cookie

ما از کوکی‌ها برای بهبود تجربه مرور شما استفاده می‌کنیم. با کلیک کردن بر روی «پذیرش همه»، شما با استفاده از کوکی‌ها موافقت می‌کنید.

avatar

አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሺን (አሚኮ)

Amhara media corporation ©

نمایش بیشتر
Advertising posts
5 044مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
+17 روز
+130 روز

در حال بارگیری داده...

معدل نمو المشتركين

در حال بارگیری داده...

በመሆኑም መንግሥት ለዘመናት የኖረች እና ከግማሽ የሀገሪቱ ህዝብ በላይ የያዘችን ቤተ ክርስቲያን ክብርና ልዕልና በሚዳፈር መልኩ በተፈጸመው ሕገ ወጥ ተግባር ላይ የተሳተፉ እና ይህን ድርጊት የፈጸሙ የጸጥታ አካላትና እንዲፈፀም ያዘዙ የመንግሥት ኃላፊዎችን በ፲፭ ቀናት ጊዜ ውስጥ ለይቶ በሕግ እንዲጠየቁ እንዲያደርግ እና ይህንንም ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ ለሕዝበ ክርስቲያኑ በግልጽ እንዲያሳውቅ እንዲሁም በተለመደው የሀሰት ውንጀላ በዓላችንን በማክበር ላይ እያሉ የመንግሥት የፀጥታ አካላት በፈፀሙት ሕገ ወጥ ተግባር ምክንያት በተፈጠረው ግርግር መነሻት የታሰሩ ምእመናንን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ እየጠየቅን ይህ የማይሆን ከሆነ ግን ቤተ ክርስቲያን መብቷን ለማስከበር ወደ ቀጣይ እርምጃዎች የምትገባ መሆኑን በአክብሮት እያሳወቅን ይህንንም ድርጊት ተከታትሎ የሚያሳውቅ እና የሚያስፈጽም የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደሥራ እንዲገባ የሚደረግም መሆኑን ጭምር እናሳስባለን፡፡ በዚህ ሕገ ወጥ ድርጊት የሊቀ ሰማዕቱን የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል ለማክበር በመምጣት ህይወቱን ላጣው ልጃችን እግዚአብሔር ነፍሱን በአብርሃም፣ በያዕቆብና በይስሐቅ እቅፍ ያኑር፣ ለቤተሰቦቹም መጽናናትን ያድልልን እያልን ቀላልም ሆነ ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰባችሁ የቤተ ክርስቲን የጭንቅ ቀን ልጆች ደማችሁን እና መከራችሁን እንደ ሰማእታት ዋጋ ይቆጥርላችሁ ዘንድ ጸሎታችን ነው፡፡ እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ የካቲት ፳፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም አዲስ አበባ፣ኢትዮጵያ
نمایش همه...
በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ ++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን በየካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገረ መንግሥት ምሥረታ ጀምሮ ያለችና መንግሥትን ያጸናች፣ የራሳቸው የጽሑፍ ቋንቋ ካላቸው ጥቂት ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ እንድትሆን ፊደል ቀርፃ ያስተማረች፣ መንግሥት የአረንጓዴ አሻራን መርሐግብር ከማስጀመሩ ከሺህ ዓመታት በፊት የአካባቢ ጥበቃን ስትሠራ የኖረችና አሁንም በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማትና አድባራት የአካባቢ ጥበቃ ሥራን የምትሠራ፣ ዘመናዊ ትምህርት ከመጀመሩ ከሺህ ዓመታት በፊት ሥርዓተ ትምህርት ቀርፃ ያስተማረችና የሀገር መሪዎችን፣ የስነ ህንፃ ባለሙያዎችን፣ የመድኃኒት አዋቂዎችንና ተመራማሪዎችን ያፈራች ቤተ ክርስቲያን ከመሆኗም በላይ ተቋም መሥርታ ለዘመናት የተቋምን ምንነት ያስተማረች ራሷ ሀገር የሆነች ናት፡፡ በተለይም ደግሞ መላው የአፍሪካ ሀገራት በቅኝ ግዛት በተያዙበት፣ አውሮፓውያን ኢትዮጵያንም ለመቀራመት ተስማምተው በፋሺስቱ የኢጣልያ መንግሥት አማካኝነት ሀገራችንን በወረረበት ጊዜ የንጉሱን የክተት አዋጅ ተከትሎ ሕዝቡ ለነፃነቱ እንዲዋደቅ የሀገር ፍቅር ለምእመኗ ያስተማረች በመሆኑ እና የንጉሱም ጥሪ ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ሀይማኖትን የመጠበቅ ጥሪም የነበረ በመሆኑ ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ንጉሱን እንዲከተል ከማድረጓም በላይ ታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስን በካህናቱ አጅባ የጦር ግንባር ድረስ በመዝመት፣ ምእመኑን እና ህዝቡን በማጽናናትና ፀሎተ ፍትሀት በማድረግ በዓድዋ ጦርነት ኢትዮጵያ ሀገራችን ድል እንድትቀዳጅና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም የነፃነት አርማ እንድትሆን በማድረግ ትልቁን የታሪክ ድርሻ እንደምትወስድ የታወቀ ሀቅ ነው፡፡ ከዚህ የድል በዓል በኋላም ኢትዮጵያ በነፃነት በቆየችባቸው ዓመታት ሁሉ ይህን የአድዋ የድል በዓል ቤተ ክርስቲያን የሰማእቱን ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦተ ሕግ ከመንበረ ክብሩ ወጥቶ ህዝቡን በመባረክ፣ ካህናቱና ምእመናኑ በታላቅ ምሥጋና እና መዝሙር በመላ ሀገሪቱ ስታከብረው የኖረች፤ወደፊትም እየፈጸመች የምትጸናበት አኩሪ ታሪኳ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ይህ በዓል ላለፉት ጥቂት ዓመታት የድል በዓል መሆኑ ቀርቶ የጠብ እና የጥላቻ በዓል እየሆነ መምጣቱ ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ያሳዘነ ተግባር ሆኗል፡፡ በተለይም ትላንት የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በተከበረው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል በቤተ ክርስቲያን ላይ የአድዋ የድል በዓልን አስታኮ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተፈፀመው እጅግ አሳዛኝ ድርጊትን ግን ቤተ ክርስቲያን ሰምታና አይታ በዝምታና በሀዘን ብቻ የምታልፈው ጉዳይ አልሆነም፡፡ በየካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የቅዱስ ጊዮርጊስ ክብረ በዓል ለማክበር ህዝቡ ከየቤቱ ተሰባስቦ ከጠዋቱ ፫፡፲፭ ላይ ታቦተ ሕጉ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የጆርጅያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ከመንበረ ክብሩ ወጥቶ ዑደት ካደረገና ሕዝቡን ባርኮ በዐውደ ምህረቱ ላይ ከቆመ በኋላ ሊቃውንቱ ያሬዳዊ ወረብ በማቅረብ ላይ እንዳሉ ከመንግሥት የጸጥታ መዋቅር የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማዊ ልዕልናን ተላልፈው በሰሜን በኩል ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ፪ ጊዜ በተኮሱት አስለቃሽ ጭስ ምክንያት የንግሥ በዓሉ በመረበሹ በዓሉ ተቋርጦ ከጠዋቱ ፬ ሰዓት ላይ ታቦተ ሕጉ ወደ መንበሩ ተመልሷል፡፡ በዚህም ምክንያት እስከአሁን በደረሰን መረጃ መሠረት በቤተ ክርስቲያን ቅጥር ከፍተኛ ረብሻ በመፈጠሩ ምክንያት ፩ ምእመን በተተኮሰው አስለቃሽ ጭስ ታፍነው ህይወታቸውን ማጣታቸውን፣ አገልጋይ ካህናት አባቶች፣ ምእመናን እና ምእመናት ከፍተኛ የሆነ አካላዊ እና ሥነ ልቡናዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ ከ፲፭ ያላነሱ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋይ ተማሪዎች በደረሰባቸው ጉዳት ምክንያት ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል፡፡ ይህ ድርጊት ከተፈፀመ በኋላም መንግሥት የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብርና ልዕልና በመዳፈር በቤተ ክርስቲያን ላይ ይህን በደል የፈፀሙ የጸጥታ መዋቅር አካላትን ለሕግ ያቀርባል፣ እንደ መንግሥት ኃላፊነቱን ይወጣል ብለን ብንጠብቅም የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ቢሮ በዓሉን አስመልክቶ በዕለቱ ባወጣው መግለጫ ችግሩን የፈጠሩት አካላት ‹‹የአደባባይ በዓሉን ለመረበሽ ሲያቅታቸው በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚደረገውን ኃይማኖታዊ በዓል ለመረበሽ ሞክረዋል፡፡ የጸጥታ መዋቅሩ ችግሩን ለመቆጣጠር በወሰደው እርምጃ ጉዳቱን ለመቀነስ ችሏል›› ሲል የችግሩን ሁኔታ ገልጧል፡፡ በዚህ መግለጫውም ላይ አሁንም ችግሩ የሌሎች ቡድኖች እንደሆነና የቤተ ክርስቲያኒቱን በዓል የረበሸው የእነዚህ አካላት እንቅስቃሴ ነው በማለት የሰጠው መግለጫ በቦታው ላይ ከነበረው እውነታ በእጅጉ የራቀ እና ድርጊቱ የተወሰኑ ግለሰቦች ሳይሆን የመንግሥት እውቅና ያለው መሆኑን እንዲሁም መንግሥት ችግሩን ለማረም እና መፍታት ፍላጎት የሌለው መሆኑን እንድንረዳ አድርጎናል፡፡ የቤተ ክርስቲያን በዓል እንዲረበሽ እና ምእመናን ህይወታቸውን እንዲያጡ እንዲሁም እንዲጎዱ ያደረገው ከመንግሥት የጸጥታ መዋቅር የተተኮሰው አስለቃሽ ጭስ እና ጥይት መሆኑ ለሁሉም የታወቀ ሆኖ እያለ ጉዳዩን ወደ ሌላ አካል ለማላከክ የተሄደበትን ርቀት ቤተ ክርስቲያን በፍፁም የምትቀበለው አይሆንም፡፡ የመንግሥት የፀጥታ አካል በቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ምእመናን ላይ ጉዳት ሲያደርስ እና የቤተ ክርስቲያንን ክብር ሲያጎድፍ ይህ የመጀመሪያው አይደለም፡፡ በጥር ፩ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም በቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን በተሰበሰቡ ምእመናን ላይ በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ብዙ ምእመናን እንዲጎዱ የተደረገ ሲሆን በጊዜው መንግሥት ይህን ድርጊት በፈጸሙ አካላት ላይ እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ ልክ እንደአሁኑ ችግሩ የሕገ ወጦች ነው በማለት ለድርጊቱ እውቅና ሰጥቶት አልፏል፡፡ በዚህ ድርጊት መንግሥት በጸጥታ መዋቅሩ ውስጥ ያሉ እና መንግሥትንና ሕዝብን እንዲሁም ተገቢ ያልሆነ ያለመግባባት የሚያባብሱትን ግለሰቦች እና አመራሮች ለይቶ እርምት ከመውሰድ ይልቅ ሕዝብና መንግሥትን ሆድና ጀርባ የሚያደርግ ተግባሩን አስፋፍቶ ቀጥሏል፡፡
نمایش همه...
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! "ከመንግስት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት የተሰጠ መግለጫ" በሚል ርዕስ በጥር ፳፰ ቀን ፳፻፲ወ፭ ዓ/ም የመንግስት ኮምዩኒኬሽን የሰጠውን መግለጫ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ህዝብ ግንኙነት መምሪያ የተሰጠ መግለጫ። በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በፍትሕ መንፈሳዊ እንዲሁም በሕገ ቤተክርስቲያን አንቀጽ ፲፱ ንኡስ አንቀጽ ፫ በተደነገገው መሠረት ጥር ፲፰ ቀን ፳፻፲ወ፭ ዓ.ም. ባካሄደው አስቸኳይ ምልዓተ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ በተፈጠረው ወቅታዊ የሃይማኖት፣ የቀኖና እና የአስተዳደራዊ ጥሰቶችን አስመልክቶ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት ሕገ ወጥ ሲመተ ጵጵስና እና መፈንቅለ ሲኖዶስ ሙከራ በፈጸሙ ግለሰቦች ላይ ሃይማኖታዊ፤ ቀኖናዊ እና አስተዳደራዊ ውሳኔ ማስተላለፉ ይታወሳል። ይህን ተከትሎ የቤተ ክርስቲያናችን የበላይ አካል በኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጡ ውሳኔዎች እና መልእክቶች ተከታታይ መድረኮች በማዘጋጀት ስለ ተፈጠረው የሃገራችን ሕግ እና የሕገ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት በቂ ግንዛቤ ሕዝባችን እንዲያገኝ በተደጋጋሚ ከቅዱስ ሲኖዶስ እና ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት አማካኝነት መግለጫ እና ማሳሰቢያ ሲሰጥ መቆየቱ ይታወሳል። ይሁንና "በወቅታዊ ጉዳይ ላይ ከመንግስት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት የተሰጠ መግለጫ" በሚል ርእስ በጥር ፳፰ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም የሰጠውን መግለጫ አስመልክቶ፤ መግለጫው ያስቀመጣቸው ነጥቦች የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ክብር፤ ታሪክ፤ እና እውነታ ቸል በማለት በጉዳዩ ላይ የተሟላ መረጃ የሌላቸው ወገኖች የተሳሳተ ግንዛቤ እንዲይዙ የሚያስችል መግለጫ በመኾኑ በመግለጫው አንኳር ነጥቦች ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ተከታዩን ምላሽ ሰጥቷል። ፩. በመግለጫው የመጀመሪያ አንቀጽ ላይ "ከሰሞኑ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል የተፈጠረው መለያየት ሰላማዊ በሆነ መንገድ፣ በውስጣዊ አሠራር መፈታት እንዳለበት መንግሥት ያምናል" ያለውን በተመለከተ ፩.፩. እንደሚታወቅ በቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች መካከል የተፈጠረ መለያየት የለም። በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት በአባልነታቸው የሚታወቁ እና የቤተ ክርስቲያናችን አባቶች ተብለው እውቅና የሚሰጣቸው ነገር ግን አለመግባባት የፈጠሩ ብፁዐን አባቶች የሉም። የመንግሥት ኮምዩኒኬሽን አገልግሎት የሰጠው መግለጫ፤ ብቸኛ ሕጋዊ ሰውነት ያላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመንፈስ ቅዱስ በታች የቤተ ክርስቲያናችን የበላይ አካል የኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ በቀኖናው መሠረት አውግዞ የለያቸውን ግለሰቦች አሁንም ሕጋዊ አካላት እንደኾኑ እና እውቅናም እንደሚሰጣቸው የሚያስረዳ መግለጫ ኾኖ ስላገኘነው ተገቢነት የሌለው ነው ብላ ቤተ ክርስቲያን ስለምታምን በመንግሥት ኮምዩኒኬሽን የተሰጠውን መግለጫ አትቀበለውም፤ ፩.፪. ሰላማዊት የኾነች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የመጨረሻው የበላይ አካል በኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ በውስጣዊ መንፈሳዊ እና አስተዳደራዊ አሠራሩ የሰጠውን የመጨረሻ ውሳኔ መንግሥት ያወጣው መግለጫ አሁንም የማይቀበለው መኾኑን የሚያመለክት ኾኖ አግኝተነዋል። ፩.፫. በመንግሥት መገናኛ ብዙኅን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ድምጽ በማፈን አንድም መግለጫዎቿን እንዳይተላለፉ ከተደረገ በኋላ ይህንን የመንግሥት መግለጫ በእነዚሁ መገናኛ ብዙኅን እንዲተላለፍ በማድረግ ብዙኅኑ አድማጭና ተመልካች የተዛባ አረዳድ እንዲኖረው የሚያደርግ ይዘት ያለው መግለጫ መኾኑን ቤተ ክርስቲያን ትገነዘባለች፡፡ ፪. በመግለጫው ሁለተኛ አንቀጽ ላይ "...የተቋማቱን አንድነት የሚፈታተኑ ችግሮች ከውስጥ ሲነሱ በውይይትና በውስጣዊ አሠራር እንዲፈቱ ድጋፍ ሲያደርግ ነበር" ያለውን በተመለከተ ፪.፩. በመግለጫው ከተጠቀሰው በተቃራኒ ቤተ ክርስቲያናችን ሕገ ወጥ ካለቻቸው ግለሰቦች እና ቡድኖች ጋር መንግሥት ጥምረት ፈጥሮ በመንቀሳቀስ ላይ መኾኑን በጥር ፳፯ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም. ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መግለጫ ማሳወቁ የሚታወስ ሲኾን፤ መንግሥት ከዚህ ድርጊቱ አለመቆጠቡን የሚያሳይ ሆኖ አግኝተነዋል፤ ፪.፪. መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ እንደማይገባ በቃሉ የሚናገር ኾኖ ሳለ በተግባር ግን ይህ መግለጫ እስከ ተሰጠበት ሰዓት ድረስ መንግሥት የሕገ ወጦቹን ስብስቦች ድጋፍ ከመስጠት ድርጊቱ አለመቆጠቡ እና በምእመናን ላይ ግድያ እስከ መፈጸም፤ የቤተ ክርስቲያናቱን ቅጽር ተዳፍሮ ለሕገ ወጥ ቡድኖቹ በመሳሪያ የታጀበ ድጋፍ በመስጠት የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ቁልፍ ሰብሮ በማስወረር ጭምር የሚፈጽመውን ፍጹም ያልተገባ እና ሕገ ወጥ የኾነ ድርጊት ለአድማጭ እና ለተመልካች ኹሉ ግልጽ ኾኖ ሳለ፤ መግለጫው ከዚህ ቀደም ክቡር ጠቅላይ ሚንስትራችን ከሰጡት እና ቅዱስ ሲኖዶስ መስመር በመስመር ነቅሶ ስህተቶቹን በመግለጽ እንዲታረም ካሳሰበው በተቃራኒ የክቡር ጠቅላይ ሚንስትራችን የተሳሳተ መግለጫ ቅጥያ ኾኖ አግኝተነዋል። ፫. በመግለጫው ፫ኛ አንቀጽ ላይ "የሀገር ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶች ሁለቱን ወገኖች በማቀራረብ.." ሲል የገለጸውን በተመለከተ ፫.፩. ቅዱስ ሲኖዶስ ለክቡር ጠቅላይ ሚንስትራችን በሰጠው ምላሽ ላይ በግልጽ እንደተቀመጠው፤ መንግሥት ተወግዞ የተለየውን አካል ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር እኩያ እና ትይዩ አድርጎ መመልከት መቀጠሉን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አሁንም እየታዘበች ትገኛለች። ፫.፪. ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅጽሮቿ እየተደፈሩ እና ልዕልናዋ በመንግስት አጋዥነት እየተጣሰ ባለበት በዚህ ሰዓት መልስ ተሰጥቶበት የተዘጋውን የውስጥ አሠራር ጉዳይ ወደ ሽምግልና አውርዶ በማሳየት መግለጫውን ለሚሰሙ ኹሉ ግርታን የሚፈጥር ምሉዕ ምስል የማይሰጥና የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የተልዕኮ ምሰሶ በኾነው "ሽምግልና" በተባለ ክቡር ሃሳብ ላይ መዘባበት ኾኖ በማግኘታችን የተሰጠው መግለጫ ተገቢነት የሌለው ነው። ፬. በመግለጫው አራተኛ አንቀጽ ላይ ከተቀመጡ ሃሳቦች መሐል "...የጸጥታ አካላት የየአካባቢውን ሕዝብና የእምነት ተቋማት ሰላምና ጸጥታ ማስከበር ግዴታቸው ነው" እንዲሁም "... የሚዲያ አካላት ችግሩን የሚያባብሱ ነገሮችን ከማቅረብ መቆጠብ ይጠበቅባቸዋል" በማለት የገለጻቸውን ፍሬ ሐሳቦች በተመለከተ፤ ፬.፩. በመግለጫው የተጠቀሰው ሀሳብ ልክነት ያለው ቢሆንም በተጨባጭ እየታየ ያለው ተግባር ግን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥር ፳፯ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው መንግሥት ለሕጋዊቷ ቤተ ክርስቲያን የሕግ ጥበቃ እና ከለላ ከመስጠት ይልቅ በተቃራኒው ለሕገ ወጥ ቡድኖች በተግባር እየሰጠ ባለው ወገንተኝነት የምእመናንን ሕይወት እየነጠቀ እና የቤተ ክርስቲያናችንን ቅጽር በተደራጀ የጸጥታ ኃይል አጀብ እየደፈረ እና እያስደፈረ መኾኑን የካደ መግለጫ መሆኑን ቤተ ክርስቲያን በፍጹም ሐሳቧ ትረዳለች። ፬.፪. የመንግሥት መገናኛ ብዙኅን የቤተ ክርስቲያኒቱን የበላይ አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰጣቸውን መግለጫዎች እንዳይዘግቡ በተግባር እቀባ ያደረገው መንግሥታችን ሕሊናዊ እና ሕጋዊ ተግባራቸውን እየፈጸሙ በሚገኙ የሚዲያ አካላት ላይ የማስፈራሪያ መግለጫ በመስጠት የቤተ ክርስቲያናችን ድምጽ ይበልጥኑ ለማፈን በመንቀሳቀስ ላይ መኾኑን በገሃድ ያመላከተ መግለጫ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ ስለሆነም ፈጽሞ ተገቢነት የሌለው ተግባር ነው፡፡
نمایش همه...
፭. በመግለጫው ፭ኛ አንቀጽ ላይ "...ሀገር ለማፍረስ በተለያዩ መንገዶች ሞክረው ያልተሳካላቸው ኃይሎች፣ ችግሩ እንዲባባስና እንዳይፈታ ለማድረግ እየሠሩ መሆኑ ተደርሶበታል።" በማለት የተገለጸውን ፍሬ ሐሳብ በተመለከተ፡- ፭.፩. ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በማንኛውም ሁኔታ ሀገር የሚያፈርሱ ተግባራትን የምትጸየፍ፤ ዋነኛ ተልእኮዋም የሀገርን ሕልውና ማስቀጠል መኾኑን በተለያዩ የጦር ሜዳ ዐውዶች ላይ ታቦተ ሕጓን በማክበር ምእመናቶቿን ለትግል በመጥራት ጭምር የሀገርን ሕልውና ያስጠበቀች እና እያስጠበቀች ያለች መሆኗ የሚታወቅ ሲሆን መንግሥት በመግለጫው የገለጸው ዓይነት ተግባር ቢፈጸም የመጀመሪያ ተቃዋሚ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መሆኗን በድጋሚ ማስታወስ ትወዳለች። ለዚህም ማሳያዋ እያንዳንዱ እንቅስቃሴዋ ፍጹም ሰላማዊ እና የሕግ አግባብ እና መሠረትን ብቻ ተከትላ እየፈጸመች መገኘቷ ነው፡፡ ፭.፪. ችግሩ እንዳይፈታና እንዲባባስ የሚፈልጉት ሀገር አፍራሽ ኃይሎች ሕገ ወጥ ቡድኖች መሆናቸውን መንግሥት ጠንቅቆ የሚያውቀውና ልዩ ድጋፍም የሚሰጠው መሆኑን ቤተ ክርስቲያን እያሳወቀች መንግሥትም ሕገ ወጦችን ከመደገፍ እና ከማገዝ ተግባሩ እንዲቆጠብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በድጋሚ ታሳስባለች። ፭.፫. እንደ መግለጫው ከሆነ ችግሩ የሚፈታው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕልውናዋን፣ ሕጋዊነቷን፣ ተቋማዊ ነጻነቷን እና ከመንግሥት ልታገኝ የሚገባውን የሕግ ከለላ አጥታ ከሕገ ወጥ አካላት እኩል ስትታይ መሆኑን መግለጫው በግልጽ ቋንቋ ያስቀመጠ መሆኑን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጽኑ የምታወግዘው እና የምትቃወመው መሆኑን ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ ፮. በመግለጫው የመጨረሻ አንቀጽ ላይ "..ችግሩን ለማባባስና በሕዝቦች መካከል ግጭት ለመፍጠር፣ ሀገርን ወደፈተና ለማስገባት በሚጥሩ አካላት ላይ መንግሥት ሕግ የማስከበር ሥራውን እንደሚሠራ በዚሁ አጋጣሚ ያሳውቃል" በማለት ያስቀመጠውን በተመለከተ፡- ፮.፩. ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የበላይ አካል ከሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ አንስቶ እስከ ታችኛው የአስተዳደር መዋቅር አልፎም እስከ ተከታይ ምዕመኖቿ ድረስ የሀገራችን ኢትዮጵያ ሰላም የሕዝቧ አንድነት እና የሕግ የበላይነት ጉዳይ ለድርድር እንደማታቀርብ በድጋሚ እያስታወስን ስልጣንን ተገን በማድረግ የቤተ ክርስቲያንችንን ሕጋዊ ጥያቄ በግድያ፤ በእስር፤ በማዋከብ እና በማስፈራራት ሊፈታ የማይችል ይልቁንም መንግሥት የተጣለበትን መንግሥታዊ ኃላፊነት ያለ አድሎ መፈጸም ሲችል ብቻ መሆኑን ቤተ ክርስቲያናችን ዳግም በጽኑ ቃል ለማሳሰብ ትወዳለች፡፡ በመጨረሻም መንግሥት ይህንን መግለጫ ሲያወጣ በጥር ፳፯ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በሻሸመኔ ከተማ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች የተፈጸመውን ሕገ ወጥ፤ አስነዋሪ እና ጭካኔ የተሞላበት የአደባባይ ግድያ እና የሕዝብ ፍጅት ያልጠቀሰና ሐዘኑን እንኳን መግለጽ ያልቻለበትና ያላወገዘ መሆኑን ስንመለከት የመንግሥትን ግልጽ ሚና በቀላሉ ለመረዳት እንድንችል ያደርገናል። ስለሆነም መንግሥት ሕገ ወጥ አካላትን ድጋፍ ከመስጠት እና የእነርሱ ልሳን ሆኖ በመቅረብ የቤተ ክርስቲያንን ክብር እና ልእልና ከሚያንኳስስ ሕገ ወጥ ድርጊት እንዲታቀብ እያሳሰብን ሕገ ወጡ ስብስቦች እየፈጸሙ ላሉት ድርጊትም የሰጠውን ድጋፍ እና እገዛ በይፋ ቤተ ክርስቲያንን ይቅርታ በመጠየቅ እንዲያቆም እናሳስባለን፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር! ጥር ፳፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ @amcethio143
نمایش همه...
በአዳማ ከተማ ሊደረግ የነበረው የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ውድድር ወደ ሌላ ከተማ እንዲዞር ተወሰነ፡፡ የዘንድሮው ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ እና የ11ኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታዎች እንዲሁም ከ14ኛ ሳምንት በኋላ ያሉ ጨዋታዎችን ማካሄጃ ከተማና ስታዲየም በተመለከተ የስራ አመራር ቦርዱ ዛሬ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ውሳኔ አሳልፏል። በዚህም መሰረት ውድድሩን በድሬደዋ ወይም ባህር ዳር ከተማ ለማከናወን የፊታችን ሰኞ ጥር 29 ሜዳዎቹን የሚገመግም ኮሚቴ(ከቦርዱ እና ውድድርና ስነስርዓት ኮሚቴ) በመላክ ፤ ማክሰኞ ጥር 30 ከሁለቱ የተመረጠውን ሜዳ በተመለከተ ውሳኔ የሚተላለፍ ሲሆን የሊግ ውድድሩ የፊታችን ቅዳሜ የካቲት 04/2015 የሚጀምር መሆኑን የፕሪሚየር ሊግ አክስዮን ማህበር ስራ አመራር ቦርድ ይፋ ማድረጉን ሶከር ኢትዮጵያ ይፋ አድርጓል፡፡ @amcethio143
نمایش همه...
ቅዱስ ሲኖዶሱ ፆመ ነነዌን ምክንያት በማድረግ በመላው አለም የሚገኙ ህዝበ ክርስቲያን በሙሉ #ጥቁር ልብስ በመልበስ በፆምና በፀሎት እንዲሁም ምሕላ በማድረግ እንግዚአብሔርን እንድትለማመኑ ሲል ጥሪ አቀረበ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ በቤተክርስቲያኗ በተከሰተው ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ መዋቅሮች በጣሰ ሁኔታ መፈንቅለ ሲኖዶስ በማድረግ በሕገወጥ መንገድ ኤጲስ ቆጶስነት ሢመት በሰጡትና በተሾሙ ግለሰቦች ላይ ጥር 18 ቃለ ውግዘት ተላልፎ እንደነበር አስታውሶ ነገር ግን እነዚህ ሕገወጥ ቡድኖች ከድርጊታቸው ሊታቀቡ ባለመቻላቸው ሆን ተብሎ በመንግሥት ኃይሎች በመታገዝ  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምታስተዳድራቸውን መንበረ ጵጵስናዎችንና ቢሮዎችን በኃይል በመውረርና በመስበር ከፍተኛ ጥፋት እያደረጉ ነው ብሏል። እንዲሁም የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችን ፣ ሠራተኞችን፣ ካህናትንና ምእመናንን በማሰርና በማንገላታት ላይ ይገኛሉ ሲል ገልጿል። ቅዱስ ሲኖዶሱ"መንግሥት ሕግ ከማስከበር ይልቅ ለሕገ ወጥ ቡድኖች ድጋፍ በመስጠት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግና መብት ሊያስከብር አልቻለም ያለ ሲሆን " ሁሉን ማድረግ ወደሚቻለው አምላካችን በመማፀን ጸሎትና ምሕላ ማድረጉ አስፈላጊ መሆኑን ተረድተናል " ሲል አሳውቋል። በዚህም መሠረት " ጾመ ነነዌን ምክንያት በማድረግ ከሰኞ እስከ ዕረቡ (ከጥር 29 እስከ ይካቲት 1) ድረስ በመላው ዓለም የሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ ጥቁር_ልብስ ብቻ በመልበስ በጾምና በጸሎት ምሕላ በመያዝ በቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት በመገኘት ወደ እግዚአብሔር ጾም፤ ጸሎትና ምሕላ እንድታቀርቡ " ሲል ቅዱስ ሲኖዶሱ ጥሪ አስተላልፏል። ጥቁር ልብስ  የምንለብሰውም በመከራ መጽናትን ለመግለጽ ነው ሲል ቅዱስ ሲኖዶሱ አክሏል። @amcethio143
نمایش همه...
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ክስ በመመስረት ሂደት ላይ መሆኗን አሳወቀች። ቤተክርስቲያኗ ይህን ያሳወቀችው ዛሬ ከህግ ባለሙያዎች ጋር በመሆን በሰጠችው መግለጫ ነው። በመግለጫውም ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክስ ለመመስረት ጥያቄ የቀርበ ሲሆን ክስ የመመስረት ሂደት ጊዜ ስለሚፈልግ ጊዜያዊ እግድ እንዲሰጥ ጥያቄ መቅርቡ ታውቋል። ክሱ ወይም እግዱ የቀረበው በልደታ ምድብ ሁለተኛ መሰረታዊ መብቶች እና ነፃነቶች ምድብ ችሎት ላይ መሆኑም ተገልጿል። ክስ የቀረበባቸው ተጠሪዎች በቀድሞ ስማቸው፦ 1ኛ. አባ ሳዊሮስ ፣ 2ኛ. አባ ኤዎስጣቴዎስ ፣ 3ኛ. አባ ዜና ማርቆስ ፤ እንዲሁም ኤጲስቆጶሳት ተብለው ተሹመዋል ተብሎ መግለጫ የተሰጠባቸው 25 ግለሰቦች ያሉበት መሆኑን እና አንድ ግለሰብ ተፀፅተው ስለተመለሱ ክሱ እንደማያካትታቸው ቤተክርስቲያን ጠቁማለች። በተጨማሪ ጠበቃ ኃይለሚካኤል ከፈሌ ተጠሪ ሆነው የተካተቱ መሆኑ ተገልጿል።እንዲሁም ሌሎች ፦የፌዴራል ፖሊስ፣የኦሮሚያ ክልል መንግስት፣የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ የክሱ ወይም የአቤቱታው አካል መሆናቸውን ቤተክርስቲያን አሳውቃለች። ቤተክርስቲያኗ ክስ ያቀረበችው ህጋዊ ሰውነቷን የጣሰ ህገወጥ ድርጊት ስለተፈፀመ፣ በአገልጋይ አባቶች ፣ ካህናት እና ምዕመናን ላይ በደል ስለተፈፀመ መሆኑም ገልጻለች። ቤተክርስቲያኗ ህገወጥ ብላ በይፋ የፈረጀችው ቡድን ወደ ቤተክርስቲያን ቅጥር እንዳይደርስ፣ ንብረት እንዳያንቀሳቅስ፣ የቤተክርስቲያኗ ጥቅምና መብት እንዲከበር ይህ ክስ በዝርዝር እስኪታይ የዕግድ ትዕዛዝ እንዲተላለፍ ለፍርድ ቤት ጠይቃለች። @amcethio143
نمایش همه...
በወቅታዊ ጉዳይ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ፡፡ •መንግስት ወጥ እና ቀጣይነት ባለው መልኩ በሁሉም የእምነት ተቋማት ላይ እየፈጸመ ያለውን ጣልቃ ገብነት ሊያቆም ይገባል። •መንግስት በአሸማጋይነት ፣ በአደራዳሪነት እና በዳኝነት ስም በተደጋጋሚ በእምነት ተቋማት ውስጥ እያደረገ ያለው ጣልቃ ገብነት "መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ፣ ሃይማኖት በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም" የሚለውንና ዓለምአቀፍ እውቅና ያለውን ዓለማዊ (Secular) የመንግስት አስተዳደር መርህ የሚጥስ እና የመንግስትን መንግስትነት ማዕረግ ዝቅ የሚያደርግ ተግባር ነው። ******** በረጅሙ የሃገራችን የኢትዮጵያ ታሪክ የእምነት ተቋማት እና መንፈሳዊ ተልዕኮዎቻቸው ለሃገራችን ስልጣኔ ፣ አንድነት እና ታላቅነት የማይተካ ሚና መጫወታቸው የሚታወቅ ነው፡፡ ሃገራችን ኢትዮጵያ የሽህ ዓመታት የመንግስትነት ታሪክ ካላቸው ጥቂት የምድራችን ሃገራት ተርታ የተሰለፈችው በነበራት የዳበረ የመንግስት አስተዳደር ስርዓት ብቻ ሳይሆን የምድራችን ታላላቅ ሃይማኖቶች የሆኑት የክርስትና ፣ የእስልምና እና የይሁዲ ሃይማኖቶች አንድም ብዙም ሆነው ባበረከቱት ታላላቅ መንፈሳዊ ፣ ማኅበራዊ እና ቁሳዊ አበርክቶዎች ጭምር መሆኑ ማንም ሊክደው የማይችለው ሃቅ ነው፡፡ በመሆኑም የእምነት ተቋሞቻችን እና መንፈሳዊ ተልዕኮዎቻቸው ከቆሙለት ሰማያዊ እና መንፈሳዊ ዓላማ ባሻገር ለሃገራችን ሰላም ፣ አንድነት እና እድገት የማይተካ ሚና ያላቸው መሆኑን ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ይረዳል፡፡ በረጅሙ የሃገራችን ታሪክ የመንግስት እና የሃይማኖት ግንኙነት ምን መምሰል አለበት የሚለው ጉዳይ ከውዝግብ ነጻ የሆነባቸው ጊዚያት ጥቂት ነው፡፡ በጥንቱ ታሪካችንም ቢሆንም መንግስት እና የእምነት ተቋማት መስመር የተላለፉባቸው ፣ ለግጭት እና ለአረመረጋጋት ምክንያት ሆነው ሕዝብ እና ሃገርን ውድ ዋጋ ያስከፈሉባቸው ጊዚያቶች ጥቂት አይደሉም፡፡ የዘውድ ስርዓቱ ላይ ይቀርቡ ከነበሩት ዋነኛ ቅሬታዎች የመንግስት እና የእምነት ተቋማት ግንኙነት አንዱ የነበረ ሲሆን ፣ ተማሪ-መር እና ወታደር-ተከል በሆነው ለውጥ ግንኝነቱ መልክ ይይዛል ተብሎ ተስፋ ቢጣልበትም በሁሉም ቤተእምነቶች ላይ ሰይፍ የመዘዘ ኮሚኒስታዊ የመንግስት አስተዳደር አስከትሎ ሃገር እና ሕዝብን የማይተካ ዋጋ አስከፍሎ አልፏል፡፡ ወታደራዊውን መንግስት በትጥቅ ትግል ጥሎ ስልጣን የያዘው ትሕነግ-መራሽ መንግስትም በእምነት ተቋማት ውስጥ አባቶችን እና መሪዎችን ሿሚ እና አባራሪ ሆኖ ችግሩን አወሳስቦት ወድቋል፡፡ በሕዝባዊ ትግል ታግዞ ሥልጣን የያዘው መንግስት ከመጣ ወዲህ ደግሞ ችግሩ ሌላ ቅርጽ እየያዘ ይገኛል፡፡ በብልጽግና የሚመራው መንግስት በሁሉም ቤተእምነቶች የሚነሱ ጥያቄዎችን ፣ ልዩነቶችን እና ችግሮችን እያሳባበ በአሸማጋይነት እና አደራዳሪነት ከፍ ሲልም በዳኝነት በየእምነት ተቋማቱ የውስጥ ጉዳይ በቀጥታ ጣልቃ እየገባ ይገኛል፡፡ ይህ የመንግስት ዝንባሌ እና ልማድ ከኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ጋር በተያያዘ በተነሱ የውስጥ ልዩነቶች ላይ ፣ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ብሔራዊ ተቋም ከሆነው መጅሊስ ጋር በተያዘዘ የተነሱ የውስጥ ችግሮች እና በትሕነግ-መራሹ መንግስት ውሳኔ ለስደት ተዳርገው ከነበሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያሪክ አቡነ መርቆሪዎስን በተመለከተ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተከስቶ ከነበረው ችግር ጋር በተያያዘ ተከስቷል፡፡ መንግስት በአሸማጋይነት ፣ በአደራዳሪነት እና በዳኝነት ስም በተደጋጋሚ በእምነት ተቋማት ውስጥ እያደረገ ያለው ጣልቃ ገብነት "መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ፣ ሃይማኖት በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም" የሚለውንና ዓለምአቀፍ እውቅና ያለውን ዓለማዊ (Secular) የመንግስት አስተዳደር መርህ የሚጥስ እና የመንግስትን መንግስትነት ማዕረግ ዝቅ የሚያደርግ ተግባር ነው። መንግስት እመራበታለሁ ፣ አከብረዋለሁ እና አስከብረዋለሁ በሚለው እና አሁን በስራ ላይ ባለው ሕገመንግስትም ቢሆን ድርጊቱ የተከለከለ ተግባር ነው፡፡ መነሻው በጎ ሃሳብ እና ምኞት ነው ቢባል እንኳ መንግስት በእምነት ተቋማት ውስጥ በሚፈጠሩ የውስጥ ልዩነቶች እና ችግሮች በቀጥታ ተሳትፎ ማድረጉ በእምነት ተቋማቱ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ከመግባት የሚያስቆጥረው እና ጊዚያዊ መፍትሄ የሚሰጥ ቢሆን እንኳ ዘላቂ ቀውስ እና ችግር የሚያስከትል በመሆኑ ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በጽኑ የሚቃወመው ተግባር ነው፡፡ ፓርቲያችን አብን የእምነት ተቋማት የሚያስፈልጋቸው የውስጥ ነጻነታቸውን የሚያከብር እና የሚያስከብርላቸው የመንግስት አስተዳደር እንጅ ለውስጥ ችግራቸው መፍትሄ የሚሰጥ መንግስት ነው ብሎ አያምንም፡፡ የኢትዮጵያ የእምነት ተቋማት የውስጥ ነጻነታቸው እስከተከበራላቸው ድረስ የውስጥ ችግራቸውን ለመፍታት የሚያስችል ለዘመናት የገነቡት በቂ ፣ አስተማማኝ እና የዳበረ አቅም እና አሰራር አላቸው ብሎ ፓርቲያችን አብን ያምናል፡፡ በየጊዜው በእምነት ተቋማት ውስጥ በሚፈጠሩ የውስጥ ችግሮች ውስጥ ዘሎ የመግባት የመንግስት ዝንባሌ እና ልማድ አሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረው ውስጣዊ ችግር ፖለቲካዊ ቅርጽ እንዲይዝ እና ከቁጥጥር ውጭ የሚሆንበትን እድል እየፈጠረ ይገኛል፡፡ በተጨማሪም የእምነት ተቋማት በራቸውን ዘግተው የውስጥ ችግራቸውን ከመፍታት እና መፍትሄ ከማፈላለግ ይልቅ ችግር እስከፈጠርን ድረስ መንግስት ያሸማግለናል የሚል መንፈስ በየእምነት ተቋማቱ ውስጥ እንዲፈጠርና የእምነት ተቋማት የውስጥ አንድነት እና ህብረት እንዲታወክ ምክንያት እየሆነ ይገኛል፡፡ መንግስት አሁን እየሄደበት ያለውን ከመርህ እና ከሕግ የሚጣረስ አካሄድ የሙጥኝ የሚል ቢሆን ፣ ጤናማ ያልሆነ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ተልዕኮ ይዞ እየሰራ እንደሆነ የሚያስገምተው እና በሃገር እና በሕዝብ ላይ የማይተካ ጉዳት የሚያስከትል መሆኑን እየገለጽን ፣ ለሚደርሰው ሃገራዊ ውድቀት እና ኪሳራ ከተጠያቂነት የማያመልጥ መሆኑን ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ለማስገንዘብ ይወዳል፡፡ ስለሆነም መንግስት በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ እያደረገ ያለውን ጣልቃ ገብነት እንዲያቆም እና የእምነት ተቋማቱን የውስጥ ነጻነት እንዲያከብር እና እንዲያስከብር ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አዲስ አበባ ፣ ሸዋ ፣ ኢትዮጵያ ጥር ፳፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም @amcethio143
نمایش همه...
በዚህ ጉዳይ ላይ ቤተ ክርስቲያናችን ለመንግሥት ያቀረበችው ሕግን የማስከበር እና የዜጎችን ሰላም የማስፈን ሥራ ጥሪ ተቀብሎ በሕገወጦች ላይ የወሰደው ምንም ዓይነት እርምጃ እንደሌለ በመጥቀስ፣ መንግሥት የተጣለበትን ኃላፊነት በመወጣት የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማዊ ልዕልና በማስከበር ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቀዋል። ቅዱስ ሲኖዶሱ ጨምሮም ይህ የማይሆን ከሆነ ግን ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት የሚሳተፉበት አገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ በማካሄድ፣ ችግሩ ተፈትቶ “የቤተ ክርስቲያኒቱ መብት እስኪረጋገጥ ድረስ ያለማቋረጥ እስከ ሕይወት መስዋዕትን ድረስ በመክፈል” ችግሯ እንዲታወቅ እንደሚያደርጉም ተገልጿል፡፡©BBC Amharic @amcethio143
نمایش همه...
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር ተቃወመ ብፁእ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከ 4 ሰአት በፊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ለካቢኔ አባሎቻቸው ሰሞኑን ሰጡትን ማብራሪያ በመቃወም መግለጫ ሰጠ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባሎች ጋር በነበራቸው ስብሰባ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረውን ውዝግብ አስመልክተው ሰፊ ማብራሪያ በመስጠት የመንግሥታቸውን አቋም ገልጸዋል። ከአንድ ሳምንት በፊት በኦሮሚያ ክልል በምትገኝ አንዲት ቤተክርስቲያን ውስጥ በሦስት ጳጳሳት አማካይነት በተሰጠ የ26 ጳጳሳት ሹመትን ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶሱ የውግዘት ውሳኔ ማሳለፉ እና የተወገዙት አባቶችም ተቃውሟቸውን መግለጻቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከካቢኔ አባሎቻቸው ጋር ባደረጉት ስብሰባ ላይ ከመናገራቸው በፊት በቤተክርስቲያኗ ውስጥ የተከሰተውን ቸግር በተመለከተ መንግሥት በይፋ ምንም ሳይል ቆይቶ ነበር። በስብሰባው ላይ ከተደረጉት ውይይቶች ተለይቶ በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ከተከሰተው ጉዳይ እና ተያያዥ ጉዳዮች ጋር ጠቅላይ ሚኒስተሩ ብቻ የተናገሩት በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ማክሰኞ ጥር 23/2015 ዓ.ም. ምሽት ከቀረበ በኋላ ነው ቅዱስ ሲኖዶሱ መግለጫ የሰጠው። በመግለጫው ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያነሷቸውን ዋና ዋና ጉዳዮች በመጥቀስም ማብራሪያ በመስጠት ስህተቶች ናቸው ያሏቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ እርማት እንዲሰጡበት አሳስቧል። በዚህም መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በካቢኔ ስብሰባው ላይ በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረው ችግር ቀላል እና በንግግር የሚፈታ ነው በማለት የተደረጉ ሙከራዎች እንዳለ ተናግረው ነበር። ቅዱስ ሲኖዶሱ ግን ይህንን በቤተ ክርስቲያኗ “አስተምህሮ ውስጥ ጣልቃ እንደመግባት እና የምታስተላልፋቸውን ሃይማኖታዊ እና ቀኖናዊ ውሳኔዎች ያላቸውን ውጤት ወደ ጎን የተወ ነው” በማለት እንደተራ ግጭት እና የግለሰቦች አለመግባባት አድርገው ማቅረባቸውን ተገቢ አለመሆኑን ገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የካቢኔ አባላት አንዳችሁም በዚህ ጉዳይ [በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ ውስጥ] እጃችሁን ማስገባት አይፈቀድላችሁም። . . . አንድም ሰው በእዚህ ጉዳይ እጁን እንዳያስገባ” በማለት የሰነዘሩትን ሃሳብንም “መንግሥት ሕግን የማስከበር ኃላፊነቱን ችላ ያለበት ነው” በማለት ተችቷል። በካቢኔ ስብሰባው ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግሥት ሁለቱን ወገኖች ለማቀራረብ መሞከሩን ጠቅሰው የነበረ ሲሆን “ምክራችን አልተደመጠም፤ አልተተገበረም” በማለት፣ የቤተክርስቲያኗ መሪዎች የተፈጠረውን አለመግባባት በውይይት እንዲፈቱ ጥሪ አቅርበው “በተለየ የምንደግፈው፣ በተለየ የምንቃወመው ኃይል የለም። ሁለቱም ኃይሎች ኦርቶዶክሶች ናቸው። ሁለቱም ጋር ጥያቄዎች እና እውነቶች አሉ” ብለው ነበር። ነገር ግን ይህ ሁለቱንም ወገኖች በአቻነት ያቀረቡበትን መንገድ የሲኖዶሱ መግለጫ ተችቶ፣ “በሕጋዊቷ ቤተ ክርስቲያን ላይ በሕገ ወጥ መንገድ የተነሱትን ሕገ ወጥ ቡድኖች በአቻ ዕይታ ተመልክተው ሊወያዩ ይገባል በማለት የሰጡት ማብራሪያ ሕገ ወጥነትን የሚያበረታታ፣ ለሕጋዊ ተቋማት መንግሥት ያለበትን የመጠበቅና ዋስትና የመስጠት ኃላፊነቱን ወደ ጎን ያደረገ ነው” ብሏል። በዚህም ሳቢያ በአሁኑ ወቅት አባላቱ ሊቃነ ጳጳሳት ከአየር ማረፊያ መታገታቸውን እንዲሁም ለሃይማኖታዊ አምልኮ የተሰበሰቡ ምእመናን እንዲበተኑ መደረጋቸውን በመጥቀስ “ለአንድ ሊቀጳጳስ የማይመጥን እንግልት እና ማዋከብ” መድረሱን መግለጫው ጠቅሷል። በተቃራኒው ደግሞ ቤተክርስቲያኗ ሕገወጥ ያለችው ቡድን አባላት በምዕራብ ወለጋ፤ በምሥራቅ ወለጋ፣ በቄለም ወለጋ እና በሆሮጉድሩ ዞኖች “በኦሮሚያ ክልል የልዩ ኃይል አባላት ልዩ እጀባ እና እንክብካቤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕጋዊ ተቋማት ተደፍረው እንዲገቡ ተደርጓል” በማለት ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ተሽከርካሪዎች እንዳይንቀሳቀሱ መደረጋቸውን ገልጿል። ስለዚህም የቤተ ክርስቲያኒቱ የአምልኮ እና የአስተዳደር ተቋማት እንዲሁም ንብረቶች አስፈላጊው ሕጋዊ ጥበቃ እንዲደረግላቸው፤ አባቶች እና የአስተዳደር ሠራተኞች የሕይወት ዋስትና እንዲያረጋግጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ አሳስቧል። መግለጫው ጨምሮም የቤተ ክርስቲያኗን ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊ እና አስተዳደራዊ አሠራር በመጣስ “መፈንቅለ ሲኖዶስ” ፈጽመው ተወግዘው ከተለዩት አባቶች ጋር በእርቅ እና ድርድር እንዲደረግ የቀረበው ሃሳብ “ሃይማኖታዊ መመሪያችሁን ጥሳችሁ ቀኖናዊ ሥርዓታችሁን አፍርሳችሁ፤ አስተዳደራዊ መዋቅራችሁን ንዳችሁ ተቀበሏቸው እንደማለት የሚያስቆጥር ነው” በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እርምት እንዲያደርጉ ጠይቋል። በአማራ እና በትግራይ ውስጥ የእምነቱ ተከታዮች በቋንቋቸው እንደሚገለገሉ የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ “ኦሮሚያ ውስጥ በኦሮምኛ ቋንቋ አገልግሎት ይሰጠን ብሎ የሚጠይቅን ምዕመን አይሰጥህም ልለው አልችልም። እኔ አይደለሁም በቋንቋው የመጠቀም መብት ያጎናፀፍኩት” ብለዋል። ይህንንም በተመለከተ ሲኖዶሱ በሰጠው ምላሽ ቤተክርስቲያኗ “የቋንቋ አገልግሎትን በሕጎቿ እውቅና የሰጠች” መሆኗን በመጥቀስ በተለይ በኦሮምኛ ቋንቋ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች በዝርዝር በመጥቀስ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ቤተክረስቲያኗ “የቋንቋ አገልግሎትን እንደተቃወመች እና በሯን እንደዘጋች የሚያስቆጥር እና ከእውነታው የራቀ ነው” ብሏል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግሥት ለቤተክርስቲያኗ እያደረገ ያለውን ድጋፍ ባብራሩበት ወቅት፣ ከሌሎቹ የዕምነት ተቋማት በብዙ እጥፍ በበለጠ ሁኔታ ባለፉት አራት ዓመታት ሰፊ ይዞታ እንደተሰጣት የገለጹበትን ማብራሪያ መግለጫው “ፍጹም ስህተት ነው” በማለት ተቃውሞታል። የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ያገኘችው ይዞታ “ለሌሎች ቤተ እምነቶች በድምሩ ከተሰጠው በሦስት እጥፍ እንደሚበልጥ እና አዲስ ይዞታ እንደተሰጠ ተደርጎ በማስመሰል የተሰጠው ማብራሪያ ፍጹም ስህተት እና ሕዝብን የሚያሳስት በመሆኑ ሊታረም ይገባል” በማለት ይህም በካርታ ተረጋግጦ እንዲሰጥ ስትጠይቅ የቆየች ንብረቷ እንጂ እንደ አዲስ ያገኘችው አለመሆኑን ገልጿል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በትግራይ ክልል ያሉ አባቶች ከዓመት በፊት በጦርነቱ ወቅት ከማዕከላዊው ሲኖዶስ መለየታቸውን ባሳወቁበት ወቅት አሁን ኦሮሚያ ውስጥ የታየውን አይነት ተቃውሞ አለመቅረቡን አንስተው በካቢኔ ስበሰባው ላይ ተችተው ነበር። ቅዱስ ሲኖዶሱ ለዚህም በሰጠው ምላሽ ላይ በትግራይ ያሉት አባቶች “የቤተክርስቲያኗን ሕጎች እና ቀኖናዎች ጥሰው ሕገወጥ ሲኖዶስ አልመሠረቱም፣ ጳጳሳትንም አልሾሙም” በማለት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር “አሁን የተፈጸመውን ሕገወጥ ሹመት እና መፈንቅለ ሲኖዶስ ሕጋዊ ሽፋን እንዲኖረው ለማድረግ” የሚያስመስል እና ሁለቱ የማይገናኙ ድርጊቶችን በንጽጽር መናገራቸው ተቃውሟል። ቅዱስ ሲኖዶሱ በመግለጫው ላይ መንግሥት ሕግ እንዲያስከብር እና ቤተክርስቲያኗን እንዲጠብቅ መጠየቃቸውን አስታውሶ ነገር ግን “በሕገ ወጥ መንገድ ተሹመናል የሚሉት አካላት” በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ወዳልተፈቀደላቸው የአገልግሎት ቦታዎች በመግባት በቤተክርስቲያኗ ላይ “ሁከት እየተፈጠረ መሆኑን ለመረዳት ችለናል” ብሏል፡፡
نمایش همه...