ar
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

إظهار المزيد
637
المشتركون
لا توجد بيانات24 ساعات
-37 أيام
-1230 أيام
أرشيف المشاركات
❤ ሮሜ አገር በደረሰችም ጊዜ ልጃቸው ስለዳነችላቸው ንጉሡና መኳንንቱ የአገሩም ሰዎች ሁሉ ተደስተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ከዚህም በኋላ አባቷ በገዳም ስለነበራት ቆይታ ልጁን ጠየቃት፡፡ እርሷም "ያ በጸሎቱ ያዳነኝ አባ ኢላርዮን የሚባል መነኩሴ አብዝቶ ይወደኛል፤ አቅፎም ይስመኛል" አለችው፡፡ ንጉሡም ይህንን ሲሰማ ልቡ ታወከና "መነኵሴ እንዴት ሴትን ለመሳም ይገባዋል" አለ፡፡ በዚህም ጊዜ "በእኔ ላይ ይጸልይ ዘንድ አገሬንም ይባርክ ዘንድ ልጄን ያዳናትን አባ ኢላርዮንን ወደኔ ላኩልኝ" ብሎ ደብዳቤ ጽፎ ወደ አስቄጥስ ገዳም ላከ፡፡ አረጋውያኑም ቅድስት ኢላርያ ጠርተው ወደ ንጉሡ አገር ሄዳ እንድትባርከው አዘዟት፡፡ እርሷም ይተዋት ዘንድ እያለቀሰች ብትለምናቸውም እነርሱ ግን "ይህ ንጉሥ ክርስቲያኖችን የሚወድ ጻድቅ ነው፣ ቅዱሳት መጻሕፍትም እንደሚያዙን ትእዛዙን መተላለፍ የለብንም" ብለው አስገድደው ላኳት፡፡ ወደ ንጉሡም በደረሰች ጊዜ ሁሉም በክብር ተቀብለው ተሳለሟት፡፡ ንጉሡና ንግሥቲቱም ለብቻቸው ሆነው ወደ ውስጠኛ ክፍል አስገቧትና ንጉሡ እንዲህ ብሎ ጠየቃት፡- "ልጄን ትስማት እንደነበር በሰማሁ ጊዜ በሀሳቤ ታውኬያለሁ፤ መነኵሴ ሴትን መ ሳም አይገባውምና ይህን ነገር ትገልጥልኝ ዘንድ እወዳለሁ" አላት፡፡ ❤ የከበረች ቅድስት ኢላርያም "በነገርኳችሁ ጊዜ ወደ አስጥስ ገዳም መሄድን ላትከለክሉኝ የከበረ ወንጌልን አምጥታችሁ ማሉልኝ" አለቻቸው፡፡ እነርሱም ማሉላት፡፡ በዚህም ጊዜ እርሷ ማለት ልጃቸው ኢላርያ መሆኗን ነገረቻቸው፡፡ እንዴት ከቤተ መንግሥት እንደወጣችም አስረዳቻቸውና በአካሏ ላይ ያለውን ምልክት አሳየቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ በቤተ መንግሥቱ ታላቅ ጩኸት ሆነ፡፡ አቅፈውም እየሳሟት አለቀሱ፡፡ "ከእኛ ዘንድ እንድትሄጂ ከቶ አንተውሽም" አሏት፡፡ እርሷም "በከበረ ወንጌል የማላቸሁትን መሐላ አስቡ" አለቻቸው፡፡ እሺ ብለው ግን እስከ 40 ቀን አብራቸው እንድትቆይ ለመኗት 40 ቀን አብራቸው ቆየች፡፡ ❤ ቅድስት ኢላርያም ወደ አስቄጥስ ገዳም ከተመለሰች በኋላ ንጉሡ ዘይኑን ለገዳሙ መነኮሳት ለፍላጎታቸው ይሆን ዘንድ የግብጽን ምድር ግብር እንዲሰጧቸው አዘዘ፡፡ በዚያም ወራት በአባ መቃርስ ገዳም 400 የመነኮሳት ቤቶች ተሠሩ፡፡ በአባ ዮሐንስ ገዳም 700 በአባ ሙሴ ገዳም 300 ቤቶቸ ተሠሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ 5 ዓመት ኖራ በሰላም ዐረፈች፡፡ ከዕረፍቷም አስቀድሞ እርሷ ሴት እንደሆነች ያወቀ የለም፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ኢላርያ ጸሎት ይማረን በከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 21 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ትሴብሖ ኢየሩሳሌም ለእግዚአብሔር። ወሰብሒዮ ለአምላክኪ ጽዮን። እስመ አጽንዐ መናሥግተ ኆኃትኪ"። መዝ 147፥1-2። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ1፥27-ፍ.ም።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "በከመ ሰማዕነ ከማሁ ርኢነ። በሀገረ እግዚአ ኃያላን በሀገረ አምላክነ። እግዚአብሔር ሣረራ ለዓለም"። መዝ 47፥8-9። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 4፥1-12፣ 2ኛ ዮሐ 1፥1-7 እና የሐዋ ሥራ 7፥30-35። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥47-57። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።                  

❤ በቀበሩዋትም ጊዜ ከዚያ ሦስት ቀን ኖሩ ዕረፍቷም የሆነው እሑድ ቀን በጥር ወር በሃያ አንድ በዚች ቀን ነበረ ጌታችንም ብርሃናውያን መላእክትን ላከ እነርሱም ሥጋዋን ከመቃብር ወስደው በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር አኖሩዋት። ❤ ሐዋርያ ቅዱስ ቶማስ ግን ያን ጊዜ አልነበረም በደመና ላይ ተጭኖ እርሱ ሲመጣ መላእክት ሲአሳርጓት እመቤታችንን አገኛት መላእክትም "ለአምላክ እናት ለእመቤታችን ድንግል ማርያም ና እጅ ንሣ" አሉት እርሱም ሰገደላትና ተሳለማት ከእርሷም ተባረከ ከዚህም በኋላ ወደ ሐዋርያት ደረሰ። እነርሱም እመቤታችን ማርያምን እንደ አረፈችና እንደ ቀበሩዋትም ነገሩት ቶማስም "ሥጋዋን እስከማይ አላምንም" አላቸው። ሥጋዋንም ያሳዩት ዘንድ ወደ መቃብርዋ በአደረሱት ጊዜ በመቃብር ወስጥ ሥጋዋን አላገኙም ደንግጠውም አደነቁ ያን ጊዜ ከመላእክት ጋር ወደ ሰማይ ስታርግ እመቤታችንን እንዳገኛት ቅዱስ ቶማስ ነገራቸው። ሐዋርያትም ይህን በሰሙ ጊዜ የእመቤታችንን ዕርገቷን ስለ አላዩ እጅግ አዘኑ ሥጋዋን በምድር ውስጥ ይተው ዘንድ እንዳልወደደ መንፈስ ቅዱስ አስገነዘባቸው። ከዚህም በኋላ አንድ ጊዜ ደግሞ እርሷን ያሳያቸው ዘንድ እንዳለው ጌታችን ቃል ኪዳን በማድረግ ተስፋ ሰጣቸው እነርሱም እሰሰከ ነሐሴ ዐሥራ ስድስት በተስፋ ኖሩ። ❤ የእመቤታችን የዕድሜዋ ዘመን ስሳ አራት ዓመት ነው በአባትና እናቷ ቤት ሦስት ዓመት ከሰባት ወር በቤተ መቅደስም ዐሥራ ሁለት ዓመት በዮሴፍ ቤት ሠላሳ አራት ዓመት ከሦስት ወር ከጌታችን ዕረገት በኋላ በወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ ቤት ዐሥራ አራት ዓመት ነው። የሕይወት የድኅነት አለኝታ የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በጸሎቷም ከክፉ ነገር ይጠብቀን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 21 ስንክሳር።                                                    ✝ ✝ ✝ ❤ #አቡነ_ጎርጎርዮስ_ዘኑሲስ፡- ይኸውም የቅዱስ ባስልዮስ ወንድም ነው፡፡ አገሩ ቂሳርያ ሲሆን የተሾመው ኑሲስ በተባለች ደሴት ላይ ነው፡፡ መናፍቁ ሰባልዮስ "አንድ ገጽ" በማለቱ ሌሎቹ መናፍቃንም መቅዶንዮስና አቡሊናርዮስ "መንፈስ ቅዱስ ህጹፅ" እና "ወልድ ሥጋ እንጂ ነፍስ አልነሳም" በማለታቸው በ381 ዓ.ም 150ው ሊቃውንት በቍስጥንጥንያ ተሰብስበው መናፍቃኑን ተከራክረው እረተው ሃይማኖትን ሲያጸኑ ከጢሞቲዎስ ጋር አንድ ላይ የጉባኤው አፈ ጉባዔ የነበረው ሊቁ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ ነበር፡፡ እርሱም በጉባኤው ላይ እነ መቅዶንዮስንና አቡሊናርዮስን ተከራክሮ በመርታት መልስ አሳጥቷቸዋል፡፡ ሃይማኖትንም አጽንቷል፡፡ ❤ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ቅዳሴ ሲቀድስ ጌታችን በርግብ አምሳል ሲወርድ ያየው ስለነበር ዘወትር እያለቀሰ ይቀድሳል፡፡ ከተጋድሎውም ጽናት የተነሣ ታማሚ ሆኖ ነበር፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት ተሹሞ 33 ዓመት ኖሯል፡፡ ከተጋድሎውም ብዛት ድካም አጋጥሞት ነበርና አንድ ቀን ወንድሙ ባስልዮስ ሊጠይቀው መጣ፡፡ ቅዱስ ጎርጎርዮስም እንደልማዱ ሊቀድስ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ እመቤታችን ተገለጠችለትና "ዕረፍትህ በዕረፍቴ ቀን ነውና ዛሬ ወደእኔ ትመጣለህ" አለችው፡፡ ጎርጎርዮስም የቁርባኑን ቅዳሴ ሲጨርስ ሕዝቡን በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ለመምከር ተነሣ ነገር ግን ከድካምና ሕመም ብዛት ሰውነቱ መቆም ስላልቻለ ወንደሙን ባስልዮስን "ዛሬ አንተ አስተምራቸው" አለው፡፡ ወዲያውም እንደሚያንቀላፋ ሆነና ዐረፍ አለ፡፡ በቀሰቀሱትም ጊዜ በሞት ዐርፎ አገኙት፡፡ ይኸውን ጥር 21 ቀን ነው፡፡ ❤ በስሙ የተጠራ አንድ ቅዳሴና ገድለ ዜና አለው፡፡ በትንቢት ተናጋሪነቱ፣ በደራሲነቱና በመምህርነቱ መጽሐፍ "ጎርጎርዮስ ዐቃቤ ሥራይ ቁስለ መድኃኒት ዘነፍስ" ይለዋል፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዑልያኖስ ወንድማማቾቹን ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በጸሎታቸው ሰዓት ደርሶባቸው እነርሱን ገድሎ መሥዋዕታቸውን ሊበላባቸው ሲመጣባቸው የቅዱስ መርቆሬዎስን ሥዕል በጸሎት ቢማጸኑ ሥዕሉ በገዘፈ ሥጋ ሆኖ በተአምራት ዑልያኖስን በጦር ወግቶ ገድሎላቸዋል፡፡                                                      ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅድስት_ኢላርያ፡- ይኽችም ቅድስት የሮሜው አገር ንጉሥ የዘይኑን ልጅ ናት፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ነው፡፡ ልጁ ቅድስት ኢላርያንም ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እያስተማረ አሳደጋት፡፡ ከሁለት ሴቶቹ ለጆቹ በቀር ወንድ ልጅ የለውም ነበር፡፡ ❤ ቅድስት ኢላርያም ዕድሜዋ ከፍ ሲል ዓለምን ፍጹም ንቃለችና የምንኵስናን ልብስ የመላእክትንም አስኬማ ትለብስ ዘንድ ወደደች፡፡ ከቤተ መንግሥትም ተደብቃ ወጥታ የወንድ ልብስ በመልበስ ወደ ግብጽ አገር ሄደች፡፡ ወደ አስቄጥስ ገዳምም ገብታ ስሙ አባ ባውሚን የሚባል ፍጹም ሽማግሌ ጻድቅ ሰውን አግኝታ የምንኩስና ሀሳቧን ነገረችው፡፡ እርሷም ሴት እንደሆነች ስትነግረው ምሥጢሯን ጠብቆ ለብቻዋ ከዋሻ ውስጥ አስገባት፡፡ እየጎበኛትም ልትሠራው የሚገባትን ሁሉ ያስተምራት ነበር፡፡ እንዲህም ሆና በዚያ ዋሻ ውስጥ 12 ዓመት ኖረች፡፡ ቅድስት ኢላርያ ፂም ስለሌላት ለአረጋውያን መነኮሳት ጃንደረባ ትመስላቸው ነበር፡፡ በወንድ ስም አጠራርም አባ ኢላርዮን ብለው ይጠሯት ነበር፡፡ ❤ ከአባቷ ዘንድ ያለችው ታናሽ እኅቷ ርኩስ መንፈስ አደረባትና ብዙ አሠቃያት፡፡ ያድኗትም ዘንድ አባቷ ብዙ በመድከም ገንዘቡን አወጣ ነገር ግን ልትድን አልቻለችም፡፡ መኳንንቶቹም ወደ ግብጽ አስጥስ ገዳም እንዲልካት ለንጉሡ ነገሩት-በዚያ ያሉ መነኮሳት ክብራቸውና ጸጋቸው በሮም አገሮች ሁሉ ታውቋልና፡፡ ንጉሡም የታመመችውን ልጁን ከብዙ ሠራዊት ጋር ወደ ግብጽ ላካት፡፡ ለመነኮሳቱም "… ሁለት ሴቶች ልጆችን ወለድኩ ነገር ግን አንደኛዋ ጥላኝ ጠፋች፣ ሁለተኛዋንም ርኩስ መንፈስ ይዞ መጨወቻ አደረገብኝ፡፡ ቅዱሳን አባቶቼ ሆይ ልጄን በጸሎታቸሁ ትፈውሱልኝ ዘንድ ቅድስናችሁን እለምናለሁ" የምትል ደብዳቤ ጽፎ ላከላቸው፡፡ መነኮሳቱም የንጉሡን ደብዳቤ ካነበቡ በኋላ በልጅቱ ላይ ጸለዩ፡፡ ነገር ግን ያደረባት ርኩስ መንፈስ ሊለቃት አልቻለም፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ አረጋውያኑ መነኮሳት ጃንደረባ የሚሏትን ኢላርያን ጠርተው እስካዳናት ድረስ የንጉሡን ልጅ ወስደህ "በላይዋ ላይ ጸልይ" ብለው ሰጧት፡፡ እርሷም "ይህ ለእናንተ እንጂ ለእኔ አይቻለኝም" ብትላቸውም ግድ አሏት፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ የታመመችውን ልጅ ወደ በዓቷ ወስዳ ጸሎት አደረገችላት፡፡ ሰይጣኑም ወዲያው ጥሏት ሸሸ፡፡ በጥቂት ቀንም ውስጥ ፈጽማ ዳነች፡፡ ቅድስት ኢላርያም እኅቷ እንደሆነች ታውቃለችና አቅፋ ትስማት ነበር ስለ ፍቅሯና ናፍቆቷም ወደ ውጭ እየወጣች ታለቅስ ነበር ነገር ግን ታማ የነበረችው እኅቷ አላወቀቻትም፡፡ ቅድስት ኢላርያም በጸሎቷ ከፈወሰቻ በኋላ ወደ አረጋውያኑ መነኰሳት ወስዳ "እነሆ በጸሎታች እግዚአብሔር ፈውሷታልና ወደ ንጉሡ አባቷ መልሷት" ብላ ሰጠቻቸው፡፡ እነርሱም እጅግ ደስ ብሏቸው ወደ አባቷ መለሷት፡፡

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ  አሜን"። ❤             ❤ #ጥር ፳፩ 21 ቀን። ❤ እንኳን #አምላክን_ለወለደች_ለእናታችን #ለእመቤታች_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም ለዕረፍቷ በዓል (ለአስተርእዮ ማርያም)፣ ለኑሲስ ኤጲስቆጶስ #ለቅዱስ_ባስልዮስ_ወንድም_ለከበረ_ለቅዱስ_ጎርጎርዮስ ዕረፍት በዓልና ለሮሜ አገር ንጉሥ ለዘይኑን ልጅ ለከበረች #ለቅድስት_ኢላርያ_ለዕረፍት በዓል በሰላምና በጤና እግዚአብሔር አምላክ አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #እመቤታችንንም_ከመጥምቁ #ቅዱስ_ዮሐንስ ጋር በደብረ ማሕው ከተገለጠችበት፣ #ከነቢዩ_ከቅዱስ_ኤርምያስ፣ #ከዮሐንስና_ከአባ_እስክንድር፣ በዋሻ ከሚኖሩ #ከቅዱስ_ኒቆላዎስና_ከኤጲስቆጶስ_ከአባ_ፊቅጦር ከሁሉም ከመታሰቢያቸው፣ በናፍቁ ንጉሥ በመርቅያን ዘመን በሰማዕትነት ከዐረፉ #ከቅዱሳን_ጳውሎስና_ከቀሲስ_ሲላስ ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                   ✝ ✝ ✝ ❤ #የእመቤታችን_የቅድስት_ድንግል_ማርያም ዕረፍት፦ ያን ጊዜ እመቤታችን በልጅዋ በጌታችን በፈጣሪያችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ መቃብሩ ቦታ ትጸልይ ነበር ከዚህም ዓለም እንደምትለይ መንፈስ ቅዱስ ነገራት ከዚህም በኋላ ከደብረ ዘይት ደናግል መጡ ጌታችን ነግሮዋቸዋልና እርሷም ነገረቻቸው። በዚያንም ጊዜ እመቤታችን እንዲህ ብላ ጸለየች "ልጄ ወዳጄም ጌታዬና ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ልመናዬን ተቀብለህ ደቀ መዝሙርህን ዮሐንስን በዚያች ሰዓት አምጣው። እንዲህም ሕያዋን እንደሆኑ ሐዋርያትን ሁሉንም ነፍሳቸውንም የለየሃቸውን አምጣቸው አንተ የሕያዋንና የሙታን አምላክ ነህና ላንተም ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን"። ❤ በዚያንም ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ ከኤፌሶን አገር ዮሐንስን ደመና ተሸክማ ወደ እመቤታችን ማርያም አደረሰችው ሰገደላትና በፊቷ ቁሞ እንዲህ አላት "ሰላምታ ይገባሻል ጌታችን ፈጣሪያችንንና መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የወለድሺው ጸጋን የተመላሽ ደስ ይበልሽ አንቺ ከዚህ ዓለም ሕይወት ትሒጂአለሽና። ይህም ስሙ ክቡር ምስጉን የሆነ ጌታችንና ፈጣሪያችን ድንቆች ተአምራቶችን በአንቺ ላይ ገለጠ በኋላ ነው"። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህን በሰማች ጊዜ እጅግ ደስ አላት እግዚአብሔርንም እንዲህ ብላ አመሰገነችው "ፈጣሪዬ ጌታዬ ላንተ ምስጋና ይሁን አንተ የለመንኩህን ሰጥተኸኛልና አሁንም ነፍሴን ተቀበለው ወደ ሰማይ ወደ አንተ ሊሳርጓት ከሚመጡ መላእክቶችህ ጋር በመምጣትህ የምለምንህን ሁሉ ስጠኝ"። ❤ በዚያንም ጊዜ ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል መጣ "እነሆ አሁን መላእክት ይደርሳሉ ሐዋርያትም ሁሉ ከምድር ዳርቻ በደመና ተጭነው ለሰማይና ለምድር ጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ወደ ሆነች ወደ ቅድስት ድንግል ይደርሳሉ"። ወዲያውኑ ሁሉም ሐዋርያት የሞቱትም ከመቃብራቸው ተነሥተው ወደ እመቤታችን ደርሰው ሰገዱላት "አምላካችን ከአንቺ የተወለደ ጸጋን የተመላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ እርሱ ከዚህ ዓለም ለይቶ ቃል ኪዳን እንደሰጠሽ በክብር በምስጋና ከርሱ ጋር የሳርግሻልና" አሏት። ❤ በዚያንም ጊዜ እመቤታችን በዐልጋዋ ላይ ተቀመጠች ሐዋርያትም እንዲህ አለቻቸው "ፈጣሪዬ ፈጣሪያችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚመጣ እናንተንም እንዳየኋችሁ እንደማየው አሁን አውቅሁ ከዚህ ከሥጋዬም ወጥቼ ወደዘላለም ሕይወት እሔዳለሁ ነገር ግን ትነግሩኝ ዘንድ እሻለሁ ከዚህም ዓለም እንደምለይ ከወዴት አወቃችሁ?"። "ጴጥሮንና ሐዋርያት ሁሉም ወዳንቺ እንመጣ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ አዘዘን በደመና ላይም በተጫን ጊዜ ወዳንቺ እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥንን ደረስን" አሏት። ❤ እመቤታችን ማርያምም ይህን ነገር ከሐዋርያት በሰማች ጊዜ ድምጿን ከፍ አድርጋ "ክርስቶስ ሆይ ክቡር ምስጉን የሆነ ስምህን ፈጽሜ አመሰግናለሁ። የእኔ የአገልጋይህን መከራ ተመልክተህ ድንቅ ኃይልን አድርገህልኛልና ከእንግዲህ ወዲያ ትውልድ ሁሉ ያከብሩኛል ያመሰግኑኛል"። ጸሎቷንና ምስጋናዋን ስትጨርስ ሐዋርያትን እንዲህ አለቻቸው "ዕጣን አምጥታችሁ በማጠን የጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ጥሩት" እነርሱም እንዳዘዘቻቸው አደረጉ። በዚያንም ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እልፍ አእላፋት መላእክት አጅበው እያመሰገኑት መጣና አረጋጋት ያዘጋጀላትንም ተድላ ደስታ ነገራት በዚያንም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተደረጉ ዕውሮች አይተዋልና ሐንካሶች ቀንተው ሒደዋልና ደንቆሮዎች ሰምተዋልና ለምጻሞች ነጹ አጋንንትም ከሰዎች ወጥተው ሔዱ ዲዳዎች ተናገሩ በሽታና ደዌ ያለበት ሁሉ ዳነ እመቤታችን ድንግል ማርያም ወዳለችበት ቤት በቀረቡ ጊዜ ከደዌያቸው ይፈወሳሉና። ❤ ከዚህም በኋላ እመቤታችን ተወዳጅ ልጅዋን እንዲህ አለችው "በአየር ውስጥ ተበትነው ከሚኖሩ ከሚያስደነግጡ ግሩማን መላእክት የተነሣ ከእሳት ባሕርም እፈራለሁ" ጌታችንም "እርሳቸው ለማንም በአንቺ ላይ ስልጣን የለውም" አላት። ከሥጋዋም የምትለይበት ጊዜ ሲደርስ ሐዋርያትና ደናግል ትባርካቸው ዘንድ እያለቀሱ ለመኑዋት እጅዋን በላያቸው ዘርግታ ባረከቻቸው በዚያንም ጊዜ ጌታችን ንጽሕት ነፍሷን ከሥጋዋ ለይቶ በመለኮታዊ እጆቹ ይዞ በብርሃን ልብስ አጐናጽፎ ወደ ከፍተኛ መኖሪያ ከእርሱ ጋር አሳረጋት ሥጋዋን ግን እንደሚገባ ገንዘው ወደ ጌቴሴማኒ ተሸክመው እንዲወስዷት ሐዋርያትን አዘዛቸው። ❤ ነፍሷ ከሥጋዋ ከመውጣቷ በፊት በሰው አንደበት ይህ ነው ተብሎ የማይነገር ብርሃንን እያያች ነበር በክብር ባለቤት ጌታችን ክርስቶስም "እንግዲህ ሥጋሽን ተድላ ወዳለበት ገነት አፈልሳለሁ ዳግመኛም ሥጋሽን ከነፍስሽ ጋር አዋህጄ አስነሥቼ መላእክት በውስጡ በፊትሽ ሁነው በሚያመሰግኑበት ተመሳሳይ በሌለው ተድላ ደስታ በአለበት ማደሪያ አኖርሻለሁ" አላት። እመቤታችንም እንዲህ አለች "አቤቱ በረቀቀ ጥበብህ ይህን ሁሉ የሠራህ አመሰግንሃለሁ ሁለተኛም ልመናዬን ትሰማ ዘንድ እለምንሃለሁ በስሜ ወዳንተ የሚለምነውን ሁሉ ልመናውን ተቀበለው በመከራም ውስጥ ሁኖ ስሜን ጠርቶ ወዳንተ የሚለምነውን ከመከራው ሁሉ አድነው በሰማይም በምድርም በሥራው ላይ ሁሉ አንተ ከሀሊ ነህና መታሰቢያዬን በውስጧ የሚያደርጉባትን ቦታ ሁሉ ባርክ በእኔ ስም የሚያቀርቡትን የሁሉንም መሥዋዕታቸውን ተቀበል"። ጌታችንም እንዲህ ብሎ መለሰላት "የለመንሺኝን ሁሉ አደርግልሻለሁ ደስ ይበልሽ ከእኔ ከአባቴ ከመንፈስ ቅዱስ ዘንድ ጸጋ ክብር ባለሟልነት ተሰጥቶሻልና ስምሽንም ጠርቶ የሚለምን ሁሉ በዚህም ዓለም በሚመጣውም ዓለም አይጠፋም"። ❤ እመቤታችንም ከአረፈች በኋላ ጌታችን እንዳዘዘ ወደ ጌቴሴማኒ ሊወስዷት ሐዋርያት ገንዘው ተሸከሟት። አይሁድም በሰሙ ጊዜ ሥጋዋን ሊአቃጥሉ ወጡ ከእርሳቸው አንዱ ስሙ ታውፋንያ ከምድር ላይ ይጥላት ዘንድ የእመቤታችንን ዐልጋዋን ያዘ ያን ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ እጆቹን በእሳት ሰይፍ ቀጣውና እጆቹ በዐልጋዋ ላይ ተንጠለጠሉ። ያን ጊዜ በጌታችን አምኖ ወደ እመቤታችን እያለቀሰ እንዲህ ብሎ ለመነ "የእውነተኛ አምላክ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እናት አንቺ በእውነት ድንግል የሆንሽ በእኔ ላይ ይቅርታ ታደርጊ ዘንድ እለምንሻለሁ" በሐዋርያትም ልመና እጆቹ ተመልሰው እንደቀድሞው ደኅነኞች ሆኑ።

❤ በዚያን ጊዜም የመኰንኑ የአርያኖስ ወንድ ልጁ ሞተበትና እጅግ አዘነ፡፡ የከበረ አባ አክሎግም በዚህ ጊዜ "ፈጣሪዬን ለምኜ ልጅህን ከሞት ባስነሣልህ ምን ትሰጠኛለህ?" አለው፡፡ መኰንኑም እጅግ አዝኖ ተጨንቋልና ቅዱስ አክሎግን "የመቶ አለቃ አድርጌ ሾሜ በታላቅ ክብር ወደ አገርህ እልክሃለሁ" አለው፡፡ ቅዱስ አክሎግ ግን "ይህንንስ ፈጽሞ አልሻም ይልቁንም አሠቃይተህ ገድለህ ሰማዕትነቴን ትፈጽምልኝ እሻለሁ፣ ሥጋዬንም ወደ አገሬ እንድትልከው ማልልኝ" አለው፡፡ መኰንኑ አርያኖስም በቅዱስ አክሎግ ቃል እጅ ተገርሞና አዝኖ እንደምኞቱ ሊፈጽምለት እሺ ብሎ ማለለት፡፡ ❤ ቅዱስ አክሎግም ወደ ጌታችን ከጸለየ በኋላ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ" ብሎ በሕፃኑ ላይ በመስቀል ምልክት ባማተበ ጊዜ ወዲያው የሞተው ሕፃን አፈፍ ብሎ ተነሣ፡፡ ይህንንም ታላቅ ተአምር ያዩ አሕዛብ ሁሉ "በእውነት ከቅዱስ አክሎግ አምላክ በቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ እኛም በቅዱስ አክሎግ አምላክ አምነናል" ብለው ጮኹ፡፡ መኰንኑም ይህንን ባየጊዜ ተቆጣ፡፡ ከከተማም አውጥተው ሰፊ ጉደጓድ ቆፍረው በውስጡ እሳት አንድደው እንዲጨምሯቸው አዘዘ፡፡ እንዳዘዘውም አደረጉባቸውና ምስክርነታቸውን በድል ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ ቁጥራቸውም ስምንት መቶ ዘጠኝ ሆነ፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ቅዱስ አክሎግን በጽኑ ሥቃይ አሠቃየው፡፡ ወደ ሀገሩም ወስደው በዚያ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡት ዘንድ አዘዘ፡፡ ቅዱስ አክሎግም ይህንን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው፡፡ ወደጌታችንም በጸለየ ጊዜ ጌታችን በክብር ተገለጠለትና "ወዳጄ የምወድህ የአባቴና የመንፈስ ቅዱስ ወዳጅ ሰላም ለአንተ ይሁን" አለው፡፡ ዳግመኛም "ዋጋህን ልከፍልህ በመንግሥቴም ውስጥ ላሳርፍህ መጣሁ፤ ሦስት አክሊላትንም አዘጋጀሁልህ፣ አንደኛው ስለ ድንግልናህ፣ ሁለተኛው ስለ ሥቃይህ፣ ሦስተኛውም የዚህም ዓለም ክብር ንቀህ ስለተውህ ነው፡፡ በዚህች ዕለት ከእኔ የምትሻውን ሁሉ አደርግልሃለሁ፡፡ ስለ ስሜ ስለተሠቃየህ የማያልቅ ተድላን እሰጥሃለሁ፣ የመላእክት ሠራዊትም እንዲያገለግሉህ አደርጋለሁ፡፡ ዘላለማዊ ሕይወት ባለው በማዕዴ ውስጥ ከሁሉ ቅዱሳን ጋር ደስ አሰኝሃለሁ፡፡ ሥጋህ ባለበት የሚማልደውን ሁሉ ርዳታ የሚሻውንም በእግር ውስጥ ያለውንም በደዌ የተያዘውንም ሁሉ እኔ አድነዋለሁ፡፡ ልጁንም በስምህ የሚሰይመውን ሁሉ እኔ ልጁን እባርክለታለሁ፣ በበጎ አስተዳደግም አሳድገዋለሁ፣ ከክፉ ነገር እጠብቀዋለሁ፡፡ በስምህ መባ የሚያገባ ለጦም አዳሪዎቸም እስከ ቀዝቃዛ ውኃ ምጽዋት የሰጠውን ኃጢአቱን ይቅር ብዬ የዘላለም ሕይወትን አርሰዋለሁ፡፡ ተክል ተክሎ፣ ዘር ዘርቶ በስምህ የሚለምነኝን ዘሩን እባርክለታለሁ፣ ፍሬውንም አበዛለታለሁ" አለው፡፡ ጌታችንም ከቅዱስ አክሎግ ጋር መነጋገርን በፈጸመ ጊዜ ባረከውና ከቀስሉ ሁሉ ፈውሶ ጤነኛ አደረገው፡፡ ሰማዕትነቱንም በትዕግስት እንዲፈጽም ነግሮት በክብር ዐረገ፡ ❤ ከዚህም በኋላ አባ አክሎግ ወደ ወታደሮቹ መለስ ብሎ "የታዘዛችሁትን ፈጽሙ" ብሎ ራሱን እንዲሰይፉት ሰጣቸው፡፡ ወታሮቹም በዚህ ጊዜ የቅዱስ አክሎግ ፊቱ እንደፀሐይ ሲያበራ አዩት፡፡ ከፊቱም የብርሃን ግርማ የተነሣ ወደ እርሱ መቅረብ ተሳናቸው፡፡ ከእነርሱም ውስጥ አንደኛው ወታደር እጁን ዘርግቶ የቅዱስ አክሎግን አንገት በሰይፍ መታውና ቅዱሱ ሰማዕትነቱን በድል ፈጸመ፡፡ ቅዱሳን መላእክትም የቅዱስ አክሎግን ነፍስ በክብር ተቀብለው በዝማሬ ወደ ሰማይ አሳረጓት፡፡ ❤ ወታደሮቹም የአባ አክሎግን ሥጋ ከባሕሩ ዳርቻ ትተው በመርከብ ተሳፍረው ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ ከዚያም ጐልማሶች ነበሩ ስለ ከበረ አባ  አክሎግን በሰማዕትነት መሞት ወደ አገር ውስ ገብተው ለሕዝቡ ነግሩዋቸው። ሕዝቡም በሰሙ ጊዜ ተሰብስበው ከካህናቱ ጋር ሔዱ አንሥተው ተሸክመውም ወደ አገር ውሰሰጥ አድርሰው በአማረ ቦታ አኖሩት፡፡ ከእርሱም ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ በአባ አክሎግ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                          ✝ ✝ ✝ ❤ "ሰላም ለመርምህናም ሰማዕት ፍጹም ኄር ገባሬ ተአምር"። ትርጉም፦ ፍጹም ደግ ተአምራትን አድርጊ ለኾነ ለሰማዕቱ መርምህናም ሰላምታ ይገባል። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ።                           ✝ ✝ ✝ ❤ "ሰላም እብል አብሮኮሮስሃ ክቡረ። ዘአድምዐ በኒቆምድያ ዘኤጲስቆጶስ መንበረ። እንዘ ይስዕም አምላክ ለአፈ ዮሐንስ ምዕረ። ስምዐ ኮነ በሰማይ ከመ ውእቱ ነጸረ። እስመ ውእቱ ረድእ ዘይተሉ መምህረ"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ) የጥር 20።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ደቂቀ እጓለ እምሕያው ይትዌከሉ በታሕተ ክነፊከ። ወይረውዩ እምጠለ ቤትከ። ወትሰቅዮሙ እምፈለገ ትፍሥሕትከ"። መዝ 35፥7፥8። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 12፥28-ፍ.ም፣ ይሁ 1፥17-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 2፥1-22። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥12-21። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ አብሮኮሮስና የቀሲስ የቅዱስ አክሎግ የዕረፍታቸው በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።                  

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ  አሜን"። ❤             ❤ #ጥር ፳ (20) ቀን። ❤ እንኳን ጌታችን ወንጌልን ይሰብኩ ዘንድ በሽተኞችንም ይፈውሱ ዘንድ መርጦ ወደ ዓለም ከላካቸው ቁጥሩ ከሰብዓ ሁለቱ አርድእትና #ከሰባቱ_ዲያቆናት_ለሆነ_ለቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌላዊው ደቀ መዝሙር #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_አብሮኮሮስ ለዕረፍት በዓል፣ ልጁን በስምህ የሚሰይመውን ሁሉ እኔ እባርከዋለሁ ብሎ ጌታችን ቃል ኪዳን ለገባለት በግብጽ አገር እልፈንት ከሚባል ከተማ ለከበረ #ቀሲስ_ለቅዱስ_አክሎግ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና ለታላቁ ሰማዕት #ለቅዱስ_መምህናም ቤተ ክርስቲያኑ ለከበረችበትና ተአምራቱ ለተገለጠበት በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከሰማዕቱ_ቅዱስ_ብሕኑ ከመታሰቢያው፣ ከወንጌሉ ዘወርቅ #ከቅዱስ_ዮሐንስም ቤተ ክርስቲያኑ ከከበረችበትና ሥጋው ወደ ሮሜ ከፈለሰችበት፣ #ከአባ_ኖኅ_ከአባ_ስልዎኖስና #ከአባ_አብድዩ ከመታሰቢያቸው ረድኤት በረከትን ያሳትፈን።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱስ_አብሮኮሮስ፦ ይህም ቅዱስ በጽርሐ ጽዮን ከሐዋርያት ጋር ሁኖ ሳለ የአጽናኝ መንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተመላ። እርሱም ሐዋርያት መርጠውት ከሰባቱ ዲያቆናት ጋር የተቆጠረ ሆነ እነርሱ መንፈስ ቅዱስ ያደረባቸው ዕውቀትም ያላቸው እንደሆኑ ሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ስርሳቸው ምስክር ሆነ። ❤ ከዚህም በኋላ ለወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ ደቀ መዝመሩ ሆነ ከእርሱም ጋር ወደ ብዙ አገሮች ሔደ በቢታንያ አገር በኒቆምድያ ከተማ ላይ በአንብሮተ እድ ኤጲስቆጶስነት ሾመው። እርሱም የክብር ባለ ቤት የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት አስተማረ ከዮናናውያንም ብዙዎችን መልሶ ወደ ቀናች ሃይማኖት አስገባቸው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው የወንጌልንም ትእዛዞች እንዲጠብቁ አስተማራቸው ቤተ ክርስቲያንንም ሠርቶ ቀሳውስትን ዲያቆናትን ሾመላቸው። ❤ ከዚህም በኋላ ያቺን አገር ወደሚከቧት አገሮች ወጣ በውስጣቸውም የከበረ ወንጌልን ሰበከ ብዙዎችንም ከስሕተት መለሳቸው አይሁድንም የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ነገር ግን ብዙ መከራና ስደት ደረሶበታል ስለ ክርስቶስ ስም ተጋድሎ በመልካም ሽምግልና ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ በቅዱስ አብሮኮሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #ቀሲስ_አባ_አክሎግ፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ዲዮስቆሮስ የእናቱ ስም አፎምያ ነው እነርሱም ከከበሩ ወገኖች ውስጥ ናቸው በወርቅ በብር ባላሞችና በበጎች በፈረሶችና በግመሎች እጅግ የበለጸጉ ናቸው ነገር ግን ልጅ የላቸውም ስለዚህም ያዝኑ ነበር። ልጅምንም ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ሲለምኑ ኖሩ ልመናቸውንም ተቀብሎ ይህን የተባረከ ልጅ ሰጣቸው ስሙንም አክሎግ ብለው ጠሩት ይህ በእግዚአብሔር ዘንድ ጣዕም ያለው ይሆናል ማለት ነው። ❤ ስምንት ዓመትም በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔርን ሕግ ይማር ዘንድ ለመምህር ሰጡት የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት ሁሉ ተማረ ሁል ጊዜም ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሔድ ምስጋናዎችንና ጸሎቶችን ይሰማል ይህንንም የሚያደርግ ወደ መምህር ከመሔዱ አስቀድሞ ነው። ❤ በአንዲትም ዕለት ከመምህሩ ዘንድ ወጣ ወደ ቤቱም ሊሔድ በፈረስ ተቀምጦ ሁለት አገልጋዮችም ተከትለውት ሲጓዙ ብዙ ወንዶችና ሴቶች ተሰብስበው ሲጮሁ አያቸው የሆነውንም ሊያይ ወደ ርሳቸው ቀረበ። እባብ የነከሰውና ለሞትም የቀረበ አንድ ሕፃን በመካከላቸው ወድቆ አገኘ። የከበረ አክሎግም "ይቺ ምልክት በስሜ የሚያምኑትን ትከተላቸዋለች በስሜም አጋንትን ያስወጣሉ አዳዲስ ቋንቋን ይናገራሉ የምድር አራዊቶችን በእጃቸው ይይዛሉ የሚጐዳቸውም ነገር የለም" ያለውን የከበረ የወንጌልን ቃል አሰበ። በዚያንም ጊዜ የሕፃኑን እጅ ይዞ "በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም" ብሎ በላዩ በመስቀል አማተበና "ሕፃን ሆይ ከዚህ ክፉ እባብ መርዝ ትድን ዘንድ እናገርሃለሁ ጌታችን ንጹሕና እውነት በሆነ ቃሉ እባቡን ጊንጡን የጠላትን ኃይል ሁሉ ትረግጡ ዘንድ እነሆ ሥልጣን ሰጠኋችሁ ምንም የሚጐዳችሁ ነገር የለም ብሏልና" አለ ወዲያውኑ ያ ልጅ ዳነ ከክፉ ነገርም ምንም ምን እንዳልደረሰበት ሆነ። ሕዝቡም ይህን ተአምር በአዩ ጊዜ እጅግ አደነቁ በቅዱሳኑ አድሮ ድንቅ ሥራ የሚሠራ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት የዚችም ተአምር ወሬዋ በአገሩ ሁሉ ተሰማ። ❤ ከመምህሩም ዘንድ ዐሥራ ሁለት ዓመት በሆነው ጊዜ አራቱን ወንጌሎች የሐዋርያት ሥራ ዐሥራ አራቱን የቅዱስ ጳውሎስን መልእክቶች ሰባቱን የሐዋርያት መልክታት የቅዱስ ዮሐንስንም ራእይ መቶ ሃምሳውን የቅዱስ ዳዊትን መዝሙራት የነቢያትንና የሰሎሞንን መኀልይ ጠንቅቆ አጠና። ሁል ጊዜ በቀንና በሌሊት ያነባል በእሑድ ሌሊትም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያገለገለ ያድራል ሁል ጊዜም አዘውትሮ ይጾማል ይጸልያል። ❤ ወላጆቹም ከአረፉ በኋላ ሰዎች መልካም ተጋድሎውን በአዩ ጊዜ ስለ እነርሱ ይጸልይ ዘንድ ቅስና እንዲሾምላቸው ኤጲስቆጶሱን ለመኑት እርሱ በዘመኑ ሁሉ በየሁለት ቀን በየሦስት ቀን በየሱባዔው ይጾማልና በልብሱም ውስጥ ማቅ ይለብሳልና። ቅስና ይሾም ዘንድ የእግዚአብሔር ጸጋ ጠራቸውና ኤጲስቆጶሱም ወስዶ ሳይወድ በግድ ቅስና ሾመው በተሾመ ጊዜም ለአባ አክሎግ የክህነት ሹመት ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል እያለ ሲጮህ ሕዝቡ ቃልን ሰሙ ኤጲስቆጶሱና ሕዝቡ ቃልን ሰሙ ኤጲስቆጶሱና ሕዝቡም እጅግ አደነቁ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። ❤ ከእነዚያ ወራቶችም በኋላ በአገሩ ሁሉ በክርስቲያን ወገኖች ላይ ከከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘንድ ታላቅ መከራና ስደት ሆነ አብያተ ክርስቲያናትንም አፈረሰ ብዙዎችም በሰማዕትነት ሞቱ። ምስክርም ይሆን ዘንድ አባ አክሎግን እግዚአብሔር ጠራው እነርሱም ቆመ ወደሰማይም ቀና በማለት እንዲህ ብሎ ጸለየ "ዓለሙን ሁሉ የያዝክ ጌታዬ ፈጣርዬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በአገርህ በሁለመናዋ ላሉ ሕዝብ ቸርነትህን ይቅርታህንና ሰላምህን አድርግ። ትባርካቸውም ዘንድ ከሰይጣናትም ስሕተት ታድናቸው ዘንድ ለእኔም ስለ ከበረው ስምህ ታጋድሎዬን እስከምፈጽም ያጸናኝ ዘንድ ቸር መልአክህን እንድትልክልኝ እለምንሃለሁ ኃይል ክብር ገንዘብህ የሆነ ለዘላለሙ አሜን"። ❤ ከዚህም በኋላ በዙሪያው ወዳሉ ሰዎች ተመልሶ "የሚሻ ይምጣ ከእኔ ጋር ይሒድ" አለ የእርሱ ሰዎችና የአገሩ ሰዎች ሦስት መቶ አርባ ተከተሉት በከፍታ ቦታ ላይም ቁመው "እኛ በግልጥ ክርስቲያን ነኝ" ብለው ጮኹ። የንጉሡም የሠራዊት አለቃ ሰምቶ አዘነ አባ አክሎግንም አሥሮ ለመኰንኑ ለአርያኖስ ሰጠው እርሱም "ለአማልክት ስገድ" አለው አባ አክሎግም "ለክብር ባለቤት እሰግዳለሁ እንጂ እኔ ለረከሱ አማልክት አልሰግድም" አለ። ❤ በዚያንም ጊዜ መኰንኑ አርያኖስም ተቆጣ ይዞ እጅግ ጽኑ በሆኑ ልዩ ልዩ ማሠቃያዎች አሠቃየው፡፡ ብዙ ካሠቃየውም በኋላ እንዲሞት ከእሳት ምድጃ ውስጥ በከተተው ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ እሳቱን እንደ ውኃ አቀዘቀዘለት፡፡ ከዚህም በኋላ መኮንኑ 340ውን ሰዎች ጠርቶ ለአማልክት እንሰግዱ ግድ አላቸው፡፡ እነርሱም "የምሰግድለት አምላካችን እግዚአብሔር ብቻ ነው" በማለት ጣዖታቱን ረገሙበት፡፡ መኰንኑም ራስ ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጧቸው ዘንድ አዘዘ፡፡ እንደትእዛዙም በየተራ ቆረጧቸውና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ የከበረቸ በረከታቸው ትደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ  አሜን"። ❤             ❤ #ጥር  ፲፱ (19) ቀን። ❤ እንኳን ለከበሩ #ለአባ_ዝሑራ°ለአባ_ባሱራ ለእናታቸው #ለቅድስት_ኔራ ሥጋቸው ለተገኘበት በዓልና #ለዘመነ_አስተርዮ_አራተኛ_ሳምንት ዕለተ እሑድ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦  #ከቅድስት_በርስጢና ከመታሰቢያዋ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                ✝✝✝ ❤ #የአባ_ዝሑራ_የአባ_ባሱራ_የእናታቸውም_የኔራ ሥጋቸው መገኘት፦ እሊህ የከበሩ ተጋዳዮችም ጣዖት በሚመለክበት ዘመን ሳብሳ ከሚባል አገር በሰማዕትነት ሞቱ ሥጋቸውም በሳብሳ አገር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚኖሩ ሆኑ ከንጹሐን ሰማዕታትም ዘመን ከዘጠኝ መቶ አርባ ሰባት ዓመት በኋላ የአፍርንጊ ሠራዊት ግብጽን ከበቧት የድምያጥንም ከተማ ወስደው በዚያ ነገሡ ከርሷ ጋርም በዙሪያዋ ያሉ ታላላቅ ከተሞችን ያዙ። ❤ የኮሞል ንጉሥም ይህም የግብጽ ንጉሥ ነው አፍርንጊያውያንንም ይወጋቸው ዘንድ ከግብጽ አገር ሁሉ ብዙ ሠራዊትን ሰበሰበ ሠራዊቱም ሲጓዙ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አፈረሱ ከፈረሱትም ውስጥ አንዲቷ የእሊህ ቅዱሳን ሰማዕታት ሥጋቸው በውስጧ ያለባት ናት። ከሠራዊቱም አንዱ የቅዱሳን ሰማዕታት ሥጋ ያለበትን ሣጥን ወሰደ በውስጡ የሚደሰትበትን የዚህ ዓለም ገንዘብ እንደሚያገኝ አስቦ በከፈተው ጊዜ ከዕንቊ የከበረ የቅዱሳንን ሥጋቸውን አገኘ ክብራቸውን ግን አላወቀም ከቤተ ክርስቲያኑ ገድግድ ላይ ሥጋቸውን በትኖ ሣጥኑን ወስዶ ሸጠው። ❤ ምሕረቱ የበዛ የሚታገሥ ልዑል እግዚአብሔር ወደ አፍርጊ ሠራዊት እስከሚደርስ በእርሱ ላይ ታገሠ ጦርነትም በገጠሙ ጊዜ ከሁሉ አስቀድሞ እርሱ ተገደለ ባልጀሮቹም ምስክር እንደሆኑ ወደ አገራቸው በተመለሱ ጊዜ የእግዚአብሔርን ክብር ፈጽመው ሰበኩ እንዲህም አሉ "እርሱ አስቀድሞ በሰይፍ ተመታ ራሱንም ተቆረጠ ጎኖቹንም ሠነጣጥቀውት በክፉ አሟሟት ሞተ"። ❤ ቅዱሳኑን ሥጋቸውን ያ ሰው በበተናቸው ጊዜ የአንድ ቄስ ሚስት የሆነች አንዲት ምእመን ሴት ቁማ ትመለከት ነበር ከዚህም በኋላ በጭልታ ወደርሳቸው ገብታ ደስ እያላት ወስዳ በመጐናጸፊያዋ ጠቀለለቻቸው እስላሞችንም ከመፍራቷ የተነሣ በቤተ ክርስቲያን ማዕዘን ውስጥ አኖረቻቸው በመጐናጸፊያዋም እንደ ተቀለሉ በጡብ ሸፈነቻቸው በዚያም ጡብ ተሸፍነው በዚያች ማዕዘን ውስጥ ሃያ ዓመት ያህል ኖሩ ከቀን ብዛትም የተነሣ ያቺ ሴት ወሬያቸውን ረሳች። ❤ እግዚአብሔርም ለወገኖቹ ጥቅም ይገልጣቸው ዘንድ በወደደ ጊዜ በዚያች ሴት ፊት ሌሎች ሰዎች አስታወሷቸው እርሷም በዚያን ጊዜ አስታወሰቻቸው ለካህናቱና ለምእመናኑ ነግራ ቦታቸውን አሳየቻቸው። ካህናቱም ገብተው ሥጋቸውን አነሡ ያማረች ሣጥንንም ሠርተው በውስጧ በክብር አኖሩዋቸው እንደ በዛሬዪቱም ዕለት በዓልን አደረጉላቸው ሁል ጊዜ በዚች ዕለት በዓል ያደርጉላቸው ዘንድ ስማቸውን በበዓላት ግጻዌ መጽሐፍ እንዲጽፉ የአገሩ ኤጲስቆጶስ አባ ገብርኤል አዝዟልና። ❤ ከዐፅሞቻቸውም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ከተአምራቶችም አንዲት የታወረች ልጅ ያለቻት ሴት ነበረች ተስፋ ከቆረጠችም በኋላ ከቅዱሳኑ ዐፅም በተማፀነች ጊዜ ዐይኖቿ ተገልጠውላት አየች እሊህም ሰማዕታት በዚህ ክብር ያከበራቸውን የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስን አመሰገነችው በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን አሜን። ምንጭ፦ የጥር 19 ስንክሳር።                        ✝️ ✝️ ✝️ ❤ "#ሰላም_እብል_ዘሥጋሆሙ_ርክበተ። ለዝሑራ ወባሱራ ወለዘወለደት እሎንተ። አመ ሣፁኖሙ ነሥአ እንዘ ይመስሎ ጥሪተ። ለዘዘረወ ሥጋሆሙ ፈደይዎ ሞተ። ወዘተማሕፀነት ቦሙ ፈወሱ ዕውርተ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥር_19።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር የዐቅዐብ ኵሎ አዕፅምቲሆሙ። ወኢይትቀጠቀጥ አሐዱ እምውስቴቶሙ። ሞቱ ለኃጥእ ጸዋግ። መዝ 33፥20-21 ወይም መዝ 78፥10-11።  የሚነበቡት መልዕክታት ቈላ 1፥27-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 5፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 4፥32-36። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 24፥3-15። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ አፍቅረነ እግዚእ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።                

ሥርዓተ ቀብራቸው በደብረ ሊባኖስ  ገዳም ይፈጸማል። ቅዱስ ሲኖዶስ የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ለ#EOTCTV እንደገለጸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የገዳማት መምሪያ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ዕንባቆም ሥርዓተ ቀብር ነገ ጥር 19 ቀን 2018 ዓ.ም በተማሩበት በመነኮሱበት እና ለረጅም ዓመታት ባገለገሉበት በታላቁ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ይፈጸማል።

#ዜና_ዕረፍት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የገዳማት መምሪያ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ #ብፁዕ_አቡነ_ዕንባቆም ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ። ብፁዕነታቸው በተለይም በተለያዩ አህጉረ ስብከት
#ዜና_ዕረፍት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የገዳማት መምሪያ የበላይ ኃላፊ ሊቀ ጳጳስ #ብፁዕ_አቡነ_ዕንባቆም ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ። ብፁዕነታቸው በተለይም  በተለያዩ አህጉረ ስብከት በአባትነት ያገለገሉ ሲሆን በተለይም የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከትና ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ተጠቃሾች ናቸው። የብፁዕነታቸው በረከታቸው ይደርብን።

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ  አሜን"። ❤           ❤ #ጥር  ፲፰ (18) ቀን። ❤ እንኳን #ለፀሓየ_ልዳ_ለኮከበ_ፋርስ ለሰማዕታት አለቃ #ለቅዱስ_ጊዮርጊስ (ለዝርወተ ዐፅሙ) ዐፅሙ ተቃጠጥሎ ተደቁሶ በይድራስ ተራራ በነፋስ ከተበተነ በኋላ ከሞት ለተነሳበት ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና በገድል ለተጸመደ ለከበረ አባት #ለቅዱስ_ኤፍሬም_ሶርያዊ_መምህሩ ቁጥሩ ከሠለስቱ ምዕት ለሆነ ለአገረ ንጺቢን ኤጲስቆጶስ #ለአባ_ያዕቆብ_ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚህ ቀን ከሚታሰቡ፦ ከአራት ቀኖች በኋላ ጌታች ከመቃብር ያነሳ  #ከአልዓዛር_እኅቶች_ከቅድስት_ማርያምና #ከቅድስት_ማርታ_ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                       ✝ ✝ ✝ ❤ #የቅዱስ_ጊዮርጊስ_ዝርወተ_አፅሙ፦ በዚች ቀን ሰባ ነገሥታት ማሰቃየት በሰለቻቸው ጊዜ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንደ መጭመቂያ ሆኖ ከተሠራ የስቃይ መሣሪያ ላይ አውጥተው ሰውነቱን እንዲሰነጥቁት ንጉሥ ዱድያኖስ አዘዘ፡፡ አንጀቱ ሁሉ ወጥቶ ከምድር ላይ እስኪዘረግፉት ድረስ እንዲህ አደረጉበት፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከስቃይ ብዛት የተነሳ ነፍሱ ከሥጋው ተለየች ሥጋውንም በሙሉ በእሳት አቃጠሉት አመድም ሆነ፡፡ ❤ ከሐዲው ንጉሥ ዱዲያኖስ የተቃጠለውን የሥጋውን አመድ አፍሰው በቀፎ አድርገው ይድራስ ወደሚባል ተራራ ወስደው ምዕመናን ራሩን አመዱን እንኳን እንዳያገኙት በነፋስ እንዲዘሩት አዘዘ፡፡ ደብረ ይድራስ ማለት ምድረ በዳ ማለት ነው፡፡ ወታደሮቹም የሥጋውን አመድ በተራራ ላይ ነስንሰው የተመለሱበት፣ የሥጋው አመድ ያረፈበት ዕፅዋት ሁሉ ጊዮርጊስ ጊዮርጊስ ያሉበት፣ ጌታችን ከመላእክት ጋር ተገልጦ አራቱን የምድር ነፋሳትንም የቅዱስ ጊዮርጊስ የሥጋውን ትቢያ እንዲሰበስብ አዞ። "የኔ ሆይ! የመረጥኩህ ወዳጄ ጊዮርጊስ ከሞት ተነሥ አትፍራ፤ እኔ አዝዤሀለሁና" ሲል ኀያሉን ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ጠራው። ያን ጊዜ ልዑል ንዑድ ጊዮርጊስም ከጫጉላ ቤት እንደሚወጣ ሙሽራ ምንም ሕማም ሳይኖርበት ተነሣ። ❤ መድኃኒታችንም ባረከው። "አትፍራ፤ ይኸንን ከሀዲ ንጉሥም እስክታሳፍረው ድረስ እኔ አጸናሀለሁ። ከእንዲህስ ወዲህ አምላኩ ከእጃችን ሊያአድነው አይችሉም እንዳይሉ እነዚህን ከሐድያን ነገሥታትና የረከሱ ጣዖታቸውን ታሳፍራቸው ዘንድ ተነሣና ወደ አገር ውጣ፤ ሰላሜ ለዘለዓለም ከአንተ ጋር ይሁን" አለው፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ተናግሮ ሳመው። በፍጹም ምስጋናም ወደ ሰማይ ዐረገ። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከጌታች ይህንንም ቃል ኪዳን የተቀበለበት ቀን ነው፡፡ ምንጭ፦ገድለ ቅዱስ ጊዮርጊስ።                                                     ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ያዕቆብ_ዘንጽቢን፦ ይህም ቅዱስ ተወልዶ ያደገው በንጽቢን ከተማ ነው እርሱ ግን ሶርያዊ ነው ከታናሽነቱም የምንኵስና ልብስ መልበስን መረጠ ከጠጕር የተሠራ ማቅንም ለበሰ በጾም በጸሎት ተወስኖ በቀን በሌሊት በበጋ በሐሩር በክረምት ቊር የሚጋደል ሆነ ያንንም ማቅ ከቶ ከሥጋው ላይ አያወጣውም ነበር ምግቡም ቅጠላቅጠል ነው የሚጠጣውም የዝናብ ውኃ ብቻ ነው ስለዚህ ሥጋው ብሩህ ሆነ ነፍሱም እጅግ በራች። ❤ እግዚአብሔርም ሀብተ ትንቢት ድንቆች ተአምራቶችንም የመሥራት ጸጋን ሰጠው ለሰዎችም ከመሆኑ በፊት የሚሆነውን ይነግራቸውና እንዲሁም ይሆናል። ተአምራቱም እጅግ ብዙ ነው በአንዲትም ቀን ሴቶች በውኃ ምንጭ ላይ ያለማፈር ሲጫወቱና ሲሣለቁ አያቸው የውኃውንም ምንጭ አደረቀ የራሳቸውንም ጠጒር ነጭ ሽበትን አደረገ በተጸጸቱና የውኃውን ምንጭ እንዲመልስላቸው እየሰገዱ በለመኑት ጊዜ የውኃቸውን ምንጭ መለሰላቸው እንዳይታበዩም ይገሠጹ ዘንድ የራሳቸውን ጠጒር ነጭ እንደሆነ ተወው። ❤ በአንዲት ዕለትም በጐዳና አልፎ ሲሔድ አንዱን ሰው አስተኝተው ሰዎችን አገኛቸው መገነዣ ልብስም ይሰጣቸው ዘንድ ቅዱሱን ለመኑት እርሱ ግን በጸሎቱ ሰውዬውን ምውት አደረገው ሰዎችም ወደርሱ በተሰበሰቡ ጊዜ ሙቶ አገኙት ተጸጽተውም ሁለተኛ ያድንላቸው ዘንድ ለመኑት አዳነላቸውም። ትሩፋቱና ደግነቱም በተሰማ ጊዜ መርጠው በአገረ ንጽቢን ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት የክብር ባለቤት የክርስቶስን መንጋዎች ከአርዮሳውያ ተኵላዎች በበጎ አጠባበቅ ጠበቀ። ❤ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱን የከበሩ አባቶች በኒቅያ ከተማ በሰበሰባቸው ጊዜ ይህ አባት አብሮ አለ ከእርሳቸውም ጋር አርዮስን አውግዞ ከክርስቲያን አንድነት ለየው የቤተ ክርስቲያንንም ሥርዓትና በሁሉ ምእመናን ዘንድ የታወቀች የሃይማኖት ጸሎትን ሠራ። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በደረሰ ጊዜ የሞተውን ሰው በጉባኤው ውስጥ አስነሥቷል። ❤ የፋርስ ንጉሥም መጥቶ አገረ ንጽቢንን በከበባት ጊዜ ይህ ቅዱስ ያዕቆብ የጭጋግ ደመና በሠራዊቱ ላይ አመጣ ትንኞችም ፈረሶቻቸውንና ጐበዛዝቶችን ነደፏቸው ፈረሶችም ማሠሪያቸውን ቆርጠው ፈረጠጡ የፋርስ ንጉሥም አይቶ ታላቅ ፍርሀትን ፈራ ተነሥቶም ሽሽቶ ወደኋላው ተመለሰ። ነፍሱን የመንጋዎቹንም ነፍስ ጽድልት ብርህት አድርጎ ገድሉንም በፈጸመ ጊዜ ጥር18 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 18 ስንክሳር።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ ኀልቀ ከመ ጢስ መዋዕልየ። ወነቅጻ(ጸ) ከመ ሣዕር አዕፅምትየ። ተቀሠፍኩ ወየብሰ ከመ ሣዕር ልብየ"። መዝ 101፥3-4። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 11፥19-33።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወእምኵሉ ያድኅኖሙ እግዚአብሔር። እግዚአብሔር የዐቅዐብ ኵሎ አዕፅምቲሆሙ። ወኢይትቀጠቀጥ አሐዱ እምውስቴቶሙ"። መዝ 33፥19-20። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 8፥35-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥1-7 እና የሐዋ ሥራ 17፥30-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥42-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ ወይም የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ጊዮርጊስ ዝርወተ ዐፅም በዓል፣ የቅዱስ ባኮስ (አቤላክ) የስዋሬ በዓል፣ የቅድስት ጸበለ ማርያም የልደት በዓልና የአቡነ ቴዎድሮስ ዘአዳይቦ የዕረፍት ። ለሁላችንም ይሁንልን።           

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤     ❤ እንኳን #ለዘመነ_አስተርዮ_ሦስተኛ ሳምንት ስለ #ቃና_ዘገሊላ_ተአምር ለሚነገርበት ለዕለተ ሰንበት (እሑድ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፫ "#ሖረ_ኢየሱስ_በትፍሥሕት_ውስተ_ከብካብ እንዘ ይገብረ ተአምረ ወመንክር በውስተ አሕዛብ፤ ሖ አዝ፣ አርአዮሙ ስብሐቲሁ አምኑ ቦቱ አርዳኢሁ፤ ሖ አዝ፣ ወይቤሎሙ ቅድሑ ማየ ወምልእዎን ለመሳብክት እስከ አፉሆን፤ ሖ አዝ፣ ጥዒሞ አንከረ ሊቀ ምርፋቅ በረከተ ዘአምላከ ገብረ፤ ሖ አዝ፣ ቤዛነ ተስፋነ #ወልደ_አምላክ ወለማይኒ ረሰዮ ወይነ"። ትርጉም፦ #ኢየሱስ_ክርስቶስ_በደስታ_ወደ_ሠርግ_ቤት_ሔደ በብዙ ሕዝብ መካከል ድንቅ ተአምርን ሊሠራ ሔደ ደቀ መዛሙርቱም ክብሩን ተአምራቱን አይተወሸ አመኑበት። ውሃም ቀድታችሁ ጋኖቹን እስከ አፋቸው ሙሏቸው። የጠጅ አሳላፊው አምላክ ከሠራው በረከት ቀምሶ አደነቀ። ቤዛች ተስፋችን #የእግዚአብሔር_ልጅ ውሃው ወይን አደረገ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የዚህ_ሳምንት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 2፥1-3፣ 1ኛ ዮሐ 5፥1-13፣ የሐዋ ሥራ 10፥34-39። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 2፥1-14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበት ለሁላችንም ይሁንልን።        

❤ ለሦስት ዓመትም ያህል ሳይጎበኙት በመቅረታቸው አባታቸው አባ መቃርስ በተጋድሎ መኖራቸውን አይቶ አደነቀ፡፡ ሥራቸውንም ይገልጥለት ዘንድ ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ጸሎቱንም ከጨረሰ በኋላ ተነሥቶ ወደ ቅዱስ መክሲሞስና ቅዱስ ዱማቴዎስ ዘንድ ሄደ፡፡ እነርሱም በመምጣቱ ደስ ተሰኙበትና በዚያች ሌሊት አብረው አደሩ፡፡ ሌሊትም ለጸሎት በተነሡ ጊዜ የእሳት ሀብል ከቅዱስ መክሲሞስና ከቅዱስ ዱማቴዎስ አፍ ሲወጣና ወደ ሰማይ ሲያርግ ሰይጣናትም እንደዝንቦች ሲከቡት ነገር ግን ቅዱሳን መላአክት በእሳት ሰይፍ ዝንቦቹን ሲቆርጧቸው አባ መቃርስ ተመለከተ፡፡ በነጋም ጊዜ አባ መቃርስ ጸልዩልኝ ብሏቸው ሊሄድ ሲነሳ አንተ ጸልይልን እንጂ ብለው ግድ አሉት፡፡ ❤ እነዚህ የከበሩ ቅዱሳን ተጋድሎአቸውን በፈጸሙ ጊዜ በመጀመሪያ ቅዱስ መክሲሞስ ታመመ፡፡ አባ መቃርስም መጥቶ ባጽናናው ጊዜ በዙሪያው ቅ ዱሳንን ከበውት ተመለከተ፡፡ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እነዚህንና ሌሎችንም በአባ መክሲሞስ ዙሪያ ተመለከታቸውና "መክሲሞስ ሆይ የተመሰገንህ ነህ" አለው፡፡ ቅዱስ ዱማቴዎስም ወዲያው በአባ መቃርስ ፊት ተምበርክኮ "ከወንድሜ ጋር ዐርፍ ዘንድ ጸልይልኝ" አለው፡፡ ቅዱስ መክሲሞስም ከተቀበረ በኋላ ቅዱስ ዱማቴዎስም ታመመ፡፡ አባ መቃርስም ወደ እርሱ ሲሄድ በመንገድ ላይ ሳለ አስቀድሞ በአባ መክሲሞስ የዕረፍቱ ጊዜ ያያቸው ቅዱሳን ሁሉ አሁንም መጥተው የአባ ዱማቴዎስ ነፍስ በክብር ሲያሳርጓት ተመለከተ፡፡ አባ መቃርስም ከቅዱሳኑ ማረፊያ በደረሰ ጊዜ አባ ዱማቴዎስን ዐርፎ አገኘው፡፡ ወስዶም ከወንድሞ ጋር በአንድ መቃብር በክብር ቀበረው፡፡ የቅዱስ መክሲሞስ የዕረፍቱ ቀን በጥር ዐሥራ አራት ነው፣ የቅዱስ ዱማቴዎስ ዕረፍት ግን በጥር ዐሥራ ሰባት ቀን ሆነ፡፡ ❤ የከበረ አባ መቃርስም ያ ቦታ በስማቸው እንዲጠራ አዘዘ። እንዲሁም ደብረ በርሞስ ተብሎ እስከዛሬ የሚጠራ ሆነ ለዘላለሙም መታሰቢያቸው ሆነ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ መክሲሞስና ዱማቴዎስ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 17 ስንክሳር።                                                             

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ  አሜን"። ❤              ❤ #ጥር ፲፯ (17) ቀን። ❤ እንኳን #ለለውንድዮስ_ለሮም_ንጉሥ_ልጅ ለሆኑ #ለከበሩና_ለተመሰገኑ_ወድማማቾች_ለቅዱስ_ዱማቴዎስ ለዕረፍት በዓልና #ለቅዱስ_መክሲሞስ ለመታሰቢያ በዓል በሰላም አደረሰን። ከእነዚህ ሁለት ወድማማቾች ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                        ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #አባ_መክሲሞስና_አባ_ዱማቴዎስ፦ እነዚህም ቅዱሳን ለሮም ንጉሥ ለለውንድዮስ ልጆቹ ናቸው። ይህም ንጉሥ ሃይማኖቱ የቀና እግዚአብሔር የሚፈራ በእውነትም የቀና ፍርድን የሚፈርድ ነበር ስለዚህም እሊህን ሁለት ቅዱሳን እግዚአብሔር ሰጠው እነርሱም ከታናሽነታቸው ጀምሮ በንጽሕና እንደ እግዚአብሔር መላእክት ሆኑ። ❤ ትሕትናን ፈሪሀ እግዚአብሔርን በማስተማር አሳደጋቸው የሚጾሙና የሚጸልዩ በቀንና በሌሊትም የብሉይና የሐዲስ መጽሐፍቶችን የሚያነቡ ሆኑ። ከዚህም በኋላ ይህ ዓለም ይተውት ዘንድ የመላእክት ልብስ ይለብሱ ዘንድ እርሷም የከበረች የምንኵስና ልብስ ናት ከዚያም ሀሳብ መጣባቸው ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ አስራ ስምንት አባቶች ወደ ተሰበሰቡባት ወደ ኒቂያ ሔደው ይጸልዩ ዘንድ እንዲያሰናብታቸው ለአባታቸው ምክንያት አቀረቡ። ይህንም ከእርሷቸው በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው። ከብዙ አገልጋዮችና ከብዙ ሠራዊት ጋር አሰናበታቸው ከኒቅያ አገርም በደረሱ ጊዜ ከከበረ ቦታ በረከትን ተቀበሉ ሠራዊቱንም ወደ ንጉሥ አባታቸው ጌታችን ንጉሥ ሆይ "እኛ ከዚህ ጥቂት ቀን መቆየት እንሻለን" የሚል ጽሑፍ ጋር ጽፈው ላኩ። ❤ ከዚህም በኋላ ለአንድ ጻድቅ መነኰስ ኀባቸውን ገለጡ እንዲህም አሉት "ከአንተ ዘንድ የምንኵስናን ልብስ እንድንለብስ እንሻለን" እርሱም "እኔ ከንጉሥ አባታችን የተነሣ እፈራለሁ ነገር ግን ወደ ሶርያ ሒዱ ስሙ አጋብዮስ የሚባል ከዚያ ሃይማኖቱ የቀና ካህን ደግ መነኰስ አለ" አላቸው ይህንንም ሲላቸው ምክሩን ተቀብለው ወደ ሶርያ ተጒዘው ወደ ቅዱስ አባ አጋብዮስ ደርሰው ኀሳባቸውን ገለጡለት እርሱም ተቀብሎ የምንኵስና ልብስን አለበሳቸው እስከሚአርፍበት ቀን ከእርሱ ዘንድ ኖሩ። ከዕረፍቱም አስቀድሞ ያየውን ራእይ ነገራቸው ታላቁ አባ መቃርስ ወደርሱ እንደመጣና "ልጆችህ መክሲሞስና ዱማቴዎስ ለኔ ልጆቼ ይሁኑኝ ዘንድ ወደ እኔ ወደ አስቄጥስ ገዳም እንዲመጡ ከመሞቴ በፊት እዘዛቸው" አለው። ዳግመኛም እንዲህ አላቸው ልጆቹ "እኔ ይህን ሰው አባ መቃርስን በሥጋው አየው ዘንድ እመኝ ነበር እነሆ በመንፈስ አየሁት እናንተም ከሞትኩ በኋላ ወደርሱ ሒዱ"። ❤ ከዐረፈም በኋላ አልሔዱም በዚያ በሶርያ አገር ኖሩ እንጂ እግዚአብሔር ሀብተ ፈውስ ሰጥቷቸው በሽተኞችን የሚፈውሱ ሆነ ወሬያቸውም በአገሮች ሁሉ ተሰማ በባሕርና በየብስ ከሚነግዱ ነጋድያንም የመርከብ መዛነቢያዎችን መሥራት ተምረው ከድካም ወጋቸው በጥቂቱ የሚመገቡና የተረፈውን ለድኆችና ለችግረኞች የሚሰጡ ሆኑ። እግዚአብሔርም በእጆቻቸው ከሚሠራቸው ድንቆች ተአምራቶች የተነሣ የቅዱሳን መክሲሞስና ዱማቴዎስን ስም መናፍስት ርኵሳን በማሰሚ ጊዜ ከሰዎች ወጥተው ይሸሻሉ ሰዎችም ያን ጊዜ በጌታ ኃይል ይድናሉ ጤነኞችም ይሆናሉ። እጅግ ታላቅ የሆነ በጐዳና አጠገብ የሚኖር ከይሲ ነበር ብዙዎች ሰዎችንም አጥፍቷል የአገር ሰዎችም ወደ ከበሩ መክሲሞስና ዱማቴዎስ መጥተው ከዚያ ከይሲ ያድኗቸው ዘንድ ለመኗቸው አባ መክሲሞስም ክርታስ አንሥቶ እንዲህ ብሎ ጻፈ "የብፁዕ መቃርዮስ አምላክ በሆነ መንፈስ ቅዱስንም በለበሰ በአባታችን በአጋብዮስ አምላክ ሕያው እግዚአብሔር አካላዊ ቃል በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይህ ደብዳቤ ከዋሻህ ደጅ ሲደርስ አንተ ወጥተህ ሙት የሰማይ ወፎችም ይብሉህ"። ❤ አንድ ሰውም ያቺን ደብዳቤ ተቀብሎ ሔደ በዚያም የዘንዶ ዋሻ ደጃፍ አኖራት በዚያንም ጊዜ ዘንዶው ወጥቶ ሞተ የሰማይ ወፎችም በሉት ሕዝቦችም ሁሉ እጅግ አደነቁ እግዚአብሔርም።እግዚአብሔርም በእነዚህ ሁለት ቅዱሳን እጆች ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ በአንዲትም ዕለት ከአባታቸው መኳንንቶች አንዱ ወደ ባሕር ዳርቻ ደረሰ፡፡ ከመርከቦችም በአንደኛው መርከብ ላይ መክሲሞስና ዱማቴዎስ የሚል ጽሑፍ ባየ ጊዜ የመርከቡን ሹም የጠቀው፡፡ የመርከቡ ሹምም "ማዕበል በተነሣ ጊዜ በጸሎታቸው ከመስጠም እግዚአብሔር እንዲያድነኝ የእነዚህን ሁለት ወንድማማቾች ቅዱሳን ስማቸውን በመርከቤ ላይ ጻፍኩ" አለው፡፡ መኰንኑም "መልካቸው ምን ይመስላል?" አለው፡፡ እርሱም የመልካቸውን ነገር ነገረው፡፡ መኮንኑም የንጉሡ ልጆች መሆናቸውን ዐውቆ ያንን ነጋዴ ወደ ንጉሡ ዘንድ ወሰደው፡፡ ንጉሡም የሁለቱን ቅዱሳን ነገር ነጋዴውን የጠቀው፡፡ እርሱም ስለ ቅዱሳኑ የሚያውቀውን ሁሉ የመልካቸውንም ነገር ነገረው፡፡ ንጉሡም ልጆቹ እንደሆኑ ተረዳ፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ እናታቸውንና እኅታቸውን ወደ ልጆቹ ዘንድ ከብዙ ሠራዊት ጋር ላከ፡፡ ደርሰው ባዩአቸውም ጊዜ ጮኸው አለቀሱ፡፡ እናታቸውም ቅዱሳኑን ወደ አባታቸው ዘንድ እንዲሄዱ ለመነቻቸው፡፡ ቅዱሳኑም "ራሳችንን ለእግዚአብሔር አሳልፈን ሰጥተናልና ይህን ማድረግ አይቻለንም" አሏት፡፡ "ነገር ግን ወደ ቤተ መንግሥትሽ ተመለሺና ሂጂ፣ አንቺንም አባታችንንም እግዚአብሔር ከመከራ ሁሉ እንዲጠብቃችሁ እንጸልያለን" ብለው አረጋጓትና ሸኟት፡፡ እርሷም ወደ ንጉሡ ባሏ በደረሰች ጊዜ የሆነውን ነገረችው፡፡ እርሱም ለሚስቱና ለባለሟሎቹ ሁሉ "በዓለም ውስጥ ያለ ክብር ሁሉ እንደ ሕልም ኃላፊ ጠፊ ነውና ልጆቼ ግን የማያልፈውን መንግሥት መርጠዋልና ለእግዚአብሔር ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋዮቹ ይሆኑ ዘንድ እንተዋቸው፣ በጸሎታቸውም እኛን ይጠብቁናል" አላቸው፡፡ ❤ በዚያም ወራት የሮሜው አገር ሊቀ ጳጳሳት ዐረፈና በእርሱ ፈንታ የሚሾሙትን ይማከሩ ዘንድ ኤጲስቆጶሳትና ጳጳሳቱ ሁሉ ተሰበሰቡ፡፡ የከበረ መክሲሞስንም አሰቡትና "ለዚህች ለከበረች ሹመት የተገባው እርሱ ነው" ተባባሉ፡፡ ቅዱስ መክሲሞስ ብዙ ድንቅ ተአምራትን እንደሚያደርግ፣ ክርስቶስም በውስጡ ስላደረ በዕውቀትና በበጎ ሥራ በሕግና በሥርዓት ፍጹም እንደሆነ ሁሉም ዐውቀዋልና፡፡ ❤ አባቱና እናቱም የቅዱስ መክሲምያኖስን ለሹመት መመረጥ በሰሙ ጊ ዜ እጅግ ደስ ብሏቸው የከበሩ ቅዱስ መክሲሞስንና ቅዱስ ዱማቴዎስን ወደ ሮሜ አገር ይልካቸው ዘንድ ለሶርያው አገረ ገዥ ደብዳቤ ጽፈው ከብዙ ሠራዊት ጋር ላኩ፡፡ ቅዱስ መክሲሞስና ቅዱስ ዱማቴዎስም ይህንን በሰሙ ጊዜ እጅግ አዘኑ፡፡ አባታቸው አጋብዮስ የመከራቸውን አስታውሰው ለብሳቸውን ለወጡና ተነሥተው ሸሽተው ወደ ኤርትራ ባሕር ዳርቻ አካባቢ ሄዱ፡፡ ነገር ግን እነርሱ ሳያስቡት የእግዚአብሔር ኃይል ወደ አባ መቃርስ አደረሰቻቸው፡፡ ❤ አባ መቃርስም በጸጋ የለመለሙ እነዚህን ሁለት ቅዱሳን ባያቸው ጊዜ ደስ ብሎት በክር ተቀበላቸው፡፡ እነርሱም በምንኩስና ተጋድሎ ከእርሱ ዘንድ መኖር እንደሚፈልጉ ሲነግሩት ፈተናው ከባድ መሆኑን ነገራቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰሌን መሥራትን አስተማራቸውና ሰሌን የሚቆርጡበትን ወንዝም አሳያቸው፡፡ የእጅ ሥራቸውን የሚሸጥላቸውና ምግባቸውን የሚያመጣላቸው አንድ ሕዝባዊ ሰው አምጥቶ አገናኛቸው፡፡ እነርሱም ከሰው ሳይገናኙ ሦስት ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ፡፡

❤ ከዚህም በኋላ ከማምጠቂያው ውስጥ ጨምረው መገዙአቸውና አመድ እስከሆኑ ከቅባትና ከጨው ጋር በብረት ምጣድ ውስጥ ቆሉአቸው ጌታችንም አስነሥቶ አዳናቸው። ወደ መኰንኑም በገቡ ጊዜ እንዲህ አላቸው "በእውነት ከሙታን ተለይታችሁ የተነሣችሁ ከሆነ ይህ ጫማዬ በእግሬ ወጥቶ እንደ ቀድሞው ሕያው እንዲሆን አድርጉ ሕፃን ቂርቆስም በጸለየ ጊዜ ያ ጫማ ታላቅ በሬ ሆነ ከአንገቱም ፍየል ወጣ። በዚያንም ሰዓት ለዐሥራ አንድ ሽህ አራት ሰዎች በሬውንና ፍየሉን አርደው ምሳ እንዲአደርጉላቸው መኰንኑ አዘዘ እንዲህም አለ ይህ "በቅቷቸው ከጠገቡ ከዚህም ሌላ ምግብ ካልፈለጉ የተሠራው ሁሉ ዕውነተኛ ነዋሪ ነው"። ❤ ከዚህም በኋላ አርደው ምሳ አደረጉላቸውና ከፍየሉ ሥጋ ስድስት እንቅብ ከበሬው ሥጋ አራት እንቅብ አተረፉ መኰንኑም የተረፈውን ሥጋ አይቶ ወደ ባሕር እንዲጥሉት አዘዘ። መኰንኑም ቢያፍር የሕፃኑን ምላስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ጌታችንም ምላሱን መለሰለት ዳግመኛም በታላቅ ጋን ውኃ አፍልተው ሕፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይጨምሩአቸው ዘንድ አዘዘ እናቱም አይታ ፈራች። ልጅዋም ወደ እግዚአብሔር በጸለየላት ጊዜ አምላካዊ ኃይልን አሳደረባትና ከልጅዋ ጋር ወደ ጋኑ ገባች። እንደ ውርጭም ቀዝቃዛ ሆነ ደግሞም በውስጡ መንኲራኵር ወዳለበት የብረት ምጣድ እንዲጨምሩአቸውና ሥጋቸው እስከሚቦጫጨቅ እንዲስቡአቸው አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ ቅዱስ ገብርኤልም በሕይወት አወጣቸው። ❤ መኰንኑም እነርሱን ማሸነፍ በተሳነው ጊዜ ቸብቸቧቸውን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚያን ጊዜ ለስም አጠራሩ ስግደት የሚገባው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ሕፃን ቅዱስ ቂርቆስንም "የምትሻውን ለምነኝ" አለው። ሕፃኑም "ሥጋዬ በምድር አይቀበር ስሜን ለሚጠራ መታሰቢያዬን ለሚያደርግ ቤተ ክርስቲያኔን ለሚሠራ የተጋድሎዬን መጽሐፍ ለሚጽፍና ለሚያጽፍ ወይም ለሚያነበው ለቤተ ክርስቲያኔ መባ ለሚያገባ በውስጧም ለሚጸልይ ለሁሉም ፍላጎታቸውን ስጣቸው ኃጢአታቸውንም ይቅር በል ስሜም በሚጠራበት በዚያች ቦታ የከብት ዕልቂት አይምጣ በሰውም ላይ አባር ቸነፈር በእህልም ላይ ድርቅ የውኃም ማነስ አይሁን"። ❤ መድኃኒታችንም "የለመንከኝ ሁሉ አስጥሃለሁ አንተም በቀኜ ትኖራለህ ሥጋህንም ኤልያስ በዐረገበት ሠረገላ ውስጥ አኖራለሁ" አለው ሕፃን ቂርቆስ በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት ጌታችንን አመሰገነው። ከዚህም በኋላ በሌሊቱ እኩሌታም ከእናቱ ጋር አንገቱን ተቆረጠ መድኃኒታችንም በማይጠፋ አክሊል ጋረደው ነፍሶቻቸውንም በታላቅ ክብር ከእርሱ ጋር አሳረገ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቂርቂቆስና በእናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_አብድዩ፦ ይህም ነቢይ የሐናንያ ልጅ ነው በንጉሥ ኢዮሳፍጥም ዘመን ትንቢት ተናገረ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው። ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው አብዝቶ መከራቸውም ገሠጻቸውም። ❤ ይህም ንጉሥ አካዝያስ ይጠሩት ዘንድ ወደ ኤልያስ ከላከቸው ሦስተኛ መስፍን ነው ከእርሱ አስቀድመው የመጡ እነዚያን ሁለት መስፍኖች በኤልያስ ቃል አሳት ከሰማይ ወርዳ ከእነርሳቸው ጋር ካሉ ወታደሮች ጋር በላቻቸው። ይህ ግን ወደ ኤልያስ በመጣ ጊዜ በፊቱ ተንበርክኮ ሰግዶ ተገዛለት እንዲህም አለው "የእግዚአብሔር ሰው ተገዛሁልህ የእሊህ የባሮችህ ሰውነትና የኔ ሰውነት በፊትህ ትክበር" በእግዚአብሔር ነቢይ ላይ ፈጽሞ አልታበየምና ነቢዩ ኤልያስም ራራለት ወርዶም ከርሱ ጋር ወደ ንጉሡ ሔደ። ❤ ይህም አብድዩ ከምድራዊ ንጉሥ አገልግሎት የኤልያስ አገልግሎት እንደምትበልጥ የኤልያስ አገልግሎት ለሰማያዊ ንጉሥ አገልግሎት ታደርሳለችና ይህን በልቡ ዐወቀ ስለዚህ ምድራውያን ነገሥታትን ማገልገል ትቶ ነቢዩ ኤልያስን ተከትሎ አገለገለው በላዩም ከእግዚአብሔር ሀብተ ትንቢት አደረበትና ትንቢትን የሚናገር ሆነ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በዘጠኝ መቶ ዓመት በሰላም በፍቅር አንድነትም ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ነቢያት ሁሉ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 15 ስንክሳር።                                                                                  ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወሥጋሆሙኒ ለጻድቃኒከ ለአራዊተ ገዳም። ወከዐዉ ደሞሙ ከመ ማይ ዐውዳ ለኢየሩሳሌም። ወኃጥኡ ዘይቀብሮሙ። መዝ 78፥2-3።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አኅለፍከነ ማእከለ እሳት ወማይ። ወአውጻእከነ ውስተ ዕረፍት። እበውእ ቤተከ ምስለ መባእየ"። መዝ 65፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 12፥1-11፣ 1ኛ ጴጥ 4፥11-15 እና የሐዋ ሥራ 16፥14-19። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 18፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ቂርቆስ የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።               

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤               ❤ #ጥር ፲፭ (15) ቀን። ❤ እንኳን #ለከበረ_ሕፃን በሦስት ዓመቱ ተጋድሎውን ለፈጸመ #ለቅዱስ_ቂርቆስ_ለዕረፍቱ ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል፣ #ለቅዱስ_ቂርቆስ_ማኅበር_ለዐሥራ_አንድ_ሽህ_አራት_ሰዎች_ሰማዕትነት ለተበቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓልና ለሐናንያ ልጅ ለዕውተኛ ነቢይ #ለቅዱስ_አብድዩ ለዕረፍት በዓል። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ በሶርያ አገር ያሉ የክርስቲያን ወገኖች #ለቅዱስ_ጎርጎርዮስ የዕረፍቱን መታሰቢያ በዓል ከመያከብሩት፣ #ከጴጥሮስ_ከሶፍያ_ከአድምራና_ከይስሐቅ ከዕረፍታቸው መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                         ✝ ✝ ✝ ❤# ሕፃኑ_ቅዱስ_ቂርቆስ፦ በዚያንም ወራት የክብር ባለቤት የሆነ ክርስቶስን በሚያምኑ የክርስቲያን ወገኖች ላይ ታላቅ መከራና ስደት ሆነ። ስሟ ኢየሉጣ የሚባል አንዲት ሴት ነበረች እርሷም ከታናሽነቷ ጀምራ ደግ ናት ስደትም እንደሆነ በሰማች ጊዜ መኰንኑን ከመፍራት የተነሣ ሕፃኗን ይዛ ከሮሜ ከተማ ተሰዳ የኪልቅያ አውራጃ ከሆነ ከጠርሴስ ደርሳ ከዚያም በአገሮች ውስጥ እየተዘዋወረች ተቀመጠች። ወደዚያች አገርም ያ ከእርሱ የሸሸችው መኰንን እለእስክድሮስ መጣ ጭፍሮቹም ክርስቲያኖችን ፈለጓቸው። ይቺንም ቅድስት ኢየሉጣን አግኝተው ያዝዋትና ወደ መኰንኑ አደረሷት የክርስቲያን ወገንም እንደሆነች ነገሩት። ❤ መኰንኑም "ሴትዮ ተናገሪ ከወዴት ሕዝብ ወገን ነሽ ነገድሽ ምንድን ነው አገርሽስ ወዴት ነው" አላት። የከበረች ኢየሉጣም እንዲህ ብላ መለሰችለት "የአንጌቤን ሰው ለሆንኩ ለእኔ ወገኖቼ ኤሳውሮሳውያን ናቸው እኔም በአንተ ምክንያት ሸሽቼ ነበር እነሆ ዛሬ ግን በእጅህ ውስጥ ነኝ" አለችው። መኰንኑም "በእጄ ውስጥ እንደተገኘሽ ታውቂያለሽን" አላት "አሁንም የሚሻልሽን ምረጪ ስምሽንም ተናገሪ እኔንም እሺ በይኝና ለአማልክት ሠዊ" የከበረች ኢየሉጣም አለችው "ለረከሱ አማልክት እኔ አልሠዋም" አለችው መኰንኑም "ስምሽን ስጪ ተናገሪ" አላት እርሷም "የኔ ስም ክርስቲያን መባል ነው" አለችው። መኰንኑም "ይህስ ስንፍና ነው የሚጠቅምሽ አይደለም እንዳትሞቺ ስምሽን ስጪ ተናገሪ" አላት። የከበረች ኢየሉጣም "የኔ ስም ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞት የሚሽረው በሰዎች ዘንድ የምጠራበትን ከፈለግህ ስሜ ኢየሉጣ ነው" ብላ መለሰችለት። መኰንኑም "ጽኑ የሆኑ ሥቃዮችን በላይሽ ሳያመጡ ተነሥተሽ መሥዋዕትን ለአማልክት አቅርቢ" አላት። የከበረች ኢየሉጣም "ዕውነት ነገርን ለመሥራት የምትሻ ከሆነ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነ ሕፃን ልጅ ይፈልጉ ዘንድ ወደ አገሩ መንደር ላክ ወዳንተም ያምጡትና የምንገዛለትንና የምናመልከውን እርሱ ይነገረን" አለችው። ❤ ያን ጊዜም የሦስት ዓመት ልጅ ይፈልጉ ዘንድ መኰንኑ ወታደሮችን ላከ የአገር ሰዎችም ልጆቻቸውን ሠውረዋልና አላገኙም ከዚያም ከከተማው ቅጽር ውጭ በፀሐይ መውጫ ወዳለው በረሀ በኩል ወጡ የቅድስት ኢየሉጣንም ልጅ አገኙት ይህ ሕፃን "የስንት ዓመት ልጅ ነው" ብለው ስለርሱ ጠየቁ ሰዎችም "ይህ ሕፃን የሦስት ዓመት ሲሆን የክርስቲያናዊት መበለት ልጅ ነው" አሏቸው። ያንንም ሕፃን ይዘው ወደ መኰንኑ ወሰዱት መኰንኑም መልኩ የሚያምርና ደም ግባት ያለው እንደሆነ በአየ ጊዜ "ደስ የምትል ደስተኛ ሕፃን ሰላምታ ይገባሃል" አለው። ሕፃኑም "እኔን ደስተኛ ማለትህ መልካም ተናገርክ ላንተ ግን ደስታ የለህም እግዚአብሔር ለዝንጉዎች ደስታ የላቸውም ብሏልና ብሎ መለሰለት መኰንኑም ሕፃኑን "ሳልጠይቅህ ይህን ያህል ትመልስልኛለህን" አለው። ሕፃኑም "ገና ከዚህ የሚበዛ ነገርን እመልስልሃለሁ" አለው። ❤ መኰንኑም "ስምኽ ማነው” ብሎ በጠየቀው ጊዜ "ከንጹሕ ዐዘቅትና ከማይለወጥ ከማይጠፋ ውኃ የተገኘ ሕፃን ስሜ ክርስቲያን መባል ነው" ብሎ መለሰለት። መኰንኑም "ዳግመኛ እንዳትሞት ስምህን ንገረኝ" አለው የከበረ ሕፃንም "ስሜ ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞክሼ ስም የምትሻ ከሆነ እናቴ የሰየመችኝ ቂርቆስ ነው" በማለት መለሰለት፡፡ መኰንኑም ሕፃን ቂርቆስን "እሺ በለኝና እሾምሃለሁ በብዙ ወርቅና ብርም አከብርሃለሁ" አለው። ሕፃኑም "የሰይጣ መልእክተኛ ለዕውነትም ጠላቷ የሆንክ ከእኔ ራቅ" አለው። መኰንኑም ሰምቶ ተቆጣ ደሙ እንደ ውኃ እስከሚፈስ ቆዳውን እንዲጨምቁትና እንዲግፉት አዘዘ። የከበረች ኢየሉጣሜ የልጅዋን ትዕግሥት በአየች ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገነችው። ❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ "ጨውና ሰናፍጭ አምጡ አለ። የሁለቱንም አፍንጮቻቸውን ከፍተው ያንን ጨውና ሰናፍጭ እንዲጨምሩባቸው አዘዘ ያን ጊዜ ሕፃኑ "ትእዛዝህ ለጒረሮዬ ጣፋጭ ሆነ ከማርና ከስኳርም ለአፌ ጣመኝ" ብሎ ጮኸ። ሁለተኛም መኰንኑ እንዲህ ብሎ አዘዘ የረዘሙና የተሳሉ በእሳትም እንደ ፍም የጋሉ ዐሥራ አራት የብረት ችንካሮች አምጡ ሰባቱን በእናቱ አካላት ውስጥ ጨምሩ በሕፃኑም ሁለት ጆሮዎቹ ሁለት በዐይኖቹ ሁለት በአፉና በአፍንጫው አንድ በልቡ ጨምሩ እንዲህ ሲጨመርበት ጆሮዎቹ እንዲአሩ ዐይኖቹም ይጠፋ ዘንድ አንደበቱም ይቃጠል ዘንድ ወደ ልቡም ጽኑ ሕማም ገብቶ እርሱ ከዚህ ዓለም በሞት እንዲለይ ለእናቱም እንዲሁ አድርጉ ችንካሮችም በቅዱሳኑ በሥጋቸው ሁሉ ተጨመሩ። የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ትእዛዝ የብረቶቹ ግለት ጠፍቶ እንደ በረዶ ቀዘቀዘ ጤነኞችም ሆኑ መኰንኑም "ወደ ወህኒ ወስዳችሁ በዚያ አሥራችሁ ዝጉባቸው" አለ። ❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ "የሥቃይ መሣሪያን ይሠራ ዘንድ እንዳዝዘው ብረትን የሚያቀልጥ ሰው አምጡልኝ" አለ። በአመጡለትም ጊዜ ሰይጣን ወደ መኰንኑ ልብ ገብቶ አንደበቱን ዘጋውና መናገር ተሳነው ሕፃኑ ፈጥኖ አክሊልን ለመቀበል እንደሚተጋ ሰይጣን ስለ አወቀ ስለዚህ ዘጋው። ❤ ከዚህም በኋላ ሕፃኑ ሠራተኛውን ጠርቶ "እኔንና እናቴን የሚያሠቃዩ በትን የሥቃይ መሣሪያ መሥራት ትችላለህ ይህ መኰንን ግን ምንም የሚያውቀው ነገር የለም" አለው። ሠራተኛውም እንደምትሻው በል ንገረኝ እምታዝዘኝ እኔ መሥራት እችላለሁ" አለው። ሕፃኑም ቅዱስ ቂርቆስ እያዘዘው...። ብረት ሠሪውም ሰምቶ እጅግ አደነቀ የሚረዱትንም ከአገር ውስጥ መቶ ሠራተኞችን ሰብስቦ መሥራት ጀምረ በአርባ ቀንም ጨረሰ። ❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ እለእሰሰክድሮስ ቂርቆስንና እናቱን ወደ አደባባይ ያመጡአቸው ዘንድ አዘዘ ያን ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ ነበርና እንዲህ አለ "ሕፃኑንና እናቱን ከቆዳቸው ጋር ራሳቸውን ላጩአቸውና በላያቸው የእሳት ፍሞችን ጨምሩ እርር ብለው እንዲቃጠሉ ዳግመኛም አራት ችንካሮችን ከትከሻዎቹ እስከ ተረከዙ ድረስ እንዲተክሉበት አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ መጥቶ ሥቃዩን ከርሱ አራቀ። ዳግመኛም ከጥዋት እስከ ማታ ከሥቃይ መሣሪያዎች ውስጥ ጨምረው አዋሏቸው ግን ማሠቃየት ተሳናቸው።

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ - إحصائيات وتحليلات قناة تيليجرام @finote_media