🕊
[ † እንኩዋን ለእናታችን "ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ ገዳማዊት" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ † ]
🕊 † ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ † 🕊
ቅድስቷ እናታችን በነገድ እሥራኤላዊ ስትሆን የተወለደችው ኢየሩሳሌም ውስጥ በ፭ [5] ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ ነው:: ወላጆቿ ክርስቲያኖች በመሆናቸው በሚገባው ፈሊጥ አሳድገው ወደ ትምሕርት አስገቧት::
አስተማሪዋ ገዳማዊ መነኮስ ነበርና ከተማ ውስጥ አያድርም:: አስተምሯት ዕለቱኑ ወደ በዓቱ ይመለስ ነበር እንጂ:: ዓመተ ክርስቶስ ብሉይ ከሐዲስ ጠንቅቃ ተማረች::
አንድ ቀን እንደ ልማዷ ልትማር ብትጠብቀውም መምሕሯ ሊመጣ አልቻለም:: ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ መነኮሱን ልትጠይቅ : አንድም ልትማር ወደ በዓቱ ሔደች::
በሩ ላይ ደርሳ ብታንኩዋኩዋም መልስም : የሚከፍትም አልነበረም:: ከውስጥ ግን ምርር ያለ የለቅሶ ድምጽ ተሰማት:: "ጌታ ሆይ! ይቅር በለኝ?" እያለ በተደጋጋሚ ይጮሃል:: ያ ደጉ መነኮስ ነበር::
ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ በቅጽበት አንድ ሐሳብ መጣላት:: "እርሱ በንጽሕና እየኖረ ስለ ነፍሱ እንዲሕ ከተማጸነ እኔማ እንደምን አይገባኝ!" ብላ ወደ ቤቷ ተመለሰች:: የለበሰችውን ልብስ አልቀየረችም:: ቤተሰቦቿን አልተሰናበተችም:: ከቤቷ አተር በዘንቢል እና ውሃ በትንሽ እቃ ይዛ ወደ ጐልጐታ ገሰገሰች::
ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ላይ ወድቃ አለቀሰች:: ጸለየችም:- "ጌታ ሆይ! ነፍሴን ወደ ዕረፍት አድርሳት? ከክፉ ጠላትም ጠብቀኝ? ይሕንን አተርና ውሃ ለእድሜ ዘመን ሁሉ ባርክልኝ::"
ይሕን ብላ እየፈጠነች ከኢየሩሳሌም ተነስታ በእግሯ ቃዴስን : ሲናይ በርሃን አቁዋርጣ ግብፅ ደረሰች:: ምርጫዋ ብሕትውና ሆኗልና ልምላሜ ከሌለበት : ፀሐዩ እንደ ረመጥ ከሚፋጅበት በርሃ ገባች::
በዚያም ከያዘችው አተር ለቁመተ ሥጋ እየበላች : ከውሃውም በጥርኝ እየተጐነጨች : ማንንም ሰው ሳታይ : በፍጹም ተጋድሎ ለ ፴፰ [38] ዓመታት ቆየች:: የቀኑ ሐሩር : የሌሊቱ ቁር [ብርድ] ልብሷን ቆራርጦ ቢጨርሰው እግዚአብሔር ፀጉሯን አሳድጐ አካሏን ሸፈነላት::
ጊዜ ዕረፍቷ ሲደርስ የቅዱሳንን ዜና የሚጽፈው ታላቁ አባ ዳንኤል ወደ እርሷ ደረሰ:: እንዳያት ተከተላት:: እርሷ ግን በተሰነጠቀ አለት ውስጥ ገብታ ተደበቀች:: አባ ዳንኤል በውጪ ሆኖ ተማጸነ :- "እባክህ አባቴ! ውጣና ባርከኝ" አለ:: ሴት መሆኗን አላወቀም ነበርና:: እርሷ ግን "ራቁቴን ነኝና አልወጣም" አለችው::
ልብሱን አውጥቶ ሰጥቷት ወጥታ ተጨዋወቱ:: በፈቃደ እግዚአብሔር ዜናዋን ሁሉ አወቀ:: ወደ በዓቷ ዘወር ሲል በዘንቢል የሞላ አተር ተመለከተ:: ለ ፴፰ [38] ዓመታት ተበልቶ ዛሬም ሙሉ ነው:: አባ ዳንኤል ይፈትነው ዘንድ ከአተሩ በደንብ በላለት:: ከውሃውም ጠጣለት:: ግን ሊጐድል አልቻለም::
እያደነቀ "እናቴ ሆይ! ልብሴን ውሰጂው" ቢላት "ሌላ አዲስ አምጣልኝ" አለችው:: ይዞላት በመጣ ቀን ግን ተሠውራለችና አላገኛትም::
አንድ ቀን ግን [ማለትም ግንቦት ፳፰ [28] አረጋውያን መነኮሳት መጥተው የገጠማቸውን ነገር ነገሩት:: እንዲሕ ሲሉ:- "ሰው ተመልክተን ወደ በዓቱ ስንገባ አተር በዘንቢልና ውሃ በመንቀል አገኘን:: ስንበላው ወዲያው አለቀ::" አባ ዳንኤል ነገሩን ገና ሳይጨርሱለት አለቀሰ::
አተሩ አለቀ ማለት ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ አርፋለች ማለት ነውና:: አረጋውያኑ ግን ቀጠሉ:- "ከበዓቱ ስንወጣ በጸጉሯ አካሏ ተሸፍኖ ወደ ምሥራቅ ሰግዳ አርፋ አግኝተን ከሥጋዋም ተባርከን ቀበርናት" አሉ:: አባ ዳንኤል ዜናዋን ጽፎላት ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ታከብራታለች::
አምላካችን በቅድስት ዓመተ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን:: ከበረከቷም ያድለን::
🕊
[ † ግንቦት ፳፰ [ 28 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]
፩. ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ ተጋዳሊት [ ገዳማዊት ]
፪. ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ [ ሥጋው ቆዽሮስ የደረሰበት ]
፫. አባ መርቆሬዎስ ገዳማዊ
፬. አባ ጌርሎስ [ ጻድቅና ሰማዕት ]
፭. ፵፭ "45" ሰማዕታት [ የአባ ጌርሎስ ደቀ መዛሙርት ]
፮. ቅዱስ አጋቦስ ሰማዕት
[ † ወርኀዊ በዓላት ]
፩. አማኑኤል ቸር አምላካችን
፪. ቅዱሳን አበው [አብርሃም : ይስሐቅና ያዕቆብ]
፫. ቅዱስ እንድራኒቆስና ሚስቱ ቅድስት አትናስያ
፬. ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ [ሰማዕት]
" ለእናንተም ጠጉርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጐናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ:: ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ:: " [፩ዼጥ.፫፥፫] (3:3)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †
[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]
† † †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖 🕊 💖