cookie

Utilizamos cookies para mejorar tu experiencia de navegación. Al hacer clic en "Aceptar todo", aceptas el uso de cookies.

avatar

✞ገድለ ቅዱሳን✞

✝✞ከኢ/ኦ/ተዋህዶ ቤ/ክ ላይ የተገኙ የየዕለቱ የቅዱሳን አባቶቻችን እና የቅዱሳት እናቶቻችን ገድል ይነገርበታል✝

Mostrar más
Advertising posts
16 218Suscriptores
-324 hours
-347 days
-11130 days

Carga de datos en curso...

Tasa de crecimiento de suscriptores

Carga de datos en curso...

††† እንኳን ለቅዱሳኑ የአስከናፍር ቤተሰብ ዓመታዊ በዓለ ዕረፍት በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ አስከናፍር ††† ††† ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት አስከናፍር የሚባል ደግ ክርስቲያን ማርታ የምትባል በሃይማኖትና ምግባር የምትመስለውን ሴት አግብቶ ይኖር ነበር:: እንደ ሕጉና ሥርዓቱ በሥጋ ወደሙ ተወሥነው እንግዳ ቢቀበሉ: ነዳያንን ቢያበሉ እግዚአብሔር ጸሎታቸውን ሰምቶ አርቃድዮስና ዮሐንስ የሚባሉ ልጆችን ሰጣቸው:: አስከናፍርና ማርታ ልጆቻቸውን ጥበብ መንፈሳዊን (ቃለ እግዚአብሔርን) አስቀድመው አስተምረው : ሥጋዊ ጥበብን እዲማሩላቸው ቢልኩዋቸው መንገድ ላይ መርከብ ተሰብሮባቸው ብዙዎቹ ሲሞቱ ወንድማማቾች ግን የመርከብ ስባሪ ወደተለያየ ቦታ አድርሷቸዋል:: አርቃድዮስና ዮሐንስ "ወደ ዓለም አንመለስም" ብለው መነኑ:: ወላጆቻቸው የሆነውን ሰምተው በጭንቅ ሃዘንና ለቅሶ ለብዙ ጊዜ ኑረዋል:: ከዘመናት በሁዋላ ግን የልጆቻቸውን መኖር በራዕይ የተረዱት አስከናፍርና ማርታ ሃብት ንብረታቸውን ለነዳያን አካፍለው ወደ በርሃ መንነው ሔደዋል:: ጥበበኛ እግዚአብሔር አራቱንም አገናኝቷቸው ለብዙ ዓመታት በአንድ ገዳም ውስጥ ተጋድለዋል:: በዚሕች ዕለትም አራቱም ወደ ሰማያዊው ሠርግ ተጠርተዋል:: ††† ቸር አምላክ ከቅዱሱ ቤተሰብ በረከት ይክፈለን:: ††† መጋቢት 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አስከናፍር : ሚስቱ ማርታ : ልጆቹ አርቃድዮስና ዮሐንስ 2.ቅዱስ አርስጥቦሎስ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት-የቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዝሙር) 3.ሰባቱ ቅዱሳን ሰማዕታት (ከተለያየ ቦታ ተሰብስበው በክርስቶስ ስም የሞቱ) ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት 2.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት 3.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ 4.አቡነ ስነ ኢየሱስ 5.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም ††† "እንግዲህ ወንዶች በሥፍራ ሁሉ አለ ቁጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሱ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ:: እንዲሁም ደግሞ ሴቶች በሚገባ ልብስ ከእፍረትና ራሳቸውን ከመግዛት ጋር ሰውነታቸውን ይሸልሙ:: እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ መልካም በማድረግ እንጂ በሽሩባና በወርቅ: ወይም በዕንቁ: ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ::" ††† (1ጢሞ. 2:8) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Mostrar todo...
