የተመከረ ሰው ምን ፈርቶ ከክፉ ሥራው ይመለሳል?
በኃጢአት ተግባር ላይ ያለ ሰው «ምን ይመጣብኝ ይሆን?›› እያለ ማሰቡ በውስጡ እግዚአብሔርን መፍራት እንዳለ ያሳያል፡፡ ምንም እንኳን ከኃጢአት መላቀቅ ባይችል ይህ ፍርሃቱ እንደ ጽድቅ ሊቆጠርለት ይችላል፡፡ ያላየውን እግዚአብሔርን መፍራት የማመን ምልክት ነውና፡፡ እግዚአብሔር የሚያመጣውን ፍርድ አስቦ መፍራት ከኃጢአት አንጽቶ እንደ ጻድቅ ሊያስቆጥር መቻሉን መጽሐፈ መነኮሳት በዚህ መልኩ ገልጾታል:: «
ፍራህ እምእንታክቲ ምግባራት እንተ ትትኄበብ ከመ ባቲ መገሥጽ እስመ ዘከመዝ ግዕዙ ይትበልሃ ከመ ውእቱ የሐውር በአፍኣ እምፍኖታ» : «ቅጣትና ተግሣጽ እንደሚያስከትል ከጠረጠርከው ሥራ ሁሉ ተጠበቅ እንዲህ ሲፈራ የሚኖረው ሰው ከኃጢአት ውጭ ነው ይባላልና›› ማለት ነው:: ማር.ይስ.አን.16 ምዕ 1
ሰው ሁሉ ክእግዚአብሔር ጋር እንድ መሆን የሚችለው ከእነዚህ ከሦስቱ መንገዶች ቢያንስ እንኳን በአንዱ መጓዝ ከቻለ ብቻ ነው:: አንደኛው ያለ ምንም ምክንያት በራሱ ተነሣሥቶ እንደ አብርሃም ፈጣሪውን ፈልጎ ካመነ። ሁለተኛው እንደ ቅዱስ ጳውሎስ በግርማ እግዚአብሔር ተገልጾ ከተመለስ፡፡ ሦስተኛ ደግሞ በክፉ ሥራው ምክንያት የሚመጣበትን ቅጣት አስቦ ከፈራ ነው፡፡ የሐዋ 9፥6፣ ማር ይስ አን 3 ምዕ1
ለምሳሌ:- እንደ ቅዱስ ወቅሪስ፡፡ ቅዱስ ወቅሪስ መልከ መልካም ነበረ። ከዕለታት በአንድ ቀን ከሴት ጋር ተቃጠረ፡፡ በዚያችም ሌሊት ራእይ አየ፡፡ ራእዩም «እርሱ ታሥሮ ከብዙ እሥረኞች ጋር በንጉሡ ፊት ቆሞ እሥረኞቹ እያንዳንዳቸው በተራ ሲመረመሩ እርሱ ግን የቀጠርኳት ሴት ባሏ አሣሥሮኝ ይሆን? እያለ ሲጨነቅና ሲፈራ በዚህ ጊዜ ጠባቂ መልዐኩ ከወዳጆቹ አንዱን መስሎ መጥቶ ይህን ሥራ ሠርተህ እንዳታሲዘኝ ማልልኝና እኔ ልዋስህ እያለ ሲያስምለው›› ነበር። ከዚያ በኋላ ሄላኔ የምትባል ደግ ሴት ነበረች ወደ እርሷ ሄዶ ያየውን ራእይ ነገራት፡፡ እርሷም ተርታ ልብስ ለብሰህ አልባሌ መስለህ ፈጣሪህን አገልግለው ይምርሐል አለችው፡፡ እርሱም እንደነገረችው አድርጐ ከፈጣሪው ታርቋል፡፡ ማር ይስ አን 3 ምዕ 1 እንዲህ ከሆነ ፍርድን አስቦ መፍራት ጻድቅ ያደርጋል ቢባል ምን ይደንቃል?
