዓመቱ የአትርሱኝ መባ የሚልኩበት በአዲስ አበባ ለገዳሙ በኪራይ የሚተዳደርበት ሱቆች አሰርተው ጃንሆይ የሰጡበት ልዕልናው ከሸዋ ገዳማት የላቀ ታላቅ ገዳም ነው። 🌹 ይህ ገዳም ዛሬ አስታዋሽ አጥቶ ቀርቷል የእግዚአብሔር ስራ ግን አልቆመበትም ብዙዎች ቦታውን በመርገጥ ከስጋ ደዌ ድነውበታል። ውድ አያቴ ልጅ በክብካብ ገብረ ማርያም ሲነግረኝ የቅርብ ቤተሰባችን የሆኑት የመራቤቴ ገዥ ክቡር ደጃዝማች ታዬ ጉልላቴ ለሞት በሚያደርስ ክፉ ሕመም ተይዘው ከለሚ በቃሬዛ ይዘናቸው ጀር ሥላሴ ገና ከግዝቱ መሬት ስንረግጥ ከአልጋው አፈፍ ብለው ተነስተዋል ነጭ የለበሰ መነኮስ "በስመ ሥላሴ ተነስ።" ሲለኝ ነቃሁ ብለው መስከረዋል። 🌹 በዘመናችን ለሳይንስ ግራ ያጋባ ተስፋ የተቆረጠበት ሕመም የታመመ ከውጭ ሐገር ሄጄ ልሙት ያለ ወንድም ሰውና ሳይንስ ሲጨርስ እግዚአብሔር ስራ ይጀምራልና ከሕመሙ ድኖ ዛሬም በሕይወት አለ። ጻድቁ ሙት ያስነሱት መስቀላቸው በእቃ ቤቱ ይገኛል። እግዚአብሔር ለፈቀደለት ብዙ የሕይወት መንገድ በሱባኤ የሚያገኝበት ስውራን ግኁሳን ተገልጠው የሚባርኩበት ነው። "መካነ ሱባኤ ወተመስጦ ጀር ቅድስት ሥላሴ ወአቡነ ኢያሱ ገዳም"። 🌹 አቡነ ኢያሱ በደብረ ሊባኖስ ገዳም የመነኰሱ ገዳማዊ ናቸው ትውልዳቸው አማራ ሳይንት ነው። ጀር ሥላሴን በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ያቀኑ ባሕታዊ ናቸው። 365 ቀን ዓመቱን ሙሉ ማሕሌት የማይቆምበት ከበሮ የማይመታበት ዓመታዊ በዓላቸው እንኳን በጽሞና በአርምሞ በቅዳሴ እና በሰዓታት የሚከብርበት እንደ ዓለመ መላእክት ኢዮር ራማ ኤረር መላእክት የሚገናኙበት ግኁሳን ባሕታውያን እንደ መብራት በርተው የሚታዮበት 24 ሰአት በምስጋና የሚታወድበት የስውራኑ ማእጠንት የሚሸትበት ቅዱስ መካን ነው።ዜና ገድላቸውን እግዚአብሔር ከተራፊ ከራሚዎቹ ይደምረንና ከእጃችሁ ይገባል የገድላቸው ገበታ ሳይገባን ያሰማን እግዚአ አለማት ሥላሴ ክብር ይግባው። የጻድቁ በረከት ይደርብን በጸሎታቸው ኢትዮጵያን ይጠብቋት ከዘረኝነት ደዌ ከፍቅር ረሐብ ከዝሙት እሳት ከምንፍቅና አሽክላ ምልጃ ጸሎታቸው ይሰውረን!። ምንጭ፦ ነገረ ቅዱሳን።             

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፲፭ (15) ቀን። 🌹 እንኳን #ለዐሥራ_ሁለቱ_ቅዱሳን_ሐዋርያት ዓለም በእጣ ለተካፈሉበት ለመታሰቢያ ቀን፣ ለቅዱስ ጳውሎስ ረድ #ለቅዱስ_ሲላስና_ለኒቆድምያ አገር ለሆነ ለሰማዕቱ ለቅዱስ ቢላሞን ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቢላሞን_ማኅበር_ከሆኑ_ከመቶ_ሃምሣ_ስምንት ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው፣ #ከሰላትዮን_ከአጥራኪስ #ከአርሞቅስ_ከአድማንያ_ከአርሚስ_ከቅድስት ጾመታ፣ #ከአባት_ኢሳይያስና_ከሐዋርያትም ከዕፍታቸው መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                           ✝ ✝ ✝ 🌹 #ከኒቆምድያ አገር የሆኑ ቅዱስ ቢላሞን፦ የዚህም ቅዱስ አባቱ ጣዖት አምላኪ ነው እናቱ ግን ክርስቲያን ናት ጥበብንም አስተማሩት ከዚህም በኋላ ስሙ አርማላስ ከሚባል ቄስ ጋር ተገናኘ። እርሱም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የቀናች ሃይማኖት አስተማረው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቀው ታላቅ የሆኑ ድንቆች ታምራትን የማድረግ ሀብትን እግዚአብሔር እስከ ሰጠው ድረስ በጾም በጸሎት ታላቅ ገድልን ተጋደለ። 🌹 በአንዲት ቀንም ለዓይኖቹ መድኃኒትን እንዲአደርግለት አንድ ዕውር ሰው ወደርሱ መጣ ቅዱስ ቢላሞንም "በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም" እያለ በዕውሩ ዐይኖች ላይ የመስቀልን ምልክት አደረገ ያን ጊዜ ዐይኖቹ ድነው አየባቸው ጤነኛም ሆነ። ንጉሥም ዐይኖቹ የተገለጡለትን የዚያን ዕውር ዜና በሰማ ጊዜ ወደርሱ አስቀረበውና "ዐይኖችህን ማን አዳነህ?" ብሎ ጠየቀው እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት "ቅዱስ ቢላሞን ፈወሰኝ እርሱ እጁን በዐይኖቼ ላይ አድርጎ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ እያለ በመስቀል ምልክት አማተበብኝ ያን ጊዜ አየሁ" ይህንንም ብሎ"እኔ ክርስቲያን ነኝ" እያለ በንጉሡ ፊት በግልጽ ጮኸ። ንጉሡም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡት የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። 🌹 ከዚህም በኋላ ወታደር ልኮ ቅዱስ ቢላሞንን አስቀረበው ስለ ሃይማኖቱም በጠየቀው ጊዜ እርሱም "ክርስቲያን ነኝ" ብሎ በፊቱ ታመነ ንጉሡም ብዙ ሽንገላን በመሸንገል አባበለው። ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት ባልሰማውም ጊዜ በእርሱ ላይ ተቆጥቶ ድምፁን ከፍ አድርጎ "ካልሰማኸኝ እኔ ጽኑ ሥቃይን አሠቃይሃለሁ" አለው። ቅዱስ ቢላሞንም "እኔ ከሥቃይህ የተነሣ ፈርቼ ሃይማኖቴን ለውጬ ፈጣሪዬን አልክድም" አለው። 🌹 ከዚያችም ቀን ጀምሮ በብዙ አይነት ሥቃይ በብዙ ቀኖች ውስጥ ማሠቃየትን ጀመረ። በግርፋት በስቃላትም በባሕር ስጥመትም ወደ እሳት በመወርወርም የሚያሠቃይበት ጊዜ አለ። በዚህም ሥቃይ ውስጥ ሳለ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጠመቀው ቄስ በአርሜላዎስ አምሳል ተገልጾለት እንዲህ የሚል የደስታ ቃል አሰማው። "የመረጥኩህ ቢላሞን ሆይ ደስ ይበልህ እኔ ሰማያዊ መንግሥትን አዘጋጅቼልሃለሁና"። 🌹 የንጉሡ ጭፍሮችም ይህን የደስታ ቃል ሰሙ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው እነርሱ በሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ የአመኑ መሆናቸውን በንጉሡ ፊት ገለጡ በዚያንም ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ ንጉሡ አዘዘ። ቅዱስ ቢላሞንንም እንዲቆርጡት አዘዘ ከእሊህ ጭፍሮች ጋርም እንዲህ ገድሉን ፈጸመ ቁጥራቸውም መቶ ኀምሣ ስምንት ነው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቢላሞን ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 15 ስንክሳር።                               ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_እብል_ለርክበተ ዐፅምክሙ ወርቅ። #አዝቂር_ወኪርያቅ። #ወሰላም_ለሲላስ ረድአ ማዕነቅ። ዘጸለለ በጌጋይ እምነጽሮታ ለጽድቅ። ዐይነ ሐሊናየ ፈውሱ በምራቅ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_15።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እነግሮሙ ስመከ ለአኀውየ። ወበማዕከለ ማኅበር እሴብሐከ። እለ ትፈርህዎ ለእግዚአብሔር ሰብሕዎ"። መዝ 21፥22-23። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 8፥31-35፣ ይሁ 1፥17-22 እና የሐዋ ሥራ 15፥22-30። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 18፥12-21። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ነው። መልካም በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችን ይሁንልን።               

ቅዱስ ሲኖዶስ በሦስተኛው ቀን ውሎው "ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ" በሚል እየተሠራጨ ያለውን መጽሐፍ አወገዘ፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ በሦስተኛ ቀን ውሎው ከአጀንዳ 7-13 ባሉት ላይ ውይይት ማድረጉና ውሳኔ ሰጥቷል። ረዳት ፕሮፌሰር መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል የጥናትና ምርምር መምሪያ እና የቅዱስ ሲኖዶስ የኮሚዩኒኬሽን ሓላፊ ዛሬም ማብራሪያውን ሰጥተዋል። በአጀንዳ ቁጥር 7 ከአርሲ ሀገረ ሰብከት ካህናትና ምእመናን የቀረበውን አቤቱታ በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶስ ተወያይቶ ውሳኔ ማሳለፉን ገልጸዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የአርሲ ሀገረ ስብከት ካህናት እና ምእመናን ያቀረቡትን አቤቱታ በንባብ በማድመጥ ጉባኤው የቀረበውን አቤቱታ አስተዳደራዊ ብቻ ሳይሆን የሒሳብ ጉዳዮችም ያሉበት በመሆኑ ዝርዝር ማጣራት ስለሚያስፈልገው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት በኩል አጣሪ ተመድቦ በሚቀርበው ሪፖርት ጉዳዩ በቋሚ ሲኖዶስ እንዲታይ እና ውሳኔ እንዲሰጥበት ጉባኤው መወሰኑን ጨምረው ገልጸዋል። በአጀንዳ ቁጥር 8 የተወያየውና ውሳኔ ያሳለፈው የሸካ ዞን ራሱን ችሎ ሀገረ ስብከት እንዲሆን የቀረበውን ጥያቄ በተመለከተ መሆኑን ነው ሓላፊው የገለጹት፡፡ በዚህም የሸካ ዞን ራሱን ችሎ በሀገረ ስብከት ደረጃ እንዲቋቋም በቀረበው ጥያቄ መነሻነት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በግንቦቱ ርክበ ካህናት በሰጠው ውሳኔ መሠረት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በኩል ተጠንቶ እንዲቀርብ መደረጉን ጉባኤው አስታውሷል፡፡ በተስጠው ውሳኔ መሠረት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የተላኩት ልዑካን ያቀረቡት ጥናት ተቀባይነት ያገኘ በመሆኑ፤ የሸካ ዞን ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ተብሎ ራሱን ችሎ በሀገረ ስብከት ደረጃ እንዲቋቋም እና ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ሊቀጳጳስ ሀገረ ስብከቱ እንዲያደራጁና እንዲመሩ ይደረግ በማለት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ውሳኔ ማሳለፉን በዕለታዊ ማብራሪያቸው ገልጸዋል፡፡ በአጀንዳ ቁጥር 9 በአንድ ግለሰብ ተዘጋጅቶ "ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ" በሚል እየተሠራጨ ያለውን መጽሐፍ አስመልክቶ ውሳኔ ማሳለፉን ገልጸዋል፡፡ ይኸውም በአንድ ግለሰብ ተዘጋጅቶ "ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ" በሚል እየተሠራጨ ያለውን መጽሐፍ የተመለከቱ የታላቁ ደብረ ሊባኖስ አንድነት ገዳም መምህር የሆኑት መጋቤ ምሥጢር አባ ክንፈሚካኤል ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት መጽሐፉ እንዲመረመር ጥያቄ ማቅረባቸውን ተከትሎ፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት መጽሐፉ እንዲመረመር እና ያለበት ግድፈትና የስሕተት ትምህርት ተለይቶ እንዲቀርብ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ የመራው ሲሆን፤ የሊቃውንት ጉባኤውም መጽሐፉን በሚገባ በመመርመር መጽሐፉ ያለበትን ግድፈትና የስሕተት ትምህርት ነቅሶ በማውጣት ከውሳኔ ሐሳብ ጋር አቅርቧል። ቅዱስ ሲኖዶስም ቀደም ሲል በሊቃውንት ጉባዔ ተመርምሮ ያለበት ግድፈትና የስሕተት ትምህርት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስያንን የማይወክል በመሆኑ "ገድለ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት" በማለት ተጽፎ የቀረበው መጽሐፍ የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ የሚያዛባ ሆኖ ስለተገኘ በቅዱስ ሲኖዶስ መወገዙ ተገልጿል፡፡ መጽሐፉ  በውስጥ የየያዛቸው የተሳሳቱ ትምህርቶች በሙሉ ተቀባይነት የሌላቸው ሲሆን  ቅዱስ ሲኖዶስ ታትሞ ሥርጭት ላይ የዋለው መጽሐፍ ሥርጭቱ እንዲታገድ፣ በድጋሚም እንዳይታተም፣ በማናቸውም ሁኔታ መጽሐፉ ለማጣቀሻም ሆነ ለምርምር እንዳይውል በመወሰን ይህም ውሳኔ ለየአህጉረ ሰብከቱ በሰርኩላር ደብዳቤ እንዲላክ በማለት መወሰኑ ተገልጿል። ቅዱስ ሲኖዶስ የሊቃውንት ጉባኤ የጀመረውን የማጣራት ሥራ በሌሎችም መጻሕፍት እንዲቀጥል እና ከምስጋና ጋር መመሪያው እንዲደርሰው፤ መጽሐፉን አሳትመው ያሰራጩት ግለሰብ በቋሚ ሲኖዶስ ተጠርተው እንዲጠየቁና የፈጸሙት ስሕተት በተመሳሳይ እንዳይደግሙ ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጣቸው መወሰኑ ተገልጿል። መጽሐፉ እንዲመረመር ያደረጉት የታላቁ ደብረ ሊባኖስ አንድነት ገዳም መምህር መጋቤ ምሥጢር አባ ክንፈሚካኤልን ቅዱስ ሲኖዶስ ማመስገኑን ሓላፊው ገልጸዋል:: በአጀንዳ ቁጥር 10 በዩናይትድ ኪንግደምና አየርላንድ ሀገረ ስብከት ሥር የሚገኙ 18 አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ተወካዮች ነን የሚሉ ወገኖች ባቀረቡት ማመልከቻ መነሻነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የውጭ ጉዳይ መምሪያ ጉዳዩን በመመልከት በሰጠው መግለጫ ላይ ተወያይቷል፡፡  በዚህም ቅዱስ ሲኖዶስ የክፍሉ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የሀገረ ስብከቱን መዋቅር በማጠናከር በቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጣቸውን ሓላፊነት በመወጣት፤ በአካል በሀገረ ስብከታቸው በመገኘት አሉ የተባሉ ችግሮችን በመፍታት በግንቦቱ የርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የአፈጻጸም ሪፖርት እንዲያቀርቡ ውሳኔ ማስተላለፉን በመግለጫቸው ገልጸዋል፡፡ በአጀንዳ ቁጥር 11 በዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ካልፎርኒያ ኔቫዳና ኦሪዞና ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት በሀገረ ስብከቱ ሥር መንፈሳዊ ኮሌጅ ለመክፈትና የአብነት ትምህርት ማስመስከሪያ ት/ቤት ለማቋቋም ዕርዳታና እውቅና እንዲሰጠው ባቀረበው የዕውቅና ጥያቄ ላይ በመወያየት መንፈሳዊ ኮሌጁና የአብነት ትምህርት ማስመስከሪያ ት/ቤቱ እንዲከፈት የተፈቀደ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ የትምህርት አሰጣጥ፣ ፖሊሲውንና ሥርዓተ ትምህርቱን፣ የሰው ኃይል ትመናውንና መዋቅራዊ ተጠሪነቱን በተመለከተ  ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ትምህርትና ማሠልጠኛ መምሪያ ቀርቦ እንዲመረመርና የመጨረሻ ጥናቱ ለግንቦት 2018 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ እንዲቀርብ ሲል ውሳኔ ማሳለፉ ተገልጿል:: በአጀንዳ ቁጥር 12 እና 13 በካናዳ በሚገኙ አህጉረ ስብከቶች ዙርያ ውሳኔ ማሳለፉን የገለጹ ሲሆን፤ በዚህም ውሳኔ ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ያቀረቡት ጥያቄ በተመለከተ የኹለቱ አህጉረ ስብከት አስተዳደር ከዚህ ቀደም በግንቦት 15 ቀን 2017 ዓ.ም በተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት እንዲፈጸም ሆኖ አንዱ በአንዱ ጣልቃ ባለመግባት በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ አርባ ንዑስ ቁጥር 3 የተመለከተው ድንጋጌ ተጠብቆ እንዲሠራበት በማለት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መካከለኛው ካናዳ ኤድመንተን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የሀገረ ስብከቱ ስያሜ እንዲስተካከል  በማለት ያቀረቡትን ጥያቄ ምልዓተ ጉባኤው ተቀብሎ የሀገረ ስብከቱ ስያሜ የመካከለኛው ካናዳ ኤድመንተንና አካባቢው በሚለው እንዲስተካከል በማለት ምልዓተ ጉባኤው በመወሰን የዕለቱን ስብሰባ ማጠናቀቁን ረዳት ፕሮፌሰር መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል ገልጸዋል፡፡

🌹 ከዚህም በኋላ ሥጋውን በታላቋ በሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን አኖሩ ከሥጋውም ብዙ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ ዕውሮች አይተዋልና ሐንካሶችም ቀንተው ይሔዳሉና ደንቆሮዎችም ይሰማሉና ለምጻሞችም ይነጻሉና አጋንንት ያደሩባቸውም ይወጡላቸዋልና ሁሉም ካለባቸው ደዌ ይድናሉና። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሙሴ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 14 ስንክሳር።             

አመሰግንሃለሁ"። የአባቱ አገልጋዮችም ብዙ ወራት በሁሉ አገሮች ሲዞሩ ኑረው ወደ አውፊምያኖስ ጌታቸው ተመለሱ። የእግዚአብሔር ሰው ቅዱስ ሙሴም ከሰንበት ቀኖች በቀር እህልን የማይቀምስ እስቲሆን ድረስ ተጋድሎውን በመጨመር በየሁለትና በየሦስት ቀኖች የሚጾም ሆነ። 🌹 ከዚህም በኋላ እመቤታችን የከበረች ድንግል ማርያም ከዚያች ቤተ ክርስቲያን ካህናት ውስጥ ለአንድ ደግ ጻድቅ ቄስ ተገልጻ እንዲህ አለቸው "በጥዋት ወደ ቤተ ክርስቲያን ውጭ ውጣ ከምሰሶ አጠገብ ብቻውን ቁሞ የሚጸልይ ሰው ታገኛለህ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ወደ ቤተ ክርስቲያን ግባ በለው በውጭ አትተወው ጾሙ ጸሎቱ በእግዚአብሔር ፊት መዓዛው ጣፋጭ እንደሆነ ዕጣን ተቀባይነትን አግኝቷልና"። ሲነጋም ያ ቄስ ወደ ቅዱስ ሙሴ ሒዶ "የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ወደ ቤተ ክርስቲያን ግባ" አለው ሙሴም "አባቴ ሆይ በከበረ ቦታ ላይ መቆም የማይገባኝ ኃጢአተኛ ነኝና ተወኝ" አለው ቄሱም "ወደ ቤተ መቅደስ አስገባህ ዘንድ ከቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም ወዳንተ ተልኬአለሁ" ብሎ መለሰለት ወደ ቤተ መቅደስም ያስገባው ዘንድ እንዳዘዘችው ነገረው ከዚህም በኋላ አስገባው። 🌹 ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ ወደ ሀገረ ጠርሴስ ይሔድ ዘንድ አስቦ እርሷም የሐዋርያው ጳውሎስ አገር ናት እንዲህም አለ "እስከ ዕለተ ሞቴ በውስጥዋ እኖራለሁ ሥጋው ምንም በሮሜ አገር የሚኖር ቢሆንም የትውልድ አገሩ ናትና በረከትን እቀበላለሁ" ብሎ ነው። 🌹 በሌሊትም ወጥቶ ወደ ባሕር ዳርቻ ሔደ ወደ ጠርሴስም ይሔድ ዘንድ በመርከብ ተጫነ በባሕር መካከልም ታላቅ ነፋስ ተነሣባቸው ባሕሩም ከነፋሱ ኃይል የተነሣ ታወከ ወደየትም እንደሚሔዱ አያውቁም ነበር ቀኑ ጨልሞባቸዋልና ስለ ነፍሳቸውም ድኅነት ወደ እግዚአብሔር ለመኑ በዚያንም ጊዜ ባሕሩ ጸጥ ብሎ ታላቅ ደስታ ሆነ ብርሃንም ታየ ወደ ሮሜ ሀገር ወደብም እንደ ደረሱ አወቁ። 🌹 ቅዱስ ሙሴም ተነሥቶ በመርከብ ውስጥ ያሉትን በሰላምታ ተሰናብቷቸው ጉዞውን ጀመረ በልቡም እንዲህ አለ "ይህ ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ እንግዲህ እስከ ዕለተ ሞቴ ራሴን ለማንም እንዳልገልጥ ሕያው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያውቀኝ የለምና በአባቴ ደጅ እኖራለሁ" ይህንንም ብሎ ወደ አባቱ ቤት ተጓዘ። በመንገድም ላይ አባቱን ተገናኘው ብዙ ሰውም ተከትሎት ነበር የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ቀረብ ብሎ አባቱ የተቀመጠበትን ፈረስ ልጓሙን ያዘ እንዲህም አለው "እግዚአብሔር የባረከህ ያከበረህ አንተ ደግ ሰው እግዚአብሔርም ኃጢአትህን ይቅር ይበልህ የልብህንም ልመና ይስጥህ እኔም መጻተኛ ድኃ ሰው እንደ ሆንኩ እወቅ ለመጻተኛነቴና ለችግረኛነቴ የምትራራ ሁነህ ከማዕድህ ፍርፋሪ ልትመግበኝ ከወደድህ መኖሪያዬን በቤትህ አንጻር በደጃፍህ አድርግልኝ ዋጋህንም የሚሰጥህ እግዚአብሔር ነውና"።በዚያንም ጊዜ አውፊምያኖስ የልጁ የሙሴን ስደት አስታውሶ በተቃጠለ ልብ አለቀሰ መኖሪያውንም በቤቱ ደጅ እንዲሠሩለት አዘዘለት። ሁለተኛም ከአገልጋዮቹ አንዱን በሚያሻው ነገር ሁሉ እንዲአገለግለው አዘዘው። 🌹 የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ያን የሚያገለግለውን "ወንድሜ ሆይ ከሰንበት ቀኖች በቀር መብልና መጠጥ እንዳታመጣልኝ እለምንሃለሁ ይኸውም ከቁርባን በኋላ ግማሽ እንጀራና የጽዋ ውኃ ብቻ ነው" አለው። በጾምና በጸሎትም እየተጋደለ በዚያ በአባቱ ደጅ ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ። 🌹 ሰውን የሚወድ ቸር ጌታችን ኢየሱስ ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው ወዶ ተገለጠለት እንዲህም አለው "የመረጥሁህ አንተ ብፁዕ ነህ አንተ ፈቃዴን ፈጽመሃልና በዚህ ዓለም ከደስታ ኃዘንን ከብልጽግና ድኅነትን መርጠሃልና እኔም የማይጠፋ ብልጽግናን እሰጥሃለሁ ዳግመኛም ስምህን የሚጠራ መታሰቢያህንም ለሚያደርግ የተራበውን ለሚያጠግብ የተጠማውን ለሚያጠጣ የተራቈተውን ለሚያለብስ ገድልህንም ለሚጽፍ ወይም ለሚያጽፍ ስለ ስምህ በጎ ሥራ ሁሉ ለሚሠራ ቃል ኪዳንን ሰጠሁህ። በሰማያዊት መንግሥትም በጎ ዋጋን እሰጠዋለሁ ተጠራጣሪ ካልሆነ በዚህ ዓለምም እጠብቀዋለሁ ከበጎ ነገር ሁሉ ምንም አላሳጣውም። አሁንም ከአራት ቀን በኋላ እወስድሃለሁ ምርጦቼ ነቢያት ሐዋርያት ጻድቃን ሰማዕታት ከአሉበትም አኖርሃለሁ" ይህንንም ብሎ ከእርሱ ዘንድ ወደ ሰማይ በታላቅ ክብር ዐረገ። 🌹 ቅዱስ ሙሴም ከእግዚአብሔር ዘንድ ይህን ጸጋ በተሰጠ ጊዜ እጅግ ደስ አለው ያን የሚያገለግለውንም ወንድሜ ሆይ እንግዲህ "ስለ እኔ ከመድከም ታርፋለህና ወረቀትና ቀለም አምጣልኝ" አለው። ያ አገልጋይም ከአነጋገሩ የተነሣ አድንቆ ወረቀቱንና ቀለሙን አመጣለት የከበረ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ገድሉን ሁሉ ጻፈ በአራተኛውም ቀን ያቺን የጻፋትን መጽሐፍ በእጁ ጨበጣት በእሑድ ቀንም በሰላም ዐረፈ። መላእክት "ነቢያት ሐዋርያት ጻድቃን ሰማዕታት ለሚያገለግሉት የዘላለም ተድላ ደስታ ለሚሰጥ ለነበረና ለሚኖር ፈጣሪያችን ምስጋና ይሁን" እያሉ ነፍሱን ተቀበሏት። ሕዝቡም ሁሉ በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተሰብስበው እያሉ ከመሠዊያው በላይ "የጌታቸውን ሕጎቹንና ሥርዓቱን የሚያደርጉ ደጎች አገልጋዮች ባሮች የተመሰገኑ ናቸው እነርሱ ወደ ዘላለም ተድላ ደስታ ይገባሉና" የሚል ቃልን ሲጮህ ሰሙ ። 🌹 ሊቀ ጳጳሳቱና ኤጲስቆጶሳቱ ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ሕዝብም ሁሉ በሰሙ ጊዜ በላያቸው ታላቅ ፍርሀት ወደቀባቸው። የቅዳሴውም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ይህን ምሥጢር ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በመጸለይ ማለዱ በዚያንም ጊዜ "የእግዚአብሔርን ሰው በአውፊምያኖስ ቤት ፈልጉት እነሆ እርሱ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጥቷልና" የሚል ቃልን ሰሙ። ሊቀ ጳጳሳቱም ይህን ነገር ሰምቶ አውፊምያኖስን ጠራውና "ይህ ታላቅ ጸጋ በቤትህ ውስጥ ሲኖር በሕይወቱ ሳለ እንድንጎበኘው በረከቱንም እንድንቀበል ለምን አልነገርከንም" አለው አውፊምያኖስም እንዲህ ብሎ መለሰ "ክቡር አባት ሆይ ቅድስናህ ይመስክር ይህን የሚመስል በቤቴ ውስጥ እንዳለ አላወቅሁም"። 🌹 በዚያንም ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱ ከሁሉ ካህናትና ሕዝብ ጋር ተነሥቶ ወደ አውፊምያኖስ ቤት ሔደ የከበረ የእግዚአብሔር ሰው ሙሴንም በዐረፈበት ቦታ አገኙት ክርታሱም በእጁ ውስጥ ነው ሊቀ ጳጳሳቱም ያቺን ክርታስ አንሥቶ "የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ የአውፊምያኖስ ልጅ እናቱም አግልያስ" እስከሚለው ስሙ እስቲደርስ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አነበባት። እናትና አባቱም በሰሙ ጊዜ ደነገጡ መራር ልቅሶንም አለቀሱ ቤተሰቦቻቸውም ሁሉ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ አጽናንቶ ጸጥ አደረጋቸው። 🌹 በዚያንም ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱ የሐር ልብስ አስመጥቶ በክብር ገነዘው ወደ ቤተ ክርስቲያንም ወስደው ከሥጋው እስከሚባረኩ በቤተ መቅደስ አኖሩት። ካህናቱና ሕዝቡ ሁሉ ከዚህም በኋላ ብዙ በሽተኞች ዕውሮች ሐንካሶች ደንቆሮዎች ዲዳዎች መጥተው ከሥጋው በተሳለሙ ጊዜ ሁሉም ከደዌያቸው ዳኑ በዚያችም ቀን ታላቅ ደስታ ሆነ። ሕዝቡም በበዙ ጊዜ የልጁን የሙሴን ሥጋ ከዐልጋው ላይ እንዳይጥሉት አውፊምያኖስ ፈራ ብዙ ገንዘብም አምጥተው ይበትኑ ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው። ሥጋውን ትተው ወደ ተበተነው ገንዘብ ይሔዳሉ ብሎ አስቦ ነበር ግን ከቶ አንድ እንኳ ወደ ገንዘብ የሔደ የለም።

🌹 ለሠርጉም የታደሙት ሁሉ እንደተኙ በሌሊት ወጥቶ ሔደ ወደ ባሕርም ዳርቻ ደርሶ በመርከብ የሚጓዙ መንገደኞችን አገኘ የዓመት መንገድ ወደሚሆን አርማንያም እስከሚደርስ ከእነርሱ ጋር ተጓዘ። ነግቶ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ በገቡ ጊዜ ሙሽራውን ልጃቸውን አላገኙትም ሙሽሪትንም "ልጃችን ወዴት አለ?" ብለው ጠየቋት እርሷም እንዲህ አለቻቸው። "በሌሊት ወደ እኔ ገባ መሐላን አማለኝ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ራሴንም ስሞኝ ከእኔ ዘንድ ወጣ እኔም እያለቀስኩ ብቻዬን አደርኩ" ነገርዋንም ሰምተው ወድቀው በመጮህ ታላቅ ልቅሶን አለቀሱ ። 🌹 በዚያችም ጊዜ በሀገሮች ውስጥ ሁሉ ልጁን ገብረ ክርስቶስን ይፈልጉት ዘንድ ንጉሡ አምስት መቶ አገልጋዮቹን ላከ ለድኆችና ለምስኪኖችም ምጽዋት አድርገው የሚሰጥዋቸውን ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው። ገብረ ክርስቶስ ግን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአርማንም አገር በተሠራች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ደጅ የሚኖር ሆነ። አባቱ የላካቸውም ሁለቱ አገልጋዮች ከዚያ ደርሰው ስለርሱ መረመሩ ግን ወሬውን ማግኘት ተሳናቸው ለድኆችም ምጽዋትን ሰጡ እርሱም ከድኆችም ጋር ምጽዋትን ተቀበለ። 🌹 በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ከኖረ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለአንድ ቄስ ተገለጸችለት ቦታውንም አመልክታ እንዲህ አለችው። "የእግዚአብሔር ሰው ገብረ ክርስቶስን ይዘህ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስገባው ከውጭ አትተወው" ቄሱም እመቤታችን እዳዘዘችው አደረገ። 🌹 ከዚህም በኋላ የተመሰገነ ገብረ ክርስቶስ በሌሊት ተነሣ ከእመቤታችንም ሥዕል ፊት ቁም ጸለየ እንዲህም አላት "እመቤቴ ሆይ የተሠወረ ሥራዬን አንቺ ለምን ገለጥሽ አሁንም ወደሚሻለኝ ምሪኝ" ይህንንም ብሎ የእመቤታችንን ሥዕሏን ተሳልሞ በሌሊት ወጥቶ ወደ ባሕሩ ወደብ ደረሰ ወደሌላ ሀገርም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ተሳፈረ። ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ከአባቱ አገር ደረሰ የአባቱና የእናቱም ባሮች እየናቁትና እየሰደቡት በአባቱ ደጅ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ። ሲገቡና ሲወጡም ሽታው እንዳያስጨንቀን "ይህን ምስኪን አስወግዱልን" ይላሉ ወጭትና ድስትም አጥበው በላዩ ይደፉበታል ውሾችም እንዲናከሱበትና እንዲበሉት የሥጋ ትርፍራፊ ይጥሉበታል ውሾች ግን ቁስሉን ይልሱለት ነበር እንደዚህም አብዝተው አሠቃዪት ። 🌹 ከዚህም በኋላ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ "ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ለአባቴና ለእናቴ ባሮች በደል እንዳይሆንባቸው ወዳንተ ውሰደኝ"። በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው። ከዚህም በኋላ ገድሉን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጻፈ በእጁም ጨብጧት ጥቅምት 14 ቀን ዐረፈ። 🌹 በእሑድ ቀንም ሕዝቡ ሁሉና ካህናቱ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳሉ "የእግዚአብሔርን ሰው በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ቤት ፈልጉት" የሚል ቃል ከሰማይ ሰሙ በዚያን ጊዜ ሔደው በአረፈበት ቦታ አገኙት። በእጁም ውስጥ የተጨበጠ ክርታስን አዩ ሊወስዷትም ሽተው መውሰድ ተሳናቸው ። ✝ በአንድነትም በጸለዩ ጊዜ እጁ ተፈትታ ወስደው አነበቧት አባትና እናቱም ልጃቸው እንደሆነ አወቁ ታላቅ ጩኸትም ሆነ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ አክብረውም ቀበሩት መቃብሩም በሽተኞችን ሁሉ በመፈወስ ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራትን የሚያደርግ ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #ከሮሜ_ሀገር_የሆነ_የከበረ_የእግዚአብሔር ሰው #ቅዱስ_ሙሴ፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አውፊምያኖስ የእናቱ አግልያስ ነው እነርሱም እግዚአብዘሔርን የሚፈሩ እጅግም ባለጸጎች ናቸው። አብዝተውም ይመጸውታሉ ሁልጊዜም ይጸልያሉ እስከ ዘጠኝ ሰዓትም ይጾማሉ ድኆችንና ችግረኞችንም ሳይይዙ አይበሉም። 🌹 ነገር ግን ልጆች የሏቸውም ነበር የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ የተባረከ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ይለምኑት ነበር ጌታችንም ልመናቸውን ተቀብሎ ይህን መልኩ እጅግ ያማረ የከበረና የተባረከ ልጅን ሰጣቸው በወለዱትም ጊዜ በርሱ ደስ ብሏቸው ለድኆችና ለምስኪኖች ታላቅ ምሳ አደረጉ ስሙንም ሙሴ ብለው ሰየሙት ትርጓሜውም የእግዚአብሔር ሰው ማለት ነው ስለእርሱ እግዚአብሔር ልመናቸውን ሰምቷልና። 🌹 ከዚህም በኋላ ሙሴን በመልካም አስተዳደግ አሳደጉት መንፈሳዊና ሥጋዊ ትምህርትን ጥበብን ሁሉ አስተማሩት። አድጎም በጎለመሰ ጊዜ አባቱ አውፊምያኖስ ሚስቱ አግልያስን "እነሆ ልጃችን ሙሴ አደገ ሚስትን ልናጋባውና በጋብቻውም ደስ ሊለን ለእኛ ይገባናል" አላት። የሙሴ እናት አግልያስም ሰምታ በዚህ ነገር ደስ አላት ከሮሜ አገር ታላላቆች ሰዎች ወገንም መልኳ እጅግ ያማረ አንዲት ብላቴና አጋቡት። ታላቅ ሠርግንም በማዘጋጀት ሸልመው አስጊጠው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በጋብቻ ሥርዓት አክሊላትን አቀዳጇቸው። ከዚህ በኋላ ሥጋውንና ደሙንም ተቀብለው ወደሚሠረጉበት ቤት ገቡ። 🌹 ከዚህም በኋላ በማግሥቱ አውፊምያኖስ ሚዜውን ጠርቶ እንዲህ አለው ሙሽራው ወደ ሙሽሪቷ ገብቶ የጋብቻውን ሕግ እንዲፈጽም ንገረው ያ ሚዜውም በነገረው ጊዜ ወደ ሙሽራዪቷ ገባ ድንቅ የሆነ ውበቷንና ደም ግባቷን ተመለከተ በልቡም አስቦ እንዲህ አለ "ይህ ሁሉ ውበትና ደም ግባት አላፊ ጠፊ አይደለምን"። ይህንንም ብሎ ወደ ሰማያዊት መንግሥቱ የሚደርስበትን መንገድ እንዲመራው እግዚአብሔርን ለመነው። ሙሽራዪቱንም እንዲህ አላት "የተባረክሽ እኅቴ ሰላም ይሁንልሽ የእግዚአብሔርም ፍቅር አንድነት ከአንቺ ጋር ይኑር ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ እስከምንገናኝ ደኅና ሁኚ"። ይህንንም በሚላት ጊዜ ልብሶቹን አውልቆ ሰጥቷት ከእርሷ ዘንድ ወጣ የተሞሸረበትንም ልብስ ለውጦ ከባሕር ዳርቻ እስከሚደርስ መንገዱን ተጓዘ። ልብሶቹንም ሁሉ ሽጦ ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋትን ሰጠ እርሱም ጨርቅ በመልበስ እንደ ድኃ ሁኖ ቁራሽ እንጀራ እየለመነ በየጥቂቱ እየተመገበ እስከ ሀገረ ሮሀ ድረስ ሔደ። 🌹 ከዚያም በደረሰ ጊዜ ወደቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገብቶ ለሮሀ ንጉሥ ለአቃርዮስ በስብከቱ ወራት የተላከለትን ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሥዕልና የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል አግኝቶ ከሥዕሎቹ ተሳልሞ በረከትን ተቀበለ ወደ ልዑል እግዚአብሔርም ፈጽሞ እያመሰገነ ጸለየ። ወጥቶም ኑሮውን ከድኆችና ከምስኪኖች ጋር አደረገ። 🌹 ከዚህም በኋላ መጸለይና መጾምን ጀመረ እስከ ምሽትም ይጾማል በቀንና በሌሊትም ጸሎቱን አያቋርጥም ምጽዋትንም ከድኆች ጋር ተቀብሎ እርሱ መልሶ ለሌሎች ይሰጣል። በዚያቺም ዕለት በነጋ ጊዜ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ ሲገቡ ሙሽራው ልጃቸው ሙሴ በጫጉላው ቤት እንደ ሌለ ሰሙ ደስታቸውም ወደ ኀዘን የሠርጉም ዘፈን ወደ ልቅሶ ወደ ዋይታ ተለወጠ። 🌹 ከዚህም በኋላ አውፊምያኖስ ባሮቹን ጠርቶ ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው እንዲህም አላቸው "ልጄን እስከምታገኙት ድረስ ሁለት ሁለት እየሆናችሁ ወደ ሀገሩ ሁሉ ሒዱ ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋትን ስጡአቸው"። እነርሱም በሀገሩ ሁሉ ተበታተኑ። ከአባቱ አገልጋዮችም ሁለቱ አገኙት ግን አላወቁትም ምጽዋትንም ከድኆች ጋር ሰጡት ቅዱስ ሙሴም አውቋቸው እንዲህ ብሎ አመሰገነ "ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ስለ አንተ ፍቅር ከአባቴ ባሮች እጅ ምጽዋትን እቀበል ዘንድ ለዚህ ታላቅ ክብር አድለህኛልና

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፲፬ (14) ቀን። 🌹 እንኳን #ከዘጠኙ_ቅዱሳን_አንዱ ለሆኑት #ለአባ_ዘሚካኤል በሚሰሩት ስራቸው አረጋዊ ለተባሉት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_አረጋዊ ከዚህ ዓለም ከሞት ለተሰወሩበት ቀን ለመታሰቢያ በዓል፣ ለቊስጥንጥንያ ንጉሥ ለቴዎዶስዮስ ልጅ ለሙሽራወ #ለቅዱስ_ለገብረ_ክርስቶስና ከሮሜ ሀገር ለሆነ ለእግዚአብሔር ሰው #ለቅዱስ_ሙሴ_ለዕረፍታቸው ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከመራክዋና ከእርሱ ጋር ካሉ ሰማዕታት፣ #ከድማቴዎስና_ከምራይስ #ከአራት_መቶ_ሠላሳ_አንድ_ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                               ✝ ✝ ✝ 🌹 #አባ_ዘሚካኤል_አቡነ አረጋዊ፦ እኚህ አባት ከ9 ቅዱሳን አባቶች አንዱ ሲሆኑ አባታቸው ይስሐቅ የሮም ንጉሥ ነበሩ፡፡ እናታቸው ንግሥት እደና ይባሉ ነበር፡፡ የመጀመሪያ ስማቸው ዘሚካኤል ነው፡፡ ጥበብ መንፈሳ ሲማሩ አድገው ወደ እስክንድርያ ገዳም ገቡ፡፡ አበምኔቱ አባ ጳኵሚስ በፈቃደ እግዚአብሔር የመጡ መሆናቸውን አውቀው መዓረገ ምንኵስና ሰጥተዋቸዋል፡፡ 🌹 የንጉሣዊ የቅንጦት ኑሮ ንቀው ትተው ገዳም ገብተው በምንኵስና ተወስነዋል፡፡ አባታችን በተጋድሏቸውም ከአባ እንጦንስ፣ ከአባ ጳውሊ እና ከአባ መቃርስ ቀጥሎ በአራተኛ ማዕረግ አበ መነኰሳት ሆነው ተመርጠዋል። 🌹 በገዳመ ዳውናስ 7 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደ ሮም ተመልሰው ሲያስተምሩ የሀገራችን ኢትዮጵያን ዜና ሰምተው ለመምጣት በ480 ዓ.ም ከአባ ፍሬምናጦስ በኋላ መንገድ ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በክንፉ ተሸክሞ አክሱም አድርሷቸዋል፡፡ ተመልሰውም ሄደው ስለ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ  መስክረዋል፡፡ "ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ጸንታ ትኖራለች" ብለው ለሰባቱ ዘመዶቻቸው አበው መነኰሳት ነገሯቸው፡፡ ስምንቱም ጓዛቸውን ጠቅልለው በሮም ነግሦ የነበሩ ይስሐቅን (አባ ገሪማን) ጨምረው ንጉሥ አልአሜዳ በነገሠ በአምስተኛ ዓመት ማለትም በ480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ዘጠኝ ሆነው መጥተዋል፡፡ 🌹 አባ አረጋዊ እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀ መዝሙራቸውን ማትያስን አስከትለው እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩና ድውያንን እየፈወሱ ደብረ ዳሞ ደረሰዋል፡፡ ከእግረ ደብር ሆነው አሁን "ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ" እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ በንግግሩ ሐሰት የሌለበት አምላካችን በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ በመዝ 90፥11-16 ላይ "በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ"። እንዳለው የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ስደሳ ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው አናት አድርሷቸዋል፡፡ 🌹 ወዲያው ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል፡፡ ቦታውም ደብረ ሃሌ ሉያ ተብሏል፡፡ በዚያ ዕለት ግማሽ ህብስት በልተው ጠገቡ፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድራዊ ሕብስት አልተመገቡም፡፡ በሰንበተ ክርስታያን ከቅዳሴ በኋላ ሕብስተ ሰማያዊ እያመጡላቸው ይመገቡ ነበር እንጂ፡፡ ኋላም ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀ መዛሙርት ተሰብስበውላቸዋል፡፡ 🌹 ስለ አባታች አቡነ አረጋዊ መሰወር፦ የእርግና ዘመኑ ደረሰ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ሆነው። በነጋም ጊዜ ቆሞ ሲለምንና ጸሎትም ሲያደርግ ተመለከተው በምን ጊዜ ወይም ሰዓት ከነሱ እንደሚሠወር ደቀ መዝሙሩ አባ ማትያስ ይጠባበቅ ወይም በልቡ ያስቡ ነበርና። 🌹 ጸሎት ያደርግ ዘንድ ቀድሞ ወደነበረበት ተመልሶ ገባ ወይም ሄደ። ዳግመኛም ሦስት ሰዓት በሆነ ጊዜ ተመልሶ መጣ ነገር ግን ከበዓቱ በደረሰ ጊዜ አላገኘውም እሱ ተሠውሯልና። በዚያም ከመቋሚያና ከመስቀል በስተቀር ምንም ያገኘው ነገር የለም ይህንኑም ለወንድምቹ ነገራቸው። እነርሱም ጮሁ ዋይ ዋይም አሉ እሱንም ያገኙ እየመሰላቸው መስቀሉንና መቋሚያውን ተሸክመው በመሳም መሪር ዕንባን አለቀሱ። 🌹 ኀዘናቸውንና ልቅሶአቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለክቡር አባታችን አቡነ አረጋዊ የተሰጠውን ቃል ኪዳን ደቀ መዝሙሩ አባ ማትያስ  "ምድራዊ መንግስትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ህልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግስቴን አወርሰሃለሁ" ብሎ ቃልኪዳን እንደሰጠው፡፡ "በስምህ የተማጸነውን እስከ ዐሥራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ አንተም ከሞት ገጽ ትሰወራለህ" ብሎ ተስፋ እደነገራቸው፡፡ ነገራቸው ወንድሞቹም ይህን በሰሙ ጊዜ ፈጽመው ተደሰቱ ኀዘናቸውም ወደ ደስታ ተለወጠ ስለዚህም እግዚአብሔር አመሰገኑት። 🌹 በዚያን ጊዜ ቀለምና ብራና አዘጋጅተው ማትያስና ዮሴፍ እየነገሯቸው ለልጅ ልጅ መታሰቢ ሆኖ ይኖር ዘንድ የገድሉንና የቃል ኪዳኑን መጽሐፍ ጻፈ። 🌹 ከዚህም በኋላ በመነኰሳት ሥርዓት ማኅበር ሥርዓት ማኅበር ይኖሩ ዘንድ የሠራላቸውን ሥርዓት አሰቡ በሥርዓት ይመራቸው ዘንድ አባታቸው አረጋዊ ለሰጣቸው ለመንፈሳዊ አባታቸው ለአባ ማትያስም ራሳቸውን ዝቅ አደረጉ ሃሳባቸውንም የአባታቸው የአረጋዊዊን መታሰቢያ ወደማድረግ ተመለሱ። 🌹 ክብር አባታችን አቡነ አሰጋዊ የተሠወረበት ቀን በኢትዮጵያ ወር አቆጣጠር በጥቅምት ዐሥራ ዐራት ቀን በዕብራውያን ደግሞ በታስሪን ዐሥራ አንድ ቀን በኢትዮጵያዊው ንጉሥ በዐፄ ገብረ መስቀል ዘመነ መንግሥት ነው። ከአባታች ከአቡነ አረጋዊ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ አረጋዊ።                                                        ✝ ✝ ✝ 🌹 #የቊስጥንጥንያ_ንጉሥ_የቴዎዶስዮስ ልጅ መሽራው #ቅዱስ_ገብረ_ክርስቶስ፦ ይህም ቴዎዶስዮስ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው ሚስቱም በጎ የምትሠራ እግዚአብሔርንም የምትፈራ ናት ስሟም መርኬዛ ነው። እነርሱም ልጅ ስለሌላቸው ያዝኑ ነበር ወደ ኢየሩሳሌምም ሒደው ስእለትን ተሳሉ ቸር መሐሪ ወደሆነ እግዚአብሔርም ለመኑ እርሱም ልመናቸውን ተቀበሎ ይህን ያማረ ልጅ ሰጣቸው ስሙንም "አብደልመሲህ" ብለው ሰየሙት ትርጓሜውም "ገብረ ክርስቶስ" ማለት ነው ። የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ የሥጋዊንም ትምህርት አስተማሩት ። 🌹 አድጎ በጕለመሰም ጊዜ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ አጭተው እንደ ሥርዓቱ አጋቡት ከሌሊቱ እኩሌታም በሆነ ጊዜ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ተነሥቶ ወደሙሽራዪቱ ገባ እጅዋንም ይዞ ከእርስዋ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ከዚያም የሃይማኖት ጸሎት በአንድ አምላክ እናምናለን የሚለውን እስከ መጨረሻ ጸለየ የተሞሸረበትንም ልብስ ከላዩ አውልቆ የግምጃ ልብስን ለበሰ ወደ ሙሽሪቷም ሒዶ ራስዋን ሳማት እንዲህም እያለ ተሰናበታት "እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኑር ከሰይጣን ሥራ ሁሉ ያድንሽ"። እርሷም አልቅሳ "ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ ለማንስ ትተወኛለህ" አለችው እርሱም "በእግዚአብሔር ዘንድ እተውሻለሁ እኔም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ልከተለው እሔዳለሁ የአባቴ መንግሥት አላፊ ነውና አንቺም መሐላሽን አስቢ" አላት ያን ጊዜ መሐላዋን አስባ ዝም አለች።

🌹 "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፲፬ (14) ቀን። 🌹 እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው፤ ሐዋርያት ኮሾሟቸው #ከሰባቱ_ዲያቆናት ውስጥ የተቆጠረ ለሆነ፤ #ኢትዮጵያዊውን_ጃንደረባ_ባኮስን (አቤላክን) ላጠመቀው #ለቅዱስ_ፊሊጶስ_ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #ቅዱስ_ፊሊጶስ፦ ጌታችንም በቂሣርያ አገር ውስጥ በአለፈ ጊዜ በውስጧ አስተምረ ትምህርቱም ሰምቶ ክብር ይግባውና ጌታችንን አምኖ ተከተለው ከሰባ ሁለቱ አርድዕትም ጋር ተቆጠረ። 🌹 ጌታችንም ይሰብኩ ዘንድ ሁለት ሁለት አድርጐ በላካቸው ጊዜ ከእርሳቸው አንዱ ይህ ደቀ መዝሙር ነው። ከመድኃኒታችንም ዕርገት በኋላ ሐዋርያት ኮሾሟቸው ከሰባቱ ዲያቆናት ውስጥ የተቆጠረ ነው። እርሱም ወደ ሰማርርያ ወርዶ አስተማረ ብዙዎችንም አሳምኖ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። 🌹 ከዚህም በኋላ የተጎዳውን ሥራየኛ ሲሞንንም አጥምቆት ነበር እርሱ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በገንዘብ ሊገዛ አስቧልና። 🌹 ከዚህም በኋላ ወደ ጋዛ በሚወስደው መንገድ ይሔድ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ፊሊጶስን አዘዘው በሔደም ጊዜ ለኢትዮጵያ ንግሥት ለህንደኬ በጅሮንዷ የሆነ ጃንደረባውን አገኘው እርሱም እንደ በግ ሊታረድ መጣ የሚለውን የነቢይ ኢሳይያስ መጽሐፍ ያነብ ነበር። ፊልጶስም ጃንደረባውን "የምታነበውን ታስተውለዋለህን?" አለው። ጃንደረባውም "ያስተማረኝ ሳይኖር እንዴት አውቃለሁ" አለ። ፊሊጶስም ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አመነ ያን ጊዜም በፊሊጶስ እጅ ከወንዝ ውኃ ውስጥ ተጠመቀ ከውኃውም በወጡ ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ፊሊጶስን ነጥቆ ወሰደው ጃንደረባውም ሁለተኛ አላየውም። 🌹 ፊሊጶስ ወደ አዛጦን ከተማ ደረሰ እያስተማረም እስከ ቂሣርያ ሔደ በከተማዎች ሁሉ በመዞር ወንጌልን ሰበከ ከአይሁድና ከሳምራውያንም ብዙዎችን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን መልሶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። 🌹 ለሐዋርያው ፊሊጶስም ከእርሱ ጋር ወንጌልን የሚሰብኩ አራት ሴቶች ልጆች ነበሩት። አገልግሎቱንም ፈጽሞ ጥቅምት 14 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ፊሊጶስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 14 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_ለከ_ፊሊጶስ_ሐዋርያ። እምሰብአ ፍልስጥኤም ወቂሣርያ። ምስለ አዋልዲከ አርባዕ እለ ይትኔበያ። አርውየኒ እምትምህርትከ በከመ ትካት ረወያ። ሀገረ ሳምር ወዓዲ እስያ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_14።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ይባርኩ ጻድቃኒከ። ስብሓት ይብሉ ለመንግሥትከ። ወይነግሩ ኃይለከ"። መዝ 140፥10። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 14፥8-15።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አፅናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 7፥36-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 2፥18-21 እና የሐዋ ሥራ 8፥26-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 19፥26-30። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ፊሊጶስ የዕረፍት በዓል፣ የአቡነ አረጋዊ የስዋሬ በዓል፣ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስ፣ የቅዱስ ሙሴ ብእሴ እግዚአብሔር የዕረፍት በዓላቸውና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።               @Teamihokidusan

#Update ቅዱስ ሲኖዶስ የአህጉረ ስብከት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ምደባ ውሳኔ አሳለፈ። 1. የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ብፁዕ አቡነ ቶማስ የአዊና የመተከል አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምሥ
#Update ቅዱስ ሲኖዶስ የአህጉረ ስብከት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ምደባ ውሳኔ አሳለፈ። 1. የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ብፁዕ አቡነ ቶማስ የአዊና የመተከል አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከትን ደርበው የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከትን እንዲመሩና እንዲይዙ ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡ 2. የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት የከሚሴ የደቡብ ወሎ ልዩ ዞን  የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ ደርበው እንዲመሩ ምልዓተ ጉባኤው  ወስኗል፡፡ 3. የምሥራቅ ወለጋንና የሆሮ ጉድሩን ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ጳጳስ ሀገረ ስብከታቸውን እንደያዙ  ደርበው እንዲመሩ የቅዱስ ሲኖዶስ  ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡ 4. ብፁዕ አቡነ ኤውስጣቴዎስ  የአሉባቦር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ  የምዕራብ ወለጋና ደርበው እንዲመሩ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡ ውሳኔዎቹ የተወሰኑት አሁን ላይ በተደራቢ እንዲመሩ የተያዙት አህጉረ ስብከት በዘላቂነት ሊቃነ ጳጳሳት ተመድበው እስከፈታ ድረስ የተወሰነ ውሳኔ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶስ አሳውቋል።