††† እንኳን ለሐዋርያው ቅዱስ አልዓዛር ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† አልዓዛር ሐዋርያ ††† ††† ቅዱስ አልዓዛር በሃገረ ቢታንያ ከእህቶቹ ማርያና ማርታ ጋር ይኖር ነበር:: ሦስቱም ድንግልናቸውን ጠብቅው ጌታችንን ያገለግሉት ነበርና አልዓዛርን ከ72ቱ አርድእት ማርያና ማርታን ደግሞ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ቆጥሯቸዋል:: በወንጌል ጌታችን ይወዳቸው እንደነበር ተገልጧል:: (ዮሐ. 11:3) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወድ የሚያበላልጥ ሆኖ አይደለም:: ይልቁኑ በምሥጢር እነርሱ ተወዳጅ የሚያደርጋቸውን ሥራ ይሠሩ እንደነበር ሲነግረን ነው እንጂ:: ቅዱስ መጽሐፍ እንደ ነገረን ጌታችን በነ አልዓዛር ቤት በእንግድነት ይስተናገድ ነበር:: (ዮሐ. 12:1) በመጨረሻዋ ምሴተ ሐሙስም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለሐዋርያቱ ያቀበላቸው በእነዚህ ቅዱሳን ቤት ውስጥ ነው:: ቅዱስ አልዓዛር በጽኑዕ ታሞ በዚሕች ቀን አርፏል:: ቅዱሳት እህቶቹ ማርያና ማርታ ከታላቅ ለቅሶ ጋር ዕለቱኑ ቀብረውታል:: (ዮሐ .11) ††† ቸር ጌታችን ክርስቶስ ከ4 ቀናት በሁዋላ ሊያስነሳው ይመጣልና ከበረከቱ ይክፈለን:: (ይቆየን) ††† መጋቢት 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አልዓዛር ጻድቅ ሐዋርያ 2.ቅዱስ ቴዎቅሪጦስ አናጉንስጢስ (ሰማዕት) 3.ቅዱስ ተላስስ ሰማዕት 4.ቅዱስ ዮሴፍ ኤዺስ ቆዾስ 5.ቅዱስ ጊዮርጊስ መስተጋድል ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ቀዳሜ ሰማዕት) 2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ) 3.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ዘቆዽሮስ 4.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ 5.አባ ገሪማ ዘመደራ 6.አባ ዸላሞን ፈላሢ 7.አባ ለትጹን የዋህ †††  "ጌታ ኢየሱስም:- 'ትንሳኤና ሕይወት እኔ ነኝ:: የሚያምንብኝ ቢሞት እንኩዋ ሕያው ይሆናል:: የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘለዓለም አይሞትም:: ይህን ታምኛለሽን?' አላት:: እርስዋም (ማርታ):- 'አዎን ጌታ ሆይ: አንተ ወደ ዓለም የሚመጣው ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ እኔ አምናለሁ::' አለችው::"††† (ዮሐ. 11:25-27) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Mostrar todo...
†† እንኳን ለሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ዓመታዊ የተአምር በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ ††† ††† ከ12ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ብዙ መከራን በማሳለፉና የጌታችንን ጐን በመዳሰሱ ይታወቃል:: ቅዱስ ቶማስ እንደ ሌሎቹ ሐዋርያት በእሥራኤል ተወልዶ በዚያውም በሥርዓተ ኦሪት አድጐ ገና በወጣትነቱ የሰዱቃውያንን ማሕበር ተቀላቅሏል:: ሰዱቃውያን ሰው ከሞተ በሁዋላ አይነሳም (አልቦ ትንሳኤ) የሚሉ ናቸው:: መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማስተማር ሲጀምር ግን ቅዱስ ቶማስ ከነበረበት ማሕበር ወጥቶ ጌታችንን ተከተለ:: ጌታችንም ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ ይሆን ዘንድ ሾመው:: የቀደመ ስሙ "ዲዲሞስ" ሲሆን ጌታችን "ቶማስ" ብሎታል:: ቅዱስ ቶማስ ጌታ አልዓዛርን ለማስነሳት በሔደ ጊዜ ሌሎች ሐዋርያት ጌታን "አይሁድ ይገድሉሃል ቅር" ሲሉት እርሱ ግን "እንሒድና አብረን እንሙት" ሲል ፍቅሩን አሳይቷል:: (ዮሐ. 11:16) ጌታችን ትንሳኤውን ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠ ጊዜ ያልነበረው ቶማስ ካላየሁ አላምንም አለ:: ምክንያቱም:- 1.ለጌታችን ከነበረው ፍቅር የተነሳ እውነት አልመስልህ ቢለው:: 2.አንድም ሌሎቹ ሐዋርያት "ትንሳኤውን አየን" እያሉ ሲያስተምሩ እኔ ግን "ሰማሁ" ብየ ማስተማሬ ነው ብሎ በማሰቡ ነበር:: ለጊዜው ጌታ ተገልጾ ቢገስጸው "እግዚእየ ወአምላኪየ (ጌታየና አምላኬ)" ብሎ ፍጹም ሃይማኖቱን ገልጿል:: ለፍጻሜው ግን የጌታችንን ጎን (መለኮትን) ይዳስስ ዘንድ ባለቤቱ እንዳደለው ያጠይቃል:: መለኮትን የዳሰሰች ይሕቺ ቅድስት እጁ ዛሬም ድረስ ሕያው ናት:: በሕንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥም በክብር ተቀምጣለች:: ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ሐገረ ስብከት ሲከፋፈሉ ለቅዱስ ቶማስ ሕንድና በዙሪያዋ ያሉ ሃገራት ደረሱት:: ከዚህ በሁዋላ ነው እንግዲህ ዘርዝረን የማንጨርሰውን ተጋድሎ የፈጸመው:: ቅዱሱ በነበረው ፍጹም ትጋት አባቶቻችን "ዘአሠርገዋ ለብሔረ ሕንደኬ (ሕንድን በወንጌል ያስጌጣት)" ሲሉ ያከብሩታል:: ቅዱስ ቶማስ ንጉሥ ሉክዮስንና የሃገሩን ሕዝብ ለማሳመን በችንካር መሬት ላይ ወጥረው ቆዳውን ገፈውታል:: ቆዳውንም እንደ ገና ሰፍተው: አሸዋ ሞልተው አሸክመውታል:: በየመንገዱ የተገፈፈ ገላውን ጨው ቢቀቡት በጎች መጥተው ግጠው በልተውታል:: በዚሕ ምክንያት:- "ኩሉ የአኪ እንዘ የአኪ ዘመኑ:: አባግዒሁ ለቶማስ እስመ አራዊተ ኮኑ::" ብለዋል ሊቃውንቱ:: በሁዋላ ግን ከፎቅ ወድቃ የሞተችውን የንጉሡን ሚስት በተገፈፈ ቆዳው በማዳኑ ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል:: ቅዱሱ ሐዋርያ ልክ እንደ ቅዱስ ዻውሎስ አንዳንዴ በፈሊጥ: ሌላ ጊዜም በመከራ ለወንጌልና ለቤተ ክርስቲያን ተጋድሏል:: ያለ ማቁዋረጥም ከሕንድ እስከ ሃገራችን ኢትዮዽያ ድረስ ለ38 ዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል:: በመጨረሻም በ72 ዓ/ም በሰማዕትነት አርፏል:: መቃብሩና ቅድስት እጁ ዛሬ ድረስ ሕንድ ውስጥ አሉ:: ከኘሮቴስታንቶች በቀር መላው ዓለም ያከብረዋል:: ††† ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአገልጋዩ ቅዱስ ቶማስ ጸጋ በረከት ይክፈለን:: ††† መጋቢት 14 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ (ጋኔን ያደረባት ሴትን ፈውሶ አሕዛብን ያሳመነበት) 2.ቅዱስ አባ ባጥል ትሩፈ ምግባር (ባንድ ወቅት ከእስክንድርያ ዝሙትን ለማጥፋት የተጋደሉ ጻድቅና አረጋዊ አባት) 3.ቅዱስ ሲኖዳ (ሺኖዳ) ሰማዕት 4.ቅዱስ ቄርሎስ ሊቀ ዻዻሳት ††† ወርሐዊ በዓላት 1.አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል) 2.ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ 3.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ 4.ቅዱስ ሙሴ (የእግዚአብሔር ሰው) 5.አባ ስምዖን ገዳማዊ 6.አባ ዮሐንስ ጻድቅ 7.እናታችን ቅድስት ነሣሒት ††† "ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ:: በመካከላቸውም ቆሞ 'ሰላም ለእናንተ ይሁን' አላቸው:: ከዚያም በሁዋላ ቶማስን 'ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ:: እጅህንም አምጣና በጐኔ አግባው:: ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን' አለው:: ቶማስም 'ጌታዬ አምላኬም' ብሎ መለሰለት:: ኢየሱስም 'ስላየኸኝ አምነሃል:: ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው' አለው::" ††† (ዮሐ. 20:26-29) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Mostrar todo...
††† እንኳን ለ40 ቅዱሳን እና ለታላቁ ቅዱስ መቃርስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ታላቁ ቅዱስ መቃርስ ††† ††† ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (ቅዱስ መቃሬ) "ጽድቅ እንደ መቃርስ" የተባለለት: የመነኮሳት ሁሉ አለቃ: ከ80 ዓመታት በላይ በበርሃ የኖረ: በግብፅ ትልቁን ገዳም (አስቄጥስን) የመሠረተ: ከ50,000 በላይ መነኮሳትን ይመራና ይመግብ የነበረ ፍፁም ጻድቅ ነው:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በዚሕች ዕለት አርዮሳውያን ደጉን ታላቅ አባት በሰንሰለት አስረው ከግብፅ ወደ እስያ በርሃ ከጉዋደኛው ቅዱስ መቃርዮስ እስክንድርያዊ ጋር አሰድደውታል:: በዚያ ለ2 ዓመታት ስቃይን ከተቀበሉ በሁዋላ በአረማውያን ፊት ድንቅ ተአምር አድርገው አረማውያንን ከነ ንጉሳቸው አጥምቀዋል:: በተሰደዱባት ሃገርም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (ስም አጠራሩ ይክበርና) እመቤታችንን: ቅዱሳን ሐዋርያትን: አዕላፍ መላእክትን: በተለይ ደግሞ ቅዱሳኑን ዳዊትን: ዮሐንስ መጥምቁንና ወንጌላዊውን: ማርቆስን: ዼጥሮስን: ዻውሎስን አስከትሎ ወርዶ ተገልጦላቸዋል:: በቅዱስ አንደበቱም የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል:: ታላቁ ቅዱስ መቃርስና ባልንጀራው መቃርዮስ ከ2 ዓመታት ስደትና መከራ በሁዋላ ስደት በወጡባት በዚችው ዕለት መልዐኩ ኪሩብ በክንፉ ተሽክሞ ወደ ግብፅ መልሷቸዋል:: በወቅቱም ጻድቁን ለመቀበል ከ50,000 በላይ የሚሆኑ ልጆቻቸው መነኮሳት በዝማሬ ወጥተዋል:: ††† ከቅዱሳን አባቶቻችን የስደት በረከት ፈጣሪ አይለየን:: †††  አርባ ሐራ ሰማይ ††† ††† አርብዐ ሐራ ሰማይ ማለት በዘመነ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ሰማዕትነትን የተቀበሉ 40 ጭፍሮች ናቸው:: "ሐራ ሰማይ" የተባሉት በምድር ሲሠሩት የቆዩትን የውትድርና ሥራ ትተው የክርስቶስ (የሰማያዊው ንጉሥ) ጭፍራ ለመሆን በመብቃቸው ነው:: አርባው ባልንጀሮች ወጣትና ጐበዝ ክርስቲያኖች ነበሩ:: በእርግጥ እነርሱ ሰማዕትነት የተቀበሉበት ጊዜ ዘመነ ሰማዕታት አልነበረም:: ነገር ግን ሰማዕትነት የጊዜ : የቦታ : የሁኔታ : የእድሜ : የጾታ : የዘር . . . ልዩነት አያግደውምና እነዚህ ወጣቶች ለዚህ ክብር በቅተዋል:: ነገሩ እንደዚህ ነው:- በ330ዎቹ አካባቢ የዓለም ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ አንዱን መኮንኑን ወደ ቂሣርያ አካባቢ ይልከዋል:: የተላከው አካባቢውን ለማስተዳደር ሲሆን ቦታው ስብስጥያ (ሴባስቲ) ይሰኛል:: መኮንኑ ክርስቲያኖችን እንዲንከባከብ ጥብቅ ትዕዛዝ ከንጉሡ ቢሰጠውም ፍቅረ ጣዖት በልቡ የነበረበት ሰው ነውና ክርስቲያኖችን ይጨቁን : ያሰቃይ : ይገድል : አብያተ ክርስቲያናትን ያፈርስ ገባ:: በጊዜው ይህንን የተመለከቱት 40ው ጭፍሮች በአንድነት መክረው መኮንኑን ገሠጹት:: ስመ ክርስቶስንም ሰበኩለት:: እርሱም በፈንታው 40ውን አስሮ ብዙ አሰቃያቸው:: በመጨረሻ ግን 40ውንም የበረዶ ግግር አስቆፍሮ: ከነ ሕይወታቸው እስከ አንገታቸው ቀብሮ : ለ39 ቀናት ያለ ምግብ በጽኑ ስቃይ አቆያቸው:: በ40ኛው ቀን ግን ከ40ው አንዱ "ይህን ሁሉ መከራ የምቀበል ለምኔ ነው?" ብሎ "አውጡኝ!" እያለ ጮኸ:: ክርስቶስን አስክደው ወደ ውሽባ ቤት (ሻወር ቤት) ሲያስገቡት ፈጥኖ ሞተ:: በነፍስም በሥጋም ተጐዳ:: ነገር ግን ከአረማውያን ወታደሮች አንዱ "እኔን አስገቡኝ" ስላለ እንደገና 40 ሆኑ:: በዚህች ዕለትም 40ውን ጭን ጭናቸውን በመጅ እየሰበሩ ሲገድሏቸው ቅዱሳን መላእክት በአክሊል ከልለው : በዝማሬ አጅበው ወደ ገነት ወስደዋቸዋል:: ታላቁ ቅዱስ ባስልዮስም በጊዜው ነበርና ገድላቸውን ጽፎ ውዳሴ ደርሶላቸዋል:: ቤተ ክርስቲያናቸውንም አንጾ የካቲት 16 ቀን እንዲቀደስ አድርጉዋል:: ብጹዕ አባታችን አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ ላይ በቅዱሳኑ ላይ የሆነውን ነገርና ሥልጣነ እግዚአብሔርን እያደነቀ እንዲህ ሲል ተናግሯል:: "ኦ አውጻኢሁ ለዘእንተ ውስጥ:: (በውስጥ ያለውን የምታስወጣ)" "ወአባኢሁ ለዘእንተ አፍአ:: (በውጪ ያለውንም የምታስገባ)" "ወይእዜኒ ስማዕ አውያቶሙ ለሕዝብከ እለ ይጼውዑከ በጽድቅ:: (እንግዲህ በእውነት የሚጠሩህን የወገኖችህን ጩኸት /ልመና/ ስማ)" ((ቅዳሴ ማርያም ቁ.146)) ስለዚህ በውስጥ ያለን አንታበይ:: ያለንበት የእኛ አይደለምና:: እንዳንወድቅም እንጠንቀቅ:: ብዙዎቹ የቆሙ ሲመስላቸው ወድቀዋልና:: ያሉ ሲመስላቸውም ወጥተዋልና:: በውጪ ያለንም ተስፋ አንቁረጥ:: ወደ ሁዋላም አንበል:: ወደ ቤቱ ሊመልሰን : በክብሩ ማደሪያ ሊያኖረን የታመነ አምላክ አለንና:: ††† ቸሩ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ገብቶ ከመውጣት : አግኝቶ ከማጣት ይሠውረን:: ከሰማዕታቱ በረከትም አይለየን:: ††† መጋቢት 13 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ-ስደቱ) 2.ቅዱስ መቃርዮስ እስክንድርያዊ 3.40 ቅዱሳን ሰማዕታት (ከሃገረ ስብስጥያ) 4.ቅዱስ ዲዮናስዮስ (ጻድቅ ሊቀ ዻዻሳት) ††† ወርኀዊ በዓላት 1.እግዚአብሔር አብ 2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት 3."99ኙ" ነገደ መላዕክት 4.ቅዱስ አስከናፍር 5."13ቱ" ግኁሳን አባቶች 6.ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ 7.አቡነ ዘርዐ ቡሩክ ††† "ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብጹዓን ናቸው:: መንግስተ ሰማያት የእነርሱ ናትና:: ሲነቅፏችሁና ሲያሳድዷችሁ: በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብጹዓን ናችሁ:: ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ:: ሐሴትንም አድርጉ:: ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲሁ አሳደዋቸዋልና::" ††† (ማቴ. 5:10) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Mostrar todo...
Inicia sesión y accede a información detallada

Te revelaremos estos tesoros después de la autorización. ¡Prometemos que será rápido!