ከክፉ ሥራ ለመመለስና ንስሐ ለመግባት ጥርጊያ ጎዳናው እግዚአብሔርን መፍራት ነው :: እግዚአብሔርን መፍራት ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረትንና ርኅራኄን እንደሚያስገኝ ከዚህ በታች የተጻፈው ታሪክ ያስረዳል:: የእግዚአብሔር ነቢይ ኤልያስ <<
በእግዚአብሔር ፊት ክፉን ሥራ ለመሥራት ራሱን ለሸጠ>> ለአክዓብ የሚደርስበትን ቅጣት ሁሉ በነገረው ጊዜ አክዓብ «ልብሱን ቀዶ ገላውን ማቅ አለበሰ፥ ጾመም፣ በማቅ ላይም ተኛ ቅስስ ብሎም ሄደ፡፡›› ይላል:: በተለይ «ቅስስ ብሎ ሄደ» የሚለው ዐረፍተ ነገር የአክዓብን ፍርሐትና ድንጋጤ ያመለክታል:: በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር «ኤልያስ ሆይ አክዓብ እንደ ደነገጠ (እንደፈራ) ተክዞም እንደሄደ አየህን? በፊቴ የተዋረደ ስለሆነ በልጁ ዘመን በቤቱ ላይ ክፉ ነገር አመጣለሁ እንጂ በእርሱ ዘመን ክፉ ነገር አላመጣም።›› በማለት በይቅርታ ወደ አክዓብ መመለሱን ተናግሯል:: 2ነገ 20፥27
ሰው በክፉ ሥራው «ምን ይመጣብኝ ይሆን?» እያለ ሲፈራ እግዚአብሐርን መፍራቱ እንጂ ሌላ አይደለም:: ከላይ የተጠቀሰው የአክዓብ ታሪክ እግዚአብሔርን መፍራት የሚያስገኘውን ታላቅ ጥቅምና በእግዚአብሔርም ዘንድም ያለውን ተወዳጅነት ያስረዳል፡፡ ሰይጣን ደግሞ ሰው እግዚአብሔርን በመፍራቱ ብቻ እንኳን የሚያገኘውን ጥቅም ያውቃልና የዓለምን ምሁራን አስነሥቶ በልዩ ልዩ ጐዳና ፍርሐተ እግዚአብሔርን ከሰው ልብ የሚያርቅ ንግግር ያናግራቸዋል፡፡ አንድ ጊዜ ፍርሐትና የበደለኝነት ስሜት ጤናን ሊያቃውስ እንደሚችል ሌላ ጊዜ ደግሞ ፍርሐት በራስ የመተማመን ጉድለትና የብቃት ማነስ ምልክት እንደ ሆነ በማስረዳት ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት በፍርሃት እንዳይመላለሱ ለማድረግ ይጥራሉ፡፡ እኛ ክርስቲያኖች ግን ምንም ከበደል መራቅ ባይቻለን ፍርድን አስቦ መፍራታችን ብቻ እንኳን ዋጋ ያለው መሆኑን እንረዳለን፡፡ ሰይጣን በውጫዊ ማንነታችን ሰልጥኖ ኃጢአት ቢያሠራንም ፍርድን አስበን መፍራታችን በውስጣችን የምንገዛው ለእግዚአብሔር መሆኑን ያመለክታል፡፡ ውጫዊው ኃላፊና ፈራሽ ሲሆን ውስጣዊው ግን ዘለዓለማዊ ነው፡፡ በውጫዊው ሰውነት ከመገዛት በውስጣዊው መገዛት በብዙ ይበልጣል:: እንዲሁም በአፍኣዊ ማንነታችን ኃጢአት እየሠራን ለሰይጣን ከምንገዛው ይልቅ በውስጣችን ለእግዚአብሔር የምንገባው አገዛዝ ይበልጣልና መጨረሻችን የእግዚአብሔር መሆን ነው:: ስለዚህ «ለእግዚአብሔር በፍርሐት እንገዛ›› መዝ 2፡11 ብንበድልም ፍርሐትን ከልባችን አናርቃት።
«ግብረ አውና>>ን መፈጸም ሰው መግደል ሊሆን ይችላል?
ብዙ ሰዎች ዘር ሲክፍሉ ወይም ሲፈሳቸው ይልቁኑም አውቀው ያደረጉት ከሆነ «ሰው እንደ መግደል ይቆጠርብኝ ይሆን?» እያሉ ራሳቸውን መጠየቃቸው አይቀርም፡፡ በእርግጥ ግብረ አውናንን እየፈጸሙ ዘርን ማፍሰስ ሰው እንደ መግደል ይቆጠር ይሆን?
ወንድና ሴት ሩካቤ ሲያደርጉ ከወንድ ዘር ከሴት ደግሞ ደም ተከፍለው ተዋሕዶ ባደረጉ ጊዜ ተከፍሎዋ እንደ የብርሃን ፋና ይሁን እንጂ በዚያው ጊዜ ነፍስም አብራ ትከፈላለች:: ነገር ግን ሴቶች በየወሩ ደም ሲያዩ ወንዶችም ዘር ሲወጣቸው ነፍስ እንደ ማጥፋት አይቆጠርባቸውም። እንዴት?
ምሥጢሩ እንዲህ ነው:- እነሆ እሳት በእንጨት ውስጥ መኖሩ የታወቀ ነው:: ሆኖም አንድ እንጨት ከሌላ ጋር ሳይሳበቅ ለብቻው እሳት መፍጠር አይችልም:: እሳት በእንጨት ውስጥ ይገኛል ቢባልም ቅሉ እንጨት መስበር እሳት እንደ ማጥፋት አይቆጠርም:: እንጨት ምሳሌነቱ እንደ ሴት ደምና እንደ ወንድ ዘር ሲሆን እሳት ደግሞ እንደ ነፍስ ነውና፤ ሴቶች ለብቻቸው የሚያስገኙት ደም ወንዶችም ለብቻቸው የሚከፍሉት ዘር ነፍስን ሊያስገኝ ስለማይችል ሰው እንደ መግደል ሊቆጠር አይችልም:: ሰው የሚባለው ራሱ አራት ባሕርያተ ሥጋ ሦስት ባሕርያተ ነፍስ ያሉት ፍጥረት ነውና፡፡ ስለ ነፍስና ሥጋ በአጠቃላይ ስለ ሰው ተፈጥሮ የበለጠ ለመረዳት በዚሁ መጽሐፍ የመጀመሪያ ክፍል የሕይወት አጀማመር የሚለውን ንዑስ ክፍል ያንብቡ፡፡ ግብረ አውናንን የሚፈጽሙ ሰዎች በተያያዥ ሊከሠትባቸው የሚችለው ቀጣዩ ጥያቄ ደግሞ ሩካቤ ሥጋ ፈጽመው የማያውቁ ከሆነ ‹‹ከዚህ በኋላ ድንግል ልባል እችላለሁ?» የሚል ነው፡፡ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ የሚሆን ሐሳብ ስለ ሴቶች ድንግልና በሚያትተው ንዑስ ክፍል «ድንግል ነኝን?» በሚለው ርዕስ ሥር የሰፈረ በመሆኑ እንዲያነቡት ተጋብዘዋል፡፡
«ግብረ አውናን» የሚያስከትለው ጉዳት
ግብረ አውናን (ሴጋ) ውጥረትን ለፈጠረ አንድ ችግር የተሳሳተ አማራጭን መጠቀም እንደመሆኑ መጠን በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ብርታትና ጥንካሬን የሚጠይቁ መንገዶችን እንድንሸሽ ያለማምዳል:: ይህ ማለት ደግሞ እጅግ ሲበዛ ሰነፍ እንድንሆን ያደርጋል ማለት ነው::
ግብረ አውናን ኃጢአት እንደ መሆኑ መጠን በዚህ ዓለምና በወዲያኛው ዓለም ቅጣትን ያስከትላል፡፡ በዚህ ዓለም ቅጣቱ እንደ አውናን ከመቀሠፍ ሊጀምር ይችላል፡፡ ዘፍ 38÷9 ሰላም ማጣት፣ ቁጭት፣ ጸጸት፣ ጭንቀት፣ መረበሽ፣ ንጹሕ ያለ መሆን ስሜትና የመሳሰሉት የግብረ አውናን እንጻራዊ ጉዳቶች ተደርገው ